“አሜሪካ ፆታዊ ጥቃቶችን አጥብቃ ትቃወማለች”
አገራቸው በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ፆታዊ ጥቃቶችን አጥብቃ እንደምትቃወምና የሴቶችን አቅም በመገንባትና በማሳደግ ረገድ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በህብረት እንደምትሰራ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ኤም ሃስላክ ገለፁ፡፡ ከህዳር 16 ጀምሮ እስከ ታህሳስ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ በዘለቀው የነጭ ሪባን ቀን፤ በኤምባሲው በተዘጋጁ የተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ ከተሳተፉት የአሜሪካ አምባሳደር ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ የአፍታ ቆይታ አድርጋለች፡፡

አምባሳደር በመሆን ተሹመው ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣትዎ በፊት ስለ ኢትዮጵያ ያውቁ ነበር?
በ1980ዎቹ በኢትዮጵያ በተከሰተው ረሃብና የድህነት ችግር ላይ ከአሜሪካ መንግስት ጋር እሰራ ነበር፡፡ በ2010 አለም አቀፍ የድህነት መዋጋትና የምግብ ዋስትና (አሁን Future Initative እየተባለ የሚጠራውን) ድርጅት ወክዬ ወደ ኢትዮጵያ መጥቻለሁ፡፡
አሁን ሲመጡ ምን ለውጥ አዩ?
ብዙ ለውጦች አሉ፡፡ አገሪቱ እያደገች በመሄድ ላይ መሆኗንም ለማየት ችያለሁ፡፡
ፆታዊ ጥቃትን አስመልክቶ ሰሞኑን በተዘጋጁ የተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ከተደራራቢ የሥራ ኃላፊነትዎ አንፃር ይህን እንዴት ተወጡት?
በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን አገሬ አጥብቃ ትቃወማለች፡፡ ለዚህም ነው በፀረ ፆታዊ ጥቃትና ሴቶችን በማብቃት ሥራ ላይ ትኩረት ሰጥተን የምንሰራው፡፡ ይህ የነጭ ሪባን ቀን ደግሞ ለፆታዊ ጥቃቶች ያለንን ተቃውሞ የምናሰማበት ስለሆነ ነው በኤምባሲው በተዘጋጁ ፕሮግራሞች ላይ ሁሉ ተሳታፊ የሆንኩት፡፡ በግሌ ደግሞ ከመሃከለኛው ህዝብ ጋር መሆን ደስታን ይሰጠኛል፡፡ ለሰዎች ድጋፍና ተስፋን ከሚሰጡ ድርጅቶች ጋር አብሮ መስራት እወዳለሁ፡፡ እንዲህ አይነት ቦታዎች ላይ መገኘትም የሚሰጠኝ ደስታ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡
በቅርቡ በቡድን በተደረገባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት ህይወቷ ያለፈው ታዳጊ ወጣት ሃና ላላንጐ ጉዳይ በአገሪቱ አነጋጋሪ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቷል፡፡ ጉዳዩ በማህበረሰቡ ዘንድ ቁጣን የቀሰቀሰ ቢሆንም አንዳንድ ወገኖች መንግሥት ስለ ጉዳዩ ብዙም ያለው ነገር የለም በማለት ይተቻሉ፡፡ በእናንተ አገር እንዲህ አይነት ጉዳይ ሲያጋጥም የመንግስት ሚና ምንድነው?
የሃና ጉዳይ በኢትዮጵያ ብቻ የተከሰተ ወይንም የሚከሰት ብቻ አይደለም፡፡ በመላው ዓለም የሚከሰትና የተከሰተም ጉዳይ ነው፡፡ ይህንን ለማስቀረት ዋንኛው መፍትሄ ህብረተሰቡን ማስተማር ነው፡፡ ሁሉም ዜጋ ለጉዳዩ ያገባኛል ማለት መቻል አለበት፡፡ ሃላፊነት መውሰድ ይኖርበታል፡፡ ባል ሚስቱን ሲደበድብ ወይም ጐረምሳው ወጣቷን ሲመታ አይቶ በዝምታ ማለፍ አግባብ አይደለም፡፡ ሁሉም ሰው እንዲህ አይነት ፆታዊ ጥቃቶች ሲፈፀሙ ሲያይ ለማስቆም ጥረት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ይህ ከሁሉም ዜጋ የሚጠበቅ ሃላፊነት ነው፡፡ ሴቶች በራሳቸው ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ለማስቆም የሚያስችል አቅም እንዲኖራቸው ለማድረግም ጥረት እናደርጋለን፡፡ በፆታዊ ጥቃቶች ላይ መንግስታችሁ ጥብቅ አቋም እንዳለው አውቃለሁ፡፡ የአስራ ስድስት ቀናቱን የነጭ ሪባን ቀን በማስተባበር እየሰራ የነበረው የሴቶች ጉዳይ ሚኒስቴር ነው፡፡ እናም መንግሥታችሁ በዚህ ጉዳይ ላይ ቁርጠኛ ነው፡፡
የሁለት ሴት ልጆች እናት ነዎት፡፡ አንደኛዋ ልጅዎ በጋዜጠኝነት ሙያ ውስጥ ተሰማርታለች፡፡ የት ነው የምትሰራው? ለጋዜጠኝነት ሙያ ያለዎት ስሜትስ ምን ይመስላል?
ሁለት ሴት ልጆች አሉኝ፡፡ አንዷ ከጥቂት ቀናት በፊት ወደ ኢትዮጵያ መጥታ ለሁለት ሳምንታት ቆይታ ሄዳለች፡፡ ለጋዜጠኝነት ፍቅር አላት፡፡ ከኒውዮርክ ዩኒቨርስቲ ስኩል ኦፍ ጆርናሊዝም ዲግሪዋን ወስዳለች፡፡ በአሁኑ ወቅት ለቢቢሲ ትራቭል እንዲሁም፣ ለኒውዮርክ ታይምስና ለሌሎች መፅሄቶች ትሰራለች፡፡ ለሙያው ጥሩ ስሜት አለኝ፡፡   

Published in ዋናው ጤና

የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ፈፃሚዎች በተለያዩ አዕምሮአዊ የጤና ችግሮች የተጠቁ ናቸው (የስነ ልቦና ባለሙያ)
ህጉ በአስገድዶ ደፋሪዎች ላይ ያስቀመጠው ቅጣት ለወንጀሉ ተመጣጣኝ አይደለም (የህግ ባለሙያ)

አየር ጤና አካባቢ ከሚገኘው ት/ቤቷ ወጥታ ወደ ቤቷ ለመሄድ በተሳፈረችበት ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ በነበሩ አምስት ወንዶች ታፍና ተወስዳ በደረሰባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት ህይወቷ ያለፈው የአስራ አምስት ዓመቷ ታዳጊ ሃና ላላንጎ ጉዳይ ከተማችንን ሲንጣት ሰንብቷል፡፡ ታዳጊዋ ታፍና ከተወሰደችበት መስከረም 21 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት የቡድን አስገድዶ መድፈር ጥቃታ ተፈፅሞባት፣ ጦር ኃይሎች ሙሉ ወንጌል ቤተክርስቲያን አካባቢ ተጥላ መገኘቷ መገቡ ይታወሳል፡፡
የህክምና እርዳታ አግኝታ ህይወቷ እንዲተርፍ የተደረገው ሙከራም የተፈፀመባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት እጅግ ከባድ በመሆኑና በስለት በመወጋቷ ሳቢያ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ይሄ ክፉ ዜና ከተሰማበት ጊዜ አንስቶ ድርጊቱም በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ቁጣን ቀስቅሷል፡፡ በታዳጊዋ ላይ ይህንን አሰቃቂ ወንጀል ፈፅመዋል ተብለው የተጠረጠሩ አምስት ወጣቶችም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው፣ ጉዳያቸው በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍ/ቤት ቂርቆስ ምድብ ችሎታ በዝግ እየታየ ይገኛል፡፡
የሟቿን ታዳጊ ጉዳይ መነሻ በማድረግ ለአስገድዶ መድፈር ወንጀል የሚያነሳሱ አፈንጋጭ የወሲብ ባህሪያትን ምንነትና የሚያስከትሏቸውን የጤና ቀውሶች እንዲሁም ለወንጀሉ የተቀመጠውን ቅጣት አስመልክቶ ከባለሙያዎች ያገኘነውን ማብራሪያና መረጃ የአዲስ አድማስ
ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ እንደሚከተለው አጠናቅራዋለች፡፡


አስገድዶ መድፈር ከስነ ልቦና
ቀውስ አንፃር
መደበኛ ከሆኑትና ከተለመዱት ወሲባዊ ድርጊቶች በተለየ መንገድ ወሲብን የመከወን ፍላጎት ያላቸው ሰዎች፣ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርይ የተጋለጡ ናቸው ተብሎ ይታመናል፡፡ ከእነዚህም መካከል አስገድዶ መድፈር፣ የቡድን ተራክቦ፣ ግብረ ሰዶማዊነት፣ ሌሎች ወሲብን ሲፈፅሙ በማየት መርካት፣ ግለ ወሲብና በሰዎች  ስቃይ እርካታን ማግኘት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የአስገድዶ መድፈርና በቡድን የሚደረጉ ተራክቦዎች በአብዛኛው የሚፈፀሙት በአልኮልና በተለያዩ የአደንዛዥ እፆች ራስን ስቶ አዕምሮ በአግባቡ እንዳያስብ በማድረግ ነው ይላሉ - ባለሙያዎች፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አመላካች የሆኑ ድርጊቶች በአገራችን እየተለመዱ መምጣታቸውን የጠቆሙት የሥነ ልቦና ባለሙያው ዶክተር አንተነህ ተስፋው፤ በተለይ ዕድሜያቸው ከ16-25 ዓመት በሚሆናቸው ወጣቶች ላይ ድርጊቱ በስፋት እየታየ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ገልጸዋል፡
ከቴክኖሎጂው እድገትና ወሲባዊ ፊልሞች እንደ አሸን ከመፍላታቸው ጋር ተያይዞ አስገድዶ መድፈር፣ የቡድን ወሲብና ግብረሰዶማዊነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፉ መምጣታቸውንም ዶክተሩ ተናግረዋል፡፡
ከአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አንዱ የሆነው አስገድዶ መድፈር የአዕምሮአዊ ጤና ቀውስ ውጤት ነው፡፡ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አጋላጭ ከሆኑ ጉዳዮች መካከል ዋንኞቹ፡-
ከአስተዳደግ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ ስነልቦናዊ ችግሮች
አዕምሮ ላይ የሚደርሱ ጉዳቶች
የሆርሞኖችና ኬሚካሎች መዛባት
የኒውሮኖች ጉዳት ናቸው፡፡
ከአስተዳደግ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የስነ ልቦና ችግሮች
ችግሩ በአብዛኛው ከአስተዳደጋችን ጋር ተያይዞ የሚከሰት ነው፡፡ ለራስ የሚሰጥ አነስተኛ ግምትና በልጅነት ዕድሜ ለወሲባዊ ጥቃት ተጋላጭ መሆን ለአፈንጋጭ የወሲብ ባህርይ ሊዳርግ ይችላል፡፡
አዕምሮ ላይ የሚደርሱ ጉዳቶች
በአዕምሮአችን ላይ በበሽታም ሆነ በተለያዩ ምክንያቶች አካላዊ ጉዳቶች ሊደርሱ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ጉዳቶች ደግሞ የአዕምሮአችንን የወሲብ ክፍል ሊጎዱትና በዚያም ሳቢያ በወሲባዊ ባህርያችን ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ለአፈንጋጭ የወሲብ ባህርይ ሊያጋልጡን ይችላሉ፡፡
የሆርሞኖችና የአዕምሮ ኬሚካሎች መጠን መዛባት
አንድሮጅንና ኤስትሮጅን የተባሉት በሰውነታችን ውስጥ የሚገኙት ሆርሞኖች ወሲባዊ ፍላጐትና ስሜታችንን ለመቆጣጠር የማረዱን ናቸው፡፡ የእነዚህ ሆርሞኖች መዛባት በወሲባዊ ባህርያችን ላይ የሚያስከትሉት ተፅእኖ ቀላል አይደለም፡፡
 የኒውሮኖች ጉዳት
የአዕምሮ ሴሎች እርስ በርስ እንዲተሳሰሩና መልእክት እንዲለዋወጡ የሚያደርጉ የአዕምሮአችን መረቦች በተለያየ ምክንያት ጉዳት በሚደርስባቸው ጊዜ አፈንጋጭ ለሆነ ወሲባዊ ባህርይ ሊያጋልጡን ይችላሉ፡፡
በአጠቃላይ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርይ ልንጋለጥ የምንችለው በተለያዩ ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች ሲሆን ችግሩ በወቅቱ ታውቆ የባለሙያ እገዛ ካላገኘ በጊዜ ብዛት አፈንጋጭ የወሲብ ባህርይው ሙሉ በሙሉ የግለሰቡን አዕምሮ በመግዛት በራስ መተማመን የሌለውና ወሲባዊ እሳቤውን ለመቆጣጠር የማይችል ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ የችግሩ ተጠቂ የሆነ ሰው ለራሱ ያለው ግምት እጅግ አነስተኛ ስለሚሆን ራሱን ከማህበረሰቡ ያገላል፡፡ ራሱን ለማጥፋትም ይፈልጋል፡፡ ይህ ከመሆኑ በፊት የችግሩ ተጠቂዎች የስነልቡና ባለሙያዎች ጋር ወይንም የስነ አዕምሮ ሐኪሞች ዘንድ በመሄድ ለችግራቸው መፍትሄ መሻት ይኖርባቸዋል፡፡
የአስገድዶ መድፈር ድርጊት የተፈፀመባት (የተፈፀመበት) ሰው ብቻ ሳይሆን የፈፀመው ግለሰብም ጭምር የህክምና እርዳታ ሊያገኝ የሚችልበት መንገድ መመቻቸት ይኖርበታል ያሉት የስነልቡና ባለሙያው ዶክተር አንተነህ፤ ይህ አሰራር በሌሎች አገራት የተለመደ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
አስገድዶ መድፈርና ህጋዊ ተጠያቂነቱ
በ15 ዓመቷ ታዳጊ ወጣት ላይ የተፈፀመው የቡድን አስገድዶ መድፈር ወንጀል ያስቆጣቸው የከተማዋ ነዋሪዎች የድርጊቱ ፈፃሚዎች በአፋጣኝ ተይዘው ለድርጊታቸው ተመጣጣኝ የሆነና ሌሎችን ሊያስተምር የሚችል (መቀጣጫ የሚሆን) ፍርድ እንዲሰጣቸው ሲጠይቁ ሰንብተዋል፡፡ የወንጀሉ ፈፃሚዎች በሞት እንዲቀጡ አሊያም የእድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲወሰንባቸው የጠየቁም በርካቶች ናቸው፡፡ ለመሆኑ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ ለዚህ መሰሉ ድርጊት የሚሰጠው የቅጣት ውሳኔ እምን ድረስ ነው? የህግ ባለሙያው አቶ ዳዊት ታዬ ለዚህ ማብራሪያ አላቸው፡፡
የኢትዮጵያ ወንጀለኛ መቅጫ ህግ፤ የአስገድዶ መድፈርን ወንጀል እስከ አስር አመት ሊደርስ በሚችል ቅጣት የሚያስቀጣ ወንጀል አድርጐ አስቀምጦታል፡፡
ድርጊቱ የተፈፀመው አስራ አምስት ዓመት ባልሞላት ሴት ልጅ ላይና በብዙ ሰዎች ተባባሪነት ከሆነ ቅጣቱ እስከ አስራ አምስት አመት ሊደርስ እንደሚችል ይገልፃል፡፡ ድርጊቱ ሞትን የሚያስከትል ሲሆን ደግሞ ቅጣቱ ከፍ ሊል ይችላል፡፡ ሆኖም በአስገድዶ መድፈር ላይ ተፈፃሚ የሚሆኑ የቅጣት ህጐች ደፋሪዎች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ለማድረግ የሚያስችል አቅም ያላቸው ናቸው ብሎ ለመናገር እንደማያስችሉ አቶ ዳዊት ይናገራሉ፡፡
“ህጉ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል የፈፀመ ሰው ወንጀሉን የፈፀመባትን ሴት ያገባ እንደሆነ ክሱ ቀሪ ሊሆን እንደሚችል ያስቀምጣል፤ ይህም የድርጊቱ ፈፃሚዎች ጋብቻ በመፈፀም ከተጠያቂነት ነፃ ሊሆኑ እንደሚችሉ ስለሚያስቡ ድርጊቱን ከመፈፀም ወደ ኋላ አይሉም፤ ምክንያቱም ወንጀሉን በጋብቻው ካስቀሩ በኋላ ጋብቻውን ደግሞ በቀላሉ ሊተውት ይችላሉና” ሲሉ አስረድተዋል አቶ ዳዊት፡፡
ተጎጂውን ለአካል ጉዳት፣ ለስነ ልቦና ቀውስና ባስ ሲልም ለህልፈት የሚዳርገውን ይህን ፆታዊ ጥቃት ለመከላከልና ከነአካቴውም ለማጥፋት የሁሉንም የጋራ ህብረትና ጥረት ይጠይቃል፡፡
 ጉዳዩ ጊዜ የሚሰጥና ለነገ በይደር የሚተው አይደለም፡፡ ግለሰቦች፣ ቤተሰብ፣ ጎረቤት፣ ማህበረሰብ፣ ፖሊስ (መንግስት)፣ መምህራንና የሥነ ልቦና ባለሙያዎች እንዲሁም የፆታ እኩልነት ተሟጋቾች ዛሬውኑ አገራዊ እንቅስቃሴ መጀመር ይኖርባቸዋል፡፡ ነገ በሃና ላይ ከተፈፀመው ጥቃት የከፋ በሌሎች ላይ ላለመፈፀሙ ምንም ማረጋገጫ እንደሌለን መዘንጋት የለብንም እሳቱን ለማጥፋት ከመረባረብ ቃጠሎ እንዳይነሳ መከላከል የተሻለ አማራጭ ነው፡፡

