የቴሌቪዥን ስርጭቶች የሚተላለፉበት አንዱ መንገድ በጠፈር ላይ የሚገኙ ሳተላይቶችን በመጠቀም ነው፡፡ በዚህ መንገድ ለኢትዮጵውያን እንደ አማራጭ ሆኖ የቀረበ የቴሌቪዢን ጣቢያ ነው - ኢቢኤስ፡፡ ጣቢያው ከተመሰረተ ጀምሮ አስተማሪና አዝናኝ ፕሮግራሞችን በማቅረብ ከአማራጭም በላይ ለመሆን ችሏል፡፡ ለዚህም ምስክሩ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ ተቀባይነትን ማግኘቱ ነው፡፡
በቅርቡ በጀመረውና ምንም ኢትዮጵያዊ መልክ በሌለው ከውጭ በተቀዳ ፕሮግራሙ ምክንያት ግን ለትችት ተጋልጧል፡፡ በግል ምልከታዬ፣ ይህ ፕሮግራም ኢቢኤስን የሚመጥን አይደለም፡፡ እስቲ ፕሮግራሙ ለኔ የሰጠኝን ስሜት ላጋራችሁ፡፡ ቅዳሜ ህዳር 27 ቀን 2006 ዓ.ም 12፡00 የተጀመረውና 35 ደቂቃ የወሰደው ሙሉ ፕሮግራም የሚከተለውን ይመስላል፡፡
ፕሮግራሙ ሲጀምር አንድ የ17 ዓመት ልጃገረድ (ተረኛ ባለ ልደት ነች) በሚያምር ሰፊ አልጋ ላይ ተኝታ ያሳያል፡፡ ይህች ተረኛ ባለ ልደት ከተኛችበት ምቹ አልጋ እየተንጠራራች ተነስታ፣ በረጅም መስታወት ፊት በመቆም ጸጉራን በጣቶቿ በተን በተን ታደርግና፣ ቻፒስቲኳን ከመደርደርያው አንስታ ከንፈሯን ትቀባለች፡፡ ከዚያም ጓደኞቿ እቤቷ ድረስ በመኪናቸው መጥተው ይወስዷታል፡፡ (የዚህች ባለ ልደት ኑሮ እንኳን ለመኖር ለማሰብም ይከብዳል‘ኮ! በቁጥርም ቢሰላ እንደሷ ባማረ አልጋ ላይ በምቾት የሚተኙ ኢትዮጵውያን ከመቶ አምስት መሙላታቸውን እንጃ፡፡ የቤታችን መስታወት‘ኮ ግማሽ ፊታችንን ብቻ የሚያሳይ ነው፤ አለባበሳችንን እንኳ እድሜ ለከተማችን ባለመስታወት ፎቆች! ወደ ግራ ወደ ቀኝ እያልን አስተካክለን እንውላለን፡፡ እኛ 95 በመቶ ኢትዮጵያውያኖች እንግዲህ እንዲህ ነው ኑሮአችን!)
ከዚያም በሚያምረው የመኖሪያ አካባቢያቸው ለመዝናኛ ተብሎ በተከለለው ስፍራ ውስጥ ለምለም ሳር ላይ ከጓደኞቿ ጋር ሩጫ  ሲወዳደሩ፣ በጀርባቸው ሲንደባለሉና የቅርጫት ኳስ ሲጫወቱ ይቆዩና፣ ተመልሰው በመጡበት መኪና ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ (እኛ 95 በመቶ ኢትዮጵያውያኖችስ? …ሆ! እኛ‘ኮ እንኳን ተከልሎልን ለምለም ሳር ላይ ልንጫወት በራሳችን ተነሳሽነት ሜዳ ብለን በሃሳብ መስመር የከለልነው አቧራማና ድንጋያማ ሜዳ ለልማት ተብሎ የታጠረብን ምስኪኖች ነን!)
ወደ ቤታቸው ከገቡም በኋላ ተጣጥበው፣ ለልደቷ ቁሳቁሶች ለመግዛት ተሰባስበው በመኪናቸው ይወጣሉ፡፡ ከዚያም በመሃል ከተማ ከሚገኙት ስመ ገናና ውድ ሱቆች ውስጥ ይገቡና እንኳን ከኪስ አውጥቶ ለመክፈል፣ ለማሰብ እንኳ በሚከብድ ዋጋ የሚፈልጉትን ገዝተው ይመለሳሉ፡፡ (እኛስ?... እኛ‘ኮ አዲስ ልብስ የምንለብሰው አዲስ አመትን ጠብቀን ነው - እሱም ከሞላልን ነው፡፡ ታዲያ የ5 በመቶ ኢትዮ-አሜሪካኖችን ኑሮ እያየን መሳቀቅ አለብን እንዴ ጎበዝ!)
በመቀጠል ያቺ የታደለች ባለልደት ከጓደኛዋ ጋር ሆና ወደ ውበት ሳሎን በማምራት፣ ይህ ቀረሽ በማይባል ደረጃ ትዋብና መጥቶ የሚወስዳትን መኪና ትጠባበቃለች፡፡ መኪናው ሲያዩት ያምራል፤ ዋጋው ግን ያስፈራል! በሚሊዮን ብር የሚገመት ነው በተባለለት በዚህ መኪና፤ በግራና በቀኝ በጥቋቁር ሞተር ሳይክሎች በመታጀብ፣ ወደተዘጋጀላት የልደት አዳራሽ ትከንፋለች፡፡ ባለሚሊዮን ብሩ መኪና መንገዱን ዚግዛግ እየመታ፣ የጎን መብራቶቹን ብልጭ ድርግም እያደረገ፣ በጥሩምባው ከተማውን እየበጠበጠ ከአዳራሹ ደረሰ፡፡ ለልደቷ የተጋበዙ ጓደኞቿ በራፍ ላይ ተኮልኩለው ጠበቋት፡፡ አላሳፈሯትም፡፡ ገና ያለችበትን መኪና ሲመለከቱ አካባቢውን በጩኸት ደባለቁት፡፡ አጠገባቸው እንደደረሰች የመኪናው በር ተከፍቶላት በቄንጥ ወረደችና ወደ አዳራሹ ዘለቀች፡፡
(እኛስ?... እኛማ እንኳን በሚሊዮን ብር መኪና  ታክሲም በግድ ነው፤ በሰልፍ እየተንገላታን፡፡ ባቡራችን ቢደርስልን እንኳ በገንዘብ መወዳደር ባንችል እንኳን በፍጥነት እንቀራረብ ነበር፡፡ ከዚህ ውጪ መቼም አማራጭ የለም፤ ያው እንደፈረደብን በአንበሳችን እንታጨቃለን እንጂ!)
አዳራሹ በእንግዶቿ ተሞልቷል፤ ወደ አዳራሹ እንደተገባ በስተቀኝ በኩል መጠነኛ መድረክ ተዘጋጅቷል፡፡
 አጋፋሪም ተመድቦለታል፤ በፈረንጅ ቡዳ የተበላ ይመስል አንድም የአማርኛ ቃል ሳይተነፍስ ነው ፕሮግራሙን የመራው፡፡ ለነገሩ ማን ያውቃል? “አማርኛ ከተናገርክ ወዮልህ!” ተብሎም ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው አስገራሚው ነገር ደግሞ አንድም የኢትዮጵያ ሙዚቃና ውዝዋዜ ሳይታይ ነው ዝግጅቱ የተጠናቀቀው፡፡
ከዚህ በኋላ “በዓይነቱ ልዩ የሆነ ኬክ” ቀርቦ ባለ ልደቷ ቆረሰች፤ ርችቶች ተለኮሱ፤ ጩኸት በረከተ፤ ኬክ ተወራወሩ፤ ፊታቸውን ተለቀለቁት፡፡ በመጨረሻም ባለ ልደቷ ወደ መድረኩ በመውጣት ጋብዛቸው ሳያሳፍሯት ለመጡ ጓደኞቿ ምስጋና አቅርባ፣ ቀሪው ጊዜ ያማረ እንዲሆን ተመኝታ ወረደች፡፡ የልደት በዓሉ እዚህ ጋ ይጠናቀቅና ከአንድ ጓደኛዋ ጋር በመሆን አረጋውያንን ስትጎበኝ ተመለከትን፡፡ (በኔ ዕይታ ከፕሮግራሙ ውስጥ ብቸኛ መልካም ተግባር ይሄ ነው፡፡)
እንግዲህ ይህ ነው “One‘s in a Life” ማለት፡፡ አንድም ኢትዮጵያዊ መልክ የሌለው (እኛን የማይመስል) ፕሮግራም እንዴት ለኢትዮጵያውያን አማራጭ ተብሎ በተመሰረተ የቴሌቪዥን ጣቢያ እንዲቀርብ ይደረጋል? በእኔ አስተያየት ፕሮግራሙ መልካምነቱ ለተመሰከረለት ጣቢያ የማይመጥን፣ የህብረተሰቡን የኑሮ ደረጃ፣ ባህልና ወግም ከግንዛቤ ውስጥ ያላስገባ ነው፡፡
ከእኛ ይልቅ ለውጭዎቹ ይበልጥ የሚቀርብም ነው፡፡ (ምናልባት ለዳያስፖራ ኢትዮጵያውያን?) እንደሚመስለኝ ባህል ወግ ልማዴን ትቼ ካልጠፋሁ እያለ ያስቸገረውን ወጣት፤ ወደ ቀድሞ ክብሩ መመለስ ባይቻል እንኳ፣ ባለበት ተረጋግቶ እንዲቆም ማድረግ የሁላችንም ኃላፊነት ነው፡፡ መልካም  ሳምንት!

