ረጅም አመታት በውጭ አገራት ያሳለፈው ገጣሚ ሃይሉ ገ/ዮሃንስ (ጎሞራው)፤ ባደረበት ህመም በሚኖርባት ስዊድን በሚገኝ ሆስፒታል ህክምና ሲከታተል ቆይቶ፣ ባለፈው ማክሰኞ በተወለደ በ79 አመቱ ከዚህ አለም በሞት ተለየ፡፡እ.ኤ.አ በ1935 በአዲስ አበባ የተወለደው ሃይሉ፤ የቤተክህነት ትምህርት እየተከታተለ ያደገ ሲሆን በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት እስከ ሁለተኛ ደረጃ ከተማረ በኋላ፣ በቅድስት ስላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የስነ መለኮት ትምህርት ተከታትሏል፡፡
በመቀጠልም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናት ተቋም ገብቶ የተማረው ገሞራው፤ በዩኒቨርሲቲ ቆይታው በግዕዝ፣ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች የተለያዩ የስነጽሁፍ ስራዎችን በማቅረብ ታዋቂነትን አትርፏል፡፡ በዩኒቨርሲቲው ይካሄድ በነበረ የግጥም ውድድር ላይ ባሸነፈበት “በረከተ መርገም” የተሰኘ ግጥሙም  ይታወቃል፡፡ በተማሪዎች እንቅስቃሴ ውስጥ በስፋት ይካፈል የነበረው ገጣሚው፤ ከዚሁ ጋር በተያያዘም ከዩኒቨርሲቲው ተባርሯል፡፡
በ1957 ዓ.ም የጻፈው “በረከተ መርገም” የተሰኘ ግጥሙ በ1966 ዓ.ም የታተመለት ሲሆን በ1980 ዓ.ም በስዊድን በድጋሚ ታትሞለታል፡፡ በአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ወቅት ለንባብ ባበቃው “አንድነት” የሚል አነስተኛ መጽሃፍ ሳቢያ ለእስር የተዳረገው ሃይሉ፣ ከእስር ከተፈታ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ በቴክኒክና በመምህራን ማሰልጠኛ ኮሌጆች በመምህርነት አገልግሏል፡፡
ወደ ቻይና በማምራትም በቤጂንግ ዩኒቨርሲቲ የቻይናን ስነጽሁፍ ያጠና ሲሆን የቻይንኛ-አማርኛ መዝገበ ቃላትና የቻይንኛ-እንግሊዝኛ የሃረጋት መጽሃፍ አዘጋጅቷል፡፡ ወደ ኖርዌይ ሄዶ የፖለቲካ ጥገኝነት ካገኘ በኋላ ለጥቂት ጊዜያት ቆይቶ ወደ ስዊድን በመጓዝ ኑሮውን በስቶክሆልም አድርጎ ቆይቷል፡፡

Published in ጥበብ

ኮንቲኔንታል የተባለው ታዋቂ የአሜሪካ ነዳጅ አምራች ኩባንያ ባለቤት ባለጸጋው ሃርሎድ ሃም፤ ከ26 አመታት በፊት ከባለቤታቸው ሲ አን ሃም ጋር የመሰረቱትን ትዳር በፍቺ በማፍረሳቸው፣ ለቀድሞ ሚስታቸው  የ1 ቢሊዮን ዶላር ካሳ እንዲከፍሉ መወሰኑን ሲኤንኤን ዘገበ፡፡በጥንዶቹ መካከል ሊታረቅ የማይችል ቅራኔ  መኖሩ ለፍቺው ምክንያት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤  ጉዳይ ሲመረምር የቆየው ፍርድ ቤት በሃርሎድ ሃም ላይ የ1 ቢሊዮን ዶላር ካሳ ቅጣት እንደጣለባቸው  አመልክቷል፡፡
የባልና ሚስቱ ፍቺ በአለማችን ታሪክ ከፍተኛ የካሳ ክፍያ የሚፈጸምበት እንደሚሆን  የገለጸው ዘገባው፤ የ68 አመቱ ባለጸጋ የ20.2 ቢሊዮን ዶላር ሃብት ያካበቱ ቢሊየነር መሆናቸውን  ጨምሮ አስታውቋል፡፡
ግለሰቡ የካሳውን አንድ ሶስተኛ በመጪው አንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንዲከፍሉና፣ ቀሪውን ቢያንስ በየወሩ 7 ሚሊዮን ዶላር እየከፈሉ በሂደት እንዲያጠናቅቁ ተፈርዶባቸዋል፡፡ ጥንዶቹ በትዳራቸው ሁለት ሴት ልጆችን እንዳፈሩ ዘገባው አስታውሷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

          የዛሬ ሳምንት በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ዋና ከተማ ሰመራ ውስጥ “አግዳ” የተባለ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴልና ሪዞርት ተመርቋል፡፡ ሆቴሉ አሁንም ግንባታው ያልተጠናቀቀ ቢሆንም እስካሁን 260 ሚሊዮን ብር እንደወጣበት ተገልጿል፡፡
ግንባታው ሲጠናቀቅ 200 አልጋዎች ይኖሩታል የተባለው ባለ አምስት ኮከብ ሆቴል፤ በአሁኑ ሰዓት በስራ ላይ ያሉ 60 የመኝታ ክፍሎች፣ ደረጃቸውን የጠበቁ ሶስት ባሮችና ሁለት ሬስቶራንቶች፣ አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ትልቅ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ለአምስት ኮከብ ሆቴል የሚመጥን የመዋኛ ገንዳ፣ ሲኒማ ቤት፣  ነፋሻማ የሆነ የተንጣለለ ግቢና ሌሎች አገልግሎቶችም ተሟልቶለታል፡፡ ለ150 ጊዜያዊና ለ60 ቋሚ ሰራተኞች የስራ እድል የፈጠረው አግዳ ሆቴልና ሪዞርት፤ በአሁኑ ሰዓት የአገር ውስጥና ውጭ ጎብኚዎችን በብቃት በማስተናገድ ላይ እንደሚገኝ ተጠቁሟል፡፡
ከመዲናዋ በ560 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በሚገኝ ቦታ እንዴት 260 ሚሊዮን ብር ኢንቨስት ለማድረግ ደፈሩ የሚል ጥያቄ ያቀረብንላቸው አቶ አሊ፤ “በዚህ ቦታ ላይ ኢንቨስት ላደርግ ከወዳጅ ዘመድ ጋር ስመካከር እንደፈተና የቀረበልኝ አሁን የተነሳው ጥያቄ ነው፤ ብዙ ወዳጅ ዘመድ በስጋትና በጭንቀት ከርመው አሁን ለምረቃው ሲያዩት እፎይ ብለዋል” ይላሉ፡፡
“በዚህ ቦታ ላይ ይህንን ሆቴል ለመገንባት ስነሳ ትርፍና ኪሳራ አስልቼ፣ ከቢዝነስ አኳያ አይቼው ሳይሆን ለክልሉና ለህዝቡ ያለኝን ፍቅር ለመግለፅ ነው፡፡ ለክልሉና ለህዝቡ ያለን ፍቅር ከእኔ እድሜ የጀመረ ሳይሆን ከአያቶቼ እየተወራረሰ የመጣ ነው” ያሉት ትግራይ ተወልደው ያደጉት የ44 ዓመቱ ጎልማሳ አቶ አሊ ግደይ፤ እንዲያው በደረቁ ህዝቡንም ክልሉንም እወዳለሁ ከማለት አንድ ቁምነገር ያለው ስራ ሰርቶ በተግባር ፍቅርን መግለፅ ተገቢ በመሆኑ ይህንን ሆቴል መገንባታቸውን፣ በዚህም ደስተኛ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ ከሆቴል ግንባታው በፊት በዚሁ አካባቢ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ትልቅ ተሳትፎ እንደነበራቸውም ገልፀዋል፡፡
“እርግጥ ነው እኛ በዚህ ከተማ ግንባታ ስንጀምር አየር መንገድ አልነበረም፤ የተንዳሆ ስኳር ፋብሪካ ግንባታ ፕሮጀክትም ገና ውጥን ነበር፣ ደረቅ ወደብም አልነበረም” ያሉት ባለሃብቱ፤ በአሁኑ ሰዓት ከላይ የተጠቀሱት በሙሉ ስራ በመጀመራቸው የቱሪስት ፍሰቱ መጨመሩንና ለበጎ ስራ ብለው የጀመሩት ስራ አሁን ከቢዝነስ አኳያ ቢታሰብም የሚያስከፋ እንዳልሆነ ይናገራሉ፡፡ የክልሉ መንግስት ተባባሪነት ለዚህ እንዳደረሳቸው የተናገሩት ባለሀብቱ፤ ከ8 ዓመት በፊት መሬቱን ከሊዝ ነፃ በሆነ መንገድ እንዳገኙም አስታውሰዋል፡፡
የአፋር ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኢስማኤል አሊሴሮ በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ በሆቴሉ እዚህ መድረስ የተሰማቸውን ደስታ ገልፀው፤ “እኛ የማንወደው መሬት ወስዶ አጥሮ የሚያስቀምጥ እንጂ በአግባቡ ለሚሰራ ሰው የፈለገውን ያህል መሬት ወስዶ እንዲሰራ እንፈልጋለን” ካሉ በኋላ፣ የእኚህን ባለሀብት ብርታትና ጥንካሬ እንደ ምሳሌ በመቁጠር፣ ፍላጎት ያለው ኢንቨስተር በየትኛውም ዘርፍ ኢንቨስት እንዲያደርግ ግብዣ አቅርበዋል፡፡
በሆቴሉ ምረቃ እለት ያገኘናቸው ነጋሽ ካህሳይ አባይ የተባሉ የእድሜ ባለፀጋ፤ ሆቴሉን ለመመረቅ ከአዲስ አበባ መሄዳቸውንና የአቶ አሊ ግደይ ዘመድ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ “አሊ በፊውዳል ስርአት ጊዜ የባላባት ልጅ ነበር፤ አባቱ አቶ ግደይ ፈጣንና የስራ ሰው ነበሩ፤ የአባቱን ፈለግ ተከትሎ ለዚህ በመድረሱ ደስተኛ ነኝ” ብለዋል፡፡ “አፋር የእናቴ አገር ስለሆነ በደንብ አውቀዋለሁ፤ እዚህ ቦታ ግንባታ ሲጀምር ይሳካ ይሆን የሚል ስጋት ነበረኝ፤ እድሜ ሰጥቶኝ ይህን በማየቴ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል” ብለዋል - አዛውንቱ፡፡
የአራት ልጆች እናትና የአቶ አሊ ባለቤት የሆኑት ወ/ሮ አዜብ ሃጎስ በበኩላቸው፤ ሆቴሉ በዚህ ቦታ ይሰራ ሲባል ቀላል መስሏቸው እንደነበር፤ ነገር ግን ከተጀመረ በኋላ በርካታ ፈተናዎች እንደገጠሟቸው ይናገራሉ፡፡ “ባለፉት ስምንት አመታት ልጆችን ለብቻ ማሳደግ፣ አዲስ አበባ የሚገኘውን የከባድ ማሽነሪዎች አከራይ ድርጅት መምራት፤ ባለቤቴ  በሳምንት ሁለት ጊዜ ከአዲስ አበባ ሰመራ፣ ከሰመራ አዲስ አበባ መመላለሱ ከባድ ፈተና ቢሆንብኝም እንደምንም ተቋቁሜ ሆቴሉ ለዚህ በመብቃቱ ከልክ በላይ ደስታ ተሰምቶኛል” ብለዋል፡፡
አቶ አሊ ግደይ፤ ለሆቴሉ ግብአት የሚሆኑ የጓሮ አትክልቶች፣ የስጋና የወተት ተዋፅኦዎች ለማምረት የአግሮ ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት ፈቃድ ያወጡ ሲሆን 50ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ወስደው ለማልማት እየተዘጋጁ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡

