የቱሪዝም ጋዜጠኛው ሄኖክ ስዩም ያዘጋጀው “የመንገድ በረከት” የተሰኘ መፅሀፍ በመጪው አርብ ከቀኑ 10፡30 ሰዓት ጀምሮ በብሄራዊ ቤተ-መፃህፍትና ቤተ-መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ እንደሚመረቅ ተገለፀ፡፡
መፅሀፉ በአገራችን አራቱም አቅጣጫዎች ጋዜጠኛው ተዘዋውሮ የጎበኛቸውን የቱሪስት መስህቦች የሚያስቃኝ ሲሆን ከአንድ ወር በፊት ለንባብ መብቃቱ ይታወሳል፡፡ ሄኖክ ስዩም የሃገሬ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን መስራችና ስራ አስኪያጅ ሲሆን በየወሩ ቱሪዝም ላይ አተኩሮ የሚወጣው “ቱባ” መፅሄት አሳታሚም ነው፡፡

Saturday, 21 February 2015 13:39

የ100ሺ ብር ግጥም

ዳሽን ቢራ አክሲዮን ማኅበር የመጀመሪያውን ዓመት “ዳሽን የኪነ ጥበባት ሽልማት” ጥር 24 ቀን 2007 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ማካሄዱ ይታወቃል፡፡ በዚሁ ወቅት በስነ - ግጥም ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡ 157 ግጥሞች መካከል 1ኛ በመውጣት 100.000 ብር ሽልማት አሸናፊ የሆነው የሰለሞን ሞገስ ግጥም ከዚህ በታች የቀረበው ነው፡፡

ሕልሞቻችሁን ፈልጉ

በንስር ጉልበቶቻችሁ በጉንዳን ጽኑ ሥርዓት፣
በቆሰለ ጅብ ተጋድሎ በሴቴ ሸረሪት ብልሃት፣
በረቂቅ የጣዝማ ጥበብ በአናብስት የወኔ ሙላት፣
ሕልሞቻችሁን ፈልጉ እስከ ከፍታችሁ አናት፡፡
    በየብስና በባህሩ፣
    በበረሃና በዱሩ፣
    በህዋው ላይ በጠፈሩ፣
    መቼም ይሁን የትም ሥፍራ፣
    በመሬት እንደ አደን ውሻ፤ በሰማይ እንደጆቢራ፣
የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!  
ያንቀላፋውን ማንነት ፍጥረታችሁን ቀስቅሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡
    የየመንገዱ ትብታብ ድር ክንፎቻችሁን ያሰረ፣
    እምቅ ወኔን የፈተተ የእልህ ጉልበት የጨመረ፣
    መገፋት፣ መውደቅ፣ መታሸት፣ መወቀጥን ያስተማረ፣
    እንኳንስ ኖረ ጨለማ እንኳን እሾህ ተፈጠረ፡፡
    አውራ ዶሮ እንኳ በአቅሙ አምፆ ባይሆን በቁጣ፣
    መች ያየው ነበር ዓለሙን ቅርፊቱን ሰብሮ ባይወጣ?
    ወትሮስ ጨለማ ከምንጩ፣ ፅልመት ፊቱን ባይፈጠር፣
    ብራው ቀን ጨለማ አልነበር?
    ወርቅም ዘመን እስኪያነሳው፣
    አፈር ላይ ነው የሚተኛው፡፡
    እና…
የውስጣችሁን ዝማሬ የነፍሶቻችሁን ቅኝት፣
የልባችሁን ተመስጦ የሕልሞቻችሁን ምሪት፣
የተፈጥሯችሁን ጥሪ የመሻታችሁን ትዕይንት፣
    የናፍቆት በገናችሁን የተስፋችሁን ነጋሪት፤
    የልባችሁን ውብ ቋንቋ፣
    የውስጣችሁን ሙዚቃ፤
    ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ አልሙ፣
    በእውቀት፣ በጥበብ ማማ ላይ  በኩራት፣ በክብር ቁሙ፡፡
        እንደ ሰንደቅ ዓላማ ክብር በከፍታ እንድታርጉ፣
        መደንዘዝ የሰወረውን መክሊታችሁን ፈልጉ፡፡
        በራስ ለራስ ዋጋ ማነስ ቅስማችሁን አታድቅቁ፣
        በተስፋ ማጣት ስብራት ስፍራችሁን አትልቀቁ፣
        ከአፈር፣ ከጭቃ መሃል ነው የሚገኘው እፁብ ወርቁ፡፡
        ጋንም እንደጥራጊ የትም መበተን ምን ይሆን?
        ዋርካ ሲቻል ሰንሰል መሆን፡፡
        በሉ እንጂ ጃል!            
በልባችሁ ላይ ያለውን ጭሱን፣ ጭጋጉን ጥረጉ፣
የነፍሳችሁን ብርሃን ሕልሞቻችሁን ፈልጉ፡፡
          ለአደን፣ ለግዳይ ተነሱ!
        እምቅ ብቃትን አስሱ!!
    የኑሮ ውጣ ውረዱ ቁልቁለትና ዳገቱ፣
    የብቸኝነት በረሃው ራብ፣ ጥምና እንግልቱ፣
    አሻጋሪ የለሽ ባህር የቀን ጨለማው ብርታቱ፣
    የአማሳኙ፣ የአዋሻኪው፣ የሸንጋዩ፣ የጽልመቱ፤
    ሕልም ካለ ይታለፋል!
ጉም፣ ጭጋጉ ይገፈፋል፡፡
ምሬት ገ’ተህ፤ እንባ አቁመህ፤ ሰበብ ጥለህ እልህ ጨምር፣
ብሶት ትተህ ማርሽ ቀይር፣
የነግ ፀሐይ ጎህ ሲወለድ፤ መጪው ዘመን አቤት ሲያምር!!
ስንት ንቀት ቢለጥፉ ስንት አሉታ ቢከምሩ፣
አበበ ነው ድል ያ’ረገው ይህን ዓለም በሌጣ እግሩ፡፡
አትሰወር!  አትደበቅ!  አንተም ንገስ በከፍታ፣
ተራራ  ሁን ወይ ኮረብታ፡፡
    ንሳ ጎበዝ!
    በጎ ተስፋ ካላለሙ ዕድሜ ከሆነ ሕልም የለሽ፣
    እንደ ደረቀ ቅጠል ነው የሰው ሕይወት ረብ የለሽ፡፡
    ራዕይ የሌለው አገር ሕልም የሌለው ትውልድማ፣
    ነፍስ የሌለው አሻንጉሊት መብራት የጠፋው ከተማ፡፡
    አዎን ጎበዝ!....
ዘመናችሁ እንዲከብር ዱካችሁ “ እከሌ” እንዲሰኝ፣
ሕይወታችሁ እንዲጣፍጥ ኑሯችሁ ትርጉም እንዲያገኝ፤
ስማችሁ በምርጦች ተራ በቀለመ - ወርቅ እንዲፃፍ፣
ፍሬያችሁ ከዘመን ዘመን እርሿችሁ ለትውልድ እንዲያልፍ፤
ተነሱ በአጭር ታጠቁ! ወገባችሁን ሸብ አ’ርጉ፣
መክሊታችሁን አስሱ ሕልሞቻችሁን ፈልጉ!!
የእናት አባት ብቻ አ’ደለም አምጦ የመፍጠር ግዱ፣
ሕልማችሁን ፀንሳችሁ እራሳችሁን ውለዱ፡፡
    የድል፣ የአርበኝነት ውሎን ለየራሳችሁ ንገሩ፣
    እንደ ያሬድ ሰባቴ ነው ወድቆ መነሳት ምስጢሩ፡፡
    መንገዳችሁ ላይ ከበራው አምፖል ከያዘው ሰማዩ፣
    ሕልም ይበልጣል ከፀሐዩ፡፡
    የሰው ልጆች ሆይ ተነሱ!
    ያንቀላፋውን ተፈጥሮ እምቅታችሁን ቀስቅሱ፣
    ጉልበታችሁን አበርቱ፤ ክንፎቻችሁን አድሱ፣
መክሊታችሁን ፈልጉ ሕልሞቻችሁን አስሱ፡፡

Published in ጥበብ

በበሃይሉ ዋሴ ተደርሶ በፍቅረየሱስ ድንበሩ የተዘጋጀውና በኩል ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበው “ሰኔ 30” የተሰኘ ፊልም ነገ በሁሉም የግል ሲኒማ ቤቶች እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡ በሰላም አሰፋ ፕሮዱዩስ የተደረገውና የ1፡42 ርዝማኔ ያለው ፊልሙ፤ ፍቅራቸውን ለመቀጠል ወይም ለማቆም ውሳኔ ላይ ለመድረስ ሰኔ 30 ቀን የተቀጣጠሩ ፍቅረኛሞች ላይ የሚያጠነጥን ነው ተብሏል። በፊልሙ ላይ ሽመልስ አበራ፣ ሰለሞን ሙሄ፤ አዚዛ መሃመድ፣ ካሌብ ደሳለኝ፣ ቤልሰን ንጋቱና ሌሎችም ተውነውበታል፡፡
ደራሲው በሃይሉ ዋሴ ከዚህ ቀደም “በልደቴ ቀን”፣ “ያ ልጅ” እና “አይራቅ” የተሰኙ የፊልም ጽሁፎችን የደረሰ ሲሆን ዳይሬክተሩ ፍቅረየሱስ ድንበሩ ደግሞ “አይራቅ”፣ “አምራን” እና “እኔ እና አንቺ” የሚሉትን ፊልሞች እንዳዘጋጀ ተጠቁሟል። ፊልሙ ከነገው ምርቃት በተጨማሪ የካቲት 23 ቀን 2007 ዓ.ም በአዶት ሲኒማና ቴአትር ቤት እንደሚመረቅም ለማወቅ ተችሏል፡፡

