ኢ/ር ይልቃል በሰብሳቢነት ተመርጠዋል

ዘጠኝ ህብረ ብሄራዊና ብሄር ተኮር ፓርቲዎች በአገሪቱ ወቅታዊና አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ የተፈራረሙ ሲሆን የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት የትብብሩ ሰብሳቢ ሆነው ተመርጠዋል፡፡
የትብብር ስምምነቱን የፈረሙት የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ የመላው ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (መኢዴፓ)፣ የመላው አማራ ህዝብ ድርጅት (መአህድ)፣ ሰማያዊ ፓርቲ (ሰማያዊ)፣ የሶዶ ጎርዶና ህዝብ ዴሞክራሲዊ ድርጅት (ሶጎህዴድ)፣ የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት ፓርቲ (አብአፓ)፣ የኦሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ህብረት (ኢህዴህ)፣ የከምባታ ህዝቦች ኮንግረስ (ከህኮ) እና የጌዲኦ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ጌህዴድ) ሲሆኑ የትብብር ስምምነቱን የመሰረቱት በሶስት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ አተኩሮ ለመስራት እንደሆነም ከትላንት በስቲያ በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡
ዋና ዋና ጉዳዮች የተባሉት ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ አሳታፊና ተአማኒ ምርጫ እንዲኖር፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ማስፋትና የዜጎች ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን በሚመለከት እንቅስቃሴ ማድረግ የሚሉ ናቸው፡፡
“የትብብር ስምምነቱን ለመመስረት ጉዞ ከተጀመረ ሁለት ዓመት ሆኖታል” ያሉት ሰብሳቢው ኢ/ር ይልቃል፤ በተለይም እስካሁን የተደረጉ የትብብር ጥረቶች ለምን አልተሳኩም የሚለውን ጥያቄ ለመመለስና መፍትሄ ለመስጠት የትብብሩ አባል ፓርቲዎች ባደረጉት ግምገማና ዳሰሳ ውጤት ላይ በመመስረት ለእነዚህ የግምገማ ውጤቶች ምላሽ ለመስጠት በጋራ የሚሰሩበትን የስምምነት ሰነድ መፈራረማቸውን ገልጸዋል፡፡ የትብብር ስምምነቱም በአገሪቱ ወቅታዊና አንገብጋቢ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው ተብሏል፡፡ ስምምነቱ በዋናነት በ2007 ምርጫ የትብብሩ አባል ፓርቲዎች በጋራ የሚቆሙበትን ሁኔታ ለማመቻቸትና በመካከላቸው ያለውን ግንኙነት አጠንክረው በመቀጠል በኢትዮጵያ መምጣት ያለበትን ለውጥ መሰረት በማድረግ በትብብር ለመስራት የሚችሉበትን ጠንካራ የጋራ የፖለቲካ ኃይል ለመፍጠር መሆኑን ገልጸዋል፡፡
“ለትብብር ስምምነቱ ባደረጋችሁት የዳሰሳ ጥናት እስከዛሬ ለትብብሩ አለመሳካት እንቅፋት ሆነው ያገኛችኋቸው ምክንያቶች ምንድንናቸው? የትብብር ስምምነቱን የተፈራረማችሁ ፓርቲዎችስ እርስ በእርስ ምን ያህል ተዋውቃችኋል?” በሚል ከአዲስ አድማስ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱም፤ “እስከዛሬ ትብብሮች ያልተሳኩት እርስ በእርስ አለመደማመጥ፣ የፖለቲካ ባህሉ የሃሳብ ልዩነቶችን የሚያከብር አለመሆን፣ በጠራ ሃሳብ ላይ የቆመ ወጥ ሃሳብ አለመኖርና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ሲያጠፉ እነሱን መናገር የተቃውሞውን ጎራ ይጎዳል በሚል ነገሮችን አለባብሶና አደባብሶ ማለፍ ስለነበረ ነው” ብለዋል፡፡ ፓርቲዎች ምን ያህል ተዋውቃችኋል የሚለውን በተመለከተ በሰጡት ምላሽም፤ “ፓርቲዎች ስምምነት ላይ የደረሱት በአገሪቱ ወቅታዊ ችግሮች ላይ በትብብር የተግባር ስራ (functional relation) ለመስራት እንጂ የመዋቅር ጉዳይ ባለመሆኑ ችግር አይፈጠርም” ብለዋል፡፡ ለትውውቁም ቢሆን በቂ ጊዜ ነው፤ ይህ ስምምነት ከ33ቱ ፓርቲዎች ትብብር ጥንስስ የመጣ ነው ያሉት የትብብሩ ኃላፊዎች፤ ግንኙነታችንን አጠንክረን እስከ ውህደት የሚያበቃንን የረጅም ጊዜ እቅድም ታሳቢ አድርገናል ብለዋል፡፡ እስከዛሬ ብዙ ትብብሮች አልተሳኩም፤ ይሄኛውስ ለቀጣይነቱ ምን መተማመኛ አለው፣ ብሄር ተኮርና ህብረ ብሄር ፓርቲዎች አብረው መስራታቸውስ በትብብሩ ላይ እንቅፋት አይፈጥርም ወይ በሚል ከጋዜጠኞች ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የትብብሩ ሰብሳቢ ኢ/ር ይልቃል፤ “እስከዛሬ በታየው የትብብሮች አለመሳካት የተነሳ በእኛም ትብብር ላይ እንደ ዜጋ ጥርጣሬ ቢያድርባችሁ ተገቢ ነው” ካሉ በኋላ፣ የትብብሩ አባል ፓርቲዎች በዳሰሳ ጥናቱ ችግሮቹን ለመለየት ባደረጉት ሙከራ ለትብብሩ አለመሳካት እንደችግር ከተነሱት ውስጥ ፓርቲዎች የውስጥ ችግሮቻቸውን መፈተሽ አለመቻል፣ በመከባበር ሽፋን ችግሮችን አለባብሶ ማለፍና ሌሎችም በመገኘታቸው እነዚህን ጉዳዮች በድፍረት ተነጋግረው ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ተናግረዋል፡፡
 “የእኛ ትብብር ረጅም ርቀት እንዲጓዝ የሚያስችለውን በጠራ ሃሳብ ላይ የመቆም ሁኔታ በዋና መሰረትነት አስቀምጠናል” ያሉት ኢ/ር ይልቃል፤ እስከዛሬ እንቅፋት ሆነው ትብብርን ሲያደናቅፉ የነበሩ የፓርቲና የግለሰብ አይነኬዎች፣ የአሸናፊና ተሸናፊ አይነት ሂደቶችና በውስጥ ችግራችን ምክንያት ለውጭ ተፅዕኖ የምንጋለጥባቸውን አሰራሮች ከእንግዲህ ተሸክመን ላለመቀጠል በግልፅ ስለተነጋገርን ትብብራችን እክል ይገጥመዋል ብለን አናስብም ብለዋል፡፡ የብሄር ተኮር እና ህብረ ብሄራዊ ፓርቲዎች በጋራ መስራታቸውን በተመለከተም ሁለቱም አይነት ፓርቲዎች የሚጮሁት ለነፃነትና ለእኩልነት በመሆኑ አብሮ መስራታቸው ችግር እንደሌለው የትብብሩ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ግርማ በቀለ ተናግረዋል፡፡
ትብብሩን በተሳካ ሁኔታ ለመምራት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ሰብሳቢ፣ አቶ ግርማ በቀለ ም/ሰብሳቢ፣ አቶ ኤርጫፎ አርዴሎ ፀሐፊ፣ አቶ ካሳሁን አበበ ም/ፀሐፊ እንዲሁም አቶ ኑሪ ሙደሲር የፋይናንስ ኃላፊ ሆነው መመረጣቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችም ወደ ትብብሩ በመምጣት በአገራቸው ጉዳይ ላይ አብረው እንዲሰሩ የትብብሩ ኃላፊዎች ጥሪ አቅርበዋል፡፡


