ገዳሙ ጨርሶ ሳይጠፋ ጉዳያቸው በሲኖዶሱ እንዲታይ መናንያኑ ጠይቀዋል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀ/ስብከት ሞረትና ጅሩ ወረዳ የሚገኘው የመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን የደብረ ብሥራት አቡነ ዜና ማርቆስ አንድነት ገዳም ተፈትቶ፣ መናንያኑና መነኰሳቱ መበተናቸውን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገለጹ፡፡ ጥንታዊውን ገዳም ለመፈታት፣ ማኅበረ መነኰሳቱንም ለመበተን ያበቃቸው በአካባቢ ተወላጅነት የገዳሙን መሬት በተለያዩ ጊዜያት ተቆጣጥረው ለግላቸው ይጠቀሙ ከነበሩ ግለሰቦች ጋር ተፈጥሮ የቆየውና በተለያዩ ምክንያቶች እየተካረረ የመጣው አለመግባባት መኾኑን ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡ በኅዳር ወር 2006 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ገዳሙን ለቀው የወጡት በቁጥር ከ50 - 80 የሚገመቱ መነኰሳት፣ መነኰሳዪያትና መናንያን ከተለያዩ አህጉረ ስብከትና ክልሎች የተሰባሰቡ ሲኾኑ በሀገረ ስብከቱ ውሳኔ ከአስተዳዳሪነት የተነሡትን አበምኔቱን መ/ር አባ ተክለ ብርሃን ሰሎሞንን ጨምሮ ከፊሎቹ በአሁኑ ወቅት በደነባ በኣታ ለማርያም ገዳም ተጠልለው እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የወረዳው መንግሥታዊ አስተዳደር፣ ከእነዋሪና ደነባ የተውጣጡ የሀገር ሽማግሌዎች ገዳማውያኑንና ግለሰቦቹን በተለያየ ጊዜ በማገናኘት ለአለመግባባቱ የመፍትሔ ሐሳብ ሲሰጡና ውሳኔ ሲያሳልፉ እንደቆዩ ያስታወሱት መነኰሳቱ፤ ‹‹ተሰዳጅና መጤ›› ከሚል በቀር ግለሰቦቹ የሚያቀርቡባቸው ክሦች መሠረተ ቢስ እንደኾኑ ተረጋግጧል ብለዋል፡፡ የገዳሙን ሥርዐተ ማኅበር በመጣስ የመሬት ይዞታውን፣ ቅርሱንና የልማት ቦታውን ለመከፋፈል የሚሹ ግለሰቦች በሥነ ምግባር ጉድለት ርምጃ ከተወሰደባቸው የስም መናንያን ጋራ በማበር ያቀረቡትን አቤቱታ ብቻ በመቀበል በፓትርያርክ የሚሾሙት አበምኔት በሀ/ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤ ውሳኔ ከሓላፊነት መነሣታቸውን ያስረዱት ማኅበረ መነኰሳቱ፣ አንዳንድ የሀ/ስብከቱን ሓላፊዎች በስም በመጥቀስ ለችግሩ መባባስ ተጠያቂ አድርገዋቸዋል፡፡ የገዳሙን መሬት ይዘው ከገዳማውያኑ ጋራ ተቀላቅለው ይኖሩ የነበሩትን የአካባቢውን አርሶ አደሮች ትክ መሬት እንዲያገኙና ለንብረታቸውም ካሳ እንዲሰጣቸው በማድረግና ጣልቃ ገብነትን በመከላከል የገዳሙን ይዞታና ሥርዐተ ማኅበሩን ያስከበሩትን፤ በግብርናና በሽመና ሥራዎች፣ በሙዓለ ሕፃናት፣ በኪራይ ቤቶች ግንባታ የራስ አገዝ ልማትን በማስፋፋት ልመናን ያስቀሩትን አበምኔት አላግባብ ከሓላፊነት ማንሣት÷ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ኤፍሬም ስለ አበምኔቱ የአስተዳደርና ትምህርት ብቃት እንዲሁም ልማታዊነት ሲሰጡ የቆዩትን ምስክርነት የሚያስተባብልና የገዳሙን መተዳደርያ ደንብ የሚጥስ ከመኾኑም በላይ በሀ/ስብከቱ ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ላይ የተንሰራፋው የመልካም አስተዳደር ችግር አስከፊ መገለጫ ነው ብለዋል ማኅበረ መነኰሳቱ፡፡

