30ኛው አፍሪካ ዋንጫ ዛሬና ነገ ለደረጃ እና ለዋንጫ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይፈፀማል፡፡ ዛሬ በደረጃ ጨዋታ አዘጋጇ አገር ኢኳቶርያል ጊኒ ከዲሞክራቲክ ሪፖብሊክ ሲጫወቱ ነገ ደግሞ ኮትዲቯርና ጋና በዋንጫ ፍልሚያ ይፋጠጣሉ፡፡ የምእራብ አፍሪካ ጎረቤታሞች የሆኑት ኮትዲቯርና ጋና  በአፍሪካ ዋንጫ የፍፃሜ  ጨዋታ ሲገናኙ  ሁለተኛቸው ሲሆን በሁሉም ውድድሮች ደግሞ ለ40ኛ ጊዜ መጋጠማቸው ነው፡፡ ሁለቱ የምእራብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድኖች በፕሮፌሽናል ተጨዋቾች ሙሉ በሙሉ መገንባታቸው፤ በአፍሪካ ዋንጫ እና በዓለም አቀፍ ውድድሮች ባላቸው ከፈትኛ ልምድ እና የውጤት ታሪክ ተመጣጣኝ በሚባል አቋም ላይ ናቸው፡፡ ኮትዲቯርና ጋና  በሁሉም ዓለም አቀፍ ውድድሮች 39 ጊዜ ተገናኝተው፤ 14 እኩል ሲሸናነፉ በ11 አቻ ተለያይተዋል፡፡ በ1992 እኤአ ኮትዲቯር እና ጋና በአፍሪካ ዋንጫ ለፍፃሜ በተገናኙበት ወቅት አሸናፊው የተለየው በመለያ ምቶች ነበረ፡፡ ኮትዲቯር ብቸኛውን የአፍሪካ ሻምፒዮናነት ክብር ተቀዳጅታበታለች፡፡ በነገራችን ላይ ኮትዲቯር በአፍሪካ ሁለት ሌሎች የዋንጫ ጨዋታዎች አሳዛኝ ተሸናፊ ነበረች፡፡ በ2002 እኤአ በግብፅ እንዲሁም በ2006 እኤአ በዛምቢያ በመለያ ምቶች ተሸንፋ ሁለት ዋንጫዎችን ተነጥቃለች፡፡ በአፍሪካ ዋንጫ የ56 ዓመታት ታሪክ በተካሄዱት 29 የፍፃሜ ጨዋታዎች አራቱ አሸናፊዎች በተጨማሪ ሰዓት ሲታወቁ፤ 7 የዋንጫ ፍልሚያዎች ደግሞ በመለያ ምቶች ሻምፒዮኖቹ ተለይተዋል፡፡ከዛሬው የደረጃ እና ከነገው የዋንጫ ጨዋታዎች በፊት በ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ግማሽ ፍፃሜ 30 ግጥሚያዎች ተካሂደው 72 ጎሎች ከመረብ ተዋህደዋል፡፡ እስከ ሩብ ፍፃሜ በመጓዝ ባስመዘገቡት ውጤት ደግሞ ከ5 እስከ 16ኛ ያለውን ደረጃ ኮንጎ ፤አልጄርያ፤ ቱኒዚያ፤ ጊኒ ፤ሴኔጋል ፤ማሊ ፤ኬፕቨርዴ ጋቦን ፤ካሜሮን ፤ዛምቢያ ፤ደቡብ አፍሪካና ቡርኪናፋሶ ያገኛሉ፡፡በ30 የአፍሪካ ዋንጫዎች  ሻምፒዮንነት  በ5 ዞኖች ሲከፋፈል  ሰሜን አፍሪካ በ10 ዋንጫዎች (7 የግብፅ እንዲሁም እያንዳንዳቸው አንድ ቱኒዚያ፤ አልጄርያ እና ሞሮኮ ) በማግኘት ይመራል፡፡ የምእራብ አፍሪካ ዞን ከ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋር በ9 ዋንጫዎች  (የጋና 4 ወይም 5 ፤ የናይጄርያ 3 እንዲሁም የኮትዲቯር 1 ወይም 2) ፤ መካከለኛው አፍሪካ በ7 ዋንጫዎች (4 የካሜሮን፤ 2 የዲ ሪ ኮንጎ 1 የኮንጎ ኪንሻሳ)፤ ምስራቅ አፍሪካ በ2 ዋንጫዎች  (የኢትዮጵያ እና የሱዳን) እና ደቡብ አፍሪካ በ2 ዋንጫዎች  (የደቡብ አፍሪካ እና የዛምቢያ) ተከታታይ ደረጃ ያገኛሉ፡፡የኢኳቶርያል ጊኒ ብሄራዊ መብረቅብሄራዊ መብረቅ በሚል ቅፅል ስም የምትጠራው ኢኳቶርያል ጊኒ  2ኛዋን የአፍሪካ ዋንጫን መሳተፏ ነበር፡፡ ሁለቱንም ደግሞ በአዘጋጅነት ነው፡፡ በ2012 እኤአ 28ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ከጋቦን ጋር በጣምራ አዘጋጅነት  ለመጀመርያ ጊዜ በመካፈል ሩብ ፍፃሜ ደረሰች፡፡ 30ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ደግሞ በምትክ አዘጋጅነት  ተረክባ በ64 ቀናት በማዘጋጀት በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ግማሽ ፍፃሜ ደርሳለች፡፡

  • የጋና ጥቋቁር ክዋክብት
  • አማካይ እድሜ 24.9 ዓመት
  • የአንድ ተጨዋች አማካይ ዋጋ እስከ  4 ሚሊዮን ዶላር
  • የእግር ኳስ ደረጃ በዓለም 37 በአፍሪካ 4
  • የቡድን ዋጋ ግምት $150,743,365

ጋና በ19 የአፍሪካ ዋንጫዎች ስትሳተፍ  4 ጊዜ ሻምፒዮን (1963, 1965, 1978, 1982)፤ 4 ጊዜ ሁለተኛ ደረጃ(1968, 1970, 1992, 2010)፤ 1 ጊዜ ሶስተኛ ደረጃን (2008) እንዲሁም ለሶስት ጊዜያት በአራተኛ ደረጃ (1996, 2012, 2013) ጨርሳለች፡፡ በእነዚህ አፍሪካ ዋንጫዎች ባስመዘገበችው 154 ነጥብ በምንግዜም የውጤት ደረጃ ሶስትኛ ናት፡፡
የኮትዲቯር ዝሆኖቹ

  • አማካይ እድሜ 26.4 ዓመት
  • የአንድ ተጨዋች አማካይ ዋጋ እስከ 8 ሚሊዮን ዶላር
  • የእግር ኳስ ደረጃ በዓለም 28 በአፍሪካ 3
  • አጠቃላይ የቡድን ዋጋ ግምት $207,628,902