      በ17 ዘርፎች ተከፍሎ ለወራት ሲካሄድ የቆየው ሁለተኛው ዙር የጉማ ፊልም ሽልማት ውድድር አሸናፊዎች ከነገ ወዲያ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቴአትር ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ በሚደረገው ሥነስርዓት እንደሚሸለሙ  የፕሮግራሙ አዘጋጆቹ ገለፁ፡፡ በኢትዮ ፊልምስ ባለቤትነት በተዘጋጀው በዚህ ውድድር፤ ከ17 ዘርፎች ምርጥ አምስቶቹ ባለፈው ጥር 7 ቀን 2007 ዓ.ም በሃርመኒ ሆቴል ይፋ የተደረጉ ሲሆን የፊታችን ሰኞ የመጨረሻዎቹ አሸናፊዎች ለክብር ሽልማት ይበቃሉ ተብሏል፡፡ በሥነ ሥርዓቱ ላይ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ ፊልም አፍቃሪዎች፣ አምባሳደሮች፣ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ በእለቱ በበደሌ ቢራ የገንዘብ ሽልማት የሚደረግለት አንድ ባለሙያ እንዳለ የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ተሸላሚው ማን እንደሆነ እንደማያውቁና ሽልማቱም ሰርፕራይዝ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ የሽልማት ስነ-ስርዓቱ በቀይ ምንጣፍ ሥነ ሥርዓት እንደሚካሄድ ተጠቁሟል፡፡

ባለፈው ሳምንት በምናርክ ሆቴል የተከፈተው “ህብር ሶስት” የስዕል አውደ ርዕይ ትላንት መጠናቀቁን አዘጋጁ “ኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ” መስራችና ዳይሬክተር ሰዓሊ ኤፍሬም ለሚ ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡ ከ135 በላይ የሆኑ የ30 ሰዓሊያን ስራዎች የቀረበበት አውደ ርዕዩ፤ በበርካታ የጥበብ አፍቃሪዎች ተጎብኝቷል ተብሏል፡፡ በዚህ አውደ ርዕይ የእንጦጦ ቴክኒክና ሙያ እንዲሁም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስዕል መምህራን ስራዎችም ለዕይታ እንደበቁ ታውቋል። ከዚህ ቀደም “ህብር አንድ” እና “ህብር ሁለት” የስዕል አውደ ርዕዮች በራዲሰን ብሉ እና በምናርክ ሆቴሎች ተዘጋጅተው እንደነበር አስታውሷል፡፡   

Saturday, 21 February 2015 13:31

የቀለም ቆጠራ ጉዳይ

የአማርኛ ሥነ ድምፀልሳን (ፎኖሎጂ) በአጠቃላይ፣ በተለይ ደግሞ የቀለም ቆጠራ በሙላት እና በቅጡ ያልተጠና በመሆኑ በዚህ መስክ እስካሁን ያለን ዕውቀት ያልተሟላ፣ ያልተደራጀና “ግልብ” ዓይነት ነው ማለት ሳይቻል አይቀርም። በአማርኛ ሥነግጥም የቀለም ቆጠራ መርህ በብዙ መልኩ የተዛባና አሳሳች ሆኖ በመቆየቱ፣ የግጥም ዓይነቶች ምደባችንም እንደዚሁ ቅጣንባር የሌለው ወደመሆኑ ተቃርቧል።
ይህንን መወናበድ ዮሐንስ ሰ. የተባሉ ጸሃፊ በጋዜጣችሁ ባቀረቧቸው መጣጥፎች ማለፊያ አድርገው አቅርበውታል። ጸሐፊው ነቅሰው ያወጡዋቸው ስህተቶችና መደናገሮች ትክክለኛ እና ተገቢ ሆነው አግኝቼአቸዋለሁ።
ዕውቀት እምነት አይደለም፤ ይመረመራል፤ ይፈተሻል፤ በየጊዜውም ይሻሻላል። ዕውቀትን በጭፍን ተቀብሎ አምልኮ ማድረግ ከጠማማና ከጽልመት ጎዳና አያወጣም። በቅጡ የተረዱትን ምርመራ በትሁት ድፍረት ማቅረብም ተገቢና የሕልውናም ጉዳይ ነው።
ስለ አማርኛ ሥነግጥም እስካሁን ከቀረቡት ሐተታዎች የመንግስቱ ለማ በብዙ መልኩ የተሻለው ነው፤ ጥቂት ማጠናከሪያ ግን ያስፈልገዋል። የብርሃኑ ገበየሁ፣ “የአማርኛ ሥነግጥም” በብዙ መልኩ የተሟላና  የተደከመበት ነው። ነገር ግን፣ በተለይ ቀለም ቆጠራንና፣ የግጥም ምደባዎችን በተመለከተ ብዙ እንከኖች አሉበት። መጽሐፉ ማስተካከያና እርማቶች ተደርገውበት፣ በሁለተኛ ኤዲሽን፣ ሊታተም ይገባ ነበረ። ነገር ግን ይሔን እንዳንጠብቅ የሚያደርገን አሳዛኝ ነገር አለ፤ አሁን ደራሲው በሕይወት የለም።
በየትኛውም መንገድ ቢሆን በአንድ የዕውቀት ዘርፍ ላይ አማራጭ መጻሕፍት የመኖራቸው ፋይዳ አሌ የሚባል አይደለም። በዚህ አጋጣሚ፣ በቅርቡ ለሕትመት የሚበቃ የአማርኛ ሥነግጥም መጽሐፍ በዝግጅት ላይ እንደሆነ ብገልጽም መልካም ነው።
በማጠቃለያውም፣ ዮሀንስ ሰ. የተባሉት ጸሐፊ፣ ላቀረቡት ማለፊያ ትንተና፣ ከልቤ ያደንቅኋቸው መሆኑን መግለጽ እወዳለሁ።
አብነት ስሜ፤ (የቋንቋና የሥነጽሑፍ መምህር፣ የ“ኢትዮጵያ ኮከብ” እና የ“ፍካሬ ኢትዮጵያ” ደራሲ)

Published in ጥበብ
Saturday, 21 February 2015 13:29

የፍቅር ጥግ

ማን እንደሚያደንቅህና እንደሚወድህ ንገረኝና ማንነትህን እነግርሃለሁ፡፡
ኢሪክ ፍሮም
የማያፈቅር ልብ ከሚኖረኝ ይልቅ የማያዩ ዓይኖች፣ የማይሰሙ ጆሮዎች፣ የማይናገሩ ከናፍሮች ቢኖሩኝ እመርጣለሁ፡፡
ሮበርት ቲዞን
ፍቅር፤ ለሁሉም እጅ ቅርብና በማንኛውም ወቅት የሚበቅል ፍሬ ነው፡፡
ማዘር ቴሬዛ
ሰዎች ኢ-ተጠያቂያዊ፣ በምክን የማይመሩና ራስ ወዳድ ናቸው፡፡ ሆኖም ውደዷቸው፡፡
ኬንት ኤም.ኪዝ
በህልምና በፍቅር ውስጥ የማይቻሉ ነገሮች የሉም፡፡
ዣኖስ አራኒ
አፍቅሮ ማግኘት ምርጥ ነው፡፡ አፍቅሮ ማጣት ሁለተኛው ምርጥ ነገር ነው፡፡
ዊሊያም ሜክፒስ ቻክሬ
ብዙ ጊዜ ፍቅር ይዞኛል … ሁሌም ካንቺ ጋር ነው፡፡
ማንነቱ ያልታወቀ ፀሓፊ  
ፍቅር ዓመታትን የመቁጠር ጉዳይ አይደለም … ዓመታቱን ትርጉም ያላቸው ማድረግ እንጂ፡፡
ሚሼል አማንድ
ገነት ሁሌም ፍቅር በከተመበት ስፍራ ይገኛል፡፡
ጆሃን ፖል ፍሬድሪክ ሪሽተር
እውነተኛ የፍቅር ታሪኮች ጨርሶ ማለቂያ የላቸውም፡፡
ሪቻርድ ባች
ለመፋቀር በተመሳሳይ መንገድ ማሰብ የለብንም፡፡
ፍራንሲስ ዴቪድ
ጨቅላ ፍቅር፤ “ስለምፈልግሽ እወድሻለሁ” ሲል፣
የበሰለ ፍቅር፤ “ስለምወድሽ እፈልግሻለሁ” ይላል፡፡
ኤሪክ ፍሮም

Published in ጥበብ
Saturday, 21 February 2015 13:18

በረከት መቀበል ማን ይጠላል?