ቦኮ ሃራም በአንድ ቀን ብቻ 209 ትምህርት ቤቶችን አቃጥሏል
ፕሬዚዳንቱ ዳግም ከተመረጥኩ ቦኮ ሃራምንና ሙስናን አጠፋለሁ ብለዋል

          ባለፈው ሰኞና ረቡዕ  ዮቤ በተባለ የናይጀሪያ ግዛት በምትገኘው ፖቲስኩም ከተማና  ኮንታጎራ በተባለች ከተማ በሚገኙ ትምህርት ቤትና ኮሌጅ ላይ በአጥፍቶ ጠፊዎች በተፈጸሙ የቦንብ ፍንዳታዎች  የሞቱትን ከ52 በላይ ተማሪዎች ጨምሮ፣ በአገሪቱ ባለፉት 18 ወራት ከ255 በላይ ተማሪዎች በአሸባሪዎች እንደተገደሉ ተዘገበ፡፡የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን፤ በተደጋጋሚ የሽብር ጥቃት ዜጎችን ለህልፈት በመዳረግ ላይ የሚገኘውን ቦኮ ሃራም የተባለ ቡድንና ሙስናን ከአገሪቱ ለማጥፋት በሚል ለሁለተኛ ዙር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚወዳደሩ አስታውቀዋል፡፡
የምዕራባውያን ትምህርት መቆም አለበት የሚል አቋም ይዞ የሚንቀሳቀሰው ቦኮ ሃራም የተባለ የአሸባሪዎች ቡድን፣ በተለይ ካለፈው አመት ግንቦት ወር ጀምሮ በአገሪቱ የተለያዩ ግዛቶች በሚገኙ ትምህርት ቤቶች የሽብር ጥቃት መፈጸሙን አጠናክሮ መቀጠሉን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለፈው ሰኞና ረቡዕ የተከሰቱት ጥቃቶችም በዚሁ አሸባሪ ቡድን እንደተፈጸሙ ይገመታል ብሏል፡፡
ባለፈው ሚያዝያ ወር በቺቦክ ከተማ ወደሚገኘው ትምህርት ቤታቸው በማምራት ላይ የነበሩ 276 ናይጀሪያውያን ልጃገረዶችን የጠለፈው አሸባሪ ቡድኑ፤ በተማሪዎች ላይ ግድያ መፈጸም ከጀመረ መቆየቱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ቦኮ ሃራም ከሳምንታት በፊት ካንኮ በተባለች ከተማ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ በነበሩ ተማሪዎች ላይ በከፈተው ተኩስ፣ 13 ያህል ተማሪዎችን መግደሉን ያስታወሰው ዘገባው፣ በከተማዋ የተለያዩ ክፍሎች ሌሎች 15 ተማሪዎችን እንደገደለም  አክሎ ገልጧል፡፡
ባለፈው የካቲት ወር በዮቢ ግዛት በሚገኝ የመንግስት ኮሌጅ ላይ ባደረሰው ጥቃት 59 ተማሪዎች መሞታቸውን፤ በመስከረም ወር ላይ በግብርና ማሰልጠኛ ተቋም 44 ተማሪዎችንና መምህራንን መግደሉን፤ በሃምሌ ወር በማሙዱ ከተማ አዳሪ ትምህርት ቤት ባደረሰው ጥቃት 29 ተማሪዎችና መምህራን መሞታቸውን አስታውሷል፡፡ ቦኮ ሃራም ባለፈው ወር፣ 209 ትምህርት ቤቶችን ማቃጠሉንና በሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር የንብረት ውድመት መፈጸሙን ዘገባው አመልክቷል፡፡ ለቦኮ ሃራም ጥቃት ተገቢውን ምላሽ አልሰጡም በሚል በዜጎቻቸው እየተተቹ ያሉት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉድላክ ጆናታን በበኩላቸው፤ ቦኮ ሃራምንና ሙስናን ከአገሪቱ የማጥፋት አላማቸውን ከግብ ለማድረስ ለሁለተኛ ዙር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚወዳደሩ ማስታወቃቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
አሸባሪ ቡድኑ አገሪቱንና ዜጎቿን ለማጥፋት ቆርጦ ተነስቷል ያሉት ጆናታን፣ ከተመረጡ ቡድኑ ያገታቸውን ልጃገረዶች እንደሚያስለቅቁና የሽብር ሰንሰለቱን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደሚበጣጥሱ ቃል ገብተዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በቻይና የመብራት ኃይል ኃላፊው ሰክረው ለ6 ሰዓት መብራት ጠፋ
እኛ አገር ማንም ሰው ሳይሰክር በቀን መቶ ጊዜ መብራት ይጠፋል    

