ዘንድሮ ለሦስተኛ ጊዜ የሚካሄደው “የላቀች ሴት” የክብር ሽልማት ሥነስርዓት በሚቀጥለው ሳምንት እሁድ እንደሚያካሂድ አሶሴሽን ኦቭ ውሜን ኢን ቢዝነስ (ኤውብ) ገለፀ፡፡ ሰሞኑን ማህበሩ በሳሮማሪያ ሆቴል በሰጠው መግለጫ፤ ለዚህ የክብር ሽልማት የሚታጩ ሴቶችን ህዝቡ ከክልልም ሆነ ከአዲስ አበባ እንዲጠቁም  ከተደረገ  በኋላ፣ ሰባት ሴቶች ተመርጠው መታጨታቸውን ጠቁሟል፡፡
ዶ/ር ቦጋለች ገብሬ የኬኢሞጂ ኢትዮጵያ መስራችና ዳይሬክተር፣ ወይዘሮ ፍሬአለም ሽባባው የባህር ዳር አካዳሚ ትምህርት ቤት መስራችና ዳይሬክተር፣ ዶ/ር ሊያ ታደሰ የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ዋና ዳይሬክተርና ምክትል ፕሮቨስት፣ ወ/ሮ ራሄል መኩሪያ በቀድሞ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የትምህርት በቴሌቪዥን ዝግጅት ክፍል ዋና ሃላፊ እና የቀድሞ ወጣት ክርስቲያን ሴቶች ማህበር (ወሴክማ) የቦርድ ፕሬዚዳንት፣ አምባሳደር ታደለች ኃ/ሚካኤል የቀድሞ የሴቶች ጉዳይ ሚኒስትር፣ አምባሳደር እና የሴቶች ልማት ፈንድ መስራችና ዳይሬክተር፣ ወ/ሮ ትርሃስ መዝገበ የሙዠዤዋግ ሎካ የሴቶች ልማት ድርጅት መስራችና ዳይሬክተር እና ወ/ሮ ዘሚ የኑስ የኒያ ፋውንዴሽን መስራችና ዳይሬክተር በእጩነት መቅረባቸውን ማህበሩ ይፋ አድርጓል፡፡
በሚቀጥለው ሳምንት እሁድ በሚደረገው የእራት ግብዣ ላይ አሸናፊዋ ሴት፣ የ2007 የኤውብ የላቀች ሴት ስያሜና የ100 ሺህ ብር ሽልማት እንደሚሰጣት የማህበሩ የወቅቱ ፕሬዚደንት ወ/ሮ ሰብለ ኃይሉ ተናግረዋል፡፡ አሸናፊዋ የተሸለመችውን ብር በበጐ አድራጐት ለተሰማራና ላመነችበት ድርጅት በስጦታ የምታበረክት ሲሆን  አመቱን ሙሉ በአምባሳደርነት ካገለገለች በኋላ፣ ማዕረጓን ለ2008 ተሸላሚ ታበረክታለች ተብሏል፡፡ ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር በማካሄደው በዚህ የላቀች ሴት ሽልማት ሥነ-ስርዓት ላይ በርካታ የመንግሥት ባለስልጣናት፣ የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካዮች፣ አምባሳደሮችና ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች እንደሚገኙም ተገልጿል፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ የ2006 ዓ.ም የላቀች ሴት ተሸላሚ የነበሩት የኔክስት ዲዛይንና ሞዴሊንግ ት/ቤት መስራችና ባለቤት ወ/ሮ ሳራ መሃመድ ተገኝተው፣ በአምባሳደርነታቸው ያከናወኗቸውን ስራዎች ተናግረዋል፡፡ የተሸላሚዋ ሴት የምርጫ መስፈርት በትምህርትም ሆነ በስራ ለግሏ ማደግና መላቅ ብቻ ሳይሆን ሌሎች እንዲያድጉ፣ እንዲሻሻሉና እንዲልቁ ያደረገችው አስተዋፅኦ በዋናነት ይታያል ተብሏል፡፡  

ያለፈው ዓመት ገቢ ከዕቅድ በታች ነው

           በኢትዮጵያ ጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት፣ የጨርቃጨርቅ ስፌት ኢንዱስትሪ በዘንድሮ  በጀት ዓመት ከተለያዩ የምርት ዓይነቶች የውጪ ንግድ 435 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ለመሰብሰብ ማቀዱን አስታወቀ፡፡ ያለፈው ዓመት ገቢው ከዕቅድ በታች መሆኑንም ገልጿል፡፡
ኢንስቲትዩቱ የዚህን ዓመት ዕቅድ ለባለድርሻ አካላት ባስተዋወቀበትና ያለፈውን ዓመት ዕቅድ በገመገመበት ወቅት፣ ይህ ዓመት፣ የመጀመሪያው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ምዕራፍ የሚጠናቀቅበት ስለሆነ፣ ዕቅዱን ለማሳካት የሞት ሽረት ጥረት ይደረጋል ብሏል፡፡ ዕቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ በዚህ ዓመት በጨርቃጨርቅና ስፌት ኢንዱስትሪ ዘርፍ በግንባታ ላይ (18 አዳዲስና 7 በማስፋፊያ) የሚገኙት 25 ፕሮጀክቶች ወደ ምርት ይገባሉ ያለው ኢንስቲትዩቱ፤ አዳዲስ ባለሀብቶች ወደ ጥጥ ልማት እንዲገቡ በማድረግ፣ የጥጥ ልማትና በዘርፉ የሚደረግ ኢንቨስትመንትን ማስፋፋት፣ የፋብሪካዎችን ምርትና ምርታማነት ማሳደግ፣ የቴክኒክና የምክር አገልግሎት መስጠት፣ የገበያ ትስስር መፍጠርና የግብይት አቅምን ማጠናከር፣ … ዕቅዱን ለማሳካት የሚደረጉ ሌሎች ጥረቶች መሆናቸውን አብራርቷል፡፡ ባለፈው ዓመትና ዘንድሮም 7 ሺህ ሄክታር መሬት በጥጥ የተሸፈነ ሲሆን ከዚህም  ከ70 ሺህ በላይ የተደመጠ ጥጥ ይገኛል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ለ10 ባለሀብቶችም ብድር ተፈቅዶ ወደ ጥጥ ልማት መግባታቸው ተገልጿል፡፡ የአምናው ክንውን ሁሉም ከዕቅድ በታች ከመሆኑን በላይ፣ አንዳንዱ ከ2005 ዕቅድ ጋር ሲነፃፀር ያነሰ ነው፡፡ ድርና ማግ (ክር) 77,147 ታቅዶ በክንውኑ የተገኘው 28,147 ነው፡፡ ብትን ጨርቅ 35,544 ታቅዶ 6,321፣ የስፌት ውጤቶች 230ሺ ታቅዶ፣ 72,148፣ የሽመና ውጤቶች 7,078 ታቅዶ፣ ክንውኑ 4,738 ሆኗል፡፡ ከካቻምናው 2005 ዓ.ም ጋር ሲነፃፀሩ፣ ብትን ጨርቅ 9,399 የነበረው አምና ወደ (6,32) ወርዷል፣ 4,916 የነበረው የሽመና ውጤቶች ወደ 4,738 ዝቅ ብሏል፡፡በአጠቃላይ ከወጪ ንግድ 350 ሺህ ዶላር ለማግኘት አቅዶ የተገኘው ግን 111.4 ሺህ ዶላር ነው፡፡ ኢንስቲትዩቱ፣ ከኤክስፖርተር ኩባንያዎች ጋር ባደረገው ውይይት፣ ባለሀብቶቹ የተለያዩ ጥያቄዎች አንስተው የመፍትሄ ሀሳብ ተሰጥቷቸዋል፡፡ በወጪ ንግድ ዘርፍ የተሰማሩ ኩባንያዎች ዋንኛ ችግር ከፍተኛ ሰው ኃይል በመሆኑ መፍትሔ ካልተፈለገለት ዘርፉን እንደሚያሽመደምደው ተገልጿል፡፡ ሰራተኞች፣ በትንሽ የደሞዝ ለውጥ ከአንዱ ድርጅት ለቀው ወደ ሌላ እንደሚገቡ፣ አንዳንድ የውጭ አማካሪዎች ሰራተኞችን እንደሚያስኮበልሉ፣ … ተገልጿል፡፡ የሥራ ማስኬጃ ካፒታል እጥረት ሌላው ችግር ነው፡፡ ባንክ ደግሞ በቀላሉ ብድር አይሰጥም፡፡ የአራት ዓመት የኮንትራት ስምምነት እንደሚጠይቅ ተናግረዋል፡፡ ሌላው የትራንስፎርሜሽኑንም ዕቅድ እንዳይሳካ ያደርጋል ተብሎ የተሰጋው፣ የኤሌክትሪክ ኃይል መጥፋትና መቆራረጥ ነው፡፡ ስለዚህ በሙሉ አቅማቸው እንደማያመርቱ ገልፀዋል፡፡ አንድ 10.5 ሺህ ሜጋ ዋት የሚያስፈልገው ፋብሪካ የሚያገኘው የኃይል መጠን 4ሺህ ሜጋ ዋት ነው፡፡ የኤክስፖርት ምርቱ ተሞክሮ በማያውቅ ሁኔታ በስዊድን ተቀባይነት አግኝቶ ኮንትራት ቢፈራረምም በኤሌክትሪክ ኃይል መጥፋትና መቆራረጥ ኃላፊነትና ግዴታውን መወጣት እንዳልቻለ ገልጿል፡፡ የጥሬ ዕቃ (ጥጥ) የክር እጥረት፣ የመንገድ ያለመስፋፋት፣ የባለስልጣኖችና ኃላፊዎች ፈጣን ምላሽ ያለመስጠት፣ … በኤክስፖርተሮቹ ከተነሱት ችግሮች ጥቂቱ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ስኬታማ ሴቶችን ታሪክ የሚዘክረውና ለዝግጅት 3 ዓመት ገደማ የፈጀው “ተምሳሌት፣ እፁብ ድንቅ ኢትዮጵያውያን ሴቶች” የተሰኘው መፅሃፍ ባለፈው ማክሰኞ ምሽት በብሔራዊ ሙዚየም ግቢ ተመረቀ፡፡
በኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ቅንጅት አሳታሚነት፣ በአሜሪካዊቷ ሜሪ ጄን ዋግል ተዘጋጅቶ፣ በጋዜጠኛ ኢዮብ ካሣ የተተረጐመው መፅሃፉ፤ የኢትዮጵያ ሴቶች ከጥንት ጀምሮ እስካለንበት ዘመን ድረስ የተጫወቱትን ጉልህ ሚና የሚዘክር ሲሆን በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርተው አንፀባራቂ ውጤት ያስመዘገቡ የ64 ኢትዮጵያዊያን ሴቶችን ታሪክ አካትቷል፡፡
በጋዜጠኝነት፣ በህግ፣ በንግድ፣ በህክምና፣ በግብርና፣ በኪነጥበብ፣ በማህበረሰብ አገልግሎት፣ በግንባታ ሙያ፣ በበጐ አድራጐት፣ በአመራር እና በሌሎች የሙያ ዘርፎች ለስኬት የበቁ እንስቶች የተካተቱበት መፅሃፉ፤ 298 ገፆች ያሉት ሲሆን በላቀ ጥራትና በማራኪ ዲዛይን ተዘጋጅቶ እንደታተመና 30 ሺህ ኮፒ ለት/ቤቶች፣ ለቤተመፃህፍትና የልጃገረዶችና ወጣት ሴቶችን አቅም በማጐልበት ሥራ ላይ ለተሰማሩ ድርጅቶች በነፃ እንደሚከፋፈል ለማወቅ ተችሏል፡፡
