የሐሙሱ የመኢአድና አንድነት ውህደት ሳይጀመረ ፈረሰ
ምርጫን ብቻ ግብ ያደረጉ ጥምረቶች ዋጋ አይኖራቸውም
የፓርቲዎች ውህደት ባይሳካም የተገኘው ልምድ ቀላል አይደለም
ለተቃዋሚዎች አለመጠናከር ኢህአዴግ ተጠያቂ ነው
“በሀገራችን የፓርቲ ፖለቲካ ብዙ ዘመን አስቆጥሯል ማለት
ባይቻልም በአሁኑ ጊዜ ፓርቲዎች ማደግ ሲገባቸው እየቀጨጩ ነው፣ በሜዳው ላይ መኖር የማይገባቸው ፓርቲዎችም አሉ፡፡ ፕሮግራማቸው አንድ ሆኖ እንኳ ተከፍለው መንቀሳቀሳቸው ትክክለኛ አካሄድ ካለመሆኑ በተጨማሪ ለገዥው ፓርቲም የስልጣን እድሜን እየሰጠ ነው ያሉት ከዚህ ቀደም በተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራረርነት ቆይተው አሁን ላይ ከፓርቲ ፖለቲካ ራሳቸው ያገለሉት ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም ናቸው፡፡

አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) እና የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ውህደት ይፈፅማሉ ተብሎ ሲጠበቅ መኢአድ ለአንድነት በፃፈው ደብዳቤ፣ ውህደቱ ለሌላ ጊዜ መተላለፉን አስታውቋል፡፡ በመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መኃሪ ፊርማ የወጣው ደብዳቤ፣ የፕሮግራምና የደንብ ጉዳይ፣ የስያሜ፣ የኃላፊነት፣ አንድነት ከመድረክ ጋር ስላለው ግንኙነት እንዲሁም የንብረት ጉዳዮችን በተመለከተ ተጨማሪ ውይይት ማድረግ እንደሚያስፈልግ ይጠቁማል፡፡
ረቡዕ እለት ደብዳቤው እንደደረሳቸው የገለፁት የአንድነት ፓርቲ ዋና ፀሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ፤ እሁድ መጋቢት 8 ቀን 2006 ዓ.ም የሁለቱም ፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት በመኢአድ ፅ/ቤት ተገናኝተው ባካሄዱት የጋራ ውይይት ላይ ድርድሩ ማለቁን በማመልከት፣ ውህደቱ ከመጋቢት 11 ቀን 2006 ዓ.ም እንዳያልፍ አሳስበው እንደነበር አስታውሰዋል፡፡
“አባላቱ በጥቃቅን ምክንያት ውህደቱን እንዳታሰናክሉ የሚል ማሳሰቢያ ሠጥተውን ነበር” ያሉት አቶ ስዩም፤በዚህ መሰረት አንድነት አስፈላጊ ዝግጅቶችን አጠናቆና  የሆቴል አዳራሽ ተከራይቶ ካጠናቀቀ በኋላ ደብዳቤው እንደደረሰው ተናግረዋል፡፡ “አሁን ኳሱ በመኢአድ እጅ ነው ያለው” ያሉት አቶ ስዩም፤ በአንድነት በኩል እንደ ምክንያት የተጠቀሱት ጉዳዮች በድርድሩ እልባት አግኝተዋል የሚል እምነት አለ ብለዋል፡፡
የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መኃሪ በበኩላቸው፤ ሰሞኑን በወጣ አንድ ጋዜጣ ላይ በአንድነት በኩል “ከመድረክ ጋር እንቀጥላለን” የሚል መግለጫ በመሰጠቱ ውህደቱን ልናዘገየው ተገድደናል ብለዋል።    “ድርድሩ ቆሟል ማለት አይደለም፤ይቀጥላል ነገር ግን መኢአድ በደብዳቤው የጠየቃቸው ካልተሟሉ ውህደቱ ላይፈፀም ይችላል” ብለዋል-ፕሬዚዳንቱ፡፡
ውህደት፣ቅንጅት፣ጥምረት…
ኢህአዴግ አገሪቱን ከተቆጣጠረ በኋላ ከተቋቋሙ የፖለቲካ ፓርቲዎች አንዱ የመላ አማራ ህዝብ ድርጅት (መአኅድ) ሲሆን ነሐሴ 5 ቀን 1994 ዓ.ም ባስተላለፈው ውሳኔ ወደ አገር አቀፍ ፓርቲነት በመለወጥ መኢአድ በሚል ስያሜ እንደሚንቀሳቀስ ይፋ አደረገ፡፡ ይሄኔ በአባላቱ መካከል ክፍፍል ተፈጠረ፡፡ መኢአድ ሆኖ ከተዋቀረ በኋላ በልዩነት ከፓርቲው የወጡ ሰዎችም ኢዴአፓን አቋቋሙ፡፡  ኢዴአፓ፤ከኢዲዩ፣ ከኢዳግ እና ከመድህን ጋር ውህደት ፈፅሟል፡፡ መስከረም 20 ቀን 1997 ዓ.ም ኢዴአፓ (ከመኢአድ የወጣ) እና መድህን መዋሀዳቸውንና  በግንቦት ወር የሚከናወነው ምርጫ፤ ነፃና ሚዛናዊ እንዲሆን  በመንግስት በኩል መሟላት ያለባቸው ጥያቄዎች ቢኖሩም በምርጫው እንደሚሳተፉ ገለፁ፡፡
ውህደታቸውን ተከትሎም ዶክተር አድማሱ ገበየሁ ፕሬዚደንት፣ ዶክተር ኃይሉ አርአያና ዶክተር ጎሹ ወልዴ ምክትል ፕሬዚዳንት እንዲሁም አቶ ልደቱ አያሌው ዋና ፀሀፊ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ በዛው ሰሞን ኢዴአፓ፣መድህንና መኢአድ ለመዋሃድ ያደረጉት ሙከራ ጫፍ ላይ ከደረሰ በኋላ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ጥቅምት 1997 ዓ.ም ኢዴአፓ መድህን፣ መኢአድ ኢድሊ እና ቀስተ ደመና ቅንጅትን መስርተው ኢህአዴግን በግንቦቱ ምርጫ በብርቱ ለመፎካከር መዘጋጀታቸውን አስታወቁ፡፡ ህዳር 9 ቀን 1997 ዓ.ም አራቱ ፓርቲዎች በምርጫው ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ በሚል ስያሜ ለመወዳደር መወሰናቸውን በፊርማቸው አረጋገጡ፡፡ በምርጫው ቢሸነፉ እንኳን ተዋህደው አንድ ፓርቲ የመሆን የረጅም ጊዜ እቅድ እንዳላቸውም አስታወቁ፡፡ ቅንጅቱ አልፎ አልፎ ከሚሰሙ ልዩነቶች ውጪ ብዙዎችን ከጎኑ በማሰለፍ እና  ደጋፊዎችን በማሰባሰብ፣ ኢህአዴግን የሚገዳደር ጠንካራ ፓርቲ ሆነ፡፡ ምርጫው ግንቦት ተካሂዶ ሰኔ ላይ የልዩነት ወሬዎች በስፋት መውጣት ጀመሩ፡፡ በዚያው ወር መኢአድ በውስጣዊ ችግር መተብተቡ የተነገረ ሲሆን ድርጅቱን ከመፍረስ ለመታደግ ኮሚቴ አቋቁሞ መንቀሳቀስ ጀመረ፡፡ የቅንጅቱ ክፍፍል እየተብላላ ቆይቶ ጥቅምት ላይ ከኢዴአፓ መድህን አቶ ልደቱ አያሌውንና አቶ ሙሼ ሰሙን አገደ፡፡
የቅንጅት አመራሮች ከታሰሩ በኋላ የተወሰኑ  ፓርላማውን የተቀላቀሉ የቅንጅቱ ተመራጮች  ኢዴፓ፣ የፓርላማ ቡድን፣ መኢአድ  እና ቅንጅት በሚል ተከፋፍለው መቀመጫቸውን ያዙ፡፡ ምርጫ 2002 ዓ.ም ሲቃረብም ምርጫን ዓላማ ያደረጉ የትብብር ስምምነቶች፣ ግንባር እና መድረክ መፍጠር እንዲሁም መቀናጀት ይፋ ተደረጉ፡፡ ህዳር 25 ቀን 2002 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ እና የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ህብረት በግንባር ደረጃ ተቀናጅተው እንደሚንቀሳቀሱ ገለፁ፡፡ የካቲት 21 ቀን 2002 ዓ.ም በምርጫ ቦርድ የተመዘገቡ አምስት የኦሮሞ ድርጅቶች- የኦሮሞ አቦ ነፃነት ግንባር፣ የኦሮሞ አንድነት ነፃነት ግንባር፣ የገዳ ስርአት አራማጅ ፓርቲ፣ የኦሮሚያ ነፃነት ብሄራዊ ፓርቲ እና የመላው ኦሮሞ ዲሞክራቲክ ፓርቲ ለቀጣዩ ምርጫ በቅንጅት ለመንቀሳቀስ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን አስታወቁ፡፡
አንድነት ከተቋቋመ በኋላም በታህሳስ 2001 ዓ.ም “መርህ ይከበር” የሚል መሪ ቃል ያነገቡ ወገኖች ከፓርቲው ወጥተው ሰማያዊ ፓርቲን አቋቋሙ፡፡ በሰኔ 2000 ዓ.ም መድረክን ለማቋቋም መምከር ተጀመረ፡፡ የካቲት 2001 ዓ.ም ደግሞ የስድስት ፓርቲዎች ጥምረት ተመሰረተ፡፡ መስከረም 24 ቀን 2003 ወደ ግንባር ተሸጋገረ፡፡ በያዝነው ዓመት አንድነት ከመድረክ የታገደ ሲሆን ብዙም ሳይቆይ  ከመኢአድ ጋር ውህደት ለመፈፀም በዝግጅት ላይ መሆኑን አስታወቀ፡፡
“ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ፓርቲዎች የተጓዙበት መንገድ ሲገመገም፣ ይህ ነው ተብሎ የሚጠቀስ ተጨባጭ ውጤት አላመጣም፡፡ ንቅናቄያቸውም በየጊዜው እየቀጨጨ የሚሄድ ሲሆን  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተለይ አብሮ ለመስራት ያላቸው ተነሣሽነትና ፍላጐት የተዳከመ ብሎም ተስፋ የሚያስቆርጥ ደረጃ ላይ የደረሰ ነው” ይላሉ - የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ አበባው መኃሪ፡፡
ባለፉት 23 አመታት በሀገሪቱ ያሉ ዋና ዋና ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሲቀናጁ፣ ሲጣመሩ፣ ሲዋሃዱ  ሲፈርሱ ነው የኖሩት፡፡ አቶ አበባው እንደሚሉት፤ለዚህ ምክንያቱ ከሃገራዊነት ስሜት ይልቅ የግለሰቦች ስሜትና ፍላጐት አይሎ መውጣቱ ነው፡፡ “የተሞከሩት ቅንጅቶች እና ጥምረቶች በሙሉ ሴራ ያልተለያቸው፤ የግለሰቦችን ፍላጐት ብቻ ጠብቀው የተፈጠሩ በመሆኑ በትንሽ ተንኮል ይፈርሳሉ፡፡ ዛሬ  ይህ ተንኮል ይበልጥ መልኩን ቀይሮ ተባብሮ ለመስራት ሳይሆን አንዱ ሌላውን ፓርቲ ለመውረስ ነው የሚጥረው” ብለዋል - አቶ አበባው። በ1997 ዓ.ም በተደረገው ምርጫ ከፍተኛ የፖለቲካ መነቃቃት የፈጠረው ቅንጅት፤ የፈረሰበት ምክንያትም በዚህ መሰሉ ሴራ ነው ይላሉ - ቅንጅቱ ፓርቲዎች ሠምና ወርቅ ሣይሆን ውሃና ዘይት ሆነው የተቀናጁበት መሆኑን በመጠቆም፡፡
በፕሬዚዳንትነት የሚመሩት መኢአድ የስበት ማዕከል ሆኖ መቆየቱን የጠቀሱት አቶ አበባው፤ፓርቲው ከሌሎች ጋር ለመጣመርና ለመዋሃድ ያደረጋቸው ሙከራዎች ያልሰመሩት ፓርቲዎች ወደ መኢአድ ሲመጡ በቅንነት ሳይሆን ህልውናውን በሚፈታተን መልኩ ስለሆነ ነው ይላሉ፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ ሠላማዊ ትግሉ በእነዚህ ምክንያቶች ውጤት አልባ ሆኖ ቆይቷል የሚሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ለውጤት አልባነቱ ኢህአዴግም የራሱን አስተዋጽኦ አበርክቷል ሲሉ ይወቅሣሉ፡፡ “የተቃዋሚ ፓርቲ አባል የሆነ ገበሬ፣ መሬት እና የግብርና ግብአቶች እንዳያገኝ፣ የመንግስት ሠራተኛ ከሆነ ከስራው እንዲፈናቀል፣ እርዳታ ፈላጊ እርዳታ እንዳያገኝ እየተደረገ፣ ሰዎች በነፃነት መብታቸውን እንዳያስከብሩና በፈለጉት የፖለቲካ ፓርቲ ጥላ ስር እንዳይሰባሰቡ ከፍተኛ የሥነ ልቦና ጫና ፈጥሯል” ሲሉ ይኮንናሉ፡፡ ኢህአዴግ  ባለፉት 23 አመታት በትጋት ተቃዋሚዎችን ለማቀጨጭና ከተቻለውም ለማጥፋት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ሲሠራ፤ ህብረቶችንና ቅንጅቶችን በሴራ ሲያፈርስ ነው የኖረው ሲሉም አምርረው ይወቅሳሉ፡፡
“ለዲሞክራሲ ምቹ የሆንን ሰዎች አይደለንም” የሚሉት አቶ አበባው፤ ከጥቂት አመታት በፊት በጦርነት ሲታመሱ የነበሩ እንደ ላይቤሪያ እና ሴራሊዮን የመሳሰሉ ሃገሮች እንኳ ከኢትዮጵያ በተሻለ ሁኔታ ዲሞክራሲን እየተገበሩ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ ተቃዋሚ ሆኖ ለዲሞክራሲ የሚደረግ ትግል ውስጥ ውጤት ለማምጣት ብዙ ሂደቶችን ማለፍ እንደሚጠበቅ ገልፀው፤ በዚህ ረገድ የሚፈለገውን ያህል ተስፋ የሚሠጥ ባይሆንም ህዝቡን በማነቃቃት ረገድ ተቃዋሚዎች የነበራቸው ሚና የሚዘነጋ አለመሆኑን አቶ አበባው አመልክተዋል፡፡
ቀደም ሲል የመኢአድ አባል በመሆን በፓርቲው ውስጥ ሲሠሩ ከቆዩ በኋላ በተፈጠሩ አለመግባባቶች አዲስ ፓርቲ ወደማቋቋም ከተሸጋገሩት አቶ ልደቱ አያሌውና ሌሎች ግለሰቦች ጋር በመሆን የኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲያዊ ፓርቲን (ኢዴፓ) የመሠረቱት አቶ ሙሼ ሰሙ በበኩላቸው፤ ባለፉት 23 አመታት በመቀናጀት፣ ግንባርና ጥምረት በመፍጠር ረገድ ውጤት ያመጣና አላማውን ያሳካ ፓርቲ አላየሁም ሲሉ የአቶ አበባውን ሃሳብ ይጋራሉ፡፡ በትንሹ ሊጠቀስ የሚችለው 1997 ላይ የተፈጠረው ቅንጅት ብቻ ነው የሚሉት አቶ ሙሼ፤ እሱም ቢሆን ጠንካራ ስላልነበረ ሙሉ ለሙሉ ውጤታማ መሆን እንዳልቻለ ይገልፃሉ፡፡ በዋናነትም የፓርቲዎች ጋብቻ ውጤታማ የማይሆነው ጥምረታቸው ከፕሮግራም፣ ከአላማ እና ከግብ አንድነት በሚመነጭ ሳይሆን ኢህአዴግን ተሰባስቦ ለማሸነፍ ካለ ፍላጐት ወቅታዊ ጉዳይን ብቻ መነሻ አድርጐ የሚፈጠር በመሆኑ ነው የሚሉት አቶ ሙሼ፤ ምርጫ ሲደርስ ብቻ ፓርቲዎች ለመቀናጀትና ለመጣመር መሯሯጣቸውም ይህን ያመለከታል፣ ምርጫን ብቻ ግብ ያደረጉ ጥምረቶች  ደግሞ ከምርጫው በኋላ ዋጋ አይኖራቸውም ብለዋል፡፡
“የውህደት ጥምረት እና ቅንጅት ምስረታ ውጥኖች ከሚከሽፉባቸው ምክንያቶች መካከልም ፓርቲዎች አንድነቱን ከመፈለግ ባሻገር ማን አመራር ይሁን በሚለውና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ በቂ የስነ ልቦና ዝግጅት አለማድረጋቸው እና አርቆ አለማሰባቸው ዋናው ነው” ይላሉ አቶ ሙሼ፡፡
ፓርቲያቸው ኢዴፓ ከተመሰረተ ጀምሮ ከሶስት ፓርቲዎች ጋር ስኬታማ ውህደት መፍጠሩን አቶ ሙሼ ይጠቅሳሉ፡፡ ከኢዳግ፣ ኢዲዩ እና ከመድህን ጋር ጥሩ ምሳሌ ሊሆን የሚችል ውጤታማ ውህደት መፈጠሩን ያስታወሱት አቶ ሙሼ፤ ከመኢአድ ጋርም በ1996 መጨረሻ አካባቢ ለመዋኃድ የተደረገው የድርድር ሂደት 90 በመቶ ከደረሰ በኋላ መክሸፉን ከፓርቲያቸው ያልተሳኩ ተሞክሮዎች አንዱ ነበር ይላሉ፡፡ በወቅቱ መኢአድ እና ኢዴፓ በበርካታ ጉዳዮች ላይ የተስማሙ ቢሆንም በስራ አስፈፃሚ ውስጥ ትልቁ ድርሻ የማን ነው? የሚለውን መሰረታዊ ጉዳይ ጨምሮ ምን አይነት የመንግስት አወቃቀር ሊኖር ይገባል፣በመሬትና በቋንቋ ጉዳይ ላይ እንዲሁም በፓርቲው ስያሜ ልዩነት ተፈጥሮ እንደነበር ይጠቅሳሉ፡፡ መኢአድ በወቅቱ የመንግስት ስርአቱ ፕሬዚዳንታዊ ይሁን ሲል ኢዴፓ የለም ፓርላሜንታዊ ይሁን በማለቱ የተፈጠሩ የፕሮግራም ልዩነቶችን መነሻ አድርጎ እስከ መዘላለፍና መወነጃጀል የደረሱ አለመግባባቶች መፈጠራቸውንም አቶ ሙሼ ያስታውሳሉ፡፡ ፓርቲያቸው ከቅንጅት ጋር የፈጠረው ጥምረትም በአላማ እና በአካሄድ ልዩነት መክሸፉን አመልክተው፣ ፓርቲው ካደረጋቸው ውጤታማ ውህደቶች መካከልም ከኢዲዩ ጋር የነበረውን ይጠቅሳሉ። በአንዳንድ ግለሰቦች ምክንያት እክል አጋጥሞት የነበረ ቢሆንም  መፍትሄ አግኝቶ አብሮ መጓዝ እንደተቻለ ያስታውሳሉ፡፡
የእስከ ዛሬው የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጉዞ ጠቅለል ብሎ ሲገመገም፣ ህዝብን ተስፋ ያስቆረጠ ነበር ያሉት አቶ ሙሼ፤ ከዚህ በኋላም ቢሆን አንድ ላይ ለመስራት ከፍላጎት ባሻገር የስነልቦና ዝግጅት ሳይደረግ የሚፈጠሩ ውህደቶች እና ጥምረቶች ከሚፈለገው ውጤት ላይ መድረስ አይችሉም ይላሉ፡፡ “የተጠናቀረ ፓርቲ መፍጠር ቀላል አይደለም” የሚሉት አቶ ሙሼ፤ 23 ዓመት ኢህአዴግን የሚገዳደር ጠንካራ ፓርቲ መፍጠር የሚያስችል በቂ ጊዜ ነበር ለማለት አያስደፍርም ብለዋል፡፡ “ማህበረሰቡ ምርጫ ያስፈልጋል ብሎ እንዲያስብ፣ ገዥው ፓርቲ ልጓም አልባ እንዳይሆን በማድረግ በኩል ተቃዋሚዎች የማይናቅ ድርሻ ነበራቸው” ይላሉ አቶ ሙሼ፡፡
ባለፉት ሁለት አስርት አመታት በሃገሪቱ ለተስተዋለው ፖለቲካዊ እና ማህበራዊ ቀውስ በስልጣን ላይ ካለው ኢህአዴግ በበለጠ ተቃዋሚዎች ተጠያቂዎች ናቸው የሚሉት ደግሞ የአንድነት ለፍትህ እና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው ናቸው፡፡ ህብረት፣ ቅንጅት፣ አማራጭ ኃይሎች፣ መድረክ እየተባለ እስከዛሬ ቢዘለቅም ያስገኘው ውጤት ሲገመገም በዜሮ የሚጣፋ ነው የሚሉት ሊቀመንበሩ፤የፓርቲ አመራሮች ከአመት አመት ከስህተታችን ሳንማር የኢትዮጵያን ህዝብ በድለነዋል፤ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ጉጉቱንም አጨልመንበታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ለኢህአዴግ ጠንካራ መሆን የተቃዋሚዎች ድክመት አስተዋፅኦ ማበርከቱን በአፅንኦት የሚገልፁት ኢ/ሩ፤ ውጤት አልባው ሂደት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ትልቁ አሳዛኝ ታሪክ ምዕራፍ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
“በሀገራችን የፓርቲ ፖለቲካ ብዙ ዘመን አስቆጥሯል ማለት ባይቻልም በአሁኑ ጊዜ ፓርቲዎች ማደግ ሲገባቸው እየቀጨጩ ነው፣ በሜዳው ላይ መኖር የማይገባቸው ፓርቲዎችም አሉ፡፡ ፕሮግራማቸው አንድ ሆኖ እንኳ ተከፍለው መንቀሳቀሳቸው ትክክለኛ አካሄድ ካለመሆኑ በተጨማሪ ለገዥው ፓርቲም የስልጣን እድሜን እየሰጠ ነው ያሉት ከዚህ ቀደም በተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራረርነት ቆይተው አሁን ላይ ከፓርቲ ፖለቲካ ራሳቸው ያገለሉት ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም ናቸው፡፡
እንደ አስተያየት ሰጪው ከሆነ የፓርቲዎች ስኬትና ውድቀት የሚያጋጥም ከመሆኑም በላይ በሀገራችን ጠንካራና አስተማማኝ ተቀናቃኝ ፓርቲ ለመፍጠር ጊዜው አልረፈደም፡፡ ከዚህ በፊት የተደረጉ የጥምረት፣ ህብረት፣ ቅንጅት--- ሙከራዎች ፍፃሜ አልሠምር ካለባቸው ምክንያቶች አንዱ የፓርቲ ስልጣን ጥመኝት ነው ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤“ጥመኝነቱ ምናልባትም ብሔራዊ ፀባያችን ሳይሆን አይቀርም” ብለዋል፡፡ እንደተቀሩት አስተያየት ሠጪዎችም ባለፉት 23 አመታት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ላለመጠናከራቸው ኢህአዴግን ተጠያቂ ያደርጋሉ። ጠንካራ ከነበረው ቅንጅት መፍረስ ጀምሮ አሁን ድረስ የሚደረጉ ተመሳሳይ ሙከራዎች ስኬት አልባ ለመሆናቸውም የገዥው ፓርቲ ረጅም እጅ አለበት ሲሉ ዶ/ር ያዕቆብ ይወቅሳሉ የፓርቲ አመራሮችን በቅንጅት ጊዜም ሆነ ከዚያ በኋላ ባሉት ጊዜያት ለእስራት መዳረጉን በዋቢነት በመጥቀስ፡፡
ከኦነግ ታጋይነት እስከ ኢህአዴግ ከዚያም የአገሪቱ ፕሬዚዳንትነት በመጨረሻም የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር የነበሩት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በበኩላቸው፤የፓርቲዎቹ የውህደት እና ጥምረት ስኬታማ ባይሆኑም የተገኘው ልምድ የማይናቅ ነው ይላሉ፡፡ ለፓርቲዎች ጥምረት ውጤት አልባነት ዶ/ር ነጋሶ በምክንያትነት ከጠቀሷቸው መካከል በፓርቲዎች መካከል የሚፈጠሩ አላስፈላጊ ፉክክሮች፣ የስልጣን ጥመኝነት፣ የአላማ እና የአደረጃጀት ግልጽ አለመሆን፣ ህዝቡ ከዳር ሆኖ ከመተቸት ባለፈ በየአደረጃጀቱ ገብቶ ተጽዕኖ ለመፍጠር አለመቻሉ እንዲሁም በፓርቲዎች ላይ ተጽእኖ ሊፈጥሩ የሚችሉ ህዝባዊ አደረጃጀቶች አለመኖራቸው ይገኙበታል፡፡
የእስከዛሬ የፓርቲዎች የቅንጅት፣ ጥምረት እና ውህደት ውጤት አልባ ናቸው የሚለውን ሃሳብ የሚጋሩት ዶ/ር ነጋሶ፤በግንባር ደረጃ ከተሄደ ግን እስከ ዛሬ ሁለት የግንባር አደረጃጀቶች መኖራቸውን ያስቀምጣሉ። አንደኛው ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ሲሆን ሌላኛው “መድረክ” ነው፡፡ የመድረክን ውጤታማነት በተመለከተ በሂደት የምናየው ይሆናል ብለዋል ፤ዶ/ር ነጋሶ፡፡
ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳንና የቀድሞውን የመከላከያ ሚኒስትር አቶ ስየ አብርሀን  በማካተት የቅንጅት አመራሮች ከእስር ከተፈቱ በኋላ የተወሰኑት አመራሮች አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ የሚል ፓርቲ አቋቋሙ። ምርጫ 2002 መቃረቡን ተከትሎ አንድነት ፣ ኦፌዴን ፣ ኦብኮ፣ አረና ተሰባስበው መድረክን አቋቋሙ፡፡