      ጋዜጠኛ ሔኖክ ስዩም፤ በ150 ገጾች የተቀነበበውን የጥበብ ሥራውን በመንገድ በረከት ስም ተይቦ፣ እንካችሁ እያለ በግብዣ ያግደረድረናል። ወደ ግብዣው ለመዝለቅ ስንዳዳ፣ እንደ እልፍኝ አስከልካይ ከፊት ለፊታችን የተደነቀረው የቀላ ሰማይ - አድማስ - የሽፋን ስዕል ነው፡፡ በእርግጥም ጉዞው ፍዝ አይደለም። የተሳፈርንበት የምናብ ታንኳ ከፍ ዝቅ እያደረገን፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያን በወፍ በረር ያስቃኘንና አፍታም ሳይፈጅበት ወደ ሰሜን ሰማይ ጠቀስ ተራሮች አናት ላይ ሊሰቅለን ክፉኛ ይጣደፋል፡፡ በጉዞው ላይ በግኡዝ ውበት ብቻ ተደምሞ ተሰብስቦ መቀመጥ አያስችልም፡፡ ለሚታየውም ለማይታየውም ቀልብን መስጠት ግድ ይላል፡፡
አስጎብኚው ብዕረኛ፣ የእርካታችን ጣሪያ በታሪካዊ ቅርሶቻችን ላይ ብቻ ተሸብቦ እንዳይቀር በማሰብ  ወደ ስነልቦናው ጎራ እንድንዘልቅ ብዙ ምልከታዎችን ያለ ስስት ያቀብለናል፡፡ ይህንንም የሚያደርገው በሆደሰፊነት ነው፡፡ በታሪኩ ላይ ለተሰለፉት ዘማዊያን ብሽቀት፣ ምሬትና ብሶት ጆሮ አይነፍጋቸውም፡፡ ምሬታቸውን፣ ምልከታቸውን እንደ ግኡዝ ቅርስ ዓይን አዋጅ ሊያደርግብን በብርቱ ይውተረተራል፡፡
የደራሲው ምናባዊ የማውጠንጠን ደረጃን አንጀት አርስነት ለመመስከር ገና የመጀመሪያ ገጾች አፋፍ ላይ ቆመን መጣደፋችንን እንጀምራለን፡፡ በገጽ 7 ላይ ጅማን ሲያስተዋውቀን እንዲህ ብሎ ይጀምራል፡
“ይህቺ ያደላት ሀገር ተኝታለች፣ስንቶቹ የእሷ እኩዮች ጨንቋቸው እንቅልፍ ካጡ ስንት ዓመታቸው?....እውነት የምታንቀላፋ….ስትተኛ መላ አካሏ ይተኛል…ከመላ አካሏ ላይ እንደምንም እንነሳለን፤ጎህ ስለቀደደ ሳይሆን፣ ወፎቹ ስለጮኹ ሳይሆን፣ ወፎቹ አላስተኛ ስላሉን…….ግን ወፎቹ ማን እንደሚያስጮኻቸው ሳስብ፣ ሳስብ…..የላካቸውን እደርስበታለሁ። አሜሪካ፣ካናዳ፣ኢጣሊያ፣….እነዚያ..ብዙ..ሀገራት.ስማቸው..የበዛ…ወሬያቸው.የበዛ--.የሚናፈቁ--.ከነአኖች--.እነሱ ሀገር ያሉ ወፎች ሥራ የኔን ሀገር ሰው በጠዋት መቀስቀስ ነው፡፡”
እዚህ ጋር የጅማን ፍዝነት፣ ማንጎላዠት አስታኮ ስለ ወል ድብታችን አብዝቶ የሚደሰኩር ይመስላል፡፡ በጸጉረ ልውጡ ዓለም መሽቶ እስኪነጋ ብክነት፣ወከባና  ሩጫ ነው፡፡ እዚህ ምንም እንዳልተፈጠረ ለሽ ብሎ ማሸለብ የአዘቦት ልማድ ነው፡፡ በጅማ የተመሰለን ግብር፣ ተከናንቦ የወደቀ ሰብዕናን ለመቀስቀስ ይህን አይነቱን የስላቅ ፍላፃ ሳያሰለስ ያስወነጭፋል፡፡
በምናባዊ ሽርሽሩ ቅርሶች ብቻ አይደሉም አይን እንዲይዙ የተፈቀደላቸው፡፡ ዥንጉርጉሩ ስነልቦናም እይታችንን ሊያጥበረብረን አብዝቶ ይተጋል፡፡ ከገጽ ወደ ገጽ በተራመድን ቁጥር የመታደስ ጥምን ከመቁረጥ የሚያደነቃቅፉን ጉሽ ስነልቦናዎች ከፊት ለፊታችን ይበዛሉ። ሰላም አየለ የምትባል ዘማዊት ደግሞ ጉሹን ልታስጎነጨን የኮማሪነትን ዘውድ ደፍታ ወዲህ ወዲያ ትላለች።  ኮረዳዋ በደራሲው የቴፕ  ቆይታ ላይ እንደ ሀገር ተነጥፋ ለዓውደ ርዕይ የምትቀርብ፣ እድሜዋን በብዙ ርቀት ያስከነዳች ትንግርት ናት። አካባቢዋን፣ገዢዎቿን ባላት አቅም ትሞግታለች፤
“አንድ ጊዜ በዓል ላይ ሀረር ሄድኩ፣ የመጨረሻዋ እህቴ ስለ ኢትዮጰያዊነት ወላ ሃንቲ የምታውቀው ነገር የለም፡፡ በኦሮሚኛ ስለ ኦሮሚያ ውበት ትዘምራለች። ውቢቷን ኢትዮጲያ እንዳታወድስ የምትማረው ነገር አጥሯታል፡፡ በቋንቋዋ ስለ አባይ ብትዘምርስ?ጎጃሜው ለሶፍ ዑመር ቢቀኝ?እርስ በእርስ የነበረንን ትስስር በጥሳችሁታል፡፡በማይመች መንገድ ተጉዘን ያፀናነውን አንድነት መንገድ ሰርታችሁ አፍርሳችሁታል፡፡በእርግጥ ተስርቷል፤ብትመጣበት ግን ከየት መጣህ የሚለው ጥያቄ ምላሽ የመጣህበት ስፍራ ያንተ እንዳልሆነ ይነግርሃል፡፡ ” ገጽ 38
ከመሬት ከፍ ያላለችው አንዲት ፍሬ ልጅ እንዲህ ያለውን ቋጥኝ እውነት ስታቀብለን ግርምታችን ይጋነንብናል፡፡ ኮሌጅ መበጠስ ድሮ ቀረ ብለን እንዳንቆጭ፣ ሰላም አየለ በእዚህኛውና በወዲያኛው ትውልድ መኻከል እንደ ድንበር ቆማ ትከላከለናለች። ይኽቺ ለአቅመ-ብስለት ተጣድፋ የደረሰች ኮረዳ፣ የምትነፍሰው አውነት ትንታግ ነው፡፡ ከመንፈስ ሸለቆ ዘልቆ የሚገባ ውስጥን የሚበሳ አረር፡፡
ተጓዡ  ብዕረኛ ከስነልቦናው ዓውደ ርዕይ ለጊዜው ገሸሽ አድርጎን ከእናት ተፈጥሮ ጋር በተፈጥሮ ቋንቋ አንድ ሁለት እንድንባባል ወደ ምድረ ገነቱ የሸካ ጫካ እንደ በትር እየመራን ያስገባናል፡፡ የሀገራችን ከያኒያን የዘነጓቸው የውበት ፈርጦች - የሻካ ጫካዎች- እዚህ አስተዋሽ አግኝተው፣ አብዝተው ሲፈግጉ ከአይናችን ይገባሉ። በእርግጥም እነኚህ የውበት ዋርካዎች እንደ አልባሌ ቸል መባላቸው፣ጥበብ መወደሷን መነፈጓ ከፉኛ ይከነክናል፡፡ ምንአልባትም ከያኒያኖቻችን የቸኩ/cliché/ ስንኞችን እየደረደሩ ከሚያታክቱን ለእንደነዚህ ላሉ ድንግል የውበት ፈርጦች  ፊት መስጠትን ቢያውቁበት ምንኛ መንፈሳችን ከፍታ ላይ ባንጠላጠሉት ብለን እንቆጫለን፡፡ ገጽ 68 ላይ በሰፈረው በደራሲው ግርምት እንደመማለን፣