             ሰሞኑን በምስራቃዊ ቻይና ሄናን በተባለች ግዛት የተሰማው ወሬ ጉድ የሚያሰኝ ነው፡፡ የመብራት ኃይል ኩባንያ ኃላፊው ድብን ብለው ሰክረው፣ ከፊል አገሪቱ ለ6 ሰዓት በጨለማ ተዋጠች ይለናል ቢቢሲ፡፡ (“አልሰሜን ግባ በሉት” አሉ!) እኛ አገር እኮ ማንም ሳይሰክር ላለፉት 6 ዓመታት መብራት ሲጠፋብን ከርሟል፡፡ (ቢቢሲን ታዘብኩት!)
እርግጥ ነው ቻይና በኢኮኖሚ አቅሟ ዓለምን በሁለተኛነት እየመራች እንደሆነ አይጠፋንም፡፡ እኛም ብንሆን ግን የዋዛ አይደለንም፡፡ ላለፉት 8 ዓመታት ባለ ሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ እድገት አስመዝግበናል፡፡ (ያውም እኮ ያለ መብራት!) አንዳንድ ጨለምተኛና የኒዮሊበራል አቀንቃኞች እድገቱን ባይቀበሉትም አይጨንቀንም፡፡ ለምን ቢሉ---እነ አይኤምኤፍ እንደሆነ ተቀብለውታል፡፡ የምዕራብ ሚዲያዎችም ዘግበውታል፡፡ ኦባማም ተደምመዋል፡፡ (አለዚያማ “የምርጫ ተሞክሮ እንለዋወጥ” አይሉም ነበራ!)
 ቢቢሲ ግን ይሄን እውነታ አላወቅሁም ለማለት-- የእኛን የ6 ዓመት የኃይል መቆራረጥ ትንፍሽ ሳይል የቻይናን ለመዘገብ ተጣደፈ፡፡ (የሚዲያ ሽፋን በዘመድ ሆነ እንዴ?) ከምሬ ነው የምላችሁ… 6 ዓመት በኃይል መቆራረጥ ከተንገላታነው ይልቅ የሚዲያ ሽፋን ማጣታችን በጣም ያበግናል፡፡ (ወይ ከመብራት ወይ ከሚዲያ አልሆንም!)
በነገራችን ላይ በቻይና መብራቱ ከመጥፋቱ በላይ የሚያስገርመው አጠፋፉ ነው፡፡ እንደኛ አገር የህዝብ ቁጥር ስለጨመረ ወይም በሙስና ፎርጅድ ትራንስፎርመር ስለተገዛ አሊያም ፊውዝ ስለተቃጠለ አይደለም ኤሌክትሪክ የተቋረጠው፡፡ ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ በሉ ስሙኝ የሆነውን ልንገራችሁ፡፡
የሄናን ግዛት የመብራት ሃይል ሰራተኞችና አለቃቸው ወደ አንድ መሸታ ቤት ጐራ ይሉና ሲጠጡ ያመሻሉ፡፡ በርካታ ሳጥን ቢራ ከጨለጡና የአልኮል መጠጦችን ከደጋገሙ በኋላ ነው ችግር የተፈጠረው፡፡ መሸታ ቤቱ አንድ ዙር በነፃ ይጋብዘን ብለው ድርቅ አሉ፡፡ መጠጥ ቤቱ ደግሞ “በምን እዳዬ?” ብሎ አሻፈረኝ ይላል፡፡ ይሄኔ ብጥብጥ ተነሳ፡፡ የመብራት ኃይል ኩባንያው ሠራተኞች እቃ ሰባበሩ፡፡ በዚህ ብቻ ግን አላበቃም፡፡ የኩባንያው ኃላፊ የመጠጥ ቤቱን መብራት እንደሚያስቆርጥባቸውም ዛተ፡፡ ዛቻውንም ወዲያው ተግባራዊ አደረገው፡፡(ዛቻ ብቻማ የፈሪ ነው!) እዚያው እያሉ ወደ መ/ቤቱ ይደውልና ለጥገና በሚል የኤሌክትሪክ ሃይል እንዲቋረጥ ያዛል፡፡ ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላም መሸታ ቤቱ ብቻ ሳይሆን  ከፊል አገሪቷ በጭለማ ተዋጠች፡፡ (“ለኃጥአን የመጣ ለጻድቃን ይተርፋል” አሉ!)
 የሃይል መቋረጡን ተከትሎም በመንግስት ባለቤትነት የሚመራው የኤሌክትሪክ ኩባንያ ይቅርታ ጠየቀ (የቻይና ይቅርታ እጅ በእጅ ነው!) ከዚያ ወደ እርምጃ ገባ፡፡ መጀመሪያ መብራቱ እንዲቋረጥ ያዘዘውን ሥራ አስኪያጅ ከስራው አባረረው፡፡ (እኛ አገር 6 ዓመት ጠፍቶብንም የተባረረ ሃላፊ የለም!) አንድ ሠራተኛ ለሁለት ዓመት ከስራ የታገደ ሲሆን ሌሎች መሸታ ቤቱን የበጠበጡ የመብራት ኩባንያው ሰራተኞችም ከገንዘብ ቅጣት ጋር ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸዋል፡፡ (የሙስና ክስም አይቀርላቸውም!)
ነገርዬው ቢያስገርምም ከእኛ አገሩ ግን አይብስም፡፡ እዚያስ አለቅዬው ሰክሮ ነው መብራት ያስጠፋው፡፡ እኛ ጋ እኮ እንኳን አልኮል ውሃ ሳይቀምሱ ነው ማጥፋት የሚጀምሩት፡፡ አንድያውን እንደ ቻይናዎቹ ጠጥተው ቢሆን እኮ ደህና ሰበብ እናገኝላቸው ነበር፡፡ (ሰበብም መላም ያጣንለት ችግር ሆነ!)
እኔ የምለው ግን የኃይል መቆራረጡ ሊሻለው ነው ስንል ብሶበት አረፈው አይደል፡፡ ባለፈው ሳምንት በተከታታይ ለ4 ቀናት መብራት የጠፋባቸው ሰፈሮች ነበሩ፡፡ መንግስት ደግሞ የግድ መልስ መስጠት ስላለበት መልስ ሰጥቷል (ዝም ነበር የሚሻለው!)
እናላችሁ---የመንግሥት ጉዳዮች ኮሙኒኬሽን ፅ/ቤት ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ባለፈው ማክሰኞ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ የሃይል መቆራረጡ የተከሰተው በጣና በለስ ማሰራጫ ጣቢያ በተፈጠረ የባትሪ ችግር እንደሆነ ጠቁመው፤በአሁኑ ወቅት ግን ችግሩ መቀረፉን ተናግረዋል፡፡ (ማረጋገጫ ሳይሰጡን እንዴት እንመናቸው?!) አጠቃላይ የሃይል መቆራረጥ ችግርን አስመልክቶ በሰጡት ምላሽም፤ ችግሩ ከማሰራጫ መስመር ጋር የተያያዘ እንደሆነና በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ ይፈታል ተብሎ እንደሚገመት ተናግረዋል፡፡ (እኔ መንግስትን ብሆን፣ እንደ አርቲስቱ “ሆድ ይፍጀው” ነበር የምለው!) ሚኒስትሩ ሌላው ቢቀር እንኳን ምነው ትንሽ ጊዜውን ገፋ ቢያደርጉት?! (ሁለት ወር ከሚሉ ሁለት ዓመት!) “ልማታዊ መንግስታችን” ቃል አባይ ነው ለማለት እኮ አይደለም (ምን ቁርጥ አድርጎኝ!) የዘንድሮ ጊዜ እንደ ድሮ አይደለም ብዬ እኮ ነው፡፡ ወዲያው ነው ከች የሚለው (የድሮ ሁለት ወር ዘንድሮ ሁለት ሳምንት ማለት ነው!) አልተጠናም  እንጂ ሳስበው የጊዜ “ግሽበት” ሳይከሰት አልቀረም፡፡
እኔ የምለው… በአገራችን 18 ሚሊዮን ህዝብ በቀላልና መካከለኛ የአዕምሮ ጤና ችግር የተጠቃ መሆኑን ሰምታችኋል? ይሄ ብቻ አይደለም፡፡ ከ1ሚ. በላይ ሰዎች በከፍተኛ የአዕምሮ ጤና ችግር እየተሰቃዩ መሆኑንስ? እንደተባለው ከሆነ እኮ፣ ከ1ሚ. በላይ ህዝብ አሁኑኑ ተኝቶ ህክምና መጀመር ያለበት ነው፡፡ ክፋቱ ግን ድሃ ነን፡፡ ለአእምሮ ህመምተኞች በአጠቃላይ ያለው አልጋ ከ700 በታች ነው ተብሏል፡፡ የሃኪሙ ቁጥር ደሞ ስንት እንደሚሆን አስቡት፡፡ (ከሃኪም ይልቅ ፖለቲከኛ፣ ከሆስፒታል አልጋዎች ይልቅ የፖለቲካ ፓርቲዎች የበዙባት አገር!)
እናላችሁ … ይሄን መረጃ ከሰማሁ በኋላ ምን አልኩ መሰላችሁ? ለአገራችን ዘርፈ ብዙ ችግሮች መንስኤው የአዕምሮ ጤና ችግር ቢሆንስ? (ከሚታከመው የማይታከመው ይበልጣል!) ይታያችሁ … እንዲህ ዓይነቶቹ ሰዎች ስልጣኑን፣ ፖለቲካውን፣ ተቋማቱን፣ ወዘተ … የመቆጣጠር ዕድል ባገኙ ጊዜ ምን እንደሚፈጠር! ግልፅ ነው፡፡ ውጥንቅጥ፣ ለማመን የሚከብዱ ክስተቶች፣ ለማሰብ የሚቸግሩ ውሳኔዎች፣ ግራ የተጋቡ እርምጃዎች … በአጠቃላይ ጤንነት የጎደላቸው እንቅስቃሴዎች በአገሪቱ ላይ ይነግሳሉ፡፡ (ደግሞም ነግሰዋል እኮ!) ለምን በማስረጃ እያስደገፍን አናያቸውም፡፡ ከቅርቡ እንጀምር፡፡
ባለፈው እሁድ ይመስለኛል፡፡ በከተማዋ የሚታወቁ የታክሲ መሳፈሪያ ፌርማታዎች ድንገት ተቀያይረው ተገኙ ተባለ፡፡ ይታያችሁ---በሚዲያ አልተነገረም፡፡ የታክሲ ሹፌሮችና ተሳፋሪዎች አልሰሙም፡፡ ፌርማታዎቹን የቀያየረው ወገን አልታወቀም፡፡ (“ኃላፊነቱን እወስዳለሁ” የሚል ጠፋ!) እናም … ሳምንቱ እንዲሁ ሲታመስ---ነዋሪዎችም ሲንገላቱና ሲያማርሩ ሰነበቱ፡፡ ጉዳዩ ይመለከተዋል የተባለው የአዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት ቢሮ ሲጠየቅ ምን ቢል ጥሩ ነው? “ችግሩን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተመካከርን ነው” (ችግር እየፈጠሩ ምክክር መቀመጥ ተጀመረ?)
እስቲ ደግሞ  ብዙ የጤና የማይመስሉ ነገሮች ወደምንታዘብበት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጎራ ደረስ ብለን እንመለስ፡፡ (ጦቢያ የተቃዋሚዎችም እኮ ናት!) እኔ የምለው---መኢአድ ውስጥ ምንድነው የተፈጠረው? መፈንቅለ መንግስት እየቀረ ነው በሚባልበት ጊዜ፣የፓርቲው የቀድሞ ፕሬዚዳንት “መፈንቅለ ሥልጣን” ተፈጸመብኝ እያሉ እኮ ነው (ኢህአዴግ በሳቅ ነው የሚሞተው!) ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት፤ በድርጊቱ “የፓርቲው የበላይ ጠባቂ” የኢንጂነር ኃይሉ ሻውል እጅ አለበት፡፡ እኔን አውርደው ለ4 ዓመት ከፓርቲው ታግደው የቆዩትን እነ ማሙሸትን ሥልጣን አሲዘዋል ብለዋል- ባለፈው ሳምንት በተካሄደው የፓርቲው ጉባኤ ከስልጣን የወረዱት አቶ አበባው መሃሪ፡፡ እኔን የገረመኝ ከሥልጣን መውረዳቸው ሳይሆን   የወረዱበት መንገድ ነው፡፡በነገራችን ላይ “የፓርቲው የበላይ ጠባቂ” ማለት ምን ማለት እንደሆነ አልገባኝም፡፡ “ሹም ሹር” የሚያካሂድ ማለት ነው እንዴ? (የቀድሞውን ፕሬዚዳንት አባባል ይዤ ነው!) ደግሞ እኮ ሌሎቹ ፓርቲዎቹ ያላቸው አይመስለኝም፡፡ የመኢአድ ልዩ ቀለም ሳይሆን አይቀርም፡፡ ይሄን “የፓርቲ የበላይ ጠባቂ” ጉዳይ ወደ አገር ከፍ ስታደርጉት ምን ይሆናል መሰላችሁ? “የኢትዮጵያ  የበላይ ጠባቂ” እናም--- አሁን ለምሳሌ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከስልጣን ሲወርዱ “የኢትዮጵያ የበላይ ጠባቂ” ተብለው ቢሾሙ ብላችሁ አስቡ፡፡ (ፈረንጅ “ዊርድ” የምትለዋን ቃል የሚጠቀመው እንዲህ ያለ ነገር ሲገጥመው ይመስለኛል!)
ለማንኛውም ግን ----ብዙ የጤንነት የማይመስሉ ነገሮች እያየን ነው፡፡ ለጊዜው መፍትሄው ምን መሰላችሁ? የዓለም ጤና ድርጅት የሥነ አእምሮ ባለሙያዎች ድጋፍ እንዲሰጠን መማጸን ብቻ ነው፡፡