ከገዳማቸው የተፈናቀሉት ማኅበረ መነኰሳቱ ሥርዐተ ማኅበራቸውን ጠብቀው በገዳሙ የጀመሩትን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ልማታዊ አገልግሎት ለመቀጠል እንዲችሉ፤ የገዳሙ ቅርሶች፣ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረቶች እንዲጠበቁ፣ በገዳሙ ያለጧሪ የቀሩት ድኩማን አረጋውያን ደኅንነትም እንዲጠበቅ ቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ውሳኔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡ የደብረ ብሥራት ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ ገዳም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዝሙር በኾኑት አቡነ ዜና ማርቆስ የተመሠረተ የዐሥራ ሁለተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ገዳም መኾኑን የገዳሙ ታሪክ ይገልጻል። ገዳምነቱን ሳይለቅ እስከ 8000 መናንያንን እያስተዳደረ በሥርዐተ ማኅበር በቆየው ገዳም፣ ሰበካ ጉባኤ በማቋቋም ወደ ደብርነት እንዲቀየርና በቃለ ዐዋዲ እንዲመራ ለማድረግ ተሞክሮ እንደነበር የገለጹት የዜናው ምንጮች÷ ሲኖዶሱ፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የገዳማት አስተዳደር መምሪያና የቅርስ ጥበቃ የሚመለከታቸው አካላት ኹሉ ከጻድቁ የእጅና የመጾር መስቀሎች ጀምሮ በርካታ ቅርሶች የሚገኙበትን የመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሥርዐተ ምንኵስናና የትምህርት ማዕከል ጨርሶ ሳይጠፋ መታደግ እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል፡፡

Published in ዜና

ከሞቱት አምስቱ የትምህርት ሚኒስቴር ሰራተኞች ናቸው

ባለፈው ረቡዕ ከቀኑ 8 ሰዓት ላይ ከትምህርት ሚኒስቴር ግቢ ተነስቶ ወደ ደብረማርቆስ ይጓዝ የነበረ ሳንሎንግ መኪና ተገልብጦ ስድስት ሰዎች ሲሞቱ፣ 18 ሰዎች መቁሰላቸው ታወቀ፡፡ ከሞቱት ውስጥ አምስቱ የትምህርት ሚኒስቴር ሰራተኞች እንደሆኑም ታውቋል፡፡ የአጠቃላይ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ጽ/ቤት ፀሐፊ ወ/ሮ ዘይነባ ይመር፣ የጽ/ቤቱ የመልዕክት ሰራተኛ ወ/ሮ መልካሟ አወቀ፣ እንደሁም አቶ ምኒልክ በቀለ፣ አቶ ተስፋዬ ጂኖሬ፣ ወ/ሮ መሠረት ደጀኔ የተባሉ የሚኒስትሩ ሠራተኞች በአደጋው ህይወታቸው አልፏል፡፡

ከኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌዴሬሽን የተወከሉት ሴት ግን ምንም አደጋ ሳይደርስባቸው በዚያው ምሽት ከቤተሰቦቻቸው ጋር መቀላቀላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ የክልሉን የስድስት ወር የትምህርት አፈፃፀም ለመገምገም ከትምህርት ሚኒስቴር የተለያዩ ባለሙያዎች፣ የዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሮች፣ ከኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌደሬሽን የልዩ ፍላጐት ትምህርት ባለሙያዎችና ከሌሎች ባለ ድርሻ አካሎች የተወከሉ ወደ 30 ያህል ሰዎች በመኪናው ውስጥ ሲጓዙ እንደነበር ከአደጋው ተርፈው ጳውሎስ ሆስፒታል በህክምና ላይ ያገኘናቸው የልዩ ፍላጐት ትምህርት ቡድን አስተባባሪ አቶ አለማየሁ ወልደቂርቆስ ገልፀዋል፡፡

የአጠቃላይ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታውን አቶ ፉአድ ኢብራሂምንና ሌሎች ባለስልጣናትን የያዘው መኪና ቀደም ብሎ የሄደ ሲሆን ደብረማርቆስ ለመድረስ 10 ኪሎ ሜትር ሲቀረው አደጋው መድረሱን ሰምቶ እንደተመለሰም ታውቋል፡፡ ከቀኑ 8 ሰዓት ላይ ከትምህርት ሚኒስቴር የተነሳው ሳንሎንግ መኪና፣ አባይ በረሃ ውስጥ አባይ ወንዝ ጋር ሊደርስ በግምት ሁለት ወይም ሶስት ኪሎ ሜትር ሲቀረው ባልታወቀ ምክንያት ድንገት ተወዛውዞ መገልበጡን፣ በቀኝ እጃቸው ላይ ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው የተረፉት በትምህርት ሚኒስቴር የሞያ ፍቃድና እድሳት ዳይሬክቶሬት ክፍል ባለሙያ የሆኑት አቶ ጴጥሮስ መላኩ ተናግረዋል፡፡ በአደጋው አራት ሴቶችና ሁለት ወንዶች ህይወታቸው ያለፈ ሲሆን፤ ከሟቾቹ ውስጥ የአምስት ልጆች እናት የሆኑትና በአጠቃላይ ትምህርት ሚኒስቴር ዴኤታ ጽ/ቤት ፀሐፊ የነበሩት ወ/ሮ ዘይነባ ይመር ይገኙበታል፡፡

