Saturday, 08 March 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትርጓሜ
ጉባዔ፡- ጉባዔ ማለት ታዋቂ ሰዎች ለየብቻቸው ሊሠሩት የማይችሉትን ነገር አንድ ላይ ሆነው በቃ ምንም ሊሠራ አይቻልም ብለው ተስማምተው የሚወስኑበት ስብሰባ ነው፡፡
*   *   *
አንድ ታላቅ ባለሥልጣን ጉባዔን ሲገልፁት፤ “ጉባዔ ማለት የአንድ ሰው መደናበር በተሰብሳቢው ቁጥር ሲባዛ የሚገኝ የስብስብ ብዛት ነው!”
*   *   *
የ25ኛ ዓመት የጋብቻ ቀኑን የሚያከብር አንድ ባል በጣም ተደብሮ ያየው ጓደኛው ሊያፅናናው እየሞከረ ሲያባብለው፤ ባልዬው ብስጭቱን ሲገልፅ እንዲህ አለ፡-
“በ5ኛው የጋብቻ በዓላችን ጊዜ ሚስቴን ልገድላት አስቤ ጠበቃዬን ባማክረው “20 ዓመት ያስፈድርብሃል ተው” ብሎኝ ተውኩ፡፡ እስቲ አስበው ወዳጄ! ይሄኔኮ ከእሥር ቤት ወጥቼ ነበር!”
*    *   *
ዳኛ (ለተከሳሹ)፡- “በአራት አመት ጥብቅ እሥራትና ከአገር እንድትባረር ተፈርዶብሃል፡፡ የምትለው ነገር አለህ?”
ተከሳሹ፡- “ጌታዬ ሁለተኛው ውሳኔ መጀመሪያ ይሁንልኝ!”
*   *   *
ዳኛ፡- “ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ከማስተላለፉ በፊት የምታቀርበው ነገር አለ?”
እሥረኛ፡- “ኧረ ምንም የለኝ ጌታዬ! 50 ብር ነበረኝ ጠበቃዬ ወሰደው”
*   *   *
ሴትዮዋ አዋቂ ዘንድ ሄዳ ዕጣ-ፈንታዬን ንገረኝ ትለዋለች፡፡
አዋቂ፡- (መዳፏን እያየላት) አንድ ረዥም ጥቁር ሰውዬ መጥቶ ሲያሳልፍሽ ይታየኛል፡፡”
ሴትዬዋ፡- “ምን ምን ያደርግልኛል ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ስጦታ በስጦታ ያደርግሻል፡፡ ናይት ክለብ ወስዶ አለምሽን ያሳይሻል፡፡ ፍቅር ለዘለዓለም ይኑር! ብለሽ ዋንጫሽን ታነሺለታለሽ”
ሴትዬዋ፡- “ጥቁሩ ሰውዬ ብዙ ገንዘብ አለው ጌታዬ?” አለች ሴትዮዋ ፍንክንክ እያለች፡፡”  
አዋቂ፡- “ምን ነካሽ? ሰውዬውኮ የአንድ ትልቅ ኩባንያ ፕሬዚዳንት ነው፡፡ ከእናት አባቱ 900,000 ብር የሚከራይ አፓርትማ ወርሷል”
ሴትዮዋ፡- “ታድዬ! እንዴት ያለ ፀጋ ፈሰሰልኝ ጌታዬ! አንድ ነገር ብቻ እንድጠይቅዎ ይፍቀዱልኝ ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ጠይቂኝ!”
ሴትዮዋ፡- “ባሌንና ሶስቱን ልጆቼን የት አረጋቸዋለሁ? ምን ይውጣቸዋል?”

Published in የግጥም ጥግ

   የአርሲ ጉዞዬ አስደናቂ ማስታወሻ

“በል እንዳትቀር እፈልግሃለሁ አልኩት፡፡ ትንሽ ቆይቶ ምልክት አደረገልኝ፤ ሞባይሌ ላይ። ደወልኩለት፡፡ ‘አንድ ልነግርህ ፈልጌ የረሳሁት ነገር አለ’ አለ፡፡ ያ ታጣቂ ገበሬኮ ራሱ መጥቶ - ያኔ ያልኳችሁ ስህተት ነው፤ የመጀመሪያው ቦታ ነው ትክክል ብሎ ነገረኝ- አለ … Can you imagine?” (አይገርምህም? እንደማለት) አለ ዶ/ር በመደመም፡፡
“That’s how the muse works! ውቃቢ ሲፈቅድ እንዲህ ነው አየህ!” እንቅልፍ የነሳው ነገር ነበረ ማለት ነው ታጣቂውን፡፡ “አዎ በስህተት ነው - እኔ ምን ሆኜ እንደሆን አላውቅም፤ መጀመሪያ በትክክል ነበርኮ የተናገርኩት’ አለ፤ አለኝ፡፡” “ታጣቂውም Re-affirm አረገ (ዳግመኛ አረጋገጠ) … ይሄ ምን ማለት ነው … ከ38 ዓመት በኋላ … በየጭንቅላቱ ውስጥ የሚሄድ ነገር አለ …”
“Guilt ም (የጥፋተኝነት ስሜት) አለ፤ ጭንቀትም አለ … ምንም ዓይነት ነገር ሊኖር ይችላል … አንድ ወዳጄ ከርቸሌ የነበረ ወዳጄ (ዘመዴም ነው) የአራት ኪሎ አካባቢ ሰው ነው-በዱሮው መንፈስ … አስከሬን እየሸኘን ሳለ ቅዳሜ ለት ቴክስት ልኬለት ነበር- ‘በጥምቀተ-ባህርም ታቦት ሲሸኝ እንዲህ በህዝብ አይጥለቀለቅም’ ብዬ፡፡ እሱ ምን ብሎ መለሰ … “Take photos of the guilt-ridden offsprings of the killers” …
(በወንጀለኝነት ስሜት የሚናወጡትን ገዳዮች ልጅ-ልጆች ፎቶ አንሣ-እንደማለት ነው)
እንግዲህ ሁሉም በየፊናው አዕምሮው ውስጥ የቀረ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ የእኛ ሰዎች እንዲህ ማሰባቸው አይገርምም! በኋላም ከዚህ ዘመዴ ጋር ስናወራ … “የላኩልህን ሚሴጅ ለሙሉጌታ አነበብክለት ወይ?” ብሎኝ ነበር፡፡ “እንዴት ብዬ ዶ/ር ሙሉጌታኮ በወፈ-ሰማይ ህዝብ ተከቦ ነበር” ብዬዋለሁ፡፡ ዞሮ ዞሮ ያው መልዕክቱን አሁን አድርሻለሁ” አልኩት፡፡ ተሳሳቅን፡፡ …
ወደ ሳጉሬ ስንገባ ፈረሰኞቹ በዛ ግርማ-ሞገስ ባለው አጀብ ሲቀበሉን the grandiosity of the moment (የዚያች ቅፅበት ድምቀት-ከግዝፈት) መግለፅ ከምችለው በላይ ነበረ! ለዚህ ነው ቴክስት የላኩለት፡፡ ቀረርቶ፣ ሽለላ፣ ለቅሶ … ድብልቅልቅ ወኔና ዕንባ፤ ከ38 ዓመት በኋላ! በጣም ስሜቴን አጥለቅልቆት ነበር! ማመን አልቻልኩም - ሙሉ ከተማ ሲንቀሳቀስ ማየት … ሲጐርፍ ሲሳብ ሲሰበሰብ፤ በአንድ አይነት የኮቴ-ቅኝት ሲፈስ መመስከር …
“አዎ ተቀነባብሮልናል፡፡ እኛ ከፍቅረማርያም ጋር ያሰብነው አባቴ ከሚካኤል ወደ ሥላሴ ይሂዱና በሰላም ይረፉ ብለን ነው፡፡ ነገሩ እንዴት ነበር መሰለህ? ክፍሌ ዘመድ ወዳጁን ሁሉ፣ በታህሣሥ 26 መሆኑ ነው፤ ሰበሰበና “እንዲህ ተገኝቷል ምን እናድርግ?” አለ፡፡ መቼ ነው ያሰባችሁት?” ሲሉት፤ የካቲት ውስጥ (ጊዜ እንዳንፈጅ ነው ብሏቸዋል)። “የት እንዲቀበር ነው የምትፈልጉት?” ሲሉት እዚያው ሥላሴ ግቢ ውስጥ አላቸው፡፡ “ይሄኮ የእናንተ፣ የአባታችሁ ቀብር ጉዳይ ብቻኮ አይደለም፡፡ የእኛንም ሰዎች ነው የምንቀብረው …”
እኛ እንግዲህ ስላሴ የክፍሌ እናት የተቀበሩበት ለመቅበር ነበር ያሰብነው … ‘በጭራሽ እኛኮ ሙስሊሞች ነን አብዛኛዎቻችን፡፡ … እዛ ቀብራችሁ እንዴት ብሎ ሌላው ዘመድ አዝማድ ይይ? አይሆንም-ፊት ለፊት፤ ሁሉም ሊያይ የሚገባበት ቦታ ነው መቀበር ያለባቸው! የእናንተ ሰው ብቻ ሳይሆን፤ ሌሎችንም ጭምር ያን ጊዜ ያለቁትን ለማስታወስ ነው የምንፈልገው - ብለው አሻፈረኝ አሉ -የአገር ሽማግሌዎቹ! … እኔም ፍቅረ ማሪያምም ሌሎችም ተሟገትናቸው - አይሆንም አሉ! ሁሉም ተቀበለ … ካሰብኩት በላይ ሆነ፡፡ ሁሉም በኋላ ሲያዩ … ቶላ በዳዳ በል፣ መኰንን አካ በል … ትላልቅ ያገር ሰዎች፤ በኋላ ሲያዩት ተደሰቱ ነው እምልህ፡፡ አይሆንም ብለው የነበሩት ሰዎች - በጣም ጥሩ ሆነ አሉ … ዘሪሁን የመቃብር ቤቱን ሥራ ጀምር ተባለ፣ … ሐውልት መሥራትና መጽሔት ማዘጋጀት አዲሳባ ያለው ኮሚቴ ሥራ ነው … ሌላው የአገሬው ኮሚቴ መስተንግዶ ይሥራ ተብሏል፡፡ በዚህ ተከፋፈልን … እኛ ገንዘብ እንደምንም ማከፋፈል ጀመርን-እዚህ ደረስን…
“ብዙ ብር አወጣችሁ?’
“አዎ ሀውልቱ ከ60 እስከ 70ሺ ሳይወስድ አልቀረም፡፡ መጽሔቱ እንደዛው ወጪ አለበት…”
“አንዱ የነካኝ ነገር አብዛኛዎቹ የቀብሩ ታዳሚዎች ሙስሊሞች ናቸው … ይሄንን ማመን አልቻልኩም፡፡ ግራ ቀኙ ሙስሊም ነው … የፕሮግራሙ መሪው የተናገረውን ታሪክ በትክክል ተረድቼው ከሆነ ፊታውራሪ ሱማሌያ ሄደው ነው ቁራን ቀርተው የመጡት ነው ያለው መሰለኝ…”
“አይ፤ እዚሁ ነው፡፡ የሱማሌ፤ ቁራን የሚያውቅ ሰው … ሱማሊኛም ይችላሉ አባቴ -የሚችሉት በዚያ ሱማሌ የተነሳ ነው፡፡ እዚሁ ነበር … እሱን አግኝተውት ቁራን ቀሩ፡፡ የአማርኛ ትምህርት በኋላ ላይ ተማሩ … እንደዚህ እንደዚህ ነው የሆነው
“መጀመሪያ ምን ነበሩ? ክርስቲያን ሆነው ነው ቁራን የቀሩት ማለት ነው?” ብዬ ጠየኩት፡፡   
“መጀመሪያማ በእኛ አካባቢ እስልምና አለ፡፡ እስልምናም ክርስትናም ባንድ አካባቢ ባንድ ዘመን ነው የገባው፡፡ የመጣው፡፡ ሳጉሬ፡፡ አያቴ ሁለቱም ሲመጡ አይተዋል! ያኔ ምናልባት በራስ ዳርጌ ጊዜ ነው - በሚኒሊክ ጊዜ መሆኑ ነው … ኦገቶ አያቴ በሚኒሊክ ጊዜ ነበሩ - ባላባት ናቸው ያን ጊዜ … እስልምናም ክርስትናም ሲመጣ - ከዛ በፊት ያው አዋማ ነው የሚባሉት - ያው በኦሮሞ አይነት አኗኗር ውስጥ የነበሩ ዕምነቶች ያልነካቸው ነበሩ …ኋላ ግን ኦገቶ እስላም ሆኑ፡፡ እስላምን ተቀበሉ። አብዛኛዎቹን የሚስቶቻቸውን ልጆች እስላም አደረጉ፡፡ የአባቴን እናት ልጆች (የሴት አያቴን) እነሱን ደሞ ክርስቲያን አረጓቸው፡፡ አንድ ቱሱራ የሚባል አለ፡፡ ክርስቲያን አልሆንም ብሎ እስላም ሆነ! ሌሎቹ አራቱ ማለት - ተክሌ፣ አበበ፣ በቀለ እና አሹ እምትባል ሴት ክርስቲያን ሆኑ! እንግዲህ፤ በኋላ ለባላባትነት አባቴን መርጠዋል ማለት ነው፡፡ ክርስትና ከተነሳህ ያው ከሥርዓቱ ጋር ቀረብ ትላለህ፡፡ ከሲስተሙ ጋር፡፡ እናቴንም ያገቡት ለዛ ነው፡፡ እናቴ እንግዲህ የማህል ሠፋሪ ልጅ ናት! ባሻ ገድሌ የእናቴ አባት የአንኮበር ሰው ናቸው፡፡ ከራስ ዳርጌ ጋር ሄደው ማህል የሰፈሩ ሰው ናቸው፡፡ አያቴ፤ የእናቴ እናት፣ ጠራ መንዝ ናቸው፡፡
“ስለዚህ አንኮበርና ጠራ ናቸዋ እናትህ?”
“አዎን፡፡ ሚስት ስጡን ቢሏቸው (በዚያን ጊዜ አጠራር) ‘ለጋላ አንሰጥም!” ብለው ነበር፡፡ በኋላ ፎከሩ፡፡ በቀለ ክርስቲያን የመሆን እድል አገኙ …. እስላም ሆነው ነበረ ማለት ነው አባቴ፡፡ … ካሜላ ነው ስማቸው … ሚካኤል ማለት መሰለኝ፡ ከካሜላ በፊት ጨዊቻ ነው እሚባሉት አባቴ፡፡ ጨዊቻ የኦሮሞ ስም ነው! ሌላ የእስላም የቁርዓን ስም ነው … ካሜላ … በኋላ የክርስትና አባታቸውን አውቅ ነበረ … ደጃች ወንድይራድ … እንደዛ ገደማ ናቸው፡፡ ከትልልቆቹ አንዱ፡፡ … ቁራንም ቀርተው፣ ክርስትናን ተነስተው፣ ባላባትነቱንም ተቀብለው ነበር ማለት ነው … አባታቸው ካረፉ በኋላ ባላባትነቱን ተረከቡ፡፡ ብዙ ልጆች ነበሩ ታላላቆችም ነበሩ፡፡ ሦስት ታላላቆች። ብዙ ጊዜ ልምዱ እንደዛ ነው - የመጀመሪያው ልጅ-የበኩር ልጅ ነው የሚወርሰው-ባላባትነቱን፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ግን እንደዚያ አልነበረም-ለአባቴ ነበር የተናዘዙላቸው!” አለኝ፡፡
እኔም በመገረም፤ “ከመስጊድና ከቤተክርስቲያን ጋር የነበራቸው ቀረቤታ በጣም ፍላጐት አሳድሮብኛል፡፡ አስገራሚ ዕውነት ነው” “Fundamental to the Ethiopian society የኢትዮጵያ ህ/ሰብ የመሠረት ደንጊያ ነው ብዬ አሰብኩ፡፡ እስካሁን ወሎ ብቻ ነበር ሲጠቀስ የኖረው - አሁን ሳጉሬ መጣ-አርሲ - a very profound aspect of religion- በአንድ አገር ውስጥ መስጊድንም እራሱ አሠርቶ፣ ቤተክርስቲያንንም (በዕውነተኛ ልቡና ሠርቶ) መጓዝ ድንቅ ነገር ነው። ትምህርት ነው፡፡ ከባድ ነው ከ38 ዓመት በኋላ ያገኘነው ማጠየቂያ (Justification)፡፡ ይኸው ሥላሴ ኮረብታ ላይ ታይቷል፡፡ በመሠረቱ የእስላም ሴት ለቅሶ ስትመጣም አላቅም… ግን መዓት መጡ … አለቀሱ … ለቀስተኞቹ በብዛት ሙስሊሞች ናቸው …በብዛት ያለቅሳሉ … በጣም ይገርማል … እንዲህ ያለ ማረጋገጫ አይገኝም - እኔ ከዚህ አኳያ (angle) ነው ያየሁት፡፡
ሌላው የእኔ የግሌ እይታ፤ በእኛ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ዘመን የአርሲ ዕድገት በህብረት ዘማቾችን ደርግ ያላቸውን አስታውሳለሁ … በትክክል ባልጠቅሰውም … “ቅምጥል ንዑስ ከበርቴዎች፣ እጃቸውን የእንጀራ ጠርዝ የሚቀደው … “ጥቁር ወተት ነጭ ኑግ አምጣ እያሉ ገበሬውን ሱሪ ባንገት ሲያስወልቁት ከርመዋል…” በሚል ዓይነት ነበር ዘማቾቹን የሚከስ የሚወቅሳቸው፡፡
“…አንተ በሦስት ማዕዘን የማይታረቅ ቅራኔ ውስጥ ገብተህ ነበረ ማለት ነበርኮ! ፀረ-ፊውዳል የተማሪ እንቅስቃሴ ባንድ በኩል፤ እሳቸው ደግሞ ፀረ-ደርግ ሆነው ይታገሉ፣ ይዋጉ ነበር፡፡ ደርግ ደግሞ በእኛ በዘማቾች ላይ ጥቁር ወተት ነጭ ኑግ እያለ ነው፡፡ በጣም ማራኪ ታሪካዊ ሦስት ማዕዘን ነው የሚታየኝ፤ በጣም ስቦኛል! … Deep inside (ውስጠ-ነገሩን ለመረመረ)   የማህበረሰባችንን አካሄድ የሚያሳይ ስዕልም ያለው ይመስለኛል… ብዙ ነገር በውስጡ የሚያልፍ የህይወት፣ የሞትና የተረፈ-ህይወት ነገር አለው” ትልቅ ፅሁፍ ይወጣዋል ከታሰበበት፡፡ የእስላም-ክርስቲያን ዕምነት ውሁድ (harmony) በኢትዮጵያ ሁሌም የነበረ፣ ያለና እሚኖር ነው፤ የሚለውን ዕሳቤ ፍንትው አድርጐ ያሳየናል፡፡ የአንድነት አገራዊ መገለጫኮ ይሄው ነው … ማሳያ ነው፡፡ አንተስ ይሰማሃል?” አልኩት፤ የኮረኮረኝን ያህል ተናግሬ፡፡  
“እኔማ አውቀዋለሁ፡፡ ድሮውኑ እስላም ክርስቲያን እኮ አንድ ላይ ነው የሚኖረው፡፡ ቆይ ልንገርህ፡፡ ኦገቶ እስላም ሆነ፡፡ እስላም ነው፡፡ አርሲ ኦሮሞ ከብት አርቢ ነው፡፡ አራሽ አይደለም ከአመጣጡ፡፡ ይሄንን እዚህ ባላባት ሆነው ከኃ/ሥላሴ ጋር … ኃ/ሥላሴ ኦገቶን በደምብ ያውቋቸዋል አሉ፡፡ ሲመጡ ከዚህ የሸዋ ኦሮሞዎችን ኑ ባካችሁ ያገሬን ሰው፣ ያገሬን ገበሬ፤ ግብርና አስተምሩልኝ ብለው የአጐቴን የመኰንንን የሰናይትን አያት፤ ሌሎችም ሰዎች እዚህ አምጥተው እንዲሠፍሩ አርገዋል፡፡ ቤት ሰጥተዋል፡፡ ከዛ ምን ሆነ አንድ ጊዜ አንድ ክርስቲያን ሰው ሞተ አሉ፡፡ የመቃብር ቦታ፣ ቤተክርስቲያን፣ የለም፡፡ የት ነው ያለው ወደ ኢቴያ። ቦሩ ጃዌ እሚባል ቦታ … በቃሬዛ፣ በጠፍር አልጋ ተሸክመው ወስደው እዛ ቀበሩ፡፡ በኋላ ኃ/ሥላሴ ጋ ሄደው፤”በል ፅላት ስጠኝ” ብለው መድኃኔ ዓለምን ቆረቆሩ!”  
“እኒሁ ኦገቶ?!” ገርሞኝ ጠየኩት፡፡
“አዎ ኦገቶ፡፡ ጋለማ ሥር ያለች ከተማ እሁድ ገበያ ትባላለች፡፡ እዛ ቆረቆሩ፡፡ ሠንሠለታማው ጋራ ሥር ያለችው እሁድ ገበያ ውስጥ ያለ ቤተክርስቲያን ኖረ ማለት ነው፡፡ አሁንም አሉ፤ የዚያ ቤተክርስቲያን፤ ቀዳሽ ቄሶች፣ ልጅ ልጆች፡፡ እዚያው ሠፈሩን መሬቱን ይዘው ይኖራሉ፡፡ ከዛ ደባል እግዚሃር-አብ አለ፡፡ በጥምቀት ጊዜ ይኬድበታል፡፡ መድኃኔዓለም ከከተማው ወጣ ያለ ነው፡፡ ወደላይ 4ኪ.ሜ ገደማ። እና አንድ አጐቴ ከሌሎች ጋር ሆነው እዚህ ከተማ ውስጥ እግዚሄርአብን ከመድህኔዓለም ደባልነት አውጥተው አሁን እሁድ ገበያ ውስጥ እንዲኖሩ አርገውታል፡፡ እና ኦገቶ ናቸው ቤተክርስቲያን ያሠሩት፡፡ የዚያን ክርስቲያን ሰውዬ መሞትና ኢቴያ ቦሩ ጃዌ ድረስ ሄዶ (50 ኪ.ሜ) መቀበር፤ ካዩ ወዲያ ነው እንግዲህ! ይሄ ዕውነተኛ ታሪክ ነው! እና ለእኔ ዓይነት ሰው እስላም - ክርስቲያን ልዩነት ዓይነት Sense (ስሜት) ምንም የለም፡፡ ምንም ማስተናገጃም የለኝም፡፡”
“ከዚህ ሁሉ ዓመት በኋላ የዛሬው ሥነ ስርዓት የፈጠረብህ ስሜት ምንድነው? እንዴት ታየዋለህ? በአጭሩ”
“እኔ አሁን እንደማየው ካሁን ወዲያ፤ የተበጣጠቀው ታሪክ መልሶ መገጣጠም የተጀመረ ይመስለኛል … ምናልባት ካሁን ወዲያ የተሻለ ህይወት ለመኖር እንችል ይመስለኛል እንጂ ካሁን በፊት ያጋጠመኝ የነበረው ስሜት … እንደጠላትነት ነበረ … ደርግ ወድቆ ይሄኛው መንግሥት ሲመጣ ምን ነበረ መሰለህ … በቀለን የገደለ ሰው እናውቃለን ለምንድነው ከሰን የማናሳስረው? ገዳዮቹን ፖሊሶች እናውቃለንኮ ለምንድነው የማናሳስረው ሲባል ነበር … ያ አይነት ስሜት ነበር፡፡ ይሄ ቂም ነው፡፡ ቂም ነው፡፡ አልተዋጠልኝም ነበረ፡፡ የመገፋፋት ሁኔታ ነበረ ልልህ ነው፡፡ እና ታላቅ ወንድሜም እሱን ሰምቶ እንዲህ ይባላል ብሎኝ ነበር፡፡ ቃታ-የሳበ ሁሉ አስተሳሰብ አያስፈልግም እና ተውኩ፡፡ ተው አልኩት፡፡ እዛ ውስጥ አንገባም ተባባልን፡፡ እና ሌላም አጐቴ ነበረ፡፡ በቂም እሚያስብ፡፡ ያጋጥመኝ ነበር … ያኔ ታስታውስ እንደሆን (የዛሬ 26 ዓመት ግድም) ሰላምና መረጋጋት የሚባል ነበረ …”
“እንዴ በደንብ ነው የማስታውሰው!”
“አሰላ ውስጥ ሰላምና መረጋጋት ውስጥ ሲያገለግል የነበረ አጐቴ ሲነግረኝ፤ አለቃው አንድ የቡድን መሪ አድራጊ-ፈጣሪ የነበረና የእኛ አባትን ታሪክ ይሄንን ያወራ የነበረ አለ፡፡ ‘ገዳዮቹ ማናቸው?’ ብሎ ይጠይቃል፤ አለ፡፡ ለምን ገዳዮቹን ሰብስበን እዚህ አንጨርሳቸውም? ከዛ በኋላ ቂማችሁን ተወጥታችኋል ማለት ነው፤ ለምን እንደዚህ አናረግም?’ አለኝ አለ፡፡ እስቲ ቆይ ዕድል ስጠኝ ብዬ በኋላ ተውኩት፤ አለ፡፡ እና እንደዛ እንደዛም ሆኖ ነበር! በዛ ውሰጥ ነው ያለፍነው! ያ ፈሊጥ ነበረ! ጊዜ ወዳንተ ሲያዘነብል ቂም መወጣት ወይም አንተን ወደዘመመበት ለማዝመም የተደረገ ሙከራ ነበረ። ጊዜው ያመቻል፡፡ አጋጥሞኛል፡፡ እሱ 2ኛ ነው፡፡ ሌላም እንደዚሁ ዘመዳችን የሆነ በጊዜው አድሃሪ ምናምን ብሎ ተሳድቧል ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ ባለፈው ቅዳሜ መጣና አየሁት፡፡ ገበሬ ማህበር ደምበኛ አብዮታዊ ባሻሪ የነበረ ነው፡፡ በኋላ ተገናኘን!! እሱኮ እደዚህ ያረገ ነው አሉኝ፡፡ አሁን ሌላ ሆነ! እሁድ ልሄድ አስቤያለሁ - ገጠር!
“ምን ልታደርግ?”
እንዲሁ ዘመዶቼን ልጠይቅ፡፡ ይቺ አሁን የነብር ቆዳ ለብሳ የፎከረችዋን ሴትዮ አላየሁዋትም ነበር፡፡ ሁሌ በሄድኩ ቁጥር እሷን አገኛለሁ …  ደሞ ያጐቴ ሚስት ልጅ አለች እሷንም ሄጄ ላያት፣ ልሰማት እፈልጋለሁ … አብረንም ብንሄድ መልካም ነው እና አሁን በረጋ መንፈስ ምንም ችግር የሌለው፤ ነገር መሥራት ይቻላል…አየህ፤ “ለካ እንዲህ ማድረግ ይቻላል?!” ነውኮ ያልነው! ይሄን ያህል አልጠበቅነውም”
“አገርን ማነቃነቅኮ ነው፡፡ እኔም በጭራሽ ለማመን አልቻልኩም”
“ዕውነት ነው አንድ አፅም ታሪክ እየሰራ ነው! ሰው እንደጉድ ፈሰሰ፡፡
በቪዲዮ በስፋት መቀረፅ ነበረበት! እንደታሪክ፣ እንደ እስላም-ክርስቲያን አንድነት፤ የብዙ ነገር ማሳያ ነው፡፡ በቲቪ መታየት ነበረበት-ለትውልድ ማስተማሪያ! አመለጠን - ብዙ ይዘጋጅ ብለን ነበረ … ታሪክና ሃይማኖት እንዴት የተሣሠሩ እንደሆኑና የመንግሥታት መለዋወጥ የማታ ማታ ንክች እንደማያደርጋቸው ያሳያል!!”
“That’s excellent! አመሰግናለሁ ዶ/ር ሙሉጌታ!”