Published in ባህል

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው አእምሮ ሀኪም ዘንድ ይሄድና…“ዶክተር፣ መጥፎ ተግባራት እየፈጸምኩ ህሊናዬ እየረበሸኝ ነው…” ይለዋል፡፡
ዶክተሩም… “እና መጥፎ ድርጊት ከመፈጸም የሚከላከል ህክምና እንዳደርግልህ ነው የምትፈልገው?” ይለዋል፡፡ ሰውየውም… “አይደለም…”  ይላል፡፡
ዶክተሩም… “ታዲያ ምን ፈልገህ መጣህ?” ይለዋል፡፡
ሰውየው ምን ቢል ጥሩ ነው…“ህሊናዬን ከሥሩ ነቅለህ አውጣልኝ!”
‘አልሰሜን ግባ በለው’ አሉ…እኛ ዘንድ ቢመጣ ህሊና እያለም እንዴት ‘ህሊናቢስ’ መሆን እንደሚቻል ‘በስምንተኛ ዲግሪ’ ደረጃ እናሰለጥነው ነበር፡፡ የምር ግን የህሊና ነገር እኮ እኛ አገር የሆነች ተረስታ ከአሮጌ አንሶላ ጋር የተጠቀለለች ነው የምትመስለው፡፡  
እናላችሁ…“ትንሽ ህሊና እንኳን የለህም!” ብሎ አማረኛ ቀረ፡፡ ህሊና የሰው ስም ብቻ የሚመስለን እየበዛን ነዋ! (“ህሊና ቢኖረኝ እዚህ አገር ታገኙኝ ነበር ወይ…” ያልከን ወዳጃችን በእግርህ አስነካኸው እንዴ!)
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ነገርየው እንዴት ነው…‘ጉልቤ’ ነገሮች በዙብና! ልክ ነዋ…ጉልቤነት ማለት እኮ የግድ ‘አገጭ ማጣመም’፣ ጥርስን ‘በመሀረብ ማስቋጠር’ ምናምን ማለት ብቻ አይደለም፡፡ የዘንድሮ ‘ጉልቤነት’… አለ አይደል…መአት መልክ አለው፡፡
እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ…የሆነ ሚኒባስ ታክሲ ላይ ያየነው ‘ጥቅስ’ ነው…‘ጥቅሱ’ ምን ይል መሰላችሁ… (ምንም ደስ ባይልም መነገር አለበት፣) “አፍህን ከምትከፍት ሱቅ ክፈት” ይላል፡፡
እናላችሁ…እንዲህ አይነት በህዝብ መገልገያ ላይ ከእግር ጥፍር እስከ ራስ ጸጉር ‘ሙልጭ የምንደረግበት ዘመን ላይ ደርሰንላችኋል፡፡ የምር ግን… እንደዚህ አይነት ነገር መጀመሪያ ስናይ ፈገግ እንደ ማለት ይቃጣናል፡፡ ግን… እኛም ተሰዳቢዎች መሆናችን ሲገባን…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ምን መሰላችሁ…‘የቤትሽን ዓመል እዛው’  ‘አትንጣጪ’ ምናምን ሲባል ዝም ተብሎ ተከረመና አሁን ደግሞ “አፍህን አትክፈት…” ወደ መባል ደርሰናል፡፡
የምር እኮ…ነገርየው በዚሁ ከቀጠለ …ቀስ ብሎ…በአንድ ወቅት እዚች ዋና ከተማችን ጎራ ያለ የገጠሩ ሰውዬ… “አዲስ አበባ ገዳይ ጠፋ እንጂ ሟች ብዙ ነበር!”  ያለበት አይነት ስድብ ነገ ተነገ ወዲያ የማይለጠፍበት ምክንያት የለም፡፡ እነማ…እንደዚህ አይነት ነገር ሲበዛብን፣
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
የምር አስቸጋሪ ጊዜ ነው፡ የደንብ ልብስ የለበሱ በከተማው ጎዳናዎች በበዙበት ጊዜ፣ ማስቲካና መፋቂያ ሻጮች ሲሯሯጡ በምናይበት ጊዜ… አንዳንድ አካባቢ ተረጋግቶ መገበያየት እንኳን እያስቸገረ ነው፡፡ እኔ የምለው… እግረ መንገዴን…የገበያተኛ መዋከብ ‘የደንብ ጥሰት’ ለመሆን ያንሳል እንዴ!
በቀደም መርካቶ ዕቃ ቢጤ ለማየት ወጣ ብለን… “አይ መርካቶ!”  ብለን ተመለስን እላችኋለሁ፡፡ የምር እኮ… የምንጣፍ ሱቆች በበዙበት አካባቢ መራመድ እስኪያቅታችሁ ድረስ ትከበባላችሁ፡፡  ‘የደላላው’ ብዛት! የሆነ ሱቅ ውስጥ ለመግባት ስታስቡ ወጣት ደላሎች እየተከተሉ… “መጋዘኑ እዛ’ጋ ነው፣ ቅናሽ አለው…” “እዛ ሱቅ ያለው አሪፍ ነው…” ምናምን እየተባለ እስኪሰለቻችሁ ድረስ የሚቀባበሏችሁ ወጣቶች ብዛታቸው… አለ አይደል… ያበሳጫል ብቻ ሳይሆን ‘ያስፈራል’ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
እንግዲህ ይህ ሁሉ ሲሆን በአካባቢው የደንብ ልብስ የለበሱ ሰዎች ውር፣ ውር ይታያሉ— የሚያስጥል የለም እንጂ፡፡ እናላችሁ… ገበያተኛ ሲጉላላ፣ ደንብ አስከባሪውም ዝም፣ ነጋዴውም ዝም፣ ሁሉም ዝም ሲሆን… አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እዚህ አገር መድረክ ላይም ‘ሙልጭ’ ተደርጎ መሰደብ እየተለመደ ነው፡፡ መጀመሪያ ሰብሳቢው…“መሀላችን የተሰገሰጉ የራሳቸው ዓላማ ያላቸው…” ምናምን እያለ ‘ሆረር’ ምናምን ነገር ይለቅባችኋል፡፡
‘አስተያየት ሰጪው’ ተነስቶ… “በተባለው ላይ የምጨምረው የለኝም…” ይልና  “ዕድገታችንን ለመግታት የሚፍጨረጨሩ አንዳንድ የስብሰባው ተካፋዮች ላይ እርምጃ ለምን እንደማይወሰድ…” በቁጭት ይጠይቃል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን እከሌ፣ እከሌ ተብሎ እስካልተጠቀሰ ድረስ አንዳንድ “…የስብሰባው ተካፋዮች…” የሚለው ሁላችንንም ስለሚመለከት…አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንድንል ያደርገናል፡፡
አሀ… ማን በበላው ማን ‘ራዳር’ ውስጥ ይገባል! ልጄ ዘንድሮ ‘…ሁሉም እንደ የሥራው…” ምናምን የሚል አባባል፣ ‘ጥቅስ’…ነገር አይሠራም፡፡ ልጄ…ዘንድሮ ሰው ‘ባልሠራው’ የሚበላበት፣ ‘ባልሠራውም’ የሚበላውን የሚያጣበት ዘመን ነው፡፡
ይቺን ስሙኝማ…የመንገድ ግንባታ ሥራ ላይ ነው አሉ፡፡ እናላችሁ…አንዱ ሠራተኛ አካፋ አልነበረውም፡፡ ታዲያ…አለቃውን፣ “አካፋ የለኝም…” ይለዋል፡፡ አለቅየውም…“ታዲያ ምን ያነጫንጭሀል! አካፋ ከሌለህ ሥራ አትሠራ!” ይለዋል፡፡ ሰውየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው… “ታዲያ እንደ ሌሎቹ ሠራተኞች ምን ተደግፌ ልቁም?” ብሎ አረፈላችሁ፡፡
እናማ…በየቢሮው፣ በየሥራ ቦታው ‘አካፋ ተደግፈን’ የምንቆም መአት ነን፡፡
ይቺን አሪፍ ነገር ስሙኝማ…ሰውየው ለጓደኛው ሲደውል ከጀርባ ድምጽ ይሰማል፡፡ “የምን ጫጫታ ነው የምሰማው?” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም… “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ይለዋል፡፡ ሰውየውም ግራ ይገባዋል፡፡ “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል ብሎ ነገር ምንድነው? ወይ ልደት ታከብራለህ፣ ወይ ዓመታዊ በዓል ታከብራለህ፡፡ ሁለቱ የሚገናኙ አይደሉም…” ይለዋል፡፡
ጓደኛየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“አይ ሞኞ…የእህቴን አሥራ ስምንተኛ ዓመት ልደት አሥራ አምስተኛ ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ብሎት አረፈ፡፡ አሪፍ አይደል!
የዕድሜ ነገር ከተነሳ… ይቺን ስሙኝማ…“በቀደም ሀያ ዘጠነኛ ዓመቴን ሳከብር ለምንድነው ስጦታ ያልሰጠኸኝ?”  ብትለው እሱዬው… “ረሳሽው እንዴ! የዛሬ አምስት ዓመት ሀያ ዘጠነኛ ልደትሽን ስታከብሪ ሽቶ አልሰጠሁሽም?” ብሏት አረፈ፡፡
እናላችሁ…ጉልቤነት መልኩን እየለዋወጠ መከራችንን እያበላን ነው፡፡ ቤት አከራይ በቀን ሁለት ባሊ ውሀ ብቻ እየፈቀደ፣ መብራት በሦስት ሰዓት ላይ እያጠፋ፣ “ከአንድ ሰዓት በኋላ ማምሸት ክልክል ነው…” አይነት ክፉ ሚስት እንኳን የማታስበው ‘ህግ እያረቀቀ’ ይቆይና አንድ ቀን ማታ በር ይንኳኳል፡፡ እናንተም ስትከፍቱ አከራያችሁ ተኮሳትረው ቆመዋል፡፡ እናንተም…“ደህና አመሹ፣ ምነው ደህና!” ስትሉ ምን ትባሉ መሰላችሁ…“ኪራዩ ላይ ከሰኞ ጀምሮ አንድ ሺህ ብር ጨምረናል፡፡
 ካልተስማማችሁ በሁለት ቀን ውስጥ ቤቱን ልቀቁልን፡፡” የምር ያበሳጫል፡፡ ስሙኝማ…የብስጭት ነገር ከተነሳ … “እንትናዬው ምን ያህል ብታበሳጨው ነው ሴቶችን እንደዚህ ጠምዶ የያዛት!” የሚያሰኝ ንግግር ገጥሟችሁ አያውቅም!
ሰውየው ጓደኛውን… “ሬድዮ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠረው በገነት ውስጥ ነው ሲሉ ሰማኋቸው፡፡
ምን ማለታቸው ነው?”  ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ጓደኝዬውም ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“እሱን የነገሩህ ሰዎች ፈጣሪ አዳምን ፈጠረ፡፡ ከዚያም ከጎኑ የጎድን አጥንት አወጣና የመጀመሪያውን ድምጽ ማጉያ ፈጠረ ማለታቸው ነው፣”  ብሎት አረፈ፡፡‘ጉልቤነትን’… አለ አይደል… ሲሆን ያስወግድልን፣ ካልሆነም የምንሸከምበትን ትከሻ ያደንድንልን፡፡
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” የምንልበትን ጊዜ ያሳጥርልን፡፡  
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

   ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት የውሃ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ደርሶ ኖሮ ከውሃው ወጥታ ወደ ባህሩ ዳርቻ ትሄዳለች፡፡ይቺ ኤሊ ቀስ እያለች በረጅሙ የአሸዋ መንገዷ ስታዘግም ሁለት ጓደኛሞች ያዩዋታል፡፡
አንደኛው ፤ “ይቺ ዔሊ ወዴት ነው የምትሄደው?” ይላል፡፡
ሁለተኛው፤ “የመውለጃ ጊዜዋ ደርሶ ይሆናል”
አንደኛው፤ “የመውለጃዋ ጊዜ ቢደርስ ወደ አሸዋው ምን ያስኬዳታል? መኖሪያዋ ውሃ ውስጥ ነው፡፡ እዚያው ወልዳ ተገላግላ እርፍ አትልም እንዴ?”
ሁለተኛው፤ “ለምን ውሃ ውስጥ እንደማትገላገል አላውቅም፤ የማውቀውና ሰዎች ሲሉ የሰማሁት ግን፤ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ሲደርስ ወደ ባሕሩ ቅርብ ዳርቻ አይደለም የምትጓዘው፡፡ ከውሃው እጅግ እርቃ ወደማይታይ አቅጣጫ ነው የምትሄደው”
“ልጆችዋን እሩቅ ቦታ ሄዳ የምትገላገል ከሆነ፤ በኋላ እንዴት አድርገው ልጆችዋ ከሷ ጋር ይገናኛሉ? እናታቸው በባሕሩ ውስጥ መሆኗንስ እንዴት ያውቃሉ?”
ይህ ጥያቄ በጣም ውስብስብና በቀላሉ የሚፈታ ስላልሆነላቸው በአቅራቢያው ወደሚገኝ አንድ ጠቢብ ዘንድ ሄደው ሊጠይቁ ይስማማሉ፡፡
ጠቢቡ ቤት ሄደውም፤ “ጠቢብ ሆይ! አንዲት የውሃ ኤሊ አየን፤ ከውሃው ወጥታ ወደ አሸዋው ዘልቃ እርቃ ሄደች፡፡ በኛ ግምት የመውለጃዋ ቀን ደርሶ ይሆናል ተባባልን፡፡ ግን አንድ ጥያቄ አነሳን፡፡ ወልዳ ወደ ባሕር ስትመለስ ልጆችዋን ማን ያመጣላታል? መቼም ህፃናት ናቸውና አውቀው ወደ ባሕሩ አይመጡም፡፡ ደግሞስ ያን ያህል ሰፊ ባሕር ውስጥ እናታቸው የት ትኑር የት እንደምን ያውቃሉ” ሲሉ ጠየቁት፡፡ ጠቢቡም “የአምላክን ተአምር የምታደንቁት እነዚህን አይነት ጉዳዮችን ለመመርመር ስትችሉ ነው፡፡ ኤሊዋ ልጆችዋን የምትወልደው እንዳላችሁት ከባሕሩ ራቅ ያለ ቦታ ሄዳ ነው፡፡ እንዳላችሁትም ከተገላገለች በኋላ የባሕሩ ዳርቻ አሸዋ እንዲሞቃቸው እዚያው ትታቸው ነው ወደ ባሕሩ የምትመለሰው፡፡ ልጆችዋ እስኪጠነክሩ ድረስ እዚያው አሸዋው ላይ ይቆዩና ሰፊውን አሸዋ አቋርጠው ወደ እናታቸው ይመለሳሉ፡፡ የተፈጥሮ ህግ ስለሆነ ያለ ጥርጥር በባሕሩ ውስጥ እናታቸው የቱ ጋ እንዳለች ያውቃሉ፡፡ ዋና አስገራሚ ነገር ግን ወደ ባሕሩ በሚመጡ ጊዜ መንገድ ላይ አደጋ መኖሩ ነው፡፡ በባሕሩ ዳርቻ ላይ የኤሊ ጫጩት እየተመገቡ የሚኖሩ ወፎች አሉ፡፡ ከጫጩቶቹ መካከል በወፎቹ ከመበላት ተርፈው እናታቸው እቅፍ ውስጥ ለመግባት የሚችሉት ጥቂቶቹ የታደሉቱ ናቸው፡፡ ይህ የአምላክ ስርዓተ ተፈጥሮ ነው፡፡ ትላንት እንደዚያ ነበረ፤ ዛሬም አለ፤ ነገም በአግባቡ ይቀጥላል፡፡” አላቸው፡፡
የፍጥረታትን ተዓምር እያደነቁ ወደመጡበት ተመለሱ፡፡
***
በዓለም ላይ በዚህም ቢሉት በዚያም ከመሆን የማይቀር ነገር አለ፡፡ መንግስታት ይለወጣሉ፤ አገሮች ባሉበት ይቆያሉ፡፡ የሚሠሩ ያገኛሉ፡፡ ዳተኞች ባዶ እጃቸውን ይቀራሉ፡፡ የሚጥሩ ዳር ይደርሳሉ፡፡ የተኙ ወደ ኋላ ይሄዳሉ፡፡ ይሄ ተፈጥሮአዊ የሆነው ነገር አይቀሬ ነው፡፡ ከኤሊ ጫጩቶች መካከል ተርፈው ለእናታቸው የሚኖሩ ጥቂቶቹ ይሁኑ እንጂ ይኖሩ ዘንድ የተፈቀደላቸው የታደሉ ናቸው፡፡ ያልታደሉት ባጭር ይቀጫሉ፡፡ ይህ ህግ ሁሌም የሚኖር ነው፡፡ ሰው የሚሰራው ነገር ተጨማሪ ነው፡፡ ያም ሆኖ
“አለ አንዳንድ ነገር
በዚህ ቢሉት በዚያ ከመሆን የማይቀር”  ይላሉ ደራሲ ከበደ ሚካኤል፡፡ በዚህ ውስጥ የተቃራኒዎች አንድነትና ትግል ሁሌም አይቀሬ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ መግዛቱን ለመቀጠል ተገዢዎች የኛም ፓርቲ የገዢነት ቦታ ሊኖረው ይገባል በማለት እስኪሸናነፉና እስኪለይላቸው ጉዞአቸውን ይቀጥላሉ፡፡
“ልምድን ከሩቅ ሆነህ አታየውም፤ ሲከሰት ግን መኖሩን ታውቃለህ” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለመማር ዝግጁ የሆነ ባወቀው ይጠቀማል፡፡ አትማር ያለው ባወቀውም ይደነቁራል፡፡ በሀገራችን ብዙ ፓርቲዎች ተወልደዋል፡፡ ብዙዎች ሞተዋል፡፡ አንዳንዶች ቀንቷቸዋል፡፡ አንዳንዶች በአጭር ተቀጭተዋል፡፡ የሁሉም የጋራ ሀብት ግን ከኖሩት አለመማር ሆኖ ታዝበነዋል፡፡ አሸናፊው ድሉን ከማሸብረቅ በቀር የሄደበትን መንገድ ዳግመኛ ለመመርመር አይቃጣውም፡፡ ተሸናፊው ቂም በቀሉን ከማመንዠክ እና ጊዜ ከመጠበቅ በቀር ያለፈውን ሁኔታ አጥንቶ በወጉ ለነገ ለመዘጋጀት ከቶም ልቦና የለውም፡፡ ይህ ሀቅ ሁሌም ምርጫ በመጣ ቁጥር የሚያጋጥመው እውነታ ነው፡፡ ትላንት በምርጫው አሸናፊ ነኝ የሚለው ወገን ለአሸናፊነት ሁሌም የታጨሁና ሁሌም የሚሳካልኝ ነኝ የሚለውን አስተሳሰብ የማይለወጥ እውነታ አድርጐ መውሰዱን አይን ካለን እናያለን፡፡ በአንፃሩ ትላንት በምርጫው ተሸናፊ የሆነው ወገን ደግሞ በመጭበርበር ተሸነፍኩ እንጂ ልክ ነበርኩ የሚለውን ሃሳቡን ሳይለውጥ አምስት አመት ይኖራል፡፡ በኢትዮጵያ ሠርጉ ካልደረሰ በርበሬ አይቀነጠስም ይባላል፡፡ አድፍጦ፣ አሳቻ ጊዜ መርጦ ለማነቅ ጀግና መባል አንዱና ዋነኛው የትግል ዘዴ በሆነበት ሀገር፣ የዲሞክራሲ እውንነት ሁሌም ጥያቄ ውስጥ ነው፡፡
ያለ ዲሞክራሲያዊ መስተጋብር ህይወት የአዘቦት መንገዷን እንጂ የተለወጠ ጐዳና ወይም እግረ መንገድ እንኳ ልትቀዳጅ አይቀናትም፡፡ የትግሉን ሂደት ከማየት ይልቅ ስወለድም እንዲህ ነበርኩ ማለትም አጉል መመካት ነው ይሉናል አበው ጠበብት፡፡ እኛ ብቻ ነን ለዚህ ስልጣን የተቀባን የሚለው ሃሳብ ግዘፍ ነስቶ የምናየው ለዚህ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን ብለን እናማትብ፡፡ አንድ የፖለቲካ ድርጅት በእውነትም ሆነ በውሸት ምርጫ ሲያሸንፍ “ፍፁም ስለሆንኩ አሸነፍኩ” የሚል አስተሳሰብ ውስጥ መዋኘቱ አይገርሜ ነው! ግቡን መምታቱ ያላጋጠሙትን አሊያም አጋጥመውት ያልዘገባቸውን መንሸራተቶችና መሰናክሎች ወይም ሰንካላ እድሎች እንዲረሳ የደረሰበት ወንበር ክፉ ንቀት ይሰጠዋል! ዛሬ እዚህ የደረስከው በሠራኸው ጥሩም፣ መጥፎም ነገር  ነው፡፡ የሚለውን ልብ አይልም፡፡ “መሠላል ያላንሸራተተው ሁሌ ጫፍ የሚወጣ ይመስለዋል” የሚለው ተረት ከላይ የተጠቀሰውን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡
“ጥሩው ብቻ አይደለም እዚህ ያደረሰህ
መጥፎም ነው እኮ ያንተ ማንነትህ” እንደማለት ነው በግጥም ሲለገጥ፡፡  