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 13 December 2014 10:56

የ“አደፍርስ” ዳግም መታተም

   የ“አደፍርስ”ን ዳግም መታተም በሰማሁ ጊዜ ልቤን ደስ አለው፡፡ ደራሲው ዳኛቸው ወርቁ በቀደመ ህትመቱ ስሜቱ ተጎድቶ ከገበያ ላይ የሰበሰበው “አደፍርስ” ድጋሚ መታተሙን አውቆ ቢያርፍ እንዴት ሸጋ ነበር፡፡ ደራሲው በህይወት በነበረበት ዘመን ድርሰቱን ፈልገው ለሚሄዱ ሰዎች ወይም ተማሪዎች ይሸጥ ነበር አሉ፡፡ ዝም ብሎ ግን አይሸጥም፤ ስለ መጽሃፉ ጥያቄዎችን ጠይቆ፣ የገዥውን የአእምሮ አቅም ለክቶ ነው፡፡ ምን ያድርግ በዚያ ጊዜ የነበሩ ሃያሲያን ወይም አንባቢያን መጽሃፉን አብጠልጥለውት ነበርና ነው፡፡ በርግጥ “አደፍርስ” ለየዋህ አንባቢ አይደለም ለተባ አንባቢም ፈተና ነው፡፡ እያንዳንዱ ቃል፣ ሀረግ፣ አረፍተ ነገር፣ ሥርዓተ ነጥብ… ሁሉ በምክንያት የገባ ነው፡፡ የደራሲውን ስራዎች ፈልጌ ለማንበብ ሞክሬያለሁ፤ ራሱ “የጽሑፍ ጥበብ መመሪያ” የሚለው ማጣቀሻ የጽሁፍ ማስተማሪያው መምሪያ ሳይሆን መመራመሪያ ነው፡፡ “እንቧ በሉ ሰዎች” (ዩኒቨርስቲ እያለ የጻፈው ግጥም) በአብዛኛው የተቃውሞ ይዘት ያላቸው ግጥሞቹ፣ “The Thirteenth Months Sun” (1973 G.C) የሚለው እንግሊዝኛ ልቦለዱ እንደ “አደፍርስ” ሁሉ ጠንካራ ናቸው፡፡ ተውኔቶችም፣ አጫጭር ልቦለዶችም አሉት፡፡ ሰውየው ከጻፈ ለሰስ ማድረግ አያውቅም!!
“አደፍርስ” በትውፊታዊ አቀራረብ የዳበረ፣ ረቂቅ ሀሳብን በሚወክሉ ገጸ ባህሪያትና የታሪክ ደጀኖች የበለጸገ ሲሆን በታሪኩ ውስጥ የቀረቡት የእንግዳ አቀባበል፣ የሰላምታና ጭውውት፣ የቤተሰብ ወግና ስርዓት፣ እሰጥ አገባ፣ ባዕድ አምልኮውና ክርስትናው፣ ስንብቱና ውይይቱ ስራውን ፍጹም ኢትዮጵያዊ ባህርይ ያጎናጽፉታል፡፡
እስኪ አንዲት ነጠላ ሀሳብ እንምዘዝና እመልከት፡-
“… ሙቶች ሙታናቸውን ይቅበሩ፡- ጌታ ያለው የፈቀደው ሲፈጸም እኮ ነው፡፡ ለራሱ ያለውን ማን ይወስድበታል?”
ከላይ የቀረበው ደራሲ ዳኛቸው ወርቁ በ1962 ዓ.ም “አደፍርስ” በሚል ርዕስ ካሳተመው ልቦለድ ታሪክ ውስጥ የተቀነጨበ ነው፡፡ ይህ የመጨረሻው ምዕራፍ ከላይ በተጠቀሰው አባ ዮሐንስ ንግግር ከመጠናቀቁ በፊት ጺወኔ ለአለም ያላት አመለካከት ግራ መጋባት ይታይበታል፡፡
በዙሪያዋ ያሉት ሁሉ “ለእሷ ብለው” የተለያየ ምክር ለግሰዋታል፡፡
ምናልባት የግራ መጋባቷ መንስኤም ይህ ሊሆን ይችላል ብዬ እገምታለሁ፡፡ ከነዚህ ሰዎች መካከል አንዱ ደግሞ አባ ዮሐንስ ናቸው፡፡
አለምን ተያት፣ አለሙ በጌጥ ቢጥበረበር፣ አለሙ አለምን ሁሉ ሊያተርፍ ቢሻ አንች አትመልከችው፤ መንኝ እያሉ የአለምን ከንቱነት ይሰብኩላታል፡፡
እዚህ ላይ መረዳት ያለብን በልቦለዱ ውስጥ የቀረቡት ታሪኮችና ድርጊያዎች የቀረቡበትን ውክልና ነው፡፡ “ትእምርት” (symbol) በአደፍርስ ውስጥ ዋና የታሪክ ማስኬጃም፣ ማምለጫም፣ የታሪኩ ማጉያና የስራው ውበታዊ ፋይዳ ሆኖ ይታያል፡፡ ዋርካው ከነቅርንጫፉ፣ የዋርካው ስር ለምለም ሳር፣ ታይታ የምትጠፋው ምንጭ፣ አደፍርስ ወደ ውሃው የወረወራት ጠጠርና የጺወኔ በወታደሩ መጠለፍ … ሁሉ ትዕምርታዊ ዳራቸው ታሪኩን ለመረዳት የሚረዱ ናቸው፡፡
ለምሳሌ በልቦለዱ ውስጥ አንድ ዋርካ ቅርንጫፉ ሰፍቶ የተንዘራፈጠ መሆኑ ተገልጿል፡፡ ታቹ ለምለም ሳር ነው፤ ከዋርካው ስር አንዳንዴ የምትፈልቅ ምንጭም አለች፡፡ ዋርካው ንጉሱ፣ ቅርንጫፎቹ ከእርሳቸው በታች ያሉት ባለሟሎች፣ ለምለሙ ሳር ለዘመናት የማይቆረቁረው፣ የማይጎረብጠው፣ የመጣው ሁሉ የሚቀመጥበት የኢትዮጵያ ህዝብ፣ አልፎ አልፎ የሚመነጨው ምንጭ ደግሞ በየጊዜው የተነሱት አመጾች ናቸው፡፡ ይህ ከሆነ በኋላ “አደፍርስ” የተባለው ባለ ታሪክ ማህበረሰቡን ሳይሆንና ሳያክል እንዲሁም ውስጣቸው ሳይገባ ልለውጣችሁ አላቸው፡፡ ሳይለውጣቸው ቀረ! ይህ በጠጠር የተመለከተው ትዕምርት (ምሳሌ) እንዲህ ነው፡፡ አደፍርስ ከአንዲት ኩሬ ዳር ሆኖ ወደ ኩሬው ጠጠር ወረወረ፡፡ መጀመሪያ ክብ ከዚያ ትልቅ ክብ፣ ከዚያ ትልልቅ፣ ትልልልቅ… ክብ እየሆነ ሄደ፡፡ እንደ ሃሳቡ ማህበረሰቡን መጀመሪያ ትንሽ መለወጥ፣ ከዚያ ከፍ ከፍ… በማድረግ መለወጥ ነበረ፡፡ ግና ምን ያደርጋል ዳር ሆኖ ጠጠሩን ወረወረና (ወደ ህዝቡ ሳይገባ) የጠበቀው ለውጥ ሳይመጣ ቀረ፡፡ መጨረሻም ያንን የረጋ ውሃ (ውሃው ህዝቡ ነው) ሳይቸግረው በጥብጦ ኢትዮጵያን አሳልፎ ሰጣት፡፡ ጺወኔ (ጥንታዊት ኢትዮጵያ) በወታደሩ መጠለፏን ልብ ይሏል፡፡ ለዚህ ነው ደራሲ ዛሬን ሳይሆን ነገን፣ ከነገ ወዲያን የሚመለከትበት መነጽር አለው የሚያስብለው፡፡ ደራሲ ትንቢተኛ ነው ብንልም ያስኬዳል፡፡ ዳኛቸው ከተነበየው አንድም እንኳ ያልሆነ የለም፡፡
ወደ ተነሳንበት እንመለስና፣ የጺወኔ ውክልና በዘመኑ ለነበረው ስርዓት ነው፡፡ ይህች ደግሞ የፊውዳል ስርአት እየገነነባት የመጣችው ጥንታዊት ኢትዮጵያ ናት፡፡ በንጽህናዋ፣ በአለችበት አቅም፣ ዕውቀት፣ ባህልና ወግ አደፍርስ አጥብቆ የሚወዳት እና የሚፈልጋት፡፡ በሌላ መንገድ የአደፍርስን ልብ የምትከፍልበት ሮማን ናት፡፡ እሷ ደግሞ ለውጥ ለመቀበል ያቆበቆበችው፣ ህዳሴ ያማራት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ምሳሌ ናት፡፡ አደፍርስም የዚህ ዘመን አካል በመሆኑ (በትምህርትም ስለገፋ) ወደ ሮማን (ዘመናዊነት) ማጋደሉ እውነት ነው፡፡ በመጨረሻው ምዕራፍ የአደፍርስ የመጨረሻ ዕጣ በሞት መሆኑ በሁለቱ ኢትዮጵያዎች መካከል (በሮማንና በጺወኔ የተወከሉት) ያለውን ድልድይ መዘርጋት ሳይችል፣ ሀሳቡ ሳይቋጭ መቅረቱን የሚያሳይ ነው፡፡
እንግዲህ አንኳር የሆነ ሀገራዊ ጉዳይን አንስቶ ዳር ሳያደርስ በሞተው አደፍርስ ቀብር ላይ ነው ጺወኔ ከነበረው ማህበረሰብ ራሷን አሸንፋ የራሷ ሰው ሆና ተነጥላ የምትጓዘው፡፡
 መድረሻዋ በርግጥ አይታወቅም - ዘመኑን ልብ ካልን የኢትዮጵያም መድረሻ አይታወቅም ነበር፡፡ አካሄዷ ግን የመወሰን ነው፡፡ “ኢትዮጵያ ለለውጥ እርምጃ መጀመሯን ማመልከቱ ይሆን” ያሰኛል፡፡ በዚህ ጊዜ ነው አባ ዮሐንስ ከመፅሐፍ ቅዱስ የሉቃስ ወንጌል ላይ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚናገረውን ጠቅሰው የሚከተሏት፡፡
“ሌላውንም ተከተለኝ አለው፡፡ እርሱ ግን አለ፡፡ አቤቱ እዘዘኝ እሄድ ዘንድ አስቀድሜ አባቴን ለመቅበር፡፡ ኢየሱስም አለው፡፡ ሙታንን ተው ሙታናቸውን ይቅበሩ፡፡ አንተስ ሂድ የእግዚአብሄርንም መንግስት አስተምር፡፡” (ሉቃስ 9፤ 59-60)
ይህ ሰው ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲከተለው ሲጠይቀው አባቴን ልቅበር በማለቱ ነው ይህ ቃል የመጣው፡፡ በርግጥ አባቱ ሞቷልን? አልሞተም፡፡ በዚያ ዘመን በነበረው ልማድና አነጋገር (አሁንም በአንዳንድ የሀገራችን ክፍሎች ይባላል) አባቴ እድሜው ደርሶ እስከሚሞት ጦሬው፣ ሲሞትም በወጉ ቀብሬው ልምጣ (ጧሪ ቀባሪ እንዲሉ) እንደ ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ግን የነበረውን ማህበረሰብ የእምነት ጉድለት በዚህም የቁምና የመንፈስ ሞታቸውን በማመስጠር፣ የቁም ሙቶች የሞቱትን ይቅበሩ፤ አንተስ ለመንፈሳዊ ዘለአለማዊነት ተመርጠሃልና እግዚአብሄርን ተከተል፤ ስለ እሱም አስተምር ሲለው እንመለከታለን፡፡
በአደፍርስ ውስጥ አባ ዮሐንስ ይህን የታላቁን መፅሐፍ ቃል ለመናገር መምረጣቸው የጺወኔን መንፈሳዊ ህያውነት ለማሳየት ይመስላል፡፡
 የዘመኑ ማህበረሰብ የአመለካከትና ልማድ ሙትነት በመፅሐፉ ውስጥ ተሰናስሎ ቀርቧል፡፡
 ይህ ጥቅስ የዳኛቸውን የትረካ ስልት ያዳበረና ያበለፀገ፣ በውስጡም ብዙ ብልሃቶችን ያካተተ እንዲሆን አድርጐታል፡፡ የታሪኩ ፍሰት ቀልብን ይዞ ከግዙፉ ታሪክ ባሻገር በቅኔያዊ (ትዕምርታዊ ፍካሬው) በልፅጐ መነሻውን ከመጨረሻ ውጤቱ ጋር ያዋደደ ነው፡፡በምዕራፍ 23 ገፅ 140 ላይ ጴጥሮስ፤ ሮማን የተሸከመችውን ውሃ የያዘ እንስራ ይሰብርባታል፡፡ ምክንያት - አደፍርስ ምንጩ ዳር ሲነካካት እንደነበር ስለሰማ በቅናት ተነሳስቶ፡፡
 በዚህ ጊዜ በውሃ እንደበሰበሰች ወደ ምንጩ ስትመለስ አደፍርስ ደነገጠ፤ ሊያቅፋትም እጆቹን ይዘረጋል፡፡ እጁ ሳይደርስ ግን የእነወርዶፋ ዱላ ይወርድበታል፡፡
ከላይ እንዳመለከትኩት ሮማን ለአዲሲቱ ኢትዮጵያ ትዕምርት ናት፡፡ አደፍርስ ሊያቅፋት ሊደርስባት የሚፈልጋት ኢትዮጵያም እሷ ናት! እስኪ ኢትዮጵያ ከፊውዳሉ ስርዓት በኋላ የተጓዘችበትን መንገድ አስተውሉ፡፡ እስኪ በዘመኑ የነበሩትን የተማሪዎች እንቅስቃሴ ዘወር ብላችሁ ተመልከቱ፡፡ አደፍርስ እኮ ወኪል እንጂ ግዘፍ ነስቶ የምናገኘው አካላዊ ሰው አይደለም፡፡ በእሱ መነፅር ግን ያች ሊያቅፏት፣ ሊደግፏት፣ ሊያዘምኗት የነበረች ኢትዮጵያ (በሮማን ተወክላ) በድንገት ደራሽ ሀይል ለልጆቿ እልቂት፣ ለእሷም ቆሞ መቅረት ምክንያት መሆኗን እናያለን፡፡ እዚህ የንቃት ደረጃ ላይ ያልደረሰው ማህበረሰብ የከፈለው ደግሞ - ዱላ፡፡
ይህ የሃሳብ ልዩነቱም ይመስለኛል የመጨረሻውን የሞት ፅዋ ያስጐነጨው፡፡
ታሪኩ በዚህ መልክ ሲፈስ ከቆየ በኋላ አንድ ግብ ላይ ይደርሳል፡፡ የራሷን ንፅህና ለአደፍርስ ደህንነት ስትል የከፈለችው ጺወኔ፤ የሀሳብ መቃተት የሚያበቃውም በውሳኔዋ የሚፀናውም ይሄኔ ነው፡፡ የጺወኔ ጉዞ የተሻለ አለም ለማግኘት የሚደረግን የሃሳብ ጥረት ያመላክታል፡፡
ባለፉት ምዕራፎች በአንድ ጐን የምድራዊውን ዓለም ከንቱነት፣ በሌላ በኩል የሰማያዊውን ዓለም የፅድቅና የቅድስና ኑሮ፣ ለዚህም የሚደረግ ትጋትን ሲሰብኳት የነበሩት አባ ዮሐንስም በመጀመሪያ አካባቢ የተፃፈውን መፅሀፍ ቅዱሳዊ ቃል እየተናገሩ ይከተሏታል፡፡ በዘመኑስ የኢትዮጵያን መጻኢ እድል መተንበይ የቻለ ነበርን? ልክ እንደ ጺወኔ ተጓዘች እንጂ መድረሻዋን እሷም እኛም አናውቅም ነበር፡፡