“እግር ጉረኛ ነው፡፡ ፎቅ ሲመለከት ባለመብረክረኩ ጀግና ይመስላል፤ግን ውሸታም ነው፡፡ ሸካ ደን መሃል ሲርበተበት ብታዩት?ቆንጆ ሴት ብቻ የምታፈዝ ይመስለኝ ነበር፡፡ ሺ አመንዘራ ቢሆኑ ተፈጥሮ እንዲህ ተኳኩላ ከወጣች ትበልጣለች፡፡ ለነገሩ ጉደኛም ሰው አለ…..ይህን መሳይ ደን ቢያሳዩት ለአስገድዶ መድፈር እንደምን ይመቻል ብሎ የሚያስብ ሰው፤ከዚህ ዓይነቱም ሰው ግን የሚበልጠው ጉድ የሸካ ተፈጥሮ ነው፡፡”
እንዲህ በሸካ ደን የውበት ድባብ አቅላችንን ጥለን ሳንጨረስ እያዋከበ ወደ ሌላ ቆፈን ውስጥ ይጨምረናል፡፡ ከምቾት አቀበት ላይ እያዳፋ ወደ ትካዜ ተዳፋት ውስጥ ያንደረድረናል፡፡ በቁዘማው ተዳፋት ላይ ደግሞ ሀብታሙ ከሚባል ሰው ጋር እንተዋወቃለን፡፡ ይህን ባለ ስል አእምሮ ኮበሌ፣ ደራሲው ጉዞውን ከደቡብ ምዕራብ ጠቅሎ ወደ ሰሜን ሲጓዝ ደብረብርሃን ከተማ ላይ ያገኘው የመንገድ ሲሳይ ነው፡፡ ሀብታሙ ስለ ባህላችን፣ ስለ እምነታችን ፣ስለ ዕውቀት ልምዳችን ተቆጭቶ ተቆጭቶ ከአንጀቱ አልጠጋ ይለዋል፡፡ በገጽ 100 ላይ እንዲህ አድርጎ ይናደፋል፡
 “ከሰለሞን ቤት የተቀዳው ጥበብ እኛ ሀገር የሞት ፍርድ ተፈርዶበት እንኳን እየኖረ ነው፡፡ በረዶ ከሰማይ የሚበትን እልፍ ደብተራ መደብ ላይ እያደረ በረሃብ ሲመታ፣የግብርና ቴክኖሎጂ ብላ የማታውቀውን ሙጥኝ ብላ አሳሯን የምታይ ሀገር “
ከቆፈኑ ተዳፋት አሁንም አልወጣንም፤ ሀገር ቸል ስላላቸው ባለ ገድለ ብዙ ጀግኖቻችን ከንፈራችንን ለመምጠጥ ሰሜን ሸዋ አንጎለላ ኪዳነ ምህረት ላይ ሀዘን እንቀመጣለን፡፡ እዚህ ስፍራ ላይ የአደዋው አድባር የፊታአውራሪ ገበየሁ አስክሬን እንደ አልባሌ ተጥሏል፡፡ ገጽ 104-105 ከሰፈረው በጥቂቱ፡
“ ገበየሁ ቢሞት ተተካ ባልቻ
 መድፍ አገላባጭ ብቻ ለብቻ
 የተባለላቸው ፊታውራሪ ገበየሁ፤ አይረሴ የአድዋ ጌጥና የጥቁር ሕዝቦች ሰማዕት ናቸው፡፡ አሁን ከፊቱ የቆምኩት የአድዋው የጦር ሳይንሳት አጽም ዘንድ ነው፡፡ ምቹ ባልሆነ ኹኔታ አንጎለላ ኪዳነ ምህረት ተቀምጦ ለጎብኚ ይታያል፡፡”
ለጀግኖቻችንን የምንሰጠው ክብር ምን ያህል እንደሆነ የጀግናው ገበየሁ አጽም ዋቢ ምስክር ነው:፡ ታሪክ የሞሸሩትን፣ ታሪክ የቀለሱትን ኹነኛ ሰዎችን እንዲህ እንደ አልባሌ ከጉድባ ውስጥ ሸሽገናቸው ስለ ታሪክ ሀብታምነታችን ብንለፍፍ ትርፉ ጉንጭ ማልፋት ይሆናል፡፡  
ብዕረኛው አስጎብኚያችን በጀግኖቻችን አመድ አፋሽነት የተሰማንን የስሜት ማሽቆልቆል ያጤነ ይመስል የመንፈስ ከፍታን በቦታ ከፍታ ሊያድስ ወደ ሰማይ ባልንጀሮቹ የሰሜን ተራሮች እንደ መንኮራኮር ይዞን ሽቅብ ይመነደጋል፡፡ በእርግጥም እዚህ ጋ በጉዞው ማሳረጊያችን ላይ ሆነን ትንሽ አየር መሰብሰብ እንጀምራለን፡፡
 አስጎብኚያችን ተራሮቹን ሲያስተዋውቀን አንዳንድ ቱባ እውነታዎችን እንደ ዋዛ ያነሳና በኩርማን አንቀጽ  አኮስምኖ ያልፋቸዋል። ሰሜን ተራራዎች ላይ የደራሲውን ንፉግነት በደንብ እናስተውልበታለን፡፡ ካራ ምሽግ ላይ ያሳየውን ስስት በየዳ ላይ ይደግመዋል፡፡ በተለያዩ መንግሥታት ከባድ የትጥቅ ትግል ስላስተናገደ ስፍራ ከስም የዘለለ ምንም አይነት መረጃ አላስጨበጠንም፡፡ ስፍራዎቹ ከትጥቅ ትግል ጋር ያላቸው ታሪካዊ ትስስር ወጋ ወጋ ተደርጎ፣ በስም ብቻ ተጠቅሶ ማለፉ የአንባቢን ስሜት ያቆረፍዳል። ቢያንስ የማሻዋን ሜሪ እና የቴፒዋን ሰላም አየለ ያህል ትኩረት ሊሰጣቸው በተገባ ነበር። ታሪካዊ ቅርሶቹ ብዙ ሊወራባቸው የሚችሉ፣ ቢቆሰቆሱ ትልቅ የፖለቲካ ዓውድን የሚከፍቱ ዓይን ማረፊያዎች እንደሆኑ እየታወቀ እንደ ዋዛ ዳምጧቸው ማለፉ እንደ አንድ ድክመት ሊቆጠር ይችላል፡፡
ሌላው የደራሲው ድክመት አንዳንድ መረጃዎችን ሲሰጠን የሚያሳየው ዝንጉነት ነው። ለምሳሌ በአፋር ስለሚገኘው እሾሃማ ዛፍ ሲያስተዋውቀን፣ ሀገሬው “ወያኔ” ዛፍ እያለ እንደሚጠራው ይነግረናል፡፡ ዛፉ በእሾሃማነቱ የተነሳ በኣካባቢው ኅብረተሰብ ላይ ሁለንተናዊ ኪሳራ ያደረሰ ነው፡፡ የቀዬውን ከብት በየጊዜው ጭዳ እያደረገ ሀገሬውን ከማራቆትም አልፎ  የአካባቢውን በረሃማነት በማባባስ  የነዋሪው ራስምታት ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡
ዛፉ ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር የተዋወቀው በኃይለስላሴ ዘመነ መንግሥት ሆኖ ሳለ፣ ግብሩ ከመጠሪያው ጋር ያለውን ዝምድና ከመነሻው አንስቶ ጫን ብሎ ሊያስተዋውቀን አለመድፈሩን ስናስብ በሰጠን መረጃ ተአማኒነት ላይ ጥርጣሬ እንዲያድርብን ያደርገናል፡፡ ቴፒ ላይ ደራሲው በሚያሳየን ክልክ ያለፈ እርጋታ ትዕግስታችን ሊከዳን ይፈታተነናል፡፡ አንዳንዴ እንደውም ጉዞውን ከእነካቴው የዘነጋው እስኪመስልን ድረስ “ቀዥቃዣነቱን” ለመቃረም አብዝተን እንባትታለን፡፡ ስለ አካባቢው ታሪካዊና ባህላዊ ቅርሶች ከሚነገርን በገገነ መልኩ ከሴተኛ አዳሪዎች ጋር ስለነበረው ቅርርብ ከልክ በላይ በመዘርዘር ጊዜውን ያጠፋል፡፡ ለታሪክ ፍሰትና ማራኪነት ሲባል በአካባቢው ልንተዋወቃቸው የሚገቡ ታሪካዊ ስፍራዎች  ቸል ተብለዋል ፡፡
 በተረፈ ጋዜጠኛ ሔኖክ ስዩም፣ ጅምሩና የሔደበት ርቀት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ ወደፊት ሁሉንም የሀገራችንን ስፍራዎች ያካለለ የጉዞ ማስታወሻን ዳጎስ ባለ የመጽሐፍ ቁመና  እንደሚያስተዋውቀን እምነቴ ነው፡፡       