ኮትዲቯር በ20 የአፍሪካ ዋንጫዎች የተሳትፎ ታሪኳ 1 ጊዜ ሻምፒዮን(1992)፤ ሁለት ጊዜ ሁለተኛ ረጃ(2006, 2012)፤ 4 ጊዜ ሶስተኛ ደረጃ (1965, 1968, 1986, 1994) እንዲሁም 2 ጊዜ አራተኛ ደረጃ (1970, 2008)ነበራት፡፡ በምንግዜም የአፍሪካ ዋንጫ የውጤት ደረጃ አምስትኛ ናት፡፡ያያ ቱሬ ከአገሩ ጋር ትልቅ ዋንጫ ይፈልጋልየኮትዲቯር አምበል ያያ ቱሬ በ10 ዓመቱ ታኬታ ተሰጥቶት በአቢጃን ጎዳናዎች ስሙ የገነነ ታዳጊ ተጨዋች  ነበር፡፡ ታላቅ ወንድሙን ኮሎ ቱሬን በመከተል በአዜክ ሚሞሳ አካዳሚ ሰለጠነና አውሮፓ ገባ፡፡ በግሪክ፤ በስፔንና በእንግሊዝ ክለቦች በመጫወት የየአገራቱ ሊጎች ሻምፒዮን ሆኗል፡፡ በተለይ በስፔኑ ክለብ ባርሴሎና 5 ትልልቅ ዋንጫዎችን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤
በዓለም ክለቦች ዋንጫ፤ በኮፓ ዴላ ሬይ እና በሌሎች ውድድሮች ወስዷል፡፡ በእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ሲቲ የፕሪሚዬር ሊግ ዋንጫ ብቻ ሳይሆን የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን አግኝቷል፡፡ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮከብ ተጨዋች ሆኖ ለአራተኛ ጊዜ በመመረጥ ባለክብረወሰን ነው፡፡ ዘንድሮ በአፍሪካ ዋንጫ የተሳተፈው ለ5ኛ ጊዜ ሲሆን በ3 ዓለም ዋንጫዎችም  ወርቃማ ትውልድ ከሚባለው የኮትዲቯር ቡድን ጋር በመካፈል የረባ ውጤት አላስመዘገበም፡፡አሳሞሃ ጂያን የጋናን የ33 ዓመታት የዋንጫ ረሃብ መታደግ ይፈልጋልየጋናው አምበል አሳሞሃ ጂያን ደቡብ አፍሪካ ባዘጋጀችው 19ኛው የዓለም ዋንጫ አፍሪካዊ ቡድን ለመጀመርያ ጊዜ ግማሽ ፍፃሜ የሚገባበትን እድል ኢሊጎሬ በመሳቱ ያበላሸ እና በዚያ ታሪክ ዝነኛ የሆነ አጥቂ ነው፡፡ በዓለም ዋንጫ የተሳትፎ ታሪኩ አምስት ጎሎች በማግባት የአፍሪካ ኮከብ ግብ አግቢ የሆነው ጂያን 4ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፉ ነው፡፡ የጋና ብሄራዊ ቡድን ከአፍሪካ ዋንጫ ለ33 ዓመታት የራቀበትን ሁኔታ መቀየር ይፈልጋል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት የነበረበትን የእንግሊዝ ክለብ ሰንደርላንድ በመልቀቅ ለዩናይትድ አረብ ኢምሬትሱ ክለብ አል አሊን አወዛጋቢ ዝውውር ፈፅሞ እየተጫወተ ይገኛል፡፡  ፈረንሳዊ ሄርቬ ሬናርድ ከእስራኤላዊ አቭራም ግራንትለ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለፍፃሜ የደረሱት ሁለቱ አሰልጣኞች ሄርቬ ሬናርድና አቭራም ግራንት ከአፍሪካ ውጭ የመጡ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ 46 ዓመታቸው የሆኑት ፈረንሳዊው ሄርቬ ሬናርድ በኮትዲቯር ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ለመስራት  የሁለት ዓመት ኮንትራት ተሰጥቷቸዋል፡፡ በ2012 እኤአ ላይ የዛምቢያን ብሄራዊ ቡድን ለሻምፒዮናነት ያበቁበት ታሪክ ትልቁ ስኬታቸው  ነው፡፡ ከ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ በፊት ሬናርድ ስለኮትዲቯር ቡድን ተጠይቀው ለያያ ቱሬ ያላቸውን አድናቆት ከገለፁ በኋላ ‹‹በምሰሶዎቹ ግንባታ ላይ ያለ ብሄራዊ ቡድን ነው፡፡  ወደ አቢጃን ዋንጫውን ይዘን ለመመለስ ተስፋ አድርገናል፡፡›› ብለዋል፡፡
አቭራም ግራንት 60 ዓመታቸውን ሊደፍኑ ሲሆን በጋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት የሁለት ዓመት ውል አላቸው፡፡ የእስራኤል ብቻ ሳይሆን የፖላንድ ዜግነት ያላቸው አቭራም ግራንት ጋና በአገር ደረጃ ለማሰልጠን ሃላፊነት ያገኙበት የመጀመርያው ብሄራዊ ቡድናቸው ነው፡፡ ከዚሁ ሃላፊነት በፊት በአውሮፓ እግር ኳስ ያካበቱት ልምድ አለ፡፡ በእንግሊዙ ክለብ ቼልሲ በዲያሬክተርነት ተቀጥረው ከዚያም በአሰልጣኝነት ሰርተዋል፡፡ በ2008 እኤአ በማንችስተር ዩናይትድ የተነጠቁት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ የማይረሳ ታሪካቸው ነው፡፡ ከቼልሲ በኋላ የፖርትስማውዝ፤ የዌስትሃምና የፓርቴዝያን ቤልግሬድ አሰልጣኝ ሆነው አገልግለዋል፡፡ በገና ብሄራዊ ቡድን ዙርያ አቭራም ግራንት አስተያየት ተጠይቀው ‹‹በየጨዋታው ከፍተኛ መሻሻል አሳይተናል፡፡ ጋናውያን ከፈቀዱ ዋንጫውን ባሸንፍም ባላሸንፍም በሃላፊነት ብቆይ ደስ ይለኛል፡፡›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡በ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ከተሳተፉት 16 ቡድኖች ሶስቱ ብቻ በአፍሪካውያን አሰልጣኝ የተመሩ መሆናቸው የአህጉሪቱ እግር ኳስ አንድ ተዳካመ ሁኔታን የሚያመለክት ሆኗል፡፡ አንዳንድ ዘገባዎች ይህ የአፍሪካውያን አሰልጣኞች ዝቅተኛ ተሳትፎ ከ1996 እኤአ በኋላ የወረደ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ ከ3ቱ የአፍሪካ አሰልጣኞች እስከ ግማሽ ፍፃሜ በመድረስ ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገቡት የዲሪ ኮንጎው ፍሎረን ኦቤንጊ ናቸው፡፡ ሌሎቹ ሁለት አፍሪካዊ አሰልጣኞች በምድብ ማጣርያ ከእነ ብሄራዊ ቡድናቸው የተሰናበቱት የደቡብ አፍሪካው ኤፍሪዬም ሼክስ ማሻባ ከደቡብ አፍሪካ እና ሆን ጃንዛ ከዛምቢያ ናቸው፡፡ በ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከተሳተፉ 16 ብሄራዊ ቡድኖች አራት ፈረንሳዊ አሰልጣኞች መወከላቸው ከፍተኛው ነው፡፡ የአልጄርያው ክርስትያን ጉርኩፍ፤ የኮትዲቯሩ ሄርቬ ሬናርድ፤ የኮንጎው ክላውድ ዲለሮይና የሴኔጋሉ ኤቴን ግሬሲ ናቸው፡፡ ሁለት ፖርቱጋላዊያን ጆርጌ ኮስታ በጋቦንና ራውል አኑዋስ በኬፕ ቬርዴ ሁለት ቤልጅማውያን ፖል ፑት በቡርኪናፋሶና ጆርጅ ዚኮንስ በቱኒዚያ የሰሩ አሰልጣኞች ናቸው፡፡ ካሜሮን በጀርመናዊው ቮልከር ፊንኬ፤ ጋና በእስራኤላዊው አቭራም ግራንት፤ ኢኳቶርያል ጊኒ በአርጀንቲናዊው ኤስቴበን ቤከር እንዲሁም ማሊ
በፖላንዳዊው ሄነሪክ ካስፐርዣክ አሰልጣኝነት የአፍሪካ ዋንጫውን ተሳትፈዋል፡፡ባለፉት 29 የአፍሪካ ዋንጫዎች አሸናፊ አሰልጣኞች 18 ከአፍሪካ ውጭ ካሉ አገራት የተገኙ ሲሆን ሻምፒዮን መሆን የቻሉት 11 አፍሪካውያን አሰልጣኞች ናቸው፡፡ ከውጭ አገር አሰልጣኞቹ 5 ፈረንሳውያን፤ 4 ዩጎስላቪያውያን፤ እንዲሁም አራት ሃንጋራዊያን ሲሆኑ 6 ሻምፒዮንአሰልጣኞች ከብራዚል፤ ከቼክ፤ ከሆላንድ ከሮማንያ፤ከጀርመንና ከዌልስ ከእያንዳንዳቸው የተገኙ ናቸው፡፡ ከነገው የ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ በኋላ ሻምፒዮን ለመሆን የተሳካላቸው የውጭ አገር አሰልጣኞች ብዛት 19 ይደርሳል፡፡
ቦነስና ሽልማትበ30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢኳቶርያል ጊኒ ተጨዋቾች በተከፈላቸው የውጤት ቦነስ የሚስተካከላቸው አልነበረም፡፡ ሩብ ፍፃሜ በመድረሳቸው ለእያንዳንዳቸው 30 ሺ ዶላር ነበር የተከፈላቸው፡፡ ጋናን አሽንፈው ለፍፃሜ ቢደርሱ 50 ሺ ዋንጫውን ከወሰዱ ደግሞ አስከ 150ሺ ዶላር  ቦነስ እንደሚሰጣቸው ቃል ተገብቶ ነበር፡፡ በዓለም ዋንጫ እና በአፍሪካ ዋንጫ በየጊዜው በቦነስ ክፍያ የሚጨቃጨቁት የጋና ብሄራዊ ቡድን ጥቋቁር ክዋክብቶች በአንድ ጨዋታ በአማካይ 5ሺ ዶላር የውጤት ቦነስ እንዲታሰብላቸው ተደራድረዋል፡፡ ዋንጫውን ካሸነፉ ለእያንዳንዳቸው 60ሺህ ዶላር እንደሚከፍል ፌደሬሽኑ ቃል ገብቷል፡፡  የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለአፍሪካ ዋንጫው በድምሩ 10 ሚሊዮን ዶላር ለሽልማት አቅርቧል፡፡ ሻምፒዮኑ 1.5 ሚሊዮን ዶላር ሲሸለም፤ ሁለተኛ ደረጃ የሚያገኘው 1 ሚሊዮን ዶላር
እንዲሁም ለደረጃ የሚጫወቱት ሁለት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 750ሺ ዶላር ይበረከትላቸዋል፡፡
በሩብ ፍፃሜ የቀሩት አራት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 600ሺ ዶላር በነፍስ ወከፍ ሲያገኙ፤ በምድብ
ማጣርያ ሶስተኛ ደረጃ የሚያገኙት አራት ቡድኖች እያንዳንዳቸው 500ሺ ዶላር እንዲሁም
በየምድባቸው የመጨረሻ ደረጃ የሚያገኙት እያንዳንዳቸው 400ሺ ዶላር ይታሰብላቸዋል፡፡