ናይል ኢንሹራንስ አክሲዮን ማህበር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከምንጊዜም የላቀ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ፡፡ የኩባንያው የዳሬክተሮች ቦርድ ሊቀ መንበር አቶ ማስረሻ ወ/ሥላሴ ሰኔ 30 ቀን የተዘጋውን የ2014 ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለባለ አክሲዮኖች ባቀረቡበት ወቅት፣ ኩባንያው፣ ከምስረታው ጀምሮ ባለፉት 20 ዓመታት አስመዝግቦ የማያውቀውን 64,845,197 ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ገልጸው፤ ይህም ትርፍ የኩባንያው የተጣራ ሀብት 35 በመቶ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
ባለፈው በጀት ዓመት ከጠቅላላ ኢንሹራንስ 300 ሚሊዮን 433 ሺህ 888 የአረቦን ገቢ መሰብሰቡን ጠቅሰው፤ ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ17 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን፣ ለዚህም ዕድገት መገኘት ኢኮኖሚው ያሳየውን አዎንታዊ ዕድገትና ኩባንያው በተለያዩ አሰራሮች ላይ የወሰዳቸውን የማሻሻያ እርምጃዎች በምክንያትነት ጠቅሰዋል፡፡
ኩባንያው በበጀት ዓመቱና ከዚያ በፊት ባሉት ዓመታት ትላልቅ መጠን ያላቸው የካሳ ጥያቄዎች ቀርበው ክፍያ መፈፀሙን የጠቀሱት አቶ ማስረሻ፤ ባለፈው ዓመት ከጠለፋ ዋስትና የተገኘው ሂሳብ ተቀንሶ 152 ሚሊዮን 539 ሺህ 344 ብር ካሣ መከፈሉንና ይህም ከካቻምናው ጋር ሲነፃፀር የ10 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ተናግረዋል፡፡ ከበጀት ዓመቱ የተጣራ ትርፍ 64, 845, 197 ብር ውስጥ የዓመቱ ህጋዊ መጠባበቂያ 6, 484, 520 ብር እንዲሁም ለዳይሬክተሮች ቦርድ የሚከፈለው 1,780,647 ብር ከተቀነሰ በኋላ ቀሪው 56,672,531 ብር የኩባንያውን የተከፈለ ካፒታል ከ100 ሚሊዮን ወደ 200 ሚሊዮን ብር እንዲያድግ ጠይቀው የባለ አክሲዮኖቹን ይሁንታ አግኝተዋል፡፡ በዓመቱ በኢንሹራንስ ኩባንያዎች መካከል የነበረው በዋጋ ላይ ያተኮረ ውድድር መጨመር፣ በኢንሹራንስ ኢንዱስትሪው አፈጻጸም ላይ የታየ ችግር እንደሆነ የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ የኢንሹራንስ ኩባንያዎችን አነስተኛነት ተከትሎ የአዳዲስ ኩባንያዎች መቋቋም፣ በአረቦን ዋጋ ላይ ብቻ ያተኮረውን ፉክክር የበለጠ ያንረዋል የሚል ስጋት እንዳላቸው ሳይገልጹ አላለፉም፡፡   

በኢትዮጵያ ያሉ የዲፕሎማት ሚስቶች ቡድን በሚቀጥለው ቅዳሜ ዓመታዊውን የበጎ አድራጎት ባዛር በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡
ከ25 ዓመት በፊት የተመሰረተው የዲፕሎማት ሚስቶች ቡድን፣ ከየአገሮቻቸው እያስመጡ የሚሸጧቸውን የተለያዩ ቁሶች ገቢ፣ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚውል የዘንድሮው የቡድኑ ፕሬዚዳንት በአፍሪካ ህብረት የአሜሪካ አምባሳደር ባለቤት ዶ/ር ሊላይ ስላሴ ገልጸዋል፡፡
ሴቶቹ ባዛሩን የሚያዘጋጁት በየተራ በተለያዩ ኤምባሲዎች ግቢና በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ እንደነበር የጠቀሱት ፕሬዚዳንቷ፣ በባዛሩ የሚሳተፉ የአገር ውስጥና የውጭ እንግዶች ቁጥር እየጨመረ ስለሄደ፣ ሁሉንም ለማሳተፍ ከ2002 ጀምሮ ባዛሩ በሚሌኒየም አዳራሽ እየተካሄደ መሆኑንና ባለፈው ዓመት ከ10ሺህ በላይ ሰዎች መጎብኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ዓመት የባዛሩን ማዘጋጃ ስፍራ ክፍያና የሥራ ማስኬጃ ወጪዎች በሙሉ ስፖንሰሮቻችን ስለሸፈኑልን ከመቶ ፐርሰንት ትርፍ ጋር ከባዛሩ ያገኘነውን ከሁለት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺህ ብር በላይ በመላ አገሪቷ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ከ25 በላይ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ሰጥቶናል ብለዋል፡፡
ሚስ ኤሪካ አሸር የድጋፍ ጠያቂ ድርጅቶች ፕሮፖዛል አጣሪ ኮሚቴ ኃላፊ ሲሆኑ በየዓመቱ ከመላው የአገሪቱ ክፍሎች፣ በርካታ የተለያዩ የድጋፍ ጥያቄዎች እንደሚቀርቡላቸው ጠቅሰው “የቅድሚያ ትኩረት የሚሰጣቸው ለሴቶች፣ ለህፃናትና በኢትዮጵያ እጅግ ተጠቂ ለሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ ለሚያደርጉ በጎ አድራጊ ድርጅቶች ነው” ብለዋል፡፡
የዲፕሎማት ሚስቶቹ ባለፉት ዓመታት የመማሪያ ክፍል ጥበት ላለባቸው ት/ቤቶች፣ የመማሪያና የመፀዳጃ ክፍሎች ግንባታ፣ ለቁሳቁስና ለመጻሕፍት መግዣ እንዲሁም ለክሊኒኮች የማዋለጃ አልጋና የሕክምና መሳሪያዎች ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
የውሃ እጥረት ላለባቸው ማህበረሰቦች የውሃ ጉድጓድ ማስቆፈራቸውን፣ መኖሪያ ለሌላቸው አረጋውያን ቤት መስጠታቸውን፣ ለጎዳና ተዳዳሪዎች የምክርና የሕይወት ክህሎት መስጫና ከስጋ ደዌ በሽታ ለዳኑ አረጋዊ ሴቶች የሽመና ማዕከል ማቋቋማቸውን፣ እንዲሁም ለአካል ጉዳተኛ ሕፃናት ለቀዶ ሕክምና አገልግሎት ድጋፍ ማድረጋቸውን የዘንድሮው የቡድኑ ተወካዮች አስረድተዋል፡፡
የዛሬ ሳምንት በሚሌኒየም አዳራሽ ከጧቱ 4 እስከ 10 ሰዓት በሚቆየው ባዛር፣ ከ60 በላይ ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች እንደሚሳተፉ ይጠበቃሉ ያሉት ፕሬዚዳንቷ፤ ከአምናው የበለጠ ገቢ ለማሰባሰብ ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡
የባዛሩ ተሳታፊዎች በአገራቸው የታወቀና ለየት ያለ ነገር ይዘው በመቅረብ ይሸጣሉ ያሉት ዶ/ር ሊላይ፤ የተለያዩ ጌጣ ጌጦች፣ የየአገሮቹ ምግቦች፣ መጠጦችና የተለያዩ ምርቶች ይቀርባሉ ብለዋል፡፡ በዚሁ ቡድን ድጋፍ የተደረገላቸው ከ20 በላይ የማህበረሰብ ድርጅቶች ምርቶቻቸውን አቅርበው እንደሚሸጡም ታውቋል፡፡
የባዛሩ መግቢያ ትኬት ከሕዳር 1 እስከ 12 ድረስ በሂልተን ሆቴል ከጧቱ 4 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ለአዋቂዎች በ30 ብር፣ ለሕፃናት በ10 ብር እየተሸጡ ነው፡፡