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…‘ቢዙ’ ሁሉ ቀዘቀዘ የሚባለው ነገር እንዴት ነው! አቤቱታ በዛማ!
ይሄንን የኑሮ በረዶ ዘመን ያሳጥርልንማ!
ይቺን አሪፍ ነገር ስሙኝማ…ቄሱን ጋቢያቸውን አንዱ ይሞጨልፋቸዋል፡፡ እናም እሳቸው ማንነቱን አውቀው “መቼስ ምን ይደረጋል!” ብለው ዝም ይላሉ፡፡
ታዲያላችሁ…አንድ ቀን መንገድ ሲሄዱ አጅሬው ያገኛቸዋል፡፡ ተንሰፍስፎም ሰላም ይላቸዋል፡፡ እሳቸውም አጸፋውን ይመልሱለታል፡፡ ከዛም “አባቴ ይፍቱኝ…” ምናምን ሲላቸው “ፈትቼሀለሁ…” ብለው መንገዳቸውን ይቀጥላሉ፡፡
ርቀው ሳይሄዱም እሱ ሆዬ ጮክ ብሎ ምን ይላል…“አባቴ እባክዎ በጸሎትዎ አይርሱኝ…” ይላል። ይሄኔ ቄሱ ምን ቢሉ ጥሩ ነው…“አልረሳህም ልጄ፡፡ ብርዱስ መቼ አስረስቶኝ!”
አንጀት ማራስ ይሏችኋል እንዲህ ነው፡፡
ዘንድሮ ብልጥነት እየበዛ ሄደና…አለ አይደል…የልቡን ሰርቶ “በጸሎትህ አትርሳኝ…” ባይ በዝቷል፡፡
እና ብዙ ነገር የረሳን ለሚመስላቸው የምንለው አለን…ብርዱ መቼ አስረስቶን፡፡
ስሙኝማ…የዚህ አገር ስልጣን ሁልጊዜ አይገረማችሁም! ልክ ነዋ፣ ወንበሩ ሲሰጥ አብሮ የሆነ ‘የስልጣን ወንበር ከትባት’ ተብሎ የሚሰጥ አለ እንዴ! ግራ ይገባናላ! “ምን የመሰለ ደግ፣ ሰው አክባሪ መሰላችሁ…” የሚባል ሰው ወንበሯ ላይ ሲቀመጥ በአንድ ጊዜ ቀንድና ጭራውን ደብቆ የመጣ ‘ሉሲፈር’ ምናምን ነገር ይመስላል፡፡
እንዴት መሰላችሁ…‘ወንበሯ’ እንደተያዘች አንበሳ ይኮንና “ባለፍኩበት መንገድ ማን ዝር ብሎ…” “የቤቴን ግንብ አጠር ማን ተጠግቶ…” አይነት ደረት መንፋት ይጀመርላችኋል፡፡ ምን አለፋችሁ… ለሰላምታ እንኳን መጠየፍ አይነት ነገር ይደርሳል። ከዛ ደግሞ መቼስ መውረድ ሲመጣ…ኧረ የሰው ያለህ፣ መደበቂያ ጉድጓድ አሳዩኝ…” ነገር ይመጣል፡፡
በተዘዋዋሪ “በጸሎትህ አትርሳኝ…” አይነት ነገር ነው፡፡ እኛም…“ብርዱስ መቼ አስረስቶኝ!” እንላለን፡፡
እንዴት ያለው ሩቅ ጭንቅ ያለው መንገድ፣
አሻቅቦ ወጥቶ ወደ ታች መውረድ፡፡
የሚሏትን ማስታወስ አሪፍ ነው፡፡
ስሙኝማ…መቼም ዘንድሮ በአንድ ጊዜ ‘ብር፣ በብር’ የሚሆን ሰው ይገጥማችኋል፡፡ እናላችሁ…የሆነ ሰው ገንዘብ ያገኛል፡፡ መቼስ ‘ወዳጅ ለመቼ ነው’ ይሉና በችግር ጊዜ ወደ እሱ ብቅ ይላሉ፡፡
“እባክህ ሚስቴ ታማብኝ እጄ ላይ ገንዘብ አጣሁ፣ ደሞዝ ላይ የምመልስህ…” ምናምን ይላሉ፡፡
እሱም “ገንዘብ ከዛፍ ላይ እንደ ቅጠል ይበጠስ መሰለህ እንዴ!” ብሎ የሞራላችሁን ሚዛን ከ75 ኪሎ ወደ 26 ኪሎ ያንደረድረዋል፡፡
እናንተም እንደሚሆን፣ እንደሚሆን ጊዜውን ታልፉታላችሁ፡፡ ታዲያላችሁ…አያልፍ የመሰለ ቀን ጋደል ይልና ሰውየው በአንድ ጊዜ ሁሉንም ነገር ያጣል። ከዛ ሲያገኛችሁ ምን ይላል…በጣም አጣዳፊ ችግር ገጥሞኝ ነው፡፡ እቁብ አትሰበስቡልኝም!” አይነት ነገር ይላል፡፡ በተዘዋዋሪ “በጸሎትህ አትርሳኝ…” አይነት ነገር ነው፡፡ እናንተም “አልረሳህም፣ ብርዱስ መቼ አስረስቶኝ!” ትሉታላችሁ፡፡
ወጥቼ ወጥቼ ሲያልቅልኝ ዳገቱ፣
ተመልሼ ወረድኩ ከነበርኩበቱ፡፡
የሚባል ነገር ይመጣልና ጋቢያችንን ወስዶ “በጸሎትህ አትርሳኝ…” አይነት ነገር ቀሺም ነው፡፡
ስሙኝማ… እንግዲህ ጨዋታም አይደል…አንድ የምናውቀው ሰው ሞባይል ስልኩ ይደወልለትና ያነሳል፡፡ “ሀሎ!” ይላል፡፡ እዛኛው ጫፍ ያለው ሰው ሰላምታ ሳያቀርብ፣ ማንነቱን ሳይናገር…ምን አለፋችሁ…“አሁን አንተም ሰው ሆነህ እኔን ማታለልህ ነው…” ምናምን ብሎት መጻፍ የማይቻሉ የስድብ አይነቶች ያወርድበታል፡፡ ከዛ ስልክ መሳሳቱን ይነግረዋል፡፡ ይሄኔ ያኛው ሰው ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው…“ነው እንዴ!” አለና ስልኩን ጠረቀመው፡፡
ምን አይነት ጊዜ ላይ እንደደረስን እሱ አንድዬ ይወቀው፡፡  
ስሙኝማ…የስልክ ነገር ካነሳን አይቀር…የሆነ ስልክ ይደወልላችኋል፡፡ “ሃሎ!” ትላላችሁ፡፡ በወዲያኛው ወገን ያለው ሰው… “ይሄ ቁጥር ስንት ነው?” ይላል፡፡ እኔ የምለው… እንዴት ነው ነገርዬው! …የደወለው ራሱ! ስንት ብሎ ነው የደወለው! እናላችሁ…ከስልክ መቋረጥ እኩል የስልክ ስነ ምግባር አስቸጋሪ ሆኗል፡፡
የሚገርማችሁ…በእናንተ ስልክ ሌላ ሰው ሲጠይቃችሁ…“ተሳስተዋል…” ምናምን ስትሉ አብዛኛው ሰው… “ይቅርታ” የምትለዋን ቃል ወይ ረስቷታል፣ ወይ ቃሏን ከተናገራት የምታንቀው ይመስላል! እናላችሁ…ጆሯችሁ ላይ ጥርቅም ያደርገዋል፡፡
የምር ግን…ይሄ የስልክ ነገር…“አሁንስ አቤቱታ ማቅረቡም ሰለቸን…” የሚባል ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡ ለሦስት ደቂቃ ንግግር አምስት ጊዜ እየተቋረጠ!
እኔ የምለው…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይቺን ስሙልኝማ፡፡ ሰውየው ሌላ ከተማ ያለ ጓደኛው ዘንድ በኦፕሬተር በኩል ይደውልና…“እባክህ ለአስቸኳይ ጉዳይ አሁኑኑ አንድ ሺህ ብር በባንክ በኩል ላክልኝ…” ይላል፡፡
“መስመሩ ተበላሽቷል መሰለኝ፡፡ የምትለው አይሰማኝም፡፡”
“ያልኩህማ ገንዘብ ስለቸገረኝ አንድ ሺህ ብር ላክልኝ፡፡”
“ዛሬ መስመሩ ልክ አይደለም፡፡ የምትለው አንዲቷም ቃል አትሰማኝም፡፡”
ይሄን ጊዜ ኦፕሬተሯ ጣልቃ ትገባና.. “ሃሎ ኦፕሬተሯ ነኝ፡፡ መስመሩ ችግር የለበትም፡፡ የሚለው ሁሉ ለእኔ በደንብ ይሰማኛል…” ትላለች፡፡ ይሄኔ ገንዘብ የተጠየቀው ሰው ምን ቢል ጥሩ ነው… “እንግዲያው አንቺ አንድ ሺህ ብሩን ላኪለት፡፡”
ስሙኝማ… እንግዲህ እውነት እንነጋገር ከተባለ…የሚባለውን እየሰማን ስልኩ ይቆራረጣል እንል የለ! ለምን ይዋሻል… የማንፈልገው ሰው ከሆነ፣ መስማት የማንፈልገው ነገር ከሆነ (ዕድሜ ለኔትወርክ መቆራራጥ!) “ኧረ ስልኩ ይቆራረጣል፣ ምንም አይሰማኝም፣” ብለን ጥርቅም ነው፡፡
ስሙኝማ…ቢሮ ውስጥ ስልክ ይደወላል… ሰውየው ያነሳና ካዳመጠ በኋላ ለሥራ ባልደረባው… “ለአንተ ነው መሰለኝ…” ይለዋል፡፡ ያኛውም ሰው፣
“መሰለኝ ብሎ ነገር ምንድነው… ወይ የአንተ ነው ወይ አይደለም ይባላል እንጂ…” ነገር ይላል፡፡ ስልኩን ያነሳው ምን አለ መሰላችሁ፤
“አይ ልክ ሀሎ ስለው የደወለው ሰው ‘አንተ ደደብ፣ አሁን በህይወት አለህ!” አለኝ፡፡
ከዚህ ይሰውራችሁ፡፡    
ስሙኝማ…ቴክኖሎጂው እየተራቀቀ ይሄ የስልክ ነገር አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡ ‘ፕራይቬሲ’ ምናምን የሚሏቸው ነገሮች ለመብት ተሟጋች ድርጅቶች ብቻ እየቀሩ ይመስላል፡፡ ልጄ… እነ አንጄላ ሜርኬል እንኳን ‘ከተጠለፉ’ በኋላ እኮ በስልክ… “ስማ፣ የሆነ ምስጢር ልነግርህ ፈልጌ ነው…” ምናምን መባባል እየከበደ ነው፡፡ ‘ሀከር’ ምናምን የሚሏቸው ነገሮች በበዙበት ዘመን፣ መንግሥታት ሁሉ ጓዳ ጎድጓዷውን በሚሰልሉበት ዘመን… “በእኔና በአንተ ብቻ ይቅር…” ብሎ ነገር ለ‘ሮማንቲክ ኮሜዲ’ ታሪኮች ብቻ ሊሆኑ ምንም አልቀራቸው።  
የምር ግን… ስልካችሁ ላይ የማይሆኑ እንግዳ ነገሮች አይገጥሟችሁም! አንድ ጽሁፍ ላይ ያነበብኳትን ስሙኝማ…እያወራችሁ እያለ ሞባይል ስልካችሁ ውስጥ ‘ቀጭ፣ ቀጭ’ ምናምን የሚሉ ድምጾች ካሉ፣ ሞባይላችሁ በቀላሉ አልዘጋ ብሎ ሲያስቸግር፣ ደግሞም…ሳትነኩት ለረጅም ጊዜ እንደ በራ ከቆየ… ነገር አለ ማለት ነው ይላል። ብዙዎቻችን እንደዚህ አይነት ነገሮች ሲገጥሙን “ድሮስ ርካሽ ሞባይል…” ምናምን ብለን እናልፈዋለን፡፡ እነኚህ የፔንታጎን ጓዳ የሚያምሱት ‘ሀከሮች’ ዓይን ውስጥ ገባን እንዴ!
ይቺን ስሙኝማ…
ትንሽ ቤት ሠራሁ እንዳቅመኛ፣
ሁለት ሦስት ሰው የሚያስተኛ፣
አላስገባ አለች ያቺው ጠባ፣
ሰው በሰው ላይ እየገባ፡፡
የሚሏት የቆየች ነገር አለች፡፡ እናላችሁ…ዘንድሮ ‘ሰው በሰው ላይ እየገባ’… አለ አይደል… መፈነጋገል በጣም የተለመደ ሆኗል፡፡ እናላችሁ… በየመሀል በቆረጣ እየተገባ ዕድላቸውን የሚነጠቁ ሰዎች መአት ናቸው፡፡ እነኛው ‘በሰው ላይ እየገቡ’ የሰው ዕድል የሚነጥቁት… ቀን ዘወር ሲልባቸው ምን ይመጣል…በተዘዋዋሪ “በጸሎትህ አትርሳኝ…” አይነት ይመጣል፡፡
እኛም…“ብርዱስ መቼ አስረስቶኝ!” እንላለን።
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