Saturday, 25 October 2014 10:15

የህፃናት ጥግ

የ4 ዓመት ህፃን ከእናቱ ጋር የፎቶ አልበም ሲመለከት ዓይኑ ነፍሰ ጡር ሆና የተነሳችው ፎቶ ላይ ያርፋል፡፡
ህፃን - ማሚ፤ ሆድሽ ለምን ትልቅ ሆነ?
እናት - አንተ ሆዴ ውስጥ ስለነበርክ፡፡
ህፃን - ያኔ ውጠሽኝ የነበረ ጊዜ?
***
ሴትየዋ የ3 ዓመት ዕድሜ ካለው የልጅ ልጃቸው ጋር በስልክ ሲያወሩ ህፃኑ የሚላቸው ስላልተሰማቸው አስሬ “ምን? ምናልከኝ?” እያሉ ያስቸግሩታል፡፡ ህፃን ሆዬም፤ “እማማ፤ ጮክ ብለሽ እያዳመጥሽኝ አይደለም?” አላቸው፡፡
***
አያት የ3 ዓመት ህፃን የሆነውችን የልጅ ልጃቸውን ለማጫወት ያስቡና፤ “ቶሎ ቶሎ እያደግሽ እኮ ነው፤ ትንሽ ቀስ ማለት አለብሽ” ይሏታል፤ እየሳቁ፡፡
ህፃኗ ኮስተር ብላ፤ “የእኔ ጥፋት እኮ አይደለም”
አያት ተገርመው፤ “ታዲያ የማነው?”
ህፃን፤ “የማሚ!”
አያት “እንዴት?”
ህፃን፤ “እሷ ናታ … ቶሎ ቶሎ ልደቴን እያከበረች”
* * *
የ8 ዓመት ህፃን ለእጅ ሥራዋ የሚሆን ጨርቅ ለመቆራረጥ እናቷን መቀስ እንዲሰጧት ትጠይቃለች፡፡ እናትም በአቅራቢያቸው የነበረውንና የወርቅ እጀታ ያለውን ውብ መቀስ አንስተው ሰጧትና፤ “በጥንቃቄ ተጠቀሚበት፤ ለእኔ ትልቅ ትርጉም አለው” ይሏታል፡፡
ህፃን፤ “ዕድሜው ብዙ ነው እንዴ?”
እናት ልጃቸው የመቀሱን ታሪክ የማወቅ ፍላጎት ያደረባት ስለመሰላቸው ማስረዳት ጀመሩ፤ “ከእናቴ ነው የወረስኩት፤ እሷ ደሞ ከእናቷ … እናቷም ….”
ህፃን፤ “ለዚህ ነዋ…”
እናት፤ “ምን የሆነው?”
ህፃን፤ “ዶልዱሞ የማይቆርጠው”