4 የጥንቃቄ ምክሮች - ለመንግስትና ለኢህአዴግ

       አለማችን፣ ከዳር ዳር እየተናጠች ግራ ግብት ብሏታል። የነ ግብፅ እና ሶሪያ እልባት ሳያገኝ፤ ውዥንብር የበዛበት የዩክሬን ትርምስ ተጨመረበት። የዘመናችንን ቀውስ ፍንትው አድርጎ በሚያሳየው የዩክሬን ትርምስ ውስጥ፣ ዋናዎቹ ተዋናዮች አንጋፋ ፖለቲከኞችና ትልልቅ ፓርቲዎች አይደሉም። በሃይማኖትና በቋንቋ ዩክሬንን ለሁለት መሰንጠቅ የጀመሩት ሁለት ነውጠኛ ቡድኖች፤ ከጥቂት ወራት በፊት እንኳን በአለም ደረጃ እዚያው ዩክሬንና ራሺያ ውስጥ ይህ ነው የሚባል ተደማጭነትና ታዋቂነት አልነበራቸውም። “ናሽናል ሶሻሊዝም” በተሰኘው የፋሺዝም ቅኝት እንደ ሞሶሎኒና እንደ ሂትለር “ከራስህ በፊት ለእናት አገርህ” እያሉ የሚዘምሩት ሁለቱ ቡድኖች፤ “አገር ትቅደም። ለአገር መስዋዕት ሁኑ፡፡ የሚል መፈክር ያስተጋባሉ። አንደኛው ቡድን፣ “ለራሺያ መስዋዕት ሁኑ” ሲል፤ ሌላኛው ደግሞ “ለዩክሬን መስዋዕት ሁኑ” እያለ ዘረኝነትንና የሃይማኖት ጥላቻን በጭፍን ስሜት  እያራገቡ በርካታ አመታትን አስቆጥረዋል - ድጋፍ ባያስገኝላቸውም።
እንደ ኒውዮርክ ታይምስ ዘገባ፣ የዩክሬንን አመፅ የመራው የ42 አመቱ ዲሚትሮ ያሮሽ፣ ከመምህራን ኮሌጅ የተመረቀ ከመሆኑ በቀር ያን ያህልም የሚታወቅ ታሪክ የለውም። ከአመታት በፊት በያሮሽ የተመሰረተው የፖለቲካ ፓርቲም ሆነ፣ ቀኝ ዘርፍ በሚል ስያሜ ያቋቋመው ነውጠኛ ቡድን የፓርላማ ወንበር የላቸውም። ፓርቲው በምርጫ ቢወዳደርም አልተሳካለትም። አሁን ግን ነገሮች ተቀይረዋል። ያሮሽ የአገሪቱ የፀጥታ ጉዳዮች ምክትል ሚኒስትር ከመሆኑም በላይ፤ የቡድኑ አባላት የዩክሬን አለኝታና የቁርጥ ቀን ልጆች ስለሆኑ ትጥቅ አይፈቱም ብሏል - በመንግስት ውስጥ ሌላ መንግስት እንደማለት ነው።
በብዛት የራሺያ ቋንቋ የሚናገሩ ሁለት ሚሊዮን ነዋሪዎችን የያዘችው ክሬሚያ፣ ከዩክሬን እንድትገነጠልና ወደ ራሺያ እንድትጠቃለል አመፅ ያካሄደው ሁለተኛው ቡድንም ተመሳሳይ ነው። በክሬሚያ ምክር ቤት ውስጥ ከ3 ወንበር በላይ ይዞ እንደማያውቅና ባለፈው ምርጫ ያገኘው ድምፅ አራት በመቶ ገደማ ብቻ እንደሆነ የታይም መፅሄት ዘገባ ገልጿል። የቡድኑ መሪ ሰርጌ አክስዮኖቭ ከታዋቂ የክሬሚያ ፖለቲከኞች ዝርዝር ውስጥ የሚጠቀስ አልነበረም። ታዋቂ ለመሆን ስላልሞከረ አይደለም። ክሬሚያ ከዩክሬን እንድትገነጠል የሕግ ረቂቅ ለምክርቤቱ በማቅረብ ዝና ለማትረፍ በተደጋጋሚ ሞክሯል - ለበርካታ አመታት። ግን ከቁም ነገር የቆጠረው ሰው አልነበረም። በቅርቡ ነው፤ ሌላ መላ የፈጠረው።
ካለፈው ጥር ወር ወዲህ፣ ከየቦታው ወጣቶችን እየመለመለ ማሰባሰብ የጀመረው አክስዮኖቭ፣  ወደ ጠረፍ አካባቢ እየወሰደ ታጣቂ ቡድን ሲያደረጅ ከርሟል። ብዙም አልቆየም። ከሁለት ወራት በኋላ ዩክሬን ስትቃወስ፣ አክስዮኖቭ ለታጣቂዎቹ የዘመቻ ትዕዛዝ አስተላለፈ። እናም ስራቸውን ሰሩ። የክሬሚያ ምክር ቤትን ወረሩትና ሁለት የአዋጅ ረቂቆች ቀረቡ። አዳራሹን ከሞሉት ሰዎች መካከል፣ የትኞቹ የምክር ቤት አባል እንደሆኑ፣ የትኞቹ ደግሞ የታጣቂ ቡድን አባል እንደሆኑ የሚታወቀው፤ መሳሪያ በመታጠቅና ባለመታጠቅ ብቻ ነው። አዋጅ ለማፅደቅ ድምፅ የሰጡት የትኞቹ እንደሆኑ ግን አይታወቅም። በአንደኛው አዋጅ፣ ክሬሚያ ከዩክሬን እንድትገነጠል በህዝብ ለማስወሰን ምርጫ ይካሄዳል ተባለ። በሁለተኛው አዋጅ ደግሞ፣ የ32 አመቱ አክስዮኖቭ፣ የክሬሚያ ፕሬዚዳንት ሆኖ ስልጣን ያዘ። ፓርቲው በምክር ቤቱ ውስጥ ያሉት ወንበሮች ሶስት ብቻ ቢሆኑም፤ በሺ የሚቆጠሩ ታጣቂዎችን ስላሰማራ፣ ከፍተኛውን ስልጣን ተቆጣጠረ። በዚህ ምክንያት የሚሰነዘሩበትን ትችቶች በማጣጣል፣ “በወቅቱ ግርግር ስለነበር ምንም ማድረግ አይቻልም” የሚለው አክስዮኖቭ፤ “ሃላፊነት የሚወስድ ሰው ጠፋ። ስለዚህ ለአገሬ መስዋዕት ለመሆን ታሪካዊ ሃላፊነት ተረከብኩ” ብሏል።
የዘር እና የሃይማኖት ልዩነትን የሚያራግቡት ሁለቱ ቡድኖች፣ ከተወሸቁበት ጉራንጉር ወጥተው እንዲህ በአገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ ገናና ለመሆን የበቁት ታጣቂ ቡድን በማደራጀታቸው አይደለም። ከሌሎች ፓርቲዎች ያን ያህል የተለየ የፖለቲካ አቋም ስላላቸውም አይደለም። አንጋፋዎቹና ትልልቆቹ ፓርቲዎችም ተመሳሳይ “የናሽናል ሶሻሊዝም” አስተሳሰብን የሚከተሉ ናቸው። የዩክሬን ገዢ ፓርቲ ምን ተብሎ እንደሚጠራ ማየት ትችላላችሁ - “አባት አገር” ይባላል። የራሺያ ገዢ ፓርቲ ደግሞ “አንዲት ራሺያ” ይሰኛል። “ብሄረተኝነት” ወይም “አገራዊነት” የሚባለው የፋሺዝም ቅኝት፣ “እያንዳንዱ ሰው፣ ከራሱ ጥቅምና ከራሱ ሕይወት በፊት፤ ከግል መብቱና ከነፃነቱ በፊት ለአገሩ፣ ለብሔሩ፣ ለጎሳው ቅድሚያ መስጠትና መስዋዕት መሆን አለበት” የሚል አስተሳሰብ ላይ የተመሰረተ ነው። ከዚህ የተለየ አዝማሚያ አላቸው የሚባሉት ሌሎቹ ፓርቲዎች፤ በአብዛኛው የሶሻሊዝምና የኮሙኒዝም እንጥፍጣፊዎች ናቸው - “እያንዳንዱ ሰው ከራሱ ሕይወትና ከግል ነፃነቱ በፊት፤ ለድሆች፣ ለጭቁኖችና ለሰፊው ሕዝብ ጥቅም ቅድሚያ መስጠትና መስዋዕት መሆን አለበት” የሚለውን ሃሳብ ያዘወትራሉ።
“ናሽናሊስቶቹ” እና “ሶሻሊስቶቹ” ያን ያህልም በሃሳብና በስሜት የሚራራቁ አይደሉም። ሁለቱም በጋራ፣ “የግለሰብ ነፃነትና መብት” የሚባለውን ነገር ይጠላሉ። አንደኛው ወገን፤ “ለአገር ወይም ለብሔር ብሔረሰብ ጥቅም ቅድሚያ እሰጣለሁ” በሚል መፈክር፤ ሌላኛው ወገን ደግሞ “ለጭቁን ሕዝብና ለድሆች ጥቅም ቅድሚያ እንሰጣለሁ” በሚል ሰበብ፤ የሰውን መብትና ነፃነት መርገጥ እንደሚቻል ያምናሉ። ይህ ብቻ አይደለም ተመሳሳይነታቸው። የትኛውን ሰበብና መፈክር ያዘወትራሉ ብለን ልንለያቸው ካልሞከርን በስተቀር፤ አንዱ የሌላኛውን መፈክር ከመጠቀም ወደ ኋላ አይልም። ዘረኝነትንና ብሔረተኝነትን በማራገብ የሚታወቁት ሂትለርና ሞሶሎኒ፣ ለሰፊው ሕዝብና ለድሆች በአለኝታነት የምንቆም ሶሻሊስቶች ነን ይሉ አልነበር? በሰፊው ሕዝብና በድሆች ስም የሚምሉ የሚገዘቱ የዩጎዝላቪያ ሶሻሊስቶችም በተራቸው፤ ዘረኝነትንና ብሄረተኝነትን በማጦዝ አገሪቱን ሰነጣጥቀው በደም አጨቅይተዋታል። የእያንዳንዱን ግለሰብ መብትና ነፃነት ለማክበር ፍላጎት የሌላቸው እነዚሁ ቅኝቶች፤ “የሕዝባዊነት አስተሳሰብ ተከታይ” (collectivist) የሚል የጋራ ስያሜ ሊሰጣቸው ይችላል። በራሺያም ሆነ በዩክሬን፣ ትልልቆቹና አንጋፋዎቹ ፓርቲዎች የዚህ አስተሳሰብ ምርኮኞች ናቸው - እያንዳንዱ ሰው፤ ምንም አይነት ነፃነት የሌለው የሕዝብ ሎሌ ወይም አገልጋይ ባርያ መሆን ይገባዋል ብለው የሚያምኑ። እያንዳንዱ ሰው የሕዝብ ሎሌ መሆን አለበት ሲባል፤ በሌላ አነጋገር የመንግስት ሎሌ፤ እናም የገዢው ፓርቲ ሎሌ ይሆናል እንደማለት ነው።
እንደዚያም ሆኖ፤ በሃሳብ ደረጃ “ሕዝባዊነት”ን የሚሰብኩ የዘመናችን ብዙ ፓርቲዎች፤ በተግባር የምኞታቸውን ያህል መሄድ አይችሉም፤ እንደ ሞሶሎኒና ሂትለር ወይም እንደ ሌኒንና ስታሊን፣ ያፈጠጠ ያገጠጠ የፋሺዝም ወይም የሶሻሊዝም ስርዓት ለማስፈን አይደፍሩም። ለምን? ሕዝባዊነት፣ በ20ኛው ክፍለዘመን ምን ያህል እልቂትና ስቃይ፣ ምን ያህል ድህነትና ረሃብ እንዳስከተለ ስለሚታወቅ፤ አብዛኛውን ወጣትና ምሁር የመማረክ ወይም የማነሳሳት ሃያልነቱ ሞቷል። ስለዚህ፤ የዩክሬን ትልልቅ ፓርቲዎችን ጨምሮ ሕዝባዊነትን የሚሰብኩ አብዛኞቹ የዘመናችን ፓርቲዎች፣ በሙሉ ልብ ሃሳባቸውን ተንትነው ቢያቀርቡ ሆ ብሎ የሚከተላቸው አያገኙም፤ ሃሳባቸውን ተግባራዊ የሚያደርጉትም በግማሽ ልብ ነው። የአስተሳሰባቸውን ያህል የሰውን ምርትና ንብረት በጠራራ ፀሐይ ባይወርሱም፤ መንግስት እለት በእለት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ ጣልቃ እየገባ በአላስፈላጊ ቁጥጥሮችና ገደቦች የሰዎችን ኑሮ እንዲያናጋ ያደርጋሉ፡፡ በተለያዩ የቀረጥና የታክስ አይነቶች የሰውን ኪስ ያራቁታሉ። የስብከታቸውን ያህል ጭልጥ ብለው ባይገቡበትም፣ በመጠኑ ዘረኝነትን ያራግባሉ። በአጭሩ ስብከታቸውና ድርጊታቸው ይለያያል። ቆጠብ ለማለት ይሞክራሉ።
አንጋፋዎቹ ፓርቲዎች ችባ ሆነዋል ቢባል የተጋነነ አይደለም። “የሕዝባዊነት” አስተሳሰባቸውን ተንትነው እንዳያቀርቡ፣ በ20ኛው ክፍለዘመን የሞተ አስተሳሰብ ነው። በስሜት ደረጃ እያግለበለቡ እንዳይሰብኩም መዘዙን እየፈሩ ቆጠብ ይላሉ። ከትንታኔም ሆነ ከስሜት አንዱንም ሳይሆኑ ይቀራሉ። ሁለቱ መናኛና ነውጠኛ ቡድኖችም ወደ ትንታኔ የመግባት ዝንባሌ የላቸውም። ነገር ግን፤ ጭፍን ስሜት ከማግለብለብ ቆጠብ የማለት ፍላጎት የላቸውም። ጭልጥ ብለው ዘረኝነት ውስጥ ገብተዋል። ጉልበት ያገኙትና ዋነኛ የጥፋት ተዋናይ ለመሆን የበቁትም በዚህ ምክንያት ነው።
በእርግጥ፣ በ20ኛው ክፍለዘመን “የሕዝባዊነት አስተሳሰብ” ነግሶ ከመሞቱ በፊት፣ ሁለት ዋና ዋና የአስተሳሰብ አይነቶች ነግሰው ሞተዋል። አንደኛው፤ ሊበራሊዝም የሚባለው የስልጣኔ ዘመን አስተሳሰብ ነው። “እያንዳንዱ ግለሰብ በራሱ ሕይወትና ንብረት ላይ ብቸኛ አዛዥና ወሳኝ መሆን ስላለበት መብቱና ነፃነቱ ሙሉ ለሙሉ ሊከበርለት ይገባል፤ በሌላ ሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ደግሞ ቅንጣት ስልጣን የለውም። ስለዚህ የማንንም ሰው መብትና ነፃነት ንክች ማድረግ የለበትም። እነካለሁ፤ በሌሎች ሰዎች ሕይወትና ንብረት ላይ ፈላጭ ቆራጭ እሆናለሁ የሚል ወንጀለኛ መኖሩ አይቀርም። መንግስት የሚያስፈልገውም በዚህ ምክንያት ነው” ይላል ሊበራሊዝም። በዚህ አስተሳሰብ፤ የመንግስት ስራ፣ ሌላ ሳይሆን የእያንዳንዱን ሰው ነፃነት ማስከበርና ይህንን የሚጥሱ ወንጀለኞችን ልክ ማስገባት ነው። አለመግባባት የፈጠሩ ሰዎችንም መዳኘት።
በአጭሩ፣ የመንግስት ስራ፤ የዳኝነት ወይም የግልግል እንዲሁም የዘበኝነት ወይም የጥበቃ ስራ ነው። እንግዲህ፣ የዲሞክራሲ ጥያቄ የሚመጣው እዚህ ላይ ነው። ሰዎች ድምፃቸውን የሚሰጡትና ውሳኔ የሚያስተላልፉት፤ የሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ለማዘዝ አይደለም። ከራሱ ከሰውዬው በስተቀር፣ ማንም የማዘዝ ስልጣን የለውም። በቁጥር የመብለጥና የማነስ ጉዳይ አይደለም።  ለብቻዬም ብሆን አልያም ሚሊዮኖችን ባስከትል ወይም ከጠቅላላው ሕዝብ ውስጥ 99 በመቶ ያህሉ የድጋፍ ድምፅ ቢሰጠኝ ለውጥ የለውም። በሌላ ሰው ሕይወትና ንብረት ላይ ቅንጣት ስልጣን አይኖረኝም። 99 በመቶም ሆነ 51 በመቶ “ሕዝብ” እና “የሕዝብ ተመራጭ”፣ እንዳሰኘው ሰውን የመግደል አልያም የሰውን ንብረት የመውረስና የመዝረፍ መብት የለውም። እና ታዲያ፣ ሕዝብ በፖለቲካ ምርጫዎች ላይ የሚሳተፈውና ድምፅ የሚሰጠው ለምንድነው? የእያንዳንዱን ሰው ነፃነት የሚያስከብሩ የመንግስት አካላትን (ማለትም ገላጋዮችና ዘበኞችን) አማርጦ ለመቅጠር ነው ምርጫ የሚካሄደው። ስልጣን አገኘሁ ወይም በቁጥር እበልጣለሁ ብሎ፣ ሰዎችን መጨፍጨፍና መዝረፍ አይቻልም።
በ17ኛው ክፍለ ዘመን ተስፋፍቶ፣ በ18ኛው ክፍለዘመን ለአሜሪካ ምስረታ ጠንካራ መሰረት ሊሆን የበቃው የ“ሊበራሊዝም” አስተሳሰብ፣ ከሁሉም በላይ ለእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነት ከፍተኛውን ክብር ይሰጣል። ዲሞክራሲ ደግሞ፣ ይህንን መብትና ነፃነት ለማስከበር የሚያገለግል መሳሪያ ወይም አሰራር ነው። ለዚህም ነው ሊበራል ዲሞክራሲ ብለው የሚጠሩት። “ዲሞክራሲ” በጥሬው ሲሆን ግን፤ 51 በመቶው “ሕዝብ” ወይም “የሕዝብ ተመራጭ” እንዳሰኘው በሰዎች ላይ የሚፈነጭ የ“አምባገነንነት” ዝርያ ይሆናል። ለዚህም ነው፤ ታላቋን የነፃነት አገር አሜሪካን የመሰረቱ ጥበበኛና አስተዋይ ፖለቲከኞች፤ የአገሪቱን የፖለቲካ ስርዓት በ“ግለሰብ ነፃነት” ላይ እንጂ በ“ዲሞክራሲ” ላይ የተመሰረተ እንዳልሆነ በአፅንኦት ሲናገሩ የነበሩት።  ለዚህም ነው፤ በአሜሪካ የነፃነት መግለጫ፤ ማንኛውም አይነት መንግስት፣ የተመረጠም ይሁን ያልተመረጠ፣ ዲሞክራሲያዊም ሆነ ንጉሳዊ፣ አገር በቀልም ይሁን መጤ፣ የእያንዳንዱን ሰው መብትና ነፃነት የማያከብር እስከሆነ ድረስ፣ ከስልጣን መወገድ የሚገባው ሕገወጥ መንግስት እንደሆነ በግልፅ የሚያውጀው። በሕገመንግስት ውስጥም እንዲሁ፣ በሕዝብ የሚመረጠው የአገሪቱ ምክር ቤት (ኮንግረስ)፣ የሰዎችን የሃሳብ ነፃነት የሚጥስ፣ በሰዎች ሃይማኖት ውስጥ ጣልቃ የሚገባ፣ ወይም ሃይማኖትን በመንግስት ጉዳይ ውስጥ እንዲገባ የሚያደርግ ሕግ የማፅደቅ ስልጣን እንደሌለው በግልፅ ተደንግጓል። በሕዝብ ተመርጬ ስልጣን ይዣለሁ ብሎ እንዳሻው የሰዎችን መብትና ነፃነት መጣስ አይችልም። ሕገመንግስት ያስፈለገውም፤ ይህንን “የሕዝብ” ወይም “የመንግስት” ስልጣን ለመገደብ ነው። በአጭሩ፤ ዋነኛው የፖለቲካ ማጠንጠኛ፣ ዲሞክራሲና ምርጫ አይደሉም - የእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነትን ማስከበር ነው አስኳሉ። ይሄው ስልጡን የፖለቲካ አስተሳሰብ፣ በአሜሪካ በስፋት ከከተገበረ በኋላ፤ በርካታ አገራት ቀስ በቀስ እንዲሻሻሉ፣ ከአምባገነንነትና ከእልቂት፣ ከድህነትና ከረሃብ እንዲላቀቁ ረድቷል። አሳዛኙ ነገር፤ እየተጠናከረ ከመሄድ ይልቅ፤ “የራስ ወዳድነት አስተሳሰብ ነው” በሚል እየተንቋሸሸና እየተሸረሸረ፣ በ20ኛው ክፍለዘመን የበላይነቱን አጥቶ በ“ሕዝባዊነት” አስተሳሰቦች አማካኝነት ተዳክሟል። አብዛኛውን ወጣትና ምሁር የመማረክ ወይም የማነሳሳት ሃያልነቱ ተመናምኗል። እናም፤ ሊበራሊዝምን የሚሰብኩ አብዛኞቹ የዘመናችን ፓርቲዎች በግማሽ ልብ ነው ተግባራዊ የሚያደርጉት። በአብዛኛውም፣ የኢኮኖሚ እድገት ለማስመዝገብ ሲሉ።