       አገራችን ባለፉት አመታት ካሳየቻቸው ለውጦች ዋነኛው የመሠረተ ልማት መስፋፋት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመንገድ፣ በባቡር፣ በውሀና በሀይል አቅርቦት እንዲሁም በቴሌኮም መስኮች ሰፊ የመሰረተ ልማት መስፋፋት ተስተውሏል። ነገር ግን ልብ ብሎ ላስተዋለው ይህ መስፋፋት ሁለት ገጽታዎች ተላብሶ ይታያል። በአንድ በኩል ይህ ፈጣን የመሠረተ ልማት ግንባታ እጅግ ብዙ ኢትዮጵያውያንን በማገናኘት የሀገሪቱን የልማትና የምርታማነት ከባቢ ያሠፋ ሲሆን በተዋናዮቹም ላይ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማት እድገት መፍጠር ችሏል፡፡
በአሁን ወቅት 24 ሚሊዮን የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን የተንቀሳቃሽ ስልክ ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ ከዛሬ አስር አመት ከነበረው አንፃር ሲታይ ይህ ቁጥር እጅግ አስገራሚ ሊባል የሚችል እድገት ማሳየቱን ይጠቁማል፡፡ ያለ ምንም ጥርጥር ይህን መሠሉ እድገት በሌሎችም መስኮች እንደሚኖር መገመት አዳጋች አይደለም፡፡ የመሠረተ ልማት እድገቱ ሌላ ገፅታ ደግሞ አለው። ይህም ከጥራት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ መቼም ጥራት የመሠረተ ልማት መስፋፋት ዋነኛ ደንቃራ መሆኑን መረዳት አያቅትም፡፡ በሁሉም የመሠረተ ልማት አይነቶች ጥራት ከፍተኛ ችግር እንደሆነ ዘልቋል፡፡ ሌሎቹን የመሠረተ ልማት አይነቶች ትቼ በስራዬና በትምህርቴ ምክንያት ስለምከታተለው የሀገሪቱ የቴሌኮም ዘርፍ፣ ከ13 ዓመታት በላይ እንዳገለገለ ባለሙያ፤ የዘርፉ የጥራት ችግር ጥልቅና ውስብስብ ምክንያቶች ያሉት እንደሆነ አስባለሁ፡፡
የማይቆራረጥ የቴሌኮም አገልግሎት ይኖር ዘንድ የማይቆራረጥ የሀይል አቅርቦት መኖር የግድ ነው፡፡ የማይቆራረጥ የሀይል አቅርቦት በሌለበትና የመጠባበቂያ ሀይል ባልተዘጋጀበት ሁኔታ ግን የቴሌኮም መስመሮችም ሆነ የማስተላለፊያ ጣቢያዎች በአግባቡ ሊሠሩ አይችሉም፡፡ ምክንያቱ ባይታወቅም የሀይል አቅርቦቱ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ መቆራረጥ ይስተጓጎላል። ይህም በምሬት ለምናስተናግደው የቴሌኮም አገልግሎት መቆራረጥ የራሱን ድርሻ መጫወቱ አልቀረም። የሀገሪቱ አቅርቦት መቆራረጡ እንዳለ ሆኖ አብዛኞቹ የቴሌኮም ማስተላለፊያ ጣቢያዎች ደግሞ ደጋፊ ወይም ምትክ የሀይል አቅርቦት መስጫ ጀኔሬተሮች የሏቸውም፡፡ ይህም ማለት የሀይል አቅርቦት በተቋረጠ ቁጥር የቴሌኮም አገልግሎትም ይቋረጣል ማለት ነው፡፡
ግልፁን እንነጋገር ከተባለ ይህ ችግር የኢትዮ ቴሌኮም ችግር ነው፡፡ እንደ ቴሌኮም አገልግሎት ሠጪ ተቋም፣ሁሌም የማስተላለፊያ ጣቢያዎቹ በቂና አስተማማኝ የሀይል አቅርቦት ማግኘታቸውን ከዛም ባለፈ ምትክ ሀይል ማቅረቡን ማረጋገጥ ይጠበቅበታል፡፡ ገንዘብ ለመሠብሠብ የሚያሳየውን ፍላጎት ያህል ይህንን ሃላፊነቱንም መዘንጋት የለበትም፡፡ አንዳንድ ሃላፊዎች ሊያደርጉት እንደሚሞክሩት፣ይህንን የቴሌኮም አገልግሎት መቆራረጥ በመሠረተ ልማት አቅራቢው ላይ መለጠፍ ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ እንደማለት ነው፡፡ የመሠረተ ልማት አቅራቢው ሀላፊነት መሠረተ ልማቱን ማቅረብና በአግባቡ መስራቱን መፈተሽ ብቻ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ያለው የቴሌኮም አገልግሎት ሰጪው ስራ ነው የሚሆነው፡፡
ሌላው እዚህ ላይ ማንሣት የሚገባው የቴሌኮም መሠረተ ልማት ጥገና ጉዳይ ነው። መቼም ኢትዮ ቴሌኮምን የሚከታተል ሁሉ የባለሙያ እጥረት የሚያንደፋድፈው ተቋም መሆኑን ለመገንዘብ ብዙም ጊዜ አይፈጅበትም። ይህ የባለሙያ እጥረቱ ደግሞ ከለውጡ በኋላ በእጅጉ ተባብሷል፡፡ በዚህም የተነሳ የጥገና ክፍሉ ተገቢውን እለታዊ (ቀላል) እንዲሁም ወቅተዊ (መካከለኛ እና ከባድ) ጥገና ማድረግ የማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ እዚህ ላይ ልብ ማለት የሚገባው የቴሌኮም መሠረተ ልማቶች ከ80 በመቶ በላይ የሆነ አቅማቸውን መጠቀም ከጀመሩበት እለት ጀምሮ ጥገና የሚያሻቸው መሆኑን ነው፡፡
ለኢትዮ ቴሌኮም፣ ጣቢያዎች መሠረታዊ የአገልግሎት አከርካሪዎች መሆናቸውን የዘነጋ ይመስላል፡፡ ተቋሙ ለወጣባቸው ወጪ ባይጨነቅ እንኳን ለሚሠጡት ኢኮኖሚያዊ ጥቅም መጨነቅ ነበረበት፡፡ መቼም አለመታደል ነው፡፡
ከላይ የተጠቀሱት ችግሮች እየተደራረቡ መጥተው አሁን የቴሌኮም መሠረተ ልማት ጥራት ችግር ህዝብን እያማረረው ይገኛል፡፡ ለነገሩማ መማረሩ ለአዲስ አበባ ነዋሪዎች መቀጠሉ አይቀርም፡፡ ለምን ቢባል ደግሞ ሀላፊነት በጎደለው የቴሌ ውሳኔ ምክንያት ነው፡፡
ቴሌ የበፊቱን መሠረተ ልማት በሙሉ ነቅሎ በሌላ ለመተካት ወስኗል፡፡ አይ ተቆጪ ማጣት! በዚህ ውሳኔ ታዲያ ሚሊዮኖች የፈሠሠበት መሠረተ ልማት ተነቅሎ ይጣልና በሌላ ሚሊዮኖች በወጣበት ይተካል፡፡ እስከዛው ታዲያ እኛም በኮሙኒኬሽን እጦት እንዳክራለን፡፡
በቴሌኮም የሚታየው የጥራት ችግር ከላይ እንደተገለፀው በሁሉም መስኮች መታየቱ አልቀረም። የሚገርመው ግን የጥራት ችግሩን አስመልክቶ አሁንም ቢሆን ተገቢው አካል ሀላፊነት አለመውሰዱና አለመጠየቁ ነው፡፡
እስከ መቼ ይሆን ባለ መንገዱ በኮንትራክተር፣ ባለ መብራቱ በመስመር፣ ባለ ስልኩ በአቅራቢ እያመካኘ የሚቀጥለው? መቼ ነው ሁሉም ወገን ለስራው ሀላፊነቱን መውሰድ የሚጀምረው? ያንን ጊዜ እንናፍቃለን፡፡
(ኪሩቤል ሆነ፤በኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ የመጀመሪያ ዲግሪ እንዲሁም በቴሌኮም ኢንጂነሪንግ የማስተርስ ዲግሪ ያላቸው ሲሆን ላለፉት 13 ዓመታት በኢትዮጵያ የቴሌኮም ሴክተር ውስጥ በተለያየ ሀላፊነት ሠርተዋል፡፡ ለበለጠ መረጃ በኢሜል አድራሻቸው በ This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ይገኛሉ፡፡)   