አደጋው ከደረሰ በኋላ ከኋላ ይጓዝ የነበረ የትምህርት ሚኒስቴር መኪናና የኩዩ ወረዳ አምቡላንስ ቶሎ ደርሰው አስቸኳይ ህክምና የሚያስፈልጋቸውን ጐሀ ፂዮን ጤና ጣቢያ፣ ሌሎቹን ኩዩ ሆስፒታል የወሰዱ ሲሆን ከፍተኛ አደጋ የደረሰባቸውን ደግሞ ወደ አዲስ አበባ እንዳመጧቸው ከአደጋው የተረፉት ሰዎች ጠቁመዋል፡፡ የአደጋውን መንስኤ በተመለከተ የትምህርት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ የሚያውቁት ነገር እንዳለ ጠይቀናቸው “ጉዳዩን ትራፊክ ፖሊስ ይዞታል፤ አሁን ምንም ነገር መግለጽ አልችልም” ብለውናል፡፡ አዲስ አበባ ትራፊክ ፖሊስ ደውለን መንስኤውን ለማጣራት ስንሞክር፤ ስማቸውን መጥቀስ ያልፈለጉ የትራፊክ ፖሊስ ባልደረባ “አደጋው የደረሰው ሌላ ክልል ውስጥ በመሆኑ በአካባቢው ፖሊስ ነው የሚጣራው” የሚል ምላሽ የሰጡን ሲሆን የአደጋው መንስኤ እየተጣራ መሆኑን እንደሰሙ አክለው ነግረውናል፡፡ በአደጋው የሞቱት ሰዎች በትላንትናው እለት በየአካባቢያቸው የቀብር ስነስርዓታቸው ተፈጽሟል፡፡

Published in ዜና

በቅርቡ የተቋቋመው “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” ከትናንት በስቲያ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሂዶ የማህበሩን የመተዳደሪያ ደንብ ያፀደቀ ሲሆን አመራሮቹንና የስራ አስፈጻሚ አካላትንም መርጧል፡፡ ጋዜጠኛ በትረ ያዕቆብ ሊቀመንበር፣ ጋዜጠኛ ስለሺ ሃጐስ ምክትል ሊቀመንበር እንዲሁም ጋዜጠኛ ነብዩ ሃይሉ ዋና ፀሃፊ በመሆን የተመረጡ ሲሆን ጋዜጠኛ አያሌው አስረስ የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ አፈ-ጉባኤ፣ ጋዜጠኛ ጌታቸው ወርቁ ምክትል አፈ-ጉባኤ እንዲሁም ጋዜጠኛ ብሩክ ከበደ የአፈ-ጉባኤ ፀሃፊ ሆነው እንደተመረጡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲስ የተመረጡት አመራሮች በጋራ በሰጡት መግለጫ፤ማህበሩ ሙያተኛውን ብቻ ማዕከል አድርጐ በመንቀሳቀስ የአባላቱን መብት እንደሚያስከብር፣የአባላቱን ሙያዊ ክህሎት በተለያዩ ስልጠናዎች እንደሚያዳብርና ሃሣብን በነጻነት የመግለጽ መብትን በተሟላ መልኩ ለማስከበር በትጋት እንደሚሰራ ጠቁመዋል፡፡ አዲሱን የጋዜጠኞች ማህበር ማቋቋም ያስፈለገው በአገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የጋዜጠኞች ማህበራት የሙያተኛውን መብት በቅጡ ማስከበር ባለመቻላቸው ነው መባሉ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና

የመኢአድ 22ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ነገ በተለያዩ ዝግጅቶች በድርጅቱ ጽ/ቤቱ የሚከበር ሲሆን ከአውሮፓ፣ ከአሜሪካና ከካናዳ ጥሪ የተደረገላቸው የድርጅቱ ተወካዮች በበዓሉ ላይ እንደሚገኙ ተገለፀ፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳድር ተወካዮችም እንደተጋበዙ ታውቋል፡፡ የመኢአድ ሊቀመንበር አቶ አበባው መሃሪ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤በዓሉን ምክንያት በማድረግ ድርጅቱ የ22 ዓመት የትግል ጉዞውን በመገምገም፣ድክመቱንና ጥንካሬውን እንዲሁም የወደፊት ራዕዩን ይፋ የሚያደርግ ሲሆን የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ የሚያስቃኝ የጥናት ፅሁፍ ቀርቦም ውይይት ይካሄድበታል፡፡