Published in ጥበብ

አቶ መለስ “መንግስት የመላዕክት ስብስብ አይደለም” ብለው ነበር

    አሜሪካዊው ዶ/ር ዊሊያም ዩሪ፤ በግጭት አፈታት፣ በእርቅና በገላጋይነት እንዲሁም በድርድር ጥበብ የተካነ ባለሙያ ነው፡፡ ፀሐፊና ደስኳሪም (speaker) ጭምር፡፡ ላለፉት 30 ዓመታት ግጭት በተከሰቱባቸው አብዛኞቹ የዓለማችን አገራት መፍትሄ በማፈላለግ ተግባር ላይ ተሳትፏል፡፡ (የአገራችን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ በሉት!) ኢትዮጵያን ጨምሮ በበርካታ የአፍሪካ አገራት እንዲሁም በመካከለኛው ምስራቅ ተጉዟል፡፡  በግጭት ላይ የሚያጠነጥን “The Third Side” የተሰኘ ዝነኛ መፅሃፍም አሳትሟል፡፡ (ማን ይሆን ሦስተኛው ወገን?)
ዩሪ፤ ለትላልቅ ኩባንያዎች፣ ለመንግስት ኃላፊዎች፣ ለፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ወዘተ… (በብዙ 100ሺዎች ለሚገመቱ ታዳሚዎች) በግጭት አፈታትና በድርድር ጥበብ ዙሪያ ደስኩሯል - ከህይወት ተመክሮው እየጨለፈ፡፡ (የዩሪ ዓይነት በእጅጉ ያስፈልገናል!) እኔም ይሄን የሰላም ሰው ያወቅሁት ሰሞኑን ነው፡፡ የድርድር ጥበብ (The art of negotiation) በሚል ርዕስ መረጃ ሳስስ Tedtalk በተባለ ዝነኛ ሰዎች በሚደሰኩሩበት የቲቪ ፕሮግራም ላይ አግኝቼ አዳመጥኩት - አንዴ ሳይሆን ደጋግሜ፡፡ ለምን መሰላችሁ? እንደኔ አይነት “የአበሻ ደም” ያለው ሰው የድርድር… የውይይት… የመግባባት…. የመከባበር…. የመደማመጥ…ነገር  ቶሎ ወደ ውስጡ ዘልቆ አይገባም፡፡ (አበሻ ነዋ!)
አያችሁ… እኛ አበሾች ደማችን ቶሎ ስለሚፈላ ከመቅፅበት በስሜት ቱግ እንላለን፡፡ (ለወገናችንም ለባዕድም ያው ነን!) በእልህ እንንተከተካለን፤ ከማሰብ ይልቅ በስሜት መነዳት ይቀናናል፡፡ “መቻቻል” ጥርሳችንን የነቀልንበት ነው ብንልም እውነቱ ግን ጨርሶ ከመቻቻል ጋር አለመተዋወቃችን ነው፡፡ እኔን ካላመናችሁኝ… የአገራችንን ፓርቲዎች (ፖለቲከኞች) እዩአቸው፡፡ (ሃቀኛ አበሾች እነሱ ናቸዋ!)
ድርድርና ውይይት የሰው ልጅ በምድር ላይ መኖር ከጀመረ ጊዜ አንስቶ የነበሩ ቢሆንም እንዳሁኑ ዘመን በከፍተኛ መጠን ተተግብረው (ለሰው ልጅ ጥቅም ውለው) አያውቁም ይለናል - ዶ/ር ዩሪ፡፡ (እንደ አንዳንድ የመጠቁ ቴክኖሎጂዎች እኛ ጋ አልደረሰም እንጂ!) የግጭት አፈታት ሊቁ ዶ/ር ዊሊያም ዩሪን ያለምክንያት አላመጣሁትም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የገዢው ፓርቲና የተቃዋሚዎች ውዝግብ እየተባባሰ በመምጣቱ ነው (የጦቢያ “ቀዝቃዛው ጦርነት” በሉት!)
እኔ የምላችሁ … ለምንድነው በአሁኑ ወቅት የሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄ የውዝግብ መነሻ የሆነው? አሁንማ እኛንም ታከተን እኮ፡፡ ተቃዋሚዎች የሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄ ያቀርባሉ፤ የሚመለከተው አካል ፈቃድ ይከለክላል፡፡ እርግጠኛ ነኝ ይሄ የሚመለከተው አካል የተቋቋመው ሰላማዊ ሰልፍ ለመከልከል አይደለም (ይሄማ ህገ መንግስቱን መፃረር ነው!) እንኳን እሱ ሌላውም የመንግስት ተቋም ህገመንግስቱን ለማስፈፀም እንጂ ለመጣስ አልተቋቋመም፡፡ ግን አንዳንዴ በተቃራኒው የሚንቀሳቀሱ አይጠፉም፡፡ ለዚህ እኮ ነው የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ (መሬት ይቅለላቸውና!) “መንግስት የመላእክት ስብስብ አይደለም” ያሉት፡፡ እናም አስበውም ሆነ ሳያስቡ ህገ መንግስቱን የሚጥስ ተግባር የሚፈፅሙ አይጠፉም፡፡ ይሄ’ኮ ፈፅሞ ለክርክር የሚቀርብ አይደለም፡፡ በቅርቡ አይደለም እንዴ…አንድ ትልቅ የመንግስት መ/ቤት ሃላፊዎች (ከላይ እስከ ታች) በሙስና ተዘፍቀው የተገኙት? በአዲስ አበባ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከተሞች ከንቲባዎችን ጨምሮ በርካታ ሃላፊዎች በመሬት ዝርፊያ ላይ ተሰማርተው መገኘታቸውንና ክስ ተመስርቶባቸው እንደተፈረደባቸውም እንዳትዘነጉ፡፡ (ህገመንግስቱን እያስከበሩ እኮ አይደለም!) ከምሬ ነው የምላችሁ… የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር “መንግስት የመላእክት ስብስብ አይደለም” የምትለዋን አባባል ባይተነፍሱ እኮ ሙሰኞች እንደ አሸን ሲፈሉ ኢህአዴግ ማጣፊያው ያጥረው ነበር፡፡ (ዕድሜ ለሳቸው!) ወደ ተነሳንበት ርእሰ ጉዳይ ልመልሳችሁ - የተቃውሞ ሰልፍ (ህዝባዊ ስብሰባ) ጥያቄና ክልከላ እንዲሁም ያንን ተከትሎ የሚፈጠር ውዝግብ… እሰጥ አገባ… ፍጥጫ…. የፖሊስ ከበባ… ዱላ… እስር… ክስ… የዲሞክራሲያዊነት ምልክቶች አይደሉም፡፡ …(ከዚህ በላይ Conflict አለ እንዴ?) ይሄ ሁሉ እኮ በሰላም አገር ነው፡፡ (ቢያንስ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አልታወጀማ!)
እኔ መንግስትን ብሆን ግን ምን መሰላችሁ የማደርገው? የሰላማዊ ሰልፍ ፈቃጅ ወይም ዕውቅና ሰጪ የተባለውን ክፍል አፍርሼ እንደገና አዋቅረው ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ? የፓርቲንም ሆነ የመንግስትን እንዲሁም የአገር ገፅታን እያበላሸ ነዋ!! ሃላፊነቱን ያለ ብዙ ግርግርና ወከባ በዘዴና በብልሃት የሚወጣ አካል ነው የሚያስፈልገው፡፡
 ተቃዋሚዎች የሰላማዊ ሰልፍ ጥያቄ ባነሱ ቁጥር ግጭትና ፍጭት ከተፈጠረማ ብቃት የለውም ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ፈርሶ እንደገና መደራጀት አለበት (እኔ መንግስት ብሆን ነው ያልኩት - “If I were a boy…አለች ቢዮንሴ! በነገራችን ላይ “የፖለቲካ ኪራይ ሰብሳቢዎች”ም ሳይኖሩ አይቀሩም ባይ ነኝ፡፡  
እኔ የምለው ግን… ሰላማዊ ሰልፍ የሚደረግባቸውና የማይደረግባቸው ስፍራዎች የሚባል ነገር አለ እንዴ? (ከሆስፒታሎችና ከሃይማኖት ተቋማት ውጭ ማለቴ ነው!) ባለፉት ሳምንታት የ“አዳር ተቃውሞ” ጥያቄው ያልተሳካለት በዘጠኝ ፓርቲዎች ጥምረት የተመሰረተው “የፓርቲዎች ትብብር” (ምርጫ ቦርድ “ዕውቅና አልሰጠሁትም” ብሏል!) የ24 ሰዓት ሰልፉን ለማድረግ የፈለገው በመስቀል አደባባይ ነበር፡፡ (ቢሳካ ኖሮ እኮ ለአገር ገፅ ግንባታ ይጠቅም ነበር፡፡) እንዴት ብትሉ…ለ24 ሰዓት የዘለቀ በምስራቅ አፍሪካ ረዥሙ የተቃውሞ ሰልፍ ተብሎ “ጊነስ ቡክ ኦፍ ዎርልድ ሪከርድ” ላይ ይመዘገብ ነበር!