ሱፕር ኢንዱራሊ እና አሶሴሽኑ
የሱፕር ኢንዱራሊ የሞተር ስፖርት ውድድሮችን ከ3 ዓመት በፊት ከሞተር ስፖርት አሶሴሽኑ ጋር በመተባበር እንዲጀመር ያስቻሉት 3 የስፖርቱ አፍቃሪዎች እና የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪዎች ናቸው፡፡  የመጀመርያው የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪ የሆነው እና በሞተር ብስክሌት በማስጎብኘት፤ ሽያጭ እና ጥገና በማድረግ የሚታወቀው ፍላቭዮ ቦናዮ ነው፡፡ ሌሎቹ ሁለት ግለሰቦች የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪዎችና በኢትዮጵያ የሞተር ስፖርት አሶሴሽን ቦርድ አባልነት የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ አንደኛው  በዓለምአቀፍ የዴቨሎፕመንት ተቋም ድርጅት የሚሰራውና የሞተር ብስክሌት ውድድሮች እና ተወዳዳሪዎች ተወካይ የሆነው ክሪስቶፍ  አምበርት ነው፡፡  ሌላኛው  በሞተር ስክሌት ውድድሮች ከፍተኛ ልምዱን በማጋራት የሚንቀሳቀሰውና በገጠር አካባቢዎች የሚካሄዱ  የመኪና ውድድሮችን በመምራት እና የተወዳዳሪዎቹ ተወካይ ሆኖ የሚያገለግለው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኤክስፐርቱ ሲሞኒ ፌራሪ ነው፡፡ የውድድሩ ስያሜ  የተገኘው ኢንዱሮ ከሚባል የሞተርሳይክል የውድድር አይነትን ለመግለፅ ከሚጠቅም የጣሊያን ቃል እና ራሊን ደግሞ የመኪና ውድድር ይወክላል ተብሎ ሁለቱን ስያሜዎች በማጣመር ሱፕር ኢንዱራሊ ተብሎ የተፈጠረ ነው። የሱፕርኢንዱራሊ የመኪና እና የሞተር ብስክሌት ውድድር የተመሰረተበት ዋና ዓላማ አሶሴሽኑ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ትኩረት የሚያገኙ ውድድሮችን በማዘጋጀት  የመንግስትን ትኩረት እና ድጋፍ ለማነሳሳት በመታሰቡ ነው፡፡ በሱፐር ኢንዱራሊ አማካኝነት በመኪናና በሞተር ብስክሌት  በየዓመቱ በገጠር አካባቢዎች ቢያንስ ሁለት ውድድሮችን ለማዘጋጀት በጠነሰሱት የመነሻ ሃሳብ ዘንድሮ ለሶስተኛ ጊዜ ውድድሩን በተሳካ መንገድ ማካሄድ ተችሏል፡፡  
 ባለፈው ሳምንት  በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ገላን ቀበሌ 3ኛው የሱፕር ኢንዱራሊ የመኪና እና የሞተር ብስክሌት ውድድር በኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት ተስፋ ሰጭ ሁኔታዎች እንዳሉ  ማስተዋል ተችሏል። የመጀመርያው ተስፋ ሰጭ ሁኔታ ከውጭ አገር ተሳታፊዎች እንዲመጡ አባላቱ እና አሶሴሽኑ  ከፍተኛ ጥረት አድርገው ስለተሳካላቸው ነው። ከጅቡቲ የመጡ ከ10 በላይ  የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪዎችን ኛው ሱፕርኢንዱራሊ አሳትፏል፡፡ በቅተዋል፡፡ በሌላ በኩል በተለያዩ ካታጎሪዎች በመኪና እና የሞተር ብስክሌት ውድድሮቹ ኢትዮጵያውያን ስፖርተኞች በብዛት መሳተፋቸውና በውጤታቸው ደረጃ ውስጥ በመግባት  ተሸላሚ መሆናቸው አበረታች ነው፡፡ በተለይ አንዳንድ ወጣት ኢትዮጵያውያን የሞተር ስፖርት አፍቃሪዎች ባላቸው አቅም መኪኖቻቸውንና የሞተር ብስክሌቶቻቸውን በመለስተኛ ጋራጆች ጠግነው ለውድድር በመቅረብ ያለቸውን የተሳትፎ ፍላጎት በማሳየት ለውድድሩ አዘጋጆች መነቃቃትን ፈጥረዋል። በሱፕርኢንዱራሊ ውድድር በተለይ በሞተር ብስክሌቶች የተካሄደው ውድድር በተወዳዳሪዎች አስገራሚ ብቃት በመወዳደደርያ ሞተሮች ጥራት እና አቅም የተሳካ ነበር፡፡ በአንፃሩ በመኪና ውድድሩ በስፖርቱ አንጋፋ የተሳትፎ ልምድ ያላቸው ተወዳዳሪዎች የነበሩ ቢሆንም ብዙዎቹ የመወዳደርያ መኪናዎች ከ10 ዓመት በላይ ያገለገሉ መሆናቸው እና በየካታጎሪው የተወዳደሩ መኪኖቹ ባላቸው አቅም እና አይነት ከፍተኛ ልዩነት ስለነበራቸው ያን ያህል የሚያረካ ፉክክር እንዳይታይ አድርጓል፡፡ በአጠቃላይ  በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ በነበረው ዝግጅት የተሻለ ነው፡፡ በገጠር አከባቢ የሚገኘውን መወዳደደርያ ስፍራ በብቃት ተሰናድቷል፡፡ በውድድሮች ወቅት አስፈላጊው ጥበቃ እና ደህንነት እንዲኖር በእቅድ ተሰርቷል፡፡ የውድድሩ ተመልካቾችን በዝተዋል። ከሞተር ስፖርት አሶሴሽን ጋር በስፖንሰር ድጋፍ ሰጪ ሆነው እስከ ስምንት ኩባንያዎች መስራታቸውም እንደ ውጤት ሊጠቀስ ይችላል። የሱፕርኢንዱራሊ ውድድሮችን ለማካሄድ የሞተር ስፖርት አፍቃሪዎች ያደረጉትን ጥረት በተባባሪነት በመደገፍ እና ከስፖርት ኮሚሽን ጋር ተቀራርቦ በመስራት የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽንም ንቁ ተሳትፎ አድርጓል፡፡ የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን በአሁኑ ወቅት 265 አባላት ያሉት ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 150ዎቹ የስፖርቱ ተወዳዳሪዎች ናቸው፡፡ በአዲስ የቦርድ መዋቅር መስራት ከጀመረ አንድ አመት ያልሆነውን አሶሴሽን በፕሬዝዳንትነት የሚመሩት አቶ ኤርምያስ አየለ ናቸው፡፡ በታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅነት በመስራት ላይ የሚገኙት አቶ ኤርምያስ አየለ የመካኒካል ኢንጅነሪንግ ምሩቅ መሆናቸው ከሞተር ስፖርት ጋር ያላቸውን ቅርበትን ያመለክታል፡፡ የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኤርምያስ አየለ የሱፕርኢንዱራሊ ውድድርን ለማዘጋጀት 150ሺ ብር ገደማ ወጪ መደረጉን ለስፖርት አድማስ ሲናገሩ ውድድሩ ስኬታማ እንደነበርና በቀጣይ ሌሎች ውድድሮችን ለማዘጋጀት በአሶሴሽኑ በኩል ለሚደረገው ጥረት አበረታች ውጤቶች የተገኙበት ነበር ብለዋል፡፡ ዘንድሮ በአሶሴሽኑ የሚካሄዱ ሌሎች ሶስት ውድድሮች እንዳሉ ያስታወቁት አቶ ኤርምያስ፤ በመጋቢት እና በግንቦት ወር መጨረሻ ሁለት የከተማ ዙር የመኪና ውድድሮች እንደሚካሄዱ እና በሰኔ ወር ደግሞ በላንጋኖ አካባቢ ልዩ የራሊ ውድድር  ለማዘጋጀት እቅድ አለን ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ የሞተር ስፖርት እንቅስቃሴ ከ65 ዓመታት በላይ ታሪክ አለው፡፡  በአሶሴሽኑ አባላት እና  የስፖርቱ አፍቃሪዎች በሚያደርጉት ጥረት  በየዓመቱ በሚካሄዱ የተለያዩ ውድድሮችን ህልውናውን ጠብቆ ቆይቷል። ይሁንና በኢትዮጵያ የሞተር ስፖርት እንቅስቃሴ በሽልማት መጠን ማነስ፤ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪዎችን በብዛት ባለማሳተፍ፤ ከፍተኛ ደረጃ ያላቸውን የውድድር መኪናዎች በበቂ ሁኔታ እና በተመጣጣኝ
ተሳትፎ ባለማግኘት ጉልህ ለውጥ እና እድገት እያስመዘገበ አይመስልም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በ1965 ላይ ዓለም አቀፍ ደረጃ የነበረውና ከፍተኛ እውቅና ያገኘ 5000 ኪሎሜትር የሚሸፍን ሃይላንድራሊ ተካሂዶ ነበር፡፡ ከዚሁ ታሪካዊ ውድድር በኋላ ግን ተመሳሳይ ደረጃ ያለውን ውድድር ለማዘጋጀት አልተቻለም፡፡ ከታሪካዊው የኢትዮጵያ ሃይላንድ ራሊ በኋላ በተለይ በ1970 ዎቹ መጀመርያ  ተቀማጭነቱን በአዲስ አበባ ባደረገው የጣሊያን ስፖርት ክለብ ጁቬንትስ አማካኝነት ለስምንት አመታት ከ41 በላይ ውድድሮች ተደርገዋል፡፡  ውድድሮቹ በተሳታፊዎች ብዛት እና በውድድር ደረጃቸው የላቁ እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ ከእነዚህ ውድድሮች በኋላ የሞተር ስፖርት አሶሴሽኑ እንቅስቃሴ ለሁለት አስርት አመታት ተስተጓጉሎ ቆይቶ መነቃቃት የጀመረው በ1990ዎቹ መግቢያ ነበር፡፡ አሶሴሽኑ በስፖርቱ ፍቅር የወደቁ አባላቱን መልሶ በማስተባበር በስፋት መንቀሳቀስ ጀምሮ ከ26 በላይ የከተማ እና የገጠር አካባቢ የመኪና ውድድሮችን በየዓመቱ በማካሄድ የስፖርቱን ተወዳጅነት ሲያጎለብት ቆይቷል፡፡
ሞተረኛው ፍላቭዮ ቦናዮ  
ባለፈው ሰሞን በተካሄደው 3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ ከመኪናው ውድድር በተሻለ በተወዳዳሪዎች ምርጥ ብቃትና ተመጣጣኝ የመወዳደደርያ ሞተር ብስክሌቶች አስደናቂ ፉክክር የተደረገበት የሞተር ብስክሌት ውድድሩ ነበር፡፡ ለውድድሩ መሳካት ደግሞ የሞተር ስፖርት አሶሴሽን አባልና የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪ የሆነው ፍላቭዮ ቦናዮ ያበረከተው ሁለገብ አስተዋፅኦ ይመሰገናል።  በኢትዮጵያ  የተወለደው ፍላቭዮ ከሞተር ጋር የተዋወቀው ገና በታዳጊነቱ ነው፡፡ በቤተሰባቸው ሞተር ብስክሌቶችን ለመጓጓዣ መጠቀም ባህል ነበር፡፡ እንደውም እናቱ በሞተር ብስክሌት ወደ ትምህርት ቤት ያመላልሱት እንደነበር ፍላቭዮ ቦናዮ ያስታውሳል፡፡ በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ ላይ የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪዎችን ከጅቡቲ በመጋበዝ፤ የመወዳደርያ ሞተሮችን በማቅረብ እና የውድድሩን ሂደት በማስተባበር ከፍተኛ ሚና የነበረው ፍላቭዮ በውድድሩ የመጀመርያ ዙር ከሞተሩ ላይ ያስፈነጠረው የመከስከስ አደጋ ገጥሞት ነበር፡፡ መለስተኛ ህክምና ከወሰደ በኋላ በቀሩት ሁለት ዙሮች የሞተር ብስክሌቱን በከፍተኛ ብቃት ነድቶ ሁለተኛ በመውጣት በስፍራው የነበሩ ተመልካቾችን አድናቆት አትርፏል፡፡ ፍላቭዮ ቦናዮ ከሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪነቱ ባሻገር በሞተር ብስክሌት ጉዞ አገርን በማስጎብኘት እየሰራ ይገኛል። በተጨማሪም ሞተሮችን ከውጭ አስመጥቶ ይሸጣል፤ የመለዋወጫ እቃዎችን ያቀርባል፡፡ የጥገና አገልግሎትም በመስጠት በስፋት ይንቀሳቀሳል፡፡ አፍሪካን ራይዲንግ አድቬንቸርስ ቱርስ በተባለ ኩባንያው ወደ ኢትዮጵያ ገብተው በሞተር ጉዞ ጉብኝት ማድረግ ለሚፈልጉ ቱሪስቶች  ምርጥ የሞተር ብስክሌቶችን በማቅረብ እና በራሱ ሞተር ጉዞውን በመምራት ይሰራል ፡፡ ፍላቭዮ በዚህ ኩባንያው የሚጠቀምባቸው 15 ሞተር ብስክሌቶች  ኬቲኤም የሚባሉ ሲሆን የኦስትሪያ ስሪቶች ናቸው፡፡ ኬቲኤም ሞተሮች  ለገጠር መንገዶች እና ለረጅም ርቀት  ጉዞዎች ተመራጮች እንደሆኑ የሚገልፀው ፍላቭዮ ከአውሮፓ ፤ ከአሜሪካ እና ከአውስትራሊያ የሚመጡ ቱሪስቶችን በብቃት እያስተናገደ እንደሆነ ተናግሯል። ለሞተር  ብስክሌት ማሽከርከርያነት እንደኢትዮጵያ የሚመች ሌላ አገር የለም የሚለው ፍላቭዮ የአየሩ ፀባይ፤ መልክዓምድሩ፤ አሸዋው፤ ተራራው፤ በርሃው በአጠቃላይ  የህዝቡ ባህልና አቀባበል ለዚህ ምክንያት ነው ይላል፡፡ ደንበኛ የሞተር ብስክሌቶች ዋጋቸው ከ80ሺ እስከ 500ሺ ብር እንደሚደርስ የገለፀው አሶሴሽኑ ከውጭ አገር ሞተር ብስክሌቶችን በማስመጣት ወጣቶችን በስፖርቱ እንዲያድጉ በማበረታት መስራት አለበት ሲል ይመክራል።  በኢትዮጵያ የሞተር ስፖርት እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳትፎ በማድረግ ከ35 ዓመታት ልምድ እንዳለው የሚናገረው ፍላቭዮ፤  የሞተር ብስክሌት ውድድሮች በተለይ ከሁለት አስርት ዓመታት በፊት በተሻለ ደረጃ እንደነበሩ  በወቅቱ የነበረው  አሶሴሽን ሞተር ብስክሌቶችን ከውጭ በማስገባት ለወጣት ስፖርተኞች የተሳትፎ እድል በመፍጠር ይሰራ እንደነበርና በዓመት ውስጥ እስከ አምስት የሞተር ብስክሌት ውድድሮች እየተዘጋጁ ከፍተኛ እድገት እየታየ  የነበረበትን ሁኔታ ባለፉት 3 ዓመታት ለመመለስ ጥረት ላይ ነን ብሏል፡፡
በመኪና ውድድር አንጋፋ የሆኑ፤ ተደጋጋሚ ተሳትፎ በማድረግ የሚታወቁ ተወዳዳሪዎችን በመለየት ወደ አገር ውስጥ ከቀረጠ ነፃ የመወዳደርያ መኪኖችን እንዲያስገቡ የሚያስችል አሰራር መፈጠር አለበት የሚሉት የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኤርምያስ አየለ፤ ይህን ተግባር ለማከናወን አሶሴሽኑ እና እና የፌደራል ስፖርት  ኮሚሽን በጋራ ተቀናጅተው አስፈላጊውን መስፈርት በማውጣት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበው፤ መንግስት  ለስፖርቱ እድገት ፈታኝ ሁኔታዎችን እየፈጠረ የሚገኘውን የመወዳደርያ መኪናዎች ችግር ለመቅረፍ ከቀረጥ ነፃ መኪኖች የሚገቡበትን አሰራር እንደሚፈቅድ ተስፋ እናደርጋለን ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የውድድር መኪኖች አርጅተዋል፤ መፍትሔውስ