በዕለቱ የቀድሞው የመኢአድ ሊቀመንበር የኢ/ር ኃይሉ ሻውልን ህይወትና የፖለቲካ ጉዞ የሚተርከው “ህይወቴ እና የፖለቲካ እርምጃዬ” የተሰኘ መጽሐፍ በዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ የሚገመገም ሲሆን ከመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መዐሕድ) እስከ መኢአድ እንዲሁም ቅንጅት… ድረስ ያለውን የትግል ጉዞ የሚያስቃኝ ጥናታዊ ፊልምና የፎቶ ኤግዚቢሽን እንደሚቀርብም ታውቋል፡፡

Published in ዜና

የአፍሪካ መንግስታት 10 በመቶ ያህል በጀታቸውን ግልጽነትና ተጠያቂነት ባለው የበጀት አጠቃቀም በውጤታማ ግብርና ላይ እንዲያውሉ ጥሪ የቀረበ ሲሆን ከ85 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያንን ከድህነት ለማውጣት ያለመ ዘመቻ በአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ስብሰባ ላይ ተጀምሯል። “ዋን” የተሰኘው አህጉር በቀል ተቋም ባለፈው ረቡዕ በአዲስ አበባ ይፋ ባደረገው ማሣሠቢያ አዘል ሪፖርት፤ ከ400 ሚሊየን በላይ ከሚሆኑት በከፋ ድህነት ውስጥ የሚዳክሩ አፍሪካውያን መካከል 70 በመቶ ያህሉ ኑሮአቸውን የመሰረቱት ውጤታማ ባልሆነ ግብርና ላይ እንደሆነ ጠቁሞ የእነዚህን ዜጐች ኑሮ ለማሻሻል ከተፈለገ ለግብርና ተገቢው ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብሏል፡፡ የአፍሪካ ገበሬዎች ህይወት እንዲሻሻል መንግስታት ሊተገብሩት ይገባል ብሎ ተቋሙ ከጠቆማቸው የመፍትሄ ሃሣቦች መካከልም በግብርና ላይ ያለውን ጾታዊ አድልኦ ማስወገድ፣ የመሬት አስተዳደርና የመሬት ኪራይ መብት ዋስትናን ማጠናከር እንዲሁም ለዘርፉ ጠንካራ በጀት መመደብ ይገኙበታል፡፡

ተቋሙ በሪፖርቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ ስምንት የአፍሪካ ሀገራት ከበጀታቸው 10 በመቶውን ለግብርና በማዋላቸው ውጤታማ እየሆኑ ነው ብሏል። በግብርና ላይ ያተኮሩ ጥናቶችን የሚያካሂደው “ዋን”፤ ከቤኒኑ ኘሬዚዳንት ያዬ ቦኒ፣ ከናይጄሪያዊው ዘፋኝ ጂባንጂ እንዲሁም ከኮትዲቫራዊው እግር ኳስ ተጫዋች ያያ ቶሬ ጋር በመሆን በአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ስብሰባ ላይ “ዲ አፍሪክ” የተሰኘ አዲስ ዘመቻ በይፋ ያስጀመረ ሲሆን ዘመቻው በግብርና ላይ በቀጥታ ያተኮረ የኢንቨስትመንት ፈሰስ በማድረግና በተሻሻለው ሁሉን አቀፍ የአፍሪካ የግብርና ልማት ኘሮግራም ፖሊሲዎች አማካኝነት ከ85 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያንን ከድህነት ለማውጣት ያለመ እንቅስቃሴ ነው ተብሏል፡፡

