ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የሥነ - ከዋክብት ተመራማሪ በአንድ የገጠር ከተማ ይኖር ነበረ፡፡ የዚህ ሰው የሁልጊዜ ፈሊጥ ማታ ማታ ከቤቱ እየወጣ የሰማይ ላይ ከዋክብትን ማየትና የሰው ልጆችን ዕጣ -ፈንታና የተፈጥሮን አካሄድ መመርመር ነበር፡፡
ይህን ክህሎቱን ከጊዜ በኋላ የተረዱ የከተማይቱ ሰዎች ቀስ በቀስ ስለሱ አዋቂነት ማውራት ጀመሩ፡፡ ዋሉ አደሩና እየተከተሉት ዕጣ - ፈንታቸውን ይጠይቁት ያዙ፡፡
አንደኛው - “የሥነ - ከዋክብት አዋቂ ሆይ! የእኔ የወደፊት ዕጣ ምን ይሆን?” ሲል ጠየቀው፡፡
አዋቂ - “ያንተን የከዋክብት ፈለግ እንዳየሁት የመጨረሻ ዕልፈትህ ጠብ ውስጥ ገብተህ ነው፡፡ ያላሰብከው ሰው ነው የሚገድልህ” አለው፡፡
አንደኛው - “ታዲያ ምን ባደርግ ነው የሚሻለኝ?”
አዋቂ - “በምንም ዓይነት ጠብ አካባቢ አትገኝ”
ሌላ ተከታዩ ይመጣል፡፡
“አዋቂ ሆይ! የእኔስ ዕጣ ምን ይሆን?”
አዋቂ - “ኮከብህ የብልጽግና ነው፡፡ ነገር ግን ምቀኞች አሉብህ”
ተከታይ - “ታዲያ ምን ባደርግ ከእነዚህ ምቀኞች ተንኮል አመልጣለሁ?”
አዋቂ - “ደግ እየመሰሉ ከሚቀርቡህ ሰዎች ተጠንቀቅ”
እንዲህ እንዲህ እያለ በየጊዜው እየተከተሉ ዕጣ - ፈንታቸውን ለሚጠይቁት ሰዎች መልስ ሲሰጥና ሲመክር ሰነበተ፡፡
አንድ ማታ እንደተለመደው ከከተማው ዋና በር (ከተምበሪ) አልፎ ሄደ፡፡
ቀና ብሎ ዐይኖቹን ሰማዩ ላይ ተከላቸው፡፡ መመራመሩን፣ መጠበቡን፣ መፈላሰፉን ቀጠለ፡፡ ይህን የየከዋክብቱን አካሄድና እንቅስቃሴ እያየ፣ እንዳንጋጠጠ፣ መራመዱን ቀጠለ፡፡ ሳያስበው ከእግሩ ሥር ካለ አንድ ደረቅ ጉድጓድ ውስጥ ድንገት ጥልቅ አለ፡፡
እዚያ ጉድጓድ ውስጥ ሆኖ እንደወቀደ ያጓራና ያቃስት ገባ፡፡ አንድ ሰው በዚያ አቅራቢያ ሲያልፍ የዚያን የሚያስጓጉር አዋቂ ድምጽ ሰማ፡፡ ወደ ጉድጓዱ አፍ ቀረበና ቁልቁል ተመለከተ፡፡ ሁኔታውን ካስተዋለ በኋላ፤
“ምን ልታደርግ እዚያ ገባህ?”
“ወድቄ ነው”
“እንዴት ይሄን የሚያህል ጉድጓድ አላየህም?”
“ሰማዩ ላይ በጣም አተኩሬ ስለበረ ነው”
“አይ ወዳጄ!” እንደዛ ታላቅ አዋቂ ነህ ብለን የተቀበልንህ ሰው፤ ሰማይ ሰማይ ስታይ እግሮችህ ወዴት እንሚወስዱህ እንኳ ካላወቅህ፤ እኔ እንደሚሰማኝ፤ አሁን ያለህበት ቦተ ተገቢ ቦታህ ነው!” አለው፡፡
* * *
ሰማይ ሰማይ ስናይ እግራችን ሥር ያለውን ነገር አንዘንጋ፡፡ ሰማዩን አተኩረን ስናይ ቀልባችን ሙሉ በሙሉ እሱ ላይ ብቻ ካረፈ፤ ከሥር እግራችንን የሚመታንን እንቅፋትና የሚያሰምጠንን ጉድጓድ አናየውም፡፡ ወደኃያላን መንግሥታት ስናንጋጥጥ የራሳችንን ህዝብ እንረሳለን፡፡ አልፈን ተርፈንም የሰዎችን ዕጣ-ፈንታ ስንናገር የራሳችንን ዕጣ-ፈንታ ሳናቅ እንዳንቀር እንጠንቀቅ!
ኃያላን መንግሥታት ሲሻቸው የበኩር ልጅ፣ ሲሻቸው የእንጀራ ልጅ ማድረግን ይችሉበታል፡፡ ኃያላን መንግሥታት “ሲሞቅ በማንኪያ ሲቀዘቅዝ በእጅ” ገንፎ መብላትን ያውቁበታል፡፡ መልዕክተኞቻቸውን ሲሻቸው በእርዳታ ሰጪ መልክ፣ ሲሻቸው በሚሲዮናውያንና በሃይማኖተኞች መልክ፣ ሲሻቸው በዲፕሎማት መልክ፤ ካልሆነም በቀጥታ ስለላ መልክተኞች - አሊያም በቱሪስት ወይም በፒስኮር መልክ ይልካሉ፡፡ ከከፋም የውስጥ ዐርበኛ ይቀጥራሉ፡፡ ላላ ያለ ካገኙም አገራቸው ድረስ ጋብዘው፣ አስተናግደው ሾመው፣ ሸልመው አንቱ ብለው ይቀባሉ፡፡
ያለ፣ የነበረ ወደፊትም የሚኖር ዘዴያቸው ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ካልተሳካ የቁርጡ ቀን መጣ ማለት ነውና እንደ ኢራቅ የጦር ዘመቻ ያካሂዳሉ፡፡ እንደግሎባላይዜሽን አበጋዞች ሳይሆን እንደጥንቶቹ ቅኝ ገዢዎች- በግልጽ ወረራ ያካሂዳሉ፡፡