ሶስተኛው ርዕዮተ ዓለም፣ ከሊበራሊዝምና ከሕዝባዊነት በፊት ገናና የነበረ ጥንታዊ ርዕዮተ ዓለም ነው - ሃይማኖታዊ ርዕዮተ ዓለም። ይሄኛው ሃይማኖታዊ የፖለቲካ አስተሳሰብም፤ ዛሬ እንደ ጥንቱ ሃያል አይደለም። ለሺ አመታት አለምን በጦርነትና በድህነት ውስጥ ዘፍቋት የቆየው ሃይማኖታዊ የፖለቲካ አስተሳሰብ፣ የበላይነቱን በሊበራሊዝም አስተሳሰብ  ተነጥቆ የስልጣኔ ብርሃን ከደመቀ ወዲህ እንደገና ሃያልነቱን መልሶ የማግኘት እድል አላገኘም።
ከእነዚህ ሶስቱ አስተሳሰቦች ውጭ (ከሃይማኖታዊ፣ ከሊበራሊዝም፣ እና ከሕዝባዊ አስተሳሰብ ውጭ) ሌላ አይነት አስተሳሰብ የለም። ግን ደግሞ ሶስቱ አስተሳሰቦች፣ አብዛኛውን ወጣትና ምሁር የመማረክና የማነሳሳት ሃይልነታቸውን አጥተዋል። እና የአለምና የታሪክ መዘውር የሚሽከረከረው በምንድነው? መድረሻችንስ የት ነው?
ሊታረቁ የማይችሉት ሶስቱ የአስተሳሰብ አቅጣጫዎች ከተዳከሙ፤ በመላው አለም ለዘብተኛነት ሰፍኖ፣ መቻቻል ነግሶ፣ ግጭት በርዶ፣ ሰላምና ብልፅግና ይሰፍናል እያሉ በየዘመኑ ሲናገሩ የነበሩ ምሁራን ጥቂት አይደሉም። ይህንን እንደ ቂልነት የምትቆጥረው ታዋቂዋ ደራሲና ፈላስፋ አየን ራንድ፣ የለዘብተኛነት መንገድ  ስንዝር እንደማያራምድና እንደማያዛልቅ ትገልፃለች። ሊበራሊዝምና አብሮት የሚመጣ የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ፣ አለምን ከጨለማ አውጥቶ፣ በበሽታና በረሃብ ሲያልቅ፣ በጦርትነትና በግጭት ሲጨፋጨፍ የነበረውን የሰው ልጅ፣ ከድሮው በሶስት እጥፍ የሚበልጥ እድሜ እንዲኖረው፣ በመቶ እጥፍ የላቀ የኑሮ ምቾት እንዲያገኝ ማድረጉን ታስረዳለች። በተቃራኒው፣ ሃይማኖታዊ የፖለቲካ አስተሳሰብና ሕዝባዊነት፤ አለምን አጨልመው፣ ምድሪቱን በደም አጨቅይተው፣ የሰውን ልጅ በረሃብ አሰቃይተዋል። ያው፤ ትክክለኛ አስተሳሰብ ወደ ስኬት ሲያደርሰን፣ የተሳሳተ አስተሳሰብ ደግሞ ወደ ጥፋት እያንደረደረ እንጦሮጦስ ያወርደናል።
ጨርሶ ጎልቶ የሚታይ አስተሳሰብ ከሌለስ? ሦስቱ አስተሳሰቦች ሲዳከሙ ውጤቱ ምን ይሆናል? ራንድ እንዲህ ትላለች - ሰዎች ወደ ትክክለኛ አስተሳሰብ አቅጣጫቸውን ካልቀየሩ በቀር፣ ከሁለተኛው የአለም ጦርነት ወዲህ ባለው አያያዛቸው ከቀጠሉ መጨረሻቸው ጨለማ ነው። ከእንሰሳ ባልተሻለ ጭፍን ስሜት እየተቧደኑ እርስ በርስ መናጨትና መበላላት የበዛበት ዘግናኝ የጨለማ ዘመን ይፈጠራል። ሰዎች አስተሳሰባቸውን ካላስተካከሉ፤ የአለም አዝማሚያ ቀስ በቀስ ወደዚሁ ትርምስ እንደሚያመራ ትናገራለች ራንድ - ከ40 ዓመታት በፊት ባሳተመቻቸው መፃህፍቷ።
የዛሬ 18 ዓመት፣ “Clash of Civilizations” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መፅሐፍ የሚታወቁት ሳሙኤል ሃቲንግተን በበኩላቸው፤ ገናናዎቹ የፖለቲካ አስተሳሰቦች መክሰማቸውን በመግለፅ፣ ሰዎች ከኢኮኖሚ ስሌት ጨርሶ ባይለያዩም በጥንታዊ የባህል፣ የቋንቋ፣ የብሄር ብሄረሰብና የሃይማኖት ውርሶች እየተሰባሰቡ መቧደን እንደሚጀምሩ ይገልፃሉ። በሌላ አነጋገር፤ ዋና ዋናዎቹ አስተሳሰቦች፣ ከሃሳብ ትንታኔ ጋር ተራርቀው ወደ ስሜት ደረጃ ይወርዳሉ። የሊበራሊዝም አስተሳሰብ፣ ዋነኛ መሰረተ ሃሳቡ ይጠፋና፣ ከተራ የፖለቲካ ምርጫ እና ከኢኮኖሚ እድገት ጋር ብቻ የተቆራኘ የምኞት ስሜት ይሆናል። እናም፣ ሰዎች አፈና ወይም የኢኮኖሚ ችግር ሲበረታባቸው፤ እና ደግሞ የሌላው አገር ነፃነትና ብልፅግና በሳተላይት ቴሌቪዥንና በኢንተርኔት ሲያዩ፣ በቅሬታ ስሜት ተሞልተው ያምፃሉ። መፍትሄውን ግን አያውቁትም።
የግብፅና የሶሪያ፣ የሴንትራል አፍሪካና የኮንጎ ግጭቶችን ተመልከቱ። አዳሜ፣ አፈናና ችጋር እየመረረው፣ ነፃነትንና ብልፅግናን በመመኘት አደባባይ ይወጣል። መንግስት ይገለበጣል፤ ግን ተመልሶ ያው ነው። ችግር፣ በራሱ ጊዜ መፍትሄ አይወልድም። ያለ ትክክለኛ አስተሳሰብ፣ በስሜት ብቻ፣ ሁነኛ መፍትሄ አይገኝም። ግብፃውያን ምን ተረፋቸው? መሃመድ ሙርሲን የመሰለ የሃይማኖት አክራሪ ወይም ጄነራል አሲሲን የመሰለ በአገርና በሕዝብ ስም የሚፎክር አምባገነን! ሶሪያውያን ምን ተረፋቸው? በአንድ በኩል፣ በአገርና በሕዝብ ስም መንደሮችን በአውሮፕላን የሚደበድብ መንግስት፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሺዓ እና ሱኒ እያሉ ሰውን የሚጨፈጭፉ የሃይማኖት አክራሪዎች! ሌላ ያተረፉት ነገር የለም። ለነገሩ፤ ሃይማኖታዊ አስተሳሰብም ሆነ ሕዝባዊነት፣ ከስሜት የዘለለ ፋይዳ የላቸውም። ሃይማኖታዊ የፖለቲካ አስተሳሰብ ለአገሬው ወይም ለአለም ችግሮች፤ ለኢኮኖሚና ለፖለቲካ ቀውሶች መፍትሄ ያመጣል በሚል ትንታኔ ሰዎችን መማረክ በፍፁም አይቻልም፤ መፍትሄ እንደማያመጣ ታይቷልና። ነገር ግን፣ በሃይማኖት ሰበብ የሰዎችን ስሜት ማነሳሳትና በሃይማኖት አቧድኖ ማጋጨት ይቻላል። የሕዝባዊነት አስተሳሰብም እንዲሁ፣ እንደ ሃያኛው ክፍለዘመን በየአገሩ የፋሺዝምና የሶሻሊዝም አብዮት የማካሄድ ጉልበት የለውም። ግን፣ ሰዎችን በዘርና በብሄር ብሄረሰብ፣ በቋንቋና በቀዬ ሰበብ እያነሳሱና እያቧደኑ ማጋጨት ይቻላል። ይሄው ነው እየሆነ ያለው።
21ኛው ክፍለ ዘመን ከ20ኛው ክፍለዘመን በእጅጉ እንደሚለይ የሚገልፁት ሃቲንግተን፤ የብሄር ብሄረሰብና የቋንቋ፣ የሃይማኖትና የባህል ጉዳይ ዋነኛ የፖለቲካ ጉዳይ ይሆናሉ በማለት ያስረዳሉ። ከዚህም በመነሳት ነው፤ በ21ኛው ክፍለዘመን የሃይማኖት አክራሪነት፣ አሸባሪነትና ግጭት እንደሚበራከት የተነበዩት። አልተበራከተም የሚል የለም። በደፈናው፣ የአለምን አዝማሚያ ብቻ ሳይሆን፣ አንድ በአንድ የተለያዩ አገራት ምን አይነት ፈተና እንደሚጠብቃቸው ሃቲንግተን ተንብየዋል። ለምሳሌ፣ ሱዳን ከሰሜንና ከደቡብ ለሁለት እንደምትገነጠል ተናግረዋል። እንዳሉትም አልቀረም። ሃይማኖትና መንግስት ሊነጣጠሉ ይገባል በሚለው መርህ ለመቶ አመታት በተጓዘችው ቱርክ፣ የሃይማኖት ጉዳይ እንደገና እያቆጠቆጠ አገሪቱን እንደሚረብሻትም ሃቲንግተን ገልፀዋል። ይሄውና ሃይማኖትንና መንግስትን ለማዛመድ በሚፈልግ ፓርቲ አማካኝነት የአገሪቱ ቀውስ ተባብሷል። በአሜሪካና በአውሮፓ ላይ ከሚሰነዘረው የአሸባሪዎች ጥቃት በተጨማሪ፣ “የሱኒ ተከታይ፣ የሺዓ ተከታይ” በሚል ሰበብ ግጭቶች እየተፈጠሩ ሶሪያ፣ ኢራቅ፣ ሊባኖስና ሌሎች በርካታ አገራት ችግር ውስጥ እንደሚገቡም ምሁሩ ተንብየዋል። ደግሞም እየሆነ ነው። ከመካከለኛው ምስራቅ የሚወጡ የየእለቱን ዜና በመስማት ማረጋገጥ ይቻላል።
ሁሉንም ለመዘርዘር ያስቸግራል። ግን፣ አንድ ሌላ ትንበያ ልጨምርላችሁ። ዩክሬን፣ ከብሄር ብሄረሰብና ከቋንቋ፣ ከሃይማኖትና ከባህል ጋር በተያያዘ ውዝግብ ለሁለት ልትሰነጠቅ እንደምትችል ሃቲንግተን ሲገልፁ፣ ክሬሚያ እና ምስራቃዊ የዩክሬን አካባቢ ወደ ራሺያ ሊጠቃለሉ እንደሚችሉ ይጠቅሳሉ። ይህንን ያሉት ከዛሬ 18 አመት በፊት ነው።
በአጠቃላይ፤ ዋና ዋናዎቹ የፖለቲካ አስተሳሰቦች የተዳከሙበት የዛሬው ዘመን፣ በጭፍን ስሜቶችና በተቀጣጣይ አደጋዎች የተከበበ፤ ብዙዎችን ግራ የሚያጋባ ዘመን ሆኗል።
መናኛ ፖለቲከኞች የሃይማኖትና የብሄር ብሄረሰብን ጉዳይ እያራገቡ ችግር ሲፈጥሩ፤ አለም የሚይዘውና የሚለቀው ጠፍቶበታል። በዩክሬን፣ እዚህ ግባ የማይባሉ ሁለት ቡድኖች አገሬውን ሲቀውጡ፣ የዩክሬን አንጋፋ ፖለቲከኞች ምን አደረጉ? ቀልባቸው የተገፈፈ አጃቢ ከመሆን የዘለለ ነገር አላደረጉም። አለምን መቶ ጊዜ የሚያጠፋ የኒኩሊዬር መሳሪያ የታጠቁት የራሺያ መሪዎችንም እዩዋቸው - በቁራሽ መሬት ነው የሚደነፉት - ቁምነገር ይመስል። መደገፍም ሆነ መቃወም አቅቷት “የሚመለከታቸው ወገኖች በውይይት ችግራቸውን ይፍቱ” ብለው ከሚንተባተቡት የቻይና ገዢዎችም የጠራ ነገር አታገኙም። ሌላው ይቅርና በስልጣኔ ደህና የተራመዱት ምዕራባዊያንስ ምን ፈየዱ? የዩክሬን ቀውስና የራሺያ ድርጊት፣ በአውሮፓ ትልቁ የ21ኛው ክፍለዘመን ቀውስ እንደሆነ የእንግሊዙ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተናግረዋል።
ግን፤ የአሜሪካና የአውሮፓ ባለስልጣናት ወዲህና ወዲያ ከመወራጨት ሌላ ምን አደረጉ? ቱ ራራሺያን አደብ ለማስገዛት የሚያስችል የአስተሳሰብ ፅናት ጠፍቶባቸው፤ የሚያደርጉትን ብቻ ሳይሆን የሚናገሩትን አጥተዋል። ከሁለት መልከ ጥፉ (ከራሺያና ከዩክሬን ‘ፋሺሽት’ ቡድኖች) አንዱን መምረጥ የቸገራቸው አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማትም፣ ጥርት ያለ ነገር አልያዙም። በአጠቃላይ፤ ዓለም የሶሪያን እልቂት በሩቁ ከመመልከት ውጭ ምንም ማድረግ እንዳልቻለው ሁሉ፤ በዩክሬን ጉዳይ ላይም እንዲሁ መያዣና መጨበጫ አላገኘለትም። መደናበር ብቻ!
ታዲያ የኢትዮጵያ መንግስትና ኢህአዴግ፤ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ ነገሩ ተደበላልቆባቸው ግራ ቢጋቡ ምን ይገርማል? እነሱን በጣም የሚያሳስባቸው፣ መንግስት በሕዝብ አመፅ ይወርዳል መባሉ ነው። ይሄ ተራ ነገር ነው። አሁን አለምን እየናጣት ያለው ቀውስ ጋር ሲነፃፀር፣ የአንድ መንግስት መውደቁና አለመውደቅ ኢምንት ነገር ነው። እጅግ አሳሳቢው ነገር፤ በየጊዜው የሚፈጠሩ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ቀውሶችን ለመፍታት የሚያስችል ጠንካራ አስተሳሰብ አለመኖሩ ነው። ከአመፅ አዙሪት የሚገላግልና ለዘላቂ የስልጣኔ ለውጥ የሚበጅ ጠንካራ አስተሳሰብ በአለማችን አለመኖሩ ነው። ደረጃውና መጠኑ ይለያይ እንጂ፤ በአለማችን የሰፈኑ ስርዓቶች በአብዛኛው በኢኮኖሚም ሆነ በፖለቲካ መስክ ቅሬታዎችና ችግሮች እየተደራረቡ እንዲከማቹ የሚያደርጉ ናቸው። ቅሬታና ችግር ተከማችቶ ምሬት ሲበዛ፣ አደባባይ ወጥቶ ከመጮህ ውጭ፣ ግልፅና ጤናማ መፍትሄ የለም። የአስተሳሰብ ኦና ሲፈጠር፤ በቦታው በብሄር ብሄረሰብና በቋንቋ፣ እንዲሁም በሃይማኖት ሰበብ የሚራገቡ መርዘኛ ስሜቶችን ለመከላከል የሚያስችል የስልጣኔ አስተሳሰብ የለም። መውጪያ የሌለው የትርምስ አዙሪት ነው የሚሆነው። ይሄ ነው ሊያሳስበን የሚገባው።
ያለ ትክክለኛ አስተሳሰብ፣ አስተማማኝ መፍትሄ ማግኘት ባይቻልም፤ ለጊዜው ጠንቀቅ ማለት ጥሩ ነው። አንደኛ፤ በዋጋ ንረትና በታክስ ጫና፣ አልያም በአላስፈላጊ የሕግ ገደቦችና የቢሮክራሲ ቁጥጥሮች ኢኮኖሚን ላለማዳከም በእጅጉ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። አለበለዚያ መዘዙን አንችለውም። ሁለተኛ፣ ጓዳና አደባባዩን ካልተቆጣጠርኩ ብሎ ዜጎችን መውጪያ መግቢያ ከማሳጣት፣ እንዲሁም በትንሽ በትልቁ ንትርክና ፍጥጫ ከመፍጠር ቆጠብ ብሎ፤ በፖለቲካውም ሆነ በፍትህ መስኮች ያለ ማቋረጥ የመሻሻል ምልክቶች እንዲታዩ መትጋት ያስፈልጋል። ሶስተኛ፡ የብሔር ብሔረሰብና የቋንቋ ጉዳዮችን ከማራገብ መቆጠብ ነው። አራተኛ፡ የሐይማኖት ጉዳይ ከፖለቲካ ጋር እንዳይቆራኝ በጥንቃቄ መስራት ያስፈልጋል።    


