በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የዓለም ስጋት በሆነው ኢቦላ ላይ ያተኮረ ህዝባዊ ውይይት የፊታችን ረቡዕ በግዮን ሆቴል ይካሄዳል፡፡
 የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚና የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር በጋራ ባዘጋጁት በዚህ ህዝባዊ ወይይት ላይ የኢቦላ ቫይረስ ምንነትና የመተላለፊያ መንገዶቹ እንዲሁም ስርጭቱ፣ ምልክቶቹ፣ የመጋለጫ መንገዶችና የቁጥጥር ዘዴዎቹን አስመልክቶ የጤና ባለሙያዎች ገለፃ እንደሚያደርጉ ታውቋል፡፡
የምዕራብ አፍሪካ አገራትን በተለይ ላይቤሪያና ሴራሊዮንን ክፉኛ ያጠቃው የኢቦላ ቫይረስ ወደ አገራችን እንዳልገባ ያስታወቀው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፤ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ  ላይ በሰዓት 1ሺ ሰዎችን መመርመር የሚያስችል ዘመናዊ መሣሪያ እንደተከተለና በድንበሮች አካባቢም ባለሙያዎች መድቦ ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን መግለጹ ይታወሳል፡፡

Published in ህብረተሰብ

ቁርስ አለመመገብ
ቁርሳቸውን የማይመገቡ ሰዎች በደማቸው ውስጥ የሚገኘው የስኳር መጠን ዝቅተኛ ይሆናል፡፡ ይህም ለአንጎል መድረስ ያለበትን ንጥረ ነገር በማስቀረት አንጎል በተገቢው ሁኔታ እንዳይሰራ ያደርገዋል፡፡
ከመጠን በላይ መመገብ
ከመጠን በላይ መመገብ የአንጎል የደም መተላለፊያ ቧንቧዎችን ያደድራቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ የአዕምሮን ኃይል ይቀንሳል፡፡
ማጨስ
ሲጋራ ወይንም ሌሎች አደገኛ ዕፆችን ማጨስ በርካታ የአንጐል ችግሮችን ከማስከተሉም ሌላ አልዚመር ለተባለ የአዕምሮ ህመም ሊያጋልጥም ይችላል፡፡
ከፍተኛ የስኳር ፍጆታ
ከፍተኛ የስኳር ፍጆታ፤ አንጎል ፕሮቲኖችንና የተለያዩ ንጥረ ነገሮችን በተገቢው ሁኔታ ጥቅም ላይ እንዳያውል ያሰናክላል፡፡ ይህም አንጎል አስፈላጊ ንጥረነገሮች እንዳያገኝ ያደርጋል፡፡
 ጭንቅላትን ተሸፋፍኖ መተኛት
በመኝታ ሰዓት ጭንቅላትን በአንሶላ፣ በፎጣ ወይም በብርድልብስ ተሸፋፍኖ መተኛት የካርቦንዳይኦክሳይድ ክምችትን ይፈጥራል፡፡ ይህም በአንጎላችን ውስጥ ያለውን የኦክስጅን ክምችት ይቀንሳል፡፡ በዚህ ምክንያትም አንጎላችን ለአደጋ ይጋለጣል፡፡

Published in ህብረተሰብ

“እሼ እዛው ነዋሪ ገበሬ ነው፡፡ ሞቅ ይለዋል! አንዱ ገንዘብ ሰጥቶ ምግብ በሳህን አርጎ ሂድ ወደሚስትህ ይለዋል፡፡
ይሄዳል፡፡ ግን በጨለማ በቀጭኑ ድንጋያማ የዘሙቴ መንገድ ሲሄድ ገንዘቡ ይጠፋዋል፡፡ ሳህኑን መሬት አስቀምጦ ገንዘብ
ፍለጋ ይመለሳል፡፡ ገንዘቡ የለም፡፡

     ታሪኩ የተባለው የማህበሩ አባል ቡታጅራ አካባቢ ሌላ የጉራጌ በዓል አክብሮ ስንትና ስንት ኪሜ ብቻውን ነድቶ ዘሙቴ መጣ፡፡ ጉድ ተባለ! ለጥቂት ወራት ጀርመን ከርሞ የመጣ ነው፡፡ ለመስዋዕትነቱ ሁሉም አድናቆቱን ችሮታል! እጅግ ሞቅ ያለ ወንድማዊ አቀባበል ነው የተደረገለት! ቤቱ በብርሃናማ ፊቶች ተጥለቀለቀ፡፡ ታሪኩን፤ የዘሙቴ መንፈስ ኃይሉ የሳበው ይመስለኛል፡፡
ባለፈው ሳምንት ህይወታቸው ማለፉን የነገርኳችሁ አቶ ጃቢር ቱፈር ይህን ነበር ያሉኝ፡፡
“በየት ነው የሚሄዱት?”
“በቡታጅራ በኩል በዝዋይ ነው የምሄደው”
“ወዴት? ወደ አዋሳ ነው የሚሄዱ?”
“የለም ለኩ ነኝ! ከአዋሳ አልፋለሁ፡፡”
“በዓመት ነው የሚመጡት ማለት ነው?”
“አዎን - አዎ!”
“ስለዘሙቴ ማርያም ልጽፍ ነው” አልኳቸው፡፡
“ይባርክህ፡፡ የዘሙቴ አምላክ ይርዳህ፡፡ እኛንም የዓመት ሰው ይበለን - የዛሬ ዓመትም እንዳትቀር! ትውልድ እንዳይረሳ አድርጉ … እኔ ታደሰ ተክሌን ሁለት ኣመት እበልጠዋለሁ፡፡ ታሟል በጣም - እግዚአብሔር ይማረው፡፡” (የሰው ህይወት ይገርማል! አቶ ታደሰ በህይወት አሉ፡፡ እኒህኛው አለፉ ምን ይደረግ፡፡ ሁን ያላለው አይሆን!) ድምፃቸው እንዴት ጠንካራ፣ አካላቸው እንዴት ቀልጣፋ፣ እንደነበር አሁንም ይታወሰኛል (ነብሳቸውን ይማር ፈጣሪ!)
ልጃቸው መጥቶ እንሂድ ሲላቸው ተሰነባበትን!
ማታ የጉራጌ ጭፈራ ውድድር ተካሂዷል፡፡ በአብነት አጎናፍር ዘፈን ዳንስ ቀልጧል፡፡ ጤናዬና ታከለ፤ የእኔን አዲሱን መፅሀፍ “ስውር ስፌትን” ተሸልመዋል፡፡ የሚደንቅ ሞቅታና ድባብ ነበረው፡፡ ከምፕ ፋየር እንዳናደርግ ዝናብ ገቶን ነው ቤት ያረግነው፡፡
“ምን ያል ጭፈራ ነው፣ ይሄ ጉራጊኛ
መለየት አቃተን ዳንሱን ከዳንሰኛ!” አሰኝቶኛል፡፡
የማህበሩ አባላት መንፈስ
የማህበሩ አባላት፣ ደስታ፣ ፈንጠዝያ፣ ጨዋታ ይችላሉ፡፡ እርስ በርስ ሲተራረቡ በሳቅ ይገላሉ፡፡ ካርታ ሲጫወቱ ያለው ቀልድ የሚደንቅ ነው - ይህን ተገርሜ ሳይ አንዱ ወዳጄ ምን አለኝ መሰላችሁ?
“አንዱ በካርታ ጨዋታ 500 ብር በልቶ ይፎክራል፡፡ ሌላው 2500 ብር የበላ ምንም የማይናገር ደሞ አለ፡፡
 ይህን ያየ ተራቢ “ፍየል አንድ ስትወልድ ጩኸቷ አገር ያስለቅቃል፡፡ አሳማ ግን መአት ስትወልድ ድምጿ አይሰማም!!” አለ፡፡
አንደኛው በጣም ዘና የሚያደርጋቸው ተራቢ አባል ካርታ ሊዘጋ ሲል ብድግ ይልና ጮክ ብሎ እንደሬስሊንግ አጫዋች “This is 500 kg from East Africa Ethiopia” ይልና ያሸነፈበትን ካርታ ጠረጴዛ ላይ ያነጥፈዋል፡፡ ካርታውን ስከታተል፤ ስለ እሼ ያወራሉ፡፡
“እሼ እዛው ነዋሪ ገበሬ ነው፡፡ ሞቅ ይለዋል! አንዱ ገንዘብ ሰጥቶ ምግብ በሳህን አርጎ ሂድ ወደሚስትህ ይለዋል፡፡ ይሄዳል፡፡ ግን በጨለማ በቀጭኑ ድንጋያማ የዘሙቴ መንገድ ሲሄድ ገንዘቡ ይጠፋዋል፡፡ ሳህኑን መሬት አስቀምጦ ገንዘብ ፍለጋ ይመለሳል፡፡ ገንዘቡ የለም፡፡
ሲመለስ ሳህኑን የት እንዳደረገው ያጣዋል፡፡ ቡድኑ በሙሉ በሱ ሁለት - አጣነት ጠዋት እንደጉድ ሲስቅ ያረፋፍዳል፡፡
ቀልደኛው፤ ካርታው ተጫዋች እየተጫወተ፣ ቀልድ ማውራት ልማዱ ነው - አሁንም ይቀልዳል፡፡
“Lack of money, lack of power ካለብህ skill ለማውጣት very hard ይላል፡፡ (ገንዘብም ሀይልም ከሌለህ ክህሎት አይኖርህም ማለቱ መሰለኝ) ይቀጥልና “እዚህ አገር የሚሰራው ሰው በጣም small ነው፡፡ እኛ ብቻ ነን የምንሠራው፡፡ ሌላው ተረት ብቻ ነው!”
“You know shit ነው! Shit is not አንሶላ! ገባችሁ?”
እንዲሁ ሲከራከር ሲሟገት የሚያድርም አጋጥሞኛል፡፡ ክርክርን እንደሱስ የሚይዙ ሰዎች እንዳሉ ተረድቻለሁ፡፡ ግን እንደጨዋታው ይረኩበታል፡፡ “ገባህ ወይስ ግራ ገባህ” ይላል ተናግሮ ተናግሮ፡፡
ካርታ ከሚጫወቱት ዙሪያ ያለው ቀልድ ይገርማል፡፡ “ዳያስፖራ” የሚባል የቅፅል ስም ያለው ከአሜሪካ የመጣ የማህበሩ አባል አለ፡፡ ካርታ ተበልቶ ተኛ!
ይሄኔ ያ ተረበኛ፤ “በዓለም ላይ በፋይናንስ እጥረት የተኛ የመጀመሪያ ዳያስፖራ አንተ ብቻ ነህ!” አለው፡፡ ዳያስፖራው በእልህ ብድግ ብሎ” እሺ ዶላር ወይም ዩሮ የሚመነዝረኝ አለ ልብ ያለው?!” አለ፡፡ ከዚያ 1200፣ 1400፣ እያሉ ቀለዱበት፡፡ ዋጋ አዋደቁበት!
ተረበኛው ይቀጥላል፡- “ማንም ሰው በ14 ዓመቱ ውጪ ካደረ ቁማርተኛ ነው የሚሆነው” ብሏል አርስቶትል፡፡ አንደበተ - ቀልጣፎችም አሉ፡፡ አንዱ ተናጋሪ አንዱን ሲገልፀው “ዕድሜው 65፣ ኪሎው 67 ነው፤ ጸሐይ መሞቅ ይወዳል፡፡
 ጆሮው አይሰማም፣ ቀዝቃዛ ነገር አይወድም፣ የሚበላውንና የሚጠጣውን አይመርጥም፡፡
ኪሎውን በየቦታው ይለካል …” ይለዋል፡፡ ደራሲ ከሚፈጥረው ባህሪ የላቀ አተራረብ ነው ያላቸው፡፡
ዘሙቴ ማርያም መዝናናት፣ መንፈሳዊነት፣ ክትፎ፣ አይቤ፣ ጎመን፣ ኖርማል ጎመን፣ ቅቅል (እንዲህ የሚጥም ቅቅል በልቼ የማቅ አልመሰለኝም) ማስቀደስ፣ መፀለይ፣ መመራረቅ … የጉራጌ አገር መስቀል ጧትም፣ ምሳም፣ ራትም ክትፎ መጠጣት ይመስለኝ ነበር፡፡ አይደለም! እንዲያውም እርካታው ልዩ ልዩ ምግብ መቅረቡ ነው! ከሁሉ የሚበልጠው ግን ፍቅሩና የደስታው መንፈስ ነው፡፡ ምግቡማ አዲሳባም አለ፡፡
የዚያን መንፈስ ኃይል ለመለካት አይቻልም፡፡ ከተፈጥሮ የፈለቀ ነው፡፡ ተፈጥሮ የሚያሰርጽብን መንፈስ ነውና ተፈጥሮ ጋ በመሄድ ብቻ የሚገኝ ነው!
በክትፎው ፏፏቴ መሀል ስለበዓሉ የጠየኳቸው አንድ መምህር ስለዘሙቴ ማርያምና ክብረበዓሉ ያለኝ መንፈሱን ያጠናክረዋል፡፡
“የእመቤታችን የቅድስተ-ቅዱሳን ድንግል ማሪያም በዓል ነው፡፡ ዕጥፍ-ድርብ ከመስቀል ጋር መገናኘቱ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ለመስቀል ልዩ ቦታ አለን፡፡
ኢትዮጵያ በመፅሀፍ ቅዱስ 42 ጊዜ ተፅፋለች፡፡ ዋናው ግማደ-መስቀሉ ግሸን ማርያም እዚሁ አለ፡፡ ፅላቱም እዚሁ አለ፡፡ ጌታችን እየሱስ ክርስቶስ ሲሰቀል እመቤታችንን ከዮሐንስ ጋር ያስተሳሰረበት ዕለት ነው፡፡ የማሪያም መንፈስ እዚህጋ አለልህ!... የዘሙቴ ፀጋም እዚህ አለ፡፡
“እግዜሃር መኖሩ በፍጥረቱ ስለፍጥረቱ” ይታወቃል - ያለው ነው ሃዋርያው ጳውሎስ…” የአቶ አበበ ወልደማርያም ግቢ መንፈስ፣ ሁሉን በፍቅር ያስተሳሰረ፣ ሁሉን በሰላም ያቆራኘ፣ ይህ ወሰንህ ይህ ዲካህ የማይባል፣ በአዘቦት ሰው መለኪያ የማይሰፈር ነው፡፡
እንዲያው በረከት ነው፡፡ እንዲያው ፀጋ ነው፡፡ ከዓመት ዓመት ሁሉን በየፍላጎቱ ዙሪያ ያቀፈ መንፈስ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እኔን ከነዚህ ወዳጆቼ ያቆራኘን ዕፁብ መንፈስ ነው፡፡ ለአቶ አበበ፣ ለልጆቻቸው ለልጅ ልጆቻቸው እንዲሁም ለዘሙቴ ወዳጆች “ኬር!” ይሁን!!  
ስንመለስ ልክ ባለእግዚሃር ጋ መኪናችን ተበላሸ፡፡ እዛው ቦታ ሚኒባስ ባጋጣሚ መጣች፡፡ ተኮናተርናት፡፡ መኪናችንን ለመስራት እንዳረፍን እዛው አጠገብ ጣሳ ባጠና ላይ አየን፡፡ “አረቄ!” ካቲካላ አለ ማለት ነው፡፡
ተፈጥሮ ሁሉ ቦታ አማኙን አይረሳም፡፡ ኮመኮምነው፡፡ ዘሙቴ የጋበዘችኝ የወጪ መሆኑ ነው!! “ኬር” ብላ ሸኘችን ዘሙቴ!!