Published in ጥበብ
Saturday, 21 February 2015 13:18

ድንገተኛው ሞት (Heart Attack)

 ለዓመታት የዘለቀውን ድብቅ ፍቅራቸውን ይፋ አውጥተው ሶስት ጉልቻ የሚመሰርቱባትን ቀን ሁለቱም በጉጉት ሲጠባበቋት ቆይተዋል፡፡ ባለፈው ጥር ወር አጋማሽ ላይ የዓለም ይሁን ተብለው ሊዳሩ ደፋ ቀናውን ከርመውበታል፡፡ የሰርግ ድግሱን የሁለቱም ወጣቶች ቤተሰቦች ተያይዘውታል፡፡ የሰርግ አዳራሽና ዲኮሩ፣ የመኪና ኪራዩ፣ የቬሎና የፀጉር ሥራ ዝግጅቱ ሁሉ ተጠናቋል፡፡ “ለህፃናት ቦታ የለንም” የሚለው የሰርግ መጥሪያ ካርድም ታድሎ አልቋል፡፡ ሙሽራውና ሙሽራዋ ከሚዜዎቻቸው ጋር የሰርግ ዝግጅቱን አስመልክቶ ውይይት ለማድረግ እየተሰባሰቡ ማምሸት ከጀመሩም ሰነባብተዋል። ሁለቱ ሙሽሮች በሚዜዎቻቸው ታጅበው አንድነታቸውን የሚያበስሩባት ቀን ደርሳለች፡፡
ከሰርጉ ዕለት ሶስት ቀናት በፊት ግን ያልታሰበ አደጋ ተከሰተ፡፡ የሁለቱን ሙሽሮች ህልምና ምኞት ያጨለመ፣ ቤተሰቦቻቸውንና ዘመድ አዝማድን ሁሉ በእጅጉ ያሳዘነ ነበር፡፡ ዕለተ ሐሙስ ምሽት ሙሽራውና ሙሽራዋ ከሚዜዎቻቸው ጋር ስለሰርጉ ዝግጅት የመጨረሻ ውይይታቸውን ለማድረግ ተገናኙ፡፡ ለሁለት ሰዓታት የቆየው ውይይታቸው ሲጠናቀቅ ሙሽራው፣ ሙሽሪትንና ሁለት ሚዜዎቿን ሃያት ኮንደሚኒየም አካባቢ ወደሚገኘው ቤቷ ሊያደርሳት ጉዞ ተጀመረ፡፡ መንገዱ በትራፊክ ተጨናንቋል። ሙሽራው መኪናውን እያሽከረከረ አልፎ አልፎ ደረቱ ላይ በግራ ጐኑ በኩል የሚሰማውን ውጋቱ ስሜት ያዳምጣል፡፡ ውጋቱ ቀኑን ሙሉ ሲሰማው አንደዋለና ብርድ ሳይመታው እንዳልቀረ ለሙሽራዋ ነገራት፡፡ ሳሚት አደባባዩን እንደዞሩ የተጨናነቀው መንገድ ቀለል እያለ ሄደ፡፡ ሙሽራዋ ከሚዜዎቿ ጋር ጨዋታ ይዛለች፡፡ መኪናቸው ድንገት አቅጣጫዋን ስታ ስትወላውል ሁሉም ግራ በተጋባ ስሜት ወደ ሙሽራው አፈጠጡ፡፡ ሙሽራው የመኪናው መሪ ላይ በግንባሩ ተደፍቷል፡፡ ዘዋሪ ያጣችው ተሽከርካሪ ወዲህና ወዲያ እየተላጋች ሄዳ፣ ከአዲሱ የባቡር ሐዲድ ግንብ ጋር ተላትማ ቆመች፡፡ ተሣፋሪዎቹ እሪታቸውን አቀለጡት፡፡ ሥፍራው በአንድ አፍታ በግርግርና ትርምስ ተሞላ፡፡ ከምሽቱ 3 ሰዓት ከሃያ ነበር፡፡ በአካባቢው የነበሩ ፖሊሶችና መንገደኞች መሪው ላይ በግንባሩ የተደፋውን ወጣት እንደምንም ተሸክመው አወጡት፡፡
በሌላ መንገደኛ መኪና ወደ ሆስፒታል ይዘውት በረሩ፡፡ ህይወቱን ለማትረፍ ግን እጅግ ዘግይተው ነበር፡፡ በሆስፒታሉ የሚገኙ የህክምና ባለሙያዎች ወጣቱ ድንገተኛ የልብ ህመም ችግር እንደገጠመው ተረድተው፣ ገና የህክምና እርዳታ ለማድረግ ሲዘጋጁ ህይወቱ አለፈች፡፡
የ34 አመቱ ወጣት ከነብዙ ህልምና ተስፋው ይህችን ዓለም ተሰናበታት፡፡ ሐዘን ልቧን የሰበረው ወጣቷ ሙሽራ የደረሰባትን እጅግ አስከፊ ሐዘን የምትገልጽበት ቃላት የላትም፡፡ የምትወደውንና ነገ የቤቴ አባወራ፣ የምወልደው ልጅ አባት ይሆናል ብላ የምትጠብቀውን ሙሽራዋን በድንገት ተነጥቃ የሁለት ወራት ፅንስ በሆዷ እንደተሸከመች ብቻዋን ቀርታለች፡፡ ሃያት ኮንዶሚኒየም ከሚገኘው የወጣቷ ሙሽሪት ቤት ለቅሶ ደርሼ ስወጣ እንደ ደራሽ ውሃ ድንገት መጥቶ ስለሚወስደው ድንገተኛ የልብ ህመም (Heart Attack) ባለሙያ አነጋግሬ ለአንባቢያን መረጃ ለመስጠት ወሰንኩ፡፡ ለመሆኑ ድንገተኛ የልብ ህመም ምንድነው? መነሻውስ? ችግሩ ሲያጋጥም የሚወሰድ አፋጣኝ የመፍትሔ እርምጃ ይኖር ይሆን?
በደም መተላለፊያ ቧንቧዎች ውስጥ አዝጋሚ በሆነ መንገድ የሚፈጠር ቁስለትና እሱን ተከትሎ በሚመጣ የደም ቧንቧዎች ጥበት ምክንያት የደም ቧንቧዎቹ ደም የማመላለስ አቅማቸው ሲዳከም ወይንም ሙሉ በሙሉ ደም ማመላለሳቸውን ሲያቋርጡ ድንገተኛ የልብ ህመም ይከሰታል፡፡
ቁስለቱ ከፍተኛ በሚሆንበት ጊዜ የደም ቧንቧው ሊቆረጥ ወይንም ሙሉ በሙሉ ሊዘጋ ይችላል፡፡ ይሄኔ የልብ ጡንቻዎች ሥራቸውን ሙሉ በሙሉ ያቆማሉ፡፡  ድንገተኛ የልብ ህመም (Heart attack) የሚባለውንም ያስከትላል፡፡
በጥቁር አንበሣ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ሐኪም የሆኑት ዶክተር አብርሃም ተስፋዬ፤ ድንገተኛ የልብ ህመም (Heart Attack) የሚባለው በሽታ በአብዛኛው በወጣትነትና በጐልማሣነት የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ወንዶችን እንደሚያጠቃም ይናገራሉ፡፡ ለችግሩ መንስኤ ሊሆኑ ይችላሉ ተብለው ከሚጠቀሱት መካከል የስኳር ህመም፣ ደም ግፊት፣ ሲጋራ ማጨስ፣ ከመጠን በላይ የሆነ የሰውነት ክብደት፣ የአልኮል ሱሰኝነትና የዕድሜ መግፋት እንደሚገኙበት ጠቁመዋል፡፡
“አኪዌት ኮርናሪ ሲንድሮም (በልብ ቧንቧ ጥበት ሳቢያ የሚከሰት ድንገተኛና አጣዳፊ ህመም) በተለይ በአደጉ አገራትና በከተሞች አካባቢ ጐልቶ ይታያል። ለዚህም ምክንያቱ ችግሩ ምቾት ከተላበሰ አኗኗር፣ የሰውነት እንቅስቃሴ አለማድረግና የተስተካከለ የአመጋገብ ሥርዓት አለመኖር ጋር ተያይዞ እየጨመረ ስለሚሄድና ሁኔታው በአደጉት አገራትና በተለይም በከተሞች አካባቢ በስፋት ስለሚታይ ነው” ብለዋል። ድንገተኛ የልብ ህመም በአገራችንም እየተበራከተ መምጣቱን የጠቆሙት ዶ/ር አብርሃም፤ ችግሩ ባለፉት ጥቂት አመታት እየጨመረ ከመሄዱም በላይ በአብዛኛው በወጣትነት የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎች የችግሩ ተጠቂ እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡
“በየጊዜው የጤና ምርመራ ማድረግና ራስን ማወቅ፣ በእኛ አገር ህብረተሰብ ዘንድ የተለመደ ነገር ባለመሆኑ በአብዛኛው ችግሮች ተባብሰውና መዳን በማይችሉበት ደረጃ ላይ ደርሰው መታወቃቸው የችግሩ ሰለባዎች መዳን እየቻሉ እንዲሞቱ እያደረጋቸው ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ የደም ግፊት ያለበት ሰው በሽታው እንዳለበት ቀደም ብሎ ቢያውቅና አስፈላጊውን ህክምናና ጥንቃቄ ቢያደርግ በደም ግፊት ሣቢያ ሊከሰት ከሚችለው ድንገተኛ የልብ ህመም (Heart Attack) እና እሱን ተከትሎ ከሚመጣው ድንገተኛ ሞት ሊድን ይችላል ያሉት ዶክተሩ፤ በቀላል ወጪና ያለ ችግር ያለንበትን የጤና ሁኔታ ለማወቅ የምንችልባቸው መንገዶች ስለሚኖሩ ሁላችንም ልንጠነቀቅ ይገባል ብለዋል፡፡
ድንገተኛ የልብ ህመም መነሻ ምክንያቱ ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው በደም ቧንቧዎች ውስጥ በሚፈጠር ቁስለት ሣቢያ የደም ቧንቧዎች ሲጠቡና በውስጣቸው ደም እንደልብ ማስተላለፍ ሲያቅተው ቢሆንም በደም ቧንቧዎች ውስጥ ቁስለት እንዲፈጠር የሚያደርጉ ነገሮች እነዚህ ናቸው ተብለው ሊገለፁ አይችሉም፡፡ ይሁን እንጂ የደም ግፊት፣ ስኳር፣ ያልተስተካከለ የሰውነት ክብደት ያለባቸውና አብዛኛውን ጊዜ በውጥረትና ጭንቀት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች  ለድንገተኛ የልብ ህመም የተጋለጡ ናቸው፡፡
ድንገተኛ የልብ ህመም እንደስሙ ሁሉ በድንገት የሚከሰትና በአጣዳፊ ሁኔታ ለሞት የሚዳርግ ቢሆንም ችግሩ ከመከሰቱ ከሰዓታት አንዳንድ ጊዜም ከቀናት በፊት ምልክቶችን ሊያሣይ ይችላል። በአብዛኛው የተለመደው የድንገተኛ የልብ ህመም ምልክት:- በደረት ላይ በተለይም በግራው የደረታችን ክፍል ተደጋጋሚ የውጋት ስሜት መከሰት፣ ትንፋሽ ማጠርና ማላብ… ጥቂቶቹ ናቸው። አንድ ሰው ድንገተኛ የልብ ህመም ሲገጥመው በፍጥነት ህክምና ካላገኘ በህይወት የመቆየት ዕድሉ እጅግ አነስተኛ ነው፡፡ በተለይም ችግሩ የገጠመው ሰው በእንቅልፍ ላይ እያለ ወይም ተቀምጦ ከሆነ ችግሩ እጅግ አደገኛ ደረጃ ላይ መድረሱን ጠቋሚ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያለ ሰው በደቂቃዎች ጊዜ ውስጥ ህክምና ማግኘት ካልቻለ ህይወቱን የሚያጣበት ዕድል ከፍተኛ ነው፡፡ ድንገተኛ የልብ ህመም ሁላችንም ልንጠነቀቀው የሚገባ አደገኛ በሽታ እንደሆነም ዶክተር አብርሃ አሳስበዋል፡፡      