    በስፖርቱ በማርኬቲንግና በኢንቨስትመንት ያሉ እንቅስቃሴዎችን ለማነቃቃት በሚል ዓላማ 1ኛው ስፖርት ኤግዚቢሽን ባዛር  ተዘጋጀ፡፡ በጂኤምኤስ ፕሮሞሽንና በፈለቀ ደምሴ የኮምኒኬሽን ስራዎች የተዘጋጀው ኤግዚብሽንና ባዛር ከመጋቢት 5 እስከ 9 በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ይካሄዳል፡፡ በኤግዚቢሽንና ባዛሩ ላይ ለመሳተፍ በፌደራል ስፖርት ኮሚሽን ምዝገባ እየተከናወነ ሲሆንን ኮሚሽኑን ጨምሮ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን፣ ፣ የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴና፣ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሌሎች ፌደሬሽኖችና የስፖርት ተቋማት በአጋርነት ይሰሩበታል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀው አገር አቀፍ የስፖርት ኤግዚቢሽንና ባዛር ላይ የስፖርት ክለቦች ማልያዎቻቸውን እንደሚያስተዋውቁ፣ የተለያዩ ስፖርታዊ ቁሳቁሶችንና ማሊያዎችን ለሽያጭ እንደሚያቀርቡ የየክለቦቻቸውን ታሪካዊ ዳራ በፎቶዎችና በቪዲዮ ምስሎች እንደሚያቀርቡበት ታውቋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡና፤ ደደቢት እና ንግድ ባንክ በዚሁ ኤግዚቢሽንና ባዛር ላይ በግንባር ቀደምነት ለመሳተፍ ከተመዘገቡት መካከል ይገኙበታል፡፡  በሌላ በኩል የስፖርት እቃ አምራች፣ አስመጪና አከፋፋይ ድርጅቶች በኤግዚብሽኑና ባዛር ላይ እንደሚሳተፉ ሲታወቅ ምርትና አገልግሎታቸውን የማስተዋወቅና የመሸጥ እድል እንደሚያገኙበት ይጠበቃል፡፡ ከስፖርቱ ጋር በተያያዘ የሚንቀሳቀሱ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት በኤግዚቢሽንና ባዛሩ ላይ መሳተፋቸው በገራ ለመስራት ያሉ ጥረቶችን እንደሚያበረታታ ተገልጿል፡፡

         ውህደት ለመፈፀም ተደጋጋሚ ድርድሮችን ሲያካሂዱና ስምምነት ሲፈፀሙ የቆዩት አንድነት ፓርቲ እና መኢአድ፣ የውህደት ጅምራቸው ካለመሳካቱም በተጨማሪ በየፊናቸው ለሁለት ለሁለት ተከፍለው ሲወዛገቡ ነው የከረሙት፡፡ በመጨረሻም የምርጫ ቦርድ፣ ከመኢአድ ፓርቲ በአቶ አበባው መሃሪ ለሚመራ ቡድን፣ ከአንድነት ፓርቲ ደግሞ በአቶ ትዕግስቱ አወሉ ለሚመራው ቡድን እውቅና ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ እውቅና ያልተሰጠው በአቶ በላይ የሚመራው የአንድነት ቡድን ብዙም ሳይቆይ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ተቀላቅሏል፡፡

Published in ዜና
  • ሰሞኑን 35 ስደተኞች የያዘ ጀልባ የመን ሳይደርስ ሰጥሟል
  • በዓመት 200 ገደማ ኢትዮጵያውያን በበረሃ እና በባህር ጉዞ ላይ ሞተዋል
  • “በህጋዊ ምዝገባ የስራ ጉዞ መታገዱ ህገወጥ ስደትን አባብሷል”