የአዲስ አበባ አስተዳደር ከንቲባ ፅ/ቤት ግን መስቀል አደባባይን በሦስት ምክንያቶች አልፈቀደም፡፡ የውጭ ድርጅቶች ያሉበትና የመንግስት ተቋማት የሚበዙበት እንዲሁም የግንባታ ሥራ የሚከናወንበት በመሆኑ ዕውቅና አልሰጠሁም ብሏል - ፅ/ቤቱ ባለፈው ሳምንት፡፡ የትብብሩ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል በበኩላቸው፤ የመንግስት ተቋማት የሚበዙበት ለተባለው በሰጡት ምላሽ፤ “እኛም ተቃውሟችንን የምናሰማው ለመንግስት ስለሆነ ተገቢ ቦታ ነው” ሲሉ ተሳልቀዋል፡፡ (ወይም የተሳለቁ መስሎኛል!) አንዳንድ ታዛቢዎች ደግሞ እንደ ዛሬ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች የተከለከለ አደባባይ፤ በበነጋታው ገዢው ፓርቲ እንዳሻው ሲሰለፍበት ይውላል ሲሉ ይተቻሉ (እውነት ነው ሃሜት?)
ታዛቢዎቹ ግን አንድ ያልገባቸው ወይም ያልሰሙት ነገር አለ፡፡ በቅርቡ እኮ ሥልጣን የያዘ ገዢ ፓርቲና ተቃዋሚ እኩል መብትና ጥቅም (privilege) ሊኖራቸው አይችልም ተብሏል፡፡  እኔ የምለው ግን… ገዢው ፓርቲ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣት ወይም ህዝባዊ ስብሰባ ማድረግ ሲፈልግ ፈቃድ ይጠይቃል እንዴ? (ማንን?) አንዳንድ “የአዲስ አበባ ነዋሪዎች” (የኢቲቪዎቹ አይደሉም!) ጠይቅልን ስላሉ እንጂ እኔማ መልሱን አውቀዋለሁ፡፡ ሥልጣን ላይ ያለ ፓርቲና ተቃዋሚዎች እኩል መብትና ጥቅም (privilege) ሊኖራቸው እንደማይችል የተናገሩት ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ነበሩ - በፓርላማ!! (ይሄ ነገር በአዋጅ ፀድቋል እንዴ?)
እናላችሁ… ከሰላማዊ ሰልፉ ይልቅ ሰልፉ የሚደረግበት ስፍራ (መስቀል አደባባይ፣ ጃንሜዳ፣ ሽሮሜዳ፣ ስታዲየም፣ ቸርችል ጐዳና ወዘተ…) በእጅጉ ያወዛገበ ሲሆን ባለፈው ቅዳሜም የተቃዋሚዎች አመራርና አባላት ያለ ፈቃድ ሰልፍ ሊወጡ ሞክረዋል ተብለው በፖሊስ ተይዘው ታስረዋል፡፡ ፍ/ቤት በቀረቡበት ወቅትም ፖሊስ ከፍተኛ ድብደባና እንግልት ፈፅሞብናል ሲሉ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ (ዱላን ምን አመጣው?) ፍ/ቤቱም መደብደብ እንደሌለባቸወና በአግባቡ ሊያዙ እንደሚገባ ትእዛዝ ሰጥቷል ተብሏል፡፡ (ፖሊስን “ለምን ደበደብክ” ብሎ መጠየቅ ነውር ነው እንዴ?)
ምናልባት ይሄ የሰላማዊ ሰልፍ ማድረጊያ ቦታ እንዲህ ያወዛገበው ከሰሞኑ የመሬት ሊዝ ዋጋ መናር ጋር በተገናኘ ይሆን እንዴ? (መርካቶ በርበሬ ተራ አንድ ካሬ ሜ. ቦታ 305ሺ ብር አውጥቷል በጨረታ!) እናም ምን አልኩ መሰላችሁ? “ወደፊት ከእነ አካቴው የሰላማዊ ሰልፍ ማድረጊያ ቦታ ስለሚጠፋ ከአሁኑ በብድርም ቢሆን ሰፋፊ መሬት ገዝቶ ማስቀመጥ ሳይበጅ አይቀርም” (ግን በሆዴ ነው!) ከምሬ እኮ ነው… ያለዚያ ሰላማዊ ሰልፍ የሚባል ነገር ታሪክ ሆኖ ሊቀር ይችላል (“እንኳንም ዘንቦብሽ…” አሉ!)
እርግጠኛ ነኝ ኢህአዴግ ወይም መንግስት የሰላማዊ ሰልፍ ውዝግቡን ተከትሎ በተከሰተው ነገር ይደሰታሉ ብዬ አላስብም፡፡ ውዝግቡ ሳይነሳ፤ ከተነሳም ደግሞ ሳይጯጯህ ቢፈታ የሚመርጥ ይመስለኛል፡፡ እስቲ ይታያችሁ… ከአንድ አመት ወዲህ እየተሰማ ያለው እኮ አስፈሪና ተስፋ አስቆራጭ ነው፡፡ (እንኳን ለሌላው ለራሱም ለኢህአዴግ!) ብዙዎቹ የአገሪቱ መፅሄቶች ተዘግተው ጋዜጠኞችና አሳታሚዎች ተሰደዋል፡፡ (የተሰደደ ጋዜጠኛ የለም ቢባልም!) አምስት ገደማ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ከግንቦት 7 ጋር ግንኙነት አላቸው በሚል በሽብር ተጠርጥረው ታስረዋል፡፡ 10 የሚጠጉ ጋዜጠኞችና ጦማሪያን እንዲሁ በሽብር ተጠርጥረው በእስር ላይ ናቸው፡፡ አሁን ደግሞ ከዘጠኝ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተውጣጡ አመራሮችና አባላት ታስረው ተፈቱ፡፡ የፈለገ ምርጫ ቢደርስ…የፈለገ ኢህአዴግ ቢጠላቸው… ይሄ ሁሉ ሰው በእስር ላይ እንዲሆን መንግስት ይፈልጋል ብዬ ማሰብ ያዳግተኛል፡፡ (“ታዲያ ማን አስገደደው” እንዳትሉኝ?) ይሄ ሁሉ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ታስሮ ምርጫ ቢያካሂድ እኮ ለገፅታ ግንባታው ጥሩ አይሆንም! (ጠላቶች “አምባገነን ጥሎ አምባገነን ሆነ” ብለው ሊያጋንኑት ይችላሉ!)
ሁሌም የሚገርመኝ ምን መሰላችሁ? ኢህአዴግ የጐረቤት አገራትን ግጭትና ፍጭት ለመፍታት ቀድሞ እየተገኘ፣ የጓዳውን ችግር ለመፍታት አቅም ማጣቱ ነው (“የራሷ አሮባት የሰው ታማስላለች” ማለት ይሄኔ ነው!) እኔ ግን ይሄን የሚፈፅሙት “የፖለቲካ ኪራይ ሰብሳቢዎች” ናቸው ባይ ነኝ፡፡ (ኢህአዴግን ለማሳጣት የሚፈልጉ!)
ቀደም ብዬ ያስተዋወቅኋችሁ አሜሪካዊ ምሁር በግጭት ወቅት “The Third Side” አስፈላጊ ነው ይላል፡፡  በእኛ አገር ግጭቱ ያለው በአውራ ፓርቲና በተቃዋሚዎች መካከል ነው፡፡ ፀቡ… ብጥብጡ… ጥሉ… እስሩ… ዛቻው… እርግማኑ… መወጋገዙ… በሁለቱ ወገኖች ላይ ያነጣጠረ ሲሆን ይሄን የሚያበርድ… የሚያቀዘቅዝ… የሚያስታርቅ… ሽምግልና የሚቀመጥ… ግራ ቀኙን የሚያዳምጥ… “ሦስተኛ ወገን” የግድ መኖር አለበት - እንደ ዩሪ አባባል፡፡ The Third  Side ይባላሉ፡፡ የ97 ምርጫ የፖለቲካ ቀውስን ተከትሎ የታሰሩ የቅንጅት ከፍተኛ አመራሮችንና መንግስትን የሸመገለው በፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ የሚመራው የአገር ሽማግሌ ቡድን “ሦስተኛ ወገን” ነው፡፡ ሁለቱን ወገኖች አደራድሮ… አስማምቶ… በይቅርታም በሉት በምህረት ከእስር እንዲፈቱ አድርጓል - ይሄ ነው የሦስተኛ ወገን ትክክለኛ ሚና፡፡
አያችሁ… ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች በስሜት እልህ ተገባብተው… የቃላት ጦርነት ውስጥ ሲገቡ፣ ቶሎ ካልተገታና በፍጥነት ወደ ውይይትና… ድርድር ካልተገባ መጨረሻው አያምርም፡፡ ሁለቱ ወገኖች እንዳይጋጩ የምንፈልገው በዋናነት ስለምንወዳቸውና ስለሚጠቅሙን ላይሆን ይችላል፡፡ የሁለቱን ጠብ/ግጭት የማንፈልገው ለልጆቻችን… ለቤተሰባችን… ለማህበረሰባችን… ለአገራችን… ሰላምና ደህንነት ስንል ነው፡፡ (ኋላቀርነትም እኮ ነው!) ፕ/ር ኤፍሬም ይስሃቅም ከአሜሪካ ድረስ በአውሮፕላን እየተመላለሱ አንዴ ቤተመንግስት፣ ሌላ ጊዜ ወህኒ እየወረዱ የሸመገሉት… ለአገርና ለህዝብ ሲሉ ነው፡፡ (ለመጪው ትውልድ የምናስረክባትን አገር አንዘንጋ!)
እስከዛሬ የተቃዋሚ አመራሮች ታስረው ቢሆን ኖሮ… ለአገር ምን ያህል  ኪሳራ እንደሚሆን አስቡት፡፡ እናም… የስሜትና የእልህ ትኩሳቱ  ከፍ ሲል… ደማቸው እየተንተከተከ ሲያስቸግር… እንደ ደቡብ አፍሪካውያን ጥንታዊ ማህበረሰቦች፣ መርዝ የተቀባውን የአደን ቀስት ጫካ ውስጥ ደብቆ ሁለቱን ወገኖች ለውይይት የሚጋብዙ ሽማግሌዎች… ተቋማት… የሃይማኖት አባቶች… ያስፈልጉናል፡፡ ቢመስለንም ባይመስለንም እውነቱ ይሄ ነው፡፡ አገር እኮ በሃይልና በህግ ብቻ አትመራም፡፡ ለዚህ እኮ ነው መንግስት የቤኒሻንጉል ታጣቂዎች ወደ ሰላማዊ ኑሮ እንዲመለሱ ሰላማዊ ጥረት የሚያደርገው፡፡ ዶ/ር ዩሪ እንዳለው፤ ዘመኑ የጉልበት ሳይሆን የድርድር ነው!!!  