Published in ጥበብ

“ስልጠናው ለመማር ማስተማሩ የጨመረው ነገር የለም” - መምህር
“ስልጠናው ውጤታማ ነው፤ መግባባትም ተፈጥሯል” - መንግሥት

    ለዩኒቨርሲቲ መምህራን በመንግስት ፖሊሲዎችና በሃገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ከተሰጠው  ስልጠና ምንም አዲስ ነገር አለማግኘታቸውን የተናገሩ ሰልጣኞች፤ ለአስር ቀናት የዘለቀው ስልጠና ውጤታማ ነበር ለማለት አያስደፍርም ይላሉ፡፡  መንግስት በበኩሉ፤ ለተማሪዎችም ሆነ ለዩኒቨርሲቲ መምህራን የተሰጠው ስልጠና ለበርካቶች ግንዛቤ እንደፈጠረና ውጤታማ እንደነበርም ገልጿል፡፡ ከአብዛኛው ሰልጣኝ ጋርም መግባባት ተፈጥሯል ይላል፤ መንግስት፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለአስር ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ በቆየው ስልጠና፣ በቀን 4 ጊዜ አቴንዳንስ (የተሳታፊ መቆጣጠሪያ መዝገብ) ላይ እየፈረሙ መሳተፋቸውን የሚናገሩት የፖለቲካል ሳይንስ መምህሩ ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ “ስልጠናው፤ ኢህአዴግ በኔ ካመናችሁ መንግስተ ሰማያት ትገባላችሁ በሚል ምሁራኑን ለራሱ ፖሊሲ ማስፈፀሚያነት ለመጠቀም የተንቀሳቀሰበት ነው” ብለዋል፡፡
በስልጠናው የታዘቡትን የጠቆሙት ዶ/ር መረራ፤ ተሳታፊዎች እሳቸው ከጠበቁት በላይ  የሃገሪቱን ዋና ዋና የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ጥያቄዎች ከሞላ ጎደል ማንሳታቸውን ይናገራሉ፡፡ ከመደብ ጥያቄ እስከ አካዳሚክ ነፃነት ድረስ እንዲሁም ስለ ሙስና፣ ስለ ምርጫ፣ ስለ ፌደራሊዝምና የመሳሰሉት ጉዳዮችም በስፋት ተነስቷል፤ ነገር ግን በቀረቡት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ላይ ከመድረኩ በቂ ምላሽ አልተገኘም ባይ ናቸው - ምሁሩ፡፡
በስልጠናው ወቅት የዩኒቨርሲቲ መምህራኑን እንደተማሪ ቆጥረው በቀን 4 ጊዜ የተሳታፊ መቆጣጠሪያ መዝገብ ላይ ማስፈረማቸው ስልጠናው በግድ የተካሄደ ነው የሚያሰኝ ነው ብለዋል፤ ዶ/ር መረራ፡፡ መምህራኑ በተለይ የአካዳሚክ ነፃነትን በተመለከተ ላነሱት ጥያቄ አሰልጣኞቹ ምላሽ መስጠት ተስኗቸው፣ ነገሮችን አድበስብሶ ለማለፍ ሲሞክሩ እንደነበር ያስታወሱት ምሁሩ፤ በብሄራዊ መግባባትና በሃይማኖት ነፃነት ላይ የቀረቡ ሃሳቦች ብዙ ጥያቄና ሰፊ ክርክር እንዳስነሱ ተናግረዋል፡፡  
“ለምንድን ነው ከብሄራዊ እርቅ የምትሸሹት? አሁን እንኳ ወደኛ ስትመጡ የእባብ ልብ ይዛችሁ ነው” የሚሉ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ሲቀርቡ ታዝቤያለሁ ያሉት ዶ/ር መራራ፤ ስልጠናው መምህራን በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ስሜታቸውን ያንፀባረቁበት፣ ቀድሞ በሃገሩ ጉዳይ ላይ ዝምታን መርጦ የነበረው ሁሉ ከተኛበት ተነስቶ  ጠንከር ያለ አስተያየትና ጥያቄ ያቀረበበት ነበር ብለዋል፡፡ በተለይ ስለ ወደብ ብዙ ጥያቄ መቅረቡን የገለፁት ምሁሩ፤ ኢህአዴግ የተኛውን ጭምር  በራሱ ላይ የቀሰቀሰበት መድረክ እንደነበር ይናገራሉ፡፡
ሌላው የስልጠናው ተሳታፊ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋና ሥነፅሁፍ ምሁር ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ በበኩላቸው፤ ለመምህራኑ የተሰጠው ስልጠና ቀድሞ ከሚታወቁት ጉዳዮች የተለየ አዲስ ነገር ይዞ የቀረበ አይደለም ብለዋል፡፡ የማወያያ ሰነዶች የተባሉትም ሆነ ርዕሰ ጉዳዮቹ ከዚህ በፊት በተለያዩ ቦታዎች የመነጋገሪያ አጀንዳ የሆኑና የመንግሥትን አቋም የሚያንፀባርቁ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡
ስልጠናው ምናልባት መንግሥት ምሁራኑ ያላቸውን አስተሳሰብና ምልከታ ለማወቅ ይረዳው እንደሆን እንጂ፣ ለመምህራኑ የሚጨምረው አዲስ እሴት ይኖራል ተብሎ አይታሰብም ያሉት ዶ/ር በድሉ፤ በመጨረሻዎቹ ሁለት ቀናት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የቦርድ  ሰብሳቢ በሆኑት አቶ ካሣ ተክለብርሃን በተመራው ውይይት ላይ ስለትምህርትና ተያያዥ ጉዳዮች ከመነሳቱ ውጪ በሌሎች ቀናት ፖለቲካዊ ጉዳዮች ብቻ ለውይይት መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ “ያም ቢሆን ከመምህራኑ ለቀረቡት ጥያቄዎች መልስ የተገኘበትና ለችግሮች መፍትሄ ያበጀ ነው ለማለት አያስደፍርም” ብለዋል፤ መምህሩ፡፡
አንድ ስልጠና ወይም ስብሰባ ውጤታማ ሆነ ሊባል የሚችለው ከስብሰባው በፊት ያለው ነገር ከስብሰባው በኋላ ሲለይ ነው የሚሉት ምሁሩ፤ በስልጠናው ከዚህ አንፃር አዲስ ነገር ተፈጥሯል ማለት እንደማይቻልና ውጤታማ ነበር ለማለት እንደማያስደፍር ተናግረዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የመብራት መቋረጥ ችግር እንዳለ የጠቆሙት ዶ/ር በድሉ፤ ለስልጠናው በወጣው ወጪ ጀነሬተር ቢገዛበት በመማር ማስተማር ሂደት ላይ በተግባር የሚታይ ለውጥ ያመጣ ነበረ ሲሉ ተችተዋል፡፡ ስልጠናው ለመማር ማስተማሩ ሂደት የጨመረው ነገር የለም ብለዋል - ምሁሩ፡፡
ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ በዩኒቨርስቲው የማህበራዊ ሳይንስ የትምህርት ክፍል መምህር፤ ስልጠናው ቀድሞ ከሚታወቁ ጉዳዮች የተለየ አዲስ ነገር ይዞ ያልመጣ፣ የሚታወቁና የነበሩ ነገሮችን የደጋገመ መድረክ ነው ብለዋል፡፡ በፖለቲካው ዙሪያ የተነሱ በርካታ አስተያየቶችና ጥያቄዎችን ተቀብሎ በጉዳዮቹ ላይ ማስተካከያ እናደርጋለን ወይም አስተያየቶቹን ተቀብለናል የሚል ነገር ከመድረክ መሪዎቹ አልሰማሁም ያሉት መምህሩ፤ “እውነታው ይሄ ነው፤ በቃ ተቀበሉ አይነት መድረክ ነበር” ይላሉ፡፡
መንግሥት ከማን ጋር ምን መስራት እንደሚፈልግ እንደማያውቅ፣ በተለይ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ምሁራኖችንና ኤክስፐርቶችን ያለመጠቀም ችግር እንዳለበት የተረዳሁበት አጋጣሚ ነው ያሉት አስተያየት ሰጪው፤ ለምሳሌ የድንበር ጉዳይን ከምህንድስና ባለሙያዎች ጋር ከመወያየት ይልቅ ከፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን ጋር መወያየት ይሻል ነበር ብለዋል፡፡
በቀን 4 ጊዜ ‘አቴንዳንስ’ መቆጣጠር በራሱ አስገራሚ ነበር ያሉት መምህሩ፤ ሂደቱ በዚህ መልክ ባይሆን ይመረጥ እንደነበር ጠቁመው ስልጠናው በብዙ መመዘኛ ማራኪና ውጤታማ ነበር ለማለት ይከብደኛል ብለዋል፡፡
ሌላው አስተያየት ሰጪ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ የኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ የትምህርት ክፍል መምህር እንዳሉት፤ ስልጠናው መከናወኑ የሚነቀፍ ባይሆንም ለስልጠናው የተመረጡት ርእሰ ጉዳዮች ግን ምሁራኑን የሚመጥኑ አይደሉም፡፡ “ብዙ የተመራመሩ ምሁራኖች ባሉበት መድረክ ስለ ሃይማኖት ገለልተኝነት፣ ስለ ኒዮሊበራሊዝም፣ ስለ ፌደራሊዝም የመሳሰሉትን ጉዳዮች አንስቶ በዚህ ዙሪያ እውቀት ያጥራችኋል፤ እናሰልጥናችሁ መባሉ ተገቢ አልነበረም” ያሉት መምህሩ፤ አሰልጣኞቹ ኋላ ላይ ለቀረቡላቸው ጠንከር ያሉ ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት እያቃታቸው ከመምህራኑ ጋር ይፋጠጡ ነበር ብለዋል፡፡
ስልጠናው ውጤታማ ነበር ወይንስ አልነበረም የሚለውን የስልጠናው ባለቤት ራሱ ቢገመግም መልካም ነው ያሉት መምህሩ፤ በግላቸው ቀድሞ በሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ከነበራቸው እውቀት የተለየ የጨመረላቸው ነገር እንደሌለ ጠቁመዋል፡፡
በዚያው ዩኒቨርስቲ መምህር የሆኑት ሌላው ስሜ አይጠቀስ ያሉ አስተያየት ሰጪ፣ ስልጠናው አቴንዳንስ የሚያዝበት ቢሆንም ከ10 ቀናት ውስጥ ለ3 ቀናት ብቻ ስልጠናው ላይ መሳተፋቸውን አስታውሰው፤ በወቅቱ ሲነሱ የነበሩት ሃገራዊ ጉዳዮች ጥሩ እንደነበሩና የውይይት መድረክ አይነት ስሜት እንደፈጠረላቸው ይናገራሉ፡፡ “እንደዚህ አይነት የፖለቲካ ውይይት የሚካሄድባቸው መድረኮች ላይ ተሳትፌ አላውቅም” ያሉት አስተያየት ሰጪው፤ በአንዳንድ የሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ግንዛቤ ለሌላቸው ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ብለዋል፡፡ በተለይ በሳይንሱ ዘርፍ ሀገሪቱ የበለጠ ለማደግ ያላት ፍላጐት የሚበረታታ ነው የሚሉት መምህሩ፤ በቀጣይ መንግሥት ከምሁራኑ ጋር ተቀራርቦ መስራት አለበት፣ በየጊዜውም ከፖለቲካው ባሻገር በችግሮቻችን ላይ ውይይቶች መካሄድ አለባቸው ሲሉ መክረዋል፡፡
በቅርቡ ከአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበርነታቸው በፈቃዳቸው የለቀቁት የዩኒቨርሲቲ መምህር ኢንጂነር ግዛቸው ሽፈራው፤ በስልጠናው ላይ ለአንድ ቀን ብቻ መሳተፋቸውን ገልፀው በቀሪዎቹ ቀናት አለመሳተፋቸውን፣ ስልጠናው አስፈላጊ አልነበረም ብለው እንደሚያምኑም፡፡
አንጋፋው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ፖለቲከኛ ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው፤ በስልጠናው ሙሉ ለሙሉ ባይሳተፉም ሰነዶቹ የፓርቲውን ፕሮግራምና አላማ እንዲሁም ርዕዮተ ዓለም የማስረፅ ሚና ያላቸው እንጂ እንደተባለው በመንግስት ፖሊሲዎች ላይ የሚሰጥ ስልጠና ሆኖ እንዳላገኙት ተናግረዋል፡፡
በየደረጃው ለመምህራንና ተማሪዎች እየተሰጠ ያለው ስልጠና የመጪው ምርጫ ቅስቀሳ አካል እንደሆነ መገንዘባቸውንም ፕ/ር በየነ ገልፀዋል፡፡ መንግስት ፖሊሲውንና የልማት ስራውን ለማስገንዘብ ብቻ አቅዶ የተንቀሳቀሰ ቢሆን ኖሮ ከስልጠና ይልቅ ሴሚናርና ዎርክሾፕ ማዘጋጀት ይበቃው ነበር ያሉት መምህሩ፤ የፓርቲ አጀንዳን በመንግስት ሃብትና መዋቅር ማስረፅ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
በሁለተኛው መደበኛ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ስብሰባ ላይ በም/ቤቱ አባላት ለቀረቡ የማሻሻያ ሞሽኖችና ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፤ “ለዩኒቨርስቲ መምህራንና ተማሪዎች በተሰጠው ስልጠና መንግሥት በተለያዩ ሀገራዊ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ላይ ሃሳቦችን አቅርቧል፤ መምህራንና ተማሪዎቹም በዲሞክራሲያዊ መንገድ የሚመስላቸውን ጥያቄና አስተያየት ሰንዝረዋል፤ በዚህም እጅግ ከአብዛኛው ሰው ጋር መግባባት ፈጥረናል” ብለዋል፡፡ ከመምህራኑ ጋር ውይይት ከተደረገ በኋላ ዩኒቨርስቲዎች በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዱ ላይ በእውቀትና በክህሎታቸው የድርሻቸውን ለመወጣት መስማማታቸውንና መጓጓታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡
ከመምህራኑ ጋር የተደረገው ውይይትም ስኬታማ ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ውይይቱ የሀገራዊ መግባባቱ አካል ነው ብለዋል፡፡ ለተማሪዎች በተሰጠው ስልጠና ላይም የጠባብነትና ትምክህተኝነት አስተሳሰቦች ላይ ውይይት ተደርጐ አመርቂ ውጤት እንደተገኘ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም አክለው ገልፀዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በነሐሴ ወር ላይ የተጀመረው ስልጠና፣ በአሁኑ ወቅት ለመንግሥት ሠራተኞች እየተሰጠ እንደሆነ ይታወቃል፡፡  