Published in ባህል
Saturday, 15 November 2014 10:52

ነፃ ገበያ ይለምልም!

ለምን መሰላችሁ ነፃ ገበያን ያወደስኩት? በእኛ አገር “ጨመረ” እንጂ “ቀነስ” የሚባል ነገር ጠፍቶ፣ “ቀነሰ” የሚለው ቃል ካልጠቀመን ምን ያደርግልናል? ከመዝገበ ቃላት ይፋቅልን! በምንልበት ጊዜ የቀነሰ ነገር በማየቴ ነው፡፡
ባለፈው ሰሞን፣ ዘመድ ሞቶብኝ በተለምዶ ዓለም ባንክ እየተባለ የሚጠራው አካባቢ ነበርኩ፡፡ ከቀብር መልስ ውሃ ጥም ሲያቃጥለኝ፣ አንድ ቢራ ልጠጣ ብዬ ግሮሰሪ ቤት ገባሁ፡፡ የምመርጠውን ቢራ ስጠይቅ “አለ” ተባልኩ፡፡ አካባቢው ሩቅ በመሆኑ ዋጋው ይጨምራል በማለት ሰግቼ “ስንት ነው?” አልኩ፡፡ አስተናጋጁ “12 ብር” አለኝ፡፡ መኻል ከተማ ከ13-16 የሚሸጠው ቢራ፣ እዚያ በ12 ብር መገኘቱ እያስገረመኝ ጠጥቼ ወጣሁ፡፡ በሳልስቱም ወደለመድኩት ቤት አመራሁ፡፡ ሁሉም ሰው ፊቱ ያስቀመጠው አዲሱን ቢራ ነው፡፡ የለመድኩትን ቢራ ጠየቅሁ፡፡ የለም ተባልኩ፡፡ ሌላ ቢራ ምን እንዳለ ስጠይቅ፤ አስተናጋጁ ሰዎች ፊት ያለውን እያሳየኝ “ከዚህ በስተቀር ምንም የለም” አለኝ፡፡ ዋጋውን ጠየቅሁ፡፡ 10 ብር አለኝ፡፡ ሌላ አካባቢ 12 እና 13 ብር የሚሸጡ ስላሉ፣ እየተገረምኩ ጠጥቼ ወጣሁ፡፡
በሌላ ጊዜ ደግሞ የረር-ጎሮ አካባቢ ነበርኩ፡፡ የምወደውን ቢራ ስጠይቅ አስተናጋጁ “እሱ የለም፤ ይኼን ይጠጡ ጥሩ ነው” አለኝ፡፡ ችግሬ ዋጋው ላይ ነውና “ስንት ነው?” አልኩት፡፡ “10 ብር ነው፡፡ ፋብሪካው‘ኮ  ከዚህ አስበልጠን እንዳንሸጥ አስጠንቅቆናል” አለኝ፡፡ የቢራውን ዋጋ የቀነሰው - ፋብሪካው መሆኑን ስሰማ፣ አዲሱ ቢራ ገበያ ውስጥ ለመግባት የቀየሰው ዘዴ ነው በማለት ደስ አለኝ፡፡
ሰሞኑን ደግሞ ሌላ አስገራሚ ነገር አየሁ፡፡ ቢጂአይ (ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ) አርማውን በያዘ ወረቀት ላይ የድራፍት ብርጭቆ እያሳየ ማክሰኞ፣ ሐሙስ፣ ቅዳሜ “Happy Hour” በማለት በየመጠጥ ቤቱ ለጥፎ አየሁ፡፡ እኔ ጊዮርጊስ ቢራም ሆነ ድራፍት ባልጠጣም የንግድ ውድድር የፈጠረው ነው በማለት በጣም ደስ አለኝ፡፡ ድራፍቱ፣ ከሆነ ጊዜ በፊት ዋጋ ጨምሮ ጃንቦው 11 ብር እየተሸጠ ነው፡፡ አሁን ማክሰኞ፣ ሐሙስና ቅዳሜ 3ብር ቀንሶ በ8 መሸጥ ጀምሯል፡፡
ጊዮርጊሶች በአንድ ጊዜ 3ብር የቀነሱት፣ ደንበኞቹ በ10 ብር ወዳገኙት አዲስ ቢራ ስላዘነበሉ ጭራሽ እንዳይሸሹት ለማባበል ነው የሚል ግምት አደረብኝ፡፡ ወደፊትም ወደ ገበያው አዳዲስ ቢራ ፋብሪካዎች ሲገቡ የንግድ ውድድሩ ይጦፋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ በዚህ የንግድ ውድድር ማን ተጠቀመ? ሸማቹ ህብረተሰብ፡፡ ለዚህ ነው ነፃ ገበያ ይለምልም ያልኩት፡፡ 