Saturday, 13 December 2014 10:51

የግጥም ጥግ

መቼ ነው ያለሁት?
ዛሬ ነግቶ መሽቶ ቀኑን አልፈውና፣
ሌላው ቀን ሲተካ ሲሆን ትናንትና፣
ይኸው እኖራለሁ አለሁ እኮ ዛሬ፣
ደግሞም ለዓመታት  ተስፋ አለኝ መኖሬ፣
    እያልሁ አስብና፣
    ሞቴን እረሳና፣
    እቅዴን አውጥቼ፣
    ምኞቴን አስፍቼ፣
ደጉን ተመኝቼ፣
ክፉውን ዘንግቼ፣
ሞትን ተሸክሜ ግን እየረሳሁት፣
ጎንበስ ቀና እያልሁ ይኸውና አለሁት፡፡
ምንም ባላውቀውም ቀኑን መሻገሬ፣
የነገን እንጃ እንጂ አለሁ ግን ለዛሬ፡፡
ሞት ትዝ ቢልም፣ ከራርሞ ከራርሞ …
    ከስንት ቀን አንዴ፣
መች ተስፋ ቆርጬ፣ ሰብዓዊ ፍጡር…
        ሰው አይደለሁ እንዴ!
ሃሳብ አይገባኝም፣ ባስብስ ምን ልሆን …
           ከቶ የማይቀረውን፣
ስለዚህ ማሰብስ፣ ዛሬን እንጂ ኑሮን …
    ፋታ የማይሰጠውን፡፡
ግን ታዲያ! …
    ማለፌን ሳስታውስ እንደገና ደግሞ፣
    ከውጥኔ በፊት ሞት ሲመጣ ቀድሞ፣
        ድንገት ፀጥ እልና፣
        ክልትው እለውና፣
        ሁሉም ይቀርና፣
        ጣጣዬ  ያከትምና፣
        ክርችም ብሎ ቁልፉ፣
        ይዘጋል ምዕራፉ፡፡
ቀነ - ሞታችንን እኔም ሆንኩ ሌላው …
          ጨርሰን አናውቀው፣
ስለዚህ ነው ሰዎች፣ “መቼ ነው ያለሁት?”
    ብዬ የምጠይቀው፡፡
                  * * *
አምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ህዳር 2007 ዓ.ም

Published in የግጥም ጥግ

    ከ6 ኪሎ ወደ ምኒሊክ በሚወስደው መንገድ በምናብህ እየኳተንክ ነው፡፡ መቼም የ6 ኪሎ ሰው ምሁር ነው፡፡ አንድ ጐረምሳ የአንስታየንን ሬላቲቪቲ ቲዎሪ እንደ አቡነዘበሰማያት በቃሉ ሲወጣው ብታይ፤ “ምን የእብድ ሰፈር ገባሁ” ብለህ እንዳትደነግጥ፡፡ እዚህ ላይ፡-
አወይ 6 ኪሎ አወይ ምኒሊክ ሆይ
አፈሩም ቅጠሉም ምሁር ይሆናል ወይ፡፡
የሚለውን የቆየ የአበው ተረት ማስታወስ አይከፋም፡፡ በስተግራህ እንደ ግራር አጥንት ችምችም ብለው የተገነቡ ሳይሆን የበቀሉ የሚመስሉ የ6 ኪሎ ልጆች በሌላው ሰፈር ላይ የተቆናጠጡትን የአእምሮ ልዕለ ሃያልነት እውን ያደረጉ ጫት ቤቶችን ታገኛለህ፡፡
ነገሩ የሆነው ልማታዊ መንግስታችን ወታደራዊውን ጁንታ መንግስት በግማሽ ቂጡ ሳይደላደል ከተቀመጠበት ወንበር ጠልዞ ከመጣሉ በፊት ነው፡፡ ዩኒቨርሲቲ በገቡ የ6 ኪሎ ልጆች ቀስቃሽነት ዘንድሮ ስታወራው “ፐ” አልያም “ንክር” ከሆንክ አጀብ የምትልበት የተማሪዎች ንቅናቄ በኋላም የEPRP ምስረታ እውን ሆነ፡፡
ታዲያ በ6 ኪሎ ልጆች የህቡእ ስብሰባ ላይ ሰርገው የገቡ የጨርቆስ ልጆች፤ በሰፈራቸው የለመዱትን “ጨርቄ ሽብር” ነጭ ሽብር የሚል የሃሳብ ሽርጥ አልብሰው አቀረቡ፡፡
ለነገር ችኩል የሆኑ የቦሌ ልጆች፣ ደርሶ ደም የሚሸታቸው የመርካቶ ልጆች፣ ሰፈራቸው ያለውን የጅብ መንጋ በመፍራት መቧደን ያደገባቸው የኮተቤ ልጆች፣ ነጭ ሽብርን በአንድ ድምፅ ደገፉ፡፡ ታዲያ ነቄዎቹ የ6 ኪሎ ልጆች ድምፀ ተአቅቦ አደረጉ፡፡
 ቅሉ ምን ዋጋ አለው? ደርግ መች ድምፀ ተአቅቦ ያውቃል እቴ! በየአደባባዩ እውቀትን ይሰብኩ፣ ጥበብን ይዘምሩ የነበሩ የ6 ኪሎ ልጆችን አናቶች እናቱ የተከለችለት ዱባ ይመስል አፈንድቶ ጨረሰው፡፡ ያኔ ታዲያ 6 ኪሎ የሀዘን ደመና ወረሳት፡፡ ለጠቢብ ልጆቿ አምርራ አለቀሰች፡፡ ይህንን ያየ የባሻ ወልዴ ችሎት አዝማሪ እንዲህ ሲል ሙሾ አወረደ፡-
አያችሁልኝ ጉድ የ6 ኪሎን
ወረቀት አንስቶ ብረት ሲፈትን!
ከሰለሞን ይሆን ጥበብ የወረሰው?
ከደሙ እኩሌታ እውቀት የፈሰሰው
አገር የሚያቀና አደይ አሳብባ
6 ኪሎ ጉዷ ልጇ ገደል ገባ፡፡
የ6 ኪሎ እናቶች አልቅሰው አላቆሙም፤ በእድል የተረፉ ልጆቻቸውን ከመጣው መቅሰፍት የሚታደጉበትን ዘዴ ዘየዱ፡፡ እነሆ የነሱ ጥንስስ ለግራር መደዳ አወዳይ መወለድ ምክንያት ሆነ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነው የ6 ኪሎ ልጅ ቢጤውን ፈልጐ “ጥግ እንያዝ” አልያም “ጭቁ እንበል” የሚለውን ሀረግ ማዘውተር የጀመረው፡፡
ከግራር መደዳ አወዳይ ቤቶች ጠርዝህን ይዘህ በመጓዝ ላይ እንዳለህ፣ ከ6 ኪሎ ሻሸመኔ ያሾልካል እንዴ እስክትል ድረስ ድሬዶች ከበዙብህ፣ በሀገራችን የዜማ ሊቅ የተሰየመው ያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ደርሰሀል ማለት ነው፡፡
አንዳንድ በሀገራችን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ላይ አንቱ የተባሉ ያሬድ ቀመስ አቀናባሪዎች፤ በያሬድና በድሬድ መካከል ያለውን ትስስር ሲያስረዱ፤ ቅዱስ ያሬድ በትል ከተፈተነ በኋላ፣ በዓፄ ገ/መስቀል አንካሴ እግሩ ከመሬት ከመሰፋቱ በፊት የሆነ በብዙ መዛግብት ያልሰፈረ ታሪክ ይነግሩሃል፡፡
ቅዱስ ያሬድ ዜማ በመድረስ ላይ እያለ በአዕምሮው የፈጠረው ዜማ አንደበቱ ሳይደርስ፣ በአናቱ ሲያሻው ቡልቅ ቡልቅ እያለ፣ ሲለው እየተነነበት ተቸገረ፡፡ ለገጠመው እክል አምርሮ ሲፀልይ መላዕክ ተገለፀለት፡፡
መላዕኩም፤ “ፀጉርህን እንደ ጠፍር አብጀው፤ እንደ መጫኛም ግመደው” የሚል ትዕዛዝ ሰጥቶት ተሰወረ፡፡ ታዲያ ያሬድ የተባለውን ቢያደርግም የጎንደርና የአክሱም ቀሳውስት “ገዳም ሳይገባ መነኮሰ” የሚል ሽሙጥ ፍራቻም፣ ነጭ ጥምጣም ጠቀለለበት፡፡ እነሆ ዛሬ አንተም በ6 ኪሎ ያገኘኸውን ድሬድ ሁሉ “ራስ-ተፈሪያን” ብለህ አትፈርጅ፡፡ “ያሬዳውያንም” ሞልተውልሃል፡፡
ፀጉርህን በእጅህ እያበጃጀህ፣ የያሬድን አጥር ታከህ ስትሄድ፣ አጥሩ ካለቀብህ ከነሙሉ  ግርማ ሞገስህ ቸሬ ሰፈር ገብተሃል፡፡ ቸሬ ሰፈር ከ6 ኪሎ ሰፈሮች ውስጥ ምትሃተኞች የሚበዙባት መንደር ነች፡፡ ከነባር ህልም ፈቺዎች 15 ቤተሰቧን በግማሽ ጆግ ቅንጬ እስከምታጠግብ አስማተኛ ልጃገረድ ድረስ በየፈርጁ ሞልተውልሃል፡፡ ምነው ታዲያ ስሙን ቸሬ አሉት፤ መቼም የታወቁ ሊቅ አስማተኛ መሆን አለባቸው፡፡ ጠጠር ለቅመው ለፈለገ ቡና፣ ለሌላው እጣን አድርገው የሚያድሉ ናቸው ካልክ ፍፁም ርቀሀል፤ በሄድክበት የሀሳብ እግርህ ተመለስ፡፡
ታሪኩ የሆነው ጣልያን ዳግመኛ ኢትዮጵያን በወረረች ጊዜ ነው፡፡ በጊዜው የነበሩ መኳንንት ከነጀሌያቸው “እንቢ ላገሬ” ብለው በዱር በገደሉ አርበኝነት ቢገቡም የነበራቸው የጦር መሳሪያ አነስተኛ ነበር፡፡ ያኔ ታዲያ ከመኳንንት ወገን የሚወለዱት አቶ ቸሩ አንድ መላ አበጁ፡፡ ሁለት ወደል አህያ ገዝተው፣ ከገጠር የገበሬ ቤት የሰበሰቡትን ብረት በፍልጥ መሃል እየዶሉ፣ ለአርበኞች ያቀብሉ ጀመር፡፡ በዚህም ብልሃታቸው የብዙ አርበኞችን ህይወት ታድገዋል፡፡
መቼም ለሰው ጠንቁ ሰው ነው፡፡ ይህንን ግብራቸውን ያወቀ ባንዳ፤ ለጣልያን ከረቢኛሬ በመንገሩ፣ ተወልደው ባደጉበት መንደር ለእናት ሀገራቸው በክብር ተሰዉ፡፡
በጊዜው የነበሩ አርበኞች ጓደኞቻቸውም እንዲህ ሲሉ አለቀሱላቸው፡-
ቸሬ ከዲነግዱ ብልሃት የወረሰ
ሶላቶን ሳንጥል ውላችን ፈረሰ፡፡
ብረቱ ይቅርብን ቸሬ አንተ ተመለስ
ብናጣህ እኮ ነው ወኔያችን የሚፈስ፡፡
ወዳጄ የቸሬ ሰፈርን ገድል ከሰማህ በኋላ ከፊል ልብህ አስማተኛ፣ ከፊል ልብህ አርበኛ ልሁን እያለ አልረጋ ብሎ አዕምሮህን ሲሞግተው ሰማሁ፡፡ ባታውቀው ነው፡፡ በ6 ኪሎ ታሪክ ሰሚ እንጂ ታሪክ ደጋሚ መች ይመሰገናል፡፡ ባይሆን የ6 ኪሎ ልጆች እሳት ከበው፣ ሞኝ-አንግሳቸውን እየጨለጡ፣ ከሰሟቸው ጥዑም የሰፈራቸው ታሪኮች መሃል አንዱን እነሆ፡-
አባባ ጃንሆይ፤ ከእንግሊዝ አብረው ጣልያንን ካባረሩ በኋላ፣ 6 ኪሎ ወደ ቀድሞ ፈንጠዝያዋ ተመለሰች፡፡ ልጅ ሳይል አዋቂ ሁሉም የ6 ኪሎ ውልድ ወርቁ ጠጅ ቤት ከተመ፡፡
 ከሸክላ ማጫወቻው የሚተመው ዘፈን ሲያቆም ብቻ ሁሉም ጨዋታውን ገታ አድርጐ፣ በቀጣይ የሚሆነውን ይጠብቃል፡፡ አንድ ልጅ - እግር ከወደ ጓዳ ወጥቶ የመሞዘቂያውን መነዌላ አጡዞት፣ ወደ መኳንንቱ መደዳ አይኑን ጣል ያደርጋል፡፡ ነገሩ የገባቸው ፊታውራሪ ኢብሳ፤ በጥቅሻ ሲያነሱት ከበር መልስ ላለው ሁሉ ጠጅ ያድላል፣ ሙዚቃው ከፍ ይላል፣ ሁካታው ይቀልጣል፣ 6 ኪሎም ጠጅ ትራጫለች፤ እንደዚያ ታመሻለች፤ እንዲያም ታነጋለች፡፡
ከዚያ ሁሉ ሁካታ መሃል አንድ ዘለግ ብሎ የሚሰማ ዝምታ ነበር፤ የሚጨንቅ ዝምታ…ፍርሃት የወለደው ዝምታ! የአየለ ስብሀቱ ዝምታ…
አየለ ስብሀቱ ሞቅ አለው፡፡ በፊትአውራሪ ግብዣ የጠጣውን ጠጅ ነገ እንደማያገኘው ተረዳ፡፡ አጥንተ - ድህነቱ ከበደው፡፡
እላዩ ላይ እንዳለው ቡትቶ አሽቀንጥሮ ሊጥለው ፈለገ፡፡ ተሳካለትም፡፡ በመንገድ ላይ ያገኛቸውን ፈረንሳዮች ጃንሜዳ ይዟቸው ገባ፡፡ “ይህ የምታዩት ሁሉ የአያት የቅድመ - አያቴ ርስትና የኔ ቤት ነው፡፡ ንብረቴን ሁሉ ሸጬ ወይራ - አምባ እናቴ ጋ መግባቴ ስለሆነ፣ 10ሺህ ብር ግዙኝ!?” አላቸው፡፡ አላቅማሙም ተስማሙ፡፡
በበነጋው አንኮላ ፈረንጅ ሁሉ አጥር ሊያጥር፣ ችካል ይዞ ጃንሜዳ ገባ፡፡ በነገሩ ግራ የተጋቡት ክቡር - ዘበኞች፤ አየለንም ፈረንሳዮቹንም ይዘው ዙፋን ችሎት ቀረቡ፡፡ ጃንሆይም በወገናቸው ብልጠት ደስ ቢሰኙም ፍርደ - ገምድል ላለመሆን እየጣሩ፣ “ልጅ አየለ ብሩን ከወዴት አደረስከው!?” አሉ፡፡ አየለም ኩታውን አደግድጐ መሬት ለጥ አለና፤ “በአገራችን ነፃ መውጣት የደስ ደስ ከበር መልስ ጠጥቼ አጠጣሁበት” አላቸው፡፡ አሁንም በመልሱ ደስ የተሰኙት ጃንሆይ፤ ብሩ ከግምዣ ቤት እንዲከፈል አዘው አየለን በሰላም አሰናበቱት፡፡ ወረኛው ወርቁ ጠጅ ቤት ሲደርስም፤ “አየለ ስብሃቱ ጃንሜዳ ነው ቤቱ!” ሲሉ አቃበጡት፡፡
 (ውድ አንባቢያን፤ ከላይ የቀረበው ወግ በቅርቡ በማህበራዊ ድረገፅ ላይ በተካሄደ የስነፅሁፍ ውድድር ያሸነፈና ለፀሃፊው የደራሲ አዳም ረታን “መረቅ” አዲስ ልብወለድ መፅሃፍ ያሸለመ እንደሆነ የውድድሩ አዘጋጆች ገልፀውልናል፡፡ እኛም ይሄን በማህበራዊ ድረገፅ የተጀመረ አዲስ የጥበብ ባህል ለማበረታታት በማሰብ፣ መጠነኛ አርትኦት አድርገንበት አትመነዋል፡፡)