      12 ዳኞች በስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነት ተነስተዋል

    ለበርካታ ዓመታት የደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ታረቀኝ አበራ አይዶ ከኃላፊነታቸው የተነሱ ሲሆን ምክትላቸው የነበሩት አቶ ሙሉጌታ አጎ፤ የጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት ሆነው ተሹመዋል፡፡ በክልሉ ከወረዳ እስከ ጠቅላይ ፍ/ቤት ሲያገለግሉ የነበሩ 12 ዳኞች፤ በስነ-ምግባር ጉድለት ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አቶ ታረቀኝ ለበርካታ ዓመታት ጠቅላይ ፍ/ቤቱን በመሩበት ወቅት ባሳዩት የሥራ ክፍተትና የስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነታቸው እንደተነሱ ምንጮቻችን ቢጠቁሙም፣ የክልሉ የጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አጎ ሃሰት ነው ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ “የጠቅላይ ፍ/ቤቱ ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ታረቀኝ፤ ሶስተኛ ዲግሪያቸውን ለመስራት ወደ ኔዘርላንድ ለመሄድ ባመለከቱት መሰረት፣ተፈቅዶላቸው መሄዳቸውን ነው የማውቀው” ብለዋል፡፡
ከክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት ጀምሮ በተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች በዳኝነት ሙያ ሲያገለግሉ የነበሩ 12 ዳኞች በስነ-ምግባር ጉድለት ከኃላፊነት መነሳታቸውን በተመለከተ የጠየቅናቸው አቶ ሙሉጌታ አጎ፤ ዳኞቹ ባሳዩት የስራ ክፍተትና የስነ-ምግባር ጉድለት በዳኞች አስተዳደር ጉባኤ ተወስኖባቸው ከሃላፊነት እንደተነሱ አስረድተዋል፡፡
ቀደም ሲል “ቡታጅራ ላይ በድንጋይና በዱላ ተደብድበው የሞቱት ኢ/ር ጀሚል ሀሰን ቤተሰቦች፤ አቶ ታረቀኝ አበራ ባስቻሉት የይግባኝ ችሎት፣“የገዳዮቹን ፍርድ ያለአግባብ ቀንሰዋል” በሚል ቅሬታ ማቅረባቸውን መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን ጉዳዩ እንደገና በሰበር ሰሚ ችሎት ታይቶ፣ በወንጀለኞቹ ላይ ከፍተኛ ቅጣት ተወስኖባቸዋል፡፡  