Published in ዋናው ጤና

“ኩርቢት” ሲነበብ

    ድንቅና ኮስታራ ልቦለዶች ከሚጽፉ ጥቂት ደራስያን አንዱ ዓለማየሁ ገላጋይ ነው። “አጥብያ”፥ “ቅበላ” እና “የብርሃን ፈለጐች”  አያሌ ተደራሲያንን ቢያስደምሙም የሚመጥናቸው ሒሳዊ ንባብ ግን እንደ ተነፈጉ ናቸው። (ኧረ ለመሆኑ ከዘመነኛ -contemporary- ልቦለድ ደራሲያን የማን የፈጠራ ውጤት ለአጥጋቢ ባይሆንም፥ ለበቂ ሒሳዊ ጥናት የተጋለጠው? ያሰኛል።) በየሁለት ሳምንት ፍቃዱ አባይ ይመራውና ያስተባብረው የነበረ የሜይ ደይ መጽሐፍ ግምገማ በሩን መዝጋቱ ለሆነ የሒስ ቦግታ ንፍገትም ነው።
የአስራ አራት አጫጭር ልቦለዶች ስብስብ “ኩርቢት” በታተመበት ወቅት በኤፍ ኤም ሬድዮ ጣቢያዎች በቅብብሎሽ ቢነበብም ጥንካሬና ድክመቱን ጠቋሚ ሒስ የዳሰሰው አይመስለኝም። የመጽሐፉ ርዕስና የሽፋኑ ገፅ ምስል አንዳች የሚደብት፥ አዲስ አንባቢን የማያጓጓ መሆኑም ያብሰከስካል። አመዛኝ ገጾቹ እንደ ዝርግ ግጥም -prose poem- በዘይቤ በተኳሉ፥ ስሜትና እሳቦት በረቀቀባቸው ተናፋቂ መስመሮች ተወረዋል። የድርጊትና ግጭት እንቅስቃሴ መወሳሰብ ጥቂት ገፀባህሪያትን አይረሴ አድርጐ ለመቅረፅ አግዘውታል። በሁለት ገጽ ከጠበበው -ግን ያልተኮማተረ- “ዝግመተ ለውጥ” እስከ ሀያ ሰባት ገጾች በተፍታታው “ኩርቢት” ትረካ  ለአስራ አራት ርዕሶች አንባቢ ምናብና ተመስጦ ለግቷል። ዓለማየሁ ገላጋይ ለመጻሕፍቱ ርዕስና ሽፋን የእንዳለጌታ ከበደ ያክል ምነው በተጠበበበት ያሰኛል። ኩርቢት ማለት “ጋያ፥ ሲጋራ ማጨሻ” ስለሆነ እንደ ተምሣሌት -መጽሐፉን ካነበብን በኋላ - አንድምታዎች ይቀፈቅፋል እንጂ እንደ ሌጣ ርዕስ ስብስቡን አይመጥነውም።
“መጽሐፍ በሽፋኑ አይመዘንም” ቢባልም ሜዳ ላይ ወይም ከመደርደሪያ ሲሰጡ አንባቢን የሚማጠኑ ማራኪ ጥበባዊ ርዕስና ምስል ተድበስብሰው ከመዘለል ይተርፋሉ። ሽፋኑ ሲጠቃቅሰን ደባብሰነው ወደ ጀርባው ጽሑፍ -blurb- እናመራለን፤ ይዘቱን ገረፍ ገረፍ ለማድረግ ገፅ እናገላብጥ ይሆናል። የአንድ ሁለት ደቂቃ ትኩረት ከምናልባት -potential- መጽሐፍ ገዢ መንጠቅ በቂ ነው። ወሳኝ መለኪያ ግን የፈጠራ አቅሙ በጥሞና ለመነበብ የሚመስጠን ከሆነ ነው። እኔ በግሌ የሽፋኑ ጥበባዊ ውበት -ምትሀትም ይሆናል- ከወሰደኝ እያየሁት በሀሳብ ለመሰወር ብቻ እንኳን እገዘዋለሁ። ሰሞኑን ለርዕሱ ተናዳፊነትና ለምስሉ ጥልቀት የከፈልኩበት መጽሐፍ የደራሲው ስም ባይገለጥም፥ ርዕሱ “መጽሓፈ ቆንጥጥ” ሲሆን ምስሉን ለናንተ ማስረዳት ያዳግተኛል፤ ምናልባት ደራሲው ከነቢይ መኮንን የተዋሳቸው ስንኞች ይገልጡት ይሆናል። “ዋናው ማርጀት መቻል/ ከልጅነት ፍቅር፥ ካብሮ አደግ ህሊና፤/ ይበቃል ቀለሙ፥ ይበቃሃል ህልምህ፥ የአእምሮህ ወዘና።” [“የራስክን እሳት ሙቅ” ከሚለው የተቀነጨበ] ሽፋንም ጀርባም ሰንኮፍ ሳይሆኑ ከእምብርቱም ይመዘዛሉ። “ኩርቢት” ከተነበበ በኋላ ባዶና ገለልተኛ ሆነን አንቀጥልም። የተመሰቃቀለ የኑሮ ልምድና ገጠመኝ እውስጣችን ሰርገው ደከምከም ይለናል፤ አንድ ህይወት ሳይሆን በንባብ ተጨማሪ ስለተቋደስን ልቦናችን አይለዝብም። አሜሪካዊ ገጣሚ Joseph Brodsky እንዳለው፤“There are worse crimes than burning books. One of them is not-reading.” (መጽሐፍን በእሳት ከማጋየት የከፋ ወንጀል አለ፤ መጽሐፍ አለማንበባችን፥ ሳይገላለጥ ችላ መባሉ) (ከወንጀሎቹ አንዱ ነው።)
ደራሲው ለትረካው የመለመላቸው ገፀባህሪያት በአመዛኙ በሰከነ፥ በተደላደለ ህይወት አውድ ውስጥ ጊዜን እየላሱ እያሾፉ፣ እንቅልፍ የሚፈትጋቸው አይደሉም። እየተንሳፈፉ ሳይሆን፥ የእለት ጉርስን ፍለጋ በሆነ ጉዳይ ለመለብለብ ኑሮ እየጠለዛቸው፣ “እህታ” እውስጣቸው ተከማችቶ፥ መንገላታትን የተላመዱ ናቸው፤ ስቀው፥ ፎክረው፥ ተፈነካክተው፥ ተፋቅረው ... የተረፋቸውን ዕድሜ በመጠጥም ይሁን በጉስቁልና የሚልጉ ናቸው። ከኖሩትና ከቀሰሙት የኅላዌ ውጥንቅጥ ብዛት የአንድ ግለሰብ መሞት፥ የአያሌ ህይወቶች መክሰም ያክል ህልፈቱ ጥልቅ ነው። እንደ ባለፀጋ ነጠላ ልሙጥ ነፍስ ሳትሆን የታሹ ዥንጉርጉር ነፍሳት ከአንድ አካል ተወሽቀው አፈር ይበላቸዋል። አስራ ሶስት አጭር ልቦለዶቹን ለክፍል ሁለት ንባብ በማቆየት ዛሬ ትኩረቴ ወደ novella - ከአጭር የሰፋ፥ ከአብይ ያነሰ- መጠነኛ ልቦለድ ለመሆን ያደላውን፥ በሃያ ሰባት ገጾች ተደራሲን የሚያስደምም፣ ለስብስቡ ርዕስ የተሾመውን “ኩርቢት” ይሆናል።
ተራኪዋ የአስራ ሁለተኛ ፈተና ውጤት የምትጠብቅ፥ አስራ ስምንት አመት ሊሞላት የተቃረበች ኰረዳ ናት። ከህፃንነቷ ጀምሮ እቤታቸው ተከራይቶ ከነበረ ሠዓሊ -ብሩኬ የምትለው- ጋር የዕድሜዋን ትዝታ እያፍተለተለች፣ እውስጧ እየተብላላ አፍቅራው ድምፁ ጭምር ያነዝራታል።
... ከደቂቃ በፊት ደወለልኝ
“ጣዎሴ” አለኝ። ለምን እንዲህ ብሎ እንደሚጠራኝ ስጠይቀው፥ “የምታምር ወፍ ነሽ” ይለኛል።
“እ?” አልኩት
“የምናውቃቸው ደህና ናቸው?”
የምናውቃቸው ጀንበሯ፥ ዛፎቹ፥ የቀበና ወንዝና አሞራው ናቸው።
“ደህና” አልኩት።
ብሩኬ ስለአራቱ ሲያወራ ስለልጆቹ የተጨነቀ አባት ይመስላል።  [ገፅ 45-46]
ጣዎስ መዝገበ ቃላት ሲፈታው “ኦፈ ገነት፥ ጅራቱ የሚብለጨለጭ፥ አንገቱና ራሱ ሰማያዊ መልክ ያለው ተለቅ ያለና እጅግ የሚያምር ወፍ።” ይለዋል። የተራኪዋ ስም ቤተልሄም -መንፈሳዊ አንድምታ ቢቋጠርም- በጣዎሴ ተነጠቀ፤ ብሩክ ሠዓሊ በመሆኑ የግሉ ዕይታ እየመራው በተፈጥሮና በሰው ይመሰጣል። በዚህ የስልክ ጥሪ የተጀመረ ትረካ፣ ኮረዳዋ -ጣዎሴ- ከልጅነቷ ያጐነቀለውን እድሜዋን በብሩክ እንቅስቃሴ፥ ድርጊትና ንግግር እየመነዘረች ትተርካለች። በማግስቱ ደውሎ “ካንቺ ጋር ማውራት ያለብኝ ነገር አለ። ድብብቁ ቢበቃን ጥሩ ነው” ሲላት ከቀጠራት ካፌ እስክትደርስ ውስጧ ይታመሳል። ይህ በሃያ ሰባት ገጾች የተወሳሰበው ትረካ፣ በዛሬና በማግስቱ ሁለት የስልክ ጥሪዎች መካከል -መቼቱ- የኮረዳዋ የአመታት ትዝታና ኑሮ በምልሰትም በአስተውሎትም ተጥዶባታል። በሃያ አራት ሰአት ውስጥ የተቀነበበ እንቅስቃሴ አያሌ ሰበዞች ከትናንቶች ተመዘውበት የአምስት ገፀባህሪያት ህይወት የኖርነው ያክል ይኮሰኩሰናል።
ቀበና ተወልዳ የቦረቀች ኮረዳ እድገቷ በስዕል ቀለም፥ በብሩሽና በተወጠረ ሽራ እንዲሁም በብሩክ ዘይቤያዊ ገለጣዎች ስለተቦካ አካባቢዋንና ገጠመኞቿን ስትተርክ በገለልተኛ ቋንቋ ሳይሆን ግጥምን በሚያደናግዙ አረፍተ ነገሮች ናቸው። ዓለማየሁ ገላጋይ በተራኪዋ አንደበት የሰዓሊን ርዕዮት የሚያጐላ የረቀቀ ቅኔያዊ ቋንቋ ለማጥለል መካኑ ያስደምማል። ሠዓሊ ጥሩነህ  እሸቱ ወይም ገጣሚ-ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ይህን ልቦለድ አንብበውት፥ እንዴት ቃላት ቀለምና ንድፍ አፍልቀው ከምናባችን ሥዕል ሊወጥሩ መብቃታቸውን በተረጐሙልን ያሰኛል። ሁለቱን የጠቀስኳቸው ለሥዕልና ሥነጽሑፍ ጥምረት አስተውሎታቸው ጥልቅ መሆኑን ስለማውቅ ነው።
“ወቅቱ ክረምት ነበር። እናቴ በሯ ላይ በበርጩማ ተቀምጣለች። በረንዳው ላይ ስጫወት ቆይቼ ወደ ጓሮ ስዞር ብሩኬ የተወጠረ ሸራውን ማስደገፊያ የክፍሉ በር ላይ ገባ አድርጐ አቁሞት አየሁ። ትርጉም አልባ መስመሮች እየሞነጫጨረ ራቅ ቀረብ ይላል።
ራቅ ሲል የጣሪያው ጠፈጠፍ ጀርባው ላይ እየነጠረ የፈንዲሻ ቅርፅ ይሰራል። መስመሮቹ እንደ ወጨፎ ከቀኝ ወደ ግራ በሰያፍ የሚዘንቡ ነበሩ። መስመሮቹን ከማድመቅ ይልቅ ዳር ዳሩን ቱቢት በመሰለ ቀለም ሲያጀበጅብ መቆየቱ ትዕግሥት አስቆራጭ ቢሆንብኝም መከታተሌን ቀጠልኩ። ዳር ዳሩን የሚያንጃብበው ቀለም ለካስ ትርጉም ኖሮታል። ትንሽ አሎሎ ትልቅ አሎሎ ላይ የተቀመጠ መስሎ እየደመቀ የመጣው የሸራው መካከለኛ ክፍል በጥቂት መነካካት በተፈጠሩ መስመሮች ቁጭ ያለች ሴት ናት።
ገረመኝ። በመነካካቱ ቀጥሏል። ጥቂት መስመሮች ሲጨመሩበት ያቺ ቁጭ ያለች ሴት እናቴን መስላ አረፈችው። እጁን ትቼ የብሩኬን ፊት ለማየት ተመቻቸሁ። አንዴም ወደ እናቴ አይመለከትም። እእምሮው ውስጥ ከትቷት ጨርሷል። ከዛ እያወጣ ነበር የሚስላት።
እናቴንና ስዕሉን እያስተያየሁ በመደነቄ ቀጠልኩ። [ገፅ 60]
ሥዕሉ ቀርቶ፥ በቅኔ መመሰጥ የሚቀናው ደራሲ፥ ገጣሚና ሐያሲ ደረጀ በላይነህ የ“ኩርቢት”ን ዝርግ ግጥሞች በተፈተነባቸው ያስመኛል። በአዲሱ “ብሌን” መጽሔት -ቅጽ 8- ረዳት ፕሮፌሰር ቴዎድሮስ ገብሬ [ገፅ 21]፤ “የሥዕልንና የሥነ ጽሑፍን ዝምድና በሌላ ጊዜ ራሱን በቻለ መጣጥፍ የምመለስበት ይመስለኛል” ባለው መሰረት “ኩርቢት”ን  እንዳማይዘነጋ ተስፋ አለኝ። ዘመነኛ የአማርኛ ደራሲያን --አዳም ረታ፥ ዓለማየሁ ገላጋይ፥ በዕውቀቱ ሥዩም ወዘተ-- በፈጠራ ውጤታቸው የልቦለድ እና የግጥምን ዘውጐች በማዋሀድ የተረኩም የተቀኙም ያክል ያስገርሙናል። በ“ኩርቢት” ትረካ እንኳን ብንወሰን ነፃ ግጥም -free verse- እና ዝርግ ግጥም -prose poem- ነቅሰን ማውጣት አያዳግትም። በልቦለዱ ትልምና ድርጊት ተቀዝፈን ስለምንሰምጥ እንጂ ተረጋግተን አንቀጾቹን እንደ ግጥም ብናጤናቸው፥ እንደ ስንኝ ከደረድራናቸው እንፈዛለን።
ዕድሜዋን በመንቀራፈፍ የምታራዝመውን ጀንበር
በትካዜ አያለሁ፥
እንዳማሩ መሞት የዘወትር ዕጣዋ መሆኑ፥
ይሄንን ሀዘን የሚያባብስ ህብረ ዜማ
ከወንዙ ከዛፉና ከነፋሱ ይንቆረቆራሉ።
የራሷ የሆነ ዘለሰኛነት አለው
አልቅሽ አልቅሽ አለኝ። [ገፅ 48]
እንዲህ ስንኞች ቁልቁል ቢጻፉ ነፃ ግጥም እንጂ ምን ሊባል? በውስጠ ምት -rhythm- የራሰው፥ ቤት ባለመድፋቱ እንደ ጥብቅ ግጥም አይሁን እንጂ ነፃ ግጥም ነው። ሰለሞን ደሬሳ --በዘበተ እልፊቱ-- “ስሜትና ቋንቋ ሲቸግርም ሃሳብና ቋንቋ የሚቋለፍበት አደራደር” ወለሎ ግጥም ነው እንዳለው አይነት።
ጀንበሯን የሚያያት እንደደረሰች ኮረዳ
........................
ቁልቁል የተደፋ የወርቅ ዝጉዳ መስላለች፥
የወጨጫ ተራራ እንደ ወለላ
ደርበብ ብሎ የሚወርደውን
ዝልግልግ ብርሃን፥
አፉን ከፍቶ ወደ ሆዱ ይልካል።
ከጩልሌው መንድፍደፍ ጋር
የዛፍ ፍሬዎች
የወርቅ እንባ እየመሰሉ