       በህጋዊ ምዝገባ ወደ አረብ አገራት የሚደረግ ጉዞ ከታገደ ወዲህ፣ በየመን በኩል እየተሰደዱ ለአደጋ የሚጋለጡ ኢትዮጵያዊያን መበራከታቸውንና ባለፉት ስድስት ወራት 47ሺ ያህል ስደተኞች የመን እንደገቡ RMMS ሰሞኑን ገለፁ፡፡ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኮሚሽን እና ሌሎች አለማቀፍ ድርጅቶች በጋራ ያቋቋሙት ይሄው ተቋም እንደሚለው፣ ዘንድሮ የስደተኞቹ ቁጥር ከአምናው በእጥፍ ይበልጣል፡፡ ባለፉት አስራ ሁለት ወራት ውስጥ 250 ስደተኞች የመን ለመግባት ሲሞክሩ፣ በባህርና በበረሃ ጉዞ ላይ መሞታቸውን ተቋሙ ጠቅሶ ከስደተኞቹ መካከል ሰማኒያ በመቶ ያህሉ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ገልጿል፡፡ ሰሞኑን በባህር ጉዞ ላይ በተፈጠረ አደጋ አንድ ጀልባ መስመጡን የዘገበው ኤኤፍፒ፤ ጀልባዋ 35 ስደተኞችን አሳፍራ ነበር ብሏል፡፡ ከጉዞ አደጋ በተጨማሪ ስደተኞቹ የመን ከገቡ በኋላም ግማሽ ያህሉ በወሮበላ ቡድኖች እንደሚታገዱ የገለፀው RMMS፤ ከእገታ ለመለቀቅ ከቤተሰብ ገንዘብ እንዲያስልኩ ይገደዳሉ ብሏል፡፡ ለስደት የሚገፋፉ ዋና ዋና ምክንያቶችን ለማወቅ በሺ በሚቆጠሩ ስደተኞችና በትውልድ አካባቢዎቻቸው ላይ ጥናት ያካሄደው ይሄው ተቋም፤ በኢትዮጵያ ዋናዎቹ መንስኤዎች የኑሮ ችግር እንዲሁም ህይወትን የሚያሻሽል ነገር ፍለጋ ናቸው ብሏል፡፡ የፖለቲካ ችግርም የተወሰነ ጫና እንደሚፈጥር ተቋሙ ጠቅሶ፣ የደላሎች ድርሻ ግን ብዙዎች እንደሚያስቡት አይደለም፤ ከመቶ ስደተኞች መካከል በደላላ ግፊት ለስደት የሚነሳሱት ከሁለት ወይም ከሦስት አይበልጡም ብሏል፡፡
ብዙ ወጣቶች ወደ ስደት የሚያቀኑት አደጋ ሊያጋጥማቸው እንደሚችል ባለማወቃቸው ነው ለማለት እንደሚያስቸግር ተቋሙ ሲያስረዳ፤ በአመት ውስጥ ወደ የመን ከገቡት ኢትዮጵያዊያን መካከል ሩብ ያህሉ ከሳዑዲ አረቢያ ወደ አገራቸው የተባረሩና ካሁን በፊት ስደትን የሞከሩ ናቸው ብሏል፡፡ ከቅርብ ወራት ወዲህ የስደተኞቹ ቁጥር የተባባሰበት ሌላው ምክንያት፣ በህጋዊ ምዝገባ ወደ ሳዑዲ አረቢያና ወደ ኩዌት ሲደረግ የነበረው የስራ ጉዞ በመንግስት መታገዱ ነው ብሏል - የተቋሙ ጥናት፡፡ በሌላ በኩል ሶማሊያ ውስጥ ከድህነት በተጨማሪ የሰላም እጦት ወጣቶችን ለስደት እንደሚገፋፋ ተቋሙ ገልፆ፤ በኤርትራ ደግሞ ከኑሮ ችግር ሌላ ዋነኛው ግፊት የመንግስት ከፍተኛ የፖለቲካ አፈና ነው ብሏል፡፡ በሊቢያና በግብጽ በኩል ወደ አውሮፓ ለመግባት ከሚሞክሩ ስደተኞች መካከል ከሶሪያዊያን በመቀጠል በቀዳሚነት የሚጠቀሱት ኤርትራዊያን መሆናቸውን የጠቀሰው ይሄው ተቋም፤ ባለፉት አራት ወራት 15ሺ ኤርትራዊያን ወደ ኢትዮጵያ እንደተሰደዱ ገልጿል፡፡ ስደት የተባባሰው በድህነትና በአፈና ምክንያት አይደለም በማለት የኤርትራ መንግስት ሲያስተባብል፤ ወጣቶች እንዲሰደዱ በማድረግ አገሪቱን ኦና ለማድረግ አለማቀፍ ሴራ እየተካሄደብኝ ነው ብሏል፡፡

 

Published in ዜና

እገዳው ለ15 አመታት ተግባራዊ ሆኖ ቆይቷል
    የአሜሪካ ፌዴራል አቪየሽን ባለስልጣን የአገሪቱ አውሮፕላኖች በተወሰኑ የኢትዮጵያ የድንበር ካባቢዎች የአየር ክልል ውስጥ እንዳይበሩ የጣለችውንና ለ15 አመታት ተግባራዊ ሆኖ የቆየውን እገዳ ማንሳቱን አስታወቀ፡፡ባለስልጣኑ የበረራ እገዳውን የጣለው የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት በተቀሰቀሰበት ወቅት እንደነበር
አስታውሶ፣ እገዳው በተጣለባቸው አካባቢዎች የደህንነትና የጸጥታ ሁኔታ እየተሻሻለ መምጣቱንና የአደጋ ስጋት የሌለበት መሆኑን በጥናት በማረጋገጡ እገዳውን ማንሳቱን ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረገው መረጃ አስታውቋል፡፡በወቅቱ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የተከሰተውን የድንበር ግጭት በድርድር ለመፍታት የተጀመረው ጥረት መስተጓጎሉን ተከትሎ፣ በአካባቢው የነበረው አጠቃላይ ሁኔታ ለአደጋ የሚያጋልጥ ነው በሚል የበረራ እገዳው እ.ኤ.አ በ2000 ግንቦት ወር መጣሉን የጠቀሰው የባለስልጣኑ መረጃ፣ እገዳው መነሳቱ በሚመለከታቸው የመንግስት አካላት መጽደቁን ተከትሎ፣ የአሜሪካ አውሮፕላኖች በየትኛውም የኢትዮጵያ የአየር ክልል ውስጥ መንቀሳቀስ እንደሚችሉ አስታውቋል፡፡