Published in ርዕሰ አንቀፅ

ምርጫው ሳይነገረን ነው የተካሄደው ብለዋል
ታዛቢዎቹን ህብረተሰቡ ነው የመረጣቸው - ምርጫ ቦርድ
  በግንቦቱ ምርጫ የሚወዳደሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ባለፈው ሳምንት የተካሄደው የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ ከህግና ደንብ ውጪ፣ የገዢው ፓርቲ አባላት የተመረጡበት ነው በማለት የተቃወሙ ሲሆን ምርጫ ቦርድ በበኩሉ፤ የህዝብ ታዛቢዎችን ህብረተሰቡ ነው የመረጣቸው ብሏል፡፡በዘጠኝ ፓርቲዎች ጥምረት የተመሰረተው የፓርቲዎች ትብብር፤ የታዛቢዎች ምርጫ በተከናወነ ማግስት “የታዛቢዎች ምርጫ የገዥውን ፓርቲና የምርጫ ቦርድን አንድነት ይበልጡን ያረጋገጠ ነው” በሚል ባወጣው መግለጫ፤ ምርጫው ዋና ዋና ፓርቲዎችን ባገለለ መልኩ የተከናወነ ነው ሲል ቅሬታውን አቅርቧል፡፡ የህዝብ ታዛቢዎች አመራረጥን በሚደነግገው መመሪያ መሠረት፤ የምርጫ ጣቢያ ሃላፊው ለህዝብ ይፋ የስብሰባ ጥሪ ማድረግ እንዳለበት ተቀምጧል ያለው የትብብሩ መግለጫ፤ ታህሣሥ 12 በተካሄደው ምርጫ ግን የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች የመረጧቸው የወጣትና የሴት ሊግ አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል ብሏል፡፡ መመሪያው ፓርቲዎች በምርጫው እንዲሳተፉ በደብዳቤ ጥሪ ይደረጋል ቢልም ከኢህአዴግ ተወካዮች ውጪ የትኛውም የተቃዋሚ ፓርቲ በፅሁፍ አልተጋበዘም ብሏል - ትብብሩ፡፡
“ምርጫ ቦርድ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ከሂደቱ ባገለለ መልኩ የምርጫ ታዛቢዎችን መርጦ መሠየሙ ለገዥው ፓርቲ መገልገያ ከመሆኑም ባሻገር ባጠቃላይ ምርጫው የኢህአዴግ የማምታቻ ፖለቲካ እንደሆነ ያረጋገጠ ነው” ይላል - መግለጫው፡፡
በ2002 ምርጫ ተመሳሳይ ነገር መፈፀሙን ያስታወሰው ትብብሩ፤ የህዝብ ታዛቢዎች ያለተወዳዳሪ የኢህአዴግ አመራር በሆኑ አስመራጮች መልካም ፈቃድ ብቻ ታዛቢ እንዲሆኑ ተደርጓል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፤ የአመራረጥ መመሪያው ለተሣታፊ ፓርቲዎች በቀጥታ ጥሪ ተደርጐላቸው እንዲታደሙ ይደረጋል እንደሚል ጠቅሰው፤ “በመገናኛ ብዙሃን ከተነገረው ውጭ በምርጫው ላይ እንድንሣተፍ ጥሪ አልቀረበልንም፤ ከዚህ አንፃር አካሄዱ ሚስጥራዊና ስህተት ያለበት ነው” ብለዋል፡፡