ከሁሉም ይሰውረን፡፡ ሲያወድሱ ሰማይ፣ ሲጥሉ እንጦር አውርደው ከትቢያ ይደባልቃሉ፡፡ የሁልጊዜ መሳሪያቸው ነው፡፡ እስካመቸናቸው እስካልቆረቆርናቸው ድረስ ያለእኛ በትክክለኛው የዕድገት መስመር ላይ ያለ አገር አይገኝም፡፡ “እንዲህ እያልሽ ውቴልሺን ሽጪ” እንዳለው ወሎ፤ የሚነግራቸው ጠፍቶ ነው፡፡ ለእነሱ የከፋን ለታ ግን ያለእኛ ኋላቀር፣ ያለእኛ ደንቆሮ፣ ያለእኛ ጦርነት ናፋቂ፣ ያለእኛ ረሃብተኛ፣ ያለእኛ መናጢ ደሃ የለም፡፡ ”እፀድቅ ብዬ ባዝላት ተንጠልጥላ ቀረች” ይሉናል፡፡
ከበረታን፤ “አላህንም አትክዳ፣ ሐረጓንም አትልቀቅ” እንዳሉት ጠቢብ ማሰብ አለብን፡፡
የኃያላኑን የቢዝነስ ኮሙኒቲ አይተን እኛ ምን እንሥራ ማለታችን ደግ ነገር ሆኖ፤ ከእዚህ ሁሉ በስተጀርባ ምን አለ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ምን ያህል ከልባቸው ነው? እነሱ፤ ለህዝባችን ይበጃል ያሉትን ማንኛውንም እኩይ ተግባር ከመፀፈም ወደኋላ ብለው ያውቃሉን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ሁሉንም በትጋት በጉጉት - ዐይን እናስተውል፡፡
የፖለቲካ ፀሐፍት እንደሚነግሩን፤ “ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚወድቁት ስህተት ስለሚሰሩ ሳይሆን ስህተታቸውን እንዴት እንደሚያርሙ ስለማያውቁ ነው፡፡ ይሄ የእኛም ችግር ነው፡፡ ሁለት ተጠቃሽ ባህሪዎቻችን፡- “ካፈርኩ አይመልሰኝ (Rigidity)”፣ እና “የአብዬን እከክ ወደእምዬ ልክክ (Blame shifting)” ናቸው፡፡ የሠራሁት ነገር ስህተት እንዳለበት ቢነገረኝም አልለቀውም፡፡ አንዴ አድርጌያለሁ ብያለሁ፡፡ ብያለሁ፡፡ ኃያላኑም ተናግረዋል፤ ማለት አይበጅም፡፡ በተቻለ መጠን በኃያላን ውዳሴ አለመማለል ብልህነት ነው! “ቅጥ - ያጣ መረጃ” ይዘን ነው እስካሁን የሄድነው ተብሏል፡፡ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ችግሮቻችን፣ የሚጨበጡትንና የማይጨበጡትን ጨምሮ፤ ስፍር - ቁጥር የላቸውም፡፡ በአንድ የድህነት ባኮ ከትተን ልንገላገላቸው መንገድ ከጀመርን ከራርመናል፡፡ አሁንም ግን በመጨለምና በንጨላጨል መካከል ነን፡፡
በሬዲዮ ጥያቄና መልስ ፕሮግራም “የሱዳን ዋና ከተማ ማን ትባላለች” ሲባል “አማርኛ ይሁንልኝ” …“የቆጡን አወርድ ብላ…” ጨርሰው ሲባል “ስፖርት ይሁንልኝ”፤ ዓይነት መልስ የሚመልስ ህብረተሰብ ይዘን እየዳከርን ነው፡፡ አገራችን፤ ላዩም ታቹም ይሄን መሳይ ነው!
በጭካኔ ፍትሕን ማምጣት (Brutal justice) እና የኢኮኖሚ አምባገነንነት (Economic Dictatorship) ቦታ ቦታ አላቸው፡፡ ጊዜ ጊዜም አላቸው፡፡ ለመተግበር ፍፁም ጥንቃቄን ይጠይቃሉ። ውጤታቸው ጠላት ማብዛት፣ ዜጋን ማስኮረፍ፣ ሕዝብን መሬት ውስጥ መክተት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆደ - ሠፊና ለጋሥ አምባገነን መሆን (Benevolent Dictator) የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ህብረተሰብን በቅጡ ማሳመን ይሻል፡፡ በተለይም የተለያየ ሃይማኖት፣ ባህልና ብሔረሰብ ባለበት አገር እጅግ ከባድ አስተዳደራዊ ምሉዕነትን ይጠይቃል፡፡ የፈረንሳዩ መሪ ደጐል “ሶስት መቶ ስልሳ ዓይነት ዐይብ ያለውን ህዝብ ማስተዳደር ከባድ ነው” የሚለን ለዚህ ነው!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

