የዓለም አቀፍ ሆቴሎችን ስም መመንተፍ ጉድ አፈላ!
        የዛሬውን ወጋችንን የምንጀምረው አንድ ሁለት ቀልዶችን ጣል በማድረግ ነው፡፡ የቀልዶቹ ዓላማ እናንተን ፈገግ ማሰኘት ነው፡፡ (ምን በወጣችሁ በመስቀል ሳምንት ደረቅ ወግ!)
የህንዱ የነፃነት ታጋይ የነበሩት ማህትማ ጋንዲ ለጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ወደ እንግሊዝ አገር ይሄዳሉ፡፡ ያኔ ጋንዲ ሸሚዝ የሚባል ነገር መልበስ እርም ብለው ነበር፡፡ እናም በለንደን አውራጎዳና ላይ ከፊል እርቃናቸውን ሆነው ይዘዋወራሉ፡፡ አንድ ትንሽ ልጅ ከእናቱ ጋር ሆኖ ወደ ጋንዲ ቀረብ ይልና፡-
“ሚስተር ጋንዲ፤ ለምን እናቴ ሸሚዝ አትገዛልዎትም?” ሲል ይጠይቃቸዋል
ጋንዲም፤ “በጣም አመሰግንሃለሁ የእኔ ልጅ፤ ግን ወንድሞቼስ?”
ትንሹ ልጅ፤ “እናቴ ለእነሱም ልትገዛላቸው ትችላለች፤ ስንት ናቸው ወንድሞችዎ?”
ጋንዲ፤ “400 ሚሊዮን!” አሉ - ፍርጥም ብለው፡፡ (የያኔውን አጠቃላይ የህንድ የህዝብ ብዛት ነበር የተናገሩት!)
አሁንም ስለጋንዲ ሌላ ቀልድ ወይም ጨዋታ ልድገማችሁ፡፡ እንግዲህ ጋንዲ ፊልም የሚባል ነገር አይተው አያውቁም አሉ፡፡ (ይታገሉ ወይስ ፊልም ይመልከቱ?) አንድ ሰው ቻርሊ ቻፕሊንን ሊያስተዋውቃቸው ይሞክራል፡፡
“ሚ/ር ጋንዲ፤ ይተዋወቁት፤ በዓለም እጅግ ዝነኛው ኮሜዲያን ቻርሊ ቻፕሊን ነው”
ጋንዲም ቶሎ ቀበል አድርገው፤ “አዝናለሁ፤ ጥርሶች ስለሌሉኝ መሳቅ አልችልም”
በዚህ አባባላቸው ቻፕሊን በሳቅ ፈረስ (ያስቃል የተባለው ስቆ ተመለሰ!)
አንድ የመጨረሻ ቀልድ ልንገራችሁና ኮስተር ወዳሉ አገራዊ ጉዳዮች እንገባለን፡፡ (ያው እሱንም ቢሆን በፈገግታ ነው!) አሁንም ከጋንዲ አልወጣንም፡፡ የታላቋ ብሪታንያ ገዢ የነበሩት ንጉስ ጆርጅ በስድስት ባለሟሎቻቸው ከኋላው እንደሙሽራ ቬሎ የተያዘ በጣም ረዥም ካፓ ለብሰዋል፡፡ ጋንዲ ግን እንደተለመደው (በህንድ ባህላዊ ሸርጣቸው) ከፊል እርቃናቸውን ነበር ንጉሱ ፊት የቀረቡት፡፡ ቤተመንግስት ድረስ የወሰዷቸው ባለሟልም ጋንዲን ከንጉሱ ጋር ያስተዋውቋቸዋል (የማን እብድ መጣብኝ ሳይሉ ይቀራሉ!)
ንጉስ ጆርጅ፡- “ሚ/ር ጋንዲ፤ ያለሸሚዝ እኔ ፊት ስትቀርብ ሃፍረት አይሰማህም?”ጋንዲ፡- “ንጉስ ሆይ፤ እርስዎ የለበሱት ለሁለታችንም ይበቃል እኮ!” (ንጉሱ ምነው ምላሴን በቆረጠው ያሉ ይመስለኛል!)አሁን በቀጥታ ወደ ጉዳያችን እንግባ፡፡ ባለፈው ሳምንት አዲስ አድማስ ጋዜጣ በፊት ለፊት ገፁ ላይ ያወጣው ዘገባ፤ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኞች፣ የተማረሩበትን የመልካም አስተዳደር ችግር የሚያጋልጥ ነበር፡፡ (ኢህአዴግ “የሥርዓቱ Top 10 ችግሮች” ብሎ ባወጣው ዝርዝር ውስጥ “የመልካም አስተዳደር ችግር” በቀዳሚነት መስፈሩን ልብ ይሏል!) እናም ጋዜጠኞቹ የመልካም አስተዳደር እጦት አማረረን ማለታቸው ፈፅሞ “surprise” አያደርገንም (ሰርፕራይዙ ችግሩ የለም ቢሉ ነበር!) እኔ የምለው ግን… ኢህአዴግ “ከሰለጠኑት አገራት መኮረጅ ነውር የለውም” እያለ (ያውም ኮማ ሳትቀር!) ስንት ነገሮች ሲኮርጅ… እንዴት መልካም አስተዳደርን ሳይኮርጅ ቀረ? (መልካም አስተዳደር ለኩረጃ አይመች ይሆናላ?) የሆኖ ሆኖ የፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኞች የመልካም አስተዳደር ችግሮች ብለው ከጠቀሷቸው መካከል በሃምሌ ወር የተደረገው የመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪ እስካሁን እኛ ጋ አልደረሰም የሚል ይገኝበታል (“ሃብታም በሰጠ…”ልል አልኩና ተውኩት፡፡) የሚገርማችሁ ግን ዜናው ውጤት ተኮር ነበር፡፡ (ወይስ ገዳም?) ዘገባው በወጣ በ48 ሰዓት ውስጥ በመልካም አስተዳደር እጦት የውሃ ሽታ ሆኖ የቀረባቸው የደሞዝ ጭማሪ ተከፈላቸው የሚል “የምስራች” ሰማን (Better late than never! አለ ፈረንጅ!) ይሄን ስሰማ ወዲያው ወደ አዕምሮዬ የመጣብኝ የፕ/ር በየነ ጴጥሮስ አባባል ነው፡፡ (“በአገሬ ተስፋ አልቆርጥም” ነው ያሉት!!)
በዚህ አጋጣሚ ለጋዜጠኞች እሮሮ ምላሽ በመስጠት መልካም አስተዳደር ለማስፈን ያለውን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር ላሳየው የፕሬስ ድርጅቱ አመራር አክብሮቴን ልገልፅ እወዳለሁ (ራሴን ወክዬ ማለት ነው!!) ግን የጋዜጠኞቹ ትግል ተጀመረ እንጂ ከዳር አልደረሰም፡፡ በጋዜጠኞቹ የተዘረዘሩት ሌሎች የመልካም አስተዳደር ችግሮችም መፍትሄ ማግኘት አለባቸው፤ ያገኛሉም፡፡ (ሃበሻ ተስፋ አይቆርጥም አሉ!!) ይሄ በዚህ እንዳለ ግን ገበናችንን ማነው ለሚዲያ ያወጣው (ያውም ለግል ፕሬስ!) በሚል “አውጫጭኝ” ቢጤ ተጀምሯል የሚባል ወሬ ተናፍሷል፡፡ (ይሄ ከፕሬስ ድርጅት አይጠበቅም!) ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ ህገ-መንግስታዊ መብት መጣስ እኮ ነው! (ይታረማል ብለን እንመን!)
ወደሌላ አጀንዳ እንሻገር፡፡ እኔ የምለው … ባለፈው ሳምንት ከ400 በላይ የሚሆኑ የሆቴል ኩባንያዎች በመዲናችን ጉባኤ ተቀምጠው እንደነበር ሰማችሁ አይደል? ይሄ መቼም ግሩም አጋጣሚ እኮ ነው፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝም በስብሰባው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ዓለም አቀፍ የሆቴል ኩባንያዎች በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች ሆቴሎቻቸውን እንዲከፍቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ጥሪ ማድረጋቸው ሸጋ ነው፡፡ ምናልባት ጠ/ሚኒስትሩ (አስታዋሽ በማጣት ይመስለኛል!) የዘነጉት ነገር አለ ብዬ አስባለሁ፡፡ ምን መሰላችሁ? ለአገር በቀሉና በሆቴል ኢንቨስትመንት ላይ ለተሰማራው ባለሀብትም ጥሪ ማቅረብ ነበረባቸው፡፡ ሆቴል ገንቡ የሚል እኮ አይደለም፡፡ (የአቅማቸውን ያህል ገንብተዋል!) “የዓለም አቀፍ ሆቴሎችን ስምና ዝና፣ ሎጎና ሌሎች ነገሮች ያለፈቃዳቸው ወርሳችሁ አትጠቀሙ” የሚል፡፡ እንዴ… በሰሞኑ ጉባኤ የተሳተፉት እኮ በዓለም የገነነ ስም ያላቸው የሆቴል ባለቤቶችና ኩባንያዎች እኮ ናቸው፡፡ እናም ስማቸውን በሆቴል ህንፃዎች ላይ በአብረቅራቂ መብራት ብልጭ ድርግም ሲል ቢመለከቱት ራሳቸውን ስተው አይወድቁም ትላላችሁ? ራሳቸውን ስተው ባይወድቁ እንኳን በጦቢያ ምድር ኢንቨስት የማድረግ ሃሳባቸውን ሊቀይሩ ይችላሉ (ስማቸውን የተመነተፉ ይኖራሉ!) ለዚህ ነው ጠ/ሚኒስትሩ በነካ እጃቸው ለሆቴል ባለቤቶቹ ምክርም ማሳሰቢያም ቢጤ ማስተላለፍ ነበረባቸው የምለው፡፡ ለነገሩ የእሳቸው ምክርና ማሳሰቢያ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ ጥብቅ ህግ ያስፈልጋል፡፡ ዓለም አቀፍ ስሞችን መመንተፍ የሚከለክል ዓለም አቀፍ ህግ! (የWTO አባል እስክንሆን ምናምን… አይሰራም!)
እኔ የምለው ግን… ካልጠፋ ስም ባህር ማዶ ተሻግሮ የፈረንጅ ስም መመንተፍ በህግ ባያስጠይቅ እንኳ ከሞራል አንፃር ተገቢ ነው እንዴ? እርግጠኛ ነኝ የስም ዝርፊያው የሚመጣው የዓለም አቀፍ ሆቴሎችን መስፈርት ለሟሟላት አቅም ብቻ ሳይሆን ልብም ጭምር ስናጣ ነው፡፡ (ያለዚያ አይታሰብማ!) ግን እንዲህ ዓይነቱ አጋጣሚ (ዓለም አቀፍ የሆቴሎች ጉባኤ) ሲፈጠር ደሞ መደነባበራችንና ግራ መጋባታችን አይቀርም፡፡ (“ምን ያለበት … ዝላይ አይችልም” አሉ!) ወዳጆቼ፤ በሆቴል በሉት በፖለቲካ፣ በግብርና በሉት በኢንዱስትሪ ወይም በሌላ ዘርፍ አየር ባየር አያዋጣም (ለፍቶ መና እኮ ነው!)
ሌላው ሁሌ የሚከነክነኝ ምን መሰላችሁ? እንዴት ይሄ ሁሌ ሆቴል እየተገነባ ባለበት ሰዓት አንጀት የሚያርስና የልብ የሚያደርስ የሆቴልና ቱሪዝም ት/ቤት አልተከፈተም? (ስምና ዝና ያለው ማለቴ ነው!) በዲግሪና ከዚያ በላይ የሚያስተምር! ምናልባትም ከምስራቅ አፍሪካ ቁጥር 1 ለመሆን ራዕይ ያለው (Think Big! ነው ነገሩ!) ጥያቄው ወይም ጥቆማው ለኢንቨስተሮች ነው፡፡ ባይ … ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሰው ሃሳብ፣ የጥበብ ስራ፣ የንግድ ስያሜ… በጠራራ ፀሐይ መመንተፍ እየተለመደ መጥቷል፡፡ ለዚህ አንድ መንስኤ የኩረጃ መበረታታት ሊሆን እንደሚችል ጠረጠርኩ (መጠርጠር መብቴ ነው!) … እናም… ኢህአዴግም ሆነ መንግስት በኩረጃ ላይ ያላቸውን አቋም በግልፅ ሊያሳውቁ ይገባል ባይ ነኝ፡፡ (ኢህአዴግና መንግስት ቢኮራረጁ እኮ ችግር የለውም!) ይኸውላችሁ… አንዳንዴ ባለስልጣኖቻችን ነሸጥ ሲያደርጋቸው በቲቪ መስኮት እየቀረቡ፣ ከሰለጠኑት አገራት መኮረጅ ችግር እንደሌለው ይናገራሉ፡፡ (ይሄ እኮ ነው ነገር ያበላሸው!) በሌላ በኩል የት/ቤት ፈተና ሊቀርብ ሰሞን በኢቴቪ የፀረ - ኩረጃ ማስታወቂያ ይጧጧፋል (የውጭ ፈንድ አለው እንዴ?) አንዴ “ኩረጃ ነውር የለውም”፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ “ኩረጃ አስነዋሪ ተግባር ነው” ይባላል፡፡ (ትውልዱ እንኳን ግራ አጋብተነው እንዲያውም እንዲያ ነው!) በራሱ በኢህአዴግ ቋንቋ ልጠቀምና ሁለቱን እያጣቀሱ መጓዝ መንገድ ነው የሚያስቀረን፡፡ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ (አፈሩ ይቅለላቸውና!) አንዴ ለተቃዋሚዎች የሰጡት ማስጠንቀቂያ ትዝ አለኝ፡- “ህጋዊነትንና ህገወጥነትን እያጣቀሱ መጓዝ አይቻልም!” ነበር ያሉት (ካልተሳሳትኩ!) ዛሬስ? አሁንስ? አንዴ “መኮረህ ነውር የለውም”፤ ሌላ ጊዜ “መኮረጅ አስነዋሪ ተግባር ነው” በሚል እያጣቀሱ መቀጠል አይቻልም (ግራ ተጋብተን ግራ አናጋባ!)አሁንማ ምን እየተባለ መሰላችሁ? “እንኳን ግለሰብ ከግለሰብ፣ አገርም ከአገር ይኮርጃል!” እኔ በበኩሌ ግን፤ ዕውቁ የፍልስፍና ምሁርና ንቁ የፖለቲካ ተሳታፊ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ በቅርቡ ለአዲስ አድማስ በተናገሩት እስማማለሁ (ኢህአዴግም … ተቃዋሚዎችም … ካድሬም … ሲቪልም ቢስማማ ነው የሚሻለው!) አዲሱ ዓመት የጤና፣ የብልፅግናና የሰላም… ምናምን የሚሉ ክሊሼዎችን ያጣጣሉት ምሁሩ፤ የኩረጃ ዘመን እንዲያበቃ ተመኝተዋል፡፡ ወዳጆቼ፤ ኩረጃ እኮ ወንዝ አያሻግርም፡፡ (የጥገኝነት ባህል ነው የሚያዳብረው!) እናም… “ኩረጃ በእኛ ይብቃ” እንበል!! (የተኮረጀውም እኮ ፍሬ አላመጣም!) መልካም ሰንበት!  

የኦባማ ደህንነቶችና የኢትዮጵያ ኤምባሲ ምን አገናኛቸው? በደንብ ይገናኛሉ። የኦባማ ደህንነቶች፣ የሰሞኑ ዋነኛየአለማቀፍ ዜናዎች ርዕስ ሆነው ሰንብተዋል። ከ15 ቀናት በፊት፣ ኦማር ጎንዛሌዝ የተባለ የቀድሞ ወታደር የኋይት ሃውስን አጥር ጥሶ ከገባ በኋላ፤ በየእለቱ አዳዲስ “የቅሌት መረጃዎች” ሲወጡ ሰንብተዋል።የዜናዎቹ ብዛትና ፍጥነት ሲታይ፣ በጥቅሉ “የዜና ማዕበል”ብንላቸው ይሻላል። ማዕበሉ ከጣራ በላይ የመጠቀው ረቡዕ እለት የደህንነቶቹ ዋና ሃላፊ ከስልጣን ሲሰናበቱ ነው። በማግስቱ ከዜና ተርታ ወጣ፤ ፀጥ ረጭ አለ።በሌላ በኩል፣ ከኋይት ሃውስ በ7 ኪሎሜትር ርቀት በኢትዮጵያ ኤምባሲ ሰኞ እለት ገዢውን ፓርቲ ከሚቃወሙ ዳያስፖራዎች ጋር በተከሰተው አምባጓሮ ዙሪያ፣ አለማቀፍ የሚዲያ ተቋማት አልዘገቡትም - ከሮይተርስ ብጣሽ ዜና በስተቀር። በአምባጓሮው ላይ ሽጉጥ የተኮሰ የኤምባሲው ሰራተኛ፣ ያለመከሰስ መብቱን ተጠቅሞ ወደ ኢትዮጵያ እንደተመለሰ የዘገበ አለማቀፍ ሚዲያ የለም። “ነገሬ” አላሉትም።
በዚህ በዚህ፣ ሁለቱም ክስተቶች አንዳችም ዝምድና የላቸውም ማለት ይቻላል። ግን ደግሞ፤ በግድ ልናዛምዳቸው እንችላለን። የፕሬዚዳንት ኦባማን እና የኋይት ሃውስን ደህንነት የመጠበቅ ስልጣን የተሰጠው Secret Service የተሰኘው የፀጥታ ተቋም፤ በአሜሪካ የሚገኙ ኤምባሲዎችን ደህንነት የመጠበቅ ሃላፊነትም አለበት። በኢትዮጵያ ኤምባሲ ዙሪያ የተከሰተውን አምባጓሮ ለማጣራት ወደ ቦታው የመጡትም፣ የዚሁ ተቋም ሰራተኞች ናቸው - የኋይት ሃውስ (የአሜሪካ ቤተመንግስት) ደህንነቶችና የፀጥታ ሰራተኞች።
በእርግጥ፣ በአምባጓሮው ሰበብ በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት የለም። ኢህአዴግን ለመቃወም የመጡት ዳያስፖራዎች ከኤምባሲው ሰራተኞች ጋር ከተፋጠጡ በኋላ ነው፣“ወደ ኤምባሲው እንገባለን፤ አትገቡም” የሚል አምባጓሮ የተፈጠረው። አንድ የኤምባሲው ሰራተኛ ሽጉጥ ወደ ላይ ተኩሷል፤ የተወሰኑ ተቃዋሚዎች ደግሞ ወደ ግቢው ገብተው ባንዴራ አውርደዋል። የአምባጓሮው አጭር ታሪክ ይህን ይመስላል። አምባጓሮውን ለማጣራት የአሜሪካ Secret Service መምጣቱ ሳይዘነጋ ማለት ነው።
በነገራችን ላይ፣ ስያሜው ከሚኒሊክ ዘመን በኋላ በኢትዮጵያ ከነበረው “የሚስጥር ፖሊስ” ከሚለው ስያሜ ጋር ይቀራረባል። ግን ማንነታቸውም ሆነ ስራቸው፣ “ሚስጥር” አይደለም። ቆባቸው ላይ “የሚስጥር ፖሊስ” የሚል ፅሁፍ እየታየ፤ እንዴት “ሚስጥር” ይሆናሉ? የአሜሪካ ፕሬዚዳንትንና ምክትላቸውን ከነቤተሰባቸው፣ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶችንና ቤተሰቦችን፣ እንዲሁም ለጉብኝት የሚመጡ የሌላ አገር መሪዎችንና ኤምባሲዎችን ደህንነት የመጠበቅ ስልጣን የተሰጠው Secret Service የተሰኘው ተቋም፣ ድብቅ ሚስጥር አይደለም።
በኋይት ሃውስ ግቢ ውስጥና በዙሪያው ዩኒፎርም ለብሰው ጥበቃ ሲያካሂዱ እያየን “ሚስጥራዊ” ልንላቸው አንችልም። ሙሉ ሱፍ ከነከረቫቱ ለብሰው፣ ጥቁር መነፅር አጥልቀው፣ ፕሬዚዳንት ኦባማን ከግራና ከቀኝ፣ ከፊትና ከኋላ አጅበው ዙሪያቸውን ሲቃኙ የምናያቸው ረዣዥም ሰዎችም፣ የተቋሙሰራተኞች ናቸው - በአሜሪካ ብቻ ሳይሆን በአለም ወደር የለሽ እንደሆኑ የሚነገርላቸው የፀጥታ ባለሙያዎች።
በ1.5 ቢሊዮን ዶላር አመታዊ በጀት የሚንቀሳቀሰው ኤጀንሲም እንዲሁ፤ በአለም አቻ የለውም የሚባልለት ዝነኛ የፀጥታ ጥበቃ ተቋም ነው - “ሚስጥራዊ” ሳይሆን “ዝነኛ”። ባለፉት ሁለት ሳምንታት ግን፣ የተቋሙ ዝና ተዋርዶ አፈር ለአፈር ሲጎተት ሰንብቷል - “የተቋሙን ጉድ” እየፈለፈሉ የሚያወጡ ጋዜጠኞች በሚዘግቡት እንደ ናዳ ፋታ የማይሰጥ፣ እንደ ማዕበል አገር ምድሩን የሚያዳርስ የዜና ስርጭት።
የናዳው እና የማዕበሉ መነሻ፣ ከሁለት ሳምንት በፊት የ44 አመቱ ጎንዛሌዝ አጥር ጥሶ ወደ ዋይት ሃውስ መግባቱ ነው። ለአስር ቀናት የዘለቀው ማዕበል፣ የኤጀንሲው ዳሬክተር ኋይት ሃውስን ለቅቀው ሲወጡ ተጠናቋል። ለ30 አመታት በተቋሙ ውስጥ የሰሩት ዳሬክተሯ ጁሊያ ፒርሰን፣ የጎንዛሌዝ መዘዝ እዚህ ደረጃ ላይ ይደርሳል ብለው አልጠበቁም ነበር - ስልጣን እስከለቀቁበት ዋዜማ ድረስ። እንዲያውም፣ የጎንዛሌዝ ነገር ተድበስብሶ ይቀራል በሚል ግምት፣ ክስተቱን በዚያው እለት ለፕሬዚዳንቱ ሪፖርት አላደረጉም።ግን ጋዜጦች ጉድ አደረጓቸው። ዳሬክተሯ መረጃዎችን ለመደበቅ ሲሞክሩ፣ ጋዜጠኞች መረጃ እየፈለፈሉ ሲያወጡ ከሰነበቱ በኋላ ነው፤ ነገሩ ግልፅ እየሆነ የመጣው። የአእምሮ ህመምተኛው ጎንዛሌዝ፣ ለካ አጥር ከመዝለልም አልፎ ሕንፃ ውስጥ ገብቷል። ለካ፣ ሕንፃው ውስጥ እንደገባ ወዲያው አልተያዘም። በፕሬዚዳንቱ መኝታ ቤት ስር አልፎ፣ የመሰብሰቢያ አዳራሽና የእንግዳ መቀበያ ክፍሎች ድረስ ዘልቋል... እንዲህ ከእለት እለት መረጃው እየጨመረ ሲመጣ፣ ከዚሁ ጋር አብሮ የቀድሞ “ስህተቶች” እና “ቅሌቶችም” በየእለቱ ሲዘገቡ ሰንብተዋል። ዋና ዋናዎቹን ልጥቀስላችሁ።
በታይላን ከአውሮፕላን የጠፋው የፀጥታ ሰራተኛ
በ2009 ለባራክ ኦባማ የደቡብ ኮሪያ ጉብኝት ዝግጅት እንዲያደርጉ የተመደቡ 70 የተቋሙ የፀጥታ ሰራተኞች፣እግረመንገዳቸውን ወደ ታይላንድ ጎራ ብለው ነበር - ዘና ለማለት። ነገር ግን፣ኦባማ ደቡብ ኮሪያ ከመግባታቸው በፊት የፀጥታ ሰራተኞች ቀድመውመድረስ አለባቸው። ችግሩ፣ አውሮፕላናቸው ጊዜ መብረር አልቻለም። አንድ የፀጥታ ሰራተኛ የት እንደገባ ሳይታወቅ ጠፍቷል። የሰራተኞቹ ተቆጣጣሪ ቢጨንቃቸው፣ ሌሎቹን ሰራተኞች ወደ ደቡብ ኮሪያ ሸኝተው የጠፋውን በግ ፍለጋ የታይላንድ ጎዳናዎችን ለማሰስ ወሰኑ።
ደግነቱ ጊዜ አልፈጀባቸውም፤ የጠፋውን የፀጥታ ሰራተኛ ወዲያውኑ አግኝተውታል። የት? የሴተኛ አዳሪዎች መንደር ውስጥ።በዚያ ላይ፣ ሲጠጣ አምሽቶ ገና ስካር አልለቀቀውም። በመንገደኞች አውሮፕላን ወደ አሜሪካ እንዲመለስ ተደረገ። ምናልባት፣የአንድ ሰራተኛ ጥፋት እንደትልቅ ቅሌት ተጋንኖ መታየት የለበትም ሊባል ይችላል። ነገር ግን፣ ጥፋት የፈፀመው ሰራተኛ አለመቀጣቱ አስገራሚ ነው ብሏል ኤምኤስኤንቢሲ።
ኋይት ሃውስ ላይ የክላሽ እሩምታ