“ተምሳሌት” ባለፈው ማክሰኞ ቀዳማዊት እመቤት ሮማን ተስፋዬ፣ ለህትመቱና ስርጭቱ ድጋፍ የሰጡ የአሜሪካና የአውሮፓ አምባሳደሮች እንዲሁም የተባበሩት መንግሥታት የሴቶች ድርጅት እና ሌሎች እንግዶች በተገኙበት ነው የተመረቀው፡፡ በምርቃቱ ሥነ-ስርዓት ላይ የመፅሃፉ አዘጋጅ ሜሪ ጄን ዋግል ከመፅሃፉ ባለታሪኮችና የበጐ ፈቃድ ሰራተኞች፣ በቪዲዮ የተቀናበረ ምስጋናና ውዳሴ ቀርቦላታል፡፡
“ለኢትዮጵያውያን ሴቶች ለሰጠሽው ክብርና ዕውቅና እናመሰግንሻለን” ብለዋታል - አመስጋኞቹ፡፡ ከዚሁ ጐን ለጐን የባለታሪኮቹን ፎቶግራፎች ላለፉት 2 ዓመታት ገደማ ስታነሳ የቆየችው ዓለምአቀፍ የፎቶግራፍ ውድድር አሸናፊዋ አይዳ ሙሉነህ ያዘጋጀችው የስኬታማ እንስቶቹ የፎቶግራፍ አውደርዕይ ለታዳሚዎች ቀርቦ ከፍተኛ አድናቆት እንደተቸረው ለማወቅ ተችሏል፡፡

በዳንኤል ቢሰጥ እቴቴ የተፃፉ ግጥሞች የተካተቱበት “አፈር ብላ” የተሰኘ የግጥም መድበል፤ ሰሞኑን ገበያ ላይ ውሏል፡፡ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሽሙጦችና ፍልስፍና ነክ ግጥሞች እንዲሁም አገራዊ ፉከራና ሽለላ ቀመስ ግጥሞች የተካተቱበት መፅሃፉ፤ ፈገግና ዘና የሚያደርጉ ርእሰ ጉዳዮችንም ይዳስሳል፡፡
በ100 ገፆች ተቀንብቦ የተዘጋጀው “አፈር ብላ” የግጥም መድበል፤ በ25 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ መፅሃፉ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ በሩሲያ የሳይንስና የባህል ማዕከል (ፑሽኪን አዳራሽ) ይመረቃል ተብሏል፡፡

 በጉራጊኛ ዘፈኑና በማራኪ ውዝዋዜው የሚታወቀው የድምፃዊ መላኩ ቢረዳ “ዳነ” የተሰኘ አዲስ የጉራጊኛ ቪሲዲ ሰሞኑን ለገበያ ቀርቧል፡፡ የ14 ዘፈኖችን ቪዲዮ ያካተተው ይኸው ስራ፤ አብዛኞቹ ግጥሞችና ዜማዎች በራሱ በድምፃዊው የተሰሩ ሲሆን ቅንብሩ በዘሪሁን ሳህለማሪያም፣ ያሬድ አስናቀ፣ አሸናፊ ከበደና በሰለሞን ኢብራሂም ነው የተሰራው፡፡
ድምፃዊው በቪሲዲው ውስጥ “ትግርኛ ምት በጉራጊኛ”፣ “አውዳመት አማርኛ በጉራጊኛ ስልት”፣ “ጐንደር በጉራጊኛ”፣ “ሱዳንኛ በጉራጊኛ” እና “ትዝታ በጉራጊኛ” የሚሉትን በማካተት ለየት ባለ ሁኔታ የቀረበ ሲሆን ከዚህ ቀደም “ትዊስት በጉራጊኛ” የተሰኘ ቪሲዲ ማውጣቱ ይታወቃል፡፡ አዲሱ ቪሲዲ በዚያዳ ሪከርድስ ታትሞ እየተከፋፈለ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ድምፃዊ መላኩ ቢረዳ በአሁኑ ሰዓት በዮድ አቢሲኒያ የባህል ምግብ ቤት አዳራሽ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡

በደራሲና አዘጋጅ ሙሉዓለም ጌታቸው ተሰናድቶ፣ በበርሄ ገ/መድህን ፕሮዱዩስ የተደረገው “ሚስቴን ቀሙኝ” የተሰኘ ኮሜዲ የፍቅር ፊልም፤ ነገ በመላ አገሪቱ በሚገኙ የግል ሲኒማ ቤቶች እንደሚመረቅ ፕሮዱዩሰሩ አቶ በርሄ ገ/መድህን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡
በሜርሲ መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ለእይታ የሚቀርበውን ይሄን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት እንደፈጀ የገለፁት ፕሮዱዩሰሩ፤ ከ600 ሺህ ብር በላይ እንደወጣበትና የ1ሰዓት ከ42 ደቂቃ ርዝማኔ እንዳለው ጠቁመዋል፡፡
በፊልሙ ላይ ዮሐንስ ተፈራ (ዳረማኛ)፣ ቃልኪዳን ጥበቡ፣ ሰገን ይፍጠር፣ ካሳሁን ፍሰሃ (ማንዴላ)፣ አስራት ታደሰ፣ ፋንቱ ማንዶዬ፣ እንዳልካቸው ሰበታና ሌሎችም ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