አልሸባብ የፍንዳታ ጥቃት ለማድረስ ዝቷል

ባለፈው እሁድ በቦሌ ሚካኤል አካባቢ ከደረሰው ፍንዳታ ጋር ተያይዞ ሁለት ተጨማሪ የፍንዳታ ጥቃት ለማድረስ አልሸባብ የተሰኘው የሶማሊያ ቡድን እንደዛተ የገለፀው የአሜሪካ ኤምባሲ፤ የዛቻው ተአማኒነት ባይረጋገጥም በኢትዮጵያ የሚገኙ አሜሪካዊያን ጥንቃቄ እንዳይለያቸው አሳሰበ፡፡
የኢትዮጵያና የናይጄሪያ ቡድኖች ግጥሚያ በሚካሄድበት ሰዓት ጥቃት ለመፈፀም ሲዘጋጁ የነበሩ ሁለት ሰዎች መሞታቸው የሚታወስ ሲሆን በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት በማወጅና ሽብር ለመፈፀም በመዛት የሚታወቀው አልሸባብ “ድርጊቱ በኔ አባላት የተፈፀመ ነው” ብሏል፡፡
አልሸባብ በቦሌ ሚካኤል ለተከሰተው ፍንዳታ ሃላፊነት እንደሚወስድ በትዊተር እንዳስታወቀ ኤምባሲው ጠቅሶ ባሰራጨው ማሳሰቢያ፤ በፒያሳና በቸርችል ጐዳና አካባቢ የፍንዳታ ጥቃት ለመፈፀም እንደዛተም ገልጿል፡፡
በቦሌ ሚካኤል በአንድ መኖሪያ ቤት ውስጥ በተከሰተው ፍንዳታ ሁለት የሶማሊያ ተወላጆች መሞታቸውን የገለፀው ፖሊስ፤ ከሟቾቹ አንዱ የኢትዮጵያ ማሊያ በመልበስ ከኳስ ተመልካቾች መሃል የፍንዳታ ጥቃት ለመፈፀም እየተዘጋጀ እንደነበር ጠቁሟል፡፡
ለጥቃት የታሰበው ፈንጂ እዚያው ፈንድቶ ነው ሁለቱ አሸባሪዎች የሞቱት ብሏል - ፖሊስ፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ የፍንዳታው ፈፃሚዎች አልሸባብ መሆናቸውን ተጠይቀው ገና አልተረጋገጠም ብለዋል፡፡
የፀረ ሽብር ግብረ ሃይል ጉዳዩን እየመረመረ እንደሚገኝ የገለፁት አቶ ሽመልስ፣ ግብረ ሃይሉ የደረሰበት ውጤት ጊዜውን ጠብቆ ይፋ እንደሚደረግ አስረድተዋል፡፡

Published in ዜና

በኢትዮጵያ እና በናይጄሪያ የእግር ኳስ ጨዋታ በጋምቤላ ክልል ኚኝኛግ ወረዳ በደጋፊዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የወረዳው አፈጉባኤ እና ወታደሮች እንደሞቱ ምንጮቻችን ገለፁ።
የደቡብ ሱዳን አዋሳኝ በሆነችው የኚኝኛግ ወረዳ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ በአዲስ አበባ ስቴዲየም ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ባደረጉት ጨዋታ፣ የናይጄሪያ ብሔራዊ ቡድን በማሸነፉ ደስታቸውን በጭፈራ በመግለጽ ላይ በነበሩ እና በድርጊቱ በተቆጡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ደጋፊዎች መካከል ግጭት ተፈጥሮ የኚኝኛግ ወረዳ አፈጉባኤና ከሁለት በላይ ወታደሮች እንደሞቱ ታውቋል፡፡
ችግሩ እንደተፈጠረ ከፌደራልና ከክልል የተውጣጡ ባለስልጣናት ቦታው ድረስ በመሄድ የማረጋጋት ስራ መሥራታቸውን ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የክልሉ ፕሬዝዳንት ሁኔታው ለማየት ወደ ስፍራው የሄዱ ሲሆን ስለ ጉዳዩ ፕሬዝዳንቱን በስልክ ለመጠየቅ ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡

Published in ዜና

ሰሸዋንዳኝ የአልበም ምርቃት የተጋበዙት ሠራዊት ፍቅሬና ሰይፉ ፋንታሁንም ተከልክለዋል

በሸራተን አዲስ ጋዝ ላይት ክለብ ከትናንት በስቲያ ሰተካሄደው የድምፃዊ ሸዋንዳኝ ኃይሉ “ስጦታሽ” አልበም ምርቃት በክብር እንግድነት የተጠራው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)፤ ሰዓት አርፍዶ በመድረሱ እንዳይገባ ተከልክሎ ከበር ተመለሰ፡፡
ቴዲ አፍሮ ከምሽቱ 5፡30 ላይ የምርቃት ስነስርዓቱ ወደሚካሄድበት ጋዝ ላይት ክለብ ሊገባ ሲል የጥበቃ ሰራተኞች “ጥሪው 4 ሰዓት እንጂ 5፡30 ሰዓት አይደለም” በማለት እንዳይገባ እንደከለከሉት ለማወቅ ተችሏል። አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬና ሰይፉ ፋንታሁንን ጨምሮ በርካታ ያረፈዱ እንግዶች ወደ ጋዝ ላይት ክለብ እንዳይገቡ መከልከላቸውን የዓይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ ሸዋንዳኝ፤ ቴዲ አፍሮ እንዳይገባ መከልከሉን የሰማው መድረክ ላይ ሆኖ እንደሆነ የገለፁት ምንጮች፤ በዚህም ማዘኑን ተናግረዋል። አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች፤ ሁለቱ እንዳላቸው ቅርበት ቴዲ አፍሮ በፕሮግራሙ ላይ ቀድሞ መገኘት ነበረበት ብለዋል፡፡ ድምፃዊ ሸዋንዳኝን ስለ ጉዳዩ በስልክ ጠይቀነው፣ መልስ ከመስጠት ተቆጥቧል፡፡
ከትላንት በስቲያ ምሽት በተካሄደው የምርቃት ስነ ስርዓት ላይ ሸዋንዳኝ ከአዲሱ አልበም አስር ዘፈኖችን የተጫወተ ሲሆን የተዘጋጀለትን አዲካ እና ኤም ጂ ፕሮሞሽን ያዘጋጁለቱንም ኬክ በዚያው ፕሮግራም ላይ ቆርሷል፡፡ ሸዋንዳኝና ቴዲ አፍሮ በአንድ የሙዚቃ ባንድ ውስጥ ለረጅም አመታት አብረው የሰሩ ሲሆን ቴዲ አፍሮ ሲያገባ ሸዋንዳኝ ሚዜው ነበር፡፡
ማርፈድ የስንፍና ምልክት መሆኑን የተናገረው አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ፤ሸራተን ስንደርስ የሆቴሉ ስራ አስኪያጅ በሩን ዘግተው እንደሄዱ ተነግሮናል ብሏል፡፡ “በሌሎች አገሮችም የተለመደ ነው፤ናይት ክለብ ከሞላ ሰው እስኪቀንስ መግባት አይቻልም” ያለው ሰራዊት፤ “እኛ ታዋቂ ስለሆንን ለምን ተከለከልን የሚል ቅሬታ አላደረብንም” ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና
  • የቀድሞ ኤርፖርት ጉምሩክ ሃላፊ በዋስ ተለቀዋል 
  • በእነ አቶ መላኩ ፈንታ ላይ የቀረበው ክስ ሠኞ እና ማክሰኞ ይሰማል