ከሁሉም የከፋ ቅሌት የተከሰተው፤ የዛሬ ሶስት አመት ገደማ ነው። ከኋይት ሐውስ በግማሽ ኪሎሜትር ርቀት የቆመ መኪና ውስጥ የነበረ ሰው፣ የፕሬዚዳንቱ ቤተሰብ መኖሪያ በሆነው የሕንፃው አንደኛ ፎቅ ላይ ሰባት ጥይቶችን አርከፍክፏል።የተኩስ ድምፅ ተሰምቷል፤ የመስተዋት መሰበርና መሰንጠቅ ድምፆችም እንዲሁ። ነገር ግን፣ ኋይት ሐውስ ሰባት ጥይቶች እንደዘነቡበት የታወቀው ከአራት ቀን በኋላ ነው።
ለወትሮው ተኳሹ የነበረበት ቦታ፣ በቤተመንግስት የፀጥታ ሰራተኞች ጥበቃ የሚደረግለት ቦታ ነው። በተለይ ፕሬዚዳንቱ በሄሊኮፕተር ከኋይትሃውስ ሲነሱ ወይም ሲመለሱ፣ በዙሪያው የፀጥታ ሰራተኞቹ ይመደባሉ። ግን ሁልጊዜ አይደለም። አንዳንዴ የፀጥታ ሰራተኞቹ አላግባብ ወደ ሌላ ቦታ እንዲሄዱ ይታዘዛሉ በማለት ዋሺንግተን ፖስት ዘግቧል -የዛሬ ሶስት አመት የተከሰተውን አጋጣሚ በምሳሌነት በመጥቀስ።
የጎረቤት ሽምግልና - የትርፍ ሰዓት ስራ
በቦታው ተመድበው የነበሩ ሁለት የፀጥታ ሰራተኞች፣ ትዕዛዝ የደረሳቸው ከዋና አለቃቸው ነው - የፀጥታ ተቋሙ ዋና ዳሬክተር ከነበሩት ማርክ ሱሊቫን።ለዚያውም ፕሬዚዳንቱ በሄሊኮፕተር ለመነሳት በተቃረቡበት ሰዓት ላይ ነው፤ ሁለቱ የፀጥታ ሰራተኞች የተመደቡበትን የጥበቃ ቦታ ትተው ወደ ሜሪላንድ እንዲሄዱ የታዘዙት። ለምን? የዳሬክተር ሱሊቫን አንዲት ረዳት በሜሪላንድ መኖሪያ ቤቷ ከጎረቤት ጋር ጭቅጭቅ ስለተፈጠረባት።
መደበኛ የፕሬዚዳንት ጥበቃቸውን ትተው፣ የጎረቤት ጭቅጭቅ እንዲሸመግሉ በመመደባቸው የተናደዱትየፀጥታ ሰራተኞች፣ሜሪላንድ ለመድረስ አንድ ሰዓት ፈጅቶባቸዋል። የሽምግልና ስራውንም፤ “ሙንላይት ኦፕሬሽን” ሲሉ በራሳቸው ላይ ቀልደዋል - የትርፍ ሰዓት ተልእኮ እንደማለት ነው።
ከሆቴል አስተናጋጆች ጋር ፍጥጫ
ግንቦት 2013 ሌላየ“ቅሌት” አጋጣሚ የተፈጠረው፤ ከዋሺንግተን ስመጥር ሆቴሎች አንዱ በሆነው ሄይ-አዳምስ ሆቴል። የአንዲት ሴት ክፍል ውስጥ ለመግባት የፈለገ አንድ የፀጥታ ተቋሙ ሰራተኛ፤ “አትገባም” ተብሎ ስለተከለከለ ከሆቴሉ አስተናጋጆች ጋር ውዝግብ ጀምሯል።ኢኚያኮ ዛሞራ ይባላል። በስልጣን አስፈራርቶ ወይም ጉልበት ተጠቅሞ መግባት አይችልም። እንደማያዋጣው ያውቃል። የሆቴሉ አስተናጋጆችና ሃላፊዎች ደግሞ ሊያስገቡት ፈቃደኛ አልሆኑም። ምክንያቱም፣ ሆቴሉ ውስጥ ያረፈችው ሴት፣ ፈቃደኛ እንዳልሆነች ነግራቸዋለች።
ከፀጥታ ተቋሙ ዋና ዋና ሃላፊዎች መካከል አንዱ እንደሆነ ቢያውቁ እንኳ እሺ አይሉትም። የትኛውም ስልጣን ቢኖረው፣ ህግ እየጣሰ በሰዎች ንብረት ላይ እንዳሻው መሆን አይችልም። የሆቴሉ ሃላፊዎች ቢቸግራቸው፣ ወደ ኋይትሃውስ ስልክ ደውለው ችግራቸውን ገለፁ። እንዲያም ሆኖ፣ ዛሞራ መናገሩን አላቋረጠም - “ልግባ አላልኩም፤ ተመልሼ ልግባ ነው ያልኩት። አሁን ነው የወጣሁት። ለአፍታ ተመልሼ ልግባና እወጣለሁ” ይላል እየደጋገመ።
በእርግጥም፣ ዛሞራበሆቴሉ ካረፈችው ሴት ጋር ክፍሏ ውስጥ ቆይቶ ነው የወጣው። ግን ተመልሶ መግባት አለበት። ለምን? ክፍሏ ውስጥ አንድ ጥይት ረስቷል። በመንግስት ተመዝግቦ የተሰጠውን ጥይት ትቶ መሄድ አይችልም። በዚያ ጥይት አንዳች ወንጀል ቢፈፀም፣ በዘመኑ የምርመራ ቴክኖሎጂ የጥይቱ ምንጭ ተጣርቶ መዘዙ ዞሮ ይመጣበታል። በዚያ ላይ፣ ዛሞራ ተራ የፀጥታ ሠራተኛ አይደለም። የፕሬዚዳንቱ ደህንነት ለመጠበቅ በቋሚነት ከተመደቡ ልዩ የፀጥታ ተቋሙ ሰራተኞች አንዱ ነው - ዛሞራ። ይህም ብቻ አይደለም። 24 የፕሬዚዳንት የግል ጠባቂዎችን የሚመራ ተቆጣጣሪ ነው። የኋላ ኋላ፣ ሆቴል ውስጥ የረሳውን ጥይት መልሶ ማግኘቱ አልቀረም። ነገር ግን፣ ከችግር አላመለጠም። ምርመራ ተካሂዶበት፣ ከሃላፊነቱ ተነስቷል፤ ከፕሬዚዳንቱ የግል ጥበቃ ቡድንም እንዲወጣ ተደርጓል።
ታላቁ የኮሎምቢያ ቅሌት - ከሴተኛ አዳሪዎች ጋር ውዝግብ
በፀጥታ ሰራተኞች ላይ ምርመራ መካሄዱ አዲስ ነገር አይደለም። የዛሬን አያድርገውና የዛሬ ሁለት አመት፣ ኢኚያኮ ዛሞራ በመርማሪነት ተመድቦ ነበር - ለዚያውም በታላቁ የኮሎምቢያ ቅሌት ላይ -በርካታ የፀጥታ ተቋሙ ሰራተኞችንና የኮሎምቢያ ሴተኛአዳሪዎችንያዳረሰ ታላቅ ቅሌት። ነገሩ እንዲህ ነው። ፕሬዚዳንት ኦባማ ለጉብኝት ኮሎምቢያ ከመድረሳቸው በፊት ቀድመው የገቡ በርካታ የፀጥታ (ሰክሬት ሰርቪስ) ሰራተኞች፣ ከስንት ጊዜ አንዴ በሚያገኟት ትንሽ ትርፍ ጊዜ መዝናናት ቢያምራቸው አይገርምም። በፀጥታና በምርመራ ሙያ አንቱ የተባሉ ሰዎች፣ አሰልቺ ሥራ ላይ አመታትን ሲያስቆጥሩ አስቡት። አንዳንዶቹኮ ከሲአይኤ እና ከኤፍቢአይ ውስጥ በላቀ ችሎታ ነው ወደ ሰክሬት ሰርቪስ የሚገቡት። አብዛኛውን ጊዜ የሚያሳልፉት ግን፣ የቤተመንግስትን ግቢ ወይም የስብሰባ አዳራሾችን ለመጠበቅ ቆመው በመዋል ነው።
እንዲህ በአሰልቺው ስራ የተንገፈገፉ 12 ያህል የፀጥታሰራተኞች ናቸው፣ኮሎምቢያ ውስጥየእርቃን ዳንስ ወደሚታይበት ሰፈር ወርደው ሲጨፍሩና ሲጠጡ ያመሹት። በመጨረሻም ወደ ሆቴላቸው ባዶ እጃቸውን አልተመለሱም። ሴተኛ አዳሪዎችን ይዘዋል። ነገሩ በዚህ ቢደመደም ኖሮ፣ አገር ምድሩን ያዳረሰ ቅሌት ለመሆን ባልበቃ ነበር። በእርግጥ ለፕሬዚዳንት ጥበቃ የተመደቡ የፀጥታ ሰራተኞችና ረዳቶች፣ በስራ ዋዜማ አለቅጥ መጠጣትም ሆነ የውጭ ዜጎችን ወደ ሆቴላቸው ይዘው መምጣት አይፈለቀድላቸውም። እናም፤ ከምርመራና ከዲሲፕሊን ቅጣት አይድኑም ነበር። ትልቅ ችግር የተፈጠረው፣ በዚያ “እብደት” ማግስት ነው። ከሴተኛ አዳሪዎች ጋር የክፍያ ጭቅጭቅ ተፈጠረ። ያው፤ አንዳንድ ሴተኛ አዳሪዎች በአተካራ የሚችላቸው የለም። ሆቴሉን በጭቅጭቅና በስድብ ቀውጢ አደረጉት። ብዙም አልቆየም፤ አለምን የሚያነጋግር ትልቅ ቅሌት ሆኖ አረፈው።ሬቸል ማደው እንደምትለው ግን ይሄ ሁሉ የአጋጣሚ ጉዳይ አይደለም። የቤተመንግስትን ፀጥታና የፕሬዚዳንቱን ደህንነትየመጠበቅ ሃላፊነት የተሰጠው ተቋም፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ ስህተትና ቅሌት እየተደራረበበት መጥቷል።ባለፉት አስራ ሁለት ወራት ደግሞ ብሶበታል ትላለች ሬቸል ማደው - የፕሬዚዳንት ኦባማ የደቡብ አፍሪካ ጉብኝትን በመጥቀስ።
ከኦባማ አጠገብ፤ ኮሜዲያን ወይም ወንጀለኛ?