Published in ዜና

ምርጫው ሳይነገረን ነው የተካሄደው ብለዋል
ታዛቢዎቹን ህብረተሰቡ ነው የመረጣቸው - ምርጫ ቦርድ

በግንቦቱ ምርጫ የሚወዳደሩ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ባለፈው ሳምንት የተካሄደው የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ ከህግና ደንብ ውጪ፣ የገዢው ፓርቲ አባላት የተመረጡበት ነው በማለት የተቃወሙ ሲሆን ምርጫ ቦርድ በበኩሉ፤ የህዝብ ታዛቢዎችን ህብረተሰቡ ነው የመረጣቸው ብሏል፡፡
በዘጠኝ ፓርቲዎች ጥምረት የተመሰረተው የፓርቲዎች ትብብር፤ የታዛቢዎች ምርጫ በተከናወነ ማግስት “የታዛቢዎች ምርጫ የገዥውን ፓርቲና የምርጫ ቦርድን አንድነት ይበልጡን ያረጋገጠ ነው” በሚል ባወጣው መግለጫ፤ ምርጫው ዋና ዋና ፓርቲዎችን ባገለለ መልኩ የተከናወነ ነው ሲል ቅሬታውን አቅርቧል፡፡
የህዝብ ታዛቢዎች አመራረጥን በሚደነግገው መመሪያ መሠረት፤ የምርጫ ጣቢያ ሃላፊው ለህዝብ ይፋ የስብሰባ ጥሪ ማድረግ እንዳለበት ተቀምጧል ያለው የትብብሩ መግለጫ፤ ታህሣሥ 12 በተካሄደው ምርጫ ግን የገዥው ፓርቲ ካድሬዎች የመረጧቸው የወጣትና የሴት ሊግ አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል ብሏል፡፡ መመሪያው ፓርቲዎች በምርጫው እንዲሳተፉ በደብዳቤ ጥሪ ይደረጋል ቢልም ከኢህአዴግ ተወካዮች ውጪ የትኛውም የተቃዋሚ ፓርቲ በፅሁፍ አልተጋበዘም ብሏል - ትብብሩ፡፡
“ምርጫ ቦርድ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ከሂደቱ ባገለለ መልኩ የምርጫ ታዛቢዎችን መርጦ መሠየሙ ለገዥው ፓርቲ መገልገያ ከመሆኑም ባሻገር ባጠቃላይ ምርጫው የኢህአዴግ የማምታቻ ፖለቲካ እንደሆነ ያረጋገጠ ነው” ይላል - መግለጫው፡፡
በ2002 ምርጫ ተመሳሳይ ነገር መፈፀሙን ያስታወሰው ትብብሩ፤ የህዝብ ታዛቢዎች ያለተወዳዳሪ የኢህአዴግ አመራር በሆኑ አስመራጮች መልካም ፈቃድ ብቻ ታዛቢ እንዲሆኑ ተደርጓል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት መድረክ (መድረክ) ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፤ የአመራረጥ መመሪያው ለተሣታፊ ፓርቲዎች በቀጥታ ጥሪ ተደርጐላቸው እንዲታደሙ ይደረጋል እንደሚል ጠቅሰው፤ “በመገናኛ ብዙሃን ከተነገረው ውጭ በምርጫው ላይ እንድንሣተፍ ጥሪ አልቀረበልንም፤ ከዚህ አንፃር አካሄዱ ሚስጥራዊና ስህተት ያለበት ነው” ብለዋል፡፡
ሙሉ ለሙሉ ህገወጥ ተግባር ነው የተከናወነው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ለምርጫ ሂደቱ ወሣኝ የሆነው የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ በዚህ መልኩ መከናወኑ ገዥው ፓርቲ ምርጫውን በቁጥጥሩ ስር ለማስገባት ያስችለዋል ብለዋል፡፡ “ቦርዱ 250ሺ የህዝብ ታዛቢ አስመርጠናል ያለው የገዢውን ፓርቲ ሰዎች በማስመረጥ ነው” ሲሉም ተችተዋል - ፕ/ር በየነ፡፡
የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባል የሆነው የመላው ኢትዮጵያውያን ብሔራዊ ንቅናቄ (መኢብን) ፕሬዚዳንት አቶ መሣፍንት ሽፈራው በሰጡት አስተያየት፤ ምርጫ ቦርድ በሰሞኑ የታዛቢዎች ምርጫ ላይ ስህተት ሠርቷል ይላሉ፡፡ “ምርጫው እንደሚካሄድ በሚገባ አላስተዋወቁም፤ ለኛም አልነገሩንም” ብለዋል - አቶ መሣፍንት፡፡
ቦርዱ ለፓርቲዎች በደብዳቤ ጥሪ ማቅረብ እንደነበረበት የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፤ ጥሪው ባለመቅረቡ የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫው አሳታፊ ነው ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡ በትክክል የህዝብ ታዛቢዎች ናቸው የተመረጡት ብሎ ለመቀበል የፓርቲዎች ውክልና ያስፈልግ ነበር ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ የፓርቲዎቹ ተወካዮች በሌሉበት ታዛቢዎቹ መመረጣቸው ፍትሃዊ አይደለም ሲሉ ተችተዋል፡፡
ከ400 በላይ አባላቱን የታዛቢዎች ምርጫ በተደረጉባቸው የአዲስ አበባ አካባቢዎች ማሰማራቱን የጠቆሙት የመኢአድ ፕሬዚዳንት አቶ ማሙሸት አማረ በበኩላቸው፤ ምርጫ ሳይከናወን በ2002 ታዛቢ የነበሩ ግለሰቦች በዘንድሮ ምርጫም እንዲቀጥሉ መደረጉን ይናገራሉ፡፡
የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ ገና ከጅምሩ እንከን ነበረበት የሚሉት አቶ ማሙሸት፤ ህብረተሰቡ ታዛቢዎቹን እንዲመርጥ በቂ ቅስቀሳ አለመደረጉንና በዚህም የተነሳ በየጣቢያው ከ20 እና 30 የማይበልጡ ሰዎች መገኘታቸውን ይገልፃሉ፡፡ ባለፈው ምርጫ ታዛቢ የነበሩ ግለሰቦች ድምፀ ውሳኔ ሳይሰጥባቸው በታዛቢነት እንዲቀጥሉ ተደርጓል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ከፓርቲው የተወከሉ ግለሰቦች ያሰባሰቡት መረጃ ለህዝብ ይፋ ከተደረገ በኋላ ቅሬታችንን ለምርጫ ቦርድ እናቀርባለን ብለዋል፡፡
በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ ወረዳ 8 ተገኝተው መታዘባቸውን የተናገሩት፣ የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ በአብዛኛው በስብሰባ ቦታው የነበሩት እናቶች መሆናቸውን ይገልጻሉ፡፡ መድረክ ላይ የነበሩት ግለሰቦች የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ እንደሚካሄድ አስተዋውቀው የእለቱ ፕሮግራም መጀመሩን የጠቆሙት አቶ ዳንኤል፤ ከተሰባሳቢው መሃል ግለሰቦች እየተጠቆሙ ይመረጣሉ የሚል ግምት የነበረኝ ቢሆንም የተደረገው ግን ከገመትኩት ውጭ ነው ይላሉ፡፡ “መድረክ ላይ የነበረው ሰብሳቢ በቀጠናው ላሉ ጣቢዎች 60 ሰዎች እንደሚስፈልግ አስተዋውቆ ስም ዝርዝራቸውን መጥራት ጀመረ፤ ከተጠሩት 60 ግለሰቦች ውስጥ በእለቱ የተገኙት 22 ያህል ብቻ ነበሩ” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ የቀሩት ሰዎች ምን ይሁኑ ሲባል አንዳንዶች እየተነሱ “በቃ እኛ እናውቃቸዋለን፤ ባይመጡም ተቀበሏቸው” ይሉ እንደነበር መታዘዛቸውን ገልፀዋል፡፡ በኋላ ላይ ተቃውሞ በመቅረቡ “ከቤቱ ይመረጡ” ተብሎ 5 ደቂቃ  ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሰዎች ወደ መድረኩ እየሄዱ በሹክሹክታ ከጠቆሙ በኋላ “በቃ 60 ሰው ሞልቷል፤ መልካም የምርጫ ጊዜ ይሁንልን” ተብሎ ስብሰባው ተበተነ ሲሉ አቶ ዳንኤል የታዘቡትን ተናግረዋል፡
“ከዚህ ቀደም በነበሩት ምርጫዎች የተደረገው የኢህአዴግ አባላትን በታዛቢነት የማስመረጥ ልምድ በዚህኛው ምርጫ ላይም ተደግሟል” ያሉት ደግሞ የኢዴፓ አመራር አባል አቶ አዳነ ታደሰ ናቸው፡፡
ኢዴፓ የወከላቸው የምርጫ ታዛቢዎች፤ የኢህአዴግ አባላት የሆኑ ግለሰቦች በታዛቢነት መመረጣቸውን እንደተመለከተ ለፓርቲው ሪፖርት ማድረጋቸውን የተናገሩት አቶ አዳነ፤ በተደጋጋሚ ተመሳሳይ ሰዎች እንዲመረጡ መደረጋቸው የምርጫውን ተአማኒነት የሚያሳጣና በህዝብ ዘንድ ጥርጣሬ የሚፈጥር ነው ብለዋል፡፡
እንዲህ አይነት ችግር እንዳይፈጠር እጩዎች አስቀድሞ ታውቀውና ተገምግመው ለህዝብ ምርጫ ይቅረቡ የሚል ሃሳብ ለምርጫ ቦርድ አቅርበን ነበር ያሉት የፓርቲው አመራር አባል ግን ቦርዱ ሃሳባችንን ውድቅ አድርጎታል ብለዋል፡፡
የምርጫ ቦርድ ፅ/ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ወንድሙ ጎላ በበኩላቸው፤ የህዝብ ታዛቢዎቹን ህብረተሰቡ ራሱ ነው የመረጠው ብለዋል፡፡ ቦርዱ በሬዲዮና በቴሌቪዥን ስለታዛቢዎች ምርጫ ማስታወቂያ በማስነገሩም በመላ ሃገሪቱ ያሉ ዜጎች ተወካያቸውን በነቂስ ወጥተው እንደመረጡ ም/ኃላፊው ተናግረዋል፡፡
ቦርዱ ቀደም ብሎ የጊዜ ሰሌዳ አውጥቶ ለሚመለከታቸው ሁሉ ማሰራጨቱን የጠቆሙት ኃላፊው፤ የታዛቢዎች ምርጫን በተመለከተ በሚዲያ በቂ ማስታወቂያ በመነገሩ፣ ፓርቲዎች በደብዳቤ ጥሪ አልደረሰንም ሲሉ የሚያቀርቡት አቤቱታ ተቀባይነት የለውም ብለዋል - መድረክ ለቦርዱ በደብዳቤ ቅሬታውን ማቅረቡን በመጠቆም፡፡
በአመራርጥ ሂደቱ ተቃዋሚዎች የጠቀሱትን ችግር በተመለከተም፣ የምርጫ ጣቢያ በትክክል ተጠቅሶ ለሚመጣ አቤቱታ ቦርዱ አጣርቶ እርምጃ እንደሚወስድ አቶ ወንድሙ አስታውቀዋል፡፡