የኢምሬትስ አየር መንገድ በቀጣይ አስር ዓመት ውስጥ ትኩረቱን በአፍሪካ ላይ በማድረግ የገቢ ድርሻውን በ40 በመቶ እንደሚያሳድግ አስታውቋል፡፡
ባለፈው ሳምንት በዱባይ በተካሄደው የአፍሪካ ዓለም አቀፍ ቢዝነስ ፎረም ላይ የኢምሬትስ አየር መንገድ ፕሬዚዳንት ቲም ክላርክ፤ አፍሪካ ለኢምሬትስ ትልቅ የዕድገት ምንጭ መሆኗን ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ኢምሬትስ በአፍሪካ የ7 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት እንዳለው ገልጸው በቀጣይ አመታት ውስጥም ተጨማሪ 10 መዳረሻዎችን በመጨመር አህጉሪቱ ከእስያ፣ ከመካከለኛው ምስራቅና ከአውስትራሊያ ጋር ያላትን የንግድ ግንኙነት ይበልጥ ለማሳደግ፣ ዱባይንም እንደማዕከል በመጠቀም አፍሪካን ከቀሪው ዓለም ጋር ለማገናኘት እየሰራን ነው ብለዋል፡፡
የአየር መንገዱ መረጃ እንደሚያመለከተው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት አየር መንገዱ 1.6 ሚሊዮን የሚደርሱ ተሳፋሪዎችንና 40 ሺህ ቶን እቃዎችን በአፍሪካና በቻይና መካከል አመላልሷል፡፡ እስከ 2020 ዓ.ም ተጨማሪ 8.5 ሚሊየን መቀመጫዎችን ለአፍሪካ እንደሚጨምር ተገልጿል፡፡
ከ5 መቶ ሺህ በላይ አፍሪካውያን በዱባይ እንደሚኖሩና በ2013 ከ8 መቶ ሺህ በላይ አፍሪካውያን ዱባይን እንደጎበኙ የተገለጸ ሲሆን በ2020 ዓ.ም 1.5 ሚሊዮን የሚደርሱ አፍሪካውያን ዱባይን እንደሚጎበኙ ተገምቷል፡፡