Published in ዜና

የሎሬትነት ማዕረግ ተሰጥቷቸዋል

         ኢትዮጵያዊቷ ተመራማሪ ዶ/ር ሰገነት ቀለሙ፣ በተለያዩ የምርምር መስኮች የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ምርጥ የአለማችን ሴት ሳይንቲስቶች በየአመቱ የሚሰጠው የሎሪያል ፋውንዴሽንና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) አለማቀፍ የሴት ሳይንቲስቶች ሽልማት የ2014 ተሸላሚ ሆኑ፡፡
ተቀማጭነቱን  በናይሮቢ ኬኒያ ያደረገው ‘ኢንተርናሽናል ሴንተር ፎር ኢንሴክት ፊዚዮሎጂ ኤንድ ኢኮሎጂ’ የተባለ አለማቀፍ ተቋም ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ዶ/ር ሰገነት ቀለሙ፤ አፍሪካንና የአረቡን አለም በመወከል ተሸላሚ መሆናቸውን ሲስኮን ሚዲያ የተባለው የፈረንሳይ ድረ ገጽ ዘግቧል፡፡  ዶ/ር ሰገነት ለ16ኛው የሎሪያል ፋውንዴሽንና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) አለማቀፍ የሴት ሳይንቲስቶች ሽልማት የበቁት፣ በእጽዋት ምርምር ዘርፍ ባደረጉት ጥናት በተለይ አነስተኛ ይዞታ ባላቸው አርሶአደሮች ዘንድ ስነ-ምህዳርን የማይጎዳ የሰብል አመራረት ዘዴ ለማስፋፋት ሁነኛ መፍትሄ የሚለግስ ተጨባጭ ውጤት በማግኘታቸው እንደሆነ ተነግሯል፡፡
ሴቶች በሳይንስ ዘርፍ ለሚያደርጉት ምርምር እውቅና የመስጠትና የማበረታታት ዓላማ ያለው ይህ አመታዊ አለማቀፍ ሽልማት፤ ዘንድሮም ከተለያዩ አህጉራት ለተመረጡና በተለያዩ የምርምር ዘርፎች የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አምስት የአለማችን ምርጥ ሴት ሳይንቲስቶች ባለፈው ረቡዕ ምሽት በፈረንሳይ ፓሪስ በተከናወነ ደማቅ ስነስርአት ላይ የተበረከተ ሲሆን ለተሸላሚዎችም የሎሬትነት ማዕረግ ተሰጥቷል።
የዘንድሮዎቹ አምስት ተሸላሚ ሴቶች፤ ልዩ ተሰጥኦ የታደሉ፣ በሙያቸው የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በቁርጠኝነትና በትጋት የሰሩና አሁንም ድረስ በአብዛኛው ወንዶች በተያዘው የሳይንስና ምርምር መስክ የላቀ ውጤት ማስመዝገብ የቻሉ በመሆናቸው ለሽልማቱ መመረጣቸውንም ዘገባው ያመለክታል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂነት ያተረፉ ሳይንቲስቶች በሰጡት ጥቆማ መሰረት፣ ራሱን የቻለ ገምጋሚ ቡድን ተቋቁሞ በተደጋጋሚ ዙር ዕጩ ተወዳዳሪዎችን ከመዘነ በኋላ በሰጠው ውጤት ነው፣ አምስቱ ተሸላሚዎች ለመጨረሻው ዙር ደርሰው ለሽልማት የበቁት፡፡
ዶ/ር ሰገነት ቀለሙ ትምህርታቸውን በአሜሪካ ካጠናቀቁ በኋላ፣ በኮሎምቢያ ሲሰሩ መቆየታቸውንና ወደ አፍሪካ ተመልሰው፣ ኢንተርናሽናል ሴንተር ፎር ኢንሴክት ፊዚዮሎጂ ኤንድ ኢኮሎጂ በተባለውና ዘርፈ ብዙ ተጨባጭ ተግባራትን እያከናወነ በሚገኘው አለማቀፍ የሳይንሳዊ ምርምር ተቋም ውስጥ በሃላፊነትና በምርምር ዘርፍ በመስራት ላይ እንደሚገኙ ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡
ላለፉት 16 አመታት በየአመቱ ሲሰጥ የቆየውን ይህን አለማቀፍ ሽልማት፣ ከ2ሺህ በላይ የሚሆኑ የተለያዩ አገራት ሴት ሳይንቲስቶች የተቀበሉት ሲሆን፣ በዘንድሮው አመትም ከኢትዮጵያዊቷ ተመራማሪ ከዶ/ር ሰገነት ቀለሙ በተጨማሪ የአሜሪካ፣ የአርጀንቲናና የጃፓን ዜግነቶች ያሏቸው አራት ሴት ሳይንቲስቶች ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡

Published in ዜና

           በአሜሪካ አገር ‹‹በድር ኢትዮጵያ›› የተሰኘውን የሙስሊም ማህበር የሚመሩ ምሁራንና ታዋቂ ሰዎች፤ የታሰሩ ሙስሊሞችን ከመንግስት ጋር ለማሸማገል በኢትዮጵያ መንግስት ፈቃድ ሰሞኑን አዲስ አበባ መግባታቸው ተነገረ።
በአወሊያ ትምህርት ቤት ሰበብ የተቀሰቀሰው ውዝግብ ቀስ በቀስ እየተካረረ፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላላ ጉባኤ ምርጫም የመወዛገቢያ ነጥብ ወደመሆን እንደተሸጋገረ የሚታወስ ሲሆን፤ በ2004 ዓ.ም በርካታ የተቃውሞ ሰልፎች ከተካሄዱ በኋላ ነው፤ በሐምሌ ወር ሃያ ዘጠኝ ሰዎች ታስረው ክስ የተመሰረተባቸው፡፡ ታህሳስ 2006ዓ.ም. አስሩ ታሳሪዎች የሚያስከስስ ጥፋት የለባቸውም ተብለው በፍ/ቤት ቢለቀቁም የአስራ ዘጠኝ ታሳሪዎች ክስ በፍ/ቤት እየታየ መሆኑ ይታወቃል፡፡
የሙስሊሙ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ በሚል ስያሜ ሲንቀሳቀሱ የነበሩት ታሳሪዎች፤ “የአወሊያ ት/ቤት ራሱን ችሎ መንቀሳቀስ አለበት፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ በተጽእኖ ስር የተከናወነ ነው” በማለት ተቃውሞ ሲያሰሙ ቆይተዋል፡፡ የአወሊያ ት/ቤትን ተገን በማድረግ አክራሪነትን ለማስፋፋት እንቅስቃሴ ሲደረግ ነበር የሚለው መንግስት በበኩሉ፤ የእስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ም/ቤት ምርጫ በአግባቡ አልተከናወነም የሚለው ተቃውሞ፤ ግጭት ለመቀስቀስ ታስቦ የተዘጋጀ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ይላል፡፡  
በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት እየታየ ባለው የክስ ሂደት አስራ ዘጠኙ ተከሳሾች በአቃቤ ህግ ለቀረበላቸው የክስ ማስረጃ መከላከያ እንዲያቀርቡ የታዘዙ ሲሆን ከሚቀጥለው ማክሰኞ ጀምሮ ለ15 ቀናት በተከታታይ መከላከያ ያሰማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በዚህ መሃል ነው፤ በሽምግልና ታሳሪዎቹን ሊያስፈቱ ይችላሉ የተባሉ ታዋቂ ሙስሊሞች ሰሞኑን ከአሜሪካ የመጡት፡፡
‹‹በድር ኢትዮጵያ›› የተሰኘው ማህበር መሪዎችና አባላት የሆኑት እነዚሁ ሙስሊም ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች አዲስ አበባ የገቡት በመንግስት ፈቃድ እንደሆነ የገለፁልን ምንጮች፤ ታሳሪዎችን ያነጋግራሉ ብለዋል፡፡

Published in ዜና

         ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ እየገነባች ያለችው የታላቁ የህዳሴ ግድብ አፄ ምኒልክ በ1902 ከእንግሊዝ ጋር የተፈራረሙትን ውል የሚጥስ ነው ሲል የግብፅ መንግስት ቃል አቀባይ ቢሮ መግለጫ ያወጣ ሲሆን አፄ ምኒልክ ውሉን ሲፈራረሙ የውሀውን ፍሰት አናቆምም እንጂ አንጠቀምበትም በሚል እንዳልተስማሙ ሰነዶች ያመለክታሉ፡፡
 የቃል አቀባይ ቢሮው ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ፤ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በአባይ ላይ እየገነባች ያለችው ግድብ በ1902 በእንግሊዝ እና በአፄ ምኒልክ የተፈረመውን የሚጥስ ነው፣ አፄ ምኒልክ የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ተብለው ስልጣን ላይ ከወጡ በኋላ ከእንግሊዝ ጋር በተፈራረሙት ውል መሰረት ከእንግሊዝ እና ሱዳን ፈቃድ ውጪ  ኢትዮጵያ በአባይ፣ በጣና ሀይቅ እና በሶባት ላይ ምንም አይነት ግንባታ እንደማታደርግ እና ለመንባት የሚሞክሩ ወገኖችንም እንደምትከለክል ተስማምታለች፤
ስለዚህ የአሁኑ ግንባታ ስምምነቱን ይጥሳል ብሏል፡፡ በአለም አቀፍ ህግ የውሀ ባለሙያ የሆኑት አቶ እምሩ ታምራት ጉዳዩን አስመልክተው ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ በመጀመሪያ ደረጃ ግብፅ የ1902 ስምምነት አካል ስላልሆነች፤ ይህን ስምምነት በመከራከሪያ ማንሳት አትትችልም፤ ሌላው የስምምነቱ  የአማርኛ ትርጓሜ  “ኢትዮጵያ ውሃውን ሙሉ በሙሉ የሚደፍን ስራ አትሰራም ይላል እንጂ ጥቅም ላይ አታውል” ብላ አልተስማማችም፡፡

