ከ40 በላይ ነዋሪዎች ተነሱ ተብለዋል
ከሃያ አራት አመታት በፊት በይዞታነት የያዝነውና ንብረት ያፈራንበት መኖሪያ ቦታችን ለ40/60 የቤት ፕሮግራም ግንባታ ይፈለጋል በሚል ተገቢው ካሣና ምትክ ቦታ ሳይሰጠን ተነሱ ተባልን ሲሉ የቦሌ ቡልቡላ ወረዳ 12 ቀጠና 5 ነዋሪዎች ቅሬታ አቀረቡ፡፡
ከ40 በላይ የሆኑት እነዚህ ቅሬታ አቅራቢዎች በቦታው ላይ ከ1982 ዓ.ም ጀምሮ መስፈራቸውን፣ ህጋዊ ነዋሪ ስለመሆናቸውም በተለያዩ ጊዜያት ወረዳው ከክፍለ ከተማው እንዲሁም ከከተማ አስተዳደሩ ጋር የተፃፃፋቸው ደብዳቤዎችና ሰነዶች በእጃቸው እንዳለ ለአዲስ አድማስ ገልፀው፤ በ2005 ዓ.ም መጀመሪያ ቦታው ለ40/60 የቤቶች ግንባታ ስለሚፈለግ “ተነሺ ናችሁ” የሚል ማሳሰቢያ ከቦሌ ክ/ከተማ የመሬት ልማት ማኔጅመንት ጽ/ቤት በተደጋጋሚ እንደተላለፈላቸው አስታውቀዋል፡፡
በህጉ መሠረት ተገቢው ምትክ ቦታና ካሣ እስከተሰጣቸው ድረስ ቅሬታ እንደሌላቸው ለከተማ አስተዳደሩ ማሳወቃቸውን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ገልፀው፤ ይሁን እንጂ የወረዳው አስተዳደሮች የአየር ካርታ ላይ ስለሌላችሁ ካሣና ምትክ ቦታ አይገባችሁም የሚል ምላሽ ሰጥተውናል ብለዋል። “እኛ በቦታው ላይ ህጋዊ ነዋሪ መሆናችንን የሚያረጋግጡ የተለያዩ ማስረጃዎች አሉን” የሚሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ግብር የከፈልንባቸውን፣ መብራት እና ውሃ ለማስገባት የተፃፃፍናቸውን ደብዳቤዎች እንዲሁም ወረዳው በተለያዩ ጊዜያት ለከተማ አስተዳደሩ ስለ ህጋዊነታችን የፃፋቸው ሰነዶችን በማስረጃነት ብናቀርብም ተቀባይነት አጥተናል ብለዋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማናጅመንት ጽ/ቤት መስከረም 16 ቀን 2006 ዓ.ም ለቦሌ ክ/ከተማ የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ጽ/ቤት በፃፈው ደብዳቤ፤ “በቀጣይ ተግባራዊ በሚደረግ የደንብ ማስፈፀሚያ መመሪያ መሠረት፤ የተነሺ መብታቸውን ለወደፊት ታሳቢ ያደረገ ውል እየተገባ፣ የልማት ስራው እንዲቀጥል” የሚል ትዕዛዝ ተላልፏል የሚሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ይሄ ከፍተኛ ስጋት አሳድሮብናል ብለዋል፡፡ ጉዳዩ ትኩረት አግኝቶ እንዲጤንላቸውም ከሁለት ጊዜ በላይ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ደብዳቤ መፃፋቸውንና ደብዳቤያቸው ምላሽ አለማግኘቱን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ “ህጋዊ መብታችን ተጥሶ ለአመታት ከኖርንበት ቦታ ያለ አግባብ ልንፈናቀል” ነው ሲሉ ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ተነሺዎቹ ባቀረቡት ቅሬታ ዙሪያ በስልክ አግኝተን ያነጋገርናቸው በቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 12 ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ፀባይ መሸሻ በሠጡን ምላሽ፤ ከ1982 እስከ 1997 ዓ.ም በቦታው በህጋዊነት ያሉት ቀደም ብሎ የወጣው መመሪያ በሚያዘው መሠረት ተገቢውን ካሣና ምትክ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችላቸውን ፎርም እየሞሉ መሆኑን አስታውቀው፣ ከ1997 ወዲህ ያሉት ግን መስተናገድ የሚችሉት በ2003 የተነሣ የአየር ካርታን መሠረት አድርጐ ነው ብለዋል፡፡ በዚህ ማዕቀፍ ለተካተቱት የካሣና የምትክ ቦታ አሠጣጥ ረቂቅ መመሪያ ገና እየወጣ መሆኑን ያመለከቱት ሃላፊው መመሪያው እስኪደርስ ድረስ የልማቱ ስራ መቆም ስለሌለበት ገና የሚወጣውን መመሪያ ታሣቢ ባደረገ መልኩ እንዲነሡ እናደርጋለን ብለዋል፡፡ “እኛም ለህዝቡ ጥቅም የቆምን ነን” ያሉት ሃላፊው፤ ለስራው ስኬታማነት ሲባልም ተነሺዎቹ ያላቸውን አጠቃላይ መረጃ በዝርዝር ያዙ በተባልነው መሠረት እየያዝን ነው ብለዋል፡፡