ከእለታት አንድ ቀን አንድ ሚስቱ ላይ የሚኮራ የሚኩራራ ጉረኛ ባል ነበረ፡፡ አንድ ማታ ሲመጣ ክፉኛ ተፈንክቷል፡፡
“ምነው ውዴ! ምን ነካህ?” አለችው ሚስቱ፡፡
“ዛሬ ምን እንደሆነ ታውቂያለሽ?” አለና ጀመረ፡፡
“ምን ሆነ የእኔ ጌታ?”
“አንዱ አጉል ልታይ ልታይ ባይ ጉራውን ሲነዛ አግኝቼው ‹እረፍ!› አልኩት”
“ማ? ማነው እሚያርፈው?” አለኝ፡፡
“አንተ ነሃ! ካንተ ሌላ ጉራ እሚነዛ አለ እንዴ?”
“አፍህ ካላረፈ እኔ ራሴ አሳርፍሃለሁ! አይለኝም?!”
‹በቃ ወጣ ብለን መተያየት ነዋ!› አልኩትና ቀድሜ ወጣሁ ከቡና ቤቱ፡፡”
ሚስትየውም “ከዛስ?” አለችው፡፡
ባል “እሱም ተከትሎኝ ወጣ!”
ሚስት “ከዛስ?”
ባል “ቀድሜ ቡጢ አቀመስኩት”
ሚስት “ከዛስ? ወደቀ?”
“አይ አልወደቀም”
“ታዲያ ምን ሆነ እሺ?”
“ተቀማመስን”
“ከዚያስ?”
“ከዚያማ እንደምታይኝ ተፈነከትኩ”
“ይሄማ ቡጢ አይደለም!... ዱላ ይዞ ነበር?”
“አይ አንቺ! ወንድ መስሎሻል? ዱላ ይዞ የሚዞር፣ የእኔኑ ነጥቆ ነው እንጂ!?”
*  *    *
የሀገራችን ታሪክ ይሄው ነው! ዱላ ያልያዘው መቺ ነው! ምነው ቢሉ፤ ባለ ዱላው ያቀብለዋልና! ተከራካሪው የሚያቀርበውን ሙግት ተፃራሪው ወስዶ ይሟገትበታል፡፡ “ከሞኝ ደጅ ሞፈር ይቆረጣልም” ነው፡፡ ያም ሆኖ የማታ ማታ ዱላ አቀብሎ ለመፈንከት አጉል መፎከር የቂል ቆንሲል መሆን ነው፡፡ ውስጠ - ሚስጥሩ ጥልቅ ነው፡፡ እነ ሆቺ ሚን በየዋሁ ዘመን “የመሣሪያ ምንጫችን ጠላታችን እራሱ ነው ይሉ ነበር!” ዛሬ ያ የሞኝነት መንገድ ይመስላል!
ችግር እያለብን ችግር የለብንም አንበል፡፡ “መንግስት ማለት የአገሩ አዕምሮ እንጂ የልቡ ሮሮ ብቻ አይደለም” ይላል የአገራችን ዋና ገጣሚ፡፡ ይህን አንርሳ!
“የአብራሄ - ህሊና፣ ዘመን  ፈላስፎች እነስፒኖዛ፣
ሎክ፣ ካንት፣ ሚል፣ ቮልቴር እና ዘመናዊዎቹ እነ ራሰልና ፐፐር … ሁሉም፡፡ ህይወት ማለት ችግር መፍታት ነው፤ ይላሉ፡፡ ምንም ፍፁም ነገር የለም! እድገት ሊመጣ የሚችለው ጥብቅና ኮስታራ እሳቤ ካለ ነው፡፡ ይህ እንግዲህ ከጭንቀት ነፃ የሆነ ነፃነትና ለታላቅነት ዕውቅና የመስጠት ብቃት ሲኖር ነው፡፡ ግን ድክመትን ለማሳየት አለመፍራት! ካለ ነው!” ይላሉ፡፡ የተባለውን ማጣራት የእኛ ፈንታ ነው፡፡ ህይወት ማለት ችግር መፍታት ነውና፡፡ ይህን ያላስተዋለ በችግር ላይ ችግር ቢፈጥር ውጤቱን እሱና እሱ ብቻ ነው የሚያገኘው!!
ከትዕዛዝ አክባሪነት ይልቅ ምክን ሊመራን ይገባል (ስፒኖዛ)፡፡  ትዕዛዝ አለማክበር በፍፁም ግብረገብነት አኳያ ሲታይ እንደጥፋት ይቆጠር ይሆናል፡፡ እንደሎሌነት ሲታሰብ ግን ትዕዛዝን መበገር አግባብ ይሆናል፡፡ ጌታ የሚያዘው የጌትነቱን ልክ ማሳያ አድርጎ ነውና!! አንዳንዴ “ልጅነትን የመሰለ ንፅህና የለም” የሚባለውን ለመቀበል መገደድ አግባብ ነው”፡፡ ቅንነት ወሳኝ ነው ለማለት ነው! ከትላንት ለመማር ቅንነት ያስፈልጋል፡፡ ቂም በቀል ሆድ ውስጥ ካመቅን ነገ ተመልሰን ወደዚያው ስህተት እናመራለን፡፡ ያ ከሆነ ከድጡ ወደማጡ መሄድ ነው፡፡ በራሳችን የትላንት ንፍቀ ክበብ ታጥረን፣ ሌላ ለማየት ተገድበን ያለፈው መርግ ከተጫነን፤ አባዜው አልለቀቀንም ማለት ነው፡፡ ገጣሚው እንዳለው፡-
“ያለፈው አልፏል እያልን፣ ዛሬም ወደዚያው ከሄድን
ድግግሞሹ ካጫጨን፣ እኛስ ከትላንት ምን ተሻልን?!”
ከክፋት ወደ ክፋት፣ ከኋላ ቀርነት ወደ ኋላቀርነት፣ ከጥፋት ወደ ጥፋት እንዳንሄድ አስተዋይ ልቦና ይስጠን፡፡ በስራም ቦታ፣ በፖለቲካ ዳርትም ሥፍራ፣ በህዝብ መሰብሰቢያም ሸንጎ፣ በኮንፈረንስና በሴሚናርም፣ በማህበረሰብም፣ በቤተሰብም፣ መልካም ነገሮችን ካላቆየን፤ ከአንዱ ወደ አንዱ መሄድ ከውድቀት ወደ ውድቀት፤ ከድቀት ወደ ድቀት እንደ መጓዝ ነው፡፡ የሀገራችን ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን እንዳለው፤
“ያገሬ ሰው ነገር፤ አብረን ወደላይ እንብቀል ሲሉት፤ አሸብልቆ ወደታች ወደመሬት ማጎንቆል” ይሆናል፡፡ የዚህ ውጤቱ የአፍሪካው ተረት ነው - “ከክፉ በሬ ጋር ውለህ፣ ወደ ክፉ ሚስት አትሂድ!”


Published in ርዕሰ አንቀፅ

“ክቡር ጠ/ሚ አባታችንን ከሞት ያድኑልን”  የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ልጆች

የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን በእስር ላይ በሚገኙት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ላይ ከአምስት አመታት በፊት የተጣለው የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እንዳይሆንና በቆንስላ ሰራተኞች መጎብኘት እንዲችሉ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ በግላቸው በላኩት ደብዳቤ መጠየቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ከትናንት በስቲያ ዘገበ የአቶ አንዳርጋቸው ልጆች አባታቸውን ከሞት እንዲታደጉላቸውና ከእስር ተፈትተው ዳግም የሚገናኙበትን መንገድ በማመቻቸት በኩል ድጋፍ እንዲያደርጉላቸው የሚጠይቅ ልብ የሚነካ ደብዳቤ እንደላኩላቸው የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን፣ የልጆቹን ጥያቄ መነሻ በማድረግ ለጠቅላይ ሚንስትር ሃይለማርያም ደብዳቤ መላካቸውን አስታውቀዋል፡፡
የእንግሊዝ የስራ ሃላፊዎች በእስር ላይ የሚገኙትን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን በቋሚነት መጎብኘት እንዲችሉ ግፊት ቢያደርጉም፣ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት በጎ ምላሽ እንዳልሰጡ ለልጆቹና ለእናታቸው በሰጡት ምላሽ የገለጹት ዴቪድ ካሜሩን፣ ከዚህ በፊት የተደረገው ጥረት ውጤታማ አለመሆኑን በማጤን በግላቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ደብዳቤ መላካቸውን አመልክተዋል፡፡የእንግሊዝ መንግስት የቆንስላ አባላት አንዳርጋቸው ጽጌን በቋሚነት መጠየቅና ማማከር የሚችሉበት ሁኔታ እንዲመቻችና መንግስታቸው ሲቃወመው የቆየው የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እንደማይሆን ማረጋገጫ እንዲሰጥ በላኩት ደብዳቤ መጠየቃቸውን የገለጹት ዴቪድ ካሜሩን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለ ማርያም ለደብዳቤያቸው በጎ ምላሽ እንደሚሰጧቸው ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡
የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ልጅ የሆነችው የ7 አመቷ ምናበ እና መንታ ወንድሟ ይላቅ፣ ለጠቅላይ ሚንስትር ዴቪድ ካሜሩን በላኩት ደብዳቤ፣ “አባታችን ልጆቹን የሚወድና የሚንከባከብ መልካም አባት ነው፡፡ አባታችንን ከእስር ለማስፈታት ምንድን ነው የሚያደርጉልን?” በማለት መጠየቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ የመጀመሪያ ል©cW የ15 አመቷ ህላዊት በበኩሏ፣ “አባታችን በጣም ናፍቆናል፡፡ እባክዎት በቅርብ ጊዜ መልሰው ወደ ቤታችን ያምጡልን” በማለት ስሜቷን እንደገለፀች ዘገባው ጠቁሟል፡፡