በዋና አብራሪ ሻምበል ሳሙኤል ግደይ ተጠልፋ ወደ ኤርትራ የገባችውን የኢትዮጵያ አየር ኃይል የሆነች ሩሲያ ሰራሽ ተዋጊ ሔሊኮፕተር ለማስመለስ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል የተጀመረ ምንም አይነት ጥረት እንደሌለ ተገለፀ፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ እውነቱ ብላታ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ምላሽ፤ “የኤርትራ መንግስት ለአካባቢያዊ ህጎችም ሆነ ለዓለም አቀፍ ህጎች ተገዢ የሆነ መንግስት ስላልሆነና ከኤርትራ መንግስት በጎ ምላሽ ይገኛል ተብሎ ስለማይታሰብ፣ ሔሊኮፕተሯን ለማስመለስ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ምንም አይነት ጥረት እየተደረገ አይደለም” ብለዋል፡፡ መንግስት ወደፊት በጉዳዩ ላይ ውሳኔ እንደሚሰጥም አክለው ተናግረዋል፡፡ቀደም ሲል የመከላከያ ሚኒስቴር በሰጠው መግለጫ፣ ረዳት አብራሪውና የሔሊኮፕተሩ ቴክኒሻን በዋና አብራሪው ሻምበል ሳሙኤል አስገዳጅነት ኤርትራ መግባታቸውን የጠቆመ ሲሆን የሔሊኮፕተሯ አብራሪ ለምን ድርጊቱን እንደፈፀመ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም፡፡አሶሼትድ ፕሬስ በጉዳዩ ዙሪያ ባቀረበው ዘገባ፤ ብዙ ጊዜ የኤርትራ ወታደሮች በአገራቸው ባለው አስቸጋሪ ሁኔታዎች የተነሳ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ ጠቁሞ “ከኢትዮጵያ ወደ ኤርትራ የሚደረግ ሽሽት ግን ያልተለመደና እንግዳ ጉዳይ ነው” ብሏል፡፡ ባለፈው አርብ ማለዳ 2፡35 ላይ ድሬደዋ ከሚገኘው የአየር ኃይል ማዘዣ ጣቢያ የዘወትር የልምምድ በረራ ለማድረግ የተነሳችው ተዋጊ ሔሊኮፕተር፤ በዋና አብራሪ ሻምበል ሳሙኤል ግደይ እየተመራች ረዳት አብራሪ መቶ አለቃ ቢልልኝ ደሳለኝንና ቴክኒሻን ፀጋ ብርሀን ግደይን ይዛ ወደ ኤርትራ መኮብለሏ የሚታወስ ነው፡፡ በተመሳሳይ በ1995 ዓ.ም ሻምበል ተሾመ ተንኮሉ በተሰኘ የአየር ኃይል ባልደረባ ኤል 39 የተሰኘ የልምምድና ቀላል የውጊያ አውሮፕላንን ለልምምድ ከመቀሌ የማዘዣ ጣቢያ ይዞ በመነሳት ወደ ኤርትራ መኮብለሉ የሚታወስ ነው፡፡ እስካሁን የኤርትራ መንግስት በጉዳዩ ላይ አንዳችም አስተያየት እንዳልሰጠ ታውቋል