ለኔልሰን ማንዴላ ስርዓተ ቀብር ወደ ደቡብ አፍሪካ የተጓዙት ፕሬዚዳንት ኦባማ፣ በህዝብ የተሞላ ስታዲዬም ውስጥ፣ ከበርካታ አገራት መሪዎች መካከል ጎልተው፣ መላው አለም በሚከታተለው ቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት፣ ሃዘናቸውን ለመግለፅ መድረክ ላይ ወጥተዋል። መድረኩ ጥይት በማይበሳው መስተዋት የተከለለ ነው። ከፕሬዚዳንቱ አጠገብ፣ ንግግራቸውን በምልክት ቋንቋ ለመተርጎም የተመደበ ግዙፍ ሰው እጆቹን ግራና ቀኝ፣ ላይና ታች ሲያንቀሳቅስ ይታያል። አስገራሚው ነገር፣ ሰውዬው የፕሬዚዳንቱን ንግግር በምልክት ቋንቋ እየተረጎመ አልነበረም። የእጆቹ እንቅስቃሴ እስከነአካቴው ትርጉም አልነበራቸውም።
ማንዴላን በመሰለ ታላቅ ሰው ቀብር ላይ፣ አሜሪካን ከመሰለ ታላቅ አገር የመጣ ፕሬዚዳንት በሚናገርበት መድረክ፣ እንዲህ አይነት “አስቂኝ” ነገር መፈጠሩ ብዙዎችን ማስቆጣቱና ማሳዘኑ አያጠራጥርም። ምን ይሄ ብቻ! የኋላ ኋላ ሲጣራ፣ ለካ ሰውዬው የአእምሮ ህመምተኛ ነው። በዚያ ላይ፣ ከሶስት ቀን በኋላ ኤንፒአር እንደዘገበው፣ ሰውዬው በግድያ ወንጀል የተጠረጠረ ተከሳሽ ነው። እናም፤ ጥይት በማይበሳው መስተዋት ውስጥ ከፕሬዚዳንቱ አጠገብ ቆሟል። የፕሬዚዳንቱን ደህንነት የሚጠብቁ የፀጥታ ሰራተኞች እያንዳንዷን ነገር ማጣራት ሲኖርባቸው፤ ይህንን እንዴት አለፉት? ለማጣራትና እርምጃ ለመውሰድ ቢሞክሩ፤ “አሜሪካዊያን ወደ አፍሪካ መጥተው አዛዥ ናዛዥ መሆን ያምራቸዋል” የሚል የትችት ውርጅብኝ እንዳይደርስባቸው ሰግተው ይሆን?
ለማንኛውም፤ ከጥቂት ወራት በኋላ መጋቢት ላይ፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ ኔዘርላንድን ሲጎበኙ፤ እንደገና የፀጥታ ሰራተኞች የዜና ርዕስ ሆነዋል - ሶስት የፀጥታ ሰራተኞች እስከ ጥግ ሰክረው ስለተገኙ፣ ከስራ መታገዳቸውን ዋሺንግተን ፖስት ተዘግቧል።እንደ ዋሺንግተን ፖስት የመሳሰሉ የአሜሪካ ጋዜጦች፣ አንድ ሁለቴ የሆነ ስህተትና እንከን ካዩ፣ መች ይለቃሉ? የፀጥታ ጥበቃ ኤጀንሲው ላይ ቅሌት እየተደራረበ የመጣበት አንዱ ምክንያትም፤ የጋዜጠኞች ክትትል ስለተበራከተ ሊሆን ይችላል።እውነትም፣ የግንቦት ወር ሌላ ቅሌት ይዞ መጣ።
ሰተት ብሎ ወደ ኋይት ሃውስ
የፕሬዚዳንት ኦባማ ልጅ በመኪና ከፀጥታ ሰራተኞች ጋር በመኪና ወደ ኋይትሃውስ ስትጓዝ፣ ከበስተኋላ ሌላ መኪና እየተከተላቸው ነበር። የፀጥታ ሰራተኞች ይህንን “የአደጋ ምልክት” ሳያስተውሉ ነው፤ የኋይትሃውስ በር ላይ የደረሱት። በር ተከፍቶላቸው ገቡ፤ ከኋላ ሲከተላቸው የነበረው መኪናም አብሯቸው ገባ። በእርግጥ ምንም አደጋ አልደረሰም። ሰውዬው፣ መንገድ ጠፍቶበት ነው፣ “በደመነፍስ” ከፊት ለፊቱ የነበሩ መኪኖችን ተከትሎ እየነዳ የመጣው። ነገር ግን፤ የፀጥታ ሰራተኞች እንዴት አላስቆሙትም? የፀጥታ ጥበቃ ላይ አንዳች ችግር አለ ማለት ነው። ችግር በመኖሩም ነው፤ የዛሬ ሁለት ሳምንት፣ ኦማር ጎንዛሌዝ የኋይትሃውስ አጥር በመዝለል ሰፊውን መስክ በማቋረጥ ወደ ህንፃው ለመሮጥ የቻለው።
በእርግጥ ማንም ቢሆን፣ በአጥር ዘልሎ ሲገባ፣ የቤተመንግስት ፀጥታ ሰራተኞች ተኩሰው ሊገድሉት አይችሉም። አይፈቀድም። የቀድሞ ሃላፊዎች እንደተናገሩት፣ የቤተመንግስት ፀጥታ ሰራተኞች ከፖሊስ የተለየ የሃይል አጠቃቀም መመሪያ የላቸውም። በአጥር የዘለለ ሰው፣ የጦር መሳሪያ ካልያዘና በሰው ህይወት ላይ አጣዳፊ አደጋ ካልደቀነ በቀር፣ የፀጥታ ሰራተኞች የጦር መሳሪያ እንዲጠቀሙ አይፈቀድላቸውም።የተቋሙ ሃላፊዎች በሰጡት የመጀመሪያ መግለጫም፤ “አጥር ጥሶ የገባውጎንዛሌዝ፣ የጦር መሳሪያ አልያዘም”ብለውነበር።የኤጀንሲው ሃላፊዎች ጉዳዩ በዚሁ እንደሚቋጭ ሳይገምቱ አልቀረም። ለነገሩማ፣ ከመነሻው በሚዲያ ተቋማት እስከነጭራሹ ጉዳዩን ላያውቁትና ላይዘግቡት ይችላሉ የሚል እምነት ነበራቸው። ለዚህም ነው የኤጀንሲው ሃላፊ ጁሊያ ፒርሰን፣ በአጥር ዘሎ የገባ ሰው፣ እስከ ህንፃው በር ድረስ መቻሉን፣ ለፕሬዚዳንቱ ሪፖርት ሳያቀርቡ ለመደበቅ የሞከሩት።
ግን ጉዳዩ በአጭሩ አልተቋጨም። የአሜሪካ ጋዜጦች ተጨማሪ መረጃዎችን ፈልፍለው ማውጣት ጀመሩ። “ሰውዬው ጩቤ ይዞ ነበር” የሚል መረጃ የመጣው በማግስቱ ነው። በሁለተኛው ቀን ደግሞ ሌላ መረጃ - የሰውዬው መኪና ውስጥ፣ 800 ጥይቶች ተገኝተዋል የሚል መረጃ። የተቋሙ ሃላፊዎች፣ መረጃ ለመደበቅ መሞከራቸው አልጠቀማቸውም።የጋዜጠኞች ዘገባ እንደ አሸን እየፈላ፣ የተቋሙ ሃላፊዎችበፍጥነት እንደሚወርድናዳ ቅሌት እየተደራረበባቸው ሲመጣ ማየት፣ ልብ አንጠልጣይ ድራማ ከማየት አይለይም።ጎንዛሌዝአጥር ከመጣስ አልፎ፣ ወደ ህንፃው ገብቶ እንደነበር ጋዜጠኞች መረጃ ያገኙትና የዘገቡት፣ ከሶስት ቀን በኋላ ነው። የተቋሙ ሃላፊዎች ይህንን መካል አልቻሉም። ግን ተጨማሪ መረጃ ለመስጠት አልፈቀዱም።
ሳምንት አልቆየም፤ ጋዜጠኞች ሌላ መረጃ ፈልፍለው አገኙ። ጎንዛሌዝ፣ ያልተቆለፈውን በር ከፍቶ ወደ ህንፃው ከገባ በኋላ አንዲት የፀጥታ ሰራተኛ ልታስቆመው ስትሞክር መትቶ ጥሏታል። ኮሪደር አቋርጦ፣ ወደ ምስራቅ አቅጣጫ ታጥፎ ዋና የመሰብሰቢያ አዳራሽ በር ላይ ሲደርስ ነው የፀጥታ ሰራተኛ በቁጥጥር ስር ያዋለው...በጋዜጠኞች የሚዘገበው አዲስ መረጃ ፋታ የሚሰጥ አልነበረም። ናዳውን መቋቋም ያቃታቸው የኤጀንሲው ሃላፊዎች፣ ከሌላ አቅጣጫም ተጨማሪ ናዳ ሲወርድባቸው ሰንብቷል - በአገሪቱ ኮንግረስ (ፓርላማ)።
በጉዳዩ ላይ ምርመራ የጀመረው የኮንግረስ ኮሚቴ፣ ማክሰኞ እለት የኤጀንሲውን ሃላፊዎች ጠርቶ ቃላቸውን ሲቀበልና በጥያቄ ሲያፋጥጥ ውሏል። የኤጀንሲው ሃላፊዎች ለኮንግረስ ቃል በሚሰጡበት እለት ነው፣ ዋሺንግተን ፖስት አዲስ ዘገባ ይዞ የወጣው። ሕንፃው ውስጥ ጎንዛሌዝ በቁጥጥር ስር የዋለው፣ ለጥበቃ በተመደበ የፀጥታ ሰራተኛ አይደለም። እረፍት የወጣና እንደአጋጣሚ ለሌላ ጉዳይ እዚያ አካባቢ የነበረ የፀጥታ ሰራተኛ ነው ጎንዛሌዝን የያዘው። ይህም ብቻ አይደለም።ከጎንዛሌዝ የአጥር ዝላይ በፊት ሶስት ቀን ቀደም ብሎ፣ ባራክ ኦባማ የኤሜሪካ የበሽታ ቁጥጥር መስሪያ ቤትን ሲጎበኙ የፀጥታ ሰራተኞች ሌላ ስህተት ፈፅመዋል - አንድ የመስሪያ ቤቱ የኮንትራት ሰራተኛ ከፕሬዚዳንቱ ጋር ሊፍት ውስጥ እንዲገባ በመፍቀድ። በጣም አስገራሚው ነገር፣ ሰውዬው ሽጉጥ ታጥቆ ነበር። እነዚህ መረጃዎች ማክሰኞ እለት በዋሺንግተን ፖስት ሲዘገቡ ነው፤ ማዕበሉ ከጣራ በላይ የወጣው። ዳሬክተሯ ስልጣናቸውን ለቀቁ። በአንድ ቀን በኋላ ደግሞ፤ የዜና ማዕበሉ ሙሉ ለሙሉ ጠፋ።

  • በዋሺንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መሳሪያ የተኮሰው

 የፀጥታ ሰራተኛ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰ

በሳምንቱ መጀመሪያ ዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተደረገውን ጥሰት ተከትሎ፣ ባለፈው ረቡዕም በስዊድን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ሙከራ መደረጉን ምንጮቻችን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በስዊድን ስቶክሆልም በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ ባለፈው ረቡዕ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ተመሳሳይ የጥሰት ድርጊት ለመፈፀምና በስዊድን የኢትዮጵያ አምባሳደር ወይንሸት አሰፋ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ጥቃት ለማድረስ እንደሞከሩ የጠቆሙ ምንጮች፤ የፀጥታ ሃይሎች ደርሰው ሙከራውን እንዳከሸፉት ገልፀዋል፡፡
በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲን ቅጥር ግቢ  ጥሰው ከገቡ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች ጋር በተፈጠረ አተካሮ መሳሪያ ወደ ላይ የተኮሰው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ ያለመከሰስ መብቱን ተጠቅሞ ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሬስ ኃላፊ ጄን ሳኪ አስታወቁ፡፡
ባለፈው ሰኞ  የተወሰኑ ያለ የዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የኢትዮጵያ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ጥሰው መግባታቸውን ተከትሎ በተፈጠረ አምባጓሮ ሰለሞን ገብረስላሴ (በቅፅል ስሙ ወዲ ወይን) የተባለው የኤምባሲው የፀጥታ ሰራተኛ መሳሪያ በመተኮሱ፣ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የግለሰቡ ያለመከሰስ መብት ተነስቶ ጉዳዩ በአሜሪካ ፍርድ ቤት እንዲታይ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን ጥያቄው በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ አገሩ እንዲመለስ ተደርጓል ተብሏል፡፡ በተመሳሳይ ምክንያት ከአሜሪካ የወጣ ማንኛውም ዲፕሎማት ወደ አሜሪካ መመለስ የሚችለው ክሱ በፍርድ ቤት እንዲታይ ብቻ ነው፡፡
በዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በዳያስፖራ ተቃዋሚዎች የተፈጸመውን ጥሰት እንዲሁም የኤምባሲውን ደህንነት ጉዳይ በተመለከተ በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ላቀረብነው ጥያቄ፣ የኤምባሲው የኢንፎርሜሽንና ፕሬስ ኃላፊ ካትሪን ዲዮፕ በሰጡት ምላሽ፤ “በኢትዮጵያ ኤምባሲ ላይ በግለሰቦች በተፈፀመው ድርጊት በጣም አዝነናል፤ ነገር ግን ጉዳዩ በምርመራ ላይ በመሆኑ አስተየያየት መስጠት አንችልም፣ በዋሽንግተን ዲሲና በሌሎች ግዛቶች ለሚገኙ ኤምባሲዎች ደህንነት አሜሪካ ትኩረት እንደምትሰጥ እናረጋግጣለን” ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በአዲስ አበባ ለሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ የሚያደርገውን ጥበቃ በእጅጉ እንደሚያደንቁም ኃላፊዋ ተናግረዋል፡፡
ከትናንት በስቲያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በፅህፈት ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መጣስንና መሳሪያ ስለተኮሰው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ባልደረባ ተጠይቀው፣ “በአሁኑ ወቅት ጉዳዩን አስመልክቶ ሙሉ ስዕል የለኝም” በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን ሌሎች የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሃላፊዎችን ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡  በሰሞነኛ አበይት ጉዳዮች ላይ ትንታኔ የሚሰጠው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ድረ ገፅም ማተሚያ ቤት እስከገባንበት ሰዓት ድረስ በጉዳዩ ላይ ያለው ነገር የለም፡፡

Published in ዜና

ማክሰኞ የቅጣት ውሳኔ ይሰጣል
         ሃሰተኛ ወሬዎችን አሳትሞ በማሰራጨት፣ ህዝብን ለአመፅ በማነሳሳት ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል ለመናድ ሲንቀሳቀሱ ነበር በሚል ክስ የቀረበባቸው “ሎሚ”፣ “አዲስ ጉዳይ” እና “ፋክት” መፅሄቶች አሳታሚዎች እና ሥራ አስኪያጆች ጥፋተኛ ናቸው ተባሉ፡፡ ጉዳዩን ሲመለከት የቆየው  የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 16ኛ ወንጀል ችሎት፣ ባለፈው ረቡዕ በሰጠው ብይን፣ የ“አዲስ ጉዳይ” መፅሄት አሳታሚ ሮዝ የህትመት ስራዎች ኃ/የተ የግል ማህበር እና ሥራ አስኪያጅ አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬ፣ የ“ሎሚ” መፅሄት አሳታሚ ዳዴሞስ የህትመትና የፕሬስ ሥራዎችና ሰራተኛና ሥራ አስኪያጁ አቶ ግዛው ታዬ እንዲሁም የ “ፋክት” መፅሄት አሳታሚ ዮፋ ኢንተርቴይመንትና የፕሬስ ስራዎች እና ስራ አስኪያጇ ፋጡማ ኑርዬ በአቃቤ ህግ በቀረበባቸው ክሶች ጥፋተኞች ናቸው ብሏል፡፡ ቀደም ሲል ሁሉም ተከሳሾች በጋዜጣ በተደረገላቸው ጥሪ መሰረት ባለመቅረባቸው በሌሉበት ጉዳያቸው እንዲታይ ብይን የተሰጠ ሲሆን አቃቢ ህግም ኦርጂናል መፅሄቶችን በማስረጃነት እንዲያቀርብ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር፡፡
 በዚህም መሰረት ረቡዕ እለት ፍ/ቤቱ የአቃቢ ህግን ማስረጃዎች መርምሮ በሁሉም ተከሳሾች ላይ የጥፋተኝነት ብይን ከሰጠ በኋላ የቅጣት ውሳኔ ለማስተላለፍ ለፊታችን ማክሰኞ መስከረም 27 ቀጥሯል፡፡ መፅሄቶቹ በተለያዩ ጊዜያት ለህትመት ያበቋቸውን ፅሁፎች በማስረጃነት በመጥቀስ መንግስት በአሳታሚዎቹና ሥራ አስኪያጆቹ ላይ ክስ መመስረቱን በሚዲያ ያስታወቀው በነሐሴ ወር 2006 ዓ.ም እንደነበር ይታወሳል፡፡
በሌላ በኩል በፌደራል የመጀመሪ ደረጃ ፍ/ቤት አራዳ ምድብ ችሎት እየታ የሚገነው የጃኖ መፅሔት እና አፍቶ ታይምስ ጋዜጣ አሳታሚዎች እና ስራ አስኪያጆች ክስ እንዴት ይቀጥል የሚለው ላይ ፍ/ቤቱ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 3 ቀን 2007 ኣ.ም ቀተሮ ሰጠ ሲሆን በእንቁ መፅሄት አሳታሚና ስራ አስኪያጅ ጉዳይ ደግሞ የመፅሄቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር እና ህግ ጠበቃው ድርጅቱን ወክለው መከራከር ይችላሉ አይችሉም በሚለው ጉዳይ ላይ ብይን ለመስጠት ጥቅምት 19 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ተይዟል፡፡  