          በከባድ የሙስና ወንጀል በተከሰሱት የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት የተለያዩ ሃላፊዎች እና ሠራተኞች እንዲሁም ታዋቂ ባለሃብቶች ላይ በፌደራል የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ የቀረበው ክስ፣ ልደታ በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት መሠማት የጀመረ ሲሆን በባለሀብቱ አቶ ማሞ ኪሮስ እና በገቢዎች ጉምሩክ ባለስልጣን የቦሌ አየር ማረፊያ ጉምሩክ የፍተሻ የስራ ሂደት መሪ በነበሩት በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ የቀረበው ክስ ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡
ተከሳሾችም በክሱ ላይ ያላቸውን የመቃወሚያ ነጥብ ያስመዘገቡ ሲሆን አቶ ዮሴፍ አዳዩ የተከሰሱበት የወንጀል አንቀጽ ከ10 አመት በታች የሚያስቀጣ በመሆኑ የዋስትና መብታቸው ተከብሮላቸዋል፡፡
አቃቤ ህግ በአቶ ማሞ ኪሮስ ላይ ያቀረበው ክስ ተከሳሹ በ1998 ዓ.ም “ከተማ ኮንስትራክሽን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ”ን በስራ አስኪያጅነት ሲመሩ ከህግ አግባብ ውጪ እቃዎች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ አድርገዋል ይላል፡፡ ተከሳሹ “የኮንክሪት ሚክሰር” እና “ቫይብሬተር” ከውጭ ከቀረጥ ነፃ ካስገቡ በኋላ፣ ከእሸቱ ኤልያስ ወልደማርያም አስመጪና ላኪ የገዙ ለማስመሰል ሃሰተኛ ሰነድ አዘጋጅተዋል የሚል የወንጀል ክስም ቀርቦባቸዋል፡፡ አቃቤ ህግ በክስ መዘርዝሩ ላይ ስለወንጀሉ አፈፃፀም ያስረዱልኛል ያላቸውን የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎች ማቅረቡንም ፍ/ቤቱ የክሱን ጭብጥ በንባብ ባሰማበት ወቅት አመልክቷል፡፡ ክሱ በችሎቱ ከተነበበ በኋላም የቀረበው ክስ የውስብስብነት ባህሪ ስለሌለው በመደበኛ ክርክር ሂደት እንዲቀጥል ብይን ተሰጥቷል፡፡
የተከሳሽ ጠበቃ የመቃወሚያ ሃሳባቸውን ተጠይቀው ሲያቀርቡም፤ የአቃቤ ህግ ክስ፣ ተከሳሽ ራሱን መከላከል በሚያስችለው ደረጃ ተዘርዝሮ በሚገባ የቀረበ አይደለም፣ የተጠቀሰው የወንጀል አንቀጽ (379) በባህሪው የሙስና ወንጀልን አያመለክትም፤ ክሱ የቀረበበት አንቀጽ ተገቢ አይደለም” ብለዋል፡፡ ከእሸቱ ኤልያስ ድርጅት ተጭበረበረ የተባለው ሰነድ የመንግስት ሰነድ አይደለም ያሉት የተከሳሽ ጠበቃ፤ ክሱ በዚህ መልኩ መቅረቡ የተከሳሹን የመከላከል እድል የሚያጠብ ስለሆነ ተሻሽሎ እንዲቀርብ ይደረግልን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ ለመቃወሚያው በሰጠው ምላሽ ክሱ ተከሳሹ በሚረዳው መልኩ በዝርዝር የቀረበ ነው፣ የተጠቀሰው አንቀጽ የሙስና ወንጀልን የሚጠቅስ ነው፣ የተጭበረበረው ሰነድ በእርግጥም ከግል ድርጅት የወጣ ነው፤ ነገር ግን የጉምሩክ መስሪያ ቤትን በዚያ ሰነድ አሳስተዋል፤ ስለዚህ ፍ/ቤቱ መቃወሚያውን ውድቅ ያድርግልን ሲል ጠይቋል፡፡
በተመሳሳይ ፍ/ቤቱ በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ የቀረቡትን ሁለት ክሶች በንባብ ያሰማ ሲሆን አንደኛው ክስ፣ ተከሳሽ በገቢዎችና ጉምሩክ የአዲስ አበባ ኤርፖርት የመንገደኞች ማስተናገጃ የፍተሻ ክፍል ሃላፊ ሆኖ በሰራባቸው ከ2002 -2003 ባሉ አመታት ከውጭ ወደ ሃገር ውስጥ የሚገቡ የተለያዩ ግለሰቦች ለያዙት እቃ ቀረጥ ሳይከፍሉ እንዲገቡ በማሰብ፣ ሳይፈተሹ እንዲያልፉ አድርጓል የሚል ነው፡፡ ከዚሁ ክስ ጋር ተያይዞም ንብረትነታቸው የገቢዎችና ጉምሩክ የሆኑ ኦርጅናል የስራ ሰነዶችን መኖሪያ ቤቱ አስቀምጦ ተገኝቷል የሚል የወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡ በተከሳሹ ላይ የቀረበው ሁለተኛ ክስ ደግሞ ህጋዊ ፍቃድ የሌለው ማካሮቭ ሽጉጥ ይዞ ተገኝቷል የሚል ነው፡፡ ለክሶቹ የሰነድና የሰው ማስረጃ እንዲሁም በኤግዚቢት የተያዙ ንብረቶች መቅረባቸውን በክሱ ማመልከቻ ተጠቅሷል፡፡
የተከሳሽ ጠበቃ የመቃወሚያ ሃሳባቸውን ያቀረቡ ሲሆን ወንጀሉ ተፈፀመ የተባለበት ትክክለኛ ቀን በዝርዝር አልተገለፀም፣ የግለሰቦቹ ማንነትና ብዛት በግልጽ መታወቅ ነበረበት፣ የጉምሩክ ሰነዶች በቤቱ ተገኝተዋል የተባለው በየትኛው የወንጀል አንቀጽ እንደሚያስጠይቅ አልተጠቆመም ብለዋል፡፡ ፍቃድ የሌለው መሣሪያ ይዞ መገኘት የሚለውን በተመለከተም ኮሚሽኑ እንዲህ አይነት ክስ ማቅረብ አይችልም፤ ጉዳዩ ከሙስና ጋር የሚገናኝ ስላልሆነ በሌላ አካል ነው መታየት ያለበት ስለዚህ ክሱን ይሰርዝ ሲሉ ጠበቃው መቃወሚያቸውን አቅርበዋል፡፡
አቃቤ ህግ ለመቃወሚያው በሰጠው ምላሽ፤ ድርጊቱ የተፈፀመው በተለያየ ጊዜ ነው፣ ሳይፈተሹ እንዲያልፉ የተደረጉት ግለሰቦች ብዛት እና ማንነት ምስክሮች ሲቀርቡና ማስረጃ በዝርዝር ሲቀርብ በሂደት የሚታይ ይሆናል፣ ሰነዶችን በተመለከተም ኦርጅናል የመስሪያቤቱን ሰነዶች ማስቀመጥ የነበረበት መኖሪያ ቤቱ ሳይሆን መስሪያ ቤት ነው ብሏል፡፡ ህገ ወጥ መሣሪያ ይዞ መገኘት በእርግጥ የሙስና ወንጀል አይደለም፤ ነገር ግን ክሱን አብሮ ለማቅረብ የስነ ስርአት ህጉ እንደሚፈቅድ በሰበር ሰሚ ችሎት ተወስኗል የሚል ምላሽ ሰጥቷል - አቃቤ ህግ፡፡
የተከሳሹ አቶ ዮሴፍ አዳዩ ጠበቃም የተጠቀሰው አንቀጽ ከ10 አመት በታች የሚያስቀጣ ስለሆነ የዋስ መብትን የሚያስከለክል አይደለም፤ የዋስትና መብቱ ይከበር ሲሉ ፍ/ቤቱን የጠየቁ ሲሆን አቃቤ ህግም በዋስ ቢለቀቁ ተቃውሞ እንደሌለው፣ ነገር ግን ከሃገር እንዳይወጡ ለኢምግሬሽንና ዜግነት ጉዳይ ትዕዛዝ ይፃፍልን ሲል አመልክቷል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር ሲያደምጥ የቆየው ፍ/ቤቱ፤ በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ በሰጠው ትዕዛዝ፣ ተከሳሹ የ5ሺህ ብር ዋስ አቅርበው እንዲለቀቁ እንዲሁም ከሀገር እንዳይወጡ ለኢምግሬሽንና ዜግነት ጉዳይ ደብዳቤ እንዲፃፍ ብሏል፡፡ መዝገቡንም ለጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡ በአቶ ማሞ ኪሮስ ላይ ፍ/ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ፣ መቃወሚያውን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 14 ቀን 2006 ቀጥሯል፡፡
በሌላ በኩል ክስ ሳይመሰረትባቸው ጉዳያቸው ወደ ምርመራ መዝገብ የተመለሠው አቶ ፍፁም ገ/መድህን፣ በእግዚአብሔር አለበልና ምህረተአብ አብርሃ ጥቅምት 6 ቀን 2006 ፍ/ቤት ቀርበው ዳኞች ተሟልተው ባለመቅረባቸው ለጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡
አቶ መላኩ ፋንታ እና አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ ክስ ቀርቦባቸው ማረሚያ ቤት የሚገኙ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች ጥቅምት 11 እና 12 ቀን 2006 ዓ.ም ክሣቸውን ለማንበብ ቀጠሮ መሰጠቱ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና

          በ15 ቀን ውስጥ ከወልቃይት  ጠገዴ ሁለት ሺ ተማሪዎች ተፈናቅለዋል”

            የመላው አማራ ህዝብ (መዐህድ) በአማራ ተወላጅ ተማሪዎች ላይ እየደረሰ ያለው መፈናቀል በአስቸኳይ እንዲቆም ጠየቀ፡፡ መአህድ ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ የአማራ ተወላጆችን መፈናቀል በተመለከተ ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ማሳወቁንና መፈናቀሉ እንዲቆም መጠየቁን ጠቁሞ፤ ጉዳዩ እስካሁን እልባት አለማግኘቱን ገልጿል፡፡
መፈናቀሉ ሊቆም ቀርቶ ተጠናክሮ መቀጠሉንና በቅርቡም ከጉራፈርዳ፣ ከቤኒሻንጉል እና ከወልቃይት ጠገዴ የአማራ ተወላጅ ተማሪዎች መፈናቀላቸውን የጠቆመው መዐህድ፤ ድርጊቱ በአገሪቱ ስርዓት አልበኝነት መንሰራፋቱን ያሳያል ብሏል፡፡
ከተማሪዎች በተጨማሪ የአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮችንም ለይቶ ማፈናቀሉ ለመሪር ሀዘን እንደዳረገው መአህድ ገልፆ፤ አንድን ብሄር ማዕከል ያደረገ ማፈናቀል እንዲቆም ጠይቋል፡፡
ባለፉት 15 ቀናት ብቻ “አካባቢያችሁ አይደለም” በሚል ከወልቃይት ጠገዴ ሁለት ሺህ ተማሪዎች መፈናቀላቸውን የገለፁት የመአህድ ፕሬዚዳንት አቶ ሸዋንግዛው ገብረስላሴ፤ ከጉራፈርዳም ተማሪዎች ተፈናቅለው ከትምህርት መስተጓጐላቸውንና ለጊዜው ቁጥራቸው በውል አለመታወቁን ፕሬዚዳንቱ ጨምረው ገልፀዋል፡፡ “ከጉራፈረዳ ምን ያህል ተማሪዎች እንደተፈናቀሉና በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ የሚያጣራ ቡድን ልከናል” ያሉት አቶ ሸዋንግዛው፤ አጣሪ ቡድኑ ሁኔታውን አጣርቶ ሲመለስ መዐህድ በድጋሚ የአቋም መግለጫ እንደሚያወጣም ተናግረዋል፡፡
“ተማሪዎች የወደፊት አገር ተረካቢ ሲሆኑ አርሶ አደሮችም የአገር ህልውና ምሰሶ ስለሆኑ በአገራቸው የትኛውም ቦታ የመማርና የመስራት መብታቸው ተከብሮ፤ ተማሪዎችም ወደ ትምህርት፣ አርሶ አደሮችም ወደ ስራ ገበታቸው እንዲመለሱ እንጠይቃለን” ብለዋል፤ ፕሬዚዳንቱ፡፡
የአማራ ተወላጆችን ከተለያዩ አካባቢዎች ከማፈናቀል በተጨማሪ የአማራውን ክልል ለማጥበብ ወደ አጐራባች ክልሎች የሚደረገው የመሬት ሽንሸና ዘመቻ በአስቸኳይ እንዲቆም መዐህድ በመግለጫው የጠየቀ ሲሆን በአማራ ህልውና ላይ በተደጋጋሚ እየደረሰ ያለው ስልታዊ እንቅስቃሴ እና ትንኮሳ ሊገታ ይገባል ሲል አሳስቧል፡፡ ሌሎች ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ሲቪል ማህበራትም ይህንን ኢ-ሰብአዊ ድርጊትና መብት ረገጣ እንዲያወግዙ ጠይቋል፡፡