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 15 November 2014 10:50

ኒቼ እና እኛ

        ቀዬውን ጥሎ ከተራራ ላይ ከመሸገ አመታት ተቆጥረዋል፡፡ ዛሬ ከምሽጉ ጋር ሰማኒያ ለመቅደድ የቆረጠበት ቀን ነው፡፡ ድንገት የስደት ባልንጀራውን ተራራውን ወደ ኋላ ጥሎ ቁልቁል ወደ ሰፊው መስክ ለመውረድ ተንደረደረ፡፡ ጥቂት ኪሎ ሜትሮችን ፈቀቅ እንዳለ፣ ቀዝቃዛው ንፋስ የሰዎችን ሁካታ እየቆነጠረ ከጆሮ ላይ ብትን ሲያደርግበት ተሰማው፡፡ ጠደፍ ጠደፍ እያለ ደረቱን የገለበጠውን አውላላ ሜዳ ከሩጫ ባልተናነሰ እርምጃ እንደ አጋመሰ በሰዎች ሁካታ ድብልቅልቅ ያለ የደራ ገበያ አገኘ፡፡ ገበያተኛው ይህንን ጸጉረ ልውጥ ልብ አላለውም፡፡ ከእዚህ ይልቅ አስማታዊ ትርኢት ለሚያሳየው አርቲስት ሁለመናውን ሰጥቷል፡፡ ጸጉረ ልውጡ ሰው ወደ ተሰብሳቢው ገበያተኛ ተጠጋና ይህንን አዋጅ ተናገረ፡-
“እዚህ እናንተ ዘንድ የተገኘሁት ከሰመመናችሁና ከድንዛዜያችሁ ትነቁ ዘንድ ጠቃሚ ዲስኩር ሹክ ልላችሁ ነው፡፡ የዲስኩሩ አርእስት ልዕለ ሰው ይባላል፡፡ ጆሮ ያለህ ስማ .. ጆሮ ያለህ ስማ …” አለ ድምጹን ከገበያው ሁኡካታ በላይ ከፍ ለማድረግ የአቅሙን እየተውተረተረ፡፡
ለእዚህ መጤ መንገደኛ ጆሮውን ያዋሰ አንድም ገበያተኛ አልነበረም፡፡ ሁሉም እንደ ለፍላፊ ወፈፌ በመቁጠር ወደ ጉዳዩ  ተመለሰ፡፡
ይህ መጤ ነብይ፣ ይህ የብዙሀን ጆሮን የተነፈገ ብጹሁ የኒቼ ዛራስቱስራ ነው፡፡ ፍሬደሪክ ኒቼ የሰው ልጅህ በመንፈሳዊ ጉስቁልና ተቀፍድዶ አበሳውን የሚያይ አሳዛኝ ፍጡር እንደሆነ ይናገራል፤ ስለዚህም ነው ብስራት አብሳሪውን፣ የንቃት ባልደራሱን ዛራስቱስራን እየደጋገመ የሚያውጅልን፡፡ የሰው ልጅ ካለበት ድቅድቅ ጨለማ ወደ ንቃት ጸሃይ ይወጣ ዘንድ ዛራስቱስራ በነብይነት የግድ መከሰት አለበት፡፡ ኒቼ የምናብ አብራክ ክፋዩን ዛራስቱስራን፣ መንፈሳዊ አዳኛችን አድርገን እንድንቀበለው በጥበብ እያዋዛ ሊሸነግለን ይሞክራል፡፡
የኒቼን ፍልስፍና ውስጠ ምስጢር በፈለፈልን ቁጥር ተመዘው ከማያልቁ ስነልቦናዊና ማህበራዊ ገበናዎች ጋር ፊት ለፊት መላተማችን አይቀሬ ነው፡፡ ፈላስፋው፤ ዛራስቱስራ የተባለውን ብጹህ ስብእናን ሲያስተዋውቀን እግረ መንገዱን የስነልቦና እርከኖቻችንን ጎሸም አድርጎ ያልፋል፡፡ በኒቼ አመለካከት የሰው ልጅ ሶስት የእድገት እርከን አለው፡፡ የመጀመሪያው ካሜል እስቴጅ ይባላል፡፡ በግመል ተፈጥሮ ብዙ ማጠራቀም ወይም ማከማቸት እንደ አንድ የስሜት ህዋስ ነው የሚቆጠረው፡፡ አንዲት ግመል አንዴ የጠጣችውን ውሃ እስከ ስድስት ወር ልትጠቀምበት ትችላለች፡፡ በእዚህ እርከን ላይ ያለ ሰው ልክ እንደ ግመሏ የማህበረሰቡን ባህል፣ እምነት፣ አመለካከት ብሎም የአኗኗር ዘይቤን እንደ ወረደ በውስጡ እያከማቸ የሚያመነዥግ ግብዝ ይሆናል፡፡ በእዚህ ሰውዬ መቃብር ላይ ሊነበብ የሚገባው መልእክት ይህ ነው፡-
“ከርሴ ተጭኖኝ ወደ ከርሰ ምድር ወርጃለሁኝ”
ሁለተኛው እርከን ላየን ስቴጅ ነው፤ ስለ አንበሳ ስናስብ ቁጡ ባህሪው፣ አልገዛም ባይነቱና ነውጠኛነቱ ውልብ ይልብናል፡፡ ይህኛውን እርከን የሚቆናጠጥ ሰው በድራጎን ከተመሰለው የማህበረሰብ አመለካከትና አገዛዝ ስርዓት ጋር ፊት ለፊት ይላተማል፡፡ በእዚህም ምክንያት  ብዙ ውክቢያና እንግልት ይደርስበታል፡፡ አሟሟቱ ከካሜል እስቴጅ ጋር ሲነጻጸር የጀግና ነው፡፡ እዚህኛው ሰው መቃብር ላይ ቃላት ሲደረደር ይሄንን ይመስላል፡-
አጥንቴም ይከስከስ ደሜም ይፍሰስላት
የማንም አይደለች ይህች ነፍስ የእኔ ናት
ወደ ሶስተኛው ደረጃ ስናልፍ ቻይልድ ስቴጅን እናገኛለን፡፡ ህጻናት በእምነቱም ሆነ በሳይንሳዊው ዓለም ያላቸው ተክለ አቋም አንድ አይነት ነው፡፡ የህጻናት ቤተመቅደስ ፍቅር እና ሰላም ነው፡፡ ወደ እዚህኛው ደረጃ የተሰቀለ ሰው ውስጡንም ሆነ አካባቢውን በቅድስና ይባርካል፡፡ ድንኮች ከሚበዙበት ግርግር መካከል ዘለግ ብሎ ይስተዋላል፡፡ መቃብሩ ላይ ቃላት ተሰካክተው ሲቆሙ ይህንን አይነት ቅርጽ ይይዛሉ፡-
“ህጻናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው ብለህ ባዘዝከው መሰረት ወደ አንተ መጥቻለሁኝ”
እኛነታችን እና ሶስቱ እርከኖች እንዲህ ተዛምደዋል፡-
ካሜል ምሁር
በግመል ልቦና ውስጥ ሁሉ ነገር አራት ነጥብ … ተከርቸም … ነው፤ ለፈጠራ ለመመራመር ከፍት የሆነ ስነልቦና ይነጥፋል፤ ግራ ቀኝ ከማያማትር እንደ ጋሪ ፈረስ ፊት ለፊቱን ከሚሸመጥጥ ግትር ስብእና ጋር ይወዳጃል፤ ሳይጠይቁ መቀበል፣ ሳይፈትሹ ማጥለቅ፣ ሳያላምጡ መዋጥ የግመል እስትንፋስ ነው፡፡
ኒቼ የዘር አጥር ሳይቸክል ለሰው ልጅ በሙሉ ያወጀውን የግመል ስብእናን ለመሰለል ስንነሳ፣ የእውቀት ባህላችንን ገበና መታዘብ እንጀምራለን፡፡ ግመል እና የእውቀት ባህላችን አንድ ሳምባን ነው የሚጋሩት፤ መሳ ለመሳ ኩታገጠም ስብእናዎች ናቸው፡፡ እንደ ግመሏ ብዙ ስናቁር፣ ስናከማች፣ ስንደራርብ የደህንነት ስሜት ይሰማናል፡፡ መጠየቅ፣ መገዳደር፣ ማፈንገጥ ከእውቀት መዘገበ ቃላታችን ላይ ተፍቀው ጠፍተዋል፡፡
የትምህርት ተቋሞቻችንም ቢሆኑ ይህንን የማቆር ግብር ከትውልድ ትውልድ እንዲሻገር ላይ ታች ከማለት አሰልሰው አያውቁም፡፡ እውቀትን እንደ መነባንብ ቃል በቃል ከመደጋገም ጋር የሚተካከል የተኮላሸ ስነልቦና በመዝራት የማይተካ ሚና ሲጫወቱ ኖረዋል፡፡ በተቋማቱ ውስጥ ያለፉ ደብተራ ሊህቃን እውቀት ማለት እንደወረደ የሚጠለቅ፣ እንደ ድግምት የሚደገም፣ መጠይቅን የሚያኮላሽ፣ እንደ ምፅአት ቀን የሚሰበክ፣ ከንፈር እየመጠጡ ጭንቅላትን እየወዘወዙ የሚደመጥ ብቻ እንደሆነ ለዘመናት ተሳስተው እያሳሳቱን ዛሬ ላይ አድርሰውናል፡፡ በእዚህም ምክንያት የእውቀት ምድረ በዳ ላይ የምንርመሰመስ ካሜል ምሁራን እንድንሆን ተፈረደብን፡፡ እኛም ትውልድ ለማስቀጠል መሃላችንን ላለማጠፍ መሰሎቻችንን ካሜል ምሁራንን ላይ ታች ብለን ለማብዛት ወገባችንን ሸብ ማድረጋችንን ተያያዝነው፡፡