Published in ዜና

አንድ ኪሎ ጤፍ በአውሮፓ ከ200 ብር በላይ ይቸበቸባል
የአሜሪካ አውሮፓና፣ እስራኤል ገበሬዎች ጤፍ እያመረቱ ነው
ከጤፍ ተፈላጊነት የኢትዮጵያ ገበሬዎች መጠቀም አለባቸው ተባለ “ጤፍ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ሱስ ነው” ትላለች - የ”ዘ ጋርዲያን” ዘጋቢዋ ኤሊሳ ጆብሰን፤ ባለፈው ሳምንት ለንባብ ባበቃችው ዘገባ ላይ፡፡ በአገሪቱ ከ6 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች ጤፍ እንደሚያመርቱና ከአገሪቱ የእርሻ መሬት ከ20 በመቶ በላይ የሚሆነውም በጤፍ እንደሚሸፈን ትገልጻለች፡፡ በአገሪቱ ለምግብነት ከሚውሉ የሰብል አይነቶች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዝና እንጀራም ብሄራዊ ምግብ እስከመሆን መድረሱን በዘገባዋ ጠቁማለች፡፡ ጤፍ ለአገር ውስጥ ፍጆታ ከመዋል አልፎ በእንጀራ መልክ ባህር ተሻግሮ በተለይ በምዕራባውያን አገራት በሚገኙ ዲያስፖራዎች መበላት ከጀመረ አስርት አመታት እንዳለፈው የምታስታውሰው ዘጋቢዋ፤ አሁን አሁን ደግሞ የጤፍ ተፈላጊነት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ትናገራለች፡፡

የኢትዮጵያ ጤፍ በአለም ገበያ ቀጣዩ ተፈላጊ ሰብል ለመሆን እንደሚችል በመግለጽ፣ ነገ ከነገ ወዲያ ኢትዮጵያ ከቡና ቀጥሎ ለአለም የምታበረክተው ሁለተኛው ስጦታ ጤፍ መሆኑ እንደማይቀር ትናገራለች፡፡ በውስጡ ካልሺየም፣ አይረን፣ ፕሮቲንና ሌሎች ንጥረነገሮችን የያዘውና ለጤና ተስማሚ የሆነው ጤፍ፤ በአለማቀፍ ደረጃ ተፈላጊነቱ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መምጣቱን ነው ዘ ጋርዲያን ከሰሞኑ ያስነበበው ዘገባ የሚያስረዳው፡፡ “ጤፍ በውስጡ የያዘውን ንጥረ ነገር ባወቅሁ ጊዜ እጅግ ነበር የተገረምኩት፡፡ በህይወት ዘመኔ ሁሉ ስመገበው የኖርኩት ጤፍ፤ እንዲህ ያለ ጠቃሚ ነገር መሆኑን አላውቅም ነበር፤ የሚገርም ነገር ነው!” ያለችው ነዋሪነቷ በለንደን የሆነው ኢትዮጵዊቷ ሶፊ ከበደ ናት፡፡ ሶፊ በጤፍ ተገርማ አላበቃችም፡፡

የግርምት ብቻ ሳይሆን የገቢ ምንጭም መሆን እንደሚችል ገብቷታል፡፡ ለዚህ ነው ተቀማጭነቱ በእንግሊዝ ለንደን የሆነ ‘ጦቢያ ጤፍ’ የተሰኘ የንግድ ኩባንያ ከባለቤቷ ጋር በማቋቋም፣ ጤፍን ከአምራች አገሮች እየገዛች ወደእንግሊዝ በማስመጣት መሸጥ የጀመረችው፡፡ የዘጋርዲያን ዘገባው እንደሚለው፣ ዛሬ “ፕላኔት ኦርጋኒክን” የመሳሰሉ የለንደን ታላላቅ መደብሮች ጤፍ አሽገው በመቸብቸብ ላይ ናቸው፡፡ በእነዚህ መደብሮች አንድ ኪሎ የጦቢያ ጤፍ ዱቄት 7 ፓውንድ (ከ200 ብር በላይ) ይሸጣል፡፡ በመደብሮቹ በጤፍ ዱቄት የተሰራና የተለያዩ ማጣፈጫዎች የታከሉበት ዳቦም ለገበያ ይቀርባል፡፡ ጤፍ አሁን የአገር ቤትና የአገር ልጅ ምግብ ብቻ አይደለም፡፡ የተለያዩ ምዕራባውያን አገራት ዜጎችም በጤፍ አምሮት መለከፍ ይዘዋል፡፡ ፍላጎቱም ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መጥቷል፡፡ “ማማ ፍሬሽ” የተባለው የንግድ ኩባንያ በአዲስ አበባ ለሚገኙ ሆቴሎችና ሬስቶራንቶች ለአመታት እንጀራ ሲያቀርብ መቆየቱንና በአሁኑ ወቅትም ወደ ፊLላንድ፣ ጀርመን፣ ስዊድንና አሜሪካ እየላከ እንደሚገኝ ዘገባው ያሳያል፡፡ ወደ አሜሪካ የሚልከውን ምርት በ2014 በእጥፍ የማሳደግ እቅድ ይዞ እየሰራ ያለው ኩባንያው፤ በቅርቡም የጤፍ ፒዛ፣ ዳቦና ብስኩት እያመረተ ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንደሚጀምር ዘገባው ያስረዳል፡፡