ከ1ሚ. በላይ ህዝብ ተኝቶ መታከም በሚያስፈልገው የአዕምሮ ህመም ይሰቃያል
በአዕምሮ ህሙማን ህክምና ማዕከል ያሉት አልጋዎች ከ700 አይበልጡም


በርካታ ሰዎች የአዕምሮ ጤና ችግር እንደገጠማቸው የሚጠቁሙ ምልክቶች ቢታይባቸውም ታማሚነታቸውን አምነው ለመቀበልና ለችግራቸው መፍትሄ ለመፈለግ ፈቃደኞች እንዳልሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ አዕምሮ በተለያዩ ምክንያቶች ለጉዳት ሊዳረግና የተለመደ ተግባሩን መወጣት ሊሳነው ይችላል፡፡ ለአዕምሮ መታወክ መንስኤ ሊሆኑ ከሚችሉ ጉዳዮች መካከል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ፣ ስነ ልቦናዊ ውጥረቶች፣ ስደት፣ ጦርነት፣ ተገዶ መደፈር፣ አደንዛዥ እፆች፣ የመኪና አደጋ፣ ኢንፌክሽን አምጪ በሽታዎችን አለመቆጣጠር፣ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ ተማሪዎችን የሚያማክሩ የስነ ልቦና ባለሙያዎች አለመኖር… ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በቅርቡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ፣ በአዳማ ከተማ “Media and Mental Illness” በሚል ርዕስ ወርክሾፕ አዘጋጅቶ የነበረ ሲሆን በወቅቱ  የቀረቡ ጥናታዊ ፅሁፎች እንደሚያመለክቱት፤ የአዕምሮ ጤና ችግር ለበርካታ ኢትዮጵያውያን  ስቃይና ሞት ምክንያት እየሆነ መጥቷል፡፡ በወርክሾፑ ላይ ጥናታቸውን ካቀረቡት ባለሙያዎች አንዱ የሆኑት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የአዕምሮ ሀኪምና በዩኒቨርሲቲው የአዕምሮ ህክምና ክፍል መምህር፣ ዶ/ር መስፍን አርአያን፣ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ፤ በአዕምሮ ጤና ችግር ዙርያ አነጋግራቸዋለች፡፡



የአዕምሮ ጤና ችግር ስንል ምን ማለታችን ነው?
የአዕምሮ ጤና ችግርን በሶስት ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡ ቀላል፣ መካከለኛና ከባድ ወይም በፈረንጅኛው ሳይኮሲስ የሚባለው ማለት ነው፡፡ ችግሮቹ እንደየሁኔታው የህክምና እርዳታ ሊደረግላቸው ይችላል፡፡ ቀላል የአዕምሮ ጤና ችግር የምንለው በተለያዩ ምክንያቶች አዕምሮአችን ሲወጣጠርና ሲጨነቅ የሚከሰት ሲሆን ይህ ችግር በከተማም ሆነ በገጠር ይስተዋላል፡፡ በዕለት ተዕለት ህይወታችን በሚገጥሙን ነገሮች ስንጨናነቅ ሊከሰት የሚችል ችግርም ነው፡፡ ይህ ችግር ያለባቸው ሰዎች ራሳቸውን በሚገባ ስለሚያውቁ ወደ ሀኪም ሔደው የህክምና እርዳታ ለመጠየቅ የሚችሉ ናቸው፡፡
መካከለኛ የአዕምሮ ጤና ችግር የምንለው ደግሞ የስሜት መዋዠቅ ይታይባቸዋል፡፡ አንድ ወቅት ድብርት ውስጥ ይገባሉ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ በተቃራኒው ይሆናሉ፡፡ እነዚህ በሁለት አይነት የአዕምሮ ጤና ችግር ውስጥ ያሉ ሰዎች፤ በአንድ አገር እስከ 20 በመቶ ሊደርሱ ይችላሉ፡፡ በአንዳንድ አገሮች ቁጥራቸው ከ25-40 በመቶ ሊደርስም ይችላል፡፡ ትንሹን እንኳን ወስደን በአገራችን ያለውን ሁኔታ ብናየው፣ በአሁኑ ወቅት በአገራችን ቢያንስ 18 ሚሊዮን የሚሆነው ህዝብ በቀላልና መካከለኛ የአዕምሮ ጤና ችግር የሚጠቃ ነው፡፡ ከባዱና ሳይኮሲስ እየተባለ በሚጠራው የአዕምሮ ጤና ችግር የተጠቁ ሰዎች ስለራሳቸው ያላቸው ግንዛቤ አናሳ ሆኖ እይታቸው፣ አመለካከትና የአስተሳሰብ ባህርያቸው ሲዛባ የሚከሰት ችግር ነው፡፡ ለሌሎች የማይታይን ነገር ማየት፣ ሌሎች የማይሰሙትን ድምፅ መስማት … አይነት ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች የባህርይ ለውጥም ያመጣሉ፡፡ ለምሳሌ ኬጂቢ ቦንብ ጠምዶ እየተከታተለኝ ነው ብለው ያስባሉ፡፡ ያን ግዜም ራሳቸውን ለመከላከል በሚወስዱት እርምጃ በሌሎች ሰዎች ላይ አደጋ ሊያስከትሉ ይችላሉ፡፡ ከፍተኛ የአዕምሮ ጤና ችግር ከምንላቸው ነገሮች ውስጥ አንዱ ድብርት ነው፡፡ ድብርት መዳን የሚችል ህመም ሲሆን በአግባቡ ካልታከመ ህይወትን የሚያሳጣ አደገኛ ችግር ነው፡፡ በዚህ ሳይኮሲስ እያልን በምንጠራው አደገኛ የአዕምሮ የጤና ችግር የተጠቁ ሰዎች በሆስፒታል ውስጥ ተገኝተው የቅርብ ክትትልና እርዳታ ማግኘት የሚገባቸው ናቸው፡፡ በአሁኑ ወቅትም በአገራችን 1.8 ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች በከፍተኛ የአእምሮ ጤና ችግር እየተሰቃዩ ነው፡፡ ዛሬውኑ ተኝቶ መታከም፣ ዛሬውኑ መድኀኒትና መርፌ ማግኘት፣ ዛሬውኑ የምክር ህክምና ማግኘት የሚገባቸው ናቸው፡፡
ለአዕምሮ ጤና ችግር ዋንኛ መንስኤዎች ተብለው የሚጠቀሱት ምንድናቸው?
ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሥነልቦናዊ ውጥረቶች፣ ተገዶ መደፈርና አደንዛዥ እፆችን መጠቀም ዋንኞቹ ብለን ልንጠራቸው እንችላለን፡፡ እነዚህ ነገሮች የአዕምሮ ጤና ችግር ሊያባብሱ ይችላሉ፡፡ ከዚህ በተረፈ ሰዎች የአዕምሮ ጤና ችግር በገጠማቸው ጊዜ ወደ ህክምና ተቋማት ሄዶ እርዳታ ማግኘት አለመፈለጋቸው በቀላሉ ሊድን የሚችለውን ችግር ውስብስብና አደገኛ ሊያደርገው ይችላል፡፡
አብዛኛው የአዕምሮ በሽተኛ በየቤቱና በየፀበሉ ታስሮ ነው ያለው፡፡ ጥቂቱ ደግሞ በየመንገዱና በየጎዳናው እየዞረ ነው፡፡ እነዚህ ወደ ህክምና ተቋማት ሄደው እርዳታ ማግኘት ቢችሉ ችግሩን ለማቃለል ይቻላል ብዬ አምናለሁ፡፡
ህሙማኑ ወደ ህክምና ተቋማት ቢሄዱ የህክምና እርዳታ ለማግኘት ይችላሉ? በአገራችን ምን ያህል ተቋማትስ አሉ?
በአሁኑ ወቅት በአገራችን የተለያዩ ቦታዎች የህክምና ተቋማት አሉ፡፡ ለአዕምሮ ጤና ችግር ህክምና የሚሰጡ ማለት ነው፡፡ አስተኝቶ ለማከም ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ በአጠቃላይ የግሉንም፣ ወታደራዊ የህክምና ተቋማትን ጨምሮ ከ700 የማይበልጡ አልጋዎች ናቸው ያሉን፡፡ ይህ ደግሞ ከችግሩ አንፃር ኢምንት ነው፡፡ ስለዚህም ሁላችንም ትኩረት ሰጥተን ልንሰራ የሚገባን መከላከሉ ላይ ነው፡፡ ያለበለዚያ ውጤት የለውም፡፡ እኛ ሃኪሞች ወደ ህክምና ተቋማት የመጡልንን ጥቂት ዕድለኞች ማከም ላይ ብቻ ተወስነን መቅረት አይገባንም፡፡ ሁላችንም መከላከሉ ላይ ትኩረት ሰጥተን ልንሰራ ይገባል፡፡