       በደራሲና ዳይሬክተር ዳንኤል በየነ ተሰርቶ፣ በሞመንተም ሚዲያ ፕሮዳክሽን የቀረበው “የመሃን ምጥ” የተሰኘ ልብ አንጠልጣይ የቤተሰብ ፊልም፤ ነገ በሁሉም የግል ሲኒማ ቤቶች ይመረቃል፡፡ ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሁለት አመት ያህል የወሰደውና የ1፡40 ርዝማኔ ያለው ይሄው ፊልም፤ በ30ዎቹ የእድሜ ክልል ላይ የሚገኝ በጥሩ ሥነ-ምግባር የታነፀና ቤተሰቡን ለማስተዳደር የሚታትር አንድ ወጣት፤ በአጋጣሚ በደረሰበት አደጋ ከተዋወቃት አንዲት ወጣት ጋር የሚያሳልፈውን ውጣ ውረድና በቤተሰቡ ላይ የደረሰውን የኑሮ ምስቅልቅል ያሳያል ተብሏል፡፡ በፊልሙ ላይ ፀጋነሽ ሃይሉ፣ ወለላ አሰፋ፣ ብርሃኑ ሽብሩ፣ ስዩም ተፈራ፣ ደሳለኝ ሃይሉና ሌሎችም ተዋንያን መሳተፋቸው ተገልጿል፡፡ ፊልሙ ነገ ከተመረቀ በኋላ በተለያዩ ሲኒማ ቤቶች ለተመልካች እንደሚቀርብ ታውቋል፡፡

Monday, 13 October 2014 07:12

ጣጠኛው ጋን

           የዘንድሮው የወይራ ፍሬ ምርት የሰጠ ነበር፡፡ ዶን ዚርፋ ሎሎ በፕሪሞሶሌ አያሌ የወይራ ዛፎች ነበሩት፡፡ የዓመቱ የተትረፈረፈ የዘይት ምርቱን አምስቱ ጋኖች መያዝ እንደማይችሉ በመገመት፣ ዲላማስትራ ከሚገኝ የጋን ፋብሪካ ጋን ለማሰራት ወሰነ፡፡ እንዲሰራለት ያዘዘው ቁመቱ የሰው ደረት ላይ የሚደርስ፣ ሰፊና ግርማ ሞገስ ያለው ውብ ጋን ነው፡፡
በዚህ የጋን ሥራ ከሸክላ ሰሪው ጋር ተጨቃጭቆ ነበር፡፡ ለነገሩ ከዶን ሎሎ ጋር የማይጨቃጨቅ ማን አለ? በትንሽ በትልቁ ከማንም ጋር እንደተቧጨቀ ነው፡፡ ከግንቡ ላይ ኮረት ወይም የሳር ዘለላ ወደቀ በሚል ከተማ ሄዶ ለመክሰስ “በቅሎዬን ጫኑልኝ” እንዳለ ነው፡፡ ለረባ ላልረባው እየተመላለሰ ያሰለቸው የሎሎ የህግ ጠበቃ፤ ለእያንዳንዷ ቁርሾ የሕጉን አንቀጽ ራሱ እንዲፈልግ መጽሐፍ ሰጠው፡፡ ይህቺው እንደ ፀሎት መጽሐፍ የነተበች የሕግ መጽሃፉ፤ የመንደሯ ነዋሪዎች ማላገጫ ሆነች፡፡ በፊት ከሎሎ ጋር የተጣሉ ሰዎች “በቅሎህን ጫን” እያሉ እንዳላሾፉበት፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “መፅሐፍህን ግለጥ” በማለት ሲያላግጡበት፣ እሱም “የውሻ ቡችሎች! ሁላችሁንም ዶግ አመድ እያለ ያስፈራራቸዋል፡፡”
አራት መህልቅ ወርቅ የተከፈለበት ጋን፣ በማጀት ቦታ እስኪገኝለት ድረስ ለጊዜው በምድር ቤት ተቀመጠ፡፡ የወይራ አተላ ዝቃጭ በሚሰነፍጥበት፣ ብርሃንና አየር በማይገባበት ሸጋታ ስፍራ፣ ያን ውብ ጋን ማየቱ ልብ ይነካል፡፡ የወይራ ፍሬ እየተገለፈፈ መሰብሰብ ከተጀመረ ሁለት ቀን አለፈው፡፡ በሶስተኛው ቀን ከገበሬዎች ሶስቱ የወይራ ፍሬ ሲለቅሙ ውለው፣ መሰላልና ዘንግ ለማስቀመጥ ወደ ቤት ገብተው ነበር፡፡ በዚህ መሃል አንደኛው በስል ቢላዋ የሄደበት ይመስል አዲሱ ጋን ለሁለት ተሰነጠቀ፡፡ ከመሃከላቸው በፍርሃት የራደው ገበሬ፣ ማንም ሳያይ እብስ እንዲሉ ሀሳብ አቀረበ፡፡ ሌላኛው ግን፣ “አብዳችኋል? ዶን ሎሎ እኛ የሰበርነው ይመስለዋል፡፡ ማንም እንዳይንቀሳቀስ” አለና ወጣ ብሎ፣ “ዶን ሎሎ … ኧረ ዶን ሎሎ” ሲል ተጣራ፡፡
ሎሎ የጋኑን ሥብራት ባየ ጊዜ እንደ እብድ አደረገው፡፡ ገበሬዎቹ ላይ አምባረቀ፡፡ አንደኛውን ጉሮሮውን አንቆ ከግንቡ ጋር አጣበቀውና፣ “… ትከፍሉኛላችሁ” ሲል ጮኸ፡፡ ባርኔጣውን መሬት ላይ ወርውሮ ለሞተ ዘመዱ እንደሚያለቅስ መሬቱን እየደቃ፤ “አዲሱ ጋን!... አራት የወርቅ ማህለቅ የተከፈለበት ገና ያልተሟሸ ጋን”! ሲል ሙሾ አወረደ፡፡
… ማን ሰበረው? … ጋኑ ራሱ ነቅቶ (ተሰንጥቆ) ይሆን? … በምቀኝነት ተነሳስቶ አንዱ ሰብሮት ይሆን? … ሰከን እንዲል ይለምኑት ጀመር፡፡ ጋኑ ሊጠገን ይችላል፡፡ አሰነጣጠቁም መጥፎ የሚባል አይደለም፡፡ ሸክላ ጠጋኝ ባለሙያ እንደ አዲስ ሊጠግነው ይችላል፡፡
በማግስቱም የፕሪሞሶሌ የጥገና ባለሙያ የሆነው ዲማ ሊካሲ በማለዳ ደረሰ፡፡ ዲማ ዘመናት እንዳስቆጠረ የወይራ ዛፍ ሰውነቱ የተጠማዘዘ ሽማግሌ ነው፡፡ የወላለቀች መነፅሩን አፍንጫው ላይ ሰካና ጋኑን በጥንቃቄ ከመረመረ በኋላ፣ “በጥሩ ሁኔታ ሊጠገን ይችላል፡፡” አለ፡፡ ሎሎም፣ “በማጣበቅ ብቻ ይጠገናል ብዬ አላምንም፡፡ መስፋትም አለበት፡፡” ሲል ሐሳቡን ገለፀ፡፡
“መሔዴ ነው” አለ ዲማ ብድግ ብሎ፡፡ … ሎሎም “ወዴት! ወዴት!.. የድሃ ቀብራራ … ይህን የሚያህል ስንጥቅ እንዴት በማጣበቅ ብቻ … የግድ መሰፋት አለበት፡፡ የማጣበቂያና የስፌቱን እከፍልሃለሁ፡፡ ስንት ታስከፍለኛለህ?”