ዘጋቢዋ እንደምትለው፤ “ጥያቄው ኢትዮጵያ እና አርሶ አደሮቿ ከዚህ አለማቀፍ ገበያ ተጠቃሚ መሆን የሚችሉበትን ሁኔታ ማረጋገጥ የሚቻለው እንዴት ነው?” የሚለው ነው፡፡ ለመሰል የተወሰኑ አገራት ምርት ብቻ የሆኑ በንጥረነገር ለበለጸጉ የምግብ እህል ሰብሎች እያደገ የመጣው አለማቀፍ ፍላጎት፣ በድህነት የሚማቅቁ የአምራች አገራትን ማህበረሰቦች ጎጂ ሲሆኑ ይታያሉ ትላለች ዘጋቢዋ፡፡ ይህን እውነታ ለማስረዳት የቦሊቪያና የፔሩን ተሞክሮ በአብነት የምትጠቅሰው ዘጋቢዋ፣ በእነዚህ አገራት የሚመረተው “ኪየኑአ” የተሰኘ የሰብል አይነት በብዛት ወደ ውጭ አገራት መላኩ፣ በአገሪቱ የምግብ እጥረት ማስከተሉን እንዲሁም ሰብሉን አምርቶ በብዛት በመሸጥ የምዕራባውያኑን ፍላጎት ለማሟላት በሚል በአርሶአደሮች ዘንድ የመሬት ሽሚያና ግጭት መፈጠሩን ትገልጻለች፡፡ “በኢትዮጵያ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ለጤፍ ያላቸው ፍላጎት እያደገ ነው፡፡ በአገሪቱ የጤፍ ዋጋ ባለፉት አስርት አመታት እየጨመረ መምጣቱን ተከትሎም ድሃ ዜጎች ጤፍ መግዛት የማይችሉበት ደረጃ ላይ እየደረሱ ናቸው፡፡ አብዛኞቹ አምራቾችም ምርታቸውን ወደ ከተማ እያወጡ በመሸጥ ላይ ናቸው፡፡” ያለችው ዘጋቢዋ፤ የመንግስትን መረጃ ጠቅሳ እንደጻፈችው፣ በከተማ የሚኖሩ ዜጎች በአመት በአማካይ 61 ኪሎግራም ጤፍ እንደሚመገቡ ይገመታል፡፡

በገጠር የሚኖሩት ደግሞ 20 ኪሎግራም፡፡ የአገሪቱ መንግስት አመታዊ የጤፍ ምርቱን በ2015 በእጥፍ የማሳደግ እቅድ አለው፡፡ ይህም የአገር ውስጥና የውጭ ገበያ አቅርቦቱን ለማሳደግ ያስችላል ተብሎ ይገመታል፡፡ የተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት፣ የንግድና ገበያ ዳይሬክተር ዴቪድ ሃላም እንደሚሉት፣ አገር በቀል የሰብል ምርቶችን ለአዳዲስ አለማቀፍ ገበያዎች በማቅረብ ጥሩ ገቢ ማግኘት መቻሉ እንዳለ ሆኖ፣ መንግስታት አነስተኛ ሰብል አምራቾች ከእነዚህ ገበያዎች የሚገባቸውን ጥቅም ማግኘት እንዲችሉ ድጋፍ ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባዮ ዳይቨርሲቲ ተቋም የቀድሞ ሃላፊ የነበሩት የግብርና ተመራማሪው አቶ ረጋሳ ፈይሳ በበኩላቸው፣ ጤፍን በከፍተኛ መጠን እያመረቱ ለውጭ ገበያ የማቅረቡ አካሄድ በአግባቡ ካልታቀደና ጥንቃቄ ካልተደረገበት አደጋ አለው ማለታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡ እሳቸው እንደሚሉት፤ ይህ አካሄድ፣ አርሶ አደሮች ለሌሎች ምርቶች ትኩረት እንዳይሰጡ ሊያደርግ ይችላል፡፡ በብዛት አምርቶ ለገበያ የማቅረቡ አካሄድ አነስተኛ ገበሬዎችን ተጠቃሚ በማያደርግ መልኩ ለጥቂት አትራፊዎች ሲሳይ ሊሆን ይችላል፡፡ በአለማቀፍ ገበያ ላይ የሚቀርበው የኢትዮጵያ ጤፍ አነስተኛ መሆኑን ተከትሎ የአሜሪካ ገበሬዎች ጤፍ ማምረት መጀመራቸውን የገለጸው ዘገባው፤ የአውሮፓ፣ የእስራኤልና የአውስትራሊያ ገበሬዎችም በሙከራ ደረጃ ጤፍ ወደማምረት መግባታቸውን ጠቁሟል፡፡