በእርግጥ ካሜል ምሁራንን በማቆር ግብራቸው ብቻ አንኮንናቸውም፡፡ ማቆር በራሱ አጥፊ አይደለም፤ ማቆር እንደውም በሰው ልጅ እና እንስሳት መካከል ጠቃሚ ግንብ በመገተር ትልቅ ሚና ይጫወታል፡፡ ዛሬ የተወለደች ድመት ከዛሬ አንድ ሺ አመት በፊት ከተወለደች ድመት ጋር በአስተሳሰብ አንድ አይነት ነች፤ የዛሬዋ ድመት ከዜሮ ነው የምትጀምረው፣ ከእዚህ ቀደም ከነበረው የድመት ማህበረሰብ ምንም አይነት ተሞክሮ እና ልምድ ቀስማ የዛሬውን ህይወቷን አትጀምርም፡፡ እኛ ግን በእዚህ ረገድ ለማቆር ምስጋና ይግባውና በተጻራሪ ጽንፍ ላይ መቆም ችለናል፡፡ ከባዶ፣ ከዜሮ አንጀምርም፡፡ ካቆርነው መሰረት አሀዱ እንላለን፡፡
ስለዚህ ማከማቸት፣ መከመር በራሱ መርገምት አይሆንም፡፡ ወደፊት ለመስፈንጠር እንደ መነሻ ንጣፍ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ችግሩ የሚመጣው የቃረምነውን እውቀት እንደ ሃይማኖት መቁጠራችን ላይ ነው፡፡ መተቸት ኩነኔ እየሆነብን፣ በአእምሯችን ያከማቸነውን እውቀት እንደ ድግምት እየደገምን፣ እንዴት የተለየ የፈጠራ ሰው ልንሆን እንችላለን፡፡
ላየን ማህበረሰብ
አንበሳ የእኛ ኢትዮጵያውያን የመንፈስ ጥንካሬ መግለጫ ነው፡፡ ነጭ፣ በበርሊን ሸንጎ ጥቁር ህዝብን በግዞት ለማኖር ምሎ ተገዝቶ አፍሪካ ላይ ሲዘምት፣ ፊት ለፊት በብቸኝነት የተፋለሙት አባቶቻችን ሁልጊዜም በታሪክ የሚዘከሩ ህያው ምስክሮች ናቸው፡፡ አልበገር ባይነታቸው፣ የአላማ ጽናታቸው የጥቁር ህዝብ ለደረሰበት የልብ ስብራት ጠጋኝ ሆኖ ኖሯል፡፡ በእዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ የሚለው ቃል፣ ከቃል በላይ ሆኖ የመንፈስ ጥንካሬንና ሀይማኖታችን እስከ መወከል ይደርሳል፡፡
ግራ አጋቢ አመክንዮ ላይ የምንደርሰው ግን አንበሳውን ወደ ቤታችን ስናመጣው ነው፡፡ አንበሳው በቤቱ ጭምት መሆንን ይመርጣል፡፡ ለወንዙ ለአድባሩ ለማዳ ባህሪውን ከመጋበዝ አይቦዝንም፡፡ ለውጪ ቀጋ ለውስጥ አልጋነቱን በግብሩ ይመሰክራል፡፡ አንበሳው ዱካ ከእንደራሴዎቻችን ፊት ባይተዋር ነው፡፡
የእኛው አፈር ያበቀላቸውን ገዢዎቻችንን እንደ ባእድ ጸጉረ ልውጦቹ በግሳታችን፣ በጩኸታችን ለማስበርገግ ጎሬያችንን ለመክፈት ስንዳዳ አካላችን አልታዘዝ ይለናል፡፡ ከማጉረምረም ይልቅ እጣ ፈንታ ላይ በማላከክ ከንፈር እየመጠጡ ማዝገምን ምርጫችን እናደርጋለን፡፡ ከፍ ዝቅ ለሚያደርጉን እንደራሴዎቻችን ሆደ ሰፊ የምንሆንበት ወሰን በእጅጉ የተጋነነ ነው፡፡
እዚህ ጋ የሰጎኗን ታሪክ ማንሳት ተገቢ ነው፤ ሰጎን በበረሃ ውስጥ ሊበላት የመጣን አውሬ እንዳመለጠችው የምታስበው ጭንቅላቷን፣ አሸዋ ውስጥ በመቅበር ነው፤ አውሬው ጥፍሩን እየሳለ ጥርሱን እያንቀጫቀጨ ከአጠገቧ ደርሶ ሰጎን ሆዬ አውሬውን ስላላየችው ብቻ ከመበላት እንደምትተርፍ ከአጓጉል ድምዳሜ ላይ ትወድቃለች፡፡
ሆደ ሰፊነቱ በዋለ ባደረ ቁጥር እኛም በሰጎኗ መላ ምት ከመደባበስ አንተርፍም፤ ገራገሩ መላ ምት አቅላችንን እንደ መርግ ተጭኖ ድብታውን ያበዛብናል፡፡ አንበሳውን ስብእናችንን ለጉሞ የበይ ተመልካች እንድንሆን ይፈርድብናል፡፡
ቻይልድ መሪ
የጥንቱ የጠዋቱ ግመል በጊዜ ሂደት ጥፍርና ጥርስ አብቅሎ ከአገኘው ጋር የሚላተም ነውጠኛ አውሬ ሆኖ ነበር፡፡ አውሬውም ጊዜው አለፈበትና ከንቃት ከፍታ ላይ ተሰቅሎ የነውጡን አለም ለአፍታ ከሰለለ በኋላ ሰላምና ፍቅር ወደ ሚፈነጩበት ኤደን ገነት ከተመ፡፡ የጨቀየውን የነውጥ አለም ክፉኛ ተጠየፈው፡፡
አሁን የሚናከሰው የሚያቆስለው አንበሳ ወደ ሰላማዊ ህጻን ተቀይሯል፡፡ ስለታም ጥፍሮቹ እንደ ሀር ለሚለሰልሱ መዳፎች ቦታቸውን አስረክበዋል፡፡ መዳፎቹን የነካ በሙሉ ከቅድስናቸው በረከት ይቋደሳል፡፡ አድሎዎና መድሎዎ የመዳፎቹ ደመኛ ጠላት ናቸው፡፡ ጡቻና ሀይል በፍቅር እዝ ምርኮ ስር ይወድቃሉ፡፡ የመዳፎቹ ጠረን እንደ ሰባሰገል እጣን በመልካም መአዛ ያውዳል፡፡
በእዚህ ደረጃ ላይ ያሉ ሰዎች በማህበረሰቡ ውስጥ ቢበዙ ፍርድ ቤቶች ስራ ይፈታሉ፡፡ የህግ ሙያ አዋጪ የስራ መስክ መሆኑ ይቀራል፡፡
በታሪክ በጣም ውስጥ በሆኑ አጋጣሚዎች ራሳቸውን ለህዝባቸው ክብርና ነጻነት አሳልፈው የሰጡ ብጹህ ህጻናት በሁሉም የአለማችን ጥግ ተስተናግደው አልፈዋል፡፡ ጋንዲ፣ ማንዴላ፣ ማርቲን ሉተር ኪንግ እያልን መዘርዘር እንችላለን፡፡ እነዚህ ሙሉ በሙሉ በህጻናት ካምፕ ውስጥ የተፈጠሩ ስብእናዎች ነበሩ፡፡ ህጻናት አለምን የሚተረጉምበት መዝገበ ቃላት ከብዙሃኑ ጋር አይገጥምም፡፡ በናዚ ጭፍጨፋ ወቅት አንድ ታሳሪ አይሁዳዊ የተናገረው ፍሬ ነገር የጨቅላ ማህበረሰብን ይወክላል፡-
“በእርግጥ የእናንተ እስር ስጋዬን መሸበብ ይቻለው ይሆናል፡፡ በእርግጥ የእናንተ ጎራዴ ጭንቅላቴንና አካሌና መቆራረጥ ይቻለው ይሆናል፡፡ ነገር ግን ነፍሴን ሊሸራርፏት አይችሉም፡፡ ነፍሴ ከአደጋና ከበትር የራቀች ናት” ብሎ ነበር፡፡ በህጻናት አይን እስር ቤት እንዲህ ከፍ ያለ ትርጉም አለው፡፡ በእዚህ መሰሉ ፈተና ውስጥ ሆነው እንኳን የብርሃናቸው ጸዳል ለእልፍ አዕላፍ ይተርፋል፡፡ እነርሱ የሚያዩትን ብርሃን ብዙሃኑ እንደ ድቅድቅ ጨለማ ነው የሚቆጥረው፡፡ ስራቸው በሙሉ ከተራው ሰው ጋር አይገጥምም፡፡
እኛም በታሪካችን ብጹህ ህጻን አላጣንም፡፡
“ህዝቤ በባእድ ሀይል እንደ በግ እንዲነዳ ተባባሪ አልሆንም፣ ከእኔ ህይወት የሀገሬ ነጻነት ይበልጥብኛል፣ ሞትን ቀድሜ ሞቼ አቸንፌዋለሁ፤ የህዝብ ልእልና ከእኔ ስጋ ልእልና ጋር ለየቅል ነው፤ ህዝብ ይዳን ስጋዬ ይቀበር” ብለው ለህዝባቸው ክብር ጭዳ የሆኑት ታላቁ አቡነ ጴጥሮስ ህያው ተምሳሌታችን ናቸው፡፡
የእኛን ቻይልድ መሪ በአቡነ ጴጥሮስ ስብእና ውስጥ እናገኘዋለን፤ ጎተራውን ሙሉ ለማድረግ እጅ የማያጥረው፣ ተድላና ፍስሃን በየማጀቱ የሚረጭ፣ ፍትህና መብትን የማያጎድል፣ እንደ ገራገር አባት ራሳችንን በፍቅር የሚደባብስ፣ እንደ ሻማ ቀልጦ እኛን ለማኖር ፊት ለፊት የሚሰለፍ ሰማእት … የእኛ ህጻን … የእኛ … ብጹህ … የእኛ … አቡነ ጴጥሮስ …. ነው፡፡  
ህፃናትን ያብዛልን!!