Published in ዜና

          ትግራይ ክልል የማይአይኒ በተባለ ስፍራ የሚገኝ የኤርትራ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ በተቀሰቀሰ ረብሻ የአንድ ሠው ህይወት ከጠፋ በኋላ፣ ተጠያቂ ናቸው የተባሉ ሰዎች እንደታሰሩ ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ ስደተኞች የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በመቃወም ቢሮዎች የሰባበሩ ሲሆን፣ ወደ ጎንደር የሚወስደውም መንገድ ተዘግቶ ነበር፡፡
የረብሻው ምንጭ፣ ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ሲጓዙ ለሞቱ በርካታ ኤርትራውያን የተዘጋጀ የመታሰቢያ ስነ ስርዓት እንደሆነ ምንጮቻችን ጠቅሰው ሻማ በማብራት የተጀመረው የመታሰቢያ ምሽት ወደ ተቃውሞ ረብሻ መቀየሩን አስታውሰዋል፡፡ በካምፑ ውስጥ የተፈጠረው ረብሻ ከቁጥጥር ውጭ ሆኗል በሚል ውሳኔ የፀጥታ ሀይሎች ጣልቃ እንደገቡ ምንጮቹ ጠቅሰው፤ በረብሻውና በግጭቱ የአንድ ሰው ህይወት እንደጠፋ ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) የህዝብ ግንኙነት ተወካይ አቶ ክሱት ገብረእግዚአብሔር፤ በሜዲትራኒያን ባህር ላምፑዱስ የተባለ ደሴት አቅራቢያ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች የሻማ ማብራት ስነ ስርአት እናደርጋለን በሚል የተጀመረው ፕሮግራም ለምን ወደ አመፅ እንዳመራ አናውቅም ብለዋል፡፡ ስደተኞቹ ወደ ጎንደር የሚወስደውን መንገድ እንደዘጉ አቶ ክሱት ጠቅሰው፣ የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እና አብረውን የሚሠሩ የሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ላይ ተቃውሞ ተቀስቅሶ የቢሮ መስኮቶችና በሮች ተሠባብረዋል ብለዋል፡፡ ካምፕ ውስጥ የነበሩና አማራጭ ያጡ ወገኖች በሊቢያ በኩል ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሞክሩ ሞተዋል የሚል ሃሳብ በስደተኞች በኩል እንደተሰነዘረ አቶ ክሱት ጠቁመዋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን፣ በህጋዊ መንገድ ስደተኞችን ቢያጓጉዝ ኖሮ የበርካቶች ህይወት አይጠፋም ነበር በማለት በኮሚሽኑ ቢሮዎች ላይ ጥቃት እንደተፈፀሙ ሰምተናል ብለዋል-አቶ ክሱት፡፡ ስደተኞች ወደተለያዩ አገራት የሚጓጓዙት በኮሚሽኑ ፍላጎት ሳይሆን በተቀባይ አገራት በጎ ፈቃድ ነው ያሉት አቶ ክሱት፤ ኮሚሽኑ ለስደተኞች እንግልት ተጠያቂ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

          በቅርቡ “ኢንተርናሽናል ስታር ፎር ኳሊቲ” የሚል ሽልማት የተሸለመው ኔክስት ዲዛይኒንግ ኢንስቲትዩት ከሌሎች ሀገራት በተለይም ከአፍሪካ ሀገራት የዲዛይኒንግ ተማሪዎች ተቀብዬ ለማስተማር አቅጃለሁ አለ፡፡ ሽልማቱ ዓለም አቀፍ ዕውቅናዬን ይጨምርልኛል ብሏል-ተቋሙ፡፡
ኔክስት ዲዛይኒንግ ኢንስቲትዩት በ1996 ዓ.ም ማስተማር የጀመረ ሲሆን በልብስ ቅድ፣ በልብስ ስፌት፣ በፋሽን እና በተያያዥ ሙያዎች በኮሌጅ ደረጃ እያስተማረ ይገኛል፡፡ ጄኔቭ የሚገኘው ቢድ ቢዝነስ ኢኒሸቲቭ፤ ኔክስት ዲዛይኒንግን የሸለመው ሰባት የጥራት መመዘኛ መርሆዎችን መመዘኛ አድርጐ ሲሆን ከነዚህም አንዱ የደንበኛን ፍላጐት እና ግምት ማርካት ነው፡፡ በርካታ የፋሽን ትርዒቶች በማቅረብም የሚታወቀው ኔክስት ዲዛይኒንግ፤ ተመራቂ ተማሪዎቹን እያወዳደረ ለአጫጭር ኮርስ ሕንድ የሚልክ ሲሆን ገንዘብ ከፍለው መማር ላልቻሉ ወገኖችም የነፃ ትምሕርት ዕድል በማመቻቸት 165 ተማሪዎች እንዳስመረቀ ከኮሌጁ የወጣው መግለጫ ያመለክታል፡፡
የትምህርት ቤቱ ባለቤት እና ሥራ አስኪያጅ ሞዴልና ዲዛይነር ወ/ሮ ሳራ መሐመድ ኦስማን በቅርቡ መሸለማቸውን አስመልክቶ “ሽልማቱ በማበረታታት ለውጥ እንድናመጣ ያደርጋል። ከሌላው ዓለም ጋርም ተወዳዳሪ ያደርገናል። ከኢትዮጵያ ውጪ ተማሪዎች እንድንቀበል ያስችለናል፡፡” ብለዋል፡፡