Published in ዜና

                   በቦሌ አየር ማረፊያ በሰዓት ለ1ሺ ሰዎች የኢቦላ ቫይረስ ምርመራ ማድረግ የሚያስችል መሳሪያ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በስራ ላይ ማዋሉን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የገለፀ ሲሆን ከምዕራብ አፍሪካ የሚመጡ ሰዎች በያረፉበት ሆቴል ለ21 ቀናት ክትትል ይደረግላቸዋል ተብሏል፡፡በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የኢቦላ መከላከል ኮሚቴ ትናንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ቫይረሱ በአለማቀፍ ተጓዦች አማካኝነት ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገባ በ8 የድንበር ኬላዎች ላይ የሚደረግ ምርመራን ጨምሮ እንግዶች በስፋት ያርፉባቸዋል ከተባሉ 130 ሆቴሎች ጋር በመተባበር በየጊዜው ምርመራ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡
 በቦሌ አየር ማረፊያ ለእንግዶች የሚደረገውን የኢቦላ ቫይረስ ምርመራ የተቀላጠፈ ለማድረግም በሰዓት ለ1ሺህ ሰዎች የኢቦላ ቫይረስ ምርመራ ለማድረግ የሚያስችል ዘመናዊ መሳሪያ ተገዝቶ ሰሞኑን አገልግሎት እንደጀመረ ታውቋል፡፡
የኢቦላ ምልክት የታየባቸውን ሰዎች ለማከም ታስቦ በተዘጋጀው የኮተቤ አዲሱ ሆስፒታል እስከዛሬ ህክምና የተደረገለት ተጠርጣሪ አለመኖሩንም ኮሚቴው አስታውቋል፡፡
በሌላ በኩል በምዕራብ አፍሪካ የኢቦላ ቫይረስ ስርጭት በከፍተኛ መጠን እየጨመረ መሆኑን የጠቆመው የአሜሪካ የበሽታ ቁጥጥር ማዕከል (CDC)፤ የዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ድጋፍ ካልታከለበት እስከ መጪው ጥር ወር ድረስ በቫይረሱ የሚያዘው ሰው ብዛት 1.4ሚ ሊደርስ እንደሚችል አስታውቋል፡
ከአንድ ወር በፊት ከላይቤሪያ ወደ አሜሪካ ዳላስ የገባ የ45 ዓመት ላይቤሪያዊ፣ ሰሞኑን በኢቦላ ቫይረስ መያዙ የተረጋገጠ ሲሆን ጉዳዩ በአሜሪካ ስጋት ፈጥሯል፡፡ ከግለሰቡ ጋር ንክኪ የነበራቸው 4 ሰዎችም ለብቻቸው ተገልለው ክትትል እየተደረገላቸው እንደሆነ ተዘግቧል፡፡
 ቶማስ ኤሪክ ዱንካን የተባለው ይሄው ላይቤሪያዊ፤ ከወር በፊት በላይቤርያ በቫይረሱ ለተያዘች ነፍሰጡር የትራንስፖርት አገልግሎት ሲሰጥ በኢቦላ ሳይያዝ እንዳልቀረ ኒውዮርክ ታይምስ ግለሰቡን ጠቅሶ የዘገበ ሲሆን ነፍሰጡሯ ከጥቂት ቀናት በኋላ ህይወቷ እንዳለፈ ታውቋል፡፡
 ግለሰቡ የበሽታው ምልክት እስኪታይበት ድረስ 5 ህፃናትን ጨምሮ ከ18 ሰዎች ጋር የቅርብ ንክኪ እንደነበረው የዘገበው ኒውዮርክ ታይምስ፤ ልጆቹ ከትምህርት ቤት ቀርተው ምልክቱ እስኪታይባቸው ድረስ ለብቻቸው ተገልለው ክትትል እየተደረገባቸው እንደሆነ ጠቁሟል፡፡
በቫይረሱ የተያዘው ላይቤሪያዊ በአሁኑ ሰዓት በዳላስ ፕሮኪባይቴሪያን ሆስፒታል የህክምና ክትትል እየተደረገለት እንደሆነ ታውቋል፡፡
ዘ ሰን ትናንት እንደዘገበው፣ በዳላስ የኢቦላ ቫይረስ ከተገኘበት ግለሰብ ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ንክኪ የነበራቸውን ሌሎች ሰዎች የመፈለግ ስራው ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡
በላይቤሪያ የሚገኘው የኤንቢሲ ቴሌቪዥን ጣቢያ አሜሪካዊ የካሜራ ባለሙያም፣ በኢቦላ መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ ግለሰቡ ለህክምና ወደ አሜሪካ ሊወሰድ እንደሆነና ሌሎች የስራ ባልደረቦቹም በአፋጣኝ ወደ አሜሪካ ሄደው ለ21 ቀናት ያህል በጥብቅ የህክምና ማዕከል እንደሚቆዩ ገልጿል፡፡ የካሜራ ባለሙያውን ጨምሮ በቫይረሱ የተያዙ አሜሪካውያን ቁጥር አምስት እንደደረሰ ዘ ሰን ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ከኢቦላ ጋር በተያያዘ ከዳላሱ ከንቲባ ማይክ ሮውሊንግስ ጋር ሰሞኑን ውይይት ያደረጉ ሲሆን፣ ቫይረሱ ወደሌሎች ሰዎች እንዳይሰራጭ የአገሪቱ መንግስት ሙሉ ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብተዋል፡፡
የኢቦላ ቫይረስ በምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ከተከሰተበት ጊዜ ጀምሮ የ3338 ሰዎችን ህይወት የቀጠፈ ሲሆን ከ3ሺህ በላይ የሚሆኑ ህፃናትንም ወላጅ አልባ አድርጓል፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት ሰሞኑን ባወጣው ሪፖርት፤ እስካሁን የኢቦላ ቫይረስ ከምዕራብ አፍሪካ ሀገራት ውጭ ወደ ሌላው የአፍሪካ ክፍል አለመዛመቱን አስታውቋል፡፡   

Published in ዜና

          በአሁን ወቅት ወደ 300 የሚሆኑ የአውሮፓ ኩባንዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሰማሩ ሲሆን የአውሮፓ ኩባንያዎችን ይበልይ ወደ ሃገር ውስጥ ለመሳብ ጥረት እተደረገ ነው ተብሏል፡፡ “የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንትና ቢዝነስ ማነቃት በሚል መርህ በአውሮፓ ህብረት ኢትዮጵያ ልኡክ እና በህብረቱ የቢዝነስ ዶርም አዘጋጅነት በአዲስ አበባ ሂልተን ሆቴል በትናንትናው እለት ኢግዚብሽንና ኮንፈረንስ የተካሄደ ሲሆን በሃገሪቱ ተፈትሸዋል፡፡
የኮንፍረንሱ ዋነኛ አላማ አውሮፓ ህብረት እና የኢትዮጵያ የቢዝነስ ባለድርሻ አካላት በኢትዮጵያ ስላለው የቢዝነስ እና ኢንቨስትመንት አማራጭ እና ለችግሮቹ መፍትሄ በሚሆኑ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት የነበረ ሲሆን በእለቱም የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡ በኮንፈረንሱ ላይም በሃገሪቱ ለአውሮፓ ባለሃብቶች ተግዳሮት ናቸው በተባሉት ታክስ፣ ንግድ ፍቃድ፣ ግብር እና የውጭ ምንዛሬ ጉዳይ ላይ ሰፊ ውይይት ተካሂዷል በእለቱ ኢትዮጵያ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በምታደርገው ጥረት ላይ ሰፊ ውይይት የተካሄደ ሲሆን ከንግድ ፍቃድ ጋር ተያይዞ ይውጭ ባለሃብቶች የሚያጋጥማቸው ተግዳሮቶች በስፋት ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