Published in ዜና

በድሬደዋ ገንደቆሬ አካባቢ ነዋሪ የነበረችው ወጣት ነፃነት መታፈሪያ፤ በጓደኛዋ በተደፋባት የፈላ ዘይት ህይወቷ አለፈ፡፡ ወጣቷ ለከፍተኛ ህክምና ወደ አዲስ አበባ የካቲት አስራ ሁለት ሆስፒታል ሪፈር ተደርጋ ለጥቂት ቀናት ህክምና ብትከታተልም ህይወቷን ማትረፍ አልተቻለም፡፡ በጓደኛዋ ላይ የፈላ ዘይት ደፍታለች ተብላ የተጠረጠረችው ወጣት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውላለች፡፡ ሟች ነፃነት መታፈሪያ፤ ከድሬደዋ ዩኒቨርሲቲ በአካውንቲንግ በዲግሪ በተመረቀች በሶስተኛው ቀን ነበር ከጓደኛዋ ጋር ስትጫወት ለማደር ከምትኖርበት ገንደቆሬ አካባቢ ሳቢያን ወዳለው የጓደኛዋ ቤት ያመራችው፡፡ምሽቱን በሳቅና በጨዋታ ያሳለፉት ሁለቱ የረዥም ዓመት ጓደኛሞች፤ ከምሽቱ 5 ሰዓት ገደማ ሲሆን ወደ መኝታቸው ያመራሉ፡፡ የቤቱ ባለቤት እንግዳ ጓደኛዋን ካስተኛች በኋላ መጣሁ ብላ ወደጓዳ ትመለሳለች፡፡ አንዳችም ክፉ ነገር ያልጠረጠረችው እንግዳ፤ ጋደም ብላ ጓደኛዋን እየጠበቀች ነበር - ጨዋታቸውን ለመቀጠል፡፡ ጓደኛዋ ግን ያሰበችውን ለመፈፀም ተዘጋጅታለች፡፡ እሳት ላይ ተጥዶ ሲፍለቀለቅ የቆየውን የፈላ ዘይት ይዛ ጓደኛዋ ወደተኛችበት አልጋ በመሄድ በሰውነቷ ላይ ገለበጠችባት፡፡ የዘይቱ ቃጠሎ አጥንቷ ድረስ ዘልቆ ያንገበገባት ተጐጂዋ፤ እሪታዋን አቀለጠችው፡፡ ወዲያው ጐረቤቶች ደርሰው ገላዋ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ በማፍሰስ ቃጠሎውን ሊያበርዱላት ሞከሩ፡፡ ሆኖም ስቃይዋን ሊያስታግሱላት አልቻሉም፡፡ ይኸኔ ነው ሌላ  ክፍል ተኝቶ የነበረው የተጠርጣሪዋ ባለቤት ወጣቷን በመኪናው ጭኖ ወደ ድል ጮራ ሆስፒታል የከነፈው፡፡ የሆስፒታሉ የህክምና ባለሙያዎች የመጀመርያ ደረጃ የህክምና እርዳታ ካደረጉላት በኋላ ጉዳቷ ከፍተኛ ህክምና የሚያስፈልገው መሆኑን በማረጋገጣቸው አዲስ አበባ ወደሚገኘው የካቲት 12 ሆስፒታል ሪፈር አደረጓት፡፡ በወጣቷ ላይ የደረሰው ዘግናኝ አደጋ ክፉኛ ያስደነገጣቸው የወጣቷ ቤተሰቦች፤ ነፃነትን ይዘው ወደ አዲስ አበባ መጡ፡፡ ለጥቂት ቀናት በየካቲት 12 ሆስፒታል ህክምና ሲደረግላት ብትቆይም ለውጥ ባለማግኘቷ ቤተሰቦቿ ወደ ኮሪያ ሆስፒታል ወሰዷት፡፡ ተጨማሪ ህክምና ለማግኘት ግን አልታደለችም፡፡ ጥቅምት 5 ቀን 2007 ዓ.ም ኮሪያ ሆስፒታል እንደደረሰች ህይወቷ አለፈ፡፡ ፖሊስ በሟች ሰውነት ላይ የፈላ ዘይት በማፍሰስ ለህልፈት የሚያደርስ ጉዳት ፈፅማለች ባላት ተጠርጣሪ ወጣት ላይ  ምርመራ እያካሄደና መረጃ እያሰባሰበ መሆኑን የድሬደዋ መስተዳድር ፖሊስ ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ዲቪዥን ኃላፊ፣ ዋና ኢንስፔክተር ገመቹ ካቻ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡    

Published in ዜና

የመንግሥት ስልጠና የምርጫ ቅስቀሳ አካል ነው ብሏል
የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ለምን ወጣ መባሉ ተገቢ አይደለም - ምርጫ ቦርድ