Published in ህብረተሰብ
Saturday, 13 December 2014 10:45

ወጣቱን በቅኔ

         በአገራችን “ወጣት የነብር ጣት” የሚል አባባል አለ፤ ወጣትነት የብርታትና የጉብዝና ዕድሜ መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡ ነብር ጥፍሮቹን በሚያድነው እንስሳ ላይ ከሰካ፣ ሰካ ነው፣ እንስሳው የትም አያመልጥም፡፡ ከዚያ በኋላ ጉሮሮውን አልያም ማጅራቱን ባንድ ንክሻ ይዞ ሲጥ ማድረግ ብቻ ነው፡፡ ወጣቶችም አንድ ነገር ከያዙ፣ ያዙ ነው - ያ ነገር ይጥቀምም ይጉዳ ሁሉ ነገራቸውን ይሰጡታል፡፡ በአገራችን በ1966ቱ አብዮት ወቅት የዩኒቨርሲቲና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች አደባባይ የወጡት ከመምህራኖቻቸው፣ ከወታደሩና ከፋብሪካ ሠራተኛው በፊት እንደነበረ ይታወሳል፡፡ ከገባቸው ነገር ያልገባቸው ቢበልጥም አብዮቱን የሙጥኝ ብለው ይዘዉት ነበር፡፡ በኋላም ኢህአፓን ተቀላቅለው ሲታገሉ የነበሩ ወጣቶች የነበራቸው ራስን እስከመሰዋት የደረሰ ድርጅታዊ ፍቅር እውነትም ወጣትነት ካልተጠነቀቁ ምን ያህል ለግብታዊነት የሚዳርግ ዕድሜ እንደሆነ የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ዛሬ የሚያስተዳድሩን ገዢዎቻችንም በወጣትነታቸው በረሃ የገቡ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡
ይህ በተገቢው መንገድ የሚያደራጀውና የሚመራው ቢያገኝ ታሪክ ሊሠራ የሚችል ኃይል ዛሬ ያለበት ሁኔታ ያሳዝነኛል፡፡ የኛ ትውልድ ወጣት ግራ የተጋባ ነው፡፡
እንደ አያቶቹ አርበኛ፣ እንደ አባቶቹ ደግሞ አብዮተኛ አይደለም፡፡ ልግመኛ ነው፡፡ ልግመኛ የሆነው ግን ወዶ አይደለም፡፡ የሚያግዘው አጥቶ ነው፡፡ በአገራችን እናቶች ተሰብስበው ቡና ሲጠጡ ከመካከላቸው አዋቂ ለሚባሉት ለአንደኛይቱ የቡናቸውን አተላ የማስነበብ ልማድ አላቸው፡፡ ይህ የባለስኒውን ዕድል ፈንታ ይገልጣል ተብሎ የሚደረግ ከአጉል እምነት የመነጨ ልማድ ነው፡፡ ተከታዩዋን ቅኔ ስናነብ ይህን አጉል ልማድ ወደ ጎን ብለን ፍሬ ነገሩን ለማግኘት በመሞከር ይሁን፡-
“የቡኑን አተላ አትድፉት ብለናል
አንባቢ ጠፋ እንጂ ስኒማ ሞልቶናል”
የጠፋው የቡና አተላ የሚያነብ አይደለም፤ እሱንማ እናቶች ተክነውበታል፡፡ ይልቅ ያጣነው የሚያነብ፣ ታሪኩን የሚያውቅና የሚጠይቅ ትውልድ ነው፡፡ ያለፈው ትውልድ በበጎ ከሚነሳባቸው ነገሮች ዋነኛው ለንባብ የነበረው ጥልቅ ፍቅር ነው፡፡  በአንጻሩ ዛሬ “ስኒማ ሞልቶናል፡፡” አዳዲስ ሲኒማ ቤቶች በየጊዜው ሲከፈቱ እናያለን፡፡ አዳዲስ አብያተ መጽሐፍት ግን ተከፈቱ ሲባል አንሰማም፡፡ ተከፍተውም ከሆነ ማስታወቂያ አይነገርላቸውም፡፡ እርግጥ ነው ሲኒማ ቤቶች ያስፈልጉናል፡፡ እንደውም እየተሠሩ ካሉት ፊልሞች የጥራት ደረጃ ጋር ሲነጻጸር አያንስም ካልተባለ በስተቀር፣ ካለን የህዝብ ብዛት አኳያ ሲኒማ ቤቶቻችን ቁጥራቸው እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ሆኖም አብያተ መጽሐፍት በእጅጉ ተመናምነዋል፡፡ በውጤቱም የማያነብ ትውልድ ተፈጥሯል፡፡ በተቃራኒው ግን በሲኒማ ቤቶች ደጃፍ ላይ ረጃጅም ሰልፍ ይታያል፡፡ አንዳንዴ ሳስበው ፊልም ሰሪዎቻችን ራሳቸው የሚያነቡ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍትን ወደ ፊልም ሲቀይሩ እምብዛም አይታዩም፡፡ የቱ ይቀድማል - መጽሐፍ ወይስ ፊልም? ቢያንስ ግን መጽሐፍ ወደ ፊልም እንጂ ፊልም ወደ መጽሐፍ ተቀየረ ሲባል አጋጥሞኝ አያውቅም፡፡
ወጣቱ እንደ ንባብ ያሉ አስተማሪ መዝናኛዎችን ብዙም እንዲወድ ባለመደረጉ ትኩረቱን ወደ አልባሌ የጊዜ ማሳለፊያዎች ለማዞር ተገዷል፡፡ እነኚህ መዝናኛዎች ገንዘብን፣ ጊዜን፣ ጤናን፣ ቤተሰባዊና ማኀበረሰባዊ ትስስርን፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ ህይወትን የሚያሳጡ ናቸው፡፡ ዛሬ ወጣቶቻችን አደጋ ተጋርጦባቸዋል - ያውም የእሳት አደጋ፡፡ እናም ይህን ተረድቶ የተጨነቀ ወገን እንዲህ ይላል፡-
“ለማዳን ባትችል ቤት ንብረትህን
እሳቱ ሳይበላህ አሽሽ ነፍስህን”
አዎ፣ ቤቱ በእሳት የተያያዘበት ሰው በቅድሚያ ማድረግ ያለበት ማቄን ጨርቄን ሳይል ህይወቱን ለማትረፍ መሸሽ ነው፡፡ ወጣቱም በሀሺሽና በተለያዩ አደንዛዥ ዕፆች ሱስ ተጠምዷል፡፡ በእኩዮች ግፊት፣ ዘመናዊነት ነው ብሎ በማሰብ ወይም መሄጃ በማጣት ተዘፍቆበታል፡፡ አንዳንድ የምሽት ክበቦች የቀን ቀን ሥራቸው ወጣቶችን ሰብስቦ ጢስ ማጠን ነው፡፡ እኔ በግሌ ቦሌ ሐያት ሆስፒታል አካባቢ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር የምሄድበት ቤት አለ፡፡ ቤቱ ጭር ያለና ሰላማዊ ነው፡፡ ሆኖም ጥቂት እንደተቀመጣችሁ ድንገት ከውስጠኛው ክፍል ከደህና ኗሪ ቤተሰብ የተገኙ የሚመስሉና ገና በታዳጊነት የዕድሜ ክልል ውስጥ ያሉ ወንዶችና ሴቶች ተግተልትለው ሲወጡ ታያላችሁ፤ ቆይተው ደግሞ ግር ብለው ተመልሰው ይገባሉ፡፡ አኳኋናቸው ሁሉ ያፈነገጠ ነው፡፡ አንድ ቀን አስተናጋጁን ጠርቼ ብጠይቀው እየተቅለሰለሰ ልጆቹ የሚመጡት ዕፅ ለመውሰድ እንደሆነና ከነሱ በስተቀር ሌላ ሰው ወደ ውስጥ መግባት እንደማይፈቀድለት ነገረኝ፡፡ እንግዲህ እንዲህ ያሉ የንግድ ቤቶች በወጣት ህይወት እየቀለዱ ያለ ከልካይ ገንዘብ ያጋብሳሉ፡፡ እሺ ልጆቹ የሚያጠፉት ገንዘብ የወላጆቻቸው ስለሆነ አይቆጫቸው ይባል፣ ግን እንዴት የገዛ የራሳቸው ህይወት አያሳስባቸውም?
በወጣቱ ላይ ወጥመድ የሆነበት ዋናው ነገር የጃማይካውያን ተፅዕኖ ነው፡፡ በፊት በፊት እዚያው ሻሸመኔ አካባቢ ይሆናል እንጂ አዲስ አበባ ውስጥ የካናቢስ ስርጭት በግልፅ ሲካሄድ እንደነበረ አላውቅም፡፡ አሁን ግን ቦሌ ከኖክ ነዳጅ ማደያ ገባ ብሎ ዕፅ አዘዋዋሪዎች ተሰማርተው እንደሚገኙ ይነገራል፡፡ ሀያ ሁለት ማዞሪያ አካባቢ አንድ የምሽት ክበብ ውስጥ አደገኛው ኮኬይን ሳይቀር በክብሪት ሳጥን ውስጥ ተደብቆ እንደሚሸጥ ሰምቻለሁ፡፡ የሚወራው ነገር ሁሉ እንዲህ ያሰኛል፡-
“ሁልጊዜ አሻጋሪ አይገኝምና
ሰምጠሽ እንዳትቀሪ ተይ ተማሪ ዋና”
ወጣቶቻችን በጃማይካውያን የአኗኗር ዘይቤና የሙዚቃ ስልት ከተመሰጡ ቆይተዋል፡፡ ሬጌ ሙዚቃ ስለ ፍቅርና ሰላም በመስበክ ቢታወቅም ሁልጊዜ እንደዚያ ነው ማለት አይደለም፡፡ ወጣቱ ከማርሎን አሸር “Ganja Farmer”፣ እስከ አፍሮማን “Before I Got High” ድረስ ማሪዋናን በግልፅ በሚያወድሱ ዘፈኖች እየተወዛወዘ ይናብዛል፡፡ ዋና መዋኘት ሳይችሉ ወንዝ ውስጥ መግባት ውጤቱ ራስን ለአስከፊ ሞት መዳረግ እንደሆነው ሁሉ በማሪዋናም ሱስ ሰምጠው የቀሩ የትየለሌ ናቸው፡፡ መቸም የፈረደበት ቤተሰብ ጦሱን ችሎ አስታምሞ አንዳንዶቹን ወደ ሰውነት ተራ ይመልሳቸው ይሆናል፡፡ ይሁንና ይህን የሱስ ወንዝ ሁሉም አይሻገሩትም፡፡ ብዙዎች ትምህርታቸውን አቁመዋል፣ ለከባድ የአእምሮ ቀውስና ባስ ሲልም ለእብደት ተዳርገዋል፡፡ በአንድ ወቅት እናደንቃቸው የነበሩ አርቲስቶቻችን ሳይቀሩ በየመንገዱ እየለፈለፉና እየተሳደቡ መሄድ ጀምረዋል፡፡በአሁኑ ወቅት የወጣቱ ብቻ ሳይሆን የመላው ኀብረተሰብ ችግር የሆነው የጫት ጉዳይም መረሳት የለበትም፡፡ በጫት የተነሳ አንድ ትውልድ ቃል በቃል እየጠፋ ነው፡፡ ስሟን በማልጠራት የጫት መዲና በሆነች ምስራቃዊ የሀገራችን ከተማ ከአምስት ሰው አንዱ አብዷል ወይም ለማበድ መንገዱን ጀምሮታል፡፡ ጫት ገሃዱን ዓለም ያስጠላል፣ ምናብ ውስጥ ይከታል፡፡ ተጠቃሚውን ከራሱና ከቤተሰቡ ጋር ያጣላል፡፡ እናም አስታራቂ እንዲህ እያለ ይለምናል፡- “እናስታርቅ ብንል አስቸገራችሁን
ምናለ ብተዉት ይህን ቂማችሁን”
ይህ ምልጃ የቀረበው ወጣቱ ከ‘ቂማ’ ብቻ ሳይሆን ከማንኛውም ሱስ እንዲወጣ ለመወትወት ነው፡፡ በረሃብ የምትታወቀው አገራችን ‘ሪሃብ’ (Rehabilitation Center) አቋቁማ ሱሰኞች እንዲያገግሙ የምትረዳበት አቅም የላትም፡፡
መፍትሔው መጥፎውን ልማድ ሙሉ ለሙሉ እርግፍ አድርጎ መተው ብቻ ነው - የአካል ክፍልን ቆርጦ እንደ መጣል ቢከብድም፡፡
እስቲ አሁን ደግሞ ስለ ወጣት እህቶቻችን አለባበስ እንነጋገር፡፡ ብዙዎቹ ስርዓት ያለውና ልከኛ አለባበስ የሚከተሉ ቢሆንም ያንዳንዶቹ አለባበስ ግን ያስበረግጋል፡፡ ታላላቆቻቸው ቢያዩዋቸው እንዲህ ሳይሉ አይቀሩም፡-
“እጅግ ተጨነቀ አዘነ ልባችን
ርቃን ስትሄድ ታናሽ እህታችን”
ወጣቷ ከምትኖርበት ኀብረተሰብ ባህል በመንፈስ መራቋ ሳያንሳት በአደባባይ ርቃን ሊባል የሚችል አለባበስ ለብሳ ስትሄድ በቤተሰቧ ላይ የሚፈጠረው መሸማቀቅ ከፍ ያለ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እንደዚያ ለብሳ ስትወጣ ያልከለከለ ወላጅ ከእሷ ባይሻል ነውም ያስብላል፡፡ እንዴት መልበስ እንዳለብኝ ማንም አይነግረኝም የሚሉ በበረከቱ ቁጥር እነሱን አይቶ ስሜቱ የተነሳሳ አለሌ መጫወቻ የሚሆኑት ሚስኪን ልጃገረዶች ዕጣ ያሳዝናል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገራችን እየተዛመተ የመጣ አንድ ክፉ ወረርሽኝም አለ፡፡ ያየውን ሁሉ ሳያመዛዝን ለቀም የሚያደርገው ወጣትም የወረርሽኙ ዋነኛ ተጠቂና አስፋፊ ሆኗል፡፡ እስቲ ቀጣዩዋን ቅኔ አንብበን የወረርሽኙን ምንነት እንድረስበት፡-
“በዱላ ምክቶሽ ፈሪው እየገባ
ሲያቀምሱት ይሸሻል አልቅሶ ደም እንባ
የዛሬው ግን ፍልሚያ ዋለ ተፋፍሞ
መንደሩ ቀለጠ ወንድ ከወንድ ገጥሞ”
ዱላ ምክቶሽ በገጠር የተለመደ ባህላዊ ጨዋታ ነው፡፡ ለነገሩ ጨዋታ ይባል እንጂ አልፎ አልፎ ሞት ሊያስከትል ይችላል፡፡ እዚህ ላይ የሱርማዎችን ‘ዶንጋ’ እናስታውሳለን፡፡ ታዲያ ሁለት ጀግኖች የተጋጠሙ እንደሆን ፍልሚያው ምንም አሰቃቂ ቢሆን ተመልካች ግን ምርጥ ነው ብሎ ያሞካሻል፡፡ የላይኛው ቅኔ የሚናገረው ግን ስለ ዱላ ምክቶሽ ሳይሆን ስለ ግብረ ሰዶማዊነት ነው፡፡ ዛሬ “ወንድ ከወንድ ገጥሟል፡፡” በርካታ ወጣቶች በዚህ አደጋ እንደተያዙ በተለያዩ ሚዲያዎች እንሰማለን፡፡ ግብረ ሰዶማውያን አደን ላይ ናቸው፡፡ እኔ እንኳ ባለኝ ጠባብ ማኀበራዊ ግንኙነት እኔን ጨምሮ ሦስት ጓደኞቼ በተለያየ ጊዜ በግብረ ሰዶማውያን ትንኮሳ ተፈጽሞብናል፡፡ ብዙ ጓደኞች፣ ያሏቸው ደግሞ ብዙ ገጠመኝ ሊሰሙ ይችላሉ፡፡ ግብረ ሰዶም በሴቶችም በኩል የተለመደ ሆኗል፤ የፌስ ቡክ ግሩፕ እስከ መመስረት ደርሰዋል፡፡ እንግዲህ የዘመናችን ወጣት ያሉበት ጋሬጣዎች በጥቂቱ እነዚህን ይመስላሉ፡፡ በራሱ ዕድል ላይ እንዲወስን አልተፈቀደለትምና መፍትሔ ከሌላ ወገን ይጠብቃል፡፡ ይህን ጊዜ መከፋቱን በቅኔ እንዲህ ይተነፍሰዋል፡-
“ጽናትን ከውድቀት ህልምን ከሌት ወርሶ
የኑሮን አቀበት ወጣት አጎንብሶ”
አዎንታዊ አስተሳሰብ ያለው ሰው ከመጥፎ ነገር ጥሩ ነገርን ያወጣል - ከውድቀት ጽናትን ይማራል፣ ከአስፈሪው ሌሊትም ህልም አልሞ ያድራል፡፡ በስተመጨረሻም ባለድል ይሆናል፡፡ ለዚህ የታደሉ ብዙ ወጣቶች ከመካከላችን ይገኛሉ - ብንከተላቸው አርአያ የሚሆኑን፡፡ ነገር ግን አብዛኛው የትውልዴ ወጣት አንገቱን አጎንብሶ ነው ያለው፡፡ አገር ተረካቢ የሚባለው ወጣት አንገቱን ካጎነበሰ እንግዲህ አገር ምን ተስፋ አላት? እኛ ወጣቶች ከወደቅንበት መሬት ተነስተን፣ አቧራውን አራግፈን፣ ቀጥ ብለን መሄድ መጀመር አለብን፡፡ መንግሥትም ከፕሮፓጋንዳ ባለፈ ወጣቱን የአገራችን ዕድገት ዋነኛ ተዋናይ ለማድረግ ከልቡ ሊሠራ ይገባል፡፡
(ማስታወሻ፡- በጽሑፉ ላይ የቀረቡት ቅኔዎች በሙሉ የጸሐፊው ናቸው፡፡)