Published in ዜና

       ሀሳብን በነፃ የመግለፅ ህገመንግስታዊ መብቴን ተጠቅሜ፣ ይህን የግል አስተያየቴን ለመላክ የተገደድኩት በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኞችን በሚመለከት ያወጣችሁትን የዜና ዘገባ መነሻ በማድረግ ነው። በዚህ አጋጣሚ ለጋዜጣችሁ የዜና ሽፋን መረጃ የሰጧችሁ ግለሰቦች እንደ ሰው ሀሳብን በነፃ የመግለፅ መብት ያላቸው በመሆኑ የሰጡትን ሀሳብ የማከብር ሲሆን እናንተም ጉዳዩን የጋዜጣችሁ አጀንዳ ማድረጋችሁ የመፃፍ መብታችሁ አንድ አካል አድርጌ እንደምቆጥርና አስተያየቴ የሚያተኩረው ማን ምን አለ የሚለው ላይ እንዳልሆነ እንዲታወቅልኝ እፈልጋለሁ። ወደ ዜናው ሽፋን ስመጣ፣ የዘገባችሁ ትኩረት እውነታን በገለልተኝነት ከማሳወቅ ይልቅ በተጋነነ ሁኔታ ተቋሙን በማብጠልጠልና አጠቃላይ ገፅታውን በማጠልሸት፣ ሰራተኛው በተቋሙና በመንግስት ላይ ጥርጣሬ እንዲያሳድር የሚያደርግ መሆኑን ልገልፅ እወዳለሁ፡፡
በተቋማችን ከመልካም አስተዳደር ችግር ጋር ተያይዞ ሰራተኛው በሀምሌ ወር 2006 ዓ.ም የመጀመሪያ ሳምንት ላይ ከተቋሙ ማኔጅመንት ጋር በግልፅ መድረክ ተወያይቷል፤ አሉ የተባሉ የአሰራር ችግሮችንም ፊትለፊትና ዴሞክራሲያዊ በሆነ አግባብ ገልጿል፤ ችግሮቹ እንዲፈቱም ጠይቋል። ማኔጅመንቱም ችግሮቹ እንደሚፈቱ ገልፆ፣ ያስተካከላቸው አሰራሮች ያሉ ቢሆንም እስካሁንም ያላስተካከላቸው ነገር ግን መስተካከል ያለባቸው ሌሎች ጉዳዮች እንዳሉ በግሌ አምናለሁ።  በዚህ አጋጣሚ ጋዜጠኛው ሀሳቡን በነፃነትና በግልፅ በማቅረብ፣ ችግር ያለበትንም ችግር አለብህ ብሎ ከመንገር ወደ ኋላ የማይል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል። ይህ ሲባል ጋዜጠኛው ኃላፊነት በማይሰማው መልኩ ተቋሙንና ጊዜያዊ ችግሮችን ለይቶ የማያይ የዋህ ነው ማለት አይደለም። በተለይ ሙያዊ ተልዕኮውን በመወጣት፣ በሀገሪቱ የልማትና ዴሞክራሲ እንዲሁም የህዝብ ተጠቃሚነት መረጋገጥ ጉዳይ ላይ ያለ ምንም ተጽዕኖ ሀሳቡን በድርጅቱ ህትመቶችና መፅሄት እንደሚገልጸው ሁሉ፣ ከራሱም አንፃር በሚፈጠሩ የአሰራር ችግሮች ሀሳቡን በነፃ የመግለፅ መብቱን ለድርድር እንደማያቀርብ ራሱ ጋዜጠኛው ምስክር ነው።
ጋዜጠኛው በራሱ ላይ የሚደርስ የመልካም አስተዳደር ችግርን አሜን ብሎ የማይቀበል፣ በመንግስትና ህዝብ ግንኙነት ባሉ አሰራሮች የሚከሰቱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችንም ገንቢ በሆነ መልኩ በግልፅ የሚተች እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ጋዜጠኛው የመልካም አስተዳደር ችግርን አሜን ብሎ የተቀበለና የተሸነፈ፣ በራሱ ተስፋ ቆርጦ ከሌላ አካል መፍትሄ የሚፈልግ ጠባቂ፣ በመንግስትም ፈፅሞ የተረሳ በማስመሰል «የፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኞች በመልካም አስተዳደር እጦት ተማረናል አሉ» ብሎ በጥቂት የሀሳብ መነሻዎች ሙሉ ሰራተኛውን ወካይ የሚመስል ግርድፍ ዘገባ መቅረቡ፣ የተቋሙን ሰራተኛ አሳንሶ እንደማየትና እንደ መስደብ እንዲሁም በሙያ አጋር ላይ እንደተሰነዘረ ጥቃት አድርጌ እቆጥረዋለሁ። የዘገባው መንፈስ ይሄ ነገር ለእውነት ከመቆርቆር የተሰራ ይሆን? የሚል ጥያቄም አጭሮብኛል።
በተቋማችን የመልካም አስተዳደር ችግር ያጋጠማቸው አንዳንድ ሰራተኞች እንዳሉ ባውቅም፣ አጠቃላይ ፍረጃው የዘገባውን ተዓማኒነት ጥያቄ ውስጥ ይከተዋል፡፡ ለመልካም አስተዳደር መስፈን ሌት ተቀን የሚሰሩ ጋዜጠኞችንም ሞራል የሚነካና ጤነኛና ገለልተኛ ያልሆነ ዘገባ ነው ብዬ አምናለሁ። በተለይ ጋዜጠኛውን የሚወክለው ትልቅ ኃላፊነት የተጣለበት የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በጋዜጣው እንደተጠቀሰው የሚያሳትማቸው አራት ጋዜጦችና በዘገባው ያልተጠቀሰው አንድ መፅሄትም የየራሳቸው መሪዎች ያሏቸው፣ በስራዎቻቸው የተሰጣቸውን ኃላፊነት ሙያው በሚፈቅደው አግባብ እየተወጡ መሆኑ እየታወቀ፣ ፕሬስ ድርጅት በአንድ ግለሰብ  ብቻ እንደሚመራና አመራሩም ደመነፍሳዊ አካሄድ እንደሚከተል ተደርጎ የቀረበው ጥቅል ፍረጃ ሚዛናዊ ነው ተብሎ ሊታመን የማይችል ነው።
በደመነፍስ ይመራል ሲባል፣ መሪው ብቻ ሳይሆን ተመሪውም የደመነፍስ አመራር ውጤት ነው ብሎ ከመግለፅ የተለየ አይደለም። ሀሳብን በነፃ የመግለፅ መብታቸውን ተጠቅመው አስተያየት የሰጡ የተወሰኑ ሰዎችን ሀሳብ ብቻ ይዞ አጠቃላይ የተቋም ውክልናን በመስጠት፣ ተቋሙ በደመ ነፍስ የሚመራ ነው ተብሏል ብሎ ማቅረብ፣ በደመነፍስ አንመራም የሚል ምላሽንም እንደ ሚዛናዊ አቀራረብ መጠቀም በራሱ ደመነፍሳዊና ሚዛናዊነትን ያልተከተለ፣ ጋዜጠኝነት የሚያስፈልገውን ሙያዊ ጥንቃቄ የዘነጋ ወገንተኛ አሰራር በመሆኑ መታረም ይኖርበታል እላለሁ። ይህ ስያሜ በተቋሙ የሚሰራውን ሰራተኛ (አጠቃላዩንም ጋዜጠኛ ጭምር) ሞራል የሚነካ፣ ጋዜጠኛውን እንደ ተላላኪ የሚቆጥር፣ ተቋሙ የተጣለበትን ሀገራዊ ኃላፊነት ለመወጣት የሚያደርገውን ጥረትም አሳንሶና አንኳሶ የሚያይ፣ ሙያዊ ኃላፊነትን የዘነጋ የዘገባ አሰራር በመሆኑ ጋዜጣው ራቅ አድርጎ ቢያይ የተገባ ነበር ብዬም አምናለሁ።
ተቋሙ መንግስት የዘነጋው ተደርጎ መቅረቡን በተመለከተ በስሜትና ባለመረዳት የተገለፀ ነው ብዬ አስባለሁ። ጋዜጠኛው ከመሰል ተቋማት አንፃር ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ በግል ባምንም፣ ተቋሙ በአደረጃጀቱም ሆነ ባህሪያዊ በሆነ መልኩ የራሱ ዓላማ ያለው በመሆኑ፣ በገቢ አቅምና መሰል በሆኑ ጉዳዮች ከሌሎች ጋር አላግባብና በተለጠጠ ሁኔታ እየተነፃፀረ መቅረቡ፣ ከዜናው ማዕከላዊ ነጥብና ፍላጎት ጋር የማይጣጣም፣ ሚዛናዊ አወዳዳሪ ሳይሆን ነጣጣይ፣ በተቋሙም ላይ ጫና የሚፈጥር ነው ብዬ እረዳለሁ። ይልቁንም ይህ አይነቱ አካሄድ ሰራተኛው ራሱን ዝቅ እንዲያደርግ፣ አልፈለግም ተረስቻለሁ ብሎ እንዲያስብ በሚያደርግ አግባብ የቀረበ በመሆኑ፣ የማይገነባና ለማንም የማይጠቅም ይመስለኛል፡፡ በነገራችን ላይ እንደ ሙያ ጓደኛ፣ ጋዜጠኛው በዚህ መሰሉ አተያይ ተስፋ የማይቆርጥ፣ በቀላሉ የሚፈቱ የዛሬ ችግሮችን ከተቋሙ ዓላማና ተልዕኮ እንዲሁም የነገ ራዕይ ጋር ቀይጦ የማያይ በመሆኑ፣ ከሙያዊ ኃላፊነቱ ይዘናጋል ብዬ አላስብም።
ከአዘጋጁ፡- ከላይ የቀረበው ፅሁፍ አንባቢ የፀሃፊውን ሃሳብና ስሜት በቅጡ ያገኘው ዘንድ ያለ ብዙ የአርትኦት ስራ (እንደወረደ በሚባል መልኩ) ማውጣታችንን ልንገልፅ እንወዳለን፡፡ ባለፈው ሳምንት “የፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኞች በመልካም አስተዳደር እጦት ተማረናል አሉ” በሚል የወጣው ዘገባ፣ በፕሬስ ድርጅቱ ስር በሚታተሙ የተለያዩ ጋዜጦች ላይ ከሚሰሩ ጋዜጠኞች የተገኘን መረጃ መሰረት ያደረገና ድርጅቱን የሚመሩ ኃላፊዎች በጉዳዩ ላይ የሰጡትን ምላሽ ያካተተ እንደሆነ የሚታወስ ነው፡፡
በዚህ የዜና ዘገባ፣ የፕሬስ ድርጅቱን ጋዜጠኞች ሃሳብ ከማንጸባረቅ ውጭ ወደ ማጠቃለልና አቋም ወደ መያዝ እንዳልገባን  ዜናውን ያነበበ ሁሉ የሚገነዘበው ነው፡፡ በሁሉም ዘገባዎቻችን እንደምናደርገው ሁሉ፣ የዜናውን ሚዛናዊነት በተቻለ መጠን ለመጠበቅም ሞክረናል ብለን እናምናለን፡፡
 ዓላማችን እውነተኛ፣ ትክክለኛና ሚዛናዊ መረጃ ለህብረተሰቡ ማድረስ ነው!!

Published in ዜና

ሶስት ፓርቲዎች በታሰሩ አባሎቻቸውና በጠበቃው ላይ የሚፈፀመው ህገወጥ ድርጊት አወገዙ

ጠበቃና የህግ አማካሪ ተማም አባቡልጉ ከሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ ክስ ሳይመሰረትባቸው በጊዜ ቀጠሮ ፍ/ቤት ለሚመላለሱት የአንድነት፣ የሰማያዊና የአረና አመራሮች የሆኑ ደንበኞቻቸው ላይ ህገ ወጥ ምርመራ እየተደረገባቸውና በአግባቡ ሊገናኙ ባለመቻላቸው፣ ከዚህ በኋላ ለጊዜ ቀጠሮ ወደ ፍ/ቤትና ወደ ማዕከላዊ ሄደው ደንበኞቻቸውን እንደማያገኙ ለፓርቲው በፃፉት ደብዳቤ አስታወቁ፡፡ ሶስቱ ፓርቲዎች በበኩላቸው፤ በአመራሮቻቸውና በጠበቃው ላይ ፍ/ቤትና ማረሚያ ቤቶች እያደረሱ ነው ያሉትን ኢ-ህገ መንግስታዊ ድርጊት አውግዘዋል፡፡
የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኑነት ኃላፊ አቶ ሃብታሙ አያሌው፣ የአንድነት ምክትል የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና ትግራይ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አብርሃ ደስታና የሰማያዊ ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ አቶ የሺዋስ አሰፋን በጥብቅና ለማገልገል የተስማሙት አቶ ተማም፤ በጊዜ ቀጠሮ ፍ/ቤት እና ማዕከላዊ እስር ቤት መገኘታቸው አስፈላጊ ሆኖ ስላላገኙት ካለፈው ረቡዕ ጀምሮ በተጠቀሱት ቦታዎች እንደማይገኙ ገልፀዋል፡፡
ደንበኞቻቸው ከተጠረጠሩበት ጉዳይ ውጪ ምርመራ እየተካሄደባቸው መሆኑን የጠቆሙት ጠበቃው፤ የፓርቲዎች የገንዘብ ምንጭ እንዲሁም ጥንካሬና ድክመት ላይ ያተኮሩ መረጃዎችን እንዲሰጡ እየተደረጉ ነው ብለዋል፡፡ ፖሊስ ያልሆኑ ግለሰቦች በምርመራው ተሳታፊ መሆናቸውን የጠቆሙት ጠበቃው፤ ደንበኞቻቸው እኛን የመመርመር መብት የላችሁም ሲሏቸው፣ ግለሰቦቹ የዘረኝነት ስድብ እየሰደቧቸውና “ለሃገር ጥቅም ሲባል ልንገድላችሁ እንችላለን” በማለት ዛቻና ማስፈራራት እንደፈፀሙባቸው ገልፀዋል፡፡
“ፖሊስ እኔንም ሆነ ሌሎች ጠበቆችን ከደንበኞቻቸው ጋር አላገናኝም በማለቱ የምርመራውን ሂደት ህገ-ወጥነት እና የደንበኞቼን አያያዝ በተመለከተ ማመልከቻ ብናቀርብም፣ ፍ/ቤት ትዕዛዝ የሰጠባቸውን ጨምሮ እርምጃ አልተወሰደም” ብለዋል አቶ ተማም፡፡
የተለያዩ ዛቻዎች እንደሚደርሷቸው የጠቆሙት ጠበቃው፤ “ካላረፍክ አደጋ ያገኝሃል እየተባልኩ የሌላውን መብት ለማስከበር እቆማለሁ ብዬ ብናገር ራሴንም ሆነ ሌላውን ከመዋሸት ለይቼ አላየው” ብለዋል፡፡ አክለውም በተጠቀሱት ሁኔታዎች ውስጥ ባለ ሂደት መሳተፍን ኢትዮጵያዊነታቸው፣ እውቀታቸውና የሙያ ስነ-ምግባራቸው የማይፈቅድላቸውና የማይቀበሉትም ጭምር እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የአረና ትግራይ ፓርቲ፣ አንድነትና ሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ጉዳዩን አስመልክቶ ባለፈው ረቡዕ  በአንድነት ፅ/ቤት “በህገ-ወጥ ድርጊት መገዛት ያብቃ” በሚል በሰጡት የጋራ መግለጫ፤ በጠበቃው ላይ የደረሰውን ጫና እንዲሁም ታሳሪ አባሎቻቸው ከጠበቃው ጋር መገናኘት እንዳይችሉ መደረጋቸውን በማውገዝ መንግስት በህገ - መንግስቱ የሰፈረውን በህግ ጥበቃ ስር ያሉ ግለሰቦችን መብት እንዲያከብር በአፅንኦት ጠይቀዋል፡፡ በቀጣይም ድርጊቱን የሚያወግዙበት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ እንደሚጀምሩ ፓርቲዎቹ ጠቁመዋል፡፡