Published in ዜና

     በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የፓትርያርኮች መንበር (መንበረ ፕትርክና) በኾነችው ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብና ንብረት በአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች መመዝበሩን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ጥቆማው የቀረበው፣ የገዳሟ ማኅበረ ካህናትና የልማት ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብና የንብረት አሰባሰብ በተመለከተ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲዘረጋ የገዳሟ ልማት ኮሚቴ የበላይ ጠባቂ ለኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ባቀረቡት ማመልከቻና ሪፖርት ነው፡፡የቤተ ክርስቲያኒቱ መተዳደርያ ቃለ ዐዋዲና ደንቡን መሠረት አድርጎ በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ መመሪያ የካህናቱን፣ የምእመናኑንና የእያንዳንዱን ሠራተኛ የሥራ ድርሻና ተጠያቂነት በግልጽ ማስቀመጡን የጠቀሱት ማኅበረ ካህናቱ÷ የገዳሟን ገንዘብና ንብረት የመቆጣጠርና የመከታተል መብታቸው በአስተዳደሩ ሓላፊዎች ተነፍጓቸው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና የንብረት ቁጥጥር ለማድረግ ሳይችሉ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ገዳሚቷ በየዕለቱና በየበዓላቱ ከምእመናን በስጦታና በስእለት የምታገኘው ሀብትና ንብረት ከራስዋ አልፎ ለተቸገሩ ገዳማትና አድባራት የሚተርፍ ቢኾንም ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው የአስተዳደሩ አሠራርና በሰበካ ጉባኤው የቁጥጥር ማነስ ሳቢያ የገቢ አቅሟን ለማጎልበት ከዓመታት በፊት የወጠነችው ኹለ ገብ ሕንፃ ግንባታ ከመጓተቱም በላይ ለሀገረ ስብከቱ መከፈል ለሚገባው ውዝፍ ዕዳ መዳረጓን ካህናቱ አስታውቀዋል፡፡ በገንዘብ አያያዝና በንብረት አሰባሰብ ረገድ በአስተዳደሩ እየተባባሰ የመጣው ሙስና እንዲወገድና ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የተስተጓጎለው የልማት ሥራ እንዲቀላጠፍ በኅዳር ወር አጋማሽ ፓትርያርኩን መጠየቃቸውንም አመልክተዋል፡፡ከገዳሚቷ የልማት ኮሚቴ ጋራ በመቀናጀት የቀረበውን የማኅበረ ካህናቱን ማመልከቻ መነሻ በማድረግ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በሰጡትና በረዳት ሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጻሚ በኾነው መመሪያ፤ የገዳሟን የገንዘብና ንብረት አሰባሰብ የሚከታተል አምስት ካህናት ያሉት የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ ኮሚቴ ኅዳር 18 ቀን መቋቋሙ ታውቋል፡፡ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ማግሥት አንሥቶ ኅዳር 19 እና 22 ቀናት ባካሔደው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ የተገኘውን ከብር 826‚000 በላይ ገቢ ጨምሮ ከንብረት ሽያጭና በሞዴል 30 የተሰበሰበውን በማካተት ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ አጠቃላይ ገቢ በአንድ ወር ብቻ መመዝገቡ ተገልጧል፡፡ በካህናቱ አስፈጻሚነት በአንድ ወር የተወሰነ ቆጠራ ብቻ ይህን ያኽል ገቢ መመዝገቡ፣ የገዳሟ ገቢ ‹‹የግለሰቦች መደራጃ ኾኖ መኖሩን የሚያሳይ ነው፤›› ብለዋል - ማኅበረ ካህናቱ፡፡ አያይዘውም ለሀገረ ስብከቱ መከፈል የሚገባው የኻያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ ሳይፈጸም አኹን በካዝና ያለው ብር 129‚000 ብቻ እንደኾነ በመጥቀስ ገዳሟ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ስትመዘበር እንደኖረችና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ኾነ ሀገረ ስብከቱ በየደረጃው ማግኘት የነበረባቸውን የፐርሰንት ፈሰስ ማጣታቸውን ስለሚያረጋግጥ ‹‹የአስተዳደር ሠራተኞቹን ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡   እንደ ማኅበረ ካህናቱ እምነት፣ የገዳሟ ገቢ ለአስተዳደር ሠራተኞቹ ምዝበራ የተጋለጠው የተጠናከረ ሰበካ ጉባኤ ባለመኖሩ ነው፡፡ አኹን ያለው የገዳሙ ሰበካ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው መሠረት፣ የገዳሙን የሥራ ክፍሎች አገልግሎት አፈጻጸም በወቅታዊ የክንውን መግለጫዎች የመከታተል፣ የሒሳብ አያያዙንና የንብረት እንቅስቃሴውን ጊዜውን ጠብቀውና እንዳስፈላጊነቱ በሚቀርቡ ሪፖርቶች የመቆጣጠር ሓላፊነቱን ካለመወጣቱም በላይ ‹‹ገዳሚቷ ችግር ላይ ስትወድቅ ዝም ብሎ የኖረ ተባባሪ›› በመኾኑና የሥራ ጊዜውም በማለፉ ጠንካራና ሓላፊነት በሚሰማው ሰበካ ጉባኤ እንዲተካ መመሪያ እንዲሰጥላቸው፣ ተጀምሮ የቆመው ልማት እንዲቀጥል፣ የገዳሟ ገቢና ወጪም በውጭ ኦዲተሮች እንዲጣራ ማኅበረ ካህናቱ ፓትርያርኩን ጠይቀዋል፡፡ ያለማኅበረ ካህናቱና ማኅበረ ምእመናኑ ፈቃድ ጊዜው በሀ/ስብከቱ ውሳኔ ተራዝሟል የተባለው ሰበካ ጉባኤ፣ በቆጠራ ኮሚቴው የተሰበሰበውን ከብር 440‚000 በላይ የገዳሚቷን ከፍተኛ ገንዘብ ያለተቆጣጣሪ ወጪ ማድረጉን ካህናቱ ገልጸው፣ ሕጋዊ ሰበካ ጉባኤ ሳይቋቋም ቀጣይ ቆጠራ እንደማይካሔድ አስጠንቅቀዋል፡፡ በገዳሚቷ አስተዳደር ውስጥ ሙስናዊ ጥቅማቸው የተነካባቸው ናቸው ያሏቸው ግለሰቦች፣ የቆጠራ ኮሚቴውን ለማፍረስ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንና ግንቦት ሰባት ናችኹ፤ ምርጫውን ለማወክ ትንቀሳቀሳላችኁ፤ ወደ ሌላ ደብር እናዘዋውራችኋለን›› በሚል ከሚያደርሱባቸው ዛቻና ማስፈራራት እንዲቆጠቡ አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡የማኅበረ ካህናቱንና የልማት ኮሚቴውን ጥያቄ ተከትሎ ፓትርያርኩ በሰጡት መመሪያ÷ ሰበካ ጉባኤው የሥራ ክንውን ሪፖርት ካቀረበ በኋላ የአዲስ ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሔድ፣ የገዳሚቷ ገቢና ወጪ ሒሳብ በአስቸኳይ በውጭ ኦዲተር ተከናውኖ እንዲቀርብ፣ የቆጠራ ኮሚቴው የአስተዳደሩን ዕውቅና አግኝቶ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በ48 ሚልዮን ብር ወጪ በኹለት ምዕራፎች የተጀመረውና የተጓተተው የባለስድስት ፎቅ የአገልግሎትና ኹለገብ ሕንፃ ግንባታ የብቃት ማረጋገጫ ባለው አካል ክትትል እንዲፋጠን ማዘዛቸው ታውቋል፡፡

Published in ዜና

      ኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል በደቡብ አፍሪካ ደርባን ከተማ በተካሄደውና ከ45 ሀገሮች የተውጣጡ ከ13ሺህ በላይ ሆቴሎች በተሳተፉበት አለማቀፍ የአገልግሎትና አጠቃላይ የሆቴል መስተንግዶ ጥራት አሸናፊ መሆኑ ተገለፀ፡፡ኢንተርኮንትኔንታል አዲስ ሆቴል አለማቀፉን ሽልማት ያገኘባቸው መስፈርቶች የሆቴል መስተንግዶና የአገልግሎት አቅርቦት መሆኑን የጠቆሙት የሆቴሉ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ዜናዊ መስፍን፤ ሆቴሎችን ገምግመው ለሽልማት እጩ የሚያደርጉ ባለሙያዎች የግምገማ ስራውን በይፋና በድብቅ ጉብኝት ማከናወናቸውን ጠቁመዋል፡፡ ሆቴሉ ለሽልማት እንዲበቃ የሠራተኞቹና የማናጅመንቱ ተናቦ መስራት በተለይም የሠራተኞቹ መልካም የመስተንግዶ ጠባይ መሆኑን ጠቅሰው ሠራተኞቻቸውን በእጅጉ አመስግነዋል፡፡ “ሠራተኞቻችን ሁሉንም እንግዳ በፈገግታ ተቀብለው በእኩል የማስተናገድ ክህሎት ያላቸው” ናቸው ያሉት ዋና ስራ አስኪያጁ፤ “ደንበኞቻችን የዚህ ምስክር ሆነው ለሽልማት በቅተናል” ብለዋል፡፡ ሆቴሉ አለማቀፍ ሽልማት ማግኘቱና ይህ የሽልማት ስነስርዓት በተለያዩ አለማቀፍ የሚዲያ አውታሮች መነገሩ ለሆቴሉ የበለጠ አለማቀፋዊ እውቅና እንደሚያስገኝለት ጠቁመው፤ ለሀገሪቱም በሆቴል መስተንግዶ ዘርፍ መልካም ገፅታ ይፈጥራል ብለዋል፡፡ አክለውም ሆቴሉን በአለማቀፍ ደረጃ ይበልጥ ለማስተዋወቅ ሽልማቱ የፕሮሞሽን አካል ሆኖ እንደሚያገለግል ስራ አስኪያጁ ገልፀዋል፡፡ ኢንተርኮንቲኔንታል አዲስ ሆቴል ከግብፅ፣ ከሞሮኮ፣ ከሲሼልስ እና ከናሚቢያ ሆቴሎች ጋር ተወዳድሮ ከአፍሪካ ምርጥ አስር ሆቴሎች ውስጥ መካተቱ ታላቅ ስኬት ነውም ተብሏል፡፡ ተሽከርካሪ ሬስቶራንትና አለማቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የስብሰባ አዳራሽ ያለው የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ በቅርቡ ሲጠናቀቅ የሆቴሉን አገልግሎት ይበልጥ እንደሚያሣድገው በጋዜጣዊ መግለጫው ተጠቁሟል፡፡