የ “ጦቢያ ጤፍ” ኩባንያ ባለቤት የሆነችው ሶፊ ከበደ፤ በለንደን ለገበያ የምታቀርበውን ጤፍ፣ ከአገር ቤት ሳይሆን ከደቡባዊ አውሮፓ አገራት ገበሬዎች እንደምትገዛ ገልጻለች፡፡ ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች የሚያመርቱትን ማኛ ጤፍ ለእንግሊዝ ገበያ የማቅረብ ፍላጎት እንዳላትና የአገሯ ገበሬዎች ምርታቸውን ለአለማቀፍ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን የማይችሉበት መንገድ እንደሌለም ለ “ዘጋርዲያን” ተናግራለች፡፡ እ.ኤ.አ በ2006 የኢትዮጵያ መንግስት ጤፍን በእንጀራ መልኩ ካልሆነ በቀር በቀጥታ ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚከለክል ህግ ማውጣቱን የወሳው ዘገባው፤ ይሄም ሆኖ ግን እገዳው ዘላቂ እንደማይሆን ገልጿል፡፡ ምክንያቱም የመንግስት ስትራቴጂ ያስቀመጠው ግብ ለአገር ውስጥ ፍጆታና ለውጭ ገበያ የሚውል በቂ የጤፍ ምርት ማምረት ነውና፡፡

Published in ዜና

ከአስራ አራት ቀን በፊት “አድዋ ይከበር ይዘከር ለዘላለም” በሚል መሪ ቃል ከአዲስ አበባ ጣይቱ ሆቴል የእግር ጉዞ የጀመሩት የጉዞ አድዋ አባላት፤ የካቲት 23 ታሪካዊቷ አድዋ አምባ እንደሚደርሱ ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ ወደ አድዋ የሚያደርጉትን ታሪካዊ ጉዞ ከመጀመራቸው በፊት በዶ/ር አኧዘ ጣዕመ፣ ሙሉ የጤንነት ምርመራ የተደረገላቸው ሲሆን “ዘ አዘር ፌስ ኦፍ ኢትዮጵያ” ሙሉ ወጪያቸውን እንዲሁም አዲካ ለቀረጻ የሚያገለግላቸውን መኪና እንዳበረከተላቸው ከተጓዦቹ አንዱ የሆነው አርቲስት መሃመድ ካሣ ገልጿል፡፡

የጉዞው ዓላማ የአድዋ ጀግኖችን መዘከርና እነሱ የተጓዙበትን አስቸጋሪ መንገድ ማስታወስ ሲሆን አባላቱ የጉዞ መስመራቸውን ያደረጉትም አጼ ሚኒልክ ጦራቸውን ከአዲስ አበባ ይዘው በወጡበት መንገድ ነው ብሏል - አርቲስት መሃመድ፡፡ በዛሬው እለት ከአዲስ አበባ ከ400 ኪሎ ሜትር በላይ በምትርቀው ሀይቅ ከተማ የሚደርሱ ሲሆን የጉዞው ፍጻሜ የአድዋ በዓል ዕለት የካቲት 23 ቀን 2006 ዓ.ም ይሆናል፡፡ የጉዞው አባላት መሃመድ ካሳን ጨምሮ 5 ሲሆኑ የኢትዮፒካ ሊንክ ሬዲዮ ፕሮግራም አዘጋጅ ብርሃኔ ንጉሴ እንዲሁም ኤርሚያስ አለሙ፣ ሙሉጌታ መገርሣ (አማሩ) እና አለም ዘውዱ ካሣሁን ይገኙበታል፡፡በጉዟቸው የጤና እክል እንዳላጋጠማቸው የገለጹት የጉዞው አባላት፤ በዶ/ር አኧዞ የቅርብ ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

Published in ዜና

በቶም ፊልም ኘሮዳክሽን የቀረበው “ፅኑ ቃል” ፊልም የካቲት 2 ቀን 2006 ዓ.ም በሁሉም የግል ሲኒማ ቤቶች እንዲሁም

የካቲት 3 በሸራተን አዲስ እና በመንግስት ሲኒማ ቤቶች ለእይታ ይቀርባል፡፡
የ1 ሰዓት ከ50 ደቂቃ ርዝማኔ ያለውን ይህን ፊልም ሠርቶ ለማጠናቀቅ ከአንድ ሚሊዮን ሶስት መቶ ሺህ ብር በላይ ወጪ