Published in ህብረተሰብ

ካለፈው የቀጠለ    -


“ለብቻ አሪፍነት የለም፤” አብረን እንሥራ፣ አብረን እንደግ!
***
“የዘመኑ ወጣት ራሱ ከነገር፣ ምላሱ ከሱስ፣ እጁ ከፌስ-ቡክ ቢላቀቅ፤ ትልቅ ሥራ እንፈጽማለን”
ከአዲሳባ ደብረዘይት 4.45 ሰዓት ፈጅቶብን የመጣንበት ስብሰባ እንደቀጠለ ነው፡፡ የጄክዶ ሥራ አስኪያጅ ከ2013 እስካሁን ያለውን የሥራ ሂደት ገለፁ፡፡ የ36 ምስርት ድርጅቶች አቅም መገንባቱን፣ ከትንሽ ወደሰፊ ማደጋቸውንና ሲዳ ባወጣው ማስታወቂያ መሰረት ካለፉ 6 ድርጅቶች መካከል የኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት አንዱ እንደሆነ አስረዱ፡፡
ለምን እንዳሸነፉ ያስረዱበት መንገድ ገርሞኛል፡፡ ምክንያቱም ማንም ለህብረተሰብ ዕድገት የሚሰራ አካል እነዚህን ማጠየቂያዎች (justifications) ቢያቀርብ መልካም መንገድ ነው ብዬ ስለማምን ነው፡፡ እስቲ እንያቸው፡-  
በምሥርት ማህበራት የባለቤትነት         ስሜት አለ ብለን እናምናለን፡፡
ተጠሪነት አለ ብለን እናምናለን፡፡
ስለምትተዋወቁ ትተማመናላችሁ -    ብለን እናምናለን፡፡
በአካባቢያችሁ ሀብት አለ - ባላችሁ    ሀብት ላይ ነው እየጨመራችሁ    የምትሠሩት - እንጂ ከ0 አትነሱም         ብለን እናምናለን፡፡
ውጤታማ ትሆናላችሁ ብለን እናምናለን፡፡ ምክንያቱም የባለቤትነት ስሜት ካለ፣ ተጠሪነት ካለ፣ መተማመን ካለ ውጤት አለ
ዘላቂ (Sustainable) ናችሁ ብለን         እናምናለን፤ በማንም ግፊት ሳይሆን     በራሳችሁ እየተንቀሳቀሳችሁ ስለሆነ፡፡
ልማቱም፣ ጥፋቱም፣ የችግሩ         መነሻም፣ መፍትሔም፣ ለውጥም፤         እዛው እናንተጋ አለ ብለን             እናምናለን፡፡
እኛ እንግዲህ ተወዳድረን ፍሬያማ የሆነው እነዚህን ይዘን ነው፡፡
ቀጥለው ከ72 ማህበራት የዛሬዎቹን ተሳታፊዎች እንዴት እንደለዩ ሲገልፁ፤ “72 ምሥርት ማህበራት ከተለያየ የአገሪቱ ክፍል አመለከቱ፡፡ 40ዎቹን ለመለየት የአማካሪ ቡድን ባለሙያዎች ከውጪ መሠረትን፡፡ በርካታ የምዘና ሥራዎች ተካሄዱ፡፡ ማንም ያንን መጠየቅ ይችላል፡፡ እናንተ ተመረጣችሁ - እንኳን ደስ አላችሁ” አሉ፡፡ ጭብጨባው አስተጋባ፡፡
በመጨረሻም ስለመፈራረም ያሳሰባቸውን ጉዳይ አነሱ፡- “ከተፈራረማችሁበት ሰዓት ጀምሮ ገንዘቡን በትክክል በሥራ ላይ ለማዋል ብርቱ መሆን ይኖርባችኋል፡፡ ለውጤት መሥራት አለባችሁ፡፡ ሥራ ተሠራ የሚባለው ውጤት ሲመጣ ነው፡፡ የ10 ልጆች ህይወት ቀይረናል፤ ስንል የእነዚህ ልጆች ህይወት መቀየሩን የሚያሳይ ተጨባጭ ነገር መኖር አለበት፡፡ ት/ቤት አይሄዱ ከሆነ መሄድ መቻላቸውን፣ አልባሳት ማግኘታቸውን፣ ደብተር ማግኘታቸውን ወዘተ ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ከህብረተሰቡ ጋር ጥሩ ግንኙነት መፍጠራቸውን ማረጋገጥ ያሻል፡፡ በተጨባጭ!”
ቀጥለው ገንዘብ (Fund) ማግኘት እየከበደ መምጣቱንም ገልፀዋል፡፡ የሁላችን፣ የአገራችንም ችግር ነውና እናስተውለው:-
“ገንዘብ ማግኘት በዓለም ላይ እየጠበበ መጥቷል፡፡ ብዙዎቹ አገሮች ወደ አገራቸው ውስጥ ጉዳይ ማተኮር ጀምረዋል፡፡ ስለሆነም ወደኛ አያዩም፡፡ ገንዘብም ቢሰጡ እነሱን የሚጠቅም ነገር እስካለ ብቻ ነው፡፡ ከእርዳታ ይልቅ ንግድ፣ ከማህበራዊ ልማት ይልቅ ኢንቨስትመንት ይቅደም ተብሏል፡፡ ዓለም ተለውጧል፡፡ ከዓለም ጋር መሄድ አለብን፡፡” …  
“ዋናው ነገር” አሉ በመጨረሻ፤ አገራዊ ፋይዳ ያለው ማጠቃለያ ነው የሰጡት:-
“በጋራ የሚያስመሰግን ሥራ ሠርተን፣ የምንሠራውን ወደን፣ ወገኖቻችንን ጥቅም ሰጥተን፣ በሥራችን ደስተኛ ሆነን፣ የመንፈስ እርካታ አግኝተን፣ የዜግነት ግዴታችንን እንደምንወጣ እርግጠኛ ነኝ! ለዚህ አደራዬ የጠበቀ ነው!” ብለዋል፡፡
የማህበራት አባላቱ እርስ በርስ በመተዋወቅ ሳሉ ደጅ የተፃፈውን የማስተዋወቂያ ሰሌዳ ሳነብ ቆየሁ - መሪ - ሰሌዳው፤
“የኢህማልድ ሲዳ የልማት አጋርነት ፕሮግራም የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን አቅም በማሳደግ ማህበረሰብን መሠረት ያደረገን ወላጆቻቸውን ያጡና ለችግር የተጋለጡ ህፃናት ድጋፍና ክብካቤ ፕሮግራም የፕሮጄክት ውል ስምምነት ሥነስርዓት” ይላል፡፡
ከማዶ “ምክረ - ሀሳቦች” የሚል ርዕስ ያለው ሰሌዳ ይታየኛል፡፡ ለማንኛችንም የሚጠቅሙ ነጥቦች ተነቁጠውበታል:-
የውል ሰነዱን በሚገባ መገንዘብ፤ የሁኔታዎችን ሪፖርት በመከታተል መሰነድ፣ የተጠቃሚዎችን የፆታ ስብጥር ማመጣጠን፡፡ የንዑሣን ኮሚቴ አባላት መተካካት፤ ዕገዛና ምክርን መሻት፤ ከአካላት ጋር መሥራት ውሳኔዎችን በቃለ - ጉባዔ ማስደገፍ፡፡ ሌላው ዐቢይ ርዕስ ለውጤት መትጋት ይላል፡፡ የመንግሥት አካላትን ጨምሮ ከሌሎች አካላት ጋር መሥራት፣ የአካባቢ ሀብትን ማንቀሳቀስ፣ የእርስ በርስ መግባባትን ማዳበር፡፡ በጐ ፈቃደኞችን ማብዛትና ሁሌም የተሻሉ ሆኖ ለመገኘት መጣር” ይላል ከታች፡፡ ተመልሼ ወደ ስብሰባው ገባሁ፡፡
የዕለቱ የመድረክ መሪ፤ አቶ ተዋበ ይዘንጋው፤
“የፕሮግራሙ አተገባበርና የሚጠበቁ ውጤቶች የምዘና ሥርዓት፤ ፕሮጀክቱ የሚያመጣቸው ተጨባጭ ለውጦች፤ የሚለውን አቶ ተስፋዬ የሰው ኃይል ማደራጃና የአቅም ግንባታ ኃላፊ፤ ያቀርባሉ፤ በጥሞና ተከታተሉ፣ ነጥብ ያዙ፤ ብለው አስገነዘቡ፡፡
አቶ ተስፋዬም፤
“ሥራዎቹ የሚካሄዱባቸውን ቦታዎች “ብሾፍቱ፣ ድሬዳዋ፣ ሻሸመኔ፣ ደብረ ብርሃን፣ ሽኒሌ፣ ቡታጅራ፣ ጂማ፣ አዲሳባ፣ እንድብር፣ ደብረሲና፣ ደብረማርቆስ፣ ባህርዳር፣ ላይ ጋይንት ወዘተ ጠቅሰው ሲቆጠሩ ወደ 17 ገደማ መሆናቸውን በጥቀስ ጀምረው ስለህፃናት እንክብካቤ የከፋ ገጽታ፡፡ አስረዱ፡፡ ከዚያም ስለ አሳዳጊዎች የኢኮኖሚ አቅም ማጐልበት አወሱ፡፡ “የየማህበሮቻችሁን አቅም አጐልብቱ” አሉ፡፡ ቀጥለውም፤ “በጋራ ልናመጣቸው የምንችል 15 ውጤቶች አሉ ብለው ቀጠሉ፡፡ ያሉን 42 ማህበራት ናቸው 2ቱ በኤልማ የተካተቱ ናቸው፡፡ ለ540 ልጆች አማራጭ መሠረታዊ ትምህርት መስጠት፣ ድጋፍ በማጣት ከት/ቤት የወጡ ተማሪዎችን መርዳት (በ10% ይገመታል)፣ 80% የልጆች ትምህርት ሁናቴ ማሻሻል፣ ሴቶችን መደገፍ (600 ያህል ታቅፈዋል)፤ ለ1ኛ ደረጃ ያልበቁ 60 ያህል ህፃናት ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግ፣ 3300 ጐልማሶች አቅም ማዳበር፣ 180 ወጣቶች ተምረው ሥራ ያልያዙትን ሥራ ማስያዝ (ሥራ መፍጠር)፣ ጥቃት የደረሰባቸው ህፃናትን ማገዝ፣ 2000 ሰዎች በህፃናት ዙሪያ ግንዛቤ ማስገኘት፣ እናንተ ማህበራቱ አቅማችሁ መገንባቱን ማረጋገጥ ነው፡፡ ዘንድሮ አበረታች ፕሮፖዛሎች በመቅረባቸው እጅግ ደስተኞች ነን” ብለዋል፡፡
መልክ ያለው ፕሮፖዛል ስለሆነ መልክ ያለው ስብሰባ ዛሬ ፈጥሮልናል” የሚል ቁልፍ ሃሳብ አስቀምጠዋል፡፡ “የሚያነክስ የገቢ ማስገኛ በፈፁም አይፈቀድም” ያሉት ሌላ ፋይዳዊ ዐረፍ-ነገር ነው፡፡ ያቅም ማጐልበት ሥራ ኃላፊ ስለሆኑ ጉዳዩ ጉዳያቸው መሆኑንም አጽንኦት ሰጥተውበታል፡፡
ገንዘብ የሚጠየቀው ማዕከላዊ ጽሕፈት ቤት መሆኑንና ከዛ ውጪ አስፈቅዶ አሳምኖ ሌላ ሥራ ለመሥራት ማስፈቀድ እንደሚቻልም አበክረው ገልፀዋል፡፡ ከዚያም ቦታዎችንና ማዕከላዊ ኃላፊነት ያላቸውን ጽ/ቤቶች አጣቅሰው አሳውቀዋል! ለምሳሌ ሽንሌና ድሬዳዋ ከድሬዳዋ ሲፒኦ ጋር ይሠራሉ” ብለዋል፡፡ ስለአመራር አሠራርና ውሳኔም አሳስበዋል፡፡
“ባትጣሉ ደስ ይለናል፡፡ በሥራው ምክንያት በተለይ ግን አትጣሉ!” “የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር የህዝብ ቁጥር መጨመር ባግባቡ ከተጠቀምንበት በጣም ይጠቅማል” ያሉትንም አስምረውበታል፡፡ ቀጥለውም “የዘመኑ ወጣት ራሱ ነገር፣ ምላሱ ከሱስ፣ እጁ ከፌስቡክ ቢላቀቅ ትልቅ ነገር እንፈጽማለን!” ያሉት ትውልድ - አቀፍ ቁም - ነገር ነው፡፡
በመጨረሻም “የተሻለ አፈፃፀም ያላቸውን “ሲቢኦ”ዎች Community Based Organization) እንሸልማለን” ያሉ ሲሆን “በፈረንጆች ታህሣሥ 19 አውደ ርዕይ ይኖራል፡፡ ለሌሎች ሥራችሁን ማስተዋወቂያ ነው” በሚል መረጃዊ ማስታወሻ ሰጥተዋል፡፡
አባላቱ በተሰጠው ማብራሪያ ላይ ጥያቄዎችን አቅርበው የሰው ኃይል ጉልበት ማደራጃ አላፊው ማብራሪያ ሰጥተውበታል፡፡
ቀጥለውም ወ/ሮ ኤልሳቤጥ ተስፋዬ የጄክዶ /ኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት/ የሂሳብ ክፍል ኃላፊ ስለ ስምምነቱ ሂሳብ አጠቃቀም አጠቃላይ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በትኩረት - ነጥብ ደረጃም፣ ማህበራቱ ከዚህ ቀደም ብዙ እንደተነጋገሩበትና ስልጠናም እንደወሰዱበት ገልፀው፤ እንደ መንደርደሪያ ለማሳሰብ፤ “የአሁኑ አሰራራችን እንደቀድሞው ተደጋግፈን የምናልፈበት አይደለም፡፡ እኛ ብናልፋችሁ ከሲዳ ይመጡና ይቆጣጠሯችኋል፡፡ ስህተት ከተገኘ አንዱ ሳይሆን 40ችንም እረብ ነው የምንለው፡፡ ስለዚህ የሚፈለገውን ማሟላት ግድ ነው ማለት ነው፡፡
…የገንዘብ መቀበያ ደረሰኝ፣ የገንዘብ መክፈያ፣ የዕቃ መረከቢያ ሰነድ፣ ዕቃ ማውጫ ሰነድ፣ የግዢ መጠየቂያ፣ የዕቃ መጠየቂያ ያስፈልጉናል፡፡ ተከታታይ ቁጥር ያላቸው መሆን አለባቸው፡፡ ካለን እሰየው! አለዛ መዘጋጀት! ሥራ ሳትገቡ እነዚህን ልብ በሉ!” ብለው አፅንኦት አድርገዋል፡፡ ከባንክ ጋር የሚሰራውን ሂሳባዊ ሂደትና ጥንቃቄም በሚገባ አብራርተዋል… የመንግሥት ቅድመ-ሁኔታዎችንም በቅጡ አውስተዋል፡፡
ወ/ሮ ኤልሣቤጥ እጅግ ጠቅላይ ሂሳብ - ነክ ማብራሪያ አቅርበው፣ የምሣ ፕሮግራም እንደሚኖር የመድረኩ መሪ አቶ ተዋበ አሳውቀው እግረ - መንገዳቸውን ግን ዋና ዋና የግንዛቤ ነጥቦች ያሏቸውን ተሰብሳቢዎቹ ልብ እንዲሉ ነቁጠው የምሣ ጊዜ ሆነ፡፡ ከምሣ መልስ አጠቃላይ ውይይት በሥራ አስኪያጁ በአቶ ሙሉጌታ ገብሩ መሪነት ቀጠለ፡፡ አያሌ ግር - ያሉ ነጥቦች ለምሳሌ “አንዱ ባጠፋ ለምን ሁሉ ይቀጣል?...ወዘተ” ተነስተውና የሚሰጠው ገንዘብ ትንሹ ብር 750,000 ትልቁ ብር 800,000 መሆኑ ተገልጦ፤ ወደ ውል ስምምነት ፊርማ ስነ - ሥርዓት ተገባ፡፡ የየማኅበራቱ ተወካዮች መጥተው ሰነድ መፈረሙን አካሄዱ፡፡
አጠቃላይ የስምምነት ፕሮግራሙ በዚሁ አበቃ
የመዝጊየ ንግግሩን አቶ ሙሉጌታ ገብሩ አደረጉ ህጋዊነትን አሰመሩበት፡፡ አደራቸውን አጉልተው ነገሩ፡፡ የህዝባዊ አገልግሎት ሥራ ግልጽነት እንደሚጠይቅ አበክረው ተናገሩ! ወገናዊነትን አጥፉ፤ ታገሉ - ለህሊናችሁ ሥሩ!! የአመራር አግባብና ቆራጥነትን አስቀድሙ፡፡ ፖለቲካ የእኛ ሥራ አይደለም፡፡ የእኛ ሥራ ልማትና ኢኮኖሚን ማገዝ ነው! የእኛ ማዕከል ደሀው ህዝብ ነው፡፡ ጥረታችንም የሁላችንም ነው! ሲሉ አበክረው ገለፁ! እንደመጣነው ሳይሆን ከደብረዘይት አዲሳባ በአርባ አምስት ደቂቃ ፉት አልናት! ተመስገን ነው!!


Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው ሚስት ፈላጊ ነው፡፡ እናማ…አገባታለሁ ለሚላት ሚስት መስፈርቶች ያወጣል፡፡ ለጓደኛውም … “እኔ የምፈልጋት ሚስት መልካም ባህሪይ ያላት፣ ብልህና ቆንጆ መሆን አለባት…” ይለዋል፡፡
ጓድኝዬው፣ “ታዲያ አስቀድመህ  እንደዚህ በግልጽ አትነግረኝም ነበር፣“ ይለዋል፡፡
ሰውየውም፣ “ይኸው ነገርኩህ እኮ…“ ሲል ይመላሳል፡፡
ጓደኝዬው ምን ቢል ጥሩ ነው… “ገና አሁን ነው ግልጽ የሆነልኝ፡፡ አንተ እኮ የምትፈልገው አንድ ብቻ ሳይሆን ሦስት ሚስት ነው፡፡ አንዲት መልካም ባህሪይ ያላት፣ አንዲት ብልህና አንዲት ቆንጆ፡ ሦስቱንም አንድ ላይ የያዘች ሴት ከፈለግህ ልብ ወለድ አንብብ!” አሪፍ አይደል!  በቃ… እዚህ ላይ እኮ ይሉኝታ አያስፈልግም፡፡ እሱ ማን የማይሆን ጥያቄ ጠይቅ አለው! ልክ ነዋ… ዘንድሮ እኰ እንትናዬዎቹ በአንዱ ነገር “ክንፍ አላት…” ሲባሉ በሌላው ደግሞ “ከእነጭራዋ ብቅ አለች…” ይባላሉ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…እንዲህ አይነት ያለ ይሉኝታ እቅጯን የሚናገሩ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ነገርዬው “…ሦስቱንም አንድ ላይ የያዘች ሴት ከፈለግህ ልብ ወለድ አንብብ!”  
ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው…ብዙም ከሰው አይገጥምም አሉ፡፡ እናላችሁ…ሠርግ አይሄድ፣ ሀዘን ላይ አይገኝ፣ አብሮ ‘ብርጭቆ አያጋጭ’…በቃ ምን አለፋችሁ በራሱ ዓለም ውስጥ የሚኖር ነው፡፡ እናላችሁ… አንድ ቀን ምን ይሉታል…
“ያቺ ዱሮ ትወዳት የነበረችው ቆንጆዋ ገርል ፍሬንድህ ባል ሞቷል፡፡ ሁልጊዜ ሀዘን ላይ አትገኝም ስለምትባል ቀብር እንዳትቀር …” ሲሉት ምን ቢል ጥሩ ነው… “እንኳን ሞተ፣ እኔም የምፈልገው እሱን አልነበር…” ይላል፡፡
በሌላ ቀን የሚስቱ ወንድም ይሞታል፡፡ ይህን ጊዜ ቀብር ላይ ተገኝቶ ሳይሰናበት እንኳን በዛው ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡ ሚስቱና ሌሎች ዘመዶች ሠልስት፣ አርባ ምናምን ሲሉ እሱ አይገኝም፡፡ በዚህ የራሱ ዘመዶች ሳይቀሩ ይበሳጩበታል፡፡ “አሁንስ አበዛው! አንድ ነገር ይደረግ…” ይባባሉና ሄደው የሚያናግሩት ሦስት ሽማግሌዎች ይመረጣሉ፡፡
ታዲያላችሁ…አንደኛው ሽማግሌ “ለዚህስ ሌላ ሰው አያስፈልግም፣ እኔ ብቻዬን ሀሳቡን አስለውጬ ወደ ጥሩ ኢትዮዽያዊነት እመልሰዋለሁ…” ይላሉ፡፡
ከዛ ይሄዱና እንዲህ ይሉታል…
“አንተ ችግርህ ምንድነው? እኛስ ምን አድርገንሀል! ማንም ሰው ሀዘን ላይ አትገኝም፡፡ አሁንም የሚስትህ ወንድም ሞቶ ቀብር ላይ ብቅ ብለህ በዛው ጠፋህ፡፡ ይሄ ነገር ይብቃ፡ ሰው ቀብር ላይ መገኘት ልመድ...” ይሉታል፡፡
እሱዬው ምን ይላቸዋል… “እኔ ትልቁን በሽታ ገድዬ ቀብሬዋለሁ…” ይላቸዋል፡፡
የተላኩት ሰው ግራ ይገባቸውና… “ምን የሚሉት በሽታ?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡
እሱም… “ይሉኝታ የሚባል በሽታ…” ይላቸዋል፡፡
ሽማግሌ ሆነው የሄዱትም ሰው ትንሽ አሰብ አድርገው ምን ቢሉ ጥሩ ነው… “አንተስ ተገላገልከው፣ እኔስ ይሉኝታን እንዴት ልገላገለው!” ብለው ቁጭ፡፡
እሳቸውም ነገሮችን የሚያደርጉት በይሉኝታ ነዋ!
እኔ የምለው… እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… እዚህ አገር ተጋፍቶ ይቅርታ መጠየቅ ከሲኒማ አድዋ ጋር አብሮ ፈርሷል እንዴ! እኛ ‘ደቃቆቹ’ ግራ ገባና! (በነገራችን ላይ…በአካልም የደቀቅን፣ በፈራንካውም የደቀቅን፣ በሞራሉም የደቀቅን፣ በተስፋውም የደቀቅን… ሰብሰብ ብለን “አይዞህ ለደግ ነው…” “አይዞሽ ሊነጋ ሲል ይጨልማል…” እያልን የምንጽናናበት ማህበር ቢጤ ብኗቋቋም አሪፍ አይደል!
ደግሞላችሁ…አሁን፣ አሁን ደግሞ ክንድና ደረቱን እየተነቀሰ በ‘ቢጢሌ’ ካናቴራ ከተማዋ ውስጥ የሚንጎማለል በዝቷል፡፡ ታዲያላችሁ… በትከሻው ዘፍ ይልባችሁና…አለ አይደል… እሱ በተጋፋው እናንተ በተገፋችሁት ገላምጧችሁ ይሄዳል፡፡ (“ጡንቻ የሚያሳብጥ ኪኒን ከዱባይ እንደ ልብ ይገባል…” የሚባለው እውነት ነው እንዴ!
እናላችሁ…ሲመጡብን ‘ጥግ እንዳንይዝ’…አገሩ ሁሉ ተቆፍሮ ‘የምንለጠፍበት ጥግ’ አጣን፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…ይሉኝታ የሚመስል ነገር መነሳት ካለበት እዚህ ላይ ነው፡፡ ‘መድቀቃችንን’ አይቶ ገፍትሮን ከመሄድ ይቅርታ ማለት ለመንግሥተ ሰማያት ‘ሲ.ቪ.’ ማጠናከሪያ ይሆናል፡፡ ልክ ነዋ…ዘንድሮ የምንገፈተረው መንገድ ላይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም የህይወታችን መስኮች ሆኗላ!
ስሙኝማ…በዛ ሰሞን አንድ ሚኒባስ ውስጥ የሆኑ ሦስት ሰዎች ጓደኛቸው ለልጁ የስም መዋጮ እንዲያደርጉ ጠይቋቸው ግራ ገብቷቸው ሲጨቃጨቁ ነበር፡፡ አስቸጋሪ ነዋ…አሁን፣ አሁን እኮ አይደለም ጓደኛ ምናምን ወላጆችም ራሳቸው ስም በማውጣቱ ግራ የተጋቡ ነው የሚመስለው፡፡
ሀሳብ አለንማ…ወይም ወላጆች “ለልጄ ስም አውጣልኝ…” ምናምን ሲሉ…አለ አይደል…አብረው ‘ቲ.ኦ.አር.’ ምናምን የሚባለውን ነገር ይላኩልን፡፡ ስሙ ዓለም አቀፍ ይዘት ያለውና ልጁ ድንገት የፊልም ተዋናይ ቢሆን ለአፍ የሚጣፍጥ ምናምን ተብሎ እቅጩ ይጻፍልን፡፡
ወይም ደግሞ…“የሚወጣው ስም የአሜሪካን ወቅታዊ ሁኔታ ያገናዘበና ልጁ በኋላ ዲጄ ሊሆን ስለሚችል ለእሱ የሚስማማ መሆን አለበት…” ተብሎ ይለይልንማ!
እኔ የምለው…የስም ነገር ካነሳን አይቀር…ለልጆች የምንሰጣቸው ስሞቻችንና የቡቲኮቻችን ‘የፈረንጅ ስም’ እየተመሳሰሉብን ነው፡፡ አሀ… ምን ይደረግ… ይሄ ኢንተርኔት የሚሉት ነገር ‘ቆርጦ መለጠፍ’ አስለመደንና ስሞች ሁሉ ‘ከት ኤንድ ፔስት’ እየተደረጉ ነው፡፡
ከሀበሻ እናትና አባት እዚህቹ በግርግር ትንፋሸ ያጠራት ከተማችን ውስጥ የተወለደን ‘ፍራንክ’ ብሎ ስም መስጠት ትንሽ አያስቸግርም፡ ወዳጆቼ እንደዛ አይነት ስም መስማታቸውን ነግረውኛል፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታም አይደል እዚህ አገር… “እሱን እንኳን ተወው፣ እንዲህማ አይደረግም…” ብሎ ነገር እየቀረ ነው፡፡ ሌላ ቦታ ሊደረግ የማይችለው ነገር… ‘አዲስ ነገር መፍጠር’ በማይሰለቻት፣ ‘ከአፍሪካ የመጀመሪያ ከዓለም ሁለተኛ’ ማለት ዓመል የሆነባት አገራችን ውስጥ ሊሆን የማይችል ነገር በጣም ጥቂት ይመስላል፡፡
እኔ የምለው…አንድ ሰሞን ፑሽኪን ‘የእኛ ነው፣ አይደለም’ ምናምን አይነት ሙግት ነበረላችሁ! ‘ቡና አብረን መጠጣት ያቆምናቸው’ ጎረቤቶቻችን በበኩላቸው “ፑሽኪንማ የራሳችን ነው!” እያሉ በላ ልበልሃ ነገሮች ነበሩ፡፡
እኔ የምለው…የፑሽኪን ዝርያዎች ራሳቸው ለመለየት ምስክርነት ቢጠሩ እኮ… “መጀመሪያ ነገር እነኚህ አገሮች የሚገኙት እስያ ነው ደቡብ አሜሪካ?” ብለው ይጠይቁ ነበር፡፡ “አፍሪካ ውስጥ ናቸው ወይ?” ለማለት መጀመሪያ አፍሪካ አገር ሳትሆን አህጉር መሆኗን ማወቅ አለባቸው፡፡ ዓለም ይሄን ያህል ነች፡፡
ልጄ እዛ ይሉኝታ ምናምን ብሎ ነገር የለማ!
ኮሚክ እኮ ነው…በተለይ በአውሮፓ በርከት ባሉ ሀገራት… “መጤዎች ይውጡልን…” “ማንም በራፋችን ዝር እንዳይል…” አይነት ነገር የሚሉ የፖለቲካ ቡድኖች ጉልበታቸው እየጠነከረ ባለበትና ‘ለዓይናቸው እየተጠየፉን’ ባሉበት ዘመን የልጅን ስም አውሮፓዊ እያደረጉ ከመሰረቱ ማንነቱ ላይ ጥቁር ነጥብ የሚያደርጉ ወላጆች ልብ ይግዙማ!
ሀሳብ አለን… ለአውሮፓ ህብረት የአባልነት ጥያቄ ይቅረብልንማ! ልክ ነዋ! ምድረ የአውሮፓ ከተማ ሁሉ የካፌና የሬስቱራንት መጠሪያ ሆኖ የለም እንዴ! ይህ ‘ወንድማማችነትን ለማጠናከር’ ያለንን ፍላጎት (ቂ…ቂ…ቂ…) ፍላጎታችንን የሚያሳይ አይደለም እንዴ! ቢያንስ ቢያንስ የታዛቢነት ወንበርማ ይገባናል፡፡
ለምሳሌ ‘ጆኒ’ ምናምን ድሮ ማቆላመጫ ነበር፡፡ አሁን ግን መደበኛ ስም ሆኖ ይወጣል አሉ፡፡
በ‘አብዮቱ’ ሁለት ልጆቻቸውን ‘ሆቺ ሚን’ እና ‘ቼ ጉቬራ’ ብለው የሰየሙ ሰዎች ነበሩ፡፡ እኔ የምለው…እንግዲህ  ጨዋታም አይደል…ዘንድሮ የ‘ቦተሊካ ነፋስ’ የነካቸው ስሞች አሉ!
ስሙኝማ… ብሰማው ደስ የሚለኝ አንድ ስም ምን መሰላችሁ… ‘ያለው ሁኔታ ነው ያለው’ የሚል ስም፡፡ ልክ ነዋ…‘ፖፑላር’ ስም ይሆናላ! ደግሞላችሁ… በየስብሰባውና በየቃለ መጠይቁ ሲደጋገም ዘመድ ወዳጅ ሁሉ… “እንዴት ቢወዱት ነው ስሙን እንዲህ የሚደጋግሙት…” ማለታቸው አይቀርማ!
እናላችሁ…ከፍ ብለን የጠቀስነው የይሉኝታ ነገር አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ በአንድ በኩል በይሉኝታ ማድረግ የማንፈልጋቸውን ነገሮች እናደርጋለን፣ መቀላቀል የማንፈልጋቸውን ስብስቦች እንቀላቀላለን፣ መሄድ የማንፈልጋቸው ቦታዎች እንሄዳለን፣ በማያስቀው እንንከተከታለን…ብቻ ምን አለፋችሁ… ይሉኝታ ነገራችንን ሁሉ አርቲፊሻል ያደርገዋል፡፡እናማ… ለማግባባት የተላኩት ሰውዬ… “አንተስ ተገላገልከው፣ እኔስ ይሉኝታን እንዴት ልገላገለው!” እንዳሉት ከልማቱ ጥፋቱ ከሚብስ ይሉኝታ የምንገላገልበትን ዘመን አንድዬ ያፋጥልንማ!    ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 15 November 2014 10:42