ምርጫ ቦርድ ከኢህአዴግ ተፅዕኖ ሙሉ ለሙሉ ነፃ መሆኑ ሳይረጋገጥና የምርጫ አፈፃፀም ችግሮች ሳይወገዱ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ለማወጅ መዘጋጀቱ ተገቢ አይደለም ሲል ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ የሚመሩት ኢማዴ-ደህአፓ ተቃወመ፡፡ መንግስት፤ የዩኒቨርሲቲ መምህራንና ተማሪዎችን ጨምሮ ለተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እየሰጠ ያለው ስልጠና የምርጫ ቅስቀሳ አካል ነው ሲልም ፓርቲው ኮንኗል፡፡
የኢትዮጵያ ማህበረ ዴሞክራሲ ደቡብ ህዝቦች አንድነት ፓርቲ ሰሞኑን ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ባስገባው ግልፅ ደብዳቤ፤ ያለፉት አገር አቀፍና የአካባቢ ምርጫዎች ከመካሄዳቸው በፊት በምርጫ ችግሮችና መፍትሄዎቻቸው ዙሪያ ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎች ጋር የሚወያይበት መድረክ እንዲዘጋጅ በተደጋጋሚ ብንጠይቅም እስካሁን ከቦርዱ የተሰጠ ተግባራዊ ምላሽ የለም ብሏል፡፡
ሃገሪቱ “በአንድ አውራ ፓርቲ” ብቸኛ ቁጥጥር ስር መውደቋ አደገኛና አሳሳቢ ነው ያለው ፓርቲው፤ የመድብለ ፓርቲ ስርአት የመገንባት ተስፋችን ጨርሶ እንዳይከስም ቦርዱ ሃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት አሳስቧል፡፡ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ የሚካሄድበትን ሁኔታ ለመፍጠር ገዥው ፓርቲና ሃቀኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚወያዩበት መድረክ እንዲያመቻች በህግ ስልጣን የተሰጠው ምርጫ ቦርድ የገባውን ቃል በማጠፍ መድረኩን ሳያመቻች የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማዘጋጀቱ ፋይዳ የለውም ብሏል - ፓርቲው፡፡
ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ በተሻሻለው የምርጫ ህግ፣ ለቦርዱ የተሰጠውን የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ መድረክ የማስተባበር ስልጣን ለመቀማት ታማኝ ፓርቲዎችን በተቃዋሚ ስም አሰባስቦ “የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ መድረክ” በመፍጠር የምርጫ ውድድር አሯሯጭ አሰልፏል ሲል ፓርቲው ተችቷል፡፡ገዥው ፓርቲ ያልተገደበ መንግስታዊ ስልጣኑን በመጠቀም የተለያዩ ጫናዎችን እያሳረፈ፣ ተቃዋሚ በሌለበት በአፈናና በጉልበት ሃገሪቱን በአምባገነንነት እየገዛ ነው ያለው ፓርቲው፤ በአሁኑ ወቅት መንግስት ለተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እየሰጠ ያለው ስልጠና የምርጫ ህግን የጣሰ የምርጫ ቅስቀሳ አካል ነው ብሏል፡፡ ለስልጠናው በሚሊዮን የሚቆጠር ሃብት ማባከኑም አግባብ አይደለም ሲል ፓርቲው ተቃውሟል፡፡ ምርጫ ቦርድ ከስነምግባር ደንቡ ውጪ የሆነውን የኢህአዴግን አካሄድ ማስቆም ሲገባው እርምጃ አለመውሰዱ ቦርዱ በፓርቲው ተፅዕኖ ስር መውደቁን ያሳያል ብሏል - ፓርቲው፡፡
የኢማዴ-ደህአፓ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጠናው በመንግስት ፖሊሲዎች ዙሪያ ግንዛቤ የማስጨበጥና መንግስታዊ ኃላፊነትን የመወጣት ስራ ነው ቢሉም ለስልጠና በተሰራጩ ሰነዶች ላይ “ፓርቲያችን ኢህአዴግ” የሚሉ አገላለፆች መስፈራቸውን ጠቁመው ይሄም በቀጥታ የመንግስት መዋቅርንና ሃብትን በመጠቀም የፓርቲን አጀንዳ የማስረፅ (ኢንዶክትሪኔሽን) ስራ ነው ብለዋል፡፡
በስልጠናው ወቅት የተበተነው ሰነድ ስለኢህአዴግ መስመር የሚተነትን ነው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ሰነዱ የፓርቲ እንደሆነ እየታወቀ ስልጠናው የመንግስት ነው ማለት ተቀባይነት እንደሌለው ተናግረዋል፡፡
“መንግስት ፖሊሲውን ለማስገንዘብና የፈፀማቸውን ተግባራት ለማሳወቅ ስልጠና ማዘጋጀት አይጠበቅበትም፤ በሴሚናርና በዎርክሾፕ መልክ መድረኮችን ማዘጋጀት ይችላል” ብለዋል ፕ/ር በየነ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በቅርቡ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ፤ “በምርጫ አሸንፎ ስልጣን የያዘ ፓርቲ የመንግስትን ፖሊሲ የማስረፅ ኃላፊነት እንዳለበት ገልፀው ለምን ይሄን አደረጋችሁ ብሎ መጠየቅ ህዝቡ ለምን መረጣችሁ እንደማለት ነው ብለዋል፡፡ የኢማዴ-ደህአፓ ደብዳቤ ለምርጫ ቦርድ ፅ/ቤት መድረሱን ያረጋገጡት የፅ/ቤቱ ም/ዋና ኃላፊ አቶ ወንድሙ ጎላ፤ ሁሉም ፓርቲዎች በምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ላይ ያላቸውን አስተያየት በፅሁፍ እንዲያቀርቡ በተጠየቀው መሰረት የቀረበ ደብዳቤ ነው፤ ቦርዱ ተሰብስቦ የሚያየው ይሆናል ብለዋል፡፡
ፓርቲው ለፅ/ቤታቸው ባስገባው ደብዳቤ፤ ተቃዋሚዎች ከኢህአዴግ ጋር የሚወያዩበት መድረክ እንዲዘጋጅ ተጠይቆ ምላሽ ሳይሰጥ የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ለማውጣት መጣደፍ አግባብ አይደለም ማለቱን የጠቀስንላቸው አቶ ወንድሙ፤ ለምርጫ ቦርድ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ትልቅ ትርጉም እንዳለው ጠቁመው፤ የጊዜ ሰሌዳ ለምን ይወጣል መባሉ ተገቢ አግባብ አይደለም ሲሉ ተችተዋል፡፡ ምክትል ዋና ኃላፊው፤ የውይይት መድረክ የተባለውን በተመለከተ ምርጫ ቦርድ በቀጣይ የሚያዘጋጀው ይሆናል ብለዋል፡፡ በጊዜያዊነት በወጣው የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ላይ የፓርቲዎች አስተያየት ከተሰበሰበ በኋላ በቦርዱ ውይይት ተደርጎበት ሲፀድቅ፣ ለህዝቡ ይፋ እንደሚደረግም አቶ ወንድሙ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