Published in ዜና

ማረሚያ ቤት ምላሽ እንዲሰጥ ፍ/ቤት አዝዟል

   “የግንቦት 7 አባል በመሆን በሽብር ድርጊቶች ተሳትፈዋል” በሚል ክስ የተመሰረተባቸው የአንድነት፣ የሰማያዊ እና የአረና ፓርቲ አመራሮች፤ ሌሊት በማረሚያ ቤት በተደረገ ድንገተኛ ፍተሻ ገንዘብን ጨምሮ የተለያዩ ንብረቶች እንደተወሰደባቸው ባለፈው ረቡዕ ለፍ/ቤት አመልክተዋል፡፡ በእነ ዘላለም ወርቅ አገኘው መዝገብ የተከሰሱት የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሀብታሙ አያሌው፣ የፓርቲው የድርጅት ጉዳይ ም/ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሸዋስ አሰፋ እና የአረና ፓርቲ አመራር አባል አቶ አብርሃ ደስታና ሌሎች ተከሳሾች በጠበቃቸው በኩል ለፍ/ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ፤ ታህሳስ 12 ለ 13 አጥቢያ ከሌሊቱ 8 ሰዓት እስከ ቀኑ 5 ሰዓት በማረሚያ ቤት ድንገተኛ ፍተሻ ተደርጎ፤ የማስታወሻ ደብተራቸው፣ ገንዘብና ሌሎች ሰነዶች እንደተወሰደባቸው ለፍ/ቤቱ አስረድተዋል፡፡
 ፈታሾቹ የማረሚያ ቤቱ ኃላፊዎች ሳይሆኑ በፊት ይመረምሯቸው የነበሩ ፖሊሶችና የደህንነት አባላት እንደሆኑም ጠቁመዋል፡፡ በተለይ የማስታወሻ ደብተራቸው እንደተወሰደባቸው አፅንኦት ሰጥተው የተናገሩት ጠበቃው ተማም አባቡልጋ፤ ተከሳሾቹ ለቀጣይ ክርክር ያዘጋጇቸውን ነጥቦች ያሰፈሩባቸው በመሆኑ በቀረበባቸው ክስ ላይ ለመከራከር እንደሚቸገሩና የስነ ልቦና ጫና እንደሚያሳድርባቸው ለፍ/ቤቱ አስረድተዋል፡፡ “ምርመራ የሚፈቀደው ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽት 2 ሰዓት ሆኖ ሳለ በሌሊት መደረጉ ህግ የጣሰ ተግባር ነው፤ ድርጊቱን የፈፀሙ ሰዎች ስልጣናቸውን ያለአግባብ በመጠቀማቸው ህጋዊ እርምጃ ይወሰድልን” በማለት ለፍ/ቤቱ ያመለከቱት ጠበቃው፤ “ደንበኞቼ የማረሚያ ቤት ቆይታቸው አደጋ ላይ የወደቀ በመሆኑ የደህንነት ስጋት አለብኝ፤ በዋስትና ይለቀቁ አሊያም ከወህኒ ቤቱ በተለየ ቦታ እንዲቀመጡ ይደረግ” ሲሉ አጠይቀዋል፡፡
አቃቤ ህግ፤ ለተከሳሾቹ አቤቱታ በሰጠው ምላሽ፤ ጠበቃ ተማም አባቡልጋ የብዙ ታራሚዎችን ደህንነት በማስጠበቅ ኃላፊነቱን እየተወጣ ያለን ማረሚያ ቤት የታራሚዎችን ደህንነት የመጠበቅ ብቃት የለውም ማለታቸው አግባብነት እንደሌለው ጠቁሞ፣ ይህን መነሻ አድርጎ ዋስትና መጠየቁም ተቀባይነት የለውም ሲል ተቃውሟል፡፡ ፖሊስ የብርበራ ትዕዛዝ ይዞ በማረሚያ ቤት ፍተሻ ማካሄድ እንደሚችልም አቃቤ ህግ አስረድቷል፡፡ ፍ/ቤቱ የቀረበውን አቤቱታ መርምሮ ብይን ለመስጠት በአቤቱታው ላይ የማረሚያ ቤቱ ምላሽ እንደሚያስፈልግ ጠቅሶ፣ በቀጣይ ቀጠሮ የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር ጉዳዩ ተፈፅሟል አልተፈፀመም በሚለው ላይ ምላሽ እንዲሰጥ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡
ፍ/ቤቱ በተጨማሪም ለጠበቃ ተማም አባቡልጋ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡ “ተቋምን ብቃት የለውም ብሎ መግለፅ አግባብ አይደለም፣ በማስረጃ አረጋግጡ ቢባሉ ሊከብድት ይችላል” ያለው ፍ/ቤቱ፤ ጠበቃው ከዚህ አይነት አገላለፅ እንዲታረሙ ተግሳፅ ሰጥቷል፡፡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ከሰጠ በኋላ አቶ ሃብታሙ አያሌው “የምናገረው አለኝ” በማለት “በማረሚያ ቤቱ ደህንነት እየተሰማኝ አይደለም፤ ፍ/ቤቱ ደህንነቴን ያስከብር” ሲሉ አቤቱታቸውን በቃል ያቀረቡ ሲሆን ፍ/ቤቱም “ድርጊቱ ስለመፈጸሙ በማስረጃ ማረጋገጥ ያስፈልጋል፤ ጉዳዩ በቀጣይ ቀጠሮ ብይን ይሰጥበታል” ሲል መልሷል፡፡ መዝገቡንም ለታህሳስ 24 ቀጥሯል፡፡

Published in ዜና

     ሠሞኑን በባህር ዳር ከተማ በእንግሊዛዊው የ50 አመት ጐልማሳ ቱሪስት ላይ የተፈፀመው ግድያ ሆን ተብሎ የተፈፀመ አለመሆኑን መንግስት ገለፀ፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል ጉዳዩን አስመልክቶ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ቱሪስቱን በመግደል ተጠርጥሮ የተያዘው ግለሰብ ፍቃድ ያለው መሣሪያ ይዞ እንደነበርና ከአንዱ ትከሻው ወደ አንዱ በሚያቀያይርበት ወቅት በድንገት ጥይት ባርቆበት አደጋው መከሰቱን ለፖሊስ ተናግሯል ብለዋል፡፡ በተጠርጣሪነት በቁጥጥር ስር የዋለው ግለሰብ ላይ የሚደረገው ተጨማሪ ምርመራ መቀጠሉንም ሚኒስትር ዴኤታው ገልፀዋል፡፡ ድርጊቱ የተፈፀመው ባለፈው ረቡዕ ከረፋዱ 4 ሰዓት ከ30 ላይ ባህርዳር ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አካባቢ መሆኑን ፖሊስ ገልፆ፤ ተጠርጣሪውን ወዲያው በቁጥጥር ስር አውሎ የሟች አስከሬን ባህርዳር ሆስፒታል እንዲቆይ ከተደረገ በኋላ ሃሙስ እለት ወደ አዲስ አበባ እንዲላክ ተደርጓል ተብሏል፡፡ የሟች አስከሬን አዲስ አበባ በደረሰበት ወቅትም የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አሚን አብዱልቃድርና በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሣደር ግሬግ ዶሪ አቀባበል ያደረጉ ሲሆን አስከሬኑ ምርመራ ከተደረገለት በኋላ ወደ ትውልድ ሀገሩ እንደሚሸኝም ለማወቅ ተችሏል፡፡ አዲስ አበባ በተደረገው አቀባበል ላይ፤ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አሚን አብዱልቃድር፤ ግድያው በልዩ አላማ ወይም በሽብር የተፈፀመ አለመሆኑን በመጥቀስ የእንግሊዛዊውን መገደል ተከትሎ የሀገሪቱ የጐብኚዎች ፍሰት አይቀንስም፤ ገጽታንም አያበላሽም ብለዋል፡፡

Published in ዜና
Page 2 of 13