“… በማጣበቂያ ብቻ ከሆነ…”
“ስፌቱ የግድ ነው፡፡ ሥራው ካለቀ በኋላ እንነጋገራለን፡፡ ካንተ ጋር የማጠፋው ጊዜ የለኝም፡፡”
ዲማ ንዴትና ንቀት ወጥሮት ስራውን ጀመረ፡፡ ጋኑን በመሰርሰር በበሳም ቁጥር ንዴቱ እየጨመረ ነበር፡፡ የተሰበረውን የጋን ሽራፊ ለመግጠም አስጠጋው፡፡ የበሳቸውን ቀዳዳዎች እኩል ርቀት ትይዩ መሆናቸውን በዓይኑ ለካ፡፡ በጣቱ የሰባራውን ጋን ጠርዝ ቀብቶ ጨረሰ፡፡ ቁርጥራጭ ሽቦና ጉጠቱን ይዞ ጋኑ ውስጥ ገባ፡፡ ለገበሬውም ቀድሞ እንዳሳየው፣ የጋኑን ስባሪ በውጪ በኩል ገጥሞ እንዲይዝለት አዘዘው፡፡ ስፌቱን ከመጀመሩ በፊትም፣ “ሳብ! የበላህ የጠጣኸውን ያህል ግፋ!” አለው፡፡
ጋኑ ግጥም ብሎ ተጣበቀ፡፡
ሽቦውን እየጠላለፈ በጉጠት ይቆለመም ጀመር፡፡ ስፌቱን ለመጨረስ አንድ ሰዓት ፈጀበት፡፡
በመጨረሻም፣ “እንግዲህ ልውጣ… አግዘኝ” አለ ዲማ፡፡ ጋኑ ሆዱ ሰፊ ቢሆንም አንገቱ ጠባብ ነበር፡፡ ዲማ ሥራውን ሲጀምር ቁጣ ውስጥ ስለነበር ይህን ልብ አላለም፡፡ እናም ከጋኑ ለመውጣት የቻለውን ያህል ቢፍጨረጨርም መውጣት አልቻለም፡፡ ገበሬው ዲማን ከመርዳት ይልቅ በሣቅ ይንከተከት ጀመር፡፡
ዲማ ራሱ በጠገነው ጋን ውስጥ እስረኛ ሆነ፡፡ ለመውጣት ያለው ብቸኛው አማራጭ ጋኑን መስበር ብቻ ነው፡፡ ሁካታው በተደባለቀበት ድባብ ዶን ሎሎ ደረሰ፡፡ ዲማ እየጮኸ “አውጡኝ! ስለእግዚአብሔር እርዱኝ!” ይል ነበር፡፡
ሎሎ የሚያየውን ማመን አቅቶት ክው አለ፡፡ እንዴት ከጋኑ ጋር አብሮ ተሰፋ…? ሎሎ ወደ ጋኑ አፍ ተጠግቶም፣ “እርዱኝ? … እ… ደደብ! ለክተህ አትገባም ነበር? … አንድ እጅህን አውጣ… አንገትህን… ቀስ በል የማይሆን ነገር ነው፡፡” ይለው ጀመር፡፡
ሎሎ ጋኑን በጣቱ አንኳኳው፡፡ ንጥር ድምፅ ልክ እንደ ደወል ያቃጭል ነበር፡፡ ጥገናውስ ድንቅ ነበር፡፡ ዲማ በወጥመድ እንደተያዘ አውሬ በንዴት ሲወራጭ፣ ሎሎ ጋኑን ደገፍ ብሎ፣ “… ወዳጄ ይህንን ጉድ ጠበቃዬ ብቻ ነው የሚፈታው፡፡ በቅሎዬን ጫኑልኝ… መብቴን ለመጠየቅ ግዴታዬን እወጣለሁ፡፡ የአንድ ቀን ክፍያህን ይሄው አምስት ሊሬ …” አለው፡፡
ዲማ ግን “ምንም አልፈልግም፤ ከመውጣት በቀር…” አለ እየተነጫነጨ፡፡
አምስት ሊሬ ጋኑ ውስጥ ወርውሮለት በቅሎው ላይ ወጥቶ ወደ ከተማ ጋለበ፡፡
ጠበቃው ጉዳዩን ሲሰማ ከት ብሎ ሳቀ፡፡ ሎሎ በጠበቃው የማያቋርጥ ሣቅ ተቆጥቶ፣
“ምን የሚያስገለፍጥ ነገር አለ?” ቢለውም መንከትከቱን አላቋረጠም፡፡ በዚህ ጉደኛ ገጠመኝ ደጋግሞ ለማሳወቅ ሲል ጉዳዩን መላልሶ እንዲነግረው መጠየቁን ቀጠለበት፡፡
“… አ… ሂሂ… እፎይ ውስጡ ተሠፋ! ታዲያ ዶን ሎሎ የሚፈልጉት ምንድን ነው? … እዚያው እንዲኖር … አሃሃ … ሂሂ… ጋኑ እንዳይሰበርብዎ እዚያው ልታኖሩት?...”
“ታዲያ ልስበረው - በማን ኪሣራ?”
“ይሄ ሰውን ማሰር ወይም ማገት ይባላል፡፡”
“ማሰር? ማን አሰረው? ራሱን አገተ እንጂ!”
ጠበቃው ሰከን ብሎ፣ “ነገሩ ሁለት መልክ አለው፡፡ አንደኛው ሰው በማሰር እንዳይከሰሱ እስረኛውን መልቀቅ፣ ሌላው ጠጋኙ ስራውን ባለመቻሉ ኪሳራ መጠየቅ…”
“ይህ ከሆነ የጋኑን ዋጋ ይከፍለኛል፡፡”
“መቼም እንደ አዲስ ሊከፍል አይችልም!”
“ለምን?”
“ሰባራ ስለነበር!”
“ሰባራ አይደለም፡፡ ፍፁም አዲስ ሆኖ ተጠግኗል፡፡ አሁን ከተሰበረ ግን ዳግም መጠገን አይችልም፡፡ ይሄ ደግሞ እኔ ከሰርኩ ማለት ነው፤ ገባህ ጌታው ጠበቃ!?”
አሁን ባለበት ሁኔታ የጋኑንም ዋጋ ለማስከፈል የሕግ ድጋፍ እንዳለው ጠበቃው አረጋገጠለት፡፡ “እንዲያውም ጠጋኙ ራሱን ዋጋውን ያስገምቱት” ሲል መከረው፡፡ ለዓይን ያዝ ሲያደርግ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ገበሬዎች በጋኑ ዙሪያ ፌሽታ እያደረጉ፣ ውሻው ሳይቀር እየዘለለና እየጮኸ የድግሱ አካል ሆኖ ነበር፡፡ ዲማ በደረሰበት ዱብ ዕዳ የምሬት ሣቅ ይስቃል፡፡ ዶን ሎሎ ወደ ጋኑ ጠጋ ብሎ፣ “ተመችቶሃል…” አለው፡፡
“ከቤቴ የበለጠ ተመችቶኛል” መለሰ ዲማ፡፡
“ለጋኑ አራት የወርቅ ማህለቅ ከፍዬበታለሁ፡፡ አሁን ስንት የሚያወጣ ይመስልሃል?”