 

Published in ዜና
Saturday, 12 October 2013 13:34

ዋልያዎቹን እንደማውቃቸው

ዋልያዎቹ በሚል ቅፅል ስያሜያቸው የገነኑት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አባላት ከዓለም ዋንጫ ቢያንስ በ180 ደቂቃዎች ርቀት ላይ ናቸው፡፡ ከስምንት ወራት በኋላ በብራዚል አስተናጋጅነት ለሚደረገው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ለማለፍ በደርሶ መልስ የጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ ዋልያዎቹ ከናይጄርያዎቹ ንስሮች ጋር ይገናኛሉ፡፡ የመጀመርያው ጨዋታ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም ይደረጋል፡፡ ለመሆኑ ከዋልያዎቹ አንዳንዶቹ ከናይጄርያ ጋር ስለሚፋለሙበት ጨዋታቸው ምን ብለዋል?…ማንነታቸው እና የግል ባህርያቸው እንዴት ይገለፃል? በስፖርት ቤተሰቡ ዘንድ የምትታወቀው ኑራ ኢማም ስለዋልያዎቹ የምታውቃቸውን እውነታዎች፤ በተለይ በቅርብ የሚያውቋቸውን እማኝነት እና አስተያየታቸውን አሰባስባ የሚከተለውን ፅሁፍ ለስፖርት አድማስ አቅርባለች፡፡
ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አብረዋቸው በስራ ያሳለፉ ሰዎች በቅድሚያ የሚያነሱት ነገር አለ ቀልደኛነታቸው…በትልልቅ ጋዜጣዊ መግለጫዎች ላይ የሚጠቀሟቸው አነጋገሮች ፈገግታን ያጭራሉ ብለውም ጋዜጠኞች ይመሰክሩላቸዋል፡፡አሰልጣኝ ሰውነት ለተጨዋቾች በሚያወጡላቸው ቅጽል ስሞችም ይታወቃሉ። ለምሳሌ ከቀደሙት የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች አንዱ የነበረውን የቀድሞ የኒያላ፣ ቅ.ጊዮርጊስና የደደቢት ተጫዋች መንግስቱ አሰፋን…ማሲንቆ የሚለውን ያወጡለት ናቸው። በዋልያዎቹ ወሳኝ ሚና ካላቸው ተጨዋቾች አንዱ ለሆነው ለአጥቂው አዳነ ግርማ “ወፍጮ” የሚለውን ስም ሸልመውታል፡፡ አዳነ ስለዚህ ቅፅል ስሙ የሚሰማውን ሲገልጽ መጀመሪያ አካባቢ በጣም እናደድ ነበር አሁን ግን በጣም የምወደው ስም ነው ይላል፡፡