Published in ዜና

          የቢጂአይ ኢትዮጵያ እህት ኩባንያ ካስቴል ወይን ጠጅ ፋብሪካ (ካስቴል ዋይነሪ) በኢትዮጵያ ያመረታቸውን ሰባት ዓይነት የወይን ጠጅ መጠጦች ዛሬ በዝዋይ ያስመርቃል፡፡
የድርጅቱ የሽያጭና የገበያ ማናጀር ወ/ሪት ዓለምፀሐይ በቀለ በተለይ ለአዲስ አድማስ እንደገለጸችው፤ ባለፈው የፈረንጆች ዓመት ካስቴል ዋይነሪ፣ ከእርሻው የለቀመውን የወይን ምርት ለመጀመሪያ ጊዜ በመጥመቅ 1.1 ሚሊዮን ጠርሙስ ወይን ጠጅ አምርቷል፡፡
የቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በ2007 ዓ.ም በፈረንሳይና በሰሜን አፍሪካ በወይን እርሻና መጠጥ ታዋቂ፣ በኢትዮጵያ ደግሞ የቢጂአይ ኢትዮጵያና የካስትል ቢራ ፋብሪካዎች ባለቤት የሆኑትን ፈረንሳዊ ሚ/ር ካስቴልን በኢትዮጵያም በወይን ጠጅ ዘርፍ እንዲሰማሩ እንደጋበዟቸውና ባለሀብቱም በጠቅላይ ሚ/ር ሐሳብ ስለተስማሙ ፕሮጀክት ተቀርፆ ወደ ሥራ መገባቱን ማናጀሯ ገልጻለች፡፡
በቀጣዩ ዓመት ከፈረንሳይ የመጡ የወይን እርሻና ጠመቃ ባለሙያዎች፣ ከተመለከቷቸው የተለያዩ ቦታዎች ዝዋይ ለወይን እርሻ የተሻለች መሆኗን በማመናቸው፣ 498 ሄክታር መሬት በሊዝ በመውሰድ፣ ከፈረንሳይ የመጡ የተለያዩ ምርጥ የወይን ዘሮች መተከላቸውንና የወይን ጠጅ ማምረቻ ፋብሪካም እዚያው መቋቋሙ ታውቋል፡፡
ዓለም አቀፍ ቫራይቲ የተባሉት ምርጥ የወይን ዝርያዎች ካቤርኔ ሶቪኞ፣ ሲራ እና ሜርሎ የተባሉት የቀይ ወይን ዝርያዎች ሲሆኑ የነጩ ወይን ደግሞ ሻርዶኔ የተባለ ዝርያ መሆኑ ታውቋል፡፡ የወይን ጠጆቹ መጠሪያ አኬሽያ (ግራር) እና ሪፍት ቫሊ (ስምጥ ሸለቆ) ሲሆን በአኬሽያ ስም ሚዲየም ስዊት ሬድ፣ ሚዲየም ስዊት ኋይት እና ድራይ ሬድ ወይን ጠጆች ይመረታሉ፡፡ በደረጃው ከፍ ያለውና በሪፍት ቫሊ ስም የሚጠመቁ ካቤርኔ ሶቪኞ፣ ሲራ፣ ሜርሎ እና ሻርዶኔ ሲባሉ፣ በአጠቃላይ ሰባት ዓይነት ወይን ጠጆች እንደሚመረቱ ማናጀሯ አስረድታለች።   
ከወይን ጠጆቹ ምርት ግማሹ አገር ውስጥ፣ የተቀረው ግማሽ ደግሞ ለውጭ ገበያ የሚቀርብ ነው፡፡ ከትላልቆቹ የውጭ ገበያ አሜሪካና ቻይና ዋናዎቹ ሲሆኑ ከአውሮፓ ፈረንሳይ፣ ጣሊያን፣… ከጎረቤት አገሮች ወደ ኬንያ፣ ዩጋንዳ፣ ጅቡቲ፣ ታንዛኒያ፣ ለመላክ ታቅዷል፡፡
የወይን ተክል ምርት የሚሰጠው በሦስት ዓመት ነው፡፡ በ2011 እና በቀጣዩ ዓመት ምርት ቢሰበስቡም መጠኑ በቂ አልነበረም፡፡ ነገር ግን ጠምቀው፣ ጥራቱ ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ መሆኑን አረጋግጠዋል። “ያለፈው ዓመት ምርት ለምንፈልገው ጠመቃ በቂ ስለሆነ ለመጀመሪያ ጊዜ 1.1 ሚሊዮን (አንድ ሚሊዮን አንድ መቶ ሺ) ጠርሙስ ወይን ጠጅ አምርተን ዛሬ እያስመረቅን ነው፡፡ ወይን ጠጁ ገበያ ላይ የሚውለው ግን በጋው ውስጥ ነው” ብላለች ወ/ሪት ዓለምፀሐይ በቀለ፡፡
ለወይን እርሻው፣ ለፋብሪካው ተከላ፣ ለጠመቃ፣ … ብዙ ካፒታል ወጪ ሆኗል፡፡ በአጠቃላይ 25 ሚሊዮን ዩሮ (ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ) መውጣቱን የጠቀሰችው ዓለምፀሐይ፤ ለ250 ቋሚና ከ500 ለሚበልጡ ጊዜያዊ ሰራተኞች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግራለች፡፡  
ካስቴል ወይን ጠጅ ፋብሪካ ለብዙ ዓመታት በመንግሥት ይዞታነት የተለያዩ የወይን መጠጦችን ሲያመርት ቆይቶ ወደ ግል ከዞረው አዋሽ ወይን ጠጅ ፋብሪካ ቀጥሎ በኢትዮጵያ የወይን መጠጦች በማምረት ሁለተኛው የግል ድርጅት መሆኑ ታውቋል፡፡

Published in ዜና

‹‹ማኅበሩን የማዳከምና የማፍረስ ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ ተልእኮ ነው››
/አባላትና ደጋፊዎ

   ማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀውን የአስተዳደር መዋቅር ተቆጣጥሮ ለፖለቲካ ጥቅም ሊያውል ይፈልጋል በማለት የሚቃወሙ የአዲስ አበባ የደብር አስተዳዳሪዎች ዛሬ ስብሰባ የሚያካሂዱ ሲሆን፤ የማህበረ ቅዱሳን አባላት በበኩላቸው ዘመቻ ተከፍቶብናል ይላሉ፡፡
የአዲስ አበባ አድባራት አስተዳዳሪዎች ማኅበሩ ሀብቱንና ንብረቱን እንዲያስረክብ ሊያስገድዱት ተዘጋጅተዋል ይላሉ የማህበሩ አባላት፡፡
ማኅበሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅር በመጣስ እንደሚንቀሳቀስ የሚጠቅሱት አስተዳዳሪዎቹ በበኩላቸው፤ ገንዘቡንና ንብረቱን የሚያንቀሳቅሰው ከጠቅላይ ቤተ ክህነት አሰራር ውጭ ስለሆነ   የሀብቱና ንብረቱ መጠን አይታወቅም ይላሉ፡፡
‹‹ማኅበሩ አቅጣጫውን የሳተ የኦርቶዶክስ ሰለፊ ነው›› በማለት ማኅበረ ቅዱሳንን የሚፈርጁ አስተዳዳሪዎች እንዳሉ የሚናገሩት የማህበሩ አባላት፤ ዘመቻ እንደተከፈተባቸው የሚገልፁ ሲሆን፤ የአድባራት አስተዳዳሪዎች በበኩላቸው ማህበሩ በቤተክርስቲያን ላይ ዘመቻ ከፍቷል ይላሉ፡፡ ማኅበሩ ለሀገረ ስብከቱ የሠራው የመዋቅር፣ የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት፣ ማኅበሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅር በመቆጣጠርና በፖለቲካ ከቤተ መንግሥቱ አጣምሮ በመያዝ ዓላማውን ለማራመድ ያዘጋጀው ነው ሲሉ የሚቃወሙ አስተዳዳሪዎች እንዳሉ ታውቋል፡፡  
‹‹ሕግ የሌለውና ለሕግ የማይታዘዘው ማኅበረ ቅዱሳን ለእኛ ሕግ ሊያወጣልን አይችልም›› የሚሉት አስተዳዳሪዎቹ፤ ከየአድባራቱ አምስት አምስት ሠራተኞች ይገኙበታል በተባለው በዛሬው ስብሰባቸው፤ ማኅበሩ ሕግ ወጥቶለት ወደ መዋቅር እንዲገባ በመግለጫቸው እንደሚጠይቁ የማኅበሩ አባላት በበኩላቸው፣ ማኅበሩ የሚመራው በ1994 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ለሦስተኛ ጊዜ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደርያ ደንብ ነው በማለት ‹‹ሕግ የሌለው ሕገ ወጥ ነው›› መባሉን ተቃውመዋል፡፡
ማኅበሩ በየዓመቱ ፈቃድ ባለውና ብቃቱ በተመሰከረለት የውጭ ኦዲተር፣ የፋይናንስ እንቅስቃሴውን እያስመረመረ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሪፖርት እንደሚያቀርብ አባላቱ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

“አስር ሳንቲም እንኳን ከአርሶ አደር ገንዘብ አልተሰበሰበም” የወረዳው ፖሊስ
        በደቡብ ክልል በጋሞ ጎፋ ዞን በቁጫ ወረዳ የሚገኙ አርሶ አደሮች የማንነት ጥያቄ በማንሳታችን በወረዳው ኃላፊዎችና ታጣቂዎች በቅጣት ስም ገንዘብ እየተዘረፍን ነው ሲሉ አማረሩ፡፡ እስካሁን ከዘጠኝ ቀበሌዎች ብቻ ከ170 ሺህ ብር በላይ በወረዳው ኃላፊዎችና ታጣቂዎች መሰብሰቡን አርሶ አደሮች ተናግረዋል፡፡ በቁጫ ወረዳ የሰላም በር ፖሊስ ፅ/ቤት እስረኞች አስተዳደር የሆኑት ኮማንደር አሰፋ ታፈሰ በበኩላቸው፤ መንግስት ሳያውቀው ያለ አግባብ ከአርሶ አደሩ የሚሰበሰብ አስር ሳንቲም የለም ሲሉ አስተባብለዋል፡፡
ቅሬታ አቅራቢዎች ግን በቅጣት ሰበብ ገንዘባቸውን ተዘርፈዋል ያሏቸውን የ273 አርሶ አደሮች ስም ዝርዝር፣ የተወሰደባቸውን የገንዘብ መጠንና ገንዘቡን ሰብስበዋል የተባሉትን የቀበሌ አስተዳዳሪዎችና ታጣቂዎችን ስም ዝርዝር መያዛቸውን ይናገራሉ፡፡ “ይህ ሁሉ በደልና ግፍ የሚደርስብን ማንነታችን ይከበር በሚል ጥያቄ በማንሳታችን ነው” ብለዋል፡፡ ለጥያቄያችን ምላሽ ለማግኘት ከዞን እስከ ክልል እንዲሁም እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩና የፌዴሬሽን ም/ቤት ድረስ አቤት ብንልም እስካሁን ሰሚ አጥተናል ሉት የቅሬታ አቅራቢዎች ተወካዮች፤ይባስ ብሎ እንግልት፣ ግርፋት፣ እስራትና በቅጣት ሰበብ የገንዘብ ዝርፊያ እየተፈፀመብን ነው ሲሉ አማረዋል፡፡
“ገንዘቡን ከአርሶ አደሩ የሚሰበስቡት የማንነት ጥያቄ አንስተሃል፣ መከፋፈልንም ፈጥረሃል፣ስለዚህ ትታሰራለህ ወይስ ገንዘብ ትቀጣለህ በሚል ማስፈራሪያ ነው” ያለው የአካባቢው ወጣት ነዋሪ፣ ህዝቡ እስር ቤት መግባትና መጉላላት ስለማይፈልግ ለፍቶ የቋጠረውን ገንዘብ እያስረከበ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ይሁን እንጂ የቀበሌው ኃላፊዎች ከፖሊስ ጋር እየሄዱ ያለደረሰኝ የሚሰበስቡት ገንዘብ ለምን ጉዳይ እንደሚውል እንደማያውቁ የገለፀው ይኸው ወጣት፤“ገንዘቡንም አንሰጥም፣ አንታሰርምም” ያሉ ነዋሪዎች ከአካባቢያቸው ሸሽተው ወደ አዲስ አበባና ሌሎች ከተሞች ለመሸሽና ለመሰደድ ተገደዋል ብሏል፡፡  ከቁጫ ሸሽተው ወደ አዲስ አበባ የመጡ ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ የአገር ሽማግሌ እንደሚሉት፤ የቀበሌው ሹሞችና ታጣቂዎች ገንዘብ ሲሰበስቡ ሻል ያለውን ሰው ብዙ ብር የሚጠይቁ ሲሆን  ከተሰበሰበው ገንዘብ እስካሁን ዝቅተኛው 300 ብር፣ ከፍተኛው አስር ሺህ ብር  ነው፡፡ ይህ ሁሉ እንግልት እንዲቆም፣ መንግስት ጣልቃ ገብቶ አንድ እርምጃ እንዲወስድና የቁጫ ህዝብ የማንነት ጥያቄ እንዲመለስ የአገር ሽማግሌው አሳስበዋል፡፡
ለደህንነታቸው ሲሉ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉና ከመኖርያቸው ሸሽተው እንደሄዱ የተናገሩ የቁጫ ተወላጅ፤“በሽምግልና ዕድሜ ሰርቼ ከቋጠርኩት ላይ 10 ሺህ ብር ተወስዶብኛል፤በዚያ ላይ ከስራ ተስተጓጉዬ ወላይታ ተደብቄያለሁ” ሲሉ አማረዋል፡፡
ታህሳስ 25 ቀን 2006 ዓ.ም የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት አቶ ኡሞድ ኡቦንግ ለክልሉ መስተዳደር በፃፉት ደብዳቤ፤ በ23/04/2006 “በቁጫ ወረዳ አመራሮች በደል እና አፈና ደርሶብናል” በሚል ከቁጫ ህብረተሰብ አቤቱታ እንደደረሳቸው ከገለፁ በኋላ፣ “የቁጫ ማህበረሰብ ዘላቂ መፍትሄ ሊያገኝ የሚችለው በክልሉ መንግስት ነው፤በመሆኑም የችግሩን ግዝፈት በማየት የቁጫ ህዝብ የማንነት ጥያቄ እልባት እንዲያገኝ፣ እየደረሰባቸው ያለው ድብደባና እንግልት በክልሉ መንግስት በኩል ታይቶ ተገቢው እርምጃ እንዲወሰድ” በሚል የቁጫን ህዝብ የአቤቱታ ደብዳቤ አያይዘው እንደላኩ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ጠቁመው ይሁን እንጂ በክልሉ መንግስት በኩል እስካሁን ምንም ምላሽ አላገኘንም ብለዋል።  ከማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ እስካሁን በአርባ ምንጭ ማረሚያ ቤት ከ280 በላይ ሰዎች በእስር ላይ እንደሚገኙ፣ሌሎች ተምረው በተለያዩ አካባቢዎች የሚኖሩ 31 ያህል የቁጫ ተወላጆች የወረዳውን ኃላፊዎች ኢ-ሰብአዊ ድርጊት በማውገዛቸው “ህገመንግስቱን በሃይል የመናድ ሙከራ አድርገዋል” በሚል ክስ ቀርቦባቸው በፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት እየተከራከሩ እንደሆነ ገልፀው፣ ይህ ሁሉ እንግልት እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ “አሁንም ቢሆን ቁጫ ቁጫ እንጂ ጋሞ አይደለም፣ፍላጎታችን በተገቢው መንገድ እስኪመለስ ጥያቄያችን ይቀጥላል” ብለዋል ቅሬታ አቅራቢዎቹ፡፡ የቁጫ ወረዳ ፖሊስ ጽ/ቤት የእስረኛ አስተዳደር ኃላፊ ኮማንደር ታደሰ ታፈሰ በበኩላቸው፤በወረዳው በውንብድና፣ በቤት ቃጠሎ፣ የመኪና መንገድ በመቁረጥ እና ያልተፈቀደ ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ተከሰው፣ የሰውና የሰነድ ማስረጃ ቀርቦባቸው የታሰሩ፣ በቁም እስር ላይ ያሉና በገንዘብ የተቀጡ ሰዎች መኖራቸውን አምነው፣ የማንነት ጥያቄ በማንሳቱ የታሰረና ገንዘብ የተወሰደበት ሰው እንደሌለ ተናግረዋል፡፡
ለልማት ስራ ከአካባቢው አርሶ አደር ገንዘብ ይሰበሰብ እንደሆነ የጠየቅናቸው ኮማንደሩ፤ “መንግስት የት ሄዶ ነው ከህዝብ ገንዘብ የምንሰበስበው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የአርባ ምንጭ ማረሚያና ማነፅ ተቋም ኃላፊ ኮማንደር አበበ ሀብቴን በዞኑ ማረሚያ ቤት ስለሚገኙ እስረኞች ሁኔታ ጥያቄ አቅርበንላቸው፤  በስልክ መረጃ ለመስጠት እንደሚቸገሩ ገልፀው፤“አርባ ምንጭ ድረስ በመምጣት ማጣራት ይኖርባችኋል” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