የሞተር ስፖርት  እንደ ቅንጦት ተግባር መታየት የለበትም የሚለው የሱፕኢንዱራሊ ተባባሪ አዘጋጅ እና የሞተር ብስክሌት ተወዳዳሪ የሆነው ክሪስቶፍ  አምበርት ሲሆን ፤ በተለይ የሞተር ብስክሌት ውድድር ለተወዳዳሪዎችም ሆነ ለአዘጋጆች ዝቅተኛ ወጭ ስለሚጠይቅ በየትኛውም አገር ሊዘወተር የሚገባ ተወዳጅ የስፖርት ውድድር እንደሆነ ያስገነዝባል። በኢትዮጵያ የሞተር ስፖርት እንቅስቃሴ ከፍተኛ እድገት ለማሳየት የማይቻልበት ምክንያት ምናልባት በመወዳዳርያ መኪናዎች  ያለው ሁኔታ ለረጅም ጊዜ ሳይቀየር መቀጠሉ እንደሆነ የሚያመለክተው ክሪስቶፍ፤ ብዙዎቹ የመወዳደርያ መኪናዎች ከ10 ዓመታት በላይ ያገለገሉ፤ ያረጁ እና የወቅቱን ደረጃ የማያሟሉ መሆናቸው የውድድሮችን ማራኪነት አደብዝዞታል ይላል፡፡ አሶሴሽኑ ካለፉት 3 ዓመታት ወዲህ በሚያዘጋጃቸው ውድድሮችን የመንግስትን ትኩረት ለማግኘት ጥረት መደረጉን የገለፀው ክሪስቶፍ ሃምበርት፤  የመወዳደርያ መኪናዎችን ወደ አገር ውስጥ ከቀረጥ ነፃ ለማስገባት በየውድድሮቹ የሚገኙ ስኬቶች አስተዋፅኦ እንዳላቸው ተናግሯል፡፡ የውድድር መኪናዎች ዋና ግልጋሎታቸው ለውድድር ብቻ እንደሆነ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን እንደሚገነዘብ አምናለሁ የሚለው ክሪስቶፍ፤ ከተወዳዳሪዎች መካከል ብዙዎቹ በራሳቸው ወጭ መኪኖችን ገዝተው ከቀረጥ ነፃ ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት በተደጋጋሚ ለሚያነሱት ጥያቄ ፈጣን ምላሽ  መገኘቱን ተስፋ እናደርጋለን ብሏል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በርካታ ወጣት ኢትዮጵያውያን  በውድድሮቻችን ለመሳተፍ ያላቸውን ፍላጎት በተደጋጋሚ እንደገለፁ ያመለከተው ክሪስቶፍ  አምበርት ፤ እነዚህ ወጣቶች ወቅቱን የጠበቀ የውድድር መኪናዎችን እና መለዋወጫዎችን ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት እንዲችሉ አስፈላጊው ትብብር መንግስት ቢያደርግላቸው ለስፖርቱ እድገት ጠቃሚ እርምጃ ይሆናል በሚል ይመክራል፡፡ ባለፈው ሰሞን በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ ከተሳተፉ የመኪና ተወዳዳሪዎች አንዱ ሰርጂዮ ኦሊቬሮ ነው፡፡ሪክ አውቶ የሚባል ኩባንያን በመወከል በኢትዮጵያ  የሞተር ስፖርት ውድድሮች ላለፉት 10 ዓመታት የተወዳደሩት ሰርጂዮ ኦሊቬሮ  ተሳትፏቸው  ለስፖርቱ ካላቸው ፍቅር የመነጨ እንደሆነና በየውድድሮቹ በሚያስመዘግቡት ውጤት ተበረታትው እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ ውድድር ላይ   ሰርጂዮ ኦሊቬሮ  ሲነዷት የተመለከትኩት የውድድር መኪና ቶዮታ ኮሮላ ኮንክዌስት የምትባል ስትሆን የተሰራችው በደቡብ አፍሪካ  ነው፡፡ በዚህች መኪናቸው በደቡብ አፍሪካና በአጎራባች አገራት በተካሄዱ በተለያዩ ውድድሮች ተሳትፎ በማድረግ ብቻ ሳይሆን በማሸነፍም እውቅና ማትረፋቸውን የነገሩኝ ሚስተር ሰርጂዮ በአንድ ወቅት በዚምባቡዌ የተዘጋጀ ራሊ ላይ ከቱርቦ መኪኖች ጋር በመወዳደር ማሸነፋቸው የማይረሱት ገድል እንደሆነ አውግተውኛል፡፡ ይህችን ታሪከኛ ቶዮታ ኮሮላ ኮንኬስት መኪና ወደ ኢትዮጵያ አስገብተው መወዳደር የጀመሩት ከ12 ዓመታት በፊት እንደነበር ያስታወሱት ሰርጂዮ አሊቬሮ ከመግባቷ በፊት ተገልበጣ ከጥቅም ውጭ ሆና ስለነበር አዲስ ሞተር እና ቦዲ አሰርተውላት ያስመጧት በአጠቃላይ እስከ 200ሺ ብር ወጭ ማድረጋቸውን ገልፀዋል።  በደቡብ አፍሪካ በሚዘጋጁ የመኪና ውድድሮች  ላይ የሚሳተፉ ስፖርተኞች በአዳዲስ መኪናዎች ለመወዳደርና ያሏቸውን መኪናዎች ብቃት ለማሳደግ የሚያስፈልጓቸውን የመለዋወጫ እቃዎች ሲገዙ ከቀረጥ ነፃ በመሆኑ ብዙም ወጭ የለብንም ነበር የሚሉት ሰርጂዮ ኦሊቬሮ መኪናቸው ወደ ኢትዮጵያ ካስገቡ በኋላ በየዓመቱ በሚካሄዱ ውድድሮች ብቃቷ እየቀነሰ መምጣቱን በቅሬታ ይገልፃሉ፡፡ በኢትዮጵያ ለሚዘጋጁ የመኪና ውድድሮች ብዙም ዋጋቸው ያልተወደደ ምርጥ  መኪናዎችን ከደቡብ አፍሪካ ማስመጣት እንደሚቀል የሚመክሩት ሚስተር ሰርጂዮ ኦሊቬሮ፤ ብዙዎቹ መኪናዎች ዋጋቸው ከ10 ሺ ዩሮ ጀምሮ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ የውድድር መኪና በሞተሩ ጉልበት ፤ በፍሬን እና በነዳጅ መስጫ ክፍሎቹ፤ በጎማው ፤ በባሌስትራው እና በተለያዩ የመኪናው አካላት የተለየ ጥንካሬ እና ብቃት የሚያስፈልግ በመሆኑ ከመደበኛው በዋጋው ይወደዳል፡፡ አንዳንድ መደበኛ መኪኖችን በተለያዩ የሞዴፊክ ስራዎች አጠናክሮ ለውድድር ብቁ አድርጎ ለማዘጋጀትም ብዙ ወጭ ይጠይቃል፡፡ በኢትዮጵያ መኪኖችን ለውድድር በደንብ አዘጋጅቶ ለመስራት አቅም ያላቸው መካኒኮች እና ጋራዦች ቢኖሩም ብቁ መኪኖችን ከውጭ ማስገባት መንግስት በሚጥለው ቀረጥ ከባድ መሆኑ የመኪና ውድድሮችን ማዳከሙን የሚናገረው ደግሞ የከተማ ውስጥ የመኪና ውድድሮችን በማስተባበር እና ተወዳዳሪዎችን በመወከል  በአሶሴሽኑ የቦርድ አባል ሆኖ የሚያገለግለው ኸርነስቶ ሞሊናሪ ነው፡፡ ኸርነስቶ ሞሊናሬ  በሞተር ስፖርት ተወዳዳሪነት የ20 ዓመታት ልምድ ካላቸው ስፖርተኞች ዋናው ተጠቃሽ ሲሆን በኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን በሚዘጋጁ ውድድሮች ካለፉት 10 ዓመታት ወዲህ በንቃት ተሳትፎ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ኤምአይኤስኤሲ የተባለ ኮንስትራክሽን ኩባንያ ባለቤት የሆነው ኸርነስቶ ሞሊናሪ እና ረዳት ሾፌሩ ኢሚሊዮ ግራፌቲ የሚነዷት መኪና ፎርድ ኤስኮርት የተባለች ናት፡፡  በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ ከነበሩት የውድድር መኪናዎች ባላት ግዙፍ የሞተር ጉልበት እና ብቃት የተለየችው የእነ ኸርነስቶ ፎርድ ኤስኮርት   በካታጎሪ 1 የተዘጋጀውን ውድድር አሸንፋለች፡፡ ተመሳሳይ ብቃት እና ጉልበት ካላቸው መኪኖች ጋር ውድድሮችን ማድረግ እንደሚያስፈልግ የሚናገረው ኸርነስቶ ሞሊናሪ በቀጣይ ጊዜያት በየካታጎሪው የሚወዳደሩ መኪናዎች በዝተው አስደናቂ ፉክክር የሚደረግባቸውን ሁኔታዎች እናፍቃለሁ ብሏል፡፡ በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ አግኝቼ ካነጋገርኳቸው የመኪና ተወዳዳሪዎች መካከል አዲስ አበባ ውስጥ የማተሚያ ቤት ያለው ሳሚ ጁሴፔ ሙሳ እና የራሱን የግል ትምህርት ቤት የሚያንቀሳቅሰው ረዳት ሾፌሩ ሳቫሪዮ ጉላ ይጠቀሳሉ። ጁሴፔ እና ሳቫሪዮ በውድድሩ የሚወዷትን መኪናቸውን በማሽከርከር በመሳተፋቸው  ብቻ እርካታ እንደሚሰማቸው ይገልፃሉ፡፡ ኦፔል ካዴት ጂኤስአይ የተባለችው መኪናቸው ባለ 2000 ሲሲ የፈረስ ጉልበት ያላት ስትሆን ካምቢዮው ብቻ 7ሺ ዩሮ የተገዛ ነው፡፡ በጣሊያን ይኖር በነበረ ጊዜ በህገወጥ የጎዳና ላይ የመኪና ሽቅድምድሞች ረጅም ጊዜ ይወዳደር እንደነበር ለስፖርት አድማስ የገለፀው ጁሴፔ በኢትዮጵያ መኖርና መስራት ከጀመረ በኋላ በስፖርት ውድድሩ ተሳትፎውን እንደቀጠለ ይናገራል።  በጣሊያን ጎዳናዎች በገንዘብ ውርርድ በሚካሄዱ የመኪና ሽቅድምድሞችን በሚኒ ኩፐር መኪናው እየተሳተፈ ደህና ገቢ ያገኝ እንደነበር የሚያስታወሰው ጁሴፔ ፤ ውድድሩ ህገወጥ ስለነበር በፖሊስ መኪና ከተወረሰችበት በኋላ እንደተወው አጫውቶኛል፡፡ ገልጿል፡፡ ጁሴፔ እና ሳቫርዮ ኦፔል ካዴት መኪናቸውን ከ13 ዓመታት በላይ ስለተወዳደሩባት በመሸጥ አዲስ መወዳደርያ የመግዛት ፍላጎት ነበራቸው፡፡ መኪናዋ ባለችበት ወቅታዊ ሁኔታ እስከ 200 ሺ ብር እንደምታወጣም ይናገራሉ፡፡ ይሁንና ወደ ኢትዮጵያ  አዲስ መኪና ለማስገባት እና ኦፔል ካዴት መኪናቸውን ለመቀየር ከባድ ወጭ ስለሚጠይቅ ሽያጩን አልደፈሩትም፡፡
አማራጭ መፍትሄ ያደረጉት ደግሞ ከየእንዳንዳንዱ ውድድር በፊት ከፍተኛ የጥገና እና የሞዲፊክ ስራ በማከናወን ብቃቷን መጠበቅ ነው፡፡ የሞተር ስፖርት ከቤተሰቡ እንደወረሰው ለስፖርት አድማስ የተናገረው ሌላው የመኪና ተወዳዳሪ ሉካ ኦሊቬሮ ይባላል፡፡  አያቱ፤ አባቱ እና አጎቱ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በደቡብ አፍሪካ በሚካሄዱ የሞተር ስፖርት ውድድሮች በተሳትፏቸው እንደሚታወቁ የሚናገረው ሉካ ኦሊቬሮ ፤ ከረዳት ሾፌሩ ጥበቡ ቸርነት ጋር  በ3ኛው ሱፕርኢንዱራሊ የተሳተፈው ፔጆት 309 1.9 ጂቲአይ በተባለች መኪና ነው፡፡ ይህችን መኪና ላለፉት ሁለት ዓመታት ከፍተኛ ጥገና በማድረግ ሲያዘጋጃት መቆየቱን የገለፀው ሉካ ኦሊቬሮ በሱፕርኢንዱራሊው ፈታኝ የመወዳደርያ ጎዳና መበላሸቷ እንደማይቀር ባውቅም በመኪና ውድድሮች በአስቸጋሪ ሁኔታ መፎካከርን እና ፈተናዎችን ማለፍ በሚፈጥረው የጀበደኛነት ስሜት ጋር ፍቅር በመውደቄ ያን ያህል አያሳስበኝም ብሎ ወደፊት አዲስ የውድድር መኪና ለመግዛት ምኙ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ተስፋ አደርጋለሁ ብሏል፡፡
የስፖርቱ የወደፊት አቅጣጫዎች
ከኢንዱራሊ ውድድሮች አዘጋጆች አንዱ የሆነው ሲሞኒ ፌራሪ በሰጠው አስተያየት በኢትዮጵያ ውስጥ የሞተር ስፖርት ውድድሮችን በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ የሚያስችሉ ተስፋ ሰጭ ሁኔታዎች አሉ፡፡ በመጀመርያ ደረጃ በአሶሴሽኑ አባልነት የሚንቀሳቀሱ በርካታ የስፖርቱ አፍቃሪዎች ለረጅም አመታት የስፖርቱ ሂደት እንዲቀጥል በተሳትፎ የሚያደርጉት ጥረት በየዓመቱ በመደበኛነት ውድድሮች እንዲዘጋጁ አስችሏል ያለው ሲሞን ፌራሪ  ፤ወደፊት  በእነዚህ ውድድሮች ላይ የውጭ አገር ተሳታፊዎች እየበዙ ከመጡ፤ የመወዳደርያ መኪናዎችን ከቀረጥ ነፃ ወደ አገር ውስጥ ማስገባት ከተቻለ ፤ በአሶሴሽኑ በኩል ከፍተኛ የቱሪዝም መስህብን የሚፈጥሩ እና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ውድድሮች ለማዘጋጀት እንደሚቻል አስገንዝቧል፡፡
በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የመኪና እና የሞተር ስፖርት ውድድር ማዘጋጀት የታሪክ ሃላፊነት እንደሆነ የገለፀው ደግሞ ክሪስቶፍ ሃምበርት ነው፡፡ ድሮ በሃይለስላሴ ዘመን የ5000 ኪሎሜትር ውድድር ሃይላንድ ራሊ በሚል ዓለም አቀፍ እውቅና ያገኘ ውድድር መዘጋጀቱን የሚያስታወሰው ክሪስቶፍ ሃምበርት ተመሳሳይ ደረጃ ያለውን ውድድር ለማዘጋጀት አሶሴሽኑ የተሟላ ብቃት እንዳለው በልበሙሉነት ይናገራል፡፡
ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የሞተር ስፖርት ውድድር በኢትዮጵያ መዘጋጀቱ ለቱሪዝም እድገት አስተዋፅኦ ይኖረዋል የሚለው ክሪስቶፍ  አምበርት፤ በኬንያ የሳፋሪ ራሊ ከመላው ዓለም በርካታ ተወዳዳሪዎችና የስፖርት አፍቃሪዎችን በመማረክ ከፍተኛ ገቢ እንደሚገኝበት በምሳሌነት ጠቅሶ ወደፊት አሶሴሽኑ በሚያዘጋጃቸው ውድድሮች በርካታ ተመልካች በማግኘት፤ ከተለያዩ አገራት ታዋቂ ተወዳዳሪዎች በብዛት በማሳተፍ እና ስፖርቱን የሚያፈቅሩ ቱሪስቶችን በመማረክ ለስፖርቱ እድገት በመስራት እና ከፍተኛ ጥቅም ለማግኘት እቅዳችን ነው ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ሞተር ስፖርት አሶሴሽን ከአባላቱ ጋር በትኩረት እየሰራ ያለው ውድድሮችን በብዛት እና ደረጃውን በጠበቀ ሁኔታ በብዛት ለማካሄድ መሆኑን ጠቅሶ ይህ ሁኔታ ለስፖርቱ እድገት የሚያግዙ የመንግስትን ድጋፎችን ለማግኘት እንደሚያስችል ስለታመነበት እንደሆነ ያስረዳል፡፡ ለሞተር ብስክሌት ውድድሩ ከጅቡቲ ተወዳዳሪዎችን  የጋበዝነው ካለን መተዋወቅ ተነስተን ነው የሚለው  ፍላቭዮ በበኩሉ ወደፊት ከኬንያ እና ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ተወዳዳሪዎችን በተለያዩ ግንኙነቶች ተጠቅሞ በመጋበዝ ውድድሩን በተሻለ ለማድመቅ ጥረት እናደረጋለን ብሏል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸውን ውድድሮች ስናዘጋጅ ለውድድሩ የሚቀርበውን ሽልማት ማሳደግ ያስፈልጋል ያለው ፍላቭዮ ቦናዮ በአውሮፓ፤ በአፍሪካ እና በደቡብ አሜሪካ እንደሚካሄዱ ውድድሮች በኢትዮጵያ ውስጥ የሞተር ስፖርት ውድድሮችን የማዘጋጀት አቅም መኖሩን በእርግጠኛነት እናገራለሁ ሲል ተናግሯል፡፡