“ከእኔው ጭምር ነው?” ዲማ ጠየቀ፡፡
ገበሬዎቹ ከት ብለው ሳቁ፡፡
“ዝም በሉ! … ጋኑ አሁን ባለበት ሁኔታ ስንት ያወጣል? አንተው ገምት”
“… የተገዛበትን ሲሶ ሊያወጣ ይችላል፡፡”
ሎሎም ተረጋግቶ፣ “ቃልህን አክብረህ የገመትከውን ዋጋ ክፈለኝ”
“ምን?” አለ ዲማ ግራ ተጋብቶ
“አንተን ለማወጣት ጋኑን መስበሬ ነው፤ ጠበቃውም እንደመከረኝ በገመትከው ልክ ትከፍላለህ፡፡” “እኔ ልከፍልህ - ትቀልዳለህ? እስክበሰብስ ድረስ እዚሁ እኖራለሁ እንጂ …” አለና ፒፓውን ለኩሶ ጭሱን ሽቅብ ይለቅ ጀመር፡፡ ሎሎ ተደናገረ፡፡
 ዲማ “አልወጣም” እንደሚል እሱም ጠበቃውም አላሰቡም ነበር፡፡ ይሄ ምን መፍትሔ አለው? በቅሎዬን ጫኑልኝ ለማለት ከጀለውና የምሽቱ መግፋት ትዝ ሲለው ተወው፡፡ “ልብ አድርጉልኝ፡፡ ላለመክፈል ብሎ ከጋኑ መውጣት አልፈለገም… በህገወጥ መንገድ ንብረትህ ባልሆነ ቦታ ላይ በመቀመጥ ክስ እመሰርትብሃለሁ፡፡” ዲማ ጭሱን ቡልቅ እያደረገ፤ “ይክሰሱኝ… መክፈል? ለምን ተብሎ! ይቀልዳሉ!”
ዶን ሎሎ፤ ቱግ ብሎ ጋኑን ሊረግጥ እግሩን አነሳና መለስ አደረገው፡፡ ከቁጣው ሰከን ብሎ፣ “ጥፋተኛው እኔ ነኝ፡፡ በረሃብ ፍግም ትላታለህ፡፡ ማን እንደሚረታ እናያለን፡፡” ብሎት ጥሎት ሄደ፡፡ ጠዋት የወረወረለትን አምስት ሊሬ አላስታወሰም፡፡
ዲማ በዚህ እንግዳ በሆነ አጋጣሚ አውድማው ላይ አብረውት ለሚያድሩት ገበሬዎች ግብዣ ቢጤ ለማድረግ ወሰነ፡፡ በአምስቷ ሊሬ ከመሸታ ቤት መጠጥ አስገዛ፡፡ ጨረቃዋ ሌሊቱን ቀን አስመስላው ነበር፡፡ ጫጫታና ሁካታው ዶን ሎሎን ከእንቅልፍ ቀሰቀሰው፡፡ ከበረንዳው ላይ ቁልቁል አማተረ፡፡
 በጨረቃዋ ብርሃን አጋንንትን ያየ መሰለው፡፡ ገበሬዎቹ ሰክረው እጅ ለእጅ ተያይዘው በጋኑ ዙሪያ እየጨፈሩ ነው፡፡ ዲማም ከጋኑ ውስጥ ጉሮሮው እስኪሰነጠቅ እየጮኸ ይዘፍን ነበር፡፡ ዶን ሎሎ ትዕግስቱ ተሟጦ፣ እንደተቆጣ ፊጋ በሬ ተንደርድሮ ጋኑን ቁልቁል አንከባለለው፡፡ ጥንብዝ ብለው የሰከሩት ገበሬዎች ጋኑ ሲንከባለል በሣቅ ከመሸኘት ውጪ ያደረጉት ነገር አልነበረም፡፡ ጋኑ እየተንከባለለ … እ.. የ.. ተ..ን..ከ..ባ..ለ..ለ ሄዶ ከትልቅ የወይራ ዛፍ ግንድ ጋር ተጋጨ፣ ፍርክስክሱም ወጣ፡፡
እናም ዲማ ረታ፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ባለፈው ሳምንት “ዜማ ቤት፤ ድጓ ጾመድጓ” በሚል ርእስ አንድ ጽሁፍ ማስነበቤ ይታወሳል፤ ዛሬም የዜማ ዘር ስለሆኑት አቋቋም፣ ቅዳሴና ዝማሬ መዋስእት ትምህርቶች መጠነኛ ቅኝት በማድረግ ስለምንነታቸውና አገልግሎታቸው ማስነበብ ይሆናል - ዓላማዬ፡፡
 ቅዳሴ
ቅዳሴ “ቀደሰ አመሰገነ” ከሚለው የግዕዝ ቃል የመጣ ሆኖ “ማመስገን፣ ማወደስ፣ ማገልገል” የሚል ትርጉም አለው፡፡ አገልግሎቱም በቤተክርስቲያን ብቻ የተወሰነና በዜማና በንባብ ፈጣሪን ማመስገን ነው፡፡ የቅዳሴ ዜማን የደረሰው ልክ እንደ ድጓውና ጾመድጓው ሁሉ ቅዱስ ያሬድ መሆኑ ይነገራል፡፡ ዜማው የተዘጋጀውም “ዕዝል” እና “ግዕዝ” በሚባሉ ሁለት የዜማ ይትበሃሎች (ዘዴዎች) ነው፡፡ በግዕዝ የሚዜመው በጾም ወቅት ሲሆን እዝል ግን ከጾም ውጭ ባሉት ጊዜያት ነው፡፡ የቅዳሴ ቁጥር 14 ሆኖ እንደየበዓሉ ሁኔታ ይለያያል፤ ለምሳሌ በጾመ ማርያም የሚቀደሰው “ቅዳሴ ማርያም” የሚባለው ሲሆን በበዓለ እግዚእ ደግሞ “ቅዳሴ እግዜእ” በመባል የሚታወቀው ነው፡፡ ቅዳሴ ልክ እንደ ድጓው ሁሉ ዘሩ (ንባቡ) አንድ ሆኖ በአዚያዚያም ልዩነት የተነሳ የተለያዩ ስያሜዎች አሉት፤ እነሱም “ደብረ ዓቢይ፣ ሰደድኩላ፣ አጫብር” በመባል ይታወቃሉ፡፡ ሁሉም ስያሜያቸውን ያገኙት ትምህርቱ በቀዳሚነት ከሚሰጥባቸው ቦታዎች ተወስዶ ነው፡፡
ለአብነት “ደብረ ዓባይ” ትግራይ ውስጥ፣ “ሰደድኩላ” ሰሜን ወሎ፣ እና “አጫብር” ጐጃም ውስጥ የሚገኙ ቦታዎች ናቸው፡፡ ሆኖም በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን በተለይ በከተሞች አካባቢ ጐልቶ የሚታወቀው “ደብረ ዓባይ” የተባለው የቅዳሴ ዜማ ነው፡፡