Published in ዜና

የመፈንቅለ መጅሊስ ሙከራው ስርዓት አልበኝነት ነው ብለዋል
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሼህ ኪያር ሼህ መሃመድ አማን አህመድ፤ ከስልጣናቸው አለመውረዳቸውንና በቅርቡ በኦሮሚያ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት የተሰጠውን መግለጫ በጥብቅ እንደሚቃወሙ ገለፁ፡፡ በቴሌቪዥን “የኦሮሚያ ክልል የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ስራ አስፈፃሚዎች በህገ ወጥ መንገድ ስርዓት አልበኝነትን ተላብሰው፣ ‹እኛ የኢትዮጵያ ፌደራል መጅሊስ ፕሬዚዳንቶች ነን› በማለት በመንግስት ሚዲያዎች መግለጫ መስጠታቸው ህገወጥ ድርጊት ነው” ብለዋል-  ፕሬዚዳንቱ ሰሞኑን በፅ/ቤታቸው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፡፡ የአንድ ክልል ሥራ አስፈፃሚ በፌደራል ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ እከሌን አባረናል፣ እከሌን አግደናል ማለቱ ከህግና መመሪያ ውጪ ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ በህገወጥነት ህጋዊ መሆን ስለማይቻል ግለሰቦቹ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ አሳስበዋል፡፡
የህዝበ ሙስሊሙ ትልቅ ተቋም የሆነውን መጅሊስ ጥቂት ስርዓተ አልበኞች ሊያምሱትና ሊያተራምሱት እንደማይችሉ የተናገሩት የምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት፤ “እኔ ለሥራ ጉዳይ ከአገር በወጣሁ ቁጥር መፈንቅለ መጅሊስ ለማድረግና በህገወጥ መንገድ ስልጣን ለመያዝ ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው ቀርቷል” ብለዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ኦሮሚያን ጨምሮ ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ የስራ አስፈፃሚ አባላት ተመሳሳይ የመፈንቅለ መጅሊስ ሙከራ አድርገው ከሃላፊነታቸው መታገዳቸውን ፕሬዚዳንቱ ታውሰዋል፡፡
“ከሁለት ዓመት በፊት በህዝብ ተመርጠን፣ ህዝበ ሙስሊሙን ለማገልገልና መንግስትን ለመርዳት
ወደ ስልጣን መጥተናል” ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ይህንን ህጋዊ አሰራር ለመቀበል ፈቃደኛ ያልሆኑ ጥቂት
ህገወጥ ግለሰቦች የሚፈፅሙት ስርዓተ አልበኝነት መቀጠል እንደማይችል ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል በየዓመቱ በየካቲት ወር የሚካሄደውን ጠቅላላ ጉባኤ ለማድረግ በዝግጅት ላይ እንደሚገኙ የገለፁት ፕሬዚዳንቱ፤ በጉባኤው ላይ አሉ የተባሉ ችግሮችን በማንሳት ውይይት ተደርጐበት ውሳኔ እንደሚተላለፍ ተናግረዋል፡፡ በህገወጥነት ታግደው የቆዩት ሥራ አስፈፃሚዎች ጉባኤው ከፈቀደላቸው ብቻ በጠቅላላ ጉባኤው እንደሚሳተፉ ተናግረዋል፡፡ ኦሮሚያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት በቅርቡ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሰጠው መግለጫ፤ የፌደራሉ መጅሊስ ፕሬዚዳንት፤ ያለአግባብ የስራ ኃላፊዎችን በማገዳቸውና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ባለመወጣታቸው ከስልጣናቸው መውረዳቸውንና ክልሉም ውክልናውን ማንሳቱን ማስታወቁ ይታወሳል፡፡  


Published in ዜና

አለማቀፍ ተቋማት ወደ 100ሚ. ይጠጋል ይላሉ

   የተለያዩ አለማቀፍ ተቋማት ሪፖርቶች የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት ወደ 100 ሚሊዮን ተጠግቷል ቢሉም የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ የሃገሪቱ ህዝብ ከ90 ሚሊዮን አላለፈም ብሏል፡፡ ኤጀንሲው ትናንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ከህዝብ ቆጠራ የተገኘ መነሻ የህዝብ ብዛት፣ ከስነ ህዝብና ጤና ጥናቶች የተገኙ የውልደትና የሞት መጠን፣ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎትና የፍልሰት መጠን ስሌትን ጨምሮ የተባበሩት መንግስታት ስነ ህዝብ ተቋም የህዝብ ትንበያ አሰራርን በመከተል በተዘጋጀው ስሌት የዚህ ዓመት የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት 90 ሚሊዮን ነው ብሏል፡፡ ከጠቅላላው የህዝብ ብዛት ውስጥ 45 ሚ. 250 ሺ ወንዶች ሲሆኑ 44 ሚ. 825 ሴቶች መሆናቸውን የኤጀንሲው ትንበያ ያስረዳል፡፡ በኢትዮጵያ በአሁን ሰዓት አንድ እናት በአማካይ 4 ልጆች ትወልዳለች ተብሎ እንደሚገመትም ሪፖርቱ ይፋ ያደረገ ሲሆን የህዝብ ብዛቱ ከቁጥጥር ውጪ እንዳይሆን ዘመናዊ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ግንዛቤን በመፍጠር ለህብረተሰቡ ተደራሽ እየተደረገ ነው ተብሏል፡፡ የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ሽፋኑም ወደ 40 በመቶ መድረሱን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
የሃገሪቱ የህዝብ ብዛት ከክልሎች አንፃር በተቀመጠው መረጃ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ደቡብ፣ ሶማሌ እና ትግራይ በቅደም ተከተላቸው ከ1-5 ያለውን ደረጃ የያዙ ሲሆን በ1999 ዓ.ም በተደረገው የቤትና የህዝብ ቆጠራ 2.7 ሚሊዮን እንደነበር የተገለጸው የአዲስ አበባ የህዝብ ብዛት ወደ 3.2 ሚሊዮን ከፍ ማለቱ በሪፖርቱ ልክቷል፡፡ ኢትዮጵያ በህዝብ ቁጥሯ ከአፍሪካ ሃገሮች ከናይጄሪያ ቀጥላ በሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ ከ50 ዓመት በኋላ ከአፍሪካ 1ኛ ትሆናለች የሚለው የተለያዩ ተቋማት ትንበያ ትክክል እንዳልሆነና
የስታትስቲክስ ኤጀንሲው የትንበያ ቀመር፣ የህዝብ ቁጥር እድገት አማካይ መጠኑ እየቀነሰ እንደሚሄድ የኤጀንሲው የስራ አመራሮች ገልፀዋል፡፡ ኤጀንሲው የመረጃ ክፍተቶችን ያስወግዳል ያለውን 4ኛውን የህዝብና ቤት ቆጠራ ከ3 ዓመት በኋላ በ2010 ዓ.ም ለማካሄድ የተለያዩ ቅድመ ዝግጅቶችን እያደረገ መሆኑም ተመልክቷል፡፡ የሃገሪቱ የህዝብ ብዛት ከ5 ዓመት በኋላ 100 ሚሊዮን እንደሚደርስና ከ20 ዓመት በኋላ ወደ 136 ሚሊዮን እንደሚጠጋ የኤጀንሲው የህዝብ ብዛት ትንበያ ያመላክታል፡፡ በሌላ በኩል የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት በዘንድሮው ዓመት ከ98 ሚሊዮን ልቋል የሚል ሪፖርት ያወጣ ሲሆን ከ150 በላይ የሚሆኑ የዊኪፒዲያ ተቋማት እንደመረጃ ምንጭ የሚጠቀሙትና አለማቀፍ አጥኚዎችን በስሩ ያሰባሰበው “ዎርልድ ሜትር” በበኩሉ፤ የህዝብ ብዛቱ 98 ሚሊዮን 942 ሺህ መድረሱን ይፋ አድርጓል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ሪፖርት ደግሞ የህዝብ ብዛቱ 92 ሚሊዮን ደርሷል ብሏል፡፡