የፈጀ ሲሆን ዳንኤል በየነ ዳይሬክት አድርጐት፣ ቶማስ ጌታቸው በደራሲነትና ኘሮዱዩሰርነት ተሣትፎበታል፡፡
የሮማንስ ሰስፔንስ ዘውግ ባለው በዚህ ፊልም ላይ መሪ ተዋናዮቹን እነ ግሩም ኤርሚያስ፣ ማህደር አሰፋና ኤልያስ

ወሰንየለህን ጨምሮ ከ450 በላይ ባለሙያዎች ተሣትፈውበታል፡፡
ቶም ፊልም ኘሮዳክሽን ከአሁን ቀደም “ስርየት” እና “ፔንዱለም” የተባሉ ፊልሞችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡

Published in ዜና

“አክሱም ዩኒቨርስቲ ውስጥ የሚገኘው የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ፎቶ እርሣቸውን አይመስልም” የሚል ዘገባ ለህትመት በማብቃቱ ዩኒቨርስቲው ክስ የመሰረተበት ሎሚ መፅሔት ዋና አዘጋጅ ሰናይ አባተ፣ ረቡዕ ዕለት ማዕከላዊ ቀርቦ ቃሉን ከሰጠ በኋላ በ5ሺ ብር ዋስ መለቀቁን የመፅሄቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጋዜጠኛ ዳንኤል ድርሻ ገለፀ፡፡ ባለፈው ህዳር ወር በመፅሄቱ ላይ የወጣው ፅሁፍ ከአንባቢ የተላከ እንደነበር ያስታወሰው ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፤ ከፎቶው ጋር የተላከው ፅሁፍ፤ “የአክሱም ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ፎቶ ቢኖርም ፎቶው ግን እርሳቸውን አይመስልም” የሚል እንደነበር ተናግሯል፡፡ አስተያየቱ የመጣው ከአክሱም አካባቢ እንደሆነና መጽሔቱም የሰዎችን ሃሳብ በማስተናገድ የሚያምን በመሆኑ፣ ፎቶውን ከእነ ፅሁፉ ማስተናገዱን ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ገልጿል፡፡

መጽሔቱ ከወጣ በኋላ የአክሱም ዩኒቨርስቲ የህዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ አቶ ቢኒያም ዳኘው ለመፅሔቱ ዝግጅት ክፍል ደውሎ፤ “እንዲህ ዓይነት ፎቶም ሆነ ሐውልት በዩኒቨርስቲያችን ውስጥ የለም፤ ስህተት ነው” በማለት ማስተባበያ እንዲያወጣ መጠየቁንም ጠቁሟል፡፡ ዩኒቨርስቲው የላከው ማስተባበያ ውስጥ “የክቡር አቶ መለስ ዜናዊም ሆነ የሌሎች ለአገሪቱ ታላላቅ ውለታ የዋሉ ሰማዕታት ሐውልት የለም” የሚል ሃሳብ የሰፈረ ሲሆን፤ ከዚህ ማስተባበያ ውስጥ “ሐውልት” የምትለው ቃል በስህተት ብትዘለልም በሩብ ገፅ አስተናግደነዋል፤ ሆኖም ዩኒቨርስቲው አንዲት ቃል ስለተዘለለች ብቻ ክስ መስርቶብናል ብሏል - ጋዜጠኛ ዳንኤል፡፡

በአሁኑ ወቅት በየአጋጣሚው ፕሬሱን ለማዳከም እየተሰራ መሆኑን የሚያሳየው፣ ሩብ ገጽ ማስተባበያ ወጥቶ በአንዲት ቃል ክስ መመስረቱ ነው” ብሏል፡፡ ከዚህ ቀደም ልጆቻቸው በመቀሌ ማረሚያ ቤት የታሰሩባቸው አቶ አስገደ ገ/ስላሴ የልጆቻቸውን መታሰርና የእስር ቤቱን አያያዝ ጉዳይ በተመለከተ ኩባ ውስጥ ከሚገኘው “ጓንታናሞ” የተባለ የአሜሪካ እስር ቤት ጋር እያመሳሰሉ የፃፉትን ጽሑፍ በማስተናገዱ የትግራይ ፖሊስ በመጽሔቱ ላይ ክስ መመስረቱን ያስታወሰው ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ፤ ይህን መሰል ክሶች የሰዎችን የመናገርና ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ ህገ-መንግስታዊ መብት የሚፃረር በመሆኑ እንደሚቃወመው ተናግሯል፡፡

Published in ዜና
Page 13 of 13