Published in ዜና

በሽብር ወንጀል የ14 ዓመት እስር ተፈርዶበት በማረሚያ ቤት የሚገኘው የቀድሞው የ“አውራምባ ታይምስ” ጋዜጣ አዘጋጅ ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ መቀመጫውን ደቡብ አፍሪካ ባደረገው ሲኤንኤን “መልቲ ቾይዝ” የሽልማት ድርጅት ተሸለመ፡፡
ጋዜጠኛው ሽልማቱን ያሸነፈው በአፍሪካ የነፃ ፕሬስ ዘርፍ ሲሆን ደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የሽልማት ስነ ስርአት ከአስራ አንድ የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 27 ጋዜጠኞች በተለያዩ ዘርፎች እንደተሸለሙ ታውቋል፡፡
ጋዜጠኛው በእስር ላይ በመሆኑ ባለቤቱ ብርሃን ተስፋዬ እና ልጁ ፍትህ ውብሸት በስፍራው ተገኝተው ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡ ውብሸት በተወዳዳሪነት በቀረበበት ዘርፍ ከፍተኛ ፉክክር እንደነበር የሽልማቱ አዘጋጆች ገልፀው፤ ጋዜጠኛው በ“አውራምባ ታይምስ” ጋዜጣ ላይ በሚሰራበት ወቅት በፀረ - ሽብር ህጉ ተከሶ የ14 አመት እስራት እንደተፈረደበት አስታውሰው፤ ለነፃ ፕሬስ መጐልበት በከፈለው መስዋዕትነት ለሽልማት መመረጡን ጠቁመዋል፡፡

Published in ዜና
  • “በስራ አጥነት ተመዝግባችሁ ተደራጁ” ተብለዋል
  • ዩኒቨርሲቲው በዘረፉ ማስተማሩን ቀጥሏል
  • ተመራቂዎች የሚቀጥረን አጣን አሉ