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
የዓመቱ የመጀመሪያው ሩብ ፉት አለ አይደል!
እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው ለሴት ጓደኛው ስጦታ መስጠት ይፈልግና ምክር ይጠይቃል፡፡
“ለጓደኛዬ ምን ስጦታ ብሰጣት ጥሩ ነው?”
“ትወድሃለች?”
“እንደምትወደኝ እርግጠኛ ነኝ፡፡” “እንግዲያው፣ ምንም ነገር ብትገዛላት ደስ ይላታል፡፡”
‘ቢሆን ኖሮ አሪፍ ነበር’ የሚባለው እንዲህ ነው፡፡ አሀ… ስጦታ መስጠትና መቀበል ራሱ ‘ትርፍ ነገር’ መሆኑ ቀርቶ ‘የመዋደድ’ ማረጋገጫ ምልክት እየሆነ ነዋ! በፊት እኮ ስጦታ…አለ አይደል… ‘ጉቦ’ ቢጤ ነገር ነበር፡፡ “ማስቲካ ብሰጥሽ ምን ትሰጭኛለሽ?” ምናምን አይነት የልጅነት ዕቃ፣ ዕቃ ጨዋታ ትዝ አይላችሁም! እና ማስቲካው ‘ጉቦ’ ነበር፡፡ ዕቃ፣ ዕቃ ጨዋታው ደግሞ የትያትር ምናምን ሰዎች እንደሚሉት ‘ኢምፕሮቫይዜሽን’ ነገር ነበር፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
ይቺን ጨዋታ ስሙኝማ…በበፊት ጊዜ ነው አሉ፡፡ ሰውየው በዘመኑ ‘የተከበሩ’ የሚባሉ አይነት ናቸው፡፡ ታዲያላችሁ… አንድ ቀን ሚስታቸውን ደስ ለማሰኘት ብለው ምን ቢያደርጉ ጥሩ ነው… እኔ ነኝ ያለ የፍየል ሙክት በሠላሳ ብር ገዝተው ቤታቸው ይመጣሉ፡፡ ፍየሉ ተጎትቶ ግቢ ሲገባ አገሬው ሁሉ በየበሩ ብቅ ብሎ ያያል አሉ፡፡ (‘በየበሩ ብቅ ብሎ ማየት ዘንድሮም እኮ በተለያየ መልኩ በሽ፣ በሽ ነው፡፡) ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…በግ ቆዳ መልስ አሥራ አምስት ብር የሚገዛበት ዘመን አልፎ አሁን ክትፎ ሳህን መልስ መቶ ስድሳ ብር ሆኖ አረፈው! የዘንድሮ አንድ ክትፎ እኮ ከጥቂት አሥርት ዓመታት በፊት ስምንትና ዘጠኝ ሙክት ይገዛ ነበር ማለት ነው፡፡ በዚህ ላይ በሠላሳ ሳንቲም ‘ያላበው ቢራ’ እግር ሰቅሎ ማንደቅደቅ ነው፡፡ ዘንድሮ በሠላሳ ሳንቲም ግፋ ቢል አንድ በጣም ቀሺም ማስቲካ ቢገዛ ነው፡፡ በግ አሥራ አምስት ብር ይገዛበት የነበረበት ዘመን ‘ዶኩሜንታሪ’ ይሠራልንማ!  
እናማ…የሌሎች ሚስቶች ሁሉ ዓይኖቻቸው ተቁለጨለጩ፡፡ “እንዲሀ ነው እንጂ ባል ማለት፣ ለሚስቱ የፍየል ሙክት የሚገዛ!” ማለት ይጀምራሉ፡፡ ይሄኔ…ባሎች ሁሉ ምን አሉ ተባለ መሰላችሁ… “ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” ብለው እርፍ!
ነገርዬው ምን መሰላችሁ… በጊዜው የናጠጠ ‘ዲታ’ ቤት ቢሆን እንኳን የፍየል ሙክት መግዛት የተለመደ አልነበረም፡፡ አለው የተባለ ‘ባል ተብዬ’ (ቂ…ቂ…ቂ…) አሀ… ሴቶቹ እንደዚያ ነው የሚያስቡት ብዬ ነዋ!) ግፋ ቢል ትልቅ ነገር ገዛ ከተባለ የሀያ ብር የበግ ሙክት ነው፡፡ እናላችሁ…“ሚስቶችን አጠገባቸው…” ያሉ ባሎች… አለ አይደል… ነገርየውን በወሬ፣ ወሬ ጃንሆይ ዘንድ አድርሰውት ነበር፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል፣ የዘንድሮ የስጦታ ነገር አስቸጋሪ ሆነ እኮ፡፡ ‘እንደ አቅም’…ስጦታ መስጠት ብሎ ነገር የለም፡፡ “ዋናው ነገር የስጦታ ዕቃው ሳይሆን ሀሳቡ ነው…” አይነት ነገር ለፊልም ፖስተር ‘ማሳመሪያ’ ይሆን እንደሁ እንጂ በዓረፍተ ነገር አሰካክ የሰዋሰው ትምህርት ውስጥ እንኳን የለም፡፡
ልክ ነዋ… የባለ አበባ ቀሚስ ዘመን አልፎበታላ! የድቡልቡል ማስቲካ ዘመን አልፎበታላ! የሁነኛው መራ ሽቶ ዘመን አልፎበታላ! የሀር ውስጥ ልብስ ዘመን አልፎበታላ! (ቂ…ቂ…ቂ…) የምር ግን…አንዳንዴ እንደዚያ አይነት ዘመን ነበረ እንዴ ያሰኛል፡፡ ልክ ነዋ…መጀመሪያ ነገር እንትናዬዎች ስጦታ ፈላጊዎች አልነበሩም፡፡
እናላችሁ… ዘንድሮ…የስጦታ ነገርም በብዙ ‘ዲጂት’ አድጓል፡፡
“ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” የሚያሰኙ ነገሮች መአት ናቸው፡፡
እናላችሁ… ‘ስጦታ’ ተብሎ ምን የመሳሰሉ መኪኖች የሚሰጡበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ እንደውም አንድ ‘የከተማው ነገር የሚገባው’ ወዳጃችን ምን አለን መሰላችሁ…“ውድድሩ የመኪና ስጦታ በማግኘት ላይ ሳይሆን በመኪናው አይነት ነው፡፡”  
ኮሚክ እኮ ነው! ስሙኝማ…አንድ ሰሞን ለስጦታ ተብላ የተፈበረከች መኪና አሁን ‘ሁሉም’ ያዛት አይደል! “…አገኘኋት በምናምን…” ተብሎ ከአሥራ ስምንት ዓመት በታች መናገርም፣ መስማትም መከልከል ይገባው የነበረ አባባል ቢጤ ነገር ሁሉ ተፈጥሮላት ነበር! ብቻ የሆነ የሚገርም ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡
ዘንድሮ…አለ አይደል… “ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” የሚያሰኙ ነገሮች በዝተዋል፡፡
“ስሚ፣ እንትና እኮ ቦይፍሬንዷ የመኪና ስጦታ ሰጣት፡፡”
“አትዪኝም!”
“አይ ስዌር!”
“ምን አይነት መኪና ሰጣት?”
“ያቺ ብራዚሊያ የሚሏት የድሮ መኪና…”
“ውይ!  ውይ! አፈር በበላሁ!”
“ምነው፣ ምነው! እሷን መኪና ነው ስጦታ ብሎ የሰጣት፡፡ ስታሳዝን!”
ልክ ነዋ…ልጄ ዘንድሮ የመኪና ስጦታ የተሰጣት እንትናዬ እኮ ከፈለገች ሸጣው እኔ ያለሁበትን መንደር መግዛት ትችላለቻ!
“ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” አይነት ነገሮች በዝተዋል፡፡
እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ይቺን አንድ ሰውዬ አላት የተባለች ነገር ስሙኝማ፡፡ “ባለፈው የገና በዓል ለሴት ጓደኛዬና ለወንድሜ ስጦታ ልኬላቸው ነበር፡፡ የሴት ጓደኛዬ በዚያ ሰሞን ደስተኛም ስላልነበረች እሷን ደስ ለማሰኘት ነበር ስጦታ መላኬ፡፡ ለእሷ አሪፍ ሽቶ፣ ለወንድሜ ደግሞ የሽጉጥ ስጦታ ነበር የላኩላቸው፡፡ ለእሷ በላኩት ስጦታ ላይ ‘ይህንን ስጦታ ራስሽ ላይ እንደምትጠቀሚው እርግጠኛ ነኝ…’ ብዬ ጽፌ ነበር፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል በስህተት የላኩላት ሽጉጡን ነበር፡፡ እንዳልኳትም ራሷ ላይ ተጠቀመችው፡፡”
‘ለአቅመ ስጦታ መስጠት’ ከደረሳችሁ ስጦታ ከማሳሳት ይሰውራችሁማ!
ስሙኝማ ዘንድሮ እኮ ለእንትናዬዎች ስጦታ ሲሰጥ…አለ አይደል…አይደለም ለተቀባዮቹ ለእኛ ለሰሚዎችም የደም ዝውውር ችግር ሊፈጥር ይችላል፡፡ እነ ሽቶና መዋቢያዎች እንኳን ሚጢጢዋ ብልቃጥ አራትና፣ አምስት ሺህ ብር ገብተዋል፡፡ከተማው ውስጥ ልወዝወዘው በእግሬ እያላችሁ…አለ አይደል…ከአንድ ከሁለት ወር በፊት ሀይገር ላይ ለመሳፈር ስትጋፋ ያያችኋት እንትናዬ ምን በመሰለች መኪና ስትፈስ ታዩዋታላችሁ፡፡ ግራ ይገባችኋል፡፡ በዚያ ሰሞን የመኪና የሎተሪ እጣ መሰጠቱን በሬድዮ ምናምን ነገር አልሰማችሁማ!
በኋላ ለሆነ ወዳጃችሁ… “አንተ… እንትና ምን የመሰለ መኪና ይዛ አየኋት…” ትሉታላችሁ፡፡
እሱም “ልጄ እሷ ጎበዝ ነች፣ አውቃበታለች…” ይላችኋል፡፡  
አውቃበታለች ብሎ ነገር ምንድነው?
“ምኑን ነው ያወቀችበት?”
“አንተ ደግሞ ዘለምህን ቢያጥቡህ፣ ቢፈትጉህ የማትጠራ ፋራ አትሁን እንጂ! የጨዋታውን ህግ አወቀችበታ! የያዘችው ቦይ ፈሬንድ አይደለም መኪና አንድ ሙሉ የሪል ስቴት መንደር መግዛት የሚችል ነው፡፡”
“ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” አይነት ነገር በዝቷል፡፡
እናላችሁ…‘ያወቁበት’ እንዲህ በመኪና ሲፈሱ፣ ‘ያላወቁበት’ ደግሞ ግፋ ቢል ‘ዊንዶው ሾፒንግ’ የሚከለክላቸው የለም፡፡ ቂ…ቂ…ቂ… (‘ያላወቃችሁበት’ እንትናዬዎች… የምክር አገልግሎት ከፈለጋችሁ ስልክ ምቱማ! ቢያንስ፣ ቢያንስ የምታንዣቡባቸውን ካፌዎች መጠቆም አያቅተንም፡፡) (“ቦሌን ባትዝናናበትም ማንም ሳይከለክልህ በእግርህ ትወዘወዝበታለህ…” ያልከኝ ወዳጄ …‘የሚወድቅ ሞራል’ ያገኘህ መስሎሀል!)
ብቻ ምን አለፋችሁ…“ለሚስቱ የፍየል ሙክት ገዝቶ ሴቶቹን አጠገባቸው…” አይነት ነገር በዝቷል፡፡
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ህብረተሰብ