ፉ።
[ገፅ 47 ተመልሶ 46]
ብርሃኑ ገበየሁ ይህን ዘውግ በጥሞና አስረጅ እየጠቀሰ አጥንቶታል። [የአማርኛ ሥነግጥም፥ ገፅ 251-260] “... ገጣሚያን ቀንበር ከሆነባቸው ጥቂት የምጣኔ ህግጋትና የተወሰነ የቤት አመታት ስልቶች በመላቀቅ እምብዛም ለነባር ህጐች የማይገዛ፥ ገጣሚው የግሉን ምናብና ፈጠራ እንዲለማመድ እድል የሚሰጥ የግጥም ዘልማድ ... free verse (ነፃ ስንኝ) በመባል ይታወቃል።” ብሏል። ልቦለድ ውስጥ፥ በዐረፍተ ነገር ታግደው የታፈኑ ግጥሞች በንቁ አእምሮ ብንዳስሳቸው ውበታቸው በየገፁ ምናባችንን ያወረዙታል። የትረካውን አውታር ያድሱታል። ወደ አንቀፅነት ሲመለሱ የትረካውን ፍጥነት በማርገብ በመቼቱ እንድንጠልቅ እና ወጣቷ -ጣዎሴ- እንዴትና ለምን በሠዓሊ ብሩክ ፍቅር በዝግታ ተነድፋ፣ ታሪኩ ሲፈፀም የተከሰተውን ሌላ ሀቅ እስኪጐመዝዛት መሸሿን እናጤንላታለን እንጂ ግጥማዊ ዜማና ውስጣዊ ምት ብቻ ሆነው አይመክኑም። ዝርግ ግጥም -prose poem- እንደ አረፍተ ነገር ከጥግ እስከ ጥግ የሚወጠር ግን ዕምቅ፥ ዘይቤያዊና ውስጠ-ምቱ መሳጭ ነው። ዓለማየሁ ገላጋይ በዚህም ምናባችንን ይወርሰዋል።
”እናቴ... እዚህ አያቶቼ ግቢ ውስጥ የኖረችው በመንፈስ ህልውና ነው ማለት እችላለሁ። ስትሄድ ኮቴዋ አይሰማም። ለዚህ ዓለም ሙቀትና ቅዝቃዜ ምንም አይነት ምላሽ ስትሰጥ አይታይም። አትስቅም፥ አታለቅስም። ሆዷ ተከፍቶ ስትበላና ስትጠጣ አጋጥሞኝ አያውቅም። ... የትኛውንም በደል እንደ ስፖንጅ መጥጦ የሚያስቀር ፊት ነበራት። መከፋትን ብቻ ሳይሆን መደሰትንም ፊቷ አስርጐ ያስቀር ነበር። ... አንድ ጠዋት ከቤት ወጥታ ጠፋች፤ ድምጿ ሳይሰማ ሰባት አመት ሆኗታል።
አንዳንድ ቀን በህልሜ ጥቂት ጥሬ በነጠላዋ ላይ ቋጥራ ጭው ባለ በረሃ ላይ ስትጓዝ አያታለሁ። መንፈስ ቅልቅል አካሄዷ አልተለወጠም። በሚንቀለቀለው በበረሃ ግልብልባት እየተንቀጠቀጠች እስክትጠፋ አያታለሁ።
 [ገፅ፥ 53/54/55]
ይህ ዝርግ ግጥም ዜማና ዘይቤ ብቻ ሳይሆን፥ ዕምቅነቱ ውስጣዊ ሰቆቃዋን ተጫጭና የምትስለመለም ነፍስ መግለጥ መቻሉ ነው። የተራኪዋ እናት -ስም የለሽ- እንደ ሰው ሳይሆን እንደ ተለጣፊ ጥላ -silhouette- ለመታወስ እንኳን ከሌላ ፍጡር የተረፈ ብርሃን ያስፈልጋታል። በሥዕልም በዕውንም ደራሲው እውስጧ የዘቀጠውን ሰቆቃ፥ በዝምታዋ የምታፍነው ሀዘን በተራኪዋ አንደበት ገለጠው እንጂ ውጫዊ ቁመናዋ አይታየንም። በጨለማ የምታደባ የሴት ቅርፅ ተክቶታል፤ መልኳ በሥነልቦናዊ መዘዟ ተደናገዘ። ልጇ የአራት አመት እድሜ እያላት ነበር ባሏ በመኪና አደጋ የሞተው። ብሩክ ስለ እናቷ በደል ሲያስረዳት ነው ጣዎሴ አይነጥላዋ የተገፈፈው።
“ለጐጆዋ እንዳለፋች፥ ለትዳሯ እንዳልማሰነች በስተመጨረሻ ሆዷን በጥወራ የምታሸንፍ፥ ፊት አይቶ ነዋሪ ተደረገች። የቁም እስረኛ ... አባትሽ ሁሉንም ሀብት በእናቱ ስም አድርጐ ነበር። ሲቀር ቀረ። ባዶ እጅና ልጅ። ላንቺ ስትል ስድስት ዓመት በነፃ ተገዛች።”  
ጤና፥ ጉልበት፥ ምናልባትም ውበት ሳያንሳት አባወራ በህይወት ሳለ ቤቱን ሲበድል ምን አኮማተራት? የብቸኛ ልጁ እናት ሆና እምነቱን ለምን ነፈጋት? ከሞተ ጀምሮ ያለኮሽታ፥ ተጠቅልሎ እንደ ተዘነጋ አልባሌ ጨርቅ ለህይወቷ ጣዕምና ትርጓሜ ሳትፍነከነክ ለምን በዝምታ ተሻረች? ዩፍታሄ ንጉሴ የተቀኘለት ዝምታ አይደለም። “ሲመታኝ ዝም ብል፥ ዝም ያልኩ መስሎታል / ሲታሰብ ነው እንጂ፥ ዝም ማለት የታል”  ልቡናዋን ያነተበ ዝምታ ነበር። እርግጥ ለልጇ የተጨነቀች ይመስላል። ለአመታት መንፈሷ ከተሰባበረ በኋላ ለመጥፋት ስትወስን ልጇን ታስመርጣታለች፤ ከእሷ ወይም ከአያቷ ለመኖር።
“ቤቲ” አለችኝ
“እ” አልኳት ጨዋታዬን ሳላቋርጥ
“ከእኔና ከእማማ ከማን ጋር ብትሆኚ ይሻልሻል?”
“ከሁለታችሁም ጋር” በግዴለሽነት
“አንዳችንን ምረጪ ብትባይስ?” ...
“እማማ ጋ”
እንደ ቀልድ የተፈተለከች ይቺ ቃል እንደ ጥይት ለዘልአለም የመለያያ ጦስ ትሆናለች ብዬ አልገመትኩም ነበር። አንድ ቀንም ሳትስቅ፥ ሳታለቅስ እንደ መንፈስ ግቢያችን ውስጥ ከወድያ ወዲህ ማለቷን ቀጠለች...
አንድ ጠዋት ከቤት ወጥታ ጠፋች፤ ድምጿ ሳይሰማ ሰባት አመት ሆኗታል። [ገፅ፥ 55-56]
ደራሲው ማንነቷን እውስጧ ቀበረው። ቅድመ ጋብቻ የነበራት ህይወት፥ ዛሬም ከሥጋ ዘመዶቿ ተገልላ መሸሸጓ፥ ይህ በብቸኝነት ተገፈታትራ ከአንድ ጥግ የመቆዘም ትዕግስት መነሻው ምንድነው? ገጿ እንደ ተሟጠጠ፣ እንደ ደረቀ ስለኖረች፣ ብሩክ የሳላት ወቅት ልጇ -ጣዎሴ- ምስሉን አይታ ደንግጣለች።
ሴቲቱ ቁርጥ እናቴን። ብቻ የስዕሏ እናቴ እያለቀሰች ነበር።
ሳይታወቀኝ “እንዴ?” ስል አንባረቅሁ።
ብሩኬ “ምነው?” እንደማለት ዞሮ አየኝ።
“ውሸት!” አልኩ
“ምኑ?”
“እናቴ አታለቅስም”
ብሩኬ ... ለራሱ የሚመስል ቃል ተናገረ። “ለቅሶዋን ልጅ አያየውም”
... ሮጨ ወደ ትልቁ ቤት ገብቼ እማማን ጠየቅኩ።
“እማማ እማማ ልጅ የማያየው ልቅሶ አለ?”
“ምን ትላለች ይቺ፥ ኋላ ልጅ የሚያየው ለቅሶ ነው ያለው?
ቀብር ጨዋታ መሰላት?” ... ወደ ጓዳ ገቡ።  [ገፅ 61]
በአያትና በተራኪዋ መካከል የተከሰተው አለመግባባት እንባ በ“ለቅሶ” መተካት የለኮሰው አንድምታ እስከ ቀብር በመፍሰሱ ነበር። ደራሲው የተራኪዋን እናት የህይወት ታሪክ በዝምታ ስለሸበበው ግቢ ውስጥ መኖሯ ከተንቀሳቃሽ ሬሳ ያልተለየ በመሆኑ ተምሳሌቱ ያንሰራራል። ሥዕል ሸራ ላይ ሲፀነስ፥ የተፈጥሮ ምትሀት ያለስስት ሲገለጥ የገፀባህሪያቱ ዳራና ታሪክ መኮማተር ለምን አስፈለገ? ተራኪዋ ሁሉን አወቅ ሳትሆን በቅርቧ ያለውን እንቅስቃሴ ብቻ ስለሚገለጥላት፥ ካልተነገራት በስተቀር የሌላውን ገመና የማወቅ አቅም ተንፍጓታል። ቢሆንም የብሩክን ገፅታ -ስለአፈቀረችውም ይሆናል- መግለጥ ከቻለች እራሷን፥ እናቷን ፥ አያቷን ... የገፃቸውን ውበት ይሁን አስቀያሚነት ማንፀር ለምን ተሳናት? ደራሲው ስለአልፈቀደ እንጂ ሌላ ምክንያት አይኖርም። ከአሁን እድሜዋ ጀምራ ወደ ኋላ  ወደ ፊት እየተመላለሰች ስትተርክ፣ የእድገቷን ሥነልቦናዊ ደረጃ በመጠበቅ ስለሆነ ደራሲው ተዋጥቶለታል። ድንቅና ተራ ደራሲን ከሚነጥላቸው ክህሎት አንዱ የልቦለድን ድርጊት የማጠንፈፍ ችሎታ ነው። ተራው ይተረትራል፤ ሁሉንም ይዘረግፋል። ብስሉ ይመርጣል፤ ከማንዛዛት ይልቅ ለጥቆማ ያደላል። ፈጠራውን መቼት ውስጥ ለማንቀሳቀስ ወሳኝ ሁነቶች፥ ግጭት፥ ምልልስ ... ይመርጣል። በ“ኩርቢት” ዓለማየሁ ገላጋይ ለመግለጥ የሚያዳግት ጥቃቅን ሁነቶች ሳይፈታተኑት፥ የገፀባህሪያቱን ህይወት -- በተለይም የተራኪዋ እናት እና ብሩክ ከግቢው ውጭ -- አልተከተላቸውም። ሁሉን አወቅ ተራኪ አለመጠቀሙ በኮረዳዋ ዕጣ ፈንታ እንድንደመም፥ ሌሎች ብርሃን ሳይሻሟት ከአእምሯችን እንድታደራ ስለወሰነ ከሆነ ሰምሮለታል።