“ሰደድኩላ” በሰሜን ወሎ አካባቢ፣ “አጫብር” ደግሞ በጐጃም የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ሰፊ አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ “ደብረዓባይ” እና “ሰደድኩላ” ቋሚ ትምህርት ቤቶች (ጉባዔያት) ያሏቸው ሲሆን “አጫብር” ግን በትውፊት መልኩ ከአባቶች ለደቀመዛሙርት (ተከታዮች ወይም ተማሪዎች) እየተላለፈ እስከ አሁን ድረስ አገልግሎት ከመስጠት አላቋረጠም፡፡
አቋቋም
ሌላው የዜማ አይነት “አቋቋም” በመባል የሚታወቀው የትምህርት ዘርፍ ነው፡፡ አቋቋም “ተፈጠረ” የሚባለው በጐንደር ዘመነ መንግሥት በተለይ ደግሞ በታላቁ ኢያሱ (አድያም ሰገድ) ዘመን ነው፡፡ ዜማውን “ደረሱት” ተብሎ የሚታመነው “አባ ኤስድሮስ” የተባሉ ባህታዊ (መናኝ) ናቸው፡፡ አባ “ጐሐ” ሆቴል ከተሰራበት ቦታ (ያኔ “ገነት ተራራ” የሚባል ጫካ ነበር) ሆነው ዘወትር ሌሊት በዜማ ይጸልዩ ነበር፤ ዜማው ከዚያ ቀደም ተሰምቶ የማይታወቅ ስለነበር የብዙዎችን ቀልብ ሳበ፡፡ ቀስ በቀስም የዜማው ምስጢር ከአፄ ኢያሱ ጆሮ ደረሰና በአግባቡ አዳመጡት፤ ግን ማን እንደሚያዜመው አልታወቅ አለ፡፡
ዜማውን በመረዋ ድምፁ የሚያንቆረቁረውን ሰው ለማወቅ ባለሙያዎች ቢመደቡም ሊያገኙት አልቻሉም፤ ምክንያቱም አባ ሌሊት በዜማ ሲጸልዩ ያድሩና ቀን ይሰወራሉ፡፡ ስለዚህ ምርጥ የሆኑና በቀለም አቀባበላቸው የተመሰገኑ ጥቂት ሊቃውንት ዜማውን እንዲያጠኑ ንጉሡ ትእዛዝ ሰጡ፡፡ ማንነቱ ከማይታወቀውና ሌሊት ብቻ ከሚያዜመው ሰው ትምህርት እንዲቀስሙ የተመደቡት ሊቃውንት፤ ከገነት ተራራ ስር ቆመው ማደር ግድ ሆነባቸው፡፡ በዚህ የተነሳ “የዜማው መጠሪያ አቋቋም” ሆነ የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡
በሌላሙ በኩል “ዝማሜ” ብለው የሚጠሩት ሊቃውንት ቁጥርም ቀላል አይደለም፡፡ ለዚህ አባባል እማኝ ሊያደርጉ የሚሞክሩት “ዜማው ጐንደር የነበረው የሸንቆ ተክል ዘመም ዘመም ሲል በማየት አለቃ ገብረሐና ፈጥረውታል፣ ከሙ ዝማሜ የተባለው ለዚህ ነው” የሚል ነው፡፡ ይህ ግን ብዙም የሚያራምድ አይመስልም፡፡ ምክንያቱም ሸንበቆ መቼም ቢሆን ነፋስ በነካው ቁጥር ዘመም ማለቱ (ጐንበስ ቀና ማለቱ) የተለመደና አዲስ ክስተት ባለመሆኑ ነው፡፡
ሆኖም አለቃ ገብረሐና ለአቋቋም ትምህርት መዳበር ምንም ድርሻ አልነበራቸውም ማለት አይቻልም፡፡ እንዲያውም እሳቸው ያስተማሩት የሥጋ ልጃቸው አለቃ ተክሌ የአቋቋሙን ዜማ በማሻሻል የላቀ ሚና ተጫውቷል፤ “ተክሌ” በመባል የሚታወቀውና መልካም ድምፅ ባላቸው ሊቃውንት ሲዜም መንፈስን የመመሰጥ ብርቱ ኃይል ያለው ይህ ዝማሜ፣ በተክሌ የተቀነባበረ ነው ተብሎ ይታወቃል፡፡ አለቃ ገብረሐና ለልጃቸው ተክሌ አስተማሩ፤ ተክሌ አሳምሮ ቀመረውና መጠሪያው ሆነ፡፡
የአቋቋም ትምህርት በሶስት ይከፈላል፤ እነሱም “ታችቤት (ተክሌ)፤ ላይቤት” እና “ፋኖ” በመባል ይታወቃሉ፡፡ “ላይቤት” ዋና ጉባዔ ቤቱን ጐንደር በዓታ አድርጐ በተለያዩ ቦታዎች የሚሰጥ ሲሆን ይበልጥ የሚታወቀውም በጸናጽል ነው፡፡ “ታችቤት (ተክሌ)” ግን ደብረታቦር ከተማ በምትገኘውና “እናቲቱ ማርያም” ተብላ በምትታወቀው ታላቅ ደብር ጉባዔውን ዘርግቶ፣ ከዚያ በሚወጡ ደቀመዛሙርት አማካይነት በተለያዩ የአገራችን ቦታዎች ትምህርቱ እየተሰጠ ይገኛል፤ ከላይቤት የሚለይበት ዋና ምክንያት በመቋሚያ ይትበሃሉ ሲሆን በዘር ከላይቤቱ የሚለይበት መንገድ የለም፡፡ በዝማሜው ግን እጅግ የተመሰገነ የትምህርት አይነት ነው፡፡
ለአቋቋም አገልግሎት የሚያስፈልጉት መሳሪያዎች መቋሚያ፣ ጸናጽልና ከበሮ ናቸው፡፡ በተለይ መቋሚያ በሁዳዴ ጾም ወቅት ብቸኛው መሣሪያ ነው፡፡ ሊቃውንቱ መቋሚያቸውን አንዴ ከፍ፣ እንደገና ዝቅ፤ አንዴ ወደ ግራ፣ መልሰው ወደ ቀኝ በመወዝወዝ ዜማውን ሲያንቆረቁሩት ከአምላክ ጋር በአካል የተገናኙ ይመስላሉ፡፡ ዜማው ግሩም ነው፤ ቢሰሙት፣ ቢያዳምጡት፣ የማይጠገብ፤ ዝማሜው ታይቶ የማይሰለች ፍፁም ውብ ጥበብ፡፡