Published in ዜና

ውህደት ለመፈፀም ተደጋጋሚ ድርድሮችን ሲያካሂዱና ስምምነት ሲፈፀሙ የቆዩት አንድነት ፓርቲ እና መኢአድ፣ የውህደት ጅምራቸው ካለመሳካቱም በተጨማሪ በየፊናቸው ለሁለት ለሁለት ተከፍለው ሲወዛገቡ ነው የከረሙት፡፡ በመጨረሻም የምርጫ ቦርድ፣ ከመኢአድ ፓርቲ በአቶ አበባው መሃሪ ለሚመራ ቡድን፣ ከአንድነት ፓርቲ ደግሞ በአቶ ትዕግስቱ አወሉ ለሚመራው ቡድን እውቅና ሰጥቻለሁ ብሏል፡፡ እውቅና ያልተሰጠው በአቶ በላይ የሚመራው የአንድነት ቡድን ብዙም ሳይቆይ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ ጋር ተቀላቅሏል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ መሪዎች ቀደም ሲል አንድነት ፓርቲ ውስጥ እንደነበሩና በክፍፍል ምክንያት ወጥተው ፓርቲ እንዳቋቋሙ የሚታወስ ሲሆን የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤ በፓርቲዎች ክፍፍል እና በወቅታዊ የፖለቲካ ውዝግቦች ዙሪያ ለጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ የሰጡትን አስተያየት አቅርበናል፡፡

የምርጫ ሰሞን የፓርቲዎች ክፍፍል
በየምርጫው የፓርቲዎች ግጭትና ክፍፍል የተለመደ ቢሆንም የዘንድሮው ይለያል፡፡ በመንግስት አቋም ተወስዶበት የተሰራ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ በራሱ ስራና ብቃት መመረጥ እንደማይችል አውቋል፡፡ ስለዚህ ህዝቡን አማራጭ ማሳጣት ይፈልጋል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ ያሉ ጥቃቅን ስህተቶችን በማጉላት እንዲሁም ሬዲዮ ፋናን፣ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንንና ምርጫ ቦርድን  በመጠቀም፣  “የተቃውሞው ጎራ እርባና ቢስ ነው፤ ብትወደኝም ባትወደኝም ከእኔ ጋር ትኖራለህ” በሚል ህዝቡ ላይ ጫና ለማሳደር የመጫን ስራ ሆን ብሎ እየሰራ ይገኛል፡፡ ለዚህም  ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በአንድነት ላይ የወሰደውን ውሳኔና የሰጠውን መግለጫ ማየት ይቻል፡፡ “የእነ ትዕግስቱ ቡድን ለእኛ ስለሚታዘዝና በእኛ ሃሳብ ስለሚስማማ እንጂ የራሱ ድክመት አለበት” በማለት አንድነትን ለእነሱ አፅድቆላቸዋል፡፡ ሌላው በእኛ በሰማያዊ ፓርቲ ላይ ቦርዱ
የጀመረው ዘመቻ ነው፡፡ ይቅርታ እንድንጠይቅ ደብዳቤ ፅፎብን ነበር፡፡ እንደ ጥፋት ያቀረባቸው
ነገሮች ግን እዚህ ግባ የማይባሉና ጥፋት ያልሆኑ ነገሮች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ትብብር ለምን ሰራችሁ፣ ያልተመቸንን ስብሰባ ትተን መውጣት መብራታችን ሆኖ ሳለ እንዴት ረግጣችሁ ትወጣላችሁ በሚል ነው የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ  የፃፈልን፡፡ ሬዲዮ ፋናንና ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ብንመለከት፣ እንደሌሎቹ ፓርቲዎች እኛ ላይ ፕሮፓጋንዳ ለመስራት ጠሩኝ፡፡ አክብሬ ሄድኩኝ፤ እዚያው ሬዲዮ ፋና ስቱዲዮ ውስጥ ለሁለት ሰዓት ከተቀረፅኩኝ በኋላ መጨረሻ ላይ ፊልሙ ተበላሽቷል አይተላለፍም አሉኝ፡፡ እኛ የቀረፅነው ስላለ እንስጣችሁ አልናቸው፤ አልፈለጉም፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተመሳሳይ ጥያቄ ይዞ የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት አቶ ዮናታንን ለአንድ ሰዓት ተኩል ያህል አነጋገራቸው፤ ግን በቴሌቪዥን አልተሰራጨም፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ለእነሱ ፕሮፓጋንዳ የሚመች መልስ ስላልሰጠን ነው፡፡ ይህን ሁሉ ስመለከተው መንግስት ሆን ብሎ ፓርቲዎችን ጥላሸት ለመቀባት ለህዝብ ለማሳየት እየተደረገ ያለ ጥረት መሆኑን እገነዘባለሁ፡፡“አንድነት” ለሁለት ስለመሰንጠቁእኔ በበኩሌ አንድነት ለሁለት ተሰነጠቀ ለማለት እቸገራለሁ፡፡ ምክንያቱም ቅር ተሰኘን የሚሉ ጥቂት ሰዎች ሄደው ለምርጫ ቦርድ ቅሬታ አቀረቡ፡፡ ከስራ አስፈፃሚው እስከ ታች ያለው የፓርቲው መዋቅር ግን በእነ አቶ በላይ ፍቃዱ የሚመራ ነው፡፡ የፓርቲው የብሔራዊ ም/ቤት አፈጉባኤ፣