አንዲት ሴት መበደሏን እንጠረጥራለን እንጂ እንደ መንፈስ -ghost- ለመኖር ደፍጥጦ ያጐበጣት ሀይል፥ ወኔና ተስፋ የሰለባትን ምክንያት ማወቅ ተስኖናል። የባሏ መሞትና ባዶ እጇን መቅረቷ ከመንፈራገጥ፥ አዲስ ህይወት ከመጀመርና በራሷና በሌሎች ጉዳይ ከመሞገት አያግዱዋትም። ልክ በስብስቡ ሌላ አጭር ልቦለድ የተቀረፁት የቦኖ እናት፤ ድህነት ሳይሰብራቸው ለእለት ጉርስ መነፈግ ሳይሰጉ ከሃብታም ጐረቤት ጋር ይላተማሉ።
“እታለማሁ መሃን በመሆናቸውና ለሰፈርተኛው የቦኖ ውኃ በማስቀዳታቸው ነው `የቦኖ እናት` የሚል ቅጥል ስም የወጣላቸው። እታለማሁ በቅጽል ስማቸው አይከፉም። እንዲያውም አንዳንዴ `እኔ የቦኖ እናት` እያሉ በራሳቸው ያሾፋሉ። ”የተራኪዋ እናት እጦት ወይም ልጄን ማን ያሳድጋታል የመሰለ ስጋት ሳይሆን ሌላ ጥልቅ ድብቅ ምክንያት ይኖራታል፤ ሰው የሚያደርጋትን ባህሪያት አወላልቃ የሰው ጥላ ለመሆን ያበቃት -dehumanized-። ሰባት አመት ከፍቅርና ወሲባዊ ፍላጐት ተገልላ በዝምታ መታፈኗም በደል ነው። የጣዎሴ ወንድ አያት የቤት አዛዥነት ስልጣናቸውን በባለቤታቸው ተቀምተዋል።
“እንደማንኛውም የአውሬ ማህበር በሰው ልጆችም ዘንድ እናት ልጆቿ እስኪያድጉ በልምምጥ ትኖርና ሲደርሱላት የበላይነቷን ትቆናጠጣለች” የትንባሆአቸውን ኩርቢት ከመማግ በስተቀር በስተእርጅና ምንም አልተረፋቸውም፤ ተሸንፈዋል። ደራሲው ሴት ስትበደል ብቻ ሳይሆን ወንድም ሲገፈተር ቀረፃቸው።
ተራኪዋ በሠዓሊ ብርኩ የልጅነት ትዝታዋ፥ በቡሩሹና ንግግሩ ውበትን ጥበብን ለማጣጣም መብቃቷ፥ ቀስ በቀስ በጥልቅ አፍላ ፍቅር እንድትወረር አደረጋት። ስልክ ደውሎ “ካንቺ ጋር ማውራት ያለብኝ ነገር አለ። ድብብቁ ቢበቃን ጥሩ ነው”  ሲላት ፍቅሩን የሚገልጥላት መስሏት ተቅበጠበጠች፥ በኑሮ ለመፍካት አለመች። ሰአቱ ደርሶ ተገናኙ፤ የደካከመው ቢመስልም አዲስ ወደ ተከራየው ቤት ይወስዳታል። እናቷን በጠፋች በአመቱ አፈላልጐ ከእሷ ጋር ትዳር መስርቶ ሁለት ልጆች ወልዷል።
ለጥቂት ደቂቃ የማደርገው ጠፋኝ። ...
”እህትና ወንድምሽ ናቸው”
ወደ እናቴ ዞሬ አየኋት። ስር ስር ይስለከለክ የነበረ እንባዋ መንጭቶ በአፍላ ግፊት እየተንዶለዶለ ነበር። አንዳች ነገር ውስጤ ከተሸሸገበት እየፈካና እየጐላ ሲመጣ ይታወቀኝ ነበር።
ትዝታዬን ተዘረፍኩ፥ ጀንበሬን ተዘረፍኩ፥ ልጅነቴን ተዘረፍኩ፥ ፍ-ፍ-ፍቅሬን ተዘረፍኩ። ...
ባዶ ሆኛለሁ። የብሩኬ ድምፅ ከውስጤ ገመገም ጋር እየተጋጨ ያስተጋባል። ገደል ለገድል ይሽሎከሎካል። ማልቀስ ተሳነኝ፤ ማልቀስ ተጐዳህ የማለት ቅብጠት ነው። ከእንግዲህ እንዳላለቅስ አውቃለሁ። መሣቅም ተደሰትኩ የማለት ቅብጠት ነው። ከእንግዲህ እንዳልስቅ አውቃለሁ። አያቴ ሲሞት የእርሱን ኩርቢት እወርሳለሁ።
    [ገፅ 71]
እንደ ሀቅ ካሳደጉት ቅዠት --ያውም የፍቅር ጥልቀት የዋጠው-- ድንገት መባነን ያጥበረብራል። Milan Kundira ስለ ጥሬነት ወይም የልምድ ማነስ -inexperience- አንድ ልቦለዱን ሲያጤን የተናገረው ጣዎሴን ይገልጣታል። ... inexperience (is) a quality of the human condition. We are born one time only, we can never start a new life equipped with the experience we have gained from a previous one. We leave childhood without knowing what youth is, ... even when we enter old age, we do not know what it is we are heading for. The old are innocent childern of their old age. [The Art of the Novel]. ጥሬነት የሰው ባህሪ ነው። አንድ ጊዜ ብቻ ስለምንወለድ ካለፈ የህይወታችን ልምድ እውስጣችን ያደረ ስንቅ ስለሌለን ልጅነት፥ ወጣትነት ብሎም እርጅናን መኖር የምንጀምረው ለእያንዳንዱ የዕድሜ ኩራባ የዋህ ሆነን ነው። ሌላው በቅድሚያ ቢነግረን እንኳን እስከ አልተዘፈዘፍንበት ድረስ ያደፈጠ ጥሬነት ጉድ ያደርገናል። ለዚህም ነው ጣዎሴ የተሰወረችው እናት መገኘት፥ የሁለት ህፃናት እህት መሆኗን መገንዘብ፥ እነዚህ ጣፋጭና ህይወት-አዳሽ ሁነቶች አልካሱዋትም፤ በደስታ አዲስ ህይወት መበርገድ ሲገባት በመደናገር ዋዠቀች። ከልቧ ለአመታት የተላወሰውን የ`ብሩኬን` ፍቅር መነጠቅ ለጋ ዕድሜዋና ውስን ገጠመኟ የማይቋቋሙት የግልብጥ እውነታ ሆነ። ለወንድ አያቷ ሽንፈት ተምሣሌት የሆነውን ኩርቢት በመውረስ፥ የቀራትን ዕድሜ እንደ ትንባሆ እየማገች ተስፋዋን በጢስ ለማባከን ወሰነች። ደግነቱ ወጣትነት ተደፍጥጦ የሚቀር ሳይሆን ዳግም የመነቃቃት -resilience- ቁልፍ ባህርዩ ነውና ታንሰራራለች። ዓለማየሁ ገላጋይ አብይ ልቦለዱን “የብርሃን ፈለጐች” ሲቋጭ ዋናው ገፀባህሪ ከሞጆ አዲስ አበባ ሲመለስ “ንፁህ” የሚላትን ጣዎሴን ፍለጋ ቀበና ድረስ መቅበዝበዙን ጦቅሞናል። ሁለቱን ሌላ ጠነን ያለ ልቦለድ የመሰለ ኑሮ መረቡን ዘርግቶ ሊያጠምዳቸው አድብቷል። ለ“ኩርቢት” ስብስብ የተሾመው አጭር ልቦለድ አዟዙረው ቢመሰጡበት ያስደምማል። ሂሳዊ ዳሰሳ የማይፈታቸው አስራ ሶስት ርዕሶች ከምናብና ጥሞና ለመላወስ አድፍጠዋል፤ በክፍል ሁለት ይነበባሉ።

Published in ጥበብ
Page 2 of 13