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 15 November 2014 11:00

ኢቦላ - የዛሬ 38 ዓመት

ቤልጂየማዊው ፒተር ፒዮ የኢቦላ ቫይረስን ለመጀመሪያ ጊዜ ከመረመሩና ለቫይረሱም ስያሜ ከሰጡ ሳይንቲስቶች አንዱ ነው፡፡ በቅርቡ  ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ የሰጠውን ቃለመጠይቅ ለጋዜጣው በሚመች መልኩ አቅርበነዋል መልካም ንባብ፡፡
“እሼ እዛው ነዋሪ ገበሬ ነው፡፡ ሞቅ ይለዋል! አንዱ ገንዘብ ሰጥቶ ምግብ በሳህን አርጎ ሂድ ወደሚስትህ ይለዋል፡፡
ይሄዳል፡፡ ግን በጨለማ በቀጭኑ ድንጋያማ የዘሙቴ መንገድ ሲሄድ ገንዘቡ ይጠፋዋል፡፡ ሳህኑን መሬት አስቀምጦ ገንዘብ
ፍለጋ ይመለሳል፡፡ ገንዘቡ የለም፡፡


ያኔ የኢቦላ ቫይረስ እንዴት እንደታወቀ ንገረኝ?
እ.ኤ.አ በ1976 በመስከረም ወር በአንዱ ቀን የሳቤና አየር መንገድ አውሮፕላን አብራሪ የነበረ ሰው በወቅቱ ዛየር በሚባለው በአሁኑ አጠራር ኮንጐ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ከሚገኝ አንድ ሃኪም በጥንቃቄ የተላከ የደም ናሙና ወደ ቤልጂየም ይዞልን መጣ፡፡ የደም ናሙናው በዛየር ያምቡኩ በተባለ ቦታ በበጎ አድራጎት ስራ ላይ ከነበሩ የቤልጂየም መነኮሳት የኣንዷ ነበር፡፡ መነኩሲቷ በማይታወቅ ህመም እየተሰቃየች የነበረ ሲሆን የደም ናሙናው ሲላክልንም ቢጫ ወባ ሊሆን ይችላል በሚል ግምት ነበር፡፡
በአሁኑ ወቅት የኢቦላ ቫይረስ ምርመራ የሚካሄደው እጅግ ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ ነው፡፡ ያኔ እንዴት ነበር?
ቫይረሱ ምን ያህል አደገኛ እንደነበር አናውቅም ነበር፡፡ በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሰራበት ላቦራቶሪም ቤልጂየም ውስጥ አልነበረም፡፡ የምንሰራው የተለመደውን ነጭ ጋውንና ጓንት አድርገን ነበር፡፡
የመነኩሲቷ የደም ናሙና ከቢጫ ወባ ጋር ግንኙነት ነበረው?
አልነበረውም፡፡ ህመሟ ከቢጫ ወባና ከታይፎይድ ጋር ግንኙነት ከሌለው ምን ሊሆን ይችላል በሚል ጥረታችንን ቀጠልን፡፡ ከተላከው ናሙና ላይ ቫይረሱን ለመለየት አይጦችንና ሌሎች የላብራቶሪ እንስሳቶችን ወጋናቸው፡፡ ለብዙ ቀናት በእንስሳቶቹ ላይ ምንም አይነት ለውጥ ስላላየን ምናልባት ናሙናው ሲመጣ በቅዝቃዜ እጦት ተጎድቶ ሊሆን ይችላል ብለን አስበን ነበር፡፡ በኋላ ግን እንስሳቱ ተራ በተራ መሞት ሲጀምሩ ናሙናው ገዳይ ነገር እንዳለው አረጋገጥን፡፡
ከዚያስ ምን አደረጋችሁ?
በትንሽ ጊዜ ውስጥ ሌላ የመነኩሲቷን ደም የያዘ ናሙና መጥቶልን በኤሌክትሮን ማይክሮስኮፕ ለመመርመር ስንዘጋጅ፣ የአለም የጤና ጥበቃ ድርጅት ናሙናውን ከፍተኛ ጥንቃቄ ወዳለበት እንግሊዝ ወደሚገኝ ላቦራቶሪ እንድንልከው መመሪያ ሰጠን፡፡ ነገር ግን አለቃዬ የፈለገው ነገር ቢሆን ስራችንን ማጠቃለል አለብን ብሎ ስላመነ ናሙናውን አልላክነውም፡፡ በወቅቱ አለቃዬ ናሙናውን ለመመርመር ሲቀበል እጁ በጣም ይንቀጠቀጥ ስለነበር፣ ከናሙናው ወደ መሬትና ወደ አንዱ ባልደረባችን እግር ላይ  ፈስሶ ነበር፡፡ ሆኖም ጓደኛችን ጠንካራ ቆዳ ጫማ አድርጎ ስለነበር ምንም አልተፈጠረም፡፡
በመጨረሻ የቫይረሱን ምንነት አወቃችሁ?
አዎ፡፡ ለመመርመር ብዙ ጊዜ የፈጀበን ቫይረስ ትልቅና ረዘም ያለ መስሎን ነበር፡፡ ቫይረሱ ከቢጫ ወባ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት የለውም፡፡ ይልቁንም በ1960ዎቹ  ጀርመን ማርበርግ ውስጥ ብዙ የላቦራቶሪ ባለሙያዎችን ህይወት ከቀጠፈው ማርበርግ ቫይረስ ጋር የሚመሳሰል ነበር፡፡
ስጋት አልፈጠረባችሁም ነበር?
ስለ ማርበርግ ቫይረስ ምንም አላውቅም ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ተማሪዎቼን ስለዚያ ወቅት ስነግራቸው ስለ ድንጋይ ዘመን የማወራላቸው ይመስላቸዋል፡፡ ላይብረሪ ሄጄ የቫይሮሎጂ አትላስ ላይ ማየት ነበረብኝ፡፡
የእኛ ውጤት በታወቀ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሲዲሲ ባወጣው መረጃ ማርበርግ እንዳልሆነ ነገር ግን ተመሳሳይነት ያለው ቫይረስ እንደሆነ ገለፀ፡፡ በወቅቱ ያምቡኩና በአቅራቢያ ባሉ ቦታዎች ብዙ ሰዎች በቫይረሱ ተጠቅተው ነበር፡፡
ወደ ዛየር ከሄዱት ሳይንቲስቶችም አንዱ ነበርክ አይደል?
አዎ፡፡ የሞተችውን መነኩሲት ጨምሮ ትንሽ ሆስፒታል ከፍተው ይሰሩ የነበሩት ቤልጂየሞች ስለነበሩ የቤልጂየም መንግስት ባለሙያ ለመላክ ሲወስን ወዲያው ፈቃደኝነቴን ገለፅኩ፡፡ ያኔ 27 አመቴ ነው፡፡ የወጣትነት ዘመን ጀብድ በለው፡፡
እንዴት ደፈርክ?
ከዚህ በፊት በአለም ያልታየ ገዳይ በሽታ የምናክም ቢሆንም ቫይረሱ ከሰውነት በሚወጡ ፈሳሾች እንደሚተላለፍ አናውቅም ነበር፡፡ ጋውንና ጓንት እንዲሁም ሞተርሳይክል አሽከርካሪዎች የሚያደርጉትን መነፅር ብቻ ነበር የምንጠቀመው፡፡ ኪንሻሳ የገዛሁትን የጋዝ ማስክ ደግሞ በሙቀቱ ምክንያት ማድረግ አልችልም ነበር፡፡ ያስፈራኝ የነበረው ነገር የደም ናሙና ስወስድ የደም ንክኪ ተፈጥሮ በበሽታው እንዳልያዝ ነበር፡፡
ግን በበሽታው ከመያዝ  አመለጥክ?
አዎ፡፡ በእርግጥ በአንድ አጋጣሚ ከፍተኛ ትኩሳት ፣ የራስ ምታትና ተቅማጥ ይዞኝ በቃ ተያዝኩ ብዬ ከክፍሌ ሳልወጣ፣ ለቀናት እንቅልፍ በአይኔ ሳይዞር አሳልፌያለሁ፡፡ በኋላ ግን እየተሻለኝ መጣ፣ የታመምኩት በጨጓራ ኢንፌክሽን ነበር፡፡ በህይወት ከሚያጋጥሙ ፈተናዎች የተሻለው ነው፡፡ ሞት ሲመጣ በአይንህ ታየዋለህ፤ ነገር ግን ለመዳን እድል አለ፡፡
ለቫይረሱ ስያሜ ከሰጡት ተመራማሪዎች አንዱ አንተ ነህ፡፡ ለምን ኢቦላ ተባለ?
ስያሜው በተሰጠበት ምሽት የተመራማሪ ቡድኑ አንድ ላይ እየተወያየ ነበር፡፡ ቫይረሱ በተከሰተበት በያምቡኩ መሰየሙ ቦታውን እስከ ወዲያኛው ያገለዋል ብለን አመንን፡፡ እናም አሜሪካዊው የቡድኑ መሪ  በአቅራቢያችን በሚገኘው ወንዝ ይሰየም አለ - ፊትለታችን ከተንጠለጠለው ካርታ ላይ የኢቦላን ወንዝ ተመልክቶ፡፡ ነገር ግን የተሰቀለው ካርታ ትንሽና የተዛቡ ነገሮች ነበሩበት፡፡ ኢቦላም በአቅራቢያ የሚገኝ ወንዝ እንዳልሆነ ብናረጋግጥም ስያሜው ግን ኢቦላ እንደሆነ ቀረ፡፡
ለቫይረሱ መዛመት የቤልጂየም መነኩሲቶች ድርሻ አለበት ይባላል...
በወቅቱ መነኩሲቶቹ በሚሰሩበት ሆስፒታል ለነፍሰጡር ሴቶች የቫይታሚን ክትባት ይሰጡ ነበር፤ ነገር ግን የመርፌው ንፅህና የተጠበቀ አልነበረም፡፡ በዚህም ምክንያት ብዙ ነፍሰጡሮች በቫይረሱ እንዲያዙ አድርገዋል፡፡ በቅርቡ በምእራብ አፍሪካ ለተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ ሆስፒታሎች የመጀመሪያውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡
ከያምቡኩ በኋላ ላለፉት ሰላሳ አመታት ኤድስ ላይ አተኩረህ ሰርተሃል፡፡ ኢቦላ አሁን አዲስ ስጋት ሆኗል፡፡ የአሜሪካን ሳይንቲስቶች በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በበሽታው ሊጠቁ እንደሚችሉ ገልፀዋል፡፡ ወረርሽኙ በዚህ ደረጃ ትጠብቀው ነበር?
በፍፁም አልነበረም፡፡ እንዲያውም ተቃራኒ ነበር፡፡
ኢቦላ እንደ ወባና ኤድስ ችግር ፈጣሪ አልነበረም፤ ምክንያቱም ሲከሰት የነበረው በጣም በተወሰኑ ገጠራማ አካባቢዎች ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ ወደ ትላልቅ ከተሞች መግባቱን ስሰማ ከወትሮው የተለየ ነገር እንደተፈጠረ ገባኝ፡፡ በተመሳሳይ ወር የድንበር የለሹ የሀኪሞች ቡድን ስጋቱን ከገለፀ በኋላ እጅግ አሳሰበኝ፡፡
የአለም የጤና ድርጅት ምላሹን የሰጠው ዘግይቶ ነው፡፡ ለምንድን ነው?
በአንድ በኩል የድርጅቱ የአፍሪካ ቢሮ ብቃት ባላቸው ሳይሆን በፖለቲካ ሹመኞች የተሞላ ነው፡፡
በሌላ በኩል ጄኔቫ ያለው የድርጅቱ ዋና ቢሮ በበጀት ቅነሳ ምክንያት ችግር ያለበት ሲሆን በተለይ ደግሞ የድንገተኛ ወረርሽኞች ዲፓርትመንቱ በጣም የተዳከመ ነው የተዳከመ ነው የተጎዳ ነው፡፡ ከነሐሴ ወር በኋላ ግን ድርጅቱ የመሪነት ሚናውን መጫወት ጀምሯል፡፡
በዛየር የመጀመሪያው ወረርሽኝ ሲከሰት የሆስፒታሎች የንፅህና መጓደል አስተዋፅኦ አድርጎ ነበር፡፡ አሁንም ተመሳሳይ ነገር ነው ያለው፡፡ ሉዊ ፓስተር “ሁሉም ነገር ያለው ባክቴሪያና ቫይረስ ላይ ነው” ብሎ ነበር፡፡ በዚህ ትስማማለህ?  
በጣም እስማማለሁ! ኤችአይቪ አሁንም አለ፡፡ ለንደን ውስጥ ብቻ በቀን አምስት ግብረሰዶማውያን በቫይረሱ ይያዛሉ፡፡ ቁጥራቸው በዛ ያሉ ባክቴሪያዎች መድሀኒት የመቋቋም አቅማቸው እየጨመረ ነው፡፡ በባክቴሪያና በቫይረስ ላይ አሸናፊነትን ለመቀዳጀት ገና ብዙ ይቀረናል፡፡
 በሌላ በኩል ደግሞ ይህ እውነት ብዙ እንድሰራ ያበረታታኛል፡፡ ለዚህም ነው በአለም ላይ ያሉ ሀያላን ለምእራብ አፍሪካ አገራት በቂ እርዳታ እንዲያደርጉ የተቻለኝን እያደረግሁ ያለሁት፡፡