Published in ዜና

            ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ማታ ላይ፤ አንድ ሰው ወደ አንድ ቡና ቤት፣ አንድ አሣማ ይዞ ይገባል። የቡና ቤቱ የመጠጥ ኃላፊ፤ በጣም ጠንቃቃና የጉጉት-ዐይን ያለው ዓይነት ሰው ነው፡፡ ሰውዬው ይዞት የመጣው አሣማ አንድ እግሩ በእንጨት የተጠገነ ነው፡፡ ይህንን የመጠጥ ኃላፊው አይቷል፡፡
ወደ እንግዳው ሄዶ እንዲህ አለው፡-
“ይህ አሣማ ምን ሆኖ ነው አንድ እግሩ እንጨት የሆነው?”
ሰውዬውም፣
“አንድ ቢራ ከሰጠኸኝ፤ ስለዚህ ልዩ ባህሪ ስላለው አሣማ ታሪክ እነግርሃለሁ!” አለው፡፡
የመጠጥ ኃላፊው፤ “መልካም፡፡ ጥሩ ታሪክ የሚወጣው ስለመሰለኝ፤ እንካ አንድ ቢራና ታሪኩን ትነግረኛለህ” አለና አንድ ቢራ አቀረበለት፡፡
“ስለዚህ ተዓምረኛ አሣማ ልንገርህ” አለና ጀመረ ያ ሰውዬ፡፡ “በጣም ልዩ አሣማ ነው፡፡ አንድ ማታ፤ ከአንድ ዓመት በፊት ገደማ፣ ድንገት ቤቴ በእሳት ተያያዘ፡፡ ይሄኔ ያ አሣማ ከበረቱ በርግዶ ወጣና፣ ወደ ቤቴ መጣ፡፡ ሁለቱን ልጆቼን ተሸክሞ ይዟቸው ወጣ፡፡ እኔና ሚስቴንም ሰላም ወደሆነው ሥፍራ ይዞን ወጣ! ስለዚህ፤ ቤተሰቤንና ህይወቴን አዳነልኝ ማለት ነው!!”     
ያ የመጠጥ ክፍል ኃላፊም፤ በታሪኩ ተገርሞ፣
“በጣም የሚገርም ጉድ ነው፡፡ ግን ለምን አንድ እግሩ እንጨት ሆነ?” አለው ደገመና፡፡  ሰውዬውም፤
“አንድ ቢራ ከጋበዝከኝ የዚህን ተዓምረኛ አሣማ ታሪክ እነግርሃለሁ” ይለዋል፡፡ የመጠጥ ክፍል ኃላፊው ምሥጢሩን ለማወቅ በጣም ጓጓ፡፡ ካረግኸው ጥሩ፤ ብሎ አንድ ቢራ ጨመረለት፡፡
ሰውዬውም፤
“ከእኔ ቤት ጀርባ አንድ ሐይቅ አለ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን፤ ጀልባ ይዤ ልቀዝፍ ወጥቻለሁ፡፡ ድንገት ማዕበል መጥቶ ጀልባዋ ተገለባበጠች፡፡ እኔ እጀልባዋ ወለል ላይ ተፈጠፈጥኩ፡፡ ከዚያ ወዲያ መዋኘት አልቻልኩም፡፡ ይሄ አሣማ ያንን አውቆ፤ በረቱን በርግዶ ወጥቶ ወደ እኔ ዋኝቶ መጥቶ ወደ ሐይቁ ዳርቻ ወሰደኝ፡፡  መተንፈስ አቅቶኝ አሸዋው ላይ ተንጋለልኩኝ፡፡ ከዚያ ወደ ቤቴ ሄዶ፣ ባለቤቴን ቀስቅሶ ይዟት መጣ፡፡ እሷ ትንፋሽ መግባኝ ነብሴን ዘራሁ፡፡ ይሄ አሣማ ህይወቴን አዳነልኝ” እልሃለሁ አለው፡፡
የመጠጥ ክፍሉ ኃላፊ በጣም ተደንቆ፣ ግን በመጠኑ ትዕግሥት አጥቶ፤ “በጣም አስደናቂ ትንግርት ነው፡፡ ግን የአንድ እግሩ እንጨት መሆን ሚሥጥር ትርጉሙ ምንድን ነው?” አለና ጠየቀው፡፡
“አንድ ሌላ ቢራ ጋብዘኝና እነግርሃለሁ…” አለው፡፡ ባለ መጠጥ ቤቱ ሌላ ቢራ ከፈተለት፡፡
“ስለዚህ ተዓምረኛ አሳማ አሁን ልንገርህ፡፡ ባለፈው ሳምንት ከፍተኛ አውሎ ንፋስ ተነስቶ እኔ ለመሸሽ ወደ ምድር ቤት ስሮጥ አዳለጠኝና ወደቅሁኝ፡፡ አሳማ ሆይ ከበረቱ በርግዶ ወጥቶ እየጐተተ ምድር ቤት አውርዶኝ ከአውሎ-ነፋሱ ተረፍኩኝ እልሃለሁ”
ባለ መጠጥ ቤቱ ይሄ የመጨረሻው ተዓምር መሆን አለበት ብሎ፤
“ይገርማል ተዓምረኛ አሣማ ነው ባክህ! ከእሣት፣ ከውሃና ከአውሎ ነፋስ አዳነህ! ግን ይሄ የእንጨት እግሩ ከየት መጣ?”
ሰውዬውም በመጨረሻ፤     
“እንዲህ ያለውን ተዓምረኛ አሣማኮ ሁሉንም ባንድ ጊዜ አትበላውም፡፡ ቀስ ቀስ እያልክ፣ ትንሽ ትንሽ ብልቱን እየለየህ፣ ነው መብላት ያለብህ!!” አለው፡፡   
*    *    *
ለአገር ባለውለታ የሆኑን ሰዎች በምንም ዓይነት ውለታቸውን መርሳት አይገባንም፡፡ ሁሉም ዜጋ የየራሱ ድርሻ አለውና ያንን አስተዋፅዖውን አለመርሳት ብልህነት ነው፡፡ የተሻለና የበለጠ ያገለገለን ዜጋ ደግሞ፤ የተሻለ እውቅና መስጠት ይገባናል፡፡ ይህ “ሥራ ለሠሪው እሾህ ላጣሪው” ዓይነት መንገድ ነው፡፡ ስለሆነም፤ የሀገርን የዕድገት መንፈስ የሚያፀና ነው!
አስተሳሰባችን ሙሉ ይሁን፡፡ ለእኛ የሚመች የሚመቸውን ብቻ የፖለቲካ መዘውር ነው ካልን የሚያጎድለን እንጂ የሚያሟላን ፀጋ አልጨበጥንም ማለት ነው፡፡ ጨቋኝና ተጨቋኝ  ባለበት አገር በድሮው አነጋገር Class based society ውስጥ የተበዳዩን ቁጥር ለመቀነስ ፍትሐዊ አስተዳደር ያስፈልጋል፡፡ “በምድር ላይ የሚራመድ አንድ ‘ባሪያ’ እስካለ ድረስ፤ ሙሉ በሙሉ ነፃ አንወጣም” ይሉናል ፀሐፍት። መልካም አስተዳደር እኛ እንደምንገምተው ቀላል አይደለም፡፡ ባህላዊ ታሳቢ እሴቶችን ሳናመዛዝን፤ የውጪውን አስገብተን እንዳለ ህዝባችን ላይ እንጫን ብንልም ዓላማው ጉዳዩን ከማወሳሰብ አያልፍም፡፡ ለዚህ ነው በሀገራችን መሻሻል የማናየው፡፡ ከመሠረታችን እንደማተባችን የማንበጥሳቸው አልበገር-ባይነት (Resistance) ውስጣችን አለ፡፡ ያንን ለማውጠንጠን ነፃ አስተሳሰብ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ መንግሥትም የራሱን ኃላፊነት መወጣት አለበት፡፡ ህዝብም እንደዚሁ ይህ ይሆን ዘንድ መጣጣር አለበት፡፡ የረዥም ጊዜ ግልፅ ውይይት፤ ሀሜትን ያስወገደ ዕውነተኛና ልባዊ ለውጥ ላይ ያተኮረ ረዥም ጉዞ ያስፈልገናል። ችግሩ እንግዲህ፤ መለወጣችንን የሚያይልን ራሱ ያልተለወጠ ሰው ከሆነ ተያይዞ ገደል መግባት ሊሆን ነው፡፡ ለምሳሌ ይሄ የእገሌ፣ ያ የእገሌ ብሄረሰብ፣ ጎሣ፣ መንደር ወዘተ ሰው ነው በሚል ሌላውን አሳንሶ የማስቀመጥ አመለካከት፤ እንደቀንድ-አውጣ ውስጣችን ያደፈጠ የለውጥ እንቅፋት ነው። ለፍቅረኞች ቀን፤ የአበበ ዘንግ ሽያጭ፤ አበባ ልብን ላያመላክት ይችላል! ገቢ አለ፡፡ በገቢው የምንሠራው ምንድነው? ይሄ ብዙ ጊዜ ተደጋግሞ ሲነገር ሰምተናል፡፡ ጠጋ ብለን፣ የችግሩ ምንጭ የት ጋ ነው ብለን ግን ለማጤን አልፈቀድንም፡፡ “አንድን ጉድ፣ ሺ ጊዜ ከሰው ከመስማት አንዴ ሄዶ በዐይን አይቶ እርፍ ማለት ይሻላል” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ የታመመ ሰውን ጠይቆ የሚነግረን ሰው፤ ስለበሽተኛው የግሉን ስሜት ብቻ አጋኖ እንደሚነግረን እረስተን፤ እኛም ያንኑ ወሬ ለሌላ ጆሮ እናስተላልፋለን፡፡ ሺ ጊዜ በማጉላትም ጣር-አልጋ ላይ ያለ ሰው አድርገነው ቁጭ እንላለን፡፡ አገራችን ታማለች ካልን ቀርቦ ማየት ነው፡፡ የሚሻለውን መምከር፣ የምትታከምበትን መላ መምታት ነው ያለብን፡፡
የሀገራችን ችግሮች እጅግ በርካታ ለመሆናቸው አዋቂ መጠየቅ አያሻንም፡፡ ተራ በተራ ለመፍታት መጣጣር ነው እንጂ የለም ብሎ መካድ ግን ቢያንስ ራስን ማታለል ነው፡፡ ከራሳችን አበሳ በተጨማሪ፤ በተጋቦት እስከሚመጡት የድምበርተኛ ጎረቤቶቻችን ችግር ድረስ፤ የችግር መተላለፊያ ኮሪዶር ነን ብለናልና፤ ኮሪዶሩ መጠረግ አለመጠረጉን አለማረጋገጥ ለባሰ መዘዝ ይዳርገናል፡፡ “እንኳን አሁንና ብዙ ትጥቅ እያለን
በጦር በጎራዴ፣ ታንክ እናማርካለን”
ማለት በዘመነ-ግሎባላይዜሽን (የለየለት ቅኝ-ገዢነት) እንደማያዋጣ ማንም ሊስተው አይገባም። የሀብት ምንጮቻችንን እንጠብቅ፡፡ የሰው ኃይላችንን፣ ጦራችንን በአግባቡ እንጠብቅ! ለገዛ ጥቅሙ በስተቀር ለእኛ ብሎ እሹሩሩ የሚለን የዓለም ታላቅ አገር የለም፡፡ “አበሻም ይሁን ፈረንጅ ማንም ህዝቡ ላይ ጫና ሊጥል አይገባም” የሚለውን አባባላችንን ማጥበቅ መልካም ነገር ነው! “አነስተኛ ነን ብለን እጃችንን መጠምዘዝ የለብንም፡፡ ችግራችን የብረት በር ሆኖብናል አንበል፡፡ “እጅግ በጣም ትልቁ የብረት በር እንኳን የሚከፈተው በትንሽ ቁልፍ መሆኑን አትርሳ” ይለናል ደራሲ ቻርልስ ዲከንስ፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል ነው ነገሩ!!   

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 7 of 17