በየቦታው የተቆፋፈረው የከተማዋ
መንገድ ትራንስፖርት አሳጥቶ መከራችንን ቢያበላንም “ግድ የለም ሊነጋጋ ሲል ይጨልማል” ብለን በተስፋ ዘለልነው፡፡ ግን በደህናውም መንገድ ጭምር ታክሲ መጥፋቱን ምን እንበለው? ጉዳዩ መንግሥትን ሊያሳስበው አይገባም? ስንል እንጠይቃለን፡፡

ሀገር ስንል ከተማ ገጠሩን ነውና ያንዱ ጉድለት የሌላውም ጉድለት፣ ያንዱ ሙላት የሌላውም ሙላት ነው፡፡ አዲስ አበባ የሀገራችን መዲና፣ የበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት መናኸሪያ፣ አልፎም የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ ናት፡፡ ይሁን እንጂ ለኛ ለነዋሪዎችዋ ግን የመከራና የምሬት ህይወት መግፊያ ከሆነች ውሎ አድሯል፡፡ እንደ አሮጌ ንስር፣ መንቁርዋን ስትሰብር ጥፍሯን ስትነቅል መታደስዋ ነው ብለን በትእግስት ብናያትም፣ ጣጣዋ መብዛቱ ብዙ እያስመረረን ነው፡፡ ይህንን ምሬት መስማት የፈለገ ሰው በቀላሉ ጧት ጧት የታክሲ ወረፋን ቢመለከት ይበቃዋል፡፡
በየቦታው የተቆፋፈረው የከተማዋ መንገድ ትራንስፖርት አሳጥቶ መከራችንን ቢያበላንም “ግድ የለም ሊነጋጋ ሲል ይጨልማል” ብለን በተስፋ ዘለልነው፡፡ ግን በደህናውም መንገድ ጭምር ታክሲ መጥፋቱን ምን እንበለው? ጉዳዩ መንግሥትን ሊያሳስበው አይገባም? ስንል እንጠይቃለን። ወይስ መንግሥት ህዝቡን የሚፈልገው ግብር እንዲከፍልለት ብቻ ነው? ህግ አክብሮ ግብር የከፈለ ሰው፣ የትራንስፖርትና ሌሎች አገልግሎቶችን ከመንግሥት መጠየቅ አይችልም ወይ?... እንደ ወጉማ ቢሆን መንግሥት የህዝብ ተቆርቋሪ ነኝ ስለሚል፣ የህዝቡ ችግር የራሱ ችግር መሆን ነበረበት፡፡ መሬት ላይ ያለው እውነታ ግን እንደዚያ አይመስልም፡፡ የኛ መንግሥት እኮ አንዳንዴ ግራ የሚያጋባ ነው፡፡ መሪዎቹ ከላይ እስከታች “ለህዝቡ ኑሮ መሻሻል---” ምናምን ሲሉ እውነት ነው ብለን አፋችንን ከፍተን፣ ጆሮአችንን አቁመን እንሰማቸዋለን፡፡ ግን ህዝብ ማለት እኛ እኮ ነን! ወይስ ሌላ በምናባቸው የፈጠሩት ህዝብ አለ? ከሁሉም የሚገርመኝ አዲስ አበባ እንባዋን በአራት ማዕዘን ስትረጭ መሪዎቿ “ልማት … ልማት” እያሉ ከበሮ መደለቃቸው ነው፡፡ ልማቱ እንደሚሉት ለእኛ ከሆነ ለምንድነው አንዳንዴ እንኳን ቀልባቸውን ሰብስበው ምሬታችንን የማይሰሙን?
 “ኢህአዴግ-መልዐክ ነው!” እያለ ይዘምርልኝ የነበረ ወዳጄ፤ ሰሞኑን እንባ ቀረሽ ምሬቱን በረዥም ስልክ አወጋኝ - ግራ የሚያጋባ ጊዜ ነው እያለ፡፡ በአንድ ክፍለ ከተማ ትላልቅ ስራዎችን ለመስራት አቅዶ ቢነሳም በአግባቡ የሚያስተናግደው እንዳጣ ተማሮ ነገረኝ፡፡ ነገሩ እውነት ይሁን ለመንግሥታችን እራርቶ ባላውቅም “ሁሉም ክፍለ ከተማ ግን እንደዚያ አይደለም” ሲል በጥቅሉ ከመውቀስ ተቆጠበ-ይሄው ወዳጄ፡፡ ይገርማል! ታዲያ ኢህአዴግ ለዚህ አይነቱ የምር ወዳጅ (ዘማሪ) እንኳን ካልሆነ ለማን ይሆናል? አልኩ - በልቤ፡፡
መቼም ኢህአዴግ በሙሉ ሙሰኛ ነው ማለት በጅምላ ማጠቃለል ይሆናል .. ጨዋዎችም እኮ አሉ፡፡ አንዳንዶች እንደ ጅል ቢቆጥሯቸውም ታማኝ ለመሆን የሚሞክሩ፣ አቅማቸው የቻለውን ያህል የሚሰሩ ሞልተዋል፡፡ እስቲ እነዚህንና ሌሎች ሀሳቦችን ጎላ ፈካ አድርጎ ያሳየን ዘንድ በአዲስ አበባና በክልሎች  የታዘብኩ ያስተዋልኳቸውን ላስቃኛችሁ።
ሰሞኑን ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ብቅ ብዬ ነበር፡፡ የዛሬ ዓመት ገደማ እዚያው ሆስፒታል ገብቼ አልትራሳውንድ ክፍል ስለገጠሙኝ ቅን ነርሶች አድንቄላችሁ ነበር፡፡ ሰሞኑን ስሄድ ግን “ጥቁር አንበሳ ሪፈራል ሆስፒታል” የሚለው ስያሜው ተቀይሮ “ጥቁር አበሳ ሆስፒታል” መባሉን ሰማሁ፡፡ እዚህ ሆስፒታል በሀገሪቱ ያሉ የተለያዩ ሆስፒታሎች የላኳቸው በርካታ ታካሚዎች ይመጣሉ፡፡ ይሁን እንጂ አብዛኞቹ ህክምናዎች እንደሌሉ ታዝቤአለሁ። ለምሳሌ እኔ ራሴ ከሰማኋቸው ውስጥ ሲቲ ስካን (MRI) ፣የደም ምርመራ (HCT) ፣ የእርግዝና ሽንት ምርመራ (HCG) ፣ የማህፀን ምርመራ (HSG)፣ የወንድ ዘር ምርመራ (Seminal analysis) የሉም። አልትራሳውንድ ደግሞ አንዱ ተረኛ አለ ሲል፣ ሌላኛው የለም ይላል፡፡ ለዚህ በቂ መረጃ አለኝ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፣ ህመምተኞችን በወጉ ማስተናገድ መቅረቱንም ታዝቤአለሁ፡፡ ማመናጨቅ እየበዛ ነው።
ባሳለፍነው ሳምንት ረቡዕ ከኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ባለቤቱ በገጠማት የፅንስ ማቋረጥ ደም እየፈሰሳት ብትቸገር፣ እንዲረዱለት ብሎ ወደዚሁ ሆስፒታል ቢያመጣትም ተቀብሎ የሚረዳው ሰው አላገኘም፡፡ ማህፀኗ ውስጥ የቀረ ነገር ካለ እንዲጠረግላት ቢማፀን ማን ይስማው? እናም “ለምን ሆስፒታሉን አትዘጉትም?” እያለ በንዴት በመጮህ ሃኪሞቹን ዘልፏቸው ሄደ፡፡ ምን ያድርግ? ቃለ-አባይ ሆነውበውት እኮ ነው፡፡ ሆኖም እነሱ ግን ነገሬም አላሉት፡፡ “አንዲትም እናት በወሊድ አትሙት” የሚለው መፈክር ነጋ ጠባ ቢያደነቁረንም ሀኪሞቻችን ግን መፈክሩን ለመተግበር ዝግጁ አይመስሉም፡፡ ሀኪሞችን ስል ግን ለወገኖቻቸው እስከ ሕይወት መስዋዕትነት የከፈሉና የሚከፍሉ እንዳሉ ዘንግቼው አይደለም፡፡ የይርጋለሙ ሀኪም ዶክተር ይገረሙ የሞተው፣ በማከም ላይ ሳለ በደም በተጋባበት በሽታ ነው፡፡ በቡታጅራ ሆስፒታል “የእናቶች እናት” የሚል ስያሜ የተሰጠው ዶክተር ጌትነት፣ ለህመምተኞች ሲል በህክምና ሥራ  ላይ ሳለ እስከ መውደቅ የደረሰ ባለሙያ ነው፡፡ ሌሎችም ወገናቸውን ለመርዳት በየገጠሩ እስከህይወት መስዋዕትነት ድረስ የሚከፍሉ ሀኪሞች እንዳሉ አውቃለሁ፤ ለነርሱ ያለኝ ክብርም ታላቅ ነው፡፡ ከሁሉ በላይ ህሊናቸው የሚሰጣቸው ክብርም የላቀ ነው፡፡ ጥቁር አንበሳ ግን “ጥቁር አበሳ” ሲሆን ለህዝብ ቆሜያለሁ የሚለው መንግሥት ምን እየሰራ ይሆን? ካድሬዎቹስ የማንን ጎፈሬ ያበጥራሉ?
እዚሁ አዲስ አበባ ውስጥ ታካሚዎችን በፍቅርና በርህራሄ የሚያገለግሉ ባለሙያዎች በአማኑኤል ሆስፒታል ውስጥ አይቻለሁ፡፡ ያውም የአእምሮ ህመምተኞችን! መንግሥታችን ክፉ አመሉ ሲሞገስና ሲደነቅ እንጂ ጉድለቱን ሲያሳዩት አለመውደዱ ነው፡፡ ለርሱ ወዳጆቹ ሀገር ሲቃጠል “ሰላም ነው!” የሚሉት አስመሳዮች ናቸው፡፡ በ1997 ምርጫ የዚህ ዓይነቶቹ ሀሰተኛ ካድሬዎች ገደል የከተቱት ኢህአዴግ ፤ዛሬም ከጭብጨባ ሌላ አታሰሙኝ እንዳለ ነው፡፡ ግን ሰምቶ ከስህተቱ ቢታረምና ቢቃና ለእኛም ሆነ ለራሱ ምንኛ ጥሩ ነበር! በተለይ ከልባቸው የሚሰሩ ሰዎች ተገቢውን ቦታ ቢያገኙ አገር እንደምትቀና ቢገነዘብ እንዴት ሸገና ነበር?
ወደ ክልል ወጥቼ ያየኋቸውን ጥቂት በጎ ነገሮች ደግሞ ልመስክር፡፡ ባለፈው ሳምንት ጉራጌ ዞን ምስቃን ወረዳ ገጠሩን ሳይቀር ለስራ ጉዳይ ዘልቄበት ነበር፡፡ ማረቆ ወረዳንም በከፊል አይቻለሁ፡፡ ታዲያ ደስ ያሉኝ ነገሮች ነበሩ፡፡ አንዱ ቀበሌ (ኩም ቀርጠፋ እሚባል ቦታ) ሳለሁ፤ ኩላሊቴን እንዳያመኝ በሚል መፀዳጃ ቤት አስፈልጎኝ አንዱን ስጠይቀው፤ አጥር ስር መሽናት እንደሚቻል ነገረኝ። አልተመቸኝም፡፡ እና ድንገት አይኔን ወደ አንድ አቅጣጫ ስሰድ በአራት ማዕዘን የተሰራች ጎጆ ቢጤ አየሁና ልጁን ጠየቅሁት፤ ለካስ መፀዳጃ ቤት ተቆፍሯል፡፡ ራሴ መጠቀሜ ብቻ ሳይሆን ህዝቡ ለዚያ አይነት አመለካከት መብቃቱ አስደሰተኝ፡፡ ውዬ ሳድር መስቃን ወረዳም ተመሳሳይ ሁኔታ እንዳለ አየሁ፡፡ እንደዚሁ ሶዶ ወረዳ ገጠር ውስጥ ወጣቶች ተደራጅተው የሰሩትን መዝናኛ፣ ሻወር ቤት ወዘተ ስመለከት ተደመምኩ፡፡ የቡታጅራ ከተማ የመንገድና የቱቦዎች ፅዳትም እንደዚሁ የሚመሰገን ነው። የህክምና ተቋማት ባለሙያዎችም ህዝቡን እንደማያጉላሉ ታዝቤአለሁ። ቢያጉላሉትም አሰራሩ ተጠያቂነት ስላለው የተሻለ አገልግሎት ይሰጣልና ሹመኞች ወደ ኋላ እንዳይመለሱ እመኛለሁ፡፡ ወገንን በቅንነት ለማገልገል መብቃት ህሊና ላለው ሁሉ ትልቅ እድልና ክብር ነው፡፡
ሌላው ለአዲስ አበባ መኪና አሽከርካሪዎች ትምህርት የሚሆነው የሻሸመኔ ከተማ አሽከርካሪዎች ስርአትና ዲሲፕሊን ነው፡፡ በሻሸመኔ ከተማ ዜብራ ባለበት መንገድ ላይ የሚያቋርጡ ከሆኑ፣ የትኛውም ተሽከርካሪ ይቆምልዎታል፡፡ እዚያው ከተማ ሁለተኛውና የባሌ ጎባ መስመር ላይ ያለውን መናኸሪያ ስርአትም ተደንቄበታለሁ። ስነ-ስርአት አስከባሪዎች አይሳደቡም አያመናጭቁም፣ ይልቁኑ በአክብሮት ያስተናግዳሉ፡፡ ምናልባት ከቡታጅራ ከተማ፣ ሆሳዕና ወላይታ በሚደረጉ ጉዞዎች ላይ መስተካከል ያለበት የመስተንግዶ ችግር አይቻለሁ።  ስለዚህ እባክህ መንግሥት ሆይ፤ ካድሬና ሰልፍ ከማብዛት ህዝብን በአግባቡ ማገልገልና ማክበር ይሻላል  እላለሁ፡፡ ካድሬዎች የሚደልቁትን ከበሮ ተወውና በዙሪያህ ያሉ እውነቶችን ለማየት ዓይንህን ግለጥ፡፡


         የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዛሬ 68 ዓመታት በፊት ሥራ የጀመረው አሜሪካውያን አውሮፕላን አብራሪዎችን በመያዝ ነበር፡፡ ከአስራ አንድ ዓመታት በኋላ በ1949 ዓ.ም የአቪየሽን አካዳሚ ከፍቶ የራሱን አብራሪዎችና የበረራ አስተናጋጆች እንዲሁም ቴክኒሻኖችን ማሰልጠን ጀመረ፡፡
ከጥቂት ዓመታት በፊት በኢትዮጵያ አየር መንገድ የአቪዬሽን አካዳሚ በአብራሪነት ለመሰልጠን የሚፈልጉ አመልካቾች በጠቅላላ እውቀት፣ በቋንቋ፣ በሂሳብና በፊዚክስ የትምህርት ዘርፎች ላይ ያተኮረ የመግቢያ ፈተና ይወስዱ ነበር። ቀጣዩ የቃል ፈተና ሲሆን ከዚያም የጤና ምርመራ ማድረግ ይከተላል፡፡ አመልካቾች እነዚህን ሁሉ በብቃት ካለፉ በኋላ ነው የአቪዬሽን አካዳሚው የበረራ ሰልጣኝ የሚሆኑት፡፡ አካዳሚው በተከፈተ የመጀመርያዎቹ ዓመታት በአብራሪነት ለመሰልጠን እስከ 1ሺ የሚደርሱ አመልካቾች ይመዘገቡ የነበረ ቢሆንም ተቀባይነት አግኝተው የሚሰለጥኑት ግን ከ20 አይበልጡም ነበር፡፡
በአቪዬሽን አካዳሚው አንድ አብራሪን አሰልጥኖ ለማውጣት ከ1 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚፈጅ የጠቆሙት ምንጮች፤ አብራሪው ይህንን ወጪ ለመሸፈን ተመርቆ ከወጣ በኋላ አየር መንገዱን ለ9 ዓመት የማገልገል ግዴታ እንዳለበት ይናገራሉ፡፡ በቀድሞው የአቪዬሽን አካዳሚው አሰራር፤ የአብራሪነት ሙሉ ስልጠናን ለማጠናቀቅ 2 ዓመት የሚፈጅ ሲሆን በዚሁ ጊዜ ውስጥ ሰልጣኙ ከአካዳሚክ ትምህርት ባሻገር፣ እስከ 200 ሰዓት የተግባር የበረራ ስልጠና ይሰጠዋል፡፡ ተጨማሪ የ50 ሰዓት በረራም በ‹‹ሲሙሌተር›› ይማራል። ሲሙሌተር፤ከመሬት የማይነሳ፣ በአየር ላይ የማይበር፣ ኮምፒውተራይዝድ የሆነና የአውሮፕላን በረራን ለመለማመድ የሚያስችል የማሰልጠኛ ማሽን ነው፡፡  አካዳሚው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አሰራሩን የቀየረ ሲሆን የአብራሪነት ሥልጠናው እንደቀድሞው ሁለት ዓመት ሳይሆን በ1 ዓመት ከ2 ወር ይጠናቀቃል፡፡
አብራሪዎች ስልጠናውን እንዳጠናቀቁ በቀጥታ ወደ አውሮፕላን በረራ አይገቡም፡፡ ልምድ ያላቸው አብራሪዎች በሚያበሩበት አውሮፕላን ውስጥ ሶስተኛ ሰው ሆነው “ታዛቢ” ወንበር ላይ በመቀመጥ ልምድ ይቀስማሉ፡፡ ሂደቱ በዚህ ብቻ ግን አያበቃም፡፡  በሲሙሌተር ላይ የማብረር ችሎታቸውን ይፈተናሉ። ይህን ፈተና ያለፉ እጩዎች፣ ረዳት አብራሪ በመሆን ከዋናው አብራሪ ጋር መስራት ይጀምራሉ፡፡ ይሄም እስከ አምስት ወራት ድረስ ሊፈጅባቸው ይችላል፡፡
ከትንሽ አውሮፕላን ወደ ትልቅ ለመሸጋገር ሥልጠናና ፈተና ይኖራል፡፡ የአብራሪነት ፈቃድ ለማደስም ሁሉም አብራሪዎች ፈተና ይጠብቃቸዋል፡፡ ይሄ ሁሉ የሚሆነው በሲሙሌተር ሲሆን  ሲሙሌተሩ ደግሞ “አንድ ለእናቱ” ነው፡፡ በዚህም የተነሳ ከዓመት ዓመት በሥራ እንደተጠመደ ይዘልቃል፡፡ ከውጭ አገር የሚመጡ ዋና አብራሪዎች ከማንኛውም የበረራ ምደባ በፊት ፈተና የሚወስዱት በዚሁ ሲሙሌተር ሲሆን ምሩቅ አብራሪዎች ይህን ወረፋ በትእግስት ጠብቀው ልምምዳቸውን ማድረግ ግድ ይሆንባቸዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአሁኑ ሰዓት በሚከተለው መመሪያ መሰረት፤ የበረራ ፈቃድ ለማደስ ዋና አብራሪ በየ 6 ወሩ፤ ረዳት አብራሪ ደግሞ በየዓመቱ የበረራ ብቃታቸውን በሲሙሌተሩ እየተፈተኑ ማለፍ ይጠበቅባቸዋል። በዋና አብራሪውና በረዳቱ መካከል ያለው ዋና ልዩነት የበረራ ልምድ ሲሆን ልምዱ የሚለካውም በበረራ ሰዓት ብዛት ነው፡፡ ቦይንግ 737 ለማብረር የሚመደቡ ዋና አብራሪዎች፤ እስከ 13ሺ ሰዓታት ያበረሩ እንዲሆኑ የሚጠበቅ ሲሆን በዚህ አውሮፕላን ውስጥ ከረዳት አብራሪነት ወደ ዋና አብራሪነት ለመሸጋገር ከፈጠነ እስከ 8 ዓመት፣ ከዘገየ ደግሞ 10 ዓመት ይወስዳል፡፡
ረዳት አብራሪ ወደ ዋና አብራሪነት የሚሸጋገርበት ሂደት ግልፅ አይደለም የሚሉ ረዳት አብራሪዎች፤ ወደ ዋና አብራሪነት ደረጃ የሚያድጉት በአንጋፋ ዋና አብራሪዎች ግምገማ እንደሆነ ጠቅሰው ብዙ ጊዜ ዋና አብራሪዎች ብቃታቸውን የሚፈትኑት በግል ባህርያቸው  ላይ ተመስርተው ነው ሲሉ ቅሬታ ያቀርባሉ፡፡
አብዛኞቹ ኢትዮጵያውያን ረዳት አብራሪዎች አብረዋቸው የሚሰሩት ዋና አብራሪዎች የውጭ ዜጐች ቢሆኑ ይመርጣሉ፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ የሚበዙት ኢትዮጵያዊያን ዋና አብራሪዎች በረዳት አብራሪዎቹ ላይ ጫና እና ጭቅጭቅ ስለሚያበዙ እንደሆነ ያነጋገርናቸው የበረራ ባለሙያዎች ገልፀዋል፡፡ ብዙዎቹ ዋና አብራሪዎች እስከ 60 ዓመት ዕድሜያቸው የሚበሩ ሲሆን እንዳላቸው ልምድና የማብረር ብቃት  ከጡረታ በኋላ ለተጨማሪ 5 ዓመታት በማብረር  እስከ 65 ዓመታቸው ድረስ አየር መንገዱን ያገለግላሉ፡፡
አየር መንገዱ ባለፉት 5 ዓመታት በርካታ አውሮፕላኖችን የገዛ ሲሆን የበረራ መዳረሻዎቹ መጨመራቸውም ይታወቃል፡፡ ይሄን ተከትሎም የውጭ አገር ዋና አብራሪዎች በብዛት ተቀጥረዋል። 75 በመቶ ያህሉ የአየር መንገዱ አብራሪዎች የውጭ ዜጎች እንደሆኑ የድርጅቱ መረጃ ይጠቁማል። እነዚህ አብራሪዎች በበረራ ሰዓት ልምዳቸው ከኢትዮጵያውያኑ በእጥፍ የሚልቁ ናቸው፡፡
አብራሪዎቹ የሚከፈላቸው ደመወዝ በአለም አቀፍ የደመወዝ መስፈርት መሰረት በመሆኑ ከኢትዮጵያዊያኑ ጋር የሚወዳደር አይደለም፡፡ በዚያ ላይ የውጭዎቹ አብራሪዎች ያለእረፍት ለበርካታ ሰዓታት ስለሚያበሩ ዳጐስ ያለ ክፍያ ያገኛሉ፡፡ ሆኖም  አብራሪዎቹ ከሁለትና ሶስት ዓመታት በላይ በአየር መንገዱ አይቆዩም፡፡ ያለ እረፍት በመስራት የሚያገኙት ክፍያ ጠቀም ያለ ስለሆነ በጥቂት ዓመታት ውስጥ የሰሩበትን ይዘው ወደ አገራቸው እንደሚመለሱ ምንጮቻችን ገልፀውልናል፡፡ በዚህም የተነሳ አየር መንገዱ በየጊዜው አዳዲስ የውጭ አብራሪዎችን ለመቅጠር ይገደዳል። በዚያ ላይ ኢትዮጵያዊያኑ አብራሪዎችም አየር መንገዱን እየለቀቁ  በሌሎች አገራት አየር መንገዶች እንደሚቀጠሩ  ምንጮች ገልፀዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን አብራሪዎች በደሞዝ ማነስ፣ ከውጪ አገር አብራሪዎች ጋር እኩል ባለመታየት እንዲሁም  በየሰበቡ በሚጣልባቸው ቅጣትና የስራ ደህንነት ማጣታት በእጅጉ እንደተማረሩ  ይገልፃሉ፡፡ ማናቸውም አብራሪዎች የሚከፈላቸው ደሞዝ እንደበረራ ሰዓታቸው፣ እንደሚያበሩት አውሮፕላንና እንደየሚሄዱበት አገር ምንዛሪ የሚለያይ ቢሆንም ኢትዮጵያዊያኖቹ አብራሪዎች በረዳት አብራሪነት ስራ ሲጀምሩ 7ሺህ ብር  ወርሃዊ ደሞዝ የሚከፈላቸው ሲሆን የበረራ ሰዓታቸው እየጨመረ በሄደ ቁጥር ክፍያቸውም እንደሚያድግ ምንጮች ይገልፃሉ፡፡ እንደ ቦይንግ 737 እና 767 ያሉ አውሮፕላን አብራሪዎች ደግሞ እስከ 30 ሺህ ብር የወር ደመወዝ ይከፈላቸዋል፡፡
አየር መንገዱ የአቪዬሽን አካዳሚውን ከከፈተ ጊዜ ጀምሮ ባለፉት 57 ዓመታት ያሰለጠናቸው ኢትዮጵያውያን አብራሪዎች ብዛት 975 ሲሆኑ 3079 ቴክኒሺያኖችንና ከ4 ሺህ በላይ የበረራ አስተናጋጆችን አሰልጥኖ ወደ ስራ ማሰማራቱን ከአየር መንገዱ የተገኙ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት አየር መንገዱ 800 ያህል አብራሪዎች ያሉት ሲሆን ከእነዚህ መካከል 75 በመቶ የሚሆኑት ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የተቀጠሩ የወጭ አገር ዜጎች መሆናቸውንም እነዚህ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በ51 አገራት 87 መዳረሻዎች ያሉትና 144 በረራዎችን በየቀኑ በማድረግ በዓመት 4.5 ሚሊዮን ተጓዦችን የሚያስተናግደው አየር መንገዱ፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ እያሰለጠነ ወደ ስራ የሚያሰማራቸው የበረራ አስተናጋጆች ቁጥር እየጨመረ ቢሄድም በአየር መንገዱ ውስጥ በስራ ላይ ያሉ የበረራ አስተናጋጆች ቁጥር ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተመናመነ መምጣቱን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ለበረራ አስተናጋጅነት ሰልጥነው ከሚቀጠሩት መካከል ቀላል የማይባሉት በደሞዝ ማነስ፣ የስራ እድገት ባለማግኘት፣በተለያዩ ጥቅማጥቅሞች አለመሟላትና በሰራተኛ አያያዝ ችግር ሳቢያ ስራቸውን ለመልቀቅ ይገደዳሉ፡፡ ይሁን እንጂ አንዲት በበረራ አስተናጋጅነት ተቀጥራ የምትሰራ ሆስተስ፤ ያለባትን የአየር መንገዱን እዳ ሳትከፍል መልቀቅም ሆነ ወደ ሌሎች አየር መንገዶች መዛወር አትችልም፡፡ በዚህም የተነሳ ለስራ በየሄዱባቸው አገራት የሚቀሩ እንዳሉ የአየር መንገዱ ሠራተኞች ነግረውናል፡፡
አየር መንገዱ ለበረራ አስተናጋጅነት ስልጠና በሚሰጥበት ወቅት ከንድፈ ሃሳብና ከተግባር ትምህርቱ በተጨማሪ የስራ ላይ ስልጠና (on job training) ሲሰጥ የኪስ ገንዘብ ስለሚከፈል አንዲት የበረራ አስተናጋጅ ሰልጣኝ የ300ሺህ ብር ባለዕዳ ሆና ነው የምትመረቀው፡፡ ለዚህም ነው እስከ 6 ዓመት ድረስ የማገልገል ግዴታ ያለባት። ማንኛዋም የበረራ አስተናጋጅ ስልጠናዋን ጨርሳ ከተመረቀችበት ጊዜ ጀምሮ እስከ 5 ዓመት ድረስ ነፃ የአውሮፕላን ትኬት አይፈቀድላትም፡፡ ይህም የሚደረገው ዕዳዋን ሳትከፍል ወደ ውጪ አገር እንዳትሄድ ታስቦ ነው ይላሉ-ምንጮች፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ በበረራ አስተናጋጅነት ተቀጥረው የሚሰሩ የተለያዩ አገራት (በተለይም ፈረንሳይኛ ተናጋሪ የአፍሪካ አገራት ዜጎች) አሉ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ቻይናውያን በበረራ አስተናጋጅነት ተቀጥረው የነበረ ቢሆንም ዓመት ያህል እንኳን ሳይሰሩ ለቀው እንደሄዱ ታውቋል፡፡
በበረራ አስተናጋጅነት ሙያ ውስጥ ረዘም ላለ ጊዜ የቆዩት ሆስተሶች (ሲኒየር ሆስተሶች) የተሻለ ደመወዝና ጥቅማጥቅም ቢከፈላቸውም አብዛኞቹ በስራቸው ደስተኞች እንዳልሆኑ ይነገራል፡፡ አየር መንገዱ ከአምስት ዓመት በፊት ለጀማሪ ሆስተስ ይከፍል የነበረውን 1200 ብር ወርሃዊ ደሞዝ አሁን ወደ 2500 ብር ቢያሳድግም አስተናጋጆቹ በበዛ የሥራ ጫና፣ በሥራ ደህንነት ማጣትና በየሰበቡ በሚጣልባቸው ቅጣት መማረራቸውን ይገልፃሉ። የስድስት ዓመት አገልግሎታቸውን  የጨረሱ አስተናጋጆችን የኢምሬትስ እና የሳውዲ አየር መንገዶች እስከ 1 ሺ ዶላር (20ሺ ብር ገደማ) ወርሃዊ ደሞዝ በመክፈል እየቀጠሯቸው እንደሆነ ለማወቅ ችለናል፡፡ ሆስተሶቹ ከሰራተኛ አያያዝ ጋር በተገናኘ የሚገጥሟቸውን ችግሮችና ጠንከር ያሉ የመብት ጥያቄዎችን ካነሱ የደመወዝ፣ የጥቅማጥቅም ቅጣቶችና የዲሲፕሊን እርምጃዎች እንደሚወሰድባቸው ይገልጻሉ፡፡ የስራ ደህንነት ማጣትም ዋንኛው ችግራችን ነው ይላሉ፡፡
ስድስት ሺህ ቋሚ ሰራተኞች እና አንድ ሺህ ጊዜያዊ ሰራተኞ እንዳሉት የሚነገረው አየር መንገዱ፤ ከሰራተኞቹ ውስጥ 600 የሚሆኑት በአለም አቀፍ ደመወዝ መስፈርት ክፍያ የሚፈፀምላቸው የውጭ አገር ዜጎች ናቸው፡፡ አየር መንገዱ እ.ኤ.አ ከ2009-2011 ዓ.ም ድረስ ከፍተኛ ትርፍ ያገኘ ሲሆን ከ1.2 ቢሊዮን ብር በላይ አትርፏል፡፡ ይሁን እንጂ እ.ኤ.አ በ2012 ዓ.ም ትርፉ ወደ 734 ሚሊዮን ብር ወርዶ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
አየር መንገዱ በአሁኑ ወቅት 62 አውሮፕላኖች ያሉት ሲሆን 33 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ለመግዛት ውል ፈፅሟል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ስምንቱ 787 ድሪም ላይነር ሲሆኑ አስራ አራቱ ደግሞ ኤርባሶች ናቸው፡፡
የሰራተኞቹን በተለይም የአውሮፕላን አብራሪዎችና የበረራ አስተናጋጆቹን ቅሬታና ወደ ተለያዩ አገራት የሚፈልሱ ባለሙያዎችን በተመለከተ የአየር መንገዱን ሃላፊዎችን አግኝተን ለማነጋገር ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ  አልተሳካም፡፡