Published in ዋናው ጤና
Saturday, 15 November 2014 11:00

ስነ - ልቦናዊ ክትባት

ብዙዎቻችን ክትባትን የምናውቀው በቫይረስ ወይም በባክቴሪያ ሊመጣ የሚችልን በሽታ ለመከላከል ጥቅም ላይ ሲውል ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን በሥነ ልቦናና በስነ አዕምሮ መስክም የአእምሮ ጤናን ለመጠበቅና ከጉዳት ለመከላከል የሚውል ክትባት አለ፡፡ ስነ ልቦናዊ ክትባት /Psychophulaxis/ ወይም ቫክሲን ፎር ሳይክ /Vaccine for psyche/ ይባላል፡፡
ስነ - ልቦናዊ ክትባት /psychological vaccine/ ከተለመደው ክትባት የተለየ ሲሆን የስሜት ወይም የአስተሳሰብ መመረዝ እንዳይነካን ብሎም የስነልቦናና የአእምሮ ቀውስ ደረጃ ላይ ሳንደርስ የመከላከያ ስልት ነው፡፡ የተለመደው የክትባት አይነት የተዳከመ ቫይረስን/weakened virus/ ወደ ሰውነታችን ውስጥ በማስገባት የተፈጥሮ በሽታ የመከላከል አቅሞን አንቅቶ በሽታ እንዲከላከል ማድረግ ሲሆን ስነ ልቦናዊ የክትባት ዘዴ ግን መራዥ ስሜቶችና አመለካከቶች ወደ ውስጣችን እንዳይገቡ በመከላከል አእምሮአዊ ጤንነትንና ደህንነትን መጠበቅ ነው፡፡
በአጠቃላይ ስነ - ልቦናዊ ክትባት ማለት ጤናማ ስሜትንና አስተሳሰብን የማዳበር ልማድ ማለት ነው፡፡ ይህም በጐና አዎንታዊ አመለካከትን፣ አስተሳሰብን፣ ስሜትንና ድርጊትን የሚያካትት ሲሆን ዋነኛ አላማውም የስነ ልቦና ቀውስንና የአእምሮ ጤና መታወክን መከላከል ነው፡፡ በአጭሩ ስነ ልቦናዊ ክትባት፤ ስነልቦናዊ ደህንነትን እንዲሁም አእምሮአዊ ጤንነትን የምንጠብቅበትና የምንከባከብበት ዘዴ ሲሆን አእምሮአዊ ንጽህና ወይም የአእምሮ ምግብ ልንለውም እንችላለን፡፡
የስነ ልቦና ክትባት ፅንሰ ሃሳብ በህክምና የመጀመሪያ የጤና ክብካቤ መርህ ውስጥ የተካተተ ቢሆንም እንደሌላው ዘርፍ በቂ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ባለመሰራቱ በማህበረሰባችን ዘንድ ትኩረት ሲሰጠው አይስተዋልም፡፡ በዚህም ምክንያት በአጭሩ መቀጨት የሚችሉ ችግሮች ለከፋ አደጋ እየዳረጉ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ የግለሰብን፣ ትዳርን፣ ቤተሰብን፣ ማህበረሰብንና ሀገርን ማፍረስ ደረጃ ላይ ሊደርስ ይችላል፡፡ ይህን የመፍረስ አደጋና ውድቀት የሚፈልግ ግን የለም፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ በስሜትና በሃሳብ መመረዝ የተነሳ እነዚህ መዋቅሮች እንዳይፈርሱ ግንዛቤ ማስጨበጥና መከላከል ነው፡፡
ሚስት፤ እንደ ስነ - ልቦና ሃኪም
አንዲት ባሏ ደንታ ቢስና ግድ የለሽ የሆነባት አዕምሮ - ብሩህና ቆንጆ ሴት ነበረች፡፡ ባሏ ፈጽሞ ለውበቷና ብሩህነቷ ግድ ያለው አልነበረም፡፡ ለእሷ የሚሆን ጊዜ ኖሮት አያውቅም፡፡ ይሄ ሚስትን ዘወትር የሚያበሳጫትና ውስጧን የሚያሳምማት ጉዳይ ነበር፡፡
አንድ ምሽት ላይ ባሏ እንደወትሮው በመጽሐፍቱ ውስጥ ተደብቆ፣ በራሱ ዓለም ውስጥ እየዋኘ ነበር፡፡ ብሩኋ ሚስትም በፈገግታ ተሞልታ ወደ ባሏ ጋ በመጠጋት፣ ማራኪ በሆነ ስሜት ታወራው ጀመር፡፡ “ፀጉሬ ወርቅ አይደለም?” ስትል ጠየቀችው፡፡
ባሏም ቀና ብሎ ሳያያት “አዎ…ትክክል ነሽ” ሲል መለሰላት
“ጥርሶቼስ እንደ እንቁ አያበሩም?” ሚስት ቀጠለች
“ኦ…በትክክል” አሁንም እንዳቀረቀረ፡፡
“እጆቼስ እንደ ጠዋት ነፋስ ለስላሳ አይደሉምን?”
“በትክክል …በትክክል…”
“እግሮቼስ እንደ ዝሆን ኩምቢ በአግባቡ የተቀረፁና የተዋቡ አይደሉም?”
“…ትክክል ነሽ…”
“ሰውነቴስ እንደ እምነበረድ የሚያበራ አይደለምን?”
“የተናገርሽው እውነት ነው፡፡” ባሏ የሞት ሞቱን መለሰ፡፡
በሚስቱ የማያባሩ ጥያቄዎች ስራው ላይ ማተኮር ያልቻለው ባል፤ ሚስቱን ቀና ብሎ ማየት ጀመረ፡፡ እሷ ግን ቀጠለች…
“መቀመጫዬስ ጥሩ የአበባ ማስቀመጫ አይመስልምን?”
“ኦህ በትክክል”
“ጡቶቼስ እንደ ጣፋጭ ኮክ ሞላ ያሉ፣ ትኩስና ጠንካራ አይደሉምን?”
“ልክ ነሽ የኔ ጣፋጭ ባልየው በመጨረሻ ተንፍሶት የማያውቀውን የአድናቆት ቃል ተናገረ፡፡ በዚህ የተደሰተችው ሚስት ባሏን አቀፈችውና “ልቤን በጣፋጭ ቃላት የምትሞላልኝ ድንቅ ባል ነህ!” ስትል አወደሰችው፡፡ (ፕሮፌሰር ናስራት ሰስኪያን፤ “አባባሎች ለአዎንታዊ ስነልቦና ህክምና”)