      በአዲስ አበባ ለመጀመሪያ ጊዜ ሱፐር ካቴክስና የእንግሊዝ ንግድና ኢንዱስትሪ በመተባበር ለሶስት ቀናት በኢሊሌ ሆቴል ያዘጋጁት የእንግሊዝ ላኪ ኩባንያዎች ምርትና አገልግሎት የካታሎግ ኤግዞቢሽን በጣም ጥሩ እንደነበር አዘጋጁና የቢዝነስ ሰዎች ገለፁ፡፡
የሱፐር ካቴክስ አባልና የኤግዚቢሽኑ አዘጋጅ ሚ/ር ጀምስ ኦ’ሲሊቫን፣ ኤግዚቢሽኑ በጣም የተሳካ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ “ከ350 እስከ 400 የቢዝነስ ሰዎች በኤግዚቢሽኑ ተሳትፈዋል፡፡ በቀን ከ100 ሰው በላይ ከጎበኘው እኛ ሥራ በዝቶብን (ቢዚ) ነበርን ማለት ነው፡፡ ይኼ ለእኛ ከጠበቅነው በላይ ነው” ብለዋል፡፡
የካታሎግ ኤግዚብሽኑን ሲጎበኝ ያገኘሁት ወጣት ነቢያት ዴሺ የተባለ የተለያዩ ቁሳቁሶች አስመጪ ኩባንያ ጄነራል ማናጀር ነው፡፡ ኤግዚብሽኑ ጥሩ መሆኑን የተናገረው ነቢያት፣ አሁን ከካታሎጉ ያገኘው ትንሽ ቢሆንም ምሪትና አገልግሎቶቹ በጣም ብዙ ስለሆኑ በሰጡት ሲዲ በኢ-ሜይል አድራሻቸው ሊያገናቸው አስቧል፡፡
አንተነህ የሚሰራው በኬሚካልና ላቦራቶሪ ዕቃዎች ላይ ነው፡፡ ወደ ኤግዚቢሽኑ የሄደው ጠቃሚ ነገር ባገኝ ብሎ ሲሆን ያያቸው ነገሮች ጥሩ መሆናቸውን ገልጿል፡፡ የእንግሊዝ ዕቃ ጥራት ያለው ስለሆነ ዋጋው ውድ እንደሚሆን ገምቷል፡፡ ውድ ቢሆኑም ጥንካሬና ረዥም ዕድሜ ስላላቸው አልጠላቸውም፡፡ የእኛ አገር ገበያ ያልለመዳቸው ቢሆኑም፣ ዝም ብሎ ከመተው ሊሞክራቸው አስቧል፡፡ ወደ ፊት ግንኙነቱ ሲፈጠር የበለጠ ጥሩ እንደሚሆን ተስፋ ሰንቋል፡፡
አብዲ ደጀኔ የሕክምና ባለሙያ ነው፡፡ ለመ/ቤቱም ሆነ ከዚያ ውጭ ጠቃሚ ምርትና አገልግሎት ባገኝ ብሎ ነው ወደ ኤግዚቡሽኑ የሄደው፡፡ አብዲ በሌሎች አገሮች ኤግዚቢሽን ተሳትፎ ያውቃል፡፡ ይህ ኤግዚብሽን በአገራችን የተለመደ ባይሆንም ብዙ ጠቃሚነገሮች እንዳገኘበትና ግንኙነቱ ሲፈጠር የበለጠ እንደሚሆን ተስፋ አለኝ ብሏል፡፡
የእንግሊዝ ኤክስፖርተሮች ወደ ውጭ የሚልኳቸው ምርቶችና አገልግሎቶች የቀረቡት በአካል ሳይሆን፤ ከ180 በላይ ኩባንያዎች የሚያመርቷቸው ከ100ሺህ በላይ ውጤቶችና የሚሰጧቸው አገልግሎቶች ምን እንደሆኑ ዝርዝር መግለጫ በያዘ ካታሎግ ነው፡፡
ኤግዚቢሽኑን የከፈቱት የኢንዱስትሪ ሚ/ሩ ክቡር አህመድ አብተውና በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ሚ/ር ግረጅ ዩሪ ሲሆኑ፤ በእንግሊዝ ኤክስፖርተሮችና በኢትዮጵያ የንግዱ ማህበረሰብ መካከል ግንኙነት፣ ትስስርና ሽርክና በመፍጠር መስራት የኤግዚቢሽኑ ዓላማ እንደሆነ አምባሳደሩ ተናግረዋል፡፡
የእንግሊዝ ባለሀብቶች፣ በኢትዮጵያ ኢንቨስት ማድረግ ውጤታማ እንደሆነ ተገንዝበው እንደ ዲያጐ ያሉና ሌሎችም ትላልቅ ኩባንያዎች ምርት መጀመራቸውን ጠቅሰው፣ አሁን በሚፈጠረው የንግድ ትስስር፣ ሌሎች በርካታ ባለሀብቶችም በኢትዮጵያ ኢንቨስት እንዲያደርጉ ለመሳብ መልካም አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል - አምባሳደሩ፡፡የእንግሊዝ ኩባንያዎች በእርሻ፣ በሆርቲካልቸር (አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ) በንግድ፣ በሕክምና፣ በጤና ክብካቤ፣ በኢንጂነሪንግ፣ በኦቶሞቲቭ፣ በኮንስትራክሽን፣ በኤሌክትሮኒክስ፣ በቤት ቁሳቁስ፣ በመሰረተ ልማት ግንባታ፣ በሆቴል ዕቃዎች አቅርቦት፣ በችርቻሮ ንግድ፣ በአላቂና የቅንጦት ዕቃዎች፣ ኃይል በማመንጨት፣ በውሃና ፍሳሽ፣ በከባድ መሳሪያዎች፣ በኢንቫይሮመንት፣ በማዕድን፣ በምግብና መጠጥ፣ በግንባታ መሳሪያዎችና ዕቃዎች፣ በእንስሳት ሕክምና፣ በትራንስፖርት፣ በመገናኛ፣ በጤናና ውበት፣… በአጠቃላይ ከ31 በሚበልጡ ዘርፎች ከኢትዮጵያውያን ጋር ተባብሮ ለመስራት ወኪልና አከፋፋይ እንደሚፈልጉ ታውቋል፡፡
ኤግዚቢሽኑን ያዘጋጁት ሱፐር ካቲክስና የእንግሊዝ ንግድ ኢንዱስትሪ ሲሆኑ፣ ሱፐር ካቲክስ በመላው ዓለም 122 የካታሎግ ኤግዚቢሽን አዘጋጅቶ 45ሺህ አዳዲስ የቢዝነስ ትብብሮች መፈጠሩን በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽኑን ያዘጋጅት የሱፐር ካቲክስ አባል ሚ/ር ጀምስ ኦ.ሱልቫን ገልፀዋል፡፡


በቅርቡ የፋይናንስ ኢንዱስትሪውን የተቀላቀለው እናት ባንክ፤ ወደ ሥራ በገባ የመጀመሪያው ዓመት ትርፋማ መሆኑን አስታወቀ፡፡
የዛሬ ሳምንት ባደረገው የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባኤ፣ የባንኩ የቦርድ ሊቀመንበር ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የባንኩን የ16 ወራት የሥራ አፈፃፀም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት፤ ባንኩ በመጀመሪያው ዓመት ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰቡንና ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር መስጠቱን ጠቅሰው፣ በአገሪቱ የባንኮች ታሪክ በመጀመሪያው የሥራ ዓመት ከፍተኛውን ተቀማጭ ገንዘብ ያሰባሰበ ባንክ ሊሆን እንደበቃ ገልፀዋል፡፡
ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት፣ እናት ባንክ አክሲዮን ማህበር 354.7 ሚሊዮን የተመዘገበ፣ 261.6 ሚሊዮን የተከፈለ ካፒታል እንዳለው በዓመታዊ ሪፖርቱ የተገለፀ ሲሆን ከ10,500 ከሚበልጡት ባለ አክሲዮኖች 63.4 በመቶው፣ ከ7,500 ደንበኞቹ መካከል ደግሞ 59 በመቶ ሴቶች መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡
በመጀመሪያው ዓመት የሥራ አፈፃፀም ከታክስ በፊት 38.5 ሚሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ አስመዘግቧል ያሉት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ወንድወሰን ተሾመ፤ የባንኩ ጠቅላላ ሀብት 1,417.3 ሚሊዮን ብር፣ ቅርንጫፎቻቸውም ዘጠኝ መሆናቸውን ጠቁመው በተያዘው የበጀት ዓመት ቅርንጫፎቹን 15 ለማድረስ እየሰሩ መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡
ለአጠራጣሪ ብድሮች መጠባበቂያ ከተቀነሰ በኋላ ባንኩ 33.42 ሚሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ያገኘ ሲሆን የተለያዩ ወጪዎች ተቀንሰውና ዋስትና ማቅረብ ለማይችሉ ሴቶች ባንኩ ሊሰጥ ላሰበው ብድር አንድ ሚሊየን ብር ከተቀመጠ በኋላ የተገኘውን የተጣራ ትርፍ 20, 031,028 ብር ለባለአክሲዮኖች 10 በመቶ ትርፍ አከፋፍሏል፡፡
እናት ባንክ የመሥራት አቅም እያላቸው ለብድር ዋስትና ማቅረብ ለማይችሉ ሴቶች፣ የገንዘብ ዋስትና ለማግኘት ባደረገው ጥረት፣ ከግለሰቦችና ከድርጅቶች 5.3 ሚሊዮን ብር ቃል ስለተገባለት ተጠቃሚ ሴቶችን በንግድ ሥራ አዋጪነት ጥናትና በሌሎች የባንኩ የብድር መስፈርቶች መሰረት እያወዳደረ ሲሆን በቅርቡ ለተመረጡ ሴቶች ብድሩን እንደሚሰጥ ተገልጿል፡፡
ባንኩ የሚሰጠውን አገልግሎት ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ ባለው እቅድ፣ መሰረት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ግኝቶችን በመጠቀም፣ የኮር ባንኪንግ አሰራር ለመጀመር ዝግጅቱን እንዳጠናቀቀና የበጀት ዓመቱ ከመገባደዱ በፊት በስራ ላይ ይውላል ተብሎ እንደሚጠበቅ የቦርድ ሊቀመንበሯ ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ገልፀዋል፡፡