ከመሸ አትሩጥ ከነጋ አትተኛ

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሽማግሌ አባት የመሞቻው ጊዜ ደርሶ ኖሮ ልጁን ወደ አልጋው እንዲመጣ ይጠራዋል፡፡ ልጁም ይጠጋውና፤
“አባቴ ሆይ ምን ላድርግልህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
አባትየውም፤
“ልጄ ሆይ! እንግዲህ የመሞቻዬ ጊዜ ደርሷል፡፡ ነገር ግን አንተን ምድር ላይ ጥዬህ ስሄድ ምንም ያጠራቀምኩልህ ጥሪት ስለሌለ ትቸገራለህ ብዬ ተጨንቄያለሁ፡፡ ሆኖም አንድ አውራ ዶሮ አለኝ፡፡ የዚህን አውራ ዶሮ አጠቃቀም ካወቅህበት ብዙ ሀብት ታፈራበታለህ” ይለዋል፡፡
ልጁም፤ “እንዴት አድርጌ?” አለው፡፡
አባቱም፤ “አውራ ዶሮ ወደማይታወቅበት አገር ሂድ፡፡ የአውራ ዶሮን ጥቅም ንገራቸው” ብሎ ሃሳቡን አስፋፍቶ ተናግሮ ሳይጨርስ ትንፋሹ ቆመ፡፡
ልጅየው አባቱን ከቀበረ በኋላ አውራ ዶሮ የማይታወቅበት አገር ለመፈለግ ከቤቱ ወጣ፡፡ ብዙ አገር ዞረ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ቦታ መአት አውራ ዶሮ ስላለ ጥቅሙን ያውቁታል፡፡ በመጨረሻ ወደ አንድ ደሴት ሲገባ አንድም ዶሮ የላቸውም፡፡ ቀን መምሸት መንጋቱን እንጂ ምንም ሰዓት አይለዩም፡፡ ስለዚህ እንዲህ አላቸው፡-
“ይሄ አውራ ዶሮ ይባላል፡፡ እዩ አናቱ ላይ ቀይ ዘውድ አለው፡፡ እንደ ጀግና ጦረኛም እግሩ ላይ ሹል ጫማ አለው፡፡ ሌሊት ሌሊት ሶስት ጊዜ ይጮሃል፡፡ ይህንንም የሚያደርገው ለእናንተው ጥቅም ነው፡፡ በየአንዳንዱ ጩኸቱ መካከል ያለው የጊዜ ርዝመት እኩል ነው፡፡ በመጨረሻ ሲጮህ ልክ ሊነጋ ሲል ነው ማለት ነው፡፡ ቀን ከጮኸ ደግሞ አየሩ ሊለወጥ መሆኑን መናገሩ ነው ማለት ነውና መዘጋጀት ይኖርባችኋል” አላቸው፡፡
ነዋሪዎቹ ሁሉ ተገረሙ፡፡ የዚያን እለት ሌሊት ማንም የተኛ ሰው የለም፡፡ አውራ ዶሮው በውብ ድምፁ አንድ ጊዜ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ፤ ጮኸ፡፡ ቀጥሎ አስር ሰዓት ላይ ጮኸ፡፡ በመጨረሻም ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ ጮኸ፡፡ ህዝቡ ጉድ አለ! ስለዚሁ አውራ ዶሮ ሲያወራ ዋለ፡፡ ነገሩ ንጉሡ ጆሮ ደረሰ፡፡ ንጉሡም እንደ ህዝቡ በሚቀጥለው ሌሊት የአውራ ዶሮውን ጩኸት ሲያዳምጡ አደሩ፡፡ በጣም ተደንቀው ልጁን አስጠርተው፤
“ይሄንን አውራ ዶሮ ትሸጥልናለህ ወይ?” አሉት፡፡
ልጁም “አዎን ግን በወርቅ ነው የምትገዙኝ” ሲል መለሰ፡፡
ንጉሡም፤ “በምን ያህል ወርቅ?” አሉት፡፡
ልጁ - “አንድ አህያ ልትሸከም የምትችለውን ያህል” አለ፡፡
ንጉሡ አንድ አህያ የምትሸከመውን ኪሎ አስጭነው ሰጡትና ወደቤቱ የአባቱን ውለታ እያሰበ ሄደ፡፡ ንጉሡም አውራ ዶሮአቸውን ወሰዱ፡፡ ከዚያን እለት ጀምሮ የዚያ ደሴት ህዝብ ጊዜና ሰዓት ለየ፡፡
***
አውራ ዶሮ የሚሸጥልን አንጣ፡፡ ሰዓትና ጊዜን መለየት ለማንኛችንም ትልቅ ፀጋ ነው፡፡ “የቸኮለች አፍሳ ለቀመችን”ና “የቆየ ከሚስቱ ይወልዳል”ን ዛሬም ባንረሳ መልካም ነው፡፡ ብልህ አባት ለልጁ የዘለአለም ሀብት ማውረሱን ካስተዋልን ዘላቂ ልማት፣ ዘላቂ አገር ይኖረናል፡፡ ቤትና ቀን የለየ፣ ጊዜና ሰዓት ያወቀ ወደፊት መሄድም፣ ባለበት መቆምም፤ ማፈግፈግም የሚያውቅ የነቃ የበቃ ወራሽ ካለን የነገን ጥርጊያ መንገድ አበጀን ማለት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ቀለበት መንገድ መስራት ብቻ ሳይሆን ከቀለበት መውጪያውንም እንድንሰራ ፈር ይቀድልናል፡፡ ከተማረ የተመራመረ የሚለው ትርጉም የሚኖረው እዚህ ላይ ነው፡፡
“ጊዜ የሥልጣን እጅ ነው” ይላል ጸሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡ ጊዜን ያላወቀ እንኳን ሥልጣኑን ራሱን ያጣል፡፡ በማንኛውም ደረጃ ላይ ቢሆን “በትክክል ጊዜን መጠቀም እወቅበት፤ ይላሉ ጠበብት፡፡ አለልክ አትጣደፍ፤ ነገሮች ከቁጥጥርህ ይወጣሉና፡፡ የትክክለኛዋ ቅፅበት ሰላይ ሁን፡፡ የጊዜን መንፈስ አነፍንፈህ አሽትት፡፡ ወደ ስልጣን (ድል) የሚወስዱህን መንገዶች በዚያ ታገኛለህ፡፡ ጊዜው ካልበሰለ ማፈግፈግን እወቅበት፡፡ ሲበስል ደግሞ ፈፅሞ ወደኋላ አትበል!” የሚሉ ፀሐፍት ታላቅ ቁምነገር እየነገሩን ነው፡፡
ጊዜን በትክክል መጠቀም የሚችል ዝግጅትን ዋና ጉልበቱ ያደርጋል፡፡ ድግሱ ከመድረሱ በፊት የምግብ እህሉን፣ የጌሾ ጥንስስ ስንቁን ማደራጀትና በመልክ መልኩ መሸከፍ፣ መጥኖ መደቆስ፣ መብሰያና መፍያ ጊዜውን በቅጡ ለድግሱ ሰዓት ማብቃትን ከሸማች እስከ አብሳዩ ውል ሊያስገቡት ይጠበቃል፡፡
“ካልተሳፈሩበት ቶሎ ተሸቀዳድሞ  
ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ”
የሚለው የደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ይሄንኑ ጊዜ እንኳን ከበሰለ በኋላ እንዲሁም መዘናጋት እንደማይገባ ያስገነዘቡት ነው፡፡
ያለመላ ግጭት ጅልነት ነው፡፡ የዝግጅት ጊዜ ወስዶ አስቦ፣ ሁሉን አመቻችቶ ነው ትግል፡፡ አንዴ ከገቡ ደግሞ መስዋዕት መኖሩን ሳይረሱ ምንጊዜም ሳያቋርጡ፣ ሳይማልሉና ሳይታለሉ መቀጠል ግድ ይሆናል፡፡
በሼክስፔር ሐምሌት ቴያትር ውስጥ፤
“ፈጥነህ ጠብ ውስጥ አትስጠም
አንዴ ከገባህበት ግን፣ እጅህ ከባላንጣህ ይቅደም!”
የሚለን የጊዜ ዕቅጩነት (Perfect - imning) ጉዳይ ነው፡፡
“አውራ ዶሮ ጮሆ፣ መንጋቱን ነገረኝ
ዛሬ ሌሊት ላርደው ቀጠሮ ነበረኝ” ያለውን ያገራችንን ወጣት ገጣሚ ረቂቅነትም አለመዘንጋት ነው!!
የሁሉ ነገር መሳሪያ ጊዜ ነው!
ዘመን የጊዜ ጥርቅምና የቅራኔና የሥምረት ውጤት ነው፡፡ ስለዚህም እንደታሪክ ክፉውንም ደጉንም ማጣጣሚያውና ያንን የመመርመር፣ ከስህተት የመማር፣ ነገን የመተለም ጉዳይ ነው ጊዜን ማወቅ ማለት መጪውንም ምርጫ በጊዜ ማስላት ነው የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጊዜን ጨበጥክ ማለት ድልን ጨበጥክ ማለት ነው፤ የሚባለው እንዲያው ለወግ አይደለም! ጊዜን እንደመሳሪያ የምንቆጥረው ከዚህ በመነሳት ነው፡፡ አውራ ዶሯችንን በጊዜ እንግዛዛ - ሌሊትን፣ ተስፋንና ንጋትን - ይንገረን፡፡ ይህ ሚጠቅመን በማታ ሩጫ እንዳንጀምር ከነጋ በኋላም እንዳንዘናጋ ነው! “ከመሸ አትሩጥ፣ ከነጋ አትተኛ” የሚለው የወላይታ ተረት አደራ የሚለን ይሄንኑ ነው!!



Published in ርዕሰ አንቀፅ
Saturday, 15 November 2014 10:40

ወዴት እየሄድን ነው?!