የኦህዴድ ሊቀመንበርና የኦሮምያ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ አለማየሁ አቶምሳ ባደረባቸው ህመም በህክምና ሲረዱ ከቆዩ በኋላ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ህይወታቸው እንዳለፈ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የዘገበ ሲሆን የቀብር ስነስርዓታቸው በዛሬው እለት በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ቤተክርስትያን ይፈፀማል ተብሏል፡፡
በጳጉሜ 2002 ዓ.ም በአዳማ ከተማ በተደረገው የኦሕዴድ ስድስተኛ ድርጀታዊ ጉባዔ ላይ አራተኛው የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት በመሆን የተመረጡት አቶ አለማየሁ አቶምሳ፤አብዛኛውን የሹመታቸውን ጊዜ በሕመም ቢያሳልፉም ለበርካታ ወራት ለህክምና በሚቆዩበት ሆስፒታል ሆነው ስራቸውን በኢንተርኔት ያከናውኑ እንደነበር ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡  
አቶ አለማየሁ አቶምሳ በፕሬዚዳንትነት ተመርጠው አንድ ዓመት ሳይሞላቸው ባጋጠማቸው ሕመም ምክንያት ከሃላፊነት ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርበው እንደነበር ያስታወሱት ምንጮቻችን፤ጥያቄያቸው ተቀባይነት ሳያገኝ በመቅረቱ ላለፉት ሶስት ዓመታት ህክምናቸውንና ሃላፊነታቸውን ጎን ለጎን ሲያካሂዱ እንደቆዩ ጠቁመዋል፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊም ከህመማቸው ቀደም ብሎ ከሃላፊነታቸው ለመልቀቅ ጠይቀው ፓርቲያቸው እንዳልተቀበላቸው በህይወት ሳሉ መናገራቸው  ይታወሳል፡፡
  ከሁለት ሳምንት በፊት የኦህዴድ ማዕከላዊ ኮሚቴ በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ላይ የተገኙት አቶ አለማየሁ፤ ከወትሮው በተለየ የህመምና የመጎሳቆል ስሜት ይታይባቸው የነበረ ቢሆንም ስብሰባውን በአግባቡ ሲመሩና ግምገማ ሲያካሂዱ ነበር ብለዋል - ምንጮች፡፡  
አቶ አለማየሁ በቅርቡ ለኦሕዴድ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ለሁለተኛ ጊዜ ያቀረቡት የሥራ መልቀቂያ ማመልከቻ ተቀባይነት ማግኘቱ የሚታወቅ ሲሆን ሃላፊነታቸውን አስረክበው ብዙም ሳይቆዩ ባደረባቸው ህመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ45 አመታቸው ከትላንት በስቲያ ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ኢቴቪ ዘግቧል፡፡ አንዳንድ ወገኖች ግን ኢቴቪ የአቶ አለማየሁን ዜና እረፍት ከማወጁ  ሶስት ቀን ቀደም ብሎ ህልፈታቸውን እንደሰሙ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ የአፄ ምኒልክ ህልፈት ከህዝቡ ተደብቆ የቆየው ብጥብጥ እንዳይነሳ ተፈርቶ እንደነበር ታሪክ ጠቅሰው ያስታወሱት አስተያየት ሰጪዎቹ፤በአሁኑ ዘመን የመንግስት ሹማምንት ህመምና የሞቱበት ቀን ለምን እንደሚደበቅ አይገባንም ይላሉ፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ትክክለኛ የህልፈት ቀን አለመነገሩን በማስታወስም ጉዳዩ  ለመጪው ትውልድ የሚተላለፍ በመሆኑ የታሪክ መዛባት እንዳይፈጠር እርምትና ጥንቃቄ መውሰድ እንደሚገባ አስተያየት ሰጪዎቹ አሳስበዋል፡፡
የኦሮምያ ክልል ርእሰ መስተዳድር ከመሆናቸው በፊት በተለያዩ የሃላፊነት ቦታዎች ላይ የሰሩት አቶ አለማየሁ አቶምሳ፤የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ስራ አስኪያጅና የኦሮሚያ ክልል ማስታወቂያ ቢሮ ኃላፊ ሆነው እንዳገለገሉም ይታወቃል፡፡ የመጀመርያ ድግሪያቸውን ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ በህግ ትምህርት ያገኙት አቶ አለማየሁ፤ሁለተኛ ድግሪያቸውን ከቤይጂንግ ዩኒቨርስቲ በህዝብ አስተዳደር አግኝተዋል፡፡ ህልፈታቸውን ተከትሎ ኦህዴድ ባወጣው የሃዘን መግለጫ፤ አቶ አለማየሁ ለኦሮምያ ህዝብ ነፃነትና ዲሞክራሲያዊ መብት መከበር ለ24 ዓመታት እንደታገሉ አስታውሶ፤በኦሮምያ ክልል ኪራይ ሰብሳቢነትን በፅናት እንደታገሉና ኢኮኖሚያዊ እድገት እድገት እንዲመዘገብ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን አመልክቷል፡፡ አቶ አለማየሁ አቶምሳ ባለትዳርና የ3 ልጆች አባት ሲሆኑ የቀብር ስነስርዓታቸው ዛሬ በቅድስት ስላሴ ካቴድራል ቤ/ክርስትያን እንደሚፈፀም ታውቋል፡፡

Published in ዜና

ስለማኅበራት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት ተጠየቀ
‹‹ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከል ይገባል›› - መንግሥት


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ‹‹ከዩኒቨርስቲ ተመርቀው ቤተ ክርስቲያንን እንምራ እያሉ ነው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ትውፊትና ሥርዓት አላት፤እንዲህ ማለት አይችሉም›› በማለት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት በንግግራቸው ቅር የተሰኙ የመንፈሳውያን ማኅበራት አገልጋዮች ጠየቁ፡፡
አገልጋዮቹ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ አቡነ ማትያስ ይሄን አስተያየት የሰነዘሩት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ከኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጋር በመተባበር የካቲት 21 እና 22 ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የስብከተ ወንጌል የምክክር ጉባኤ በተካሔደበት ወቅት ነው፡፡
በምክክር ጉባኤው መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ‹‹በባዮሎጂና ኬምስትሪ እንቀድስ እያሉ ነው፤›› ያሉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹ምን እያልኹ እንደኾን ይገባችኋል›› በማለት ማንን እንደሆነ የማሳየት ያህል የጠቆሙበት አስተያየት ያልተለመደና ጥቂት የማይባሉ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ያሳዘነ እንደነበር የጉባኤው  ምንጮች አመልክተዋል፡፡
በምክክር ጉባኤው ላይ ለውይይት በቀረቡ ጽሑፎች፣ እስከ ሰማንያ ሺሕ የሚገመቱ መንፈሳውያን ማኅበራት በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም በአዲስ አበባ እንደሚንቀሳቀሱ የተጠቀሰ ሲሆን  ቤተ ክርስቲያኒቱ ማህበራቱ በሕግና በሥርዐት የሚመሩበት ደንብ አውጥታ እስካልተቆጣጠረቻቸው ድረስ እየተከሠቱና ሊከሠቱ የሚችሉ ችግሮች በቀላሉ እንደማይታዩ ተመልክቷል፡፡
ቅሬታ አቅራቢዎቹ በበኩላቸው፤በማኅበር ሽፋን ለግል ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው የሚሯሯጡ፣ የሃይማኖትና የሥነ ምግባር ሕጸጽ የሚታይባቸው ማኅበራት የመኖራቸውን ያህል ጥሩ ሥነ ምግባር ያላቸው፣ ምእመናንን በማትጋት ለበለጠ ሀብተ ጸጋ የሚያበቁ ጠንካራ ማኅበራትም እንዳሉ ገልጸዋል፡፡  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በምክክር መድረክና በቤተ ክህነቱ ጉባኤያት እየታየ ያለው “ማኅበራት አላሰራ አሉን” በሚል በጅምላ የመፈረጅና የመኰነን ዝንባሌ፣ አብዛኞቹ ማኅበራት ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን እያበረከቱ ያለውንና  በቤተ ክህነቱ ቀጥተኛ አቅም ሊሸፈን የማይችለውን ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት ያላመዛዘነ ነው ብለዋል -የማህበራት አገልጋዮች፡፡
“በአሁኑ ጊዜ ማኅበራት የአባሎቻቸውንና የበጎ አድራጊ ምእመናንን የገንዘብ፣ የዕውቀትና ሞያዊ አቅም በማስተባበር የገጠር አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማት፣ አድባራትና የአብነት ት/ቤቶች በተቀናጀ መንገድ እንዲረዱ ያደርጋሉ፤ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ዕድገት የሚጠቅሙ ልዩ ልዩ ጥናቶችን ያካሒዳሉ፤ በጠረፍ የሀገሪቱ ክፍል በሚያከናውኑት የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ ምእመኑ በቋንቋው የሚገለገልበትን ኹኔታ ያመቻቻሉ፤ የቅዱሳት መካናት ተሳላሚዎችን ጉዞ በማስተባበር ሕዝቡ ቅርሱንና ባህሉን አውቆ እንዲጠብቀውና እንዲከባከበው ከማስቻላቸው ባሻገር ለሀገር ውስጥ ቱሪዝም መስፋፋትና መጠናከርም ያላቸው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡” ሲሉ የማህበራትን ጥቅም አብራርተዋል፡፡
ማኅበራቱ አብዛኞቹን ተግባራት የሚያከናውኑት በየደረጃው ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሓላፊዎች ፈቃድ እያገኙና መመሪያ እየተቀበሉ መኾኑን የሚገልጹት አገልጋዮቹ፣ በግንቦት 2004 ዓ.ም. የማኅበራትን ቁጥር ስለመቆጣጠር ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ በነበረው ጥናት መነሻነት ምልዓተ ጉባኤው ራሱን የቻለና ማኅበራቱን የሚያሠራ ሕግ እንዲዘጋጅ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሕግ ባለሞያዎች ያሉበት ደንብ አዘጋጅ ኮሚቴ ሠይሞ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ የማኅበራት አደረጃጀትና የፋይናንስ ቁጥጥር መርሕን ጠብቆ እንደሚወጣ ሲጠበቅ የቆየው ደንብ ከሚገባው በላይ መዘግየቱ ችግሩ ከቤተ ክህነቱ እንጂ ከማኅበራቱ አገልግሎትና ብዛት አለመኾኑን እንደሚያመለክት ይከራከራሉ፡፡
ፓትርያርኩ አድልዎ በሌለው መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማስተዳደር በዕለተ ሢመታቸው ቃለ መሐላ መፈጸማቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፣ በምክክር ጉባኤው ላይ በተጠቀሰው አኳኋን የመናገራቸው ግፊት የተለያየ መነሻ ሊኖረው እንደሚችል አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
የመጀመሪያው መንሥኤ፣ የሙስናንና ብልሹ አሠራርን ችግር ለመቅረፍና ለማድረቅ በቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የተሠራው የመዋቅር፣የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት ተቃዋሚዎች የጥናቱ ባለቤት ነው በማለት በሚከሡት ማኅበረ ቅዱሳን ላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ አመራር አማካይነት እንዲፈጠር የሚሹት ጫና ነው፡፡ ኹለተኛው ደግሞ በመንግሥት በኩል፣ ‹‹በኦርቶዶክስ ሃይማኖት ውስጥ አክራሪነትና ጽንፈኝነት የሚታየው ህልውናቸውና ዓላማቸው ሃይማኖታዊና በሃይማኖቱ የበላይ ጠባቂዎች ይኹንታ በተቋቋሙ የወጣት ማኅበራት አደረጃጀቶች ውስጥ በመሸጉ አካላት ነው፤ ስለዚህም ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከሉ  ይገባል፤›› የሚለው ክሥ በመሪዎቹ ላይ ያሳደረው ማኅበራቱን የመቆጣጠር ጫና ነው፡፡
የአክራሪነትንና ጽንፈኝነትን ምንነትና መፍትሔዎችን በሚተነትኑት የመንግሥት ሰነዶች፣ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጋቸዋል ከሚባሉት ኹኔታዎች ውስጥ÷ የሃይማኖት ተቋማቱ የሰው ኃይል አስተዳደርና የፋይናንስ ሥርዐት ለተከታዩ ሕዝብ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሌላቸው መኾናቸው፣ በሙስናና በአስተዳደር በደል ሳቢያ የሚፈጠር ግጭት፣ የሰው ኃይል አስተዳደር በዘመድ አዝማድና በጉቦ እየኾነ የሥራ ብቃት በሌላቸው ሰዎች የሚሠራበት፣ የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ የሚተችበትና አስተያየት የሚሰጥበት ሥርዐት አለመዳበሩ፣ ተከታዮችን አክራሪነትን የሚቋቋም በሃይማኖት ዕውቀት የማስታጠቅ ክፍተት ይገኙበታል፡፡
በመንግሥት ትንታኔ መሠረት፣አክራሪነትን የመዋጊያው ቁልፍ መሣሪያ ልማትንና ዕድገትን በማፋጠን የመልካም አስተዳደር ችግርን መቅረፍ፣ሕዝቡን በሃይማኖታዊ ዕውቀት ማስታጠቅ ነው፡፡ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጓቸዋል የተባሉት የመልካም አስተዳደርና የብልሹ አሠራር ችግሮች÷ ማኅበረ ቅዱሳን በተቃዋሚዎች አላግባብ በሚከሠሥበት የመዋቅር፣ የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ትግበራ በማፋጠን እንዲኹም ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ በርካታ ማኅበራት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ የገዳማትና የአብነት ት/ቤት ማኅበረሰብን በልማትና ተራድኦ ከመደገፍ ጀምሮ በሚያከናውኑት ሐዋርያዊ ተልእኮ ንቃት ሊወገድ እንደሚችል ቅሬታ አቅራቢዎቹ ያምናሉ፡፡ ከዚኽም አንጻር ፓትርያርኩ ንግግራቸውን መልሰው በማጤን ማኅበራት አገልግሎታቸውን አጠናክረው ለመቀጠል የሚያስችላቸው ኹኔታ እንዲያመቻቹ ጠይቀዋል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 08 March 2014 12:14