ሌላውን ዋልያ በሀይሉ አሰፋንም የሚገርም ስም አውጥተውለታል፡፡ በሀይሉ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጊዜ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚሰጠውን ማብራሪያ በማየት አፈ-ጉባኤ ብለውታል፡፡ እያዝናኑ መስራቱን ያውቁበታል ፡፡
ጀማል ጣሰው ቡሽራ በፕሪሚዬር ሊግ እና በክለብ ውድድሮች በተደጋጋሚ በሚያጋጥሙት ጉዳቶች ይታወቃል፡፡ በ2002 ዓ.ም የፕሪሚዬር ሊጉ ኮከብ ተጫዋች የነበረው ግብ ጠባቂው ጀማል ጣሰው…ከሩቅ ለሚመለከተው አይን አፋርና ዝምተኛ ሆኖ ይስተዋላል…ከተግባባ እና ከቀረበ በኋላ ደግሞ የሚጥላቸው አማርኛዎች ለየት የሉ ናቸው፡፡ የሰፈረ - ሰላሙ ሰው በቀልድ አዋዝቶ የሚፈልገውን መልእክት ጣል ማድረጉን ተክኖበታል፡፡
ደጉ ደበበ ገብረየስ የዋልያዎቹ አምበል ነው፡፡ ለብሔራዊ ቡድን መጫወት የጀመረው አሁን ካለው ስብስብ ውስጥ ቀደም ብሎ ነው፡፡ ከ10 ዓመታት በላይ አሳልፏል፡፡ የሰውን ሃሳብ መረዳት የሚችል ስብእና አለው፤ ለስራው የሚሰጠው ትኩረት እና ታዛዥነቱ ብዙዎቹ ያመሰግኑታል። ተግባቢና ሰው አክባሪ ነው፡፡ ስለ ተጋጣሚያቸው ናይጄርያ ሲናገር ‹‹ናይጀሪያን ለማሸነፍ ትኩረት ሰጥተን እየሰራን ነው፡፡ እነሱም ቢሆኑ ከ2012ቱ አፍሪካ ዋንጫ እኛ እንዳስቀረናቸው የሚረሱት አይመስለኝም›› ብሏል፡፡
አይናለም ሃይለ ረዳ አዲግራት እያለ ኳስን የጀመረው በሚሰራበት ፕሮጀክት በግብ ጠባቂነት በመሰለፍ ነበር። በልጅነቱ ቁጡና ሃይለኛ ነበር አሁንም በስራው ላይ ይህ ኮስታራነቱ እንደቀጠለ ነው፡፡…ትልቁ ነገሩ ግን ተነጋግሮ ይግባባል፤ ከዛ ውጪ ባለው ህይወቱ የቀረበውን ለማስጠጋት ችግር የለበትም፡፡ በትንሸ ነገር ቢናደድም ቂመኛ ግን አይደለም፡፡ ከኳሱ ጐን ለጐን ንግዱንም እያስኬደ ነው፤ የአንድ ልጅ አባትም ነው፡፡
ስዩም ተስፋዬ ሞገስ በብሄራዊ ቡድን የቀኝ የተከላካይ መስመር ሃላፊነት ተጥሎበታል፡፡ ሰውን እስኪግባባ ተቸጋሪ ነው ፡፡ ቀድመው ከቀረቡት ግን የሚከብድ ሰው አይደለም፡፡ ሁሌም የተረጋጋ ስፍራን ይመርጣል፡፡ ወከባን ነፍሱ ትጠላለች…ለቀለደው ይቀልዳል ቁም ነገር ላወራው ያወራል…አስተያየት ከመስጠቱ በፊት ቁጥብነትን ያበዛል…ጥንቃቄውም ለጉድ ነው…ከቡድኑ ልጆች ጋር ግን ጥሩ ግንኙነት አለው፡፡ ወደፊት በበጐ አድራጐት ጉዳዮች ላይ የመሳተፍ ፍላጐት እንዳለው ይናገራል፡፡ ድክመቱን በአግባቡ ለሚነገረው ማንም ሰው ቅድሚያ ይሰጣል፡፡ ስለ ወሳኙ ጨዋታ በሰጠው አስተያየት ‹‹…ለናይጀሪያ ብለን ልዩ ስራ አንሰራም ጥሩ ነገር እንጠብቃለን ፡፡›› ብሏል፡፡
አበባው ቡጣቆ ቡኔ ኳስን መጫወት የጀመረው አሁን በሚሰለፍበት የተከላካይ መስመር ነው፡፡