በሐዋሳ ከተማ የህግ ባለሙያውን አቶ ዳንኤል ዋለልኝን በጥይት ገድለው ተሰውረዋል ተብለው የተጠረጠሩት ባለሃብት ከ12 ቀናት የፖሊስ ክትትል በኋላ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የፖሊስ ምንጮች ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡ተጠርጣሪው ባለሃብት አቶ ታምራት ሙሉ ባለፈው እሁድ አዲስ አበባ ሜክሲኮ አካባቢ በቁጥጥር ስር መዋላቸው ታውቋል፡፡
በአሁን ሰዓትም ለደህንነታቸው ሲባል ይርጋለም ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው የደቡብ ፖሊስ ማሰልጠኛ ኮሌጅ ታስረው እንደሚገኙ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
 ባለሃብቱ ብሉናይል እና ኢቪኒንግ ስታር የተባሉ ሆቴሎች የነበራቸው ሲሆን፤ ኢቪኒንግ ስታር የተባለውን ሆቴላቸውን ለአንድ ባለሀብት ከሸጡ በኋላ በተፈጠረ አለመግባባት ለፍርድ ቤት ክስ አቅርበው እንደነበርና ሟች አቶ ዳንኤል ውክልና ወስደው ሲከራከሩ እንደነበር ታውቋል
ተጠርጣሪው “ለምን ከጠላቶቼ ጎን ቆምክ” በሚል ምክንያት በጠበቃው ላይ ግድያውን ሳይፈፅሙ እንዳልቀረ የሟች ቤተሰቦች ለአዲስ አድማስ የገለፁ ሲሆን ግለሰቡ ቀደም ሲል በደረቅ ቼክ ማጭበርበር ወንጀል 12 ዓመት ተፈርዶባቸው በፖሊስ ሲፈለጉ እንደነበር ታውቋል፡፡
ተጠርጣሪው መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም በሃዋሳ ከተማ ፒያሳ አካባቢ ዳሽን ባንክ ህንፃ ላይ ወደ ሚገኘው የሟች ቢሮ ከጠዋቱ 2፡30 ላይ በመግባት ሰላምታ የሚያቀርቡ መስለው በታጠቁት ሽጉጥ ግድያውን እንደፈፀሙና የሟችን ረዳት እንዳቆሰሉ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
ሟች አቶ ዳንኤል ዋለልኝ በሃዋሳ ከተማ የታወቁ የህግ ባለሙያ እምደመነሩ የሚገልፁት ቤተሰቦቻቸው፤ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ በህግ መምህርነት ከማገልገላቸውም ባሻገር ላለፉት 3 ዓመታት በጠበቃነትና በህግ አማካሪነት ሲሰሩ እንዲቆዩ ጠቁመዋል፡፡  


Published in ዜና

አዲሱ ፕሬዚዳንት ካቢኔያቸውን አዋቅረዋል

የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ (አንድነት) ፓርቲ ፕሬዚዳንት የነበሩት ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በገዛ ፍቃዳቸው ስልጣን መልቀቃቸው የፓርቲው የዲሞክራሲ ባህል የላቀ ደረጃ ላይ መድረሱን ያመላከተ ነው ያለው ፓርቲው፤ በሂደቱ ላይም የደንብ ጥሰት እንዳልተፈፀመ አስታውቋል፡፡ “አንዳንድ ወገኖች በሽግግሩ የደንብ ጥሰት የተፈጸመ በማስመሰል ጫጫታ ለመፍጠር እየተንቀሳቀሱ ነው” ያለው ፓርቲው፤ የስልጣን ሽግግሩ ደንቡን ተከትሎ ዲሞክራሲያዊ በሆነ ሂደት ያለፈና የፀደቀ ነው ብሏል፡፡ ኢ/ር ግዛቸው በገዛ ፍቃዳቸው ለፓርቲው ቀጣይ ጉዞ ይበጃል በማለት ስልጣን መልቀቃቸው የፓርቲው የዲሞክራሲ ባህል የላቀ ደረጃ ላይ መድረሱ በትክክል የታየበት፣ ፓርቲው በተሻለ ቁመና እንዲጓዝ በር የከፈተ ትልቅ እርምጃ በመሆኑ ሊደነቅ እንደሚገባው ጠቁሞ፤ አንድነት ልዩነቶችን በውይይትና በመረጋጋት መፍታት የሚችል፣ ለሌሎችም አርአያ የሚሆን ልምድ ያለው ፓርቲ እንደሆነ አሳይቷል ብሏል፡፡ አዲሱ ፕሬዚዳንት አቶ በላይ ፍቃዱ፤ ካቢኔያቸውን አቋቁመው ወደ ስራ መግባታቸውን የጠቆመው አንድነት፤ የተሻለ እንቅስቃሴ ለማድረግም ፓርቲውን የማጥራትና የማስተካከል ስራ እየተሰራ እንደሆነ አስታውቋል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ኢ/ር ግዛቸው አንዳንድ የዳያስፖራ ደጋፊዎች ፓርቲውን በገንዘባቸው ለመጠምዘዝ ይፈልጋሉ በማለት ሥልጣን የለቀቁት በተፅዕኖ እንደሆነ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ የፓርቲው ተጠባባቂ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አስራት አብርሃም በበኩላቸው፤ በዚህ አይስማሙም፡፡ “ኢ/ሩ ለብሄራዊ ምክር ቤቱ የገለፁት ከህሊናቸው ጋር ተማክረው ለፓርቲው ቀጣይ ሂደት ይጠቅማል በሚል በገዛ ፍቃዳቸው ስልጠናቸውን መልቀቃቸውን እንጂ በተፅዕኖ ነው የለቀቅሁት አላሉም” ብለዋል፡፡ በግፊትና በተፅዕኖ ነው የለቀቁት የሚለው አያስኬድም ያሉት አቶ አስራት፤ “ኢ/ር ግዛቸው ሌላ ፍላጎት ቢኖራቸው የስልጣን ገደባቸው እስኪጠናቀቅ ፓርቲውን መምራት ይችሉ ነበር፤ ሆኖም ለፓርቲው ይበጃል ያሉትን እርምጃ ወስደዋል” ብለዋል፡፡
ኢ/ር ግዛቸው የፓርቲው ህልውና ተጠብቆ እንዲጓዝ ትልቅ እርምጃ መውሰዳቸውን የጠቀሱት ኃላፊው፤ በገዛ ፍቃዳቸው ከስልጣን ለመልቀቅ በመወሰናቸው ፓርቲው በእጅጉ ያከብራቸዋል፤ በቀጣይም  አመራሩን በምክር ያግዛሉ ብለን እንጠብቃለን ብለዋል - ኢ/ር ግዛቸው የፓርቲው ብሔራዊ ምክር ቤት አባል ሆነው እንደሚቀጥሉ በማመልከት፡፡በፓርቲው ዙሪያ ብዙ አፍራሽ አስተያየቶች እየተሰነዘረ መሆኑን ያመለከቱት አቶ አስራት፤ አሁን ያለው አመራር የፓርቲውን ቀጣይ ህልውና ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ቀጣዩን ምርጫ ታሳቢ ያደረጉ ተግባራት እያከናወነ ነው ብለዋል፡፡ አዲሱ የፓርቲው ፕሬዚዳንት አቶ በላይ ፍቃዱ ባለፈው እሁድ 12 አባላት ያሉት የስራ አስፈጻሚ አባላት መርጠው በም/ቤቱ አፀድቀዋል፡፡ የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዘካሪያስ የማነብርሃን፣ ዋና ፀሐፊ አቶ ስዩም መንገሻ፣ የማህበር ጉዳይ ኃላፊ አቶ አለነ ማህፀነቱ፣ የህግ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ደምሴ መንግስቱ፣ የፖለቲካ ጉዳይ ኃላፊ አቶ ብሩ ብርመጂ፣ የወጣቶች ጉዳይ ኃላፊ አቶ እንግዳ ወልደፃድቅ ሲሆኑ ቀደም ሲል ከኢ/ር ግዛቸው ጋር መስራት አንችልም በማለት ከስራ አስፈፃሚነታቸው ለቀው የነበሩት አቶ ተክሌ በቀለ እና አቶ ዳንኤል ተፈራ በአዲሱ አመራር ውስጥ ተካትተዋል፡፡ የፓርላማ አባሉ አቶ ግርማ ሰይፉም የስራ አስፈፃሚው አባል ሆነዋል፡፡  

Published in ዜና
Page 3 of 15