Published in ዜና

ወላጆች የጥርሳቸውን ጤንነት ሊከታተሉላቸው ይገባል

የእንግሊዝ የማህበረሰብ ጤና ተመራማሪዎች፤ 54ሺ ገደማ የሚሆኑ ህፃናትን ጥርሶች ከመረመሩ በኋላ 12 በመቶ በሚሆኑት ህፃናት ላይ የጥርስ መበስበስ ምልክቶችን እንዳገኙ ይፋ አደረጉ፡፡ ህፃናቱ በአማካይ ሶስት ጥርሶቻቸው አንድም በስብሰዋል አሊያም ወልቀዋል ወይም ደግሞ ተሞልተዋል ብለዋል ተመራማሪዎቹ፡፡ ከቦታ ቦታ የጥናት ውጤቱ ከፍተኛ ልዩነት ያሳየ ሲሆን በሌችስተር አካባቢ 34 በመቶ ያህሉ ህፃናት የጥርስ መበስበስ ሲስተዋልባቸው በሌሎች አካባቢዎች ደግሞ 2 በመቶ ያህሉ ብቻ የችግሩ ተጠቂዎች መሆናቸው ታውቋል፡፡
አንዳንድ ህፃናት ገና በለጋ ዕድሜ ላይ የሚከሰት የተለየ ዓይነት የጥርስ መበስበስ እንደተገኘባቸው ተመራማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
ይሄ ችግር የሚያጠቃው የላይኛውን የፊት ጥርሶች ሲሆን በፍጥነትም ወደ ሌሎች ጥርሶች የሚሰራጭ እንደሆነ ታውቋል፡፡
እንዲህ ዓይነቱ የጥርስ መበስበስ ችግር በጡጦ ወይም በኩባያ ጣፋጭ አሊያም ስኳር የበዛባቸው ፈሳሾችን በመውሰድ የሚከሰት ነው ተብሏል፡፡
የእንግሊዝ የማህበረሰብ ጤና ተመራማሪዎች፤ ወላጆች ለልጆቻቸው ጣፋጭ ምግቦችንና መጠጦችን አልፎ አልፎና በጣም በትንሹ መስጠት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ የእናት ጡት ያቆሙ ህፃናት በሚወስዷቸው ምግቦችና መጠጦች ላይም ስኳር እንዳይጨምሩ ለወላጆች ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡
ወላጆችና ሞግዚቶች፤ ህፃናቱ የመጀመሪያ ጥርሳቸውን እንዳበቀሉ መቦረሽ መጀመር አለባቸው የሚሉት የህክምና ባለሙያዎች፤ ልጆቹ ሰባት ወይም ስምንት ዓመት እስኪሆናቸው ድረስም የጥርስ ንፅህና አጠባበቃቸውን መቆጣጠር እንዳለባቸው ጠቁመዋል፡፡

Published in ዋናው ጤና

በእድሜያቸው የገፉ ሰዎችን የማሽተት ችሎታ በመለካት፣ በቀጣይ በህይወት የሚቆዩበትን ጊዜ ለመተንበይ እንደሚቻል በአሜሪካ የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች የተሰራ ጥናት ማረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ተመራማሪዎች ከ57 እስከ 85 አመት እድሜ ክልል ውስጥ በሚገኙ 3ሺህ ሰዎች ላይ ያደረጉትን ጥናት ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ጥሩ የማሽተት ችሎታ ያላቸው ሰዎች፣ የማሽተት ችሎታቸው ዝቅተኛ ከሆኑ ሰዎች ጋር ሲነጻጸር ቀጣዮቹን 5 አመታት በህይወት የመቆየት ዕድላቸው ከፍ ያለ ነው፡፡
ጥናቱ በተከናወነባቸው ሰዎች ላይ የተመዘገበው ውጤት እንደሚያሳየው፣ ዝቅተኛ የማሽተት ችሎታ ካላቸው ሰዎች መካከል 39 በመቶ የሚሆኑት በአምስት አመት ጊዜ ውስጥ ሲሞቱ፤ ጥሩ የማሽተት ችሎታ ካላቸው ሰዎች መካከል በተመሳሳይ ጊዜ ውስጥ የሞቱት 10 በመቶው ብቻ ናቸው፡፡
ተመራማሪዎቹ ለግለሰቦቹ የአሳ፣ የብርቱካን፣ የጽጌረዳ አበባ፣ የቆዳና የናና መዓዛዎችን በእስክርቢቶ ጫፍ ላይ በማድረግ እንዲያሸቱና የምን መዓዛ እንደሆነ እንዲለዩ በመጠየቅ የማሽተት ችሎታቸውን መዝግበዋል፡፡ ከአምስት አመታት በኋላም፣ ጥናቱ ከተሰራባቸው ሰዎች፣ ምን ያህሉ በህይወት እንዳሉና ምን ያህሉ እንደሞቱ አረጋግጠዋል፡፡ በመቀጠልም የሞት መጠኑን ከማሽተት ችሎታ ጋር በማጣመር፣ በሁለቱ ነገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጥናት ሞክረዋል፡፡
የማሽተት ችሎታ እየቀነሰ መምጣት በቀጥታ ለሞት እንደማይዳርግ የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይሄም ሆኖ ግን ክስተቱ እንደማስጠንቀቂያ ሊወሰድ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
“የማሽተት አቅም መቀነስ በቀጥታ ለሞት አይዳርግም፡፡ ይሄም ሆኖ ግን በግለሰቡ ጤንነት ላይ ጉዳት እንደደረሰ የሚያመላክት ቅድመ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ በምርምሩ ያገኘናቸው ውጤቶች በጤና ምርመራ ላይ እገዛ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ለአደጋ የመጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ የሆኑ በሽተኞችን ለይቶ ለማወቅ የሚያግዝ ፈጣንና ወጪ የማይጠይቅ የምርመራ ዘዴ ሆኖ ሊያገለግል ይችላል” ብለዋል የተመራማሪ ቡድኑ መሪ የሆኑት ፕሮፌሰር ጃያንት ፒንቶ፡፡
በህይወት የመቆየት ዕድልን የሚወስኑ እርጅና፣ የምግብ አወሳሰድ፣ የሲጋራ ሱሰኝነት፣ ድህነትና አጠቃላይ የጤና ሁኔታን የመሳሰሉ ጉዳዮች እንዳሉ ሆነው፣ የማሽተት ችሎታቸው በጣም ዝቅተኛ የሆኑ ሰዎች ለሞት የመዳረግ እድላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ተመራማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን የማሽተት ችሎታ መቀነስ፣ በምን መንገድ በህይወት ላለመቆየት እድል አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት በግልጽ ባይታወቅም፣ ተመራማሪዎቹ በሁለቱ መካከል ያለውን ግንኙነት በተመለከተ የራሳቸውን ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡
አነስተኛ የማሽተት ችሎታ መኖር፣ በግለሰቦች ሰውነት ውስጥ የሚገኙ ያረጁ ህዋሶች የሚታደሱበት መጠን አነስተኛ መሆኑን ሊያመላክት ይችላል ብለዋል ተመራማሪዎቹ፡፡ ጤናማ የማሽተት ችሎታ እንዲኖር ከሚያደርጉ ነገሮች መካከል፣ በአፍንጫ ውስጥ የሚገኙ ህዋሳት በየጊዜው መታደሳቸው ይጠቀሳል ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ሰዎች ዝቅተኛ የማሽተት ችሎታ ስላላቸው መጨነቅ እንደሌለባቸው የመከሩት ፕሮፌሰር ፒንቶ፤ ጉዳዩ ከጉንፋን፣ ከአለርጂክና ሳይነስን ከመሳሰሉ የጤና ችግሮች ጋር የተያያዘ ሊሆን እንደሚችልም ተናግረዋል፡፡ የማሽተት ችግሩ እየተባባሰ ከመጣ ግን፣ ሃኪማቸውን ማማከር እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡
የካርዲፍ ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ የሆኑትና በጥናቱ ውስጥ ያልተሳተፉት ፕሮፌሰር ቲም ጃኮብ በበኩላቸው፤ በጥሩ ሁኔታ የተከናወነው ይህ ጥናት፣ የማሽተት ስሜትና ጤንነት በእጅጉ እንደሚቆራኙ ያመላከተ ነው ብለዋል፡፡
በሰውነት አጠቃላይ ሁኔታና በስነ-ልቦና መካከል ትስስር እንዳለ የጠቆሙት ጃኮብ፤ ለአብነትም ማሽተት አለመቻል ድብርት እንደሚፈጥር፣ ድብርትም በመስማት ችሎታ ላይ ተጽዕኖ ሊፈጥር እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

Published in ዋናው ጤና
Page 14 of 15