ምግብና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ

“የታሰረን ምላስ ወይን ጠጅ ይፈታዋል”

በአለም ላይ የሚፈጠሩትን ግጭቶችና ፈጠራ የታከለባቸውን ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴዎች በተመለከተ ምግብ ምን አይነት ትምህርት ሊሠጣችሁ ይችላል ተብላችሁ ብትጠየቁ ምን አይነት መልስ ትሠጣላችሁ?
ሳሎን ቤት ውስጥ ተቀምጠው የተለያዩ ግላዊ፣ ማህበረሠባዊና ሀገራዊ ጉዳዮችን እያነሱ እርስ በእርስ እየተጫወቱ ያሉትን ከተለያየ ቦታ የመጡ፣ የተለያየ ወግ፣ ባህል፣ ሀይማኖትና ዘር ያላቸውን እንግዶችዎን ቤት ያፈራውን ምግብ አዘጋጅተው ሊጋብዟቸው ሽር ጉድ የሚሉባትን ማድቤትዎን ወይም ኩሽናዎን እስኪ ለአንድአፍታ ያስቧት! መቼም መጥበብና መስፋቷ፣ ባህላዊ አሊያም ዘመናዊ የመሆኗ ነገር ከሁሉም ቀድሞና ፈጥኖ ወደ አዕምሮዎ ሊመጣልዎ እንደሚችል ምንም አያጠራጥራም፡፡ ማድቤትዎ ወይም ኩሽናዎ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ከሚቦካባቸው ቦታዎች መካከል አንዱ ይሆናል የሚል ሀሳብ ግን ወዲያውኑ እንደማይመጣልዎ በእርግጠኝነት መገመት ይቻላል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ማድቤቶች ወይም ኩሽናዎች በተለይ ደግሞ ምግብ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ የአለም ዲፕሎማሲ ሰርክ እየተጠነሰሰ ከሚጠመቅባቸው ዋነኛ ነገሮች አንዱ ሆኗል፡፡
ምግብ የሰው ልጅ በህይወት ለመቆየት ከሚተነፍሰው አየር ቀጥሎ የሚያስፈልገው መሠረታዊ ፍላጐቱ ነው ብሎ መናገር መቼም የአንባቢን ንቃተ ህሊና ዝቅ አድርጐ እንደ መገመት ተደርጐ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ለምን ቢባል? ማንኛውም የሰው ልጅ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ጠንቅቆ የሚያውቀው ጉዳይ ስለሆነ ነው፡፡
ከዚህ መሠረታዊ እውነት ባለፈ ግን ምግብ ሁሌም ቢሆን የሚቀርበው በውስጡ የአቅራቢውን ዘርና ባህል ይዞ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለሰው ልጆችና ለውጭ ግንኙነታቸው እጅግ አስፈላጊ የሆነና ጠንካራው ቅመም ወይም ግብአት ነው፡፡ ይህ መሠረታዊ ጉዳይ በሌላ አነጋገር ሲገለጽ ምግብ የተለያየ ዘርና ባህል ያላቸው ሰዎችም ሆኑ ማህበረሰቦች እርስ በርሳቸው የሚገናኙበት የግንኙነት መስመር ነው ማለት ነው፡፡
ምግብ ለውጭ ጉዳይ ፖሊሲና ፖሊሲው በተግባር ለሚገለጽበት የዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ ታሪካዊ አስፈላጊነት እድሜውን አሀዱ ብሎ መቁጠር የሚጀምረው ከጥንታውያኑ ግሪኮችና ሮማውያን ስልጣኔ ዘመን ነው፡፡ ጥንታውያኑ ግሪኮችና ሮማውያን በዘመናቸው ምግባቸውን እየተመገቡ፣ ከተለያዩ ሀገራት እንግዶች ጋር በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ድርድሮችን ያካሂዱ ነበር፡፡ የተለያዩ ግጭቶችን ለማስወገድም ሁነኛ መላ ያበጁ ነበር፡፡
እነዚሁ ጥንታውያን ግሪኮችም ሆኑ ሮማውያን “የታሰረን ወይም የተቆለፈን ምላስ ማለፊያ የወይን ጠጅ ደህና አድርጐ ይፈታዋል፡፡” የሚል ዘመን የጠገበ ምሳሌአዊ አነጋገር አላቸው፡፡ እናም ከሌላ ሀገር እንግዶች ጋር ማዕድ ቀርቦ ለመብል በተሰየሙ ጊዜ፣ ከማለፊያው የወይን ጠጅ ፈታ ባለ እጅ፣ ከፍ ባለ ልግስና እንግዶቹን በመጋበዝ፣ በሀገር ፍቅር ወኔና በአርበኝነት ስሜት የተዘጉ ልቦች እንዲለዝቡ፣ የታሰሩ ምላሶችም እንዲፈቱ በማድረግ የእንግዶቹን ሀገር ከፍተኛ ሀገራዊ ምስጢር አስዘክዝከው የአደባባይ ላይ ወግ እንዲሆን ያደርጉ ነበር፡፡
ይህን የመሠለው የጥንታዊያኑ ግሪኮችና ሮማውያን የምግብ ዲፕሎማሲ፣ ዛሬም ቢሆን ጨርሶ አልጠፋም፡፡ በያዝነው ዘመን በተለያዩ የአለማችን ሀገራት አገሮቻቸውን ወክለው የሚገኙ ኤምባሲዎች የየሀገሮቻቸውን ብሔራዊ ቀናት ወይም ሌሎች ከፍ ያለ ቦታና ግምት የሚሠጧቸውን በአላት ምክንያት በማድረግ ተገቢና በቂ ነው ያሉትን የምግብና የመጠጥ ድግስ ደግሰው ታላላቅ የመንግስት ሹማምንት፣ የፖለቲካ፣ የወታደራዊ፣ የሲቪል ማህበረሠብና የንግድ መሪዎችን እንዲሁም የሌሎች ሀገራት አምባሳደሮችን የሚጋብዙበት የዲፕሎማሲ ባህል መነሻ መሠረቱ ሌላ ነገር ሳይሆን ይሄው ነው፡፡
ዋና አላማውም የድርድር፣ የውይይት፣ የአዲስ ግንኙነት ፈጠራ፣ የመረጃ ልውውጥ፣ ስለላና የመሳሠሉትን የውጭ ግንኙነትና የዲፕሎማሲ ስራዎችን አቅም በፈቀደ መጠን ማካሄድ ነው፡፡
ይህ እድሜ የጠገበ የምግብ የውጭ ግንኙነትና የዲፕሎማሲ ስራ አሁን ባለንበት ዘመን አዲስና እንደ ጊዜው የዘመነ አቅጣጫና ይዘት እንዲኖረው ለማድረግ በልባቸውና በመንፈሳቸው የቆረጡ የአዲስ ትንሳኤ አርበኞችን አግኝቷል ተብሏል፡፡
በአለማችን ያለውን የምግብ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ጠቀሜታ አበክረን ተረድተናል ያሉ የአሜሪካ የአለም አቀፍ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲና የዲፕሎማሲ ሊቃውንት፣ ሙያውን በከፍተኛ ደጃ በማሳደግ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ የሚሠጥ አሪፍ የትምህርት ዘርፍ ለማድረግ በቅተናል ብለዋል፡፡
ዋሽንግተን ዲሲ የሚገኘው አሜሪካን ዩኒቨርሲቲም በምግብ ዲፕሎማሲ (Culinary Diplomacy) እግ በግጭት ምግቦች (Conflict Cuisines) በዲግሪ ደረጃ ትምህርት ለመስጠት ዝግጅቱን አጠናቆ ተማሪዎችን ለመቀበል ምዝገባ የሚያካሂድበትን ቀን ቆርጦ አሳውቋል፡፡
የሆኖ ሆኖ ግጭቶች ምንም እንኳ ቀጥተኛ ትርጉማቸው ረጅም ታሪካዊ ሁነቶችን ቢያስታውሱንም በመላው አለም አዲስ የምግብ ዲያስፖራ በመፍጠሩ ረገድ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት የተፈጠሩት ግጭቶች ያሳደሩት ተጽዕኖ በጣም ከፍተኛ ነው፡፡
አዲስ የተፈጠረው የምግብ ዲያስፖራም የደቡብ ምስራቅ እስያን፣ የመካከለኛው ምስራቅን የካሪቢያንን፣ የተለያዩ የመካከለኛው አሜሪካን ምግቦችና አመጋገባቸውን የአውሮፓውያንን የምግብ ባህል ትከተል ወደነበረችው አሜሪካ አስገብቷል፡፡
የምግብ ዲፕሎማሲ ነገርም የአለም አቀፍ ተጓዦችን እንቅስቃሴ ተከትሎ ማደግ ችሏል፡፡ ምግብ የተለያዩ የዲያስፖራ ማህበረሠቦች ሀገር-በቀል ባህል አንዱና ዋነኛው መገለጫ መሆኑም ለምግብ ዲፕሎማሲ እድገት የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ዛሬ በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ በሚገኙ ታላላቅ ከተሞች ውስጥ የኢትዮጵያው ተወዳጅ ምግብ ዶሮ ወጥና ሽሮ፣ የኔፕልስ የባስማቲ ሩዝ እንዲሁም የቱርክ ሺሽክባብና ሸዋርማ ተሠናድተው ከሚቀርቡባቸው የተለያዩ ምግብ ቤቶች መስኮቶች አለምን በጨረፍታም ቢሆን አሻግሮ መመልከት ይቻላል፡፡
ሴኔጋላውያን “ምርጡ ዛፍ ጭው ካለው ገደል አፋፍ ላይ ይበቅላል፡፡” ይላሉ፡፡ እነዚህ የተለያዩ የአለማችንን ህዝቦች ባህልና ወግ የሚያሳዩ ምግቦችም አብዛኛውን ጊዜ በግጭቶች የተወለዱ ናቸው፡፡ የእነዚህ ምግቦች አሰራርና የተለያዩ ግብአቶች በአውሮፓውም ሆነ በአሜሪካ ታላላቅ ከተሞች መገኘት የቻሉት የተሻለ ህይወትንና ነፃነትን ፍለጋ የትውልድ ቀያቸውን ጥለው ከተሰደዱት ስደተኞች ጋር አብረው በመሠደድ ነው፡፡ ዛሬ በመላው የአለማችን ሀገራት  በሚሊዮን የሚቆጠሩ ስደተኞች ምግብ ቤት ከፍተው የሀገራቸውን ባህላዊ ምግቦች በማቅረብ በነዋሪው ዘንድ ቀላል የማይባል እውቅና አትርፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በተለይ የአንዳንድ ሀገራት ስደተኞች ለግንኙነት ቋንቋ ብቻውን በቂ በማይሆንበት ጊዜ በከፈቱት ምግብ ቤት አማካኝነት ምግብ ምን ያህል ድንቅ የግንኙነት መሳሪያ እንደሆነ መረዳትም ማስረዳትም ችለዋል፡፡
ይህን ጉዳይ በምሳሌ ማስረዳት ምናልባት ጉዳዩን ቀለል ሊያደርግልን ይችላል፡፡ አሜሪካ ከኩባ ጋር ኦፊሴላዊ የዲፕሎማቲክ ግንኙነት የላትም፡፡ ይሁን እንጂ አንድ አሜሪካዊ የኩባን ምግብ ከሚያሚ ግዛት ውጪም ቢሆን እንደፈለገው ማግኘት ይችላል፡፡ የአሜሪካና የቬየትናም የዲፕሎማሲ ግንኙነት በድጋሚ የታደሰው በ1995 ዓ.ም ነው፡፡ በአሜሪካ የሚገኙ የቬትናም ምግብ ቤቶች ግን ከዚህ ጊዜ ቀደም ብሎ ጀምሮ ባህላዊ ምግባቸው ለአሜሪካውያን ደንበኞቻቸው ያቀርቡ ነበር፡፡
ከ1998 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል የተካሄደው አሳዛኝ ጦርነት ለሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መቋረጥ ምክንያት ሆኗል፡፡ ይሁን እንጂ በርካታ ኤርትራውያን በአውሮፓና አሜሪካ በሚገኙ ታላላቅ ከተሞች በሚገኙ የኢትዮጵያ ምግብ ቤቶች ጐራ በማለት የምግብ ናፍቆታቸውን ይወጣሉ፡፡
አንድ ተጨማሪ ምሳሌ እናቅርብ፡፡ በኮሎምቢያ የእርስ በርስ ግጭት በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ግጭቱ የኮሎምቢያ የምግብ አብሳዮች የልኡካን ቡድንን ወደ ዋሽንግተን ዲሲ አምርቶ “ምግብና ሰላም” በሚል ርዕስ ንግግር ከማድረግ አልገታውም፡፡
ምግብ እጅግ ባስቸጋሪ ወቅት ህዝቦች እርስ በርስ እንዲቀራረቡ የማድረግ ጠንካራ አቅም አለው፡፡ ይህ ግን ሁልጊዜ እውን አይሆንም፡፡ የእህል (ምግብ) ማዕቀብ በተጣለ ጊዜ ወደ ጦር መሳሪያነት ተቀይሮ ማገልገል ይችላል፡፡ አሳዛኙ የሶሪያ ሰብአዊ ቀውስ ለዚህ አንዱ አብነት ነው፡፡
በአሁኑ ወቅት አለማችን ምግብን የተመለከተ እንደ ኋላ ቀር ግብርና፣ ድርቅ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ ድህነት፣ ረሀብ የምግብ ዋስትና ማጣትና የመሳሰሉ በርካታ ችግሮች አሉባት፡፡ ይህም ሁሉ ሆኖ ግን የምግብን የውጭ ግንኙነትና የዲፕሎማሲ ሀይል በመጠቀም፣ ህዝቦች የጋራ የሆነ ጉዳዮችን እንዲያፈላልጉ ማበረታታት ይቻላል፡፡ ፍራንዝ ካፍካ በአንድ ወቅት “ምግብ በአፍህ ውስጥ እስካለ ድረስ ሁሉንም አይነት ጥያቄዎችህን ለጊዜው ፈታኻቸው ማለት ነው፡፡” ያለውም ለዚሁ ነው፡፡

Published in ባህል