         እንደ ሀገር እየተጓዝንበት ያለው ጎዳና ትክክል ነው ወይ? ጉዞዋችንስ? እውነት የያዝነው መንገድ ካሰብንበት ያደርሰናል? ወዴት እየሄድን ነው? ሠርክ በውስጤ የሚመላለሱ፣ አእምሮዬም መልስ ፍለጋ የሚደክምላቸው ጥያቄዎች ናቸው፡፡ እንድጠይቅ የሚያደርገኝ ደግሞ አንድም በየመስኩ እየተጓዝንበት ያለው ጎዳና እና የጉዞው ስልት በበቂ የተጠና ስለማይመስለኝ፣ አንድም ከማስተዋል ይልቅ በጥድፊያና በ“በል በል” ስሜት የተቃኘ ስለሚመስለኝ ነው፡፡ አስተያየቴ ግብታዊ ቢመስልም ዝግ ብላችሁ ስታስተውሉት እንደምንስማማ ተስፋ በማድረግ ጥያቄዬን ይዤ ልቀጥል፡፡ ወዴት እየሄድን ነው?!
ጥያቄውን የሚመልሱ የሚመስሉ (የሚመስሉ ነው ያልኩት) ንግግሮችን ከተለያዩ እቅዶችና አቅጣጫዎች ላይ አንብበን ወይንም ሲነበብ ሰምተን፣ እንዲሁም ከመንግስት ሹማምንት አንደበት ሲነገር አድምጠን ይሆናል፡፡ እርግጥ ነው ለማመን መስማት አንዱ ምክንያት ቢሆንም የምንሰማው ከምናየው ጋር ካልሰመረ ግን ለማመን ይገደናል፡፡ (ደግሞም ከምንሰማው ይልቅ የምናየው ውሃ ይቋጥራልና የምናየውን እናምናለን፡፡) እናም ገለጻዎቹን በአንድም ሆነ በብዙ ምክንያቶች ለማመን እቸገራለሁ፡፡ ለዚህም አንድ ሁለት ምክንያቶችን ላንሳ፡፡
አንደኛ የአስተያየቶቹ ባለቤት “ጉዞውን የሚመራው” መንግስት በመሆኑ “ባስያዘን” ጎዳና ላይ በቂ ጥናቶችን ከማድረግ ይልቅ ለአላስፈላጊ ፕሮፓጋንዳዎች ትኩረት በመስጠት ላይ የሚጠመድ ስለሚመስለኝ ነው፡፡ ይህንንም በየጊዜው ትክክለኛ አቅጣጫዎች ናቸው ብሎ ካወጃቸው፣ አውጆም ከተገበራቸው ሆኖም (እሱ በገሀድ ባያምንም) ብዙም ሳይቆይ ከሰረዛቸው (ሲተቻቸው ባንሰማም) አቅጣጫዎቹና ተግባራቱ በተደጋጋሚ ታዝበናል፡፡
ሁለተኛ በየመስኩ የተቀመጡት ሕጎችና መመሪያዎች ለአንድ ግብ የቆሙ እንዲሆኑ ስለሚጠበቅ እርስ በርስ ሊመጋገቡና ሊናበቡ የሚገባ ቢሆንም ከዚያ ይልቅ እርስ በርስ የሚጋጩ መሆናቸው ነው፡፡ ይህ አለመናበብና እርስ በርስ መጋጨት በአንድ ከተማ ውስጥ በሚገኙ ሁለት ክፍለ ከተሞች ውስጥ ወይንም በአንድ ክፍለ ከተሞች ውስጥ በሚገኙ ሁለት ወረዳዎች ውስጥ የተለያዩ ሕጎች/መመሪያዎች ተፈጻሚ ሲሆኑ እስከማየት ይደርሳል፡፡ አንዱ ጋ የሚፈቀደው ሌላው ጋ ክልክል ሊሆን ይችላል፡፡ አንዱ ጋ የሚያስቀጣው ድርጊት ሌላው ጋ ሊያስመሰግን ይችላል፡፡ ሌላም ብዙ! እናም ጥያቄዬ መልስ ይሻልና እጠይቃለሁ፡፡ እውነት ወዴት እየሄድን ነው?
እውነት እላችኋለሁ ነገራችን ሁሉ የተጠና እና የምር የታሰበበት አይመስልም፡፡ ስለሆነም ያለንበትን ጎዳና አላምነውም፡፡ የሚተገበሩትን ስልቶች አልመካባቸውም፡፡ ይህንን የሚያስረግጡ በርካታ አስረጂዎችን ማንሳት ይቻላል፡፡ ጥቂት ብቻ ብናስተውል ብዙ ነገሮችን ልብ እንላለን፡፡ ብዙ ልክ ያልሆኑ ነገሮችን!
አንድ ተጓዥ ያሰበበት ለመድረስ ወደዚያ ሊያደርሰው የሚችለውን ትክክለኛ ጎዳና መምረጥ አለበት፡፡ በመረጠበት ጎዳናም በጽናትና በትጋት መጓዝ ይጠበቅበታል፡፡ ጉዞውን ከመጀመሩ በፊት ግን ጎዳናው እንደሚያደርሰው ፍጹም እርግጠኛ መሆን አለበት፡፡ አለዚያ  እንኳንስ ለቀናት ለዘመናት ቢኳትንም ካሰበበት አይደርስም፡፡ መድረስን ይመኛል እንጂ አይጨብጠውም፡፡ ይህ የሚያስማማን ይመስለኛል፡፡ እናም እዚህ ላይ ቆመን ጥቂት ነጥቦችን እናንሳ፡፡
አንድ፦ እየሄድንበት ያለው ጎዳና ተገቢውና ትክክለኛው ነው? ትውልድና ሀገር የሚጓዙበት የመሆኑን ያህል ተገቢው ጥናት ተደርጎበታል? ተደርጎበታል ካልን ውጤቱ ምን ይመስላል? ጥያቄው በቅጡ ሊመለስ ይገባል፡፡ እርግጥ ነው ትክክለኛው እንደሆነ ጎዳናውን የመረጡት “የጉዞው መሪዎች” ደጋግመው ነግረውናል፤ እየነገሩንም ነው፡፡ ግን ደግሞ እነሱ ትክክል ነው ከማለት ውጪ ሌላ ሊሉን ይችላሉ? አይመስለኝም፡፡ ድክመታችንን እና ስህተታችንን ማመን ተራራን የመሸከም ያህል ያስፈራናል፡፡
ብዙዎች ራሳቸው የመረጡትን ነገር አያሄሱም፡፡ ራሳቸውን ቢያሄሱ የሚጠፉ ይመስላቸዋል፡፡ ሂስን የሚፈራ አያድግም! ደግሞም ጎዳናውም ሆነ አጓጓዙ ሌሎችን ስላደረሰ ብቻ እኛንም ያደርሰናል ማለት አይደለም፡፡ ምክንያቱም የእኛ ማንነት (ማንነት በርካታ ጉዳዮችን ይይዛል፡፡) ከሌሎች ይለያል፡፡ ከማንነታችን የሚሰርጸው አቅማችንም ከሌሎች አቅም ጋር አንድ አይደለም፡፡
ሁለት፦ የጉዞ ስልቶቻችንስ ምን ያህል ትክክል ናቸው? ሌላው መልስ የሚሻ ጥያቄ ነው፡፡ ወደ ኋላ መለስ ብለን ብዙም ሳንርቅ አንዳንድ ነገሮችን ለማስታወስ እንሞክር፡፡ እንደ ጦር ግንባር ተልዕኮ የተለያዩ ስያሜዎች ተሰጥቶአቸውና የጊዜ ወሰን ተበጅቶላቸው የተቀመጡ እቅዶችንና ተግባራትን እንዲሁም በዘመቻ የተቃኘ አፈጻጸማቸውን እናስታውስ፡፡ ውጤታቸው ምን ነበር? ቢያንስ ከፊሎቹ ውጤታማ እንዳልነበሩ እናውቃለን፡፡ ትክክል ከነበሩ ለምን ውጤታማ አልሆኑም?
እርግጥ ነው እቅድ ሁሉ መቶ በመቶ ውጤታማ እንዲሆን አይጠበቅም፡፡ ያ ማለት ግን ግማሽ በግማሽ ውጤታማ አይሆንም ማለት አይደለም፡፡ ይህ ሊከሰት የሚችለው አዋጪነቱ ያልተጠና እና በአስተማማኝ መልኩ ያልተፈተሸ እቅድ ከተተገበረ ብቻ ነው፡፡ እናም እላለሁ፤ አሁን እየተገበርናቸው ያሉትስ ስልቶች ካሰብንበት የሚያደርሱን ናቸው?
ሦስት፦ በጎዳናው ተጉዘን ያሰብንበት ለመድረስ ጉዞው የሚጠይቀው ጽናትና ትጋት አለን ወይ? ማንም ስለፈለገ ብቻ ያሰበበት አይደርስም፡፡ እርግጥ ነው መፈለግ አንዱና ቀዳሚው ግብአት ነው፡፡ ሆኖም መፈለግ ወደ ድርጊት እስካላደገ ድረስ አእምሮ ውስጥ ሲላወስ የሚኖር ምኞት ነው፡፡  ድርጊት ደግሞ ጽናትና ትጋትን ይጠይቃል፡፡
ጥያቄው ማቆሚያ ያለው አይመስልም፡፡ የጉዞው ተዋናዮችስ መድረሻው የሚገዳቸው ናቸው? ጉዞውን ለማሳካትስ ብቃቱና ፍላጎቱ አላቸው? ኃላፊነትስ ይሰማቸዋል? እነዚህን መፈተሽ፣ ፈትሾም እውነቱን መመስከር ይገባል፡፡ የዛሬው መከራችን ነገም እንደማይቀጥል መተማመኛ እንሻለን፡፡ የያዝነው ጎዳና እንደ ሀገር ከተቸነከርንበት  የችግርና የመከራ ማጥ ውስጥ መንጥቆ ያወጣናል ወይንስ ወደባሰ አዘቅት ይከተናል? እርግጡን ማወቅ እንፈልጋለን! እርግጡን ማን ይነግረናል?
ስለያዝነው መንገድ ተገቢ መሆን አለመሆን ብዙዎች ብዙ ቢሉንም ምንም እያሉን አይደለም፡፡ የዚህም ምክንያቱ እየነገሩን ያሉት አካላት ሊነግሩን የሚገቡት ስላልሆኑ ነው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ስለ ጎዳናውና ጉዞዋችን የምንሰማቸው አስተያየቶች ሁለት ፅንፍ የወጡ ናቸው፡፡ ገዢው ፓርቲና ከእሱ ጋር የወገኑት “እንከን የሌለውና ፍጹም ውጤታማ ጎዳና” ላይ እንዳለን ሠርክ ሊሰብኩን፣ ሰብከውም ሊያሳምኑን ይሞክራሉ፡፡ (ልብ በሉ! እስከ አሁን ድረስ በአለም ላይ እንከን የሌለው ጎዳና አልታየም፡፡ እነሱ ግን የእኛ እንከን የለውም ይሉናል፡፡)
በሌላው ጽንፍ የቆሙት የሚሰጡት አስተያየት ደግሞ ከፊተኞቹ ፍፁም ተቃራኒ ነው፡፡ ለእነዚህኞቹ ጎዳናውና ስልቱ ፍጹም ጎጂ ነው፤ አንድም መልካም ጎን የሌለው ስህተትና ጥፋት፡፡ ማጠንጠኛቸውም ይሄ ቢስተካከል ሳይሆን ሙሉውን ቢቀየር የሚል ነው፡፡ አንዳንዴም “እኛ ካልጋገርነው እንዴት ጣፍጦ” ሲሉም ይሰማል፡፡ ሁለቱም አካላት ስላለንበት ጎዳና እርግጡን የሚነግሩን አይደሉም፡፡ አንዱ በፍጹም ፍቅር ሁለተኛው በፍጹም ጥላቻ ውስጥ ወድቀው እኛንም ሊጥሉን የሚሞክሩ ናቸው፡፡ ሦስተኞቹስ?
ወደ ሦስተኞቹ ጣቴን እቀስራለሁ፡፡ ወደ የመስኩ ምሁራን እና ባለሙያዎች፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ሀገራችን ለምሁራንና ለባለሙያዎች ያላት ክብርና የምትሰጠው ጆሮ  የሚያሳፍር ነው፡፡ ከእውቀት ይልቅ ድፍረት ነግሶአል፡፡ ከብቃት ይልቅ ቲፎዞ ነው የሚታፈረው፡፡ ማንም ባልዋለበትና ባልደከመበት መስክ ላይ ያሻውን በድፍረት ሲደሰኩር ቅንጣት ማመንታት አይታይበትም፡፡ በዚህ ትርምስ ውስጥ ምሁራንና ባለሙያዎች ቦታና ሰሚ አጥተዋል፡፡ ይህንን በሚገባ አውቃለሁ፡፡ ሆኖም ወደ እነሱ ጣቴን የምቀስረው ስለያዝነው መንገድ ከእነሱ የተሻለ ሊነግረንና ልናምነው የምንችለው አካል አለ ብዬ ስለማላስብ ነው፡፡
ምናልባትም ከእነሱ አንዱ ይህንን እያነበበ “ይቀልዳል እንዴ? ማን ሰምቶን ነው እኛ የምንናገረው?” በማለት በፌዝና በመገረም ፈገግ ይል ይሆናል፡፡ እኔ ግን እላለሁ፡፡ “ማንም ባይሰማህስ ለምን ይገደሀል?” ደግሞም አምናለሁ፤ የሚጮህ አንደበት እውነትን እስከተናገረ ድረስ አንድ ቀን ይሰማል፡፡ መሰማት ከጀመረ ደግሞ ማቆሚያ ያለውም! በፍጹም፡፡  የምናውቀውን ሁሉ የመግለጽ ሞራላዊ ግዴታ ያለብን ይመስለኛል፡፡ ከእንጀራችን ባለፈ ለወገናችንና ለሀገራችንም ልንኖርና ልንደክም ይገባል፡፡
እነሆ ስላለንበት ጎዳና ሁለት ተቃራኒ ፅንፍ የሆኑ ሀሳቦች ሲነገሩን ዘመናት ላይመለሱ ነጎዱ፡፡ አንዱ ከፍጹም ፍቅር ሁለተኛውም ከፍጹም ጥላቻ የሚመነጩ በመሆናቸው ሚዛናዊ አይደሉም፡፡ ግባቸውም እንደሰባኪ ሁሉ ተከታዮችን ማፍራት ነው፡፡ ተከታዮችን የሚሻ ስብከትን ሳይሆን ሀቀኛና ገለልተኛ አስተያየትን መስማት እንሻለን፡፡ ጥያቄዎቹ ሊመለሱ ይገባል፡፡ ጎዳናው የት ያደርሰናል? ወዴትስ እየሄድን ነው?! እውነቱን ማወቅ እንፈልጋለን!! መልካም ሰንበት!!

Saturday, 15 November 2014 10:38

አስገራሚ የቃላት ፍቺዎች

ብልጥ
ድንገት ወንዝ ውስጥ ቢወድቅ፣ በዚያው ገላውን ታጥቦ የሚወጣ ሰው
ፀጥታ
የመጀመሪያው ልጅ ከመወለዱ በፊትና የመጨረሻው ልጅ ትዳር ይዞ፣ከወላጆቹ ቤት ሲወጣ ብቻ  የሚገኝ  
ግብዣ
ለሴቶች - ከሌሎች ተጋባዥ ሴቶች የተሻለ አምሮና  ተውቦ ለመታየት የሚፎካከሩበት
ለወንዶች - ምግብ በጥራትና በገፍ የሚገኝበት መልካም  አጋጣሚ
ሻይ ቡና
ለሴቶች - ሻይ ቡና
ለወንዶች - ቁርጥ፣ ወይን ጠጅና ቢራ
ሃያሲ
እንደ እበት ትል ከሌሎች ቆሻሻ ላይ እንጀራውን የሚያገኝ    

Published in ጥበብ
Page 10 of 19