አቋቋም የሚያገለግለው ልክ እንደ ቅዳሴው ሁሉ አምላክን ለማመስገን ነው፡፡ ንባቡ የተቀመረውም ቅዱስ ያሬድ ከመጽሐፍ ቅዱስ አውጣጥቶ ከአዘጋጀው “ድጓ፣ ጾመድጓና ዚቅ” ከተባሉ የዜማ መጻሕፍት ነው፡፡
ከድጓ፣ ከጾመድጓ፣ ወይም ከምዕራፍም ሆነ ከመዋስእት ለበዓሉ (ለዕለቱ) ተስማሚ የሆነው ተመርጦ ሥርዓቱ በሚፈቅደው አዚያዚያም መሠረት (ግዕዝ ወይም ዕዝል) መጀመሪያ ይዜምና ቀጥሎ በመቋሚያ በመታጀብ ዝማሜው ይከናወናል፤ ከዝማሜው (በአቋቋም የታጀበው ዜማ) ሲጠናቀቅ በጸናጽል እና በከበሮ እየተደጋገመ ይዜማል፤ የዜማዎቹ መጠሪያም “ንዑስ (ትንሽ) መረግድ” በሚባል ቀስ ያለ የዜማ ስርዓት ይጀምርና ወደ ከፍተኛ (ዐባይ) መረግድ (የዜማ አይነት) ይሸጋገራል፤ ከዚያም ምቱ ፈጣን ወደሆነ ዜማ (ጽፋት) ተቀይሮ በመቋሚያ የተጀመረው ምስጋና ይጠናቀቃል፤ ሆኖም ይህ ድርጊት በአንድ ቀን፤ ግን በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ሊደጋገም ይችላል፡፡
 ዝማሬ መዋስእት
ዝማሬ መዋስእት የተደረሰው በ6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በቅዱስ ያሬድ ሆኖ፣ የተደረሰበት ቦታም በደቡብ ጐንደር ዞን የሚገኝ ሲሆን “ዙር አምባ” ይባላል፡፡
ዝማሬ መዋስእት የሚያገለግለው ለሁለት ጉዳዮች ነው፤ አንደኛ ከቅኔ በኋላ በቤተክርስቲያን ውስጥ በሚከናወን ሥርዓት ላይ ከእጣነ ሞገር (ቅኔ) በፊት የሚፈጸም ነው፡፡
መጀመሪያ መምህሩ ወይም ለዚህ ተግባር የተመረጠ ባለሙያ እየመራ፤ እሱ የሚመራውን ዜማ ሌላ ሰው ከፊት ለፊቱ እግሮቹን ገጥሞ ቆሞ በዜማ እየተመራ ዘሩን (የዕለቱን ዝማሬ መዋስእት) ይዘልቃል፡፡ ከዚያ ካህናቱ በዝማሜ ሊደግሙት ይችላሉ፤ ወይም በጸናጽልና ከበሮ ብቻ በማዜም ሊያጠናቅቁት ይችላሉ፡፡
ካልሆነም አንድ ሰው ብቻውን በዜማ ሊዘልቀውና ሥርዓቱ በዚሁ ሊጠናቀቅ ይችላል፡፡ከዚህ በተለየ ሁኔታ ዝማሬ መዋስእት ሰው ሲሞት ለፍትሐት አገልግሎትም ይውላል፤ ከመዝሙረ ዳዊት የተወሰነውን በዜማ በማጀብ የያሬድ መዋስእት ሥራ ላይ ይውላል፡፡
የዜማው ሥርዓት በአብዛኛው ሐዘንን የሚገልፅና ጠንከር ያለ ነው፡፡ከዚህ ሌላ ዜማ ወጥቶላቸው ሥርዓት ተበጅቶላቸው የሚዜሙ በርካታ የትምህርት አይነቶች አሉ፤ ለምሳሌ የሰባቱ ቀኖች ውዳሴ ማርያም፣ መልክአ ማርያም፣ መልክአ ኢየሱስ፣ አርባዕት፣ ሰለስት፣ ወዘተ በዜማ የሚጸለይባቸውና በተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ናቸው፡፡መልኮችም ሆኑ ውዳሴ ማርያምና ሌሎች ዘሮች የተደረሱት ለተለያዩ ሰዎች መሆኑ ቢታመንም የዜማው ምንጭ ግን ቅዱስ ያሬድ መሆኑን ሊቃውንት ይስማሙበታል፡፡ ቸር ይግጠመን!

Published in ጥበብ
Saturday, 11 October 2014 15:53

የፍቅር ጥግ

ሚስት ያላገባ ወንድ፣ አበባ አልባ የአበባ ማስቀመጫ እንደማለት ነው፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
የሚስትህን የልደት ቀን ለማስታወስ ትክክለኛው መንገድ አንድ ጊዜ መርሳት ነው፡፡
- ኤች.ቪ. ፕሮንችኖው
ፍቅር እውር ነው፤ ትዳር ግን የብርሃን ፀጋውን መልሶ ያጐናፅፈዋል፡፡
ሳሙኤል ሊችቴንበርግ
ትዳር፤ ከጠላትህ ጋር አንድ አልጋ የምትጋራበት ብቸኛው ጦርነት ነው፡፡
ፍራንሶይስ
ብዙ ቤተሰብ ባለበት ቤት ውስጥ ነው ያደግሁት፡፡ እውነት ለመናገር ሚስት እስካገባ ድረስ ብቻዬን ተኝቼ አላውቅም፡፡
ልዊስ ግሪዛርድ
ባል ማግባቴን እወደዋለሁ፡፡ በቀሪው ህይወታችሁ ልታበሽቁት የምትፈልጉት አንድ የራሳችሁ ሰው ማግኘት ድንቅ ነው፡፡
ሪታ ሩድነር
ትዳር እስከምይዝ በፍፁም በፍቺ አምኜ አላውቅም፡፡
ዲያኔ ፎርድ
ብቸኛ ለመሆን እርግጠኛው መንገድ ትዳር መያዝ ነው፡፡
ኖራ ኢፍሮን
ማንኛውም ያገባ ወንድ ስህተቶቹን መርሳት አለበት - ሁለት ሰዎች ተመሳሳይ ነገር ማስታወሳቸው ምንም ፋይዳ የለውም፡፡
ዱዌኔ ዴዌል
ትዳር ሌሊት ብቻቸውን መተኛት ለሚፈሩ ሰዎች ጥሩ ነው፡፡
ሴይንት ጄሮሜ
ከፍቅር የምንወደው ትኩሳቱን ነው፤ ትዳር ደግሞ አልጋ ላይ ያስተኛውና ይፈውሰዋል፡፡
ሚኞን ማክላውግሊን


Published in ጥበብ
Page 8 of 15