ምክትል አፈጉባኤ፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት ሰብሳቢ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች ኃላፊ…  ከእኛ ጋር ቀላቀሉት ናቸው፡፡ ሌላው አንድነት የት አለ? ከእኛ ጋር ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የፓርቲው ትልቁን የኃላፊነት ቦታ የያዙት ስለሆኑ እኔ አንድነት ተሰነጠቀ አልልም፤ ከኛ ጋር ተዋሃደ እንጂ አልተሰነጠቀም፡፡ በአሁኑ ሰዓት እዚህ እየመጡ እየተመዘገቡ ነው በክልልም ለምርጫው እጩ እስከማቅረብ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ እስካሁን ከእኛ ጋር የተቀላቀሉትን ብዛት በቁጥር ለመግለፅ እቸገራለሁ፡፡ በአጠቃላይ በአቶ በላይ ፈቃዱ ሲመሩ የነበሩት እውነተኛዎቹ የአንድነት አባላት ከነመዋቅራቸው ወደ እኛ መጥተዋል፡፡ “አንድነት ሰማያዊ ሴራ ፈረሰ” ስለመባሉበብዕር ስም ተፅፎ የወጣው፤ ዘገባ ሃሰት ነው፡፡ ምክንያቱም በእስር ላይ ያሉትን እነ ሃብታሙ አያሌውን ሁልጊዜ እናገኛቸዋለን፡፡ እንደውም ወደፊት አብረን ስለምንሰራበት ሁኔታ በየጊዜው እንወያያለን፡፡ ከሃብታሙም ሆነ ከየሺዋስ ጋር ጓደኛሞች ነን፡፡ የአንድነት ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ወደ ሰማያዊ ፓርቲ በመግባታቸው ኢህአዴግ በደረሰበት ድንጋጤ ሆን ብሎ የሚያስወራው ነው፡፡ እዚያ ዘገባ ላይ ከተፃፈው አንድ ምሳሌ ልንገርሽ፡፡ በበላይ ፍቃዱ የሚመራው ቡድን በዶ/ር ያዕቆብ ሸምጋይነት ከሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ጋር በተናጠል ሲደራደር ቆይቷል ተብሎ ተፅፏል፡፡ ይሄ አይን ያወጣ ውሸት ነው፡፡ እኔና በላይ ፍቃዱ ከጓደኝነታችን የተነሳ ለመገናኘት ሽማግሌ
አያስፈልገንም፤ ሁልጊዜም ቢሆን እየተገናኘን በአገራችን ወቅታዊ በጎና መጥፎ ጉዳዮች ላይ ሌት
ተቀን የምንነጋገር የምንከራከር ነን፡፡ እኔና ዶ/ር ያዕቆብ አንድ ላይ ሆነን ሻይ ጠጥተን እንደማናውቅ ላረጋግጥልሽ እወዳለሁ፡፡ ይሄ ሁሉ የሚመራብን ወሬ  የኢህአዴግን ድንጋጤ የሚያሳይ ነው፡፡
እንደ ክፍፍሉ ውህደቱ መፍጠኑአሁን ጥቃቅንና አነስተኛ የፕሮግራም ልዩነቶችን እያነሳን ጊዜ የምናባክንበት ወቅት ላይ አይደለንም፡፡ በመሰረቱ አንድነትና ሰማያዊ በአብዛኛው ፕሮግራሞቻቸው ላይ ልዩነት የላቸውም፡፡ ስለዚህ ዋና ዋናዎቹ ላይ ከተስማማን በጥቂትና ጥቃቅን የፕሮግራም ልዩነቶች ላይ በሂደት በውይይትና በክርክር የምንስማማባቸው ይሆናሉ፡፡ አብረን ለመስራት የሚከለክሉን ስላልሆኑ ይሄ
አያስጨንቀንም፤ በአሁኑ ሰዓት እንደ ቁምነገር የምናነሳው አይደለም፡፡ የአንድነት አባላት በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ የሚኖራቸው የአመራር ቦታቀደም ብዬ እንደተናገርኩት ወደኛ የመጡት የአንድነት ሰዎች በትልልቅ የአመራር ቦታ ላይ የነበሩ ናቸው፡፡ በፓርቲው ስልጣንና ሹመት ውስጥ ብቻ ሳይሆን አሁን አዲስ አበባ ላይ በምናቀርባቸው እጩዎች ላይ ጥሩ ጥሩ ተፎካካሪዎችን ማቅረብ ይችላሉ፡፡ የመመረጥ መብታቸው እስከ ከፍተኛ አመራር ድረስ ክፍት ስለሆነ መብታቸው ነው፡፡ ይህንን ጉዳይ በተደጋጋሚ ተነጋግረንበታል፡፡ አሁን ከተቀላቀሉን ውስጥ ብዙዎቹ ጥሩ ጥሩ የአመራር ብቃት ያላቸው ስለሆኑ ለፓርቲያችን ያስፈልጉናል፡፡ በፓርቲው ወሳኝ ወሳኝ ቦታ ላይ ገብተው የመስራት መብት አላቸው፡፡ በቀሪው አንድ ሳምንት ውስጥ በእጩነት እንዲገቡም እናደርጋለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሁሌም “ፓርቲዎች ትከፋፈላላችሁ፤ አትግባቡም” እንባለለን፡፡ ይሄ ቁጭት በውስጣችን እያለና ገዢው ፓርቲ ሆን ብሎ “ተጣልተዋል፤ ተከፋፍለዋል” የሚለውን ስራዬ ብሎ በተቆጣጠራቸው ሚዲያዎች እያናፈሰ ባለበት አስቸጋሪ ሰዓት ፓርቲያችንን የሚያግዝና የሚያጎለብተን ኃይል ሲመጣ እንዴት አንደሰትም፡፡ ከዛ በተረፈ በሁለቱም ፓርቲዎች በኩል ያለን ሰዎች የምንተዋወቅና የምንግባባ ስለነበርን እንደ አዲስ አንተያይም፤ አብረን ለመስራት ሁሉንም ነገር ያቀልልናል፡፡ለምርጫ ስላቀረቧቸው እጩዎች ብዛት እስካሁን ፓርቲያችን በአገር አቀፍ ደረጃ ወደ 400 የሚጠጉ እጩዎችን አስመዝግበናል፡፡ አሁን ደግሞ እጩ የማስመዝገቡ ሂደት ለአንድ ሳምንት ተራዝሟል፡፡ በዚህ በቀረን አንድ ሳምንት አዲስ ከተቀላቀሉን ሰዎች ውስጥ የምናስመዘግባቸው ይኖራሉ፡፡ በአጠቃላይ የእጩዎቻችን ቁጥር ወደ 500 ከፍ ሳይል እንደማይቀር እገምታለሁ፡፡ መጀመሪያ ላይ ልናስመዘግብ ያቀድነው የእጩዎች ብዛት 300 ነበር፡፡ በምርጫ ዘመቻ የፓርቲዎች ስህተትና ትኩረትምርጫው እየቀረበ እንደመሆኑ መጠን በውስብስብና አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው የምንገኘው፡፡ በትናንሽ ጉዳዮችና በእርስ በርስ ፉክክር ላይ ከማተኮር ይልቅ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ትልቁን የአገራቸውን ምስል እንዲያዩ እመክራለሁ፡፡ ልዩነትም ቅራኔም ቢኖር መቻቻልና ቅራኔን በጥበብ
በመያዝ ለውጤት ወደሚያበቃ ትግል ተጠናክረን መግባት አለብን፡፡ ዛሬ የምንሰራው ስህተት ልብ ሰብርና ህዝቡን ተስፋ የሚያሳጣ እንዳይሆን በመጠንቀቅ በጥበብ መጓዝና ለምንታገልለት ህዝብ የተስፋ ብርሃን መፈንጠቅ ይኖርብናል፡፡ ፓርቲዎች የገዢውን ፓርቲ ከፋፋይ ሴራ በማወቅ፣ ከፍተኛ
ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ጥሪ አቀርባለሁ፡፡