ሴትየዋ ጋግርታም ባል ምን ያደርግልኛል ብላ ለመፍታት አልቸኮለችም፡፡ ተስፋ በመቁረጥና በሃዘን ስሜት ውስጥም አልዋኘችም፡፡ ባሌ ችላ ያለኝ ቆንጆ ባለመሆኔ ነው ብላም ከራሷ ጋር አልተጣላችም፡፡ ይኸ ሰው አይፈልገኝም ማለት ነው ወይም ሌላ ቆንጆ ማየት ጀምሯል ስትል በቅናት አልተንጨረጨረችም፡፡ በአጠቃላይ የደንታ ቢስ ባሏን ህይወት አውካ ራሷንም አልረበሸችም፡፡ ከባሏ ጋር ያላትን አለመግባባት የፈታችው በብልህነት ነው፡፡ ታዲያ ይህቺ ባለብሩህ አዕምሮ ሴት ባሏን እንዲናገር በመገፋፋትም ትዳሯን አላከመችም? እሱንስ ከጋግርታምነቱ አላዳነችውም? ድክመቱ ላይ ሳይሆን ጠንካራ ጐኑ ላይ በማተኮር እሱንም ራሷንም አስደስታለች፡፡ በጥረቷና በብልህነቷ  ከተደበቀበት ዓለም እንዲወጣና ትኩረቱ ወደ እሷ እንዲሆን አድርጋለች፡፡
ብዙዎቻችን ግን ችግራችንን እንደዚህች ሴት በብልሃት አንፈታም፡፡ ሌላ ሰው ጋ የተለየ ስሜት ካየን፣ “የሆነ ነገር ሆኖ ነው እንጂ በደህናው እንደዚህ አይሆንም” ብለን አናስብም፡፡ ለመርዳትም አንሞክርም፡፡ ይልቁንም “ጀመረው፣ መጣበት ደግሞ፣ ተነሳበት፤ ወዘተ” አይነት ፍረጃ ውስጥ ገብተን ችግሩን እናባብሳለን፡፡ መፍትሔ ከመሻት ይልቅ የችግሩ አካል እንሆናለን፡፡ በግለሰብ፣ በጥንዶች (ባልና ሚስት)፣ በቤተሰብ፣ በማህበረሰብ እና በሀገር ደረጃ የምናየው ይህን ዓይነት አጉል ፍረጃ ነው፡፡ ፍረጃው ወደ ጠብ፣ አለመተማመን እንዲያም ሲል ወደ ጦርነት ይወስደናል፡፡ በዚህ ሂደት ደግሞ አእምሮአችንም ይታወካል፡፡
እኔ በሙያዬ እንደታዘብኩት፤ በየእለቱ የስነልቦና ድጋፍና እገዛ የማደርግላቸው ሰዎች በአብዛኛው ከስሜት ወይም ከአስተሳሰብ መመረዝ ጋር የተያያዘ ችግር ያለባቸው ናቸው፡፡ ችግሩ እንደገጠማቸው ስሜታቸውንና አስተሳሰባቸውን ቢያክሙ ኖሮ የስነ ልቦናም ሆነ የአእምሮ ችግር ውስጥ ባልገቡ ነበር፡፡
  ክትባቱን እንዴት መውሰድ ይቻላል?
የስነ-ልቦናዊ ክትባት የሚከተሉትን ተግባራት ያካትታል፡-
አዎንታዊ አስተሳሰብን /Positive thinking/ ማዳበር፡-
በጎና አዎንታዊ አስተሳሰብን ማዳበር ጥሩ ስሜት እንደሚሰማን፣ ምክንያታዊ አስተሳሰባችን እንዲጐለብትና ወደ በጎ ተግባር እንድንገባ የሚረዳ መሳሪያ ነው፡፡ የአዎንታዊ አስተሳሰብ ጠንቆች ከሚባሉት መካከል ዘወትር ጎደሎ ጎደሎውን ማየት፣ አእምሮአዊ ግነትን መፍጠር፣ አልችልም ብሎ ማሰብ፣ ይህቺ አለም ኢ-ፍትሃዊና አድሏዊ ነች ብሎ መደምደምና መትከንከን ይጠቀሳሉ፡፡
ጥሩ ስነ-ምግባርን ማጐልበት /Cultivating good conduct/
ጥሩ ስነ-ምግባር ጥሩ የአእምሮ ምግብ ማለት ነው፡፡ ስራችንን፣ ማህበራዊ ግንኙነታችንንና አካላችንን በጥሩ ስነ-ምግባር የተቃኘ ማድረግ እንደ አንድ ስነ-ልቦናዊ ክትባት ይቆጠራል፡፡
ግብረ ገብነትንና ጥሩ መንፈሳዊ ባህሪን መላበስ /Having morale and good spiritual life/፣ ህይወታችንና ኑሯችን የእኛ ብቻ አይደለም፡፡ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከሌሎች ጋር ይገናኛል፡፡ ማህበረሰባዊና መንፈሳዊ እሴቶች ሌላኛዎቹ የስነ-ልቦና ክትባት ምንጮች ናቸው፡፡ ከነዚህ ምንጮች አለመራቅ እንዲያውም ከምንጩ ቀድተን መጠጣት ይኖርብናል፡፡ ይህን ስናደርግ ከግጭት ነፃ የሆነ ህይወት እንመራለን፡፡
አእምሮን ማሰልጠን /Training the mind/:-
ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራት በየእለት ተእለት ህይወታችን ለመተግበር አእምሮአችንን ማለማመድና ማሰልጠን ተገቢ ነው፡፡ የዚህ ልምምድ የመጀመሪያ መርህ “አለምን መቀየር ስለማትችል አለምን የምታይበትን መነፅር ቀይር” የሚል ነው፡፡ እኛ መቆጣጠር የምንችለው የራሳችንን ስሜትና አስተሳሰብ ብቻ ነው፡፡ የሌሎችን አስተሳሰብ ለመቆጣጠር ስንሞክር ሚዛናችንን እንስታለን፡፡ አስተሳሰባችንንም በማይመለከቱን ክፉ ሃሳቦች እንመርዛለን፡፡
ስነ-ልቦናዊ ክትባትን የት ማግኘት ይቻላል?
ስነ-ልቦናዊ ክትባት ከሌላው የክትባት አይነት የሚለየው ክትባቱ ሁልጊዜ በእጃችን በመሆኑ ነው፡፡ ተከታቢውም ከታቢውም እኛ ራሳችን ነን፡፡ “በእጅ የያዙት ወርቅ …” እንዲሉ ግን ዋጋውን አናውቀውም፡፡ አንጠቀምበትምም፡፡ ይህን ክትባት በአካባቢያችን፣ በቤታችን፣ በቤተሰብ፣ በጎረቤት፣ በማህበረሰብ፣ በትምህርት ቤት፣ በጤናና  በሐይማኖት ተቋማት ጭምር እናገኘዋለን፡፡
 በአካባቢያችን የምንመለከታቸው በጎና መጥፎ ነገሮች ይኖራሉ፡፡ ግን እስቲ ለአፍታ የተቸሩንን በጎ ፀጋዎች ብቻ እናስብ፤ በእነሱም እንደሰት፡፡ የሌሉንን ነገሮች እንርሳቸው፡፡ እጃችን ላይ ባሉ ነገሮች ስንደሰት፣ በእርግጠኝነት ከፍርሃትና ከፀፀት ነፃ እንሆናለን፡፡
 አእምሮአችንና ስሜታችንም በቅንጅት መስራት ይጀምራሉ፡፡ ያን ጊዜ ችግሮችን የመፍታት አቅማችን ብቻ ሳይሆን የመፍጠር ችሎታችንም ከወትሮው ይጨምራል፡፡ ሆኖም የስሜት መረበሽ ወይም ከአስተሳሰብና ከባህሪ ጋር የተያያዙ የስነ-ልቦና ችግሮች ሲያጋጥሙ የባለሙያ ድጋፍ ማግኘት እንዳለብን አንርሳ፡፡  

Published in ህብረተሰብ