ከጐንደር ዩኒቨርስቲ በ“ልማትና የአካባቢ እንክብካቤ ጥናት” የተመረቁ ተማሪዎች በመንግስትም ይሁን በግል መስሪያ ቤቶች የስራ መደብ ዝርዝር ውስጥ ባልተካተተ የትምህርት ዘርፍ በመመረቃችን ስራ አጥ ሆነናል ሲሉ አማረሩ። የትምህርት ክፍሉ ሃላፊዎች በበኩላቸው፤ ከፌደራልና ከክልል ሲቪል ሠርቪስ መስሪያ ቤቶች ጋር ተነጋግረን ችግሩን ለመፍታት ጥረት እያደረግን ነው፤ ጥቂት የማይባሉ ተመራቂዎችም ስራ ማግኘት ጀምረዋል ብለዋል፡፡
በ2003 ዓ.ም ከትምህርት ክፍሉ በመጀመሪያ ዲግሪ መመረቃቸውን የሚገልፁት ክብሮም ሃጐስና ጓደኞቹ፤ በትምህርት ክፍሉ ሲመደቡ ጀምሮ ስራ የመቀጠር ዕድል እንደሌላቸው እያወቁ ምርጫ በማጣት ትምህርቱን ለመማር መገደዳቸውን ያስታውሳሉ፡፡ በሶስት አመታት ቆይታቸው ዲፓርትመንቱ በግለሠቦች ይሁንታ መጀመሩን በሚገልፅ መልኩ “የሙሉቀን ልጆች” እየተባሉ ይጠሩ እንደነበር የገለፁት እነ ክብሮም፤ በትምህርት አሠጣጡ ላይ ቅሬታ ያለው ተማሪ ባይኖርም ለአመታት በደከሙበት የትምህርት መስክ ከተመረቁ በኋላ ስራ ማጣታቸው በርካቶችን ተስፋ እንዳስቆረጠ ተናግረዋል፡፡ “በግሌም ሆነ የተማሪዎቹን ጥያቄ ይዤ ለበርካታ ጊዜያት የፌደራል ሲቪል ሠርቪስ ሚኒስቴር ድረስ በመመላለስ በትምህርት መስኩ የስራ እድሎች እንዲፈጠሩ ለመጠየቅ ሞክሬያለሁ” የሚለው ክብሮም፤ እስከዛሬ ግን ምላሽ አለማግኘቱን ገልጿል፡፡
በሃገሪቱ በሚወጡ የስራ ማስታወቂያዎች “በልማትና የአካባቢ እንክብካቤ የትምህርት ዘርፍ የተመረቀ” የሚል የስራ መደብ ማስታወቂያ እስከዛሬ ወጥቶ አያውቅም ያለው ተማሪው፤ በ2004 ዓ.ም የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር በ“ዴቨሎፕመንታል ስተዲስ” የትምህርት መስክ ማስታወቂያ ሲያወጣ ተያያዥነት አለው በሚል ለመመዝገብ ሄደው እንደነበር አስታውሶ፣ “የተመረቃችሁበት የትምህርት መስክ አይታወቅም” ተብለው ማስረጃቸው እንደተመለሰላቸው ገልጿል።
የስራ እድሉን ለማግኘት በአዲስ አበባ ከተማ 114 ወረዳዎች እየዞረ ከቀጣሪ አካላት ጋር መነጋገሩን የሚገልፀው ክብሮም፤ ሁሉም ግን ለትምህርት መስኩ የሚሆን የስራ መደብ እንደሌላቸው መረዳቱን ተናግሯል፡፡ እንደውም በሚኖርበት የካ ክፍለ ከተማ፣ የክፍለ ከተማውን አስተዳደር ባነጋገረበት ወቅት “ለምን በስራ አጥነት ተመዝግባችሁ አትደራጁም” የሚል ምላሽ እንደተሠጠው ገልጿል።
“ከተመረቅንበት ጊዜ ጀምሮ በየእለቱ የሚወጡ የስራ ማስታወቂያዎችን ከጓደኞቼ ጋር ሆነን አንድም ቀን ሣናሣልፍ ስንከታተል ቆይተናል” የሚለው ተማሪው፤ “ተያያዥ ለሆኑ የስራ መስኮች የትምህርት ማስረጃ ስናስገባ በመጀመሪያ አካባቢ ‘ይሄ የትምህርት መስክ አይታወቅም’ እየተባልን ማመልከቻችን ተመላሽ ይደረግ ነበር፤ እየቆየ ግን ማመልከቻችንን ይቀበሉንና በኋላ ያስወጡናል” ብሏል፡፡ በዚህም ምክንያት “የቤተሠቦቻችንን ሃብት አባክነን፣ ተምረን እንዳልተማርን ሆነን መና ቀርተናል” የሚለው ክብሮም፤ በግለሠቦች በጐ ፈቃድ እንደተጀመረ የሚነገርለት የትምህርት ክፍሉ ግን ዛሬም ተማሪዎችን እየተቀበለ ማስተማሩንና ማስመረቁን እንደቀጠለ ገልጿል፡፡
“ልማትና የአካባቢ እንክብካቤ ጥናት” የተባለው የትምህርት መስክ በጐንደር ዩኒቨርስቲ ብቻ እንደሚሠጥና በ1999 ዓ.ም እንደተጀመረ የሚናገሩት ተማሪዎቹ፤ ከ2003 ቀደም ብሎ የተመረቁትም ሆኑ ከዚያ በኋላ የተመረቁት አብዛኞቹ ተማሪዎች ስራ አጥ እንደሆኑ ይገልፃሉ፡፡ አንዳንዶቹም ከትምህርት መስኩ ውጭ ባሉ ስራዎች መሠማራታቸውን ተናግረዋል፡፡
ወደ ትምህርት ክፍሉ ተመድበው በገቡበት ወቅት በተሠጣቸው ማብራሪያ ላይ ከሴቶችና ህፃናት ጉዳይ፣ ከቱሪዝም፣ ከአካባቢ ጥበቃ፣ ከስርአተ ፆታ እንዲሁም ከፖሊሲ ቀረፃ ጋር በተገናኙ የስራ መስኮች ሠፊ የስራ እድል አላችሁ ተብሎ ተነግሮናል ያሉት ተመራቂዎቹ፤ ሆኖም የተባሉት የመንግስትም ሆነ የግል ተቋማት ጀርባቸውን እንደሰጧቸው ይናገራሉ፡፡
የትምህርት ክፍሉ ተጠሪ የነበሩትን አቶ ሲሣይ ምስጋናውን ስለ ጉዳዩ ጠየቀናቸው በሰጡት ምላሽ፤ ችግሩ መኖሩን አምነው፤ ከፌደራል እስከ ክልል ካሉ የሲቪል ሠርቪስ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ችግሩን ለመፍታትና ተመራቂዎች በተማሩበት መስክ የስራ እድል እንዲያገኙ ጥረት መደረጉንና አሁንም ጥረቱ እንደቀጠለ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ “ችግሩ ጐልቶ የሚታየው አዲስ አበባ ባሉ የ2003 ተመራቂዎች ላይ ሲሆን በተቀሩት አመታት የተመረቁ በርካታ ተማሪዎች የትምህት ክፍሉ ባደረገው ጥረት በአማራ፣ በትግራይና በደቡብ ክልሎች የስራ መደብ ተፈጥሮላቸው ተቀጥረው እየሠሩ ነው፤ በአዲስ አበባና በተቀሩት ክልሎች ግን እስካሁንም ለትምህርት መስኩ እውቅና ለመስጠት ማንገራገሮች አሉ” ብለዋል-አቶ ሲሳይ፡፡ በ2002 ዓ.ም የፌደራል ሲቪል ሠርቪስ ሚኒስቴር በሁሉም የክልል መስተዳድሮች በሚገኙ ወረዳዎች ሣይቀር በዚህ የትምህርት መስክ የተመረቁ ስራ ፈላጊዎች የሚሣተፉበት የስራ መደብ ተፈጥሮ ቅጥሮች እንዲከናወኑ የሚያዝ መመሪያ መተላለፉን ያስታወሡት አቶ ሲሣይ፤ መመሪያውን ተግባራዊ ለማድረግ ግን ቸልተኝነት መስተዋሉን ገልፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ የትምህርት ክፍሉ አሁንም ቢሆን ሠፊ የስራ እድል ያለው በመሆኑ አመለካከቱን ለመቀየርና ሁሉም ተመራቂዎች ስራ እንዲያገኙ ለማድረግ ከሚመለከታቸው ባለ ድርሻ አካላት ጋር በሠፊው እየተነጋገሩበት እንደሆነ አቶ ሲሣይ ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የትምህርት ክፍሉ በግለሰቦች በጐ ፈቃድ ነው የተከፈተው የሚባለው ግን አቶ ሲሳይ አይቀበሉትም፡፡ “ዲፓርትመንቱ በዩኒቨርስቲው የተከፈተው ህጋዊ ሆኖ ነው፤ መጀመሪያ የፍላጐት ጥናት (need assesment)፣ ከዚያም የተለያዩ ወርክሾፖች ተካሂደው ነው ወደ ስራ የተገባው” ሲሉም አስረድተዋል፡፡

Published in ዜና
Page 8 of 16