Published in ዜና

“ክፍያውን በቀድሞ ታሪፍ መቀጠል ይችላሉ፤ ቤታቸው ግን መለካት አለበት” - የወረዳው አስተዳደር

   በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1፣ በተለምዶ ለቡ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የሚገኙ ከ25 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በካሬ ሜትር 0.50 ሳንቲም ሲከፍሉ የቆዩት የመሬት ግብር ወደ 3 ብር ማደጉ አግባብ አይደለም ሲሉ ተቃወሙ፡፡ ከ1990 ዓ.ም  አንስቶ የመኖሪያ ቤት በማህበር ለመስራት ከመንግስት በሊዝ ቦታ መመራታቸውን ያስታወሱት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ቦታውን ሲወስዱ በካሬ ሜትር 0.50 ሳንቲም ሊከፍሉ መስማማታቸውንና እስከ 2005 ድረስ በተመሳሳይ ክፍያ መቀጠላቸውን ጠቁመው ከዚያ በኋላ በካሬ ሜትር ሶስት ብር እንዲከፍሉ መደረጋቸውን ይናገራሉ፡፡“ይህን ክፍያ የከፈልነው በአስሩም ክፍለ ከተማ መመሪያ የወጣ መስሎን ነበር” ያሉት የቅሬታ አቅራቢዎቹ ተወካይ፤ በኋላ ጉዳዩን ሲያጣሩ ግን ከ1996 ዓ.ም በፊት ቦታ የተመሩትን የሶስት ብሩ ክፍያ እንደማይመለከታቸው ማወቃቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ላለፉት ሁለት ዓመታት ያላግባብ የከፈሉት ክፍያ እንዲመለስላቸውና በ0.50 ሳንቲም ክፍያቸውን እንዲቀጥሉ በየተዋረዱ ላሉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች አቤት ቢሉም ምላሽ ማጣታቸውን የተናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ከጥቂት ወራት በፊት ችግራቸውን ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት መናገራቸውንም አስታውሰዋል፡፡ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎችም በሬዲዮ ፋና ቀርበው፣ ከ1996 በፊት በሊዝ ቦታ የወሰዱትን በካሬ ሜትር 3 ብር ክፍያ እንደማይመለከታቸው ማረጋገጣቸውን ጠቅሰው፤ እነዚሁ ኃላፊዎች ወረዳው በአስቸኳይ መፍትሄ ሊሰጣቸው እንደሚገባ መግለፃቸውንና ለወረዳው መሬት አስተዳደር የትዕዛዝ ደብዳቤ መፃፉን ነገር ግን እስካሁን ምላሽ አለማግኘታቸውን ይናገራሉ፡፡ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን በሌሎች ክፍለ ከተሞች ተመሳሳይ ስህተት ተፈፅሞ ከሆነ እንዲታረም በፃፈው ደብዳቤ፤ ከ1996 ዓ.ም በፊት በእጣና በምደባ ቦታ ተሰጥቷቸው በሊዝ ውል የገቡ ነዋሪዎች አዲሱ ታሪፍ እንደማይመለከታቸው መግለፁንም ጠቅሰዋል፡፡
“እኛ ቤቱን የሰራነው መንግስት በሰጠን ፕላንና መመሪያ ነው፤ ከአፈር ግብር በተጨማሪም ጣሪያና ግድግዳ አስለክተን የከፈልንበት ደረሰኝ አለን” ያሉት ተወካዮቹ፤ የፕላንና የካርታ ለውጥ ሳያደርጉና ቤት በፎቅ መልክ ሳይቀጥሉ ይለካ መባሉ ግራ እንዳጋባቸው ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡ መንግስት አስለካሁ ካለ ማስለካት እንደሚችል፤ ነገር ግን ለመሃንዲስ 500 ብርና ለታክሲ 300 ብር ክፈሉ መባላቸውን እንደማይቀበሉት ነዋሪዎቹ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡ ጉዳዩን በተመለከተ ያነጋገርናቸው የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ፣ የወረዳ አንድ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ታሪክ ፍቅሬ፤ የነዋሪዎቹ ቅሬታ ተገቢነት እንዳለው አልካዱም፡፡ ወደ ኃላፊነቱ ከመጡ ገና 15 ቀናት ብቻ እንዳስቆጠሩ የጠቆሙት ዋና ስራ አስፈፃሚው፤ 0.50 ሳንቲም መክፈል እያለባቸው በካሬ ሶስት ብር መክፈላቸው ስህተት መሆኑን አምነው፣ እስከዛሬ የከፈሉት እላፊ ሂሳብ በወደፊት ክፍያቸው ላይ ይታሰብ ወይስ ይመለስላቸው በሚለው ላይ ከሌሎች ኃላፊዎች ጋር ተነጋግረው ምላሽ ለመስጠት ለፊታችን ረቡዕ ቀጠሮ መያዙን ገልፀዋል፡፡ ከአሁን ጀምሮ ነዋሪዎቹ ክፍያቸውን በ0.50 ሳንቲም መቀጠል እንደሚችሉ የተናገሩት አቶ ታሪክ፤ ነገር ግን የቤቱን ግድግዳና ጣሪያ የማስለካት ግዴታ እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡ ቅሬታ አቅራቢዎቹ በበኩላቸው፤ አሁን ክፍያ እንድንፈፅም ጠይቀን ካላስለካችሁ መክፈል አትችሉም ስለተባልን ግራ ገብቶናል፤ ለቅጣትም ልንዳረግ ነው ብለዋል፡፡ አቤቱታቸውን ለወረዳው ገቢዎች ፅ/ቤት ሊያቀርቡ ገብተው በጽ/ቤቱ ኃላፊ ዘለፋና ስድብ እንደደረሰባቸው የገለፁት ተወካዮቹ፤ ህዝብን ሊያገለግሉ የተቀመጡ ሰዎች አያቶቻቸው የሚሆኑ ሰዎችን መሳደብና ማዋረዳቸው አግባብ አይደለም ሲሉ ነቅፈዋል፡፡ የወረዳው ዋና ስራ አስፈፃሚ፤ የቤት ማስለካቱ ጉዳይ ተገቢ ነው አይደለም፣ በሶስት ብር ሂሳብ የከፈሉት ክፍያ ልዩነቱ ታስቦ ይመለስ ወይስ በወደፊት ክፍያቸው ላይ ታሳቢ ይሁን፣ ለመሃንዲስና ለታክሲ ይከፈል የተባለው 800 ብር ተገቢ ነው አይደለም የሚለውንና ተያያዥ ጉዳዮችን ከሌሎች የስራ ኃላፊዎች ጋር መክረው የፊታችን ረቡዕ ምላሽ እንደሚሰጡ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡     

Published in ዜና

     ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ 36 ሺህ ሊትር ናፍጣ ከሸጠ በኋላ እንዳይታወቅበት የነዳጅ መላለሻ መኪናውን በእሳት አጋይቷል ተብሎ የተከሰሰ ሾፌር ሰሞኑን በፍ/ቤት ጥፋተኛ ተባለ፡፡ ተከሳሹ ከጅቡቲ 44ሺህ ሊትር ናፍጣ የጫነ መኪና ወደ ጅማ ማድረስ እንደነበረበት የገለፀው አቃቤ ህግ፤ በመሃል የቦቴ መኪናውን እሽግ በመፍታት ከ36 ሺህ በላይ ሊትር በድብቅ ሸጧል ብሏል፡፡ ተከሳሹ ሹፌር ነዳጅ መስረቁና መሸጡ እንዳይታወቅበት፤ የተፈታውን እሽግ መልሶ በማያያዝ መኪናውን በእሳት አቃጥሎታል ብሏል - የፀረ ሙስና አቃቤ ህግ፡፡ በጂማ ስኮሩ ወረዳ አካባቢ ነሐሴ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ማለዳ መኪናውን ከነተሳቢው ያቃጠለው በድንገተኛ አደጋ ቃጠሎ የደረሰበት ለማስመሰል ነው ሲልም ክሱን አስረድቷል፡፡ ሹፌሩ ሀዱሽ ገብረክርስቶስ በአቃቤ ህግ የተጠቀሰበትን ወንጀል እንዳልፈፀመ በመግለፅ፤ የተከራከረ ሲሆን፤ አቃቤ ህግ ግን ተከሳሽ መኪናውን ሲያቃጥል ታይቷል በማለት ምስክሮችን አቅርቧል፡፡ የተሸጠውና የተቃጠለው ነዳጅ ከ600 ሺ ብር በላይ እንደሚያወጣ አቃቤ ህግ ገልፆ፤ ከመኪናው ዋጋ ጋር የ2 ሚሊዮን ብር ንብረት ወድሟል ብሏል፡፡
ጉዳዩን የተመለከተው የፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ ወንጀል ችሎት፣ ሰሞኑን ተከሳሽ
ጥፋተኛ ነው በማለት ፍርድ የሰጠ ሲሆን፤ የቅጣት ውሳኔ ከማስተላለፉ በፊት የቅጣት አስተያየት
ለማድመጥ ለየካቲት 11 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ 

Published in ዜና
Page 12 of 13