ቶሎ ተናዳጅ ነው፤ ብዙም የመጨነቅ ነገር አይሆንለትም፡፡ ህይወትን ቀለል አድርጐ መግፋት ይፈልጋል፡፡ ከእሱ ጋር ግን ለመግባባት መጀመሪያ መጨረሻ የሚባል ነገር የለም ቀለል አርጐ ይቀርባል…ሙዚቃ ይወዳል ለአሰልጣኝ ትእዛዝ ግን ጆሮ ይሰጣል…ከስራው ውጪ መዝናናት ይወዳል …ግልጽነትም መለያው ነው፡፡
አስራት መገርሳ ጐበና አስቸጋሪ የህይወት ውጣ ውረዶችን ያስተናገደ ጠንካራ ሰው ነው ፡፡ በግሉ ያያቸው ነገሮች አስተማሪዎቹ ሆነዋል ቀልደኛና ተግባቢ ነው። በዕምነቱ ጠንከር ያለ አቋም አለው፡፡ ቁመቱ ረጅሙ ተጫዋች…ሚስጥር ማፈኑን ያውቅበታል ይሉታል፡፡ በቡድኑ አባላትም ተወዳጅ ነው፡፡ እርስ በእርስ በመቀላለድም ዋናው ተዋናይ ነው፡፡ የዋልያዎቹ ስብስብ በጨዋታ እና እየሰሩ በመዝናናት ተወዳዳሪ እንዳልተገኘለት ብዙዎቹ ይናገራሉ፡፡
አዲስ ህንፃ ተክሌ በክረምቱ ዝውውር የሱዳኑን አል ሂላል ሸንዲ ተቀላቅሏል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ መልከመልካም ከተባሉ አማላይ ተጨዋቾች መካከል ሶስተኛ ደረጃን አግኝቷል፡፡ በዚሁ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ከዛምቢያ ጋር በተደረገው የምድቡ መክፈቻ ጨዋታ ላይ ኮከብ ተብሎም ነበር፡፡ ግድየለሽ እና ብዙም የንግግር ችሎታ ከማይሆንላቸው የዋልያዎቹ አባላት ውስጥ ይመደባል፡፡ የዋህ ነው ፡፡ላመነበት ነገር ስለ ማንም የማይጨነቅ ቀጥተኛ ተናጋሪ ነው፡፡ በጣም ለቀረበው እና ለወደደው ደግሞ ጆሮ ይሰጣል፡፡ እሱም ጭንቃ ጭንቅ ነገር አይመቸውም፡፡ …ብሶት የሚያበዛን የቡድን አጋር በማብሸቅ ደግሞ የሚያክለው የለም፡፡
ሽመልስ በቀለ ጐዶ ከዋልያዎቹ መካከል ለጐል ምቹ የሆኑ ኳሶችን በማቀበል ፤ የመሃል ሜዳ ሞተር ሆኖ ቡድኑን በማንቀሳቀስ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፡፡ ከፊቱ ላይ ፈገግታ አይታጣም፤ ሳቂታና ደስተኛም ነው፡፡ በየጨዋታው ከመሳተፍ ይልቅ በጓደኞቹ መቀላለድ ይደሰታል፡፡ ያልገባውንም ይጠይቃል፡፡ ብዙ ከማውራት ለማዳመጥ ትኩረት ይሰጣል፡፡
ከናይጄርያ ጋር ስለሚደረገው የዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ የሚያስበውን ሲገልፅ ‹‹ባለፈው አመት የኛ ነበር፡፡ ዘንድሮም ይደገማል፡፡›› ብሏል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሊቢያው ክለብ አልኢትሃድ የሚጫወተው ሽመልስ በዚሁ ክለብ የሚጫወት ናይጄርያዊ ስለ ዓለም ዋንጫው የጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ እየጠየቀ አላስቀምጥ ብሎት መሰንበቱን ሲናገር ምላሹ አሁን ምንም መናገር አልፈልግም የሚል ነበር። ሙያ በልብ ነው፡፡
ምንያህል ተሾመ በየነ በዋልያዎቹ አስደናቂ ታሪክ ውስጥ ከብዙዎች አዕምሮ በማይጠፉ ክስተቶች ትኩረት የሳበ ነው፡፡ ሁለት የቢጫ ካርድ ቅጣት እያለበት ከቦትስዋና ጋር በተደረገው ጨዋታ ተሰልፎ ብሄራዊ ቡድኑ 3 ነጥብ ለተቀነሰበት ጥፋት ምክንያት መሆኑ የመጀመርያው ነው። ሌላው ደግሞ በምድብ ማጣርያው የመጨረሻ ጨዋታ ላይ በኮንጐ ብራዛቪል ወሳኟን የማሸነፊያ ጐል ከመረብ በማዋሃድ ታሪክ ሰሪ ሆኖ ጥፋቱን ያረመበት ነው። ምንያህል ተረበኛና ቀልደኛ ነው፡፡

ትንሽ የመነጫነጭ ባህርይ ቢኖረውም እያዝናና ስሜቱን በመናገር ይታወቃል። በብሄራዊ ቡድን ሲጫወት ለውጤታማነት በሚከፍለው መስዋትነትና ያልተቆጠበ ጥረት በአሰልጣኙ እንዲወደድ አድርጐታል፡፡ ምንያህል ለመጀመሪያ ጊዜ ለብሔራዊ ቡድኑ የተሰለፈው ከአራት ዓመት በፊት በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ከናይጄሪያ ጋር በተደረገው የመልስ ግጥሚያ ነበር፡፡ ያንግዜ ዋልያዎቹ በናይጄርያ ሜዳ 4ለ0 በሆነ ውጤት በንስሮቹ መሸነፋቸው ይታወሳል፡፡ ዘንድሮ ግን ናይጄርያን ጥለን በማለፍ በዓለም ዋንጫ ከስፔንና አርጀንቲና ጋር መጫወት እንፈልጋለን እያለ ነው፡፡
አዳነ ግርማ ገ/የስ አትዮጵያ ከ31 ዓመታት በኋላ ወደራቀችበት አህጉራዊ ውድድር በመመለስ በ29ኛው አፍሪካው ዋንጫ ላይ በተሳተፈችበት ወቅት ብቸኛዋን ጎል ለብሄራዊ ቡድኑ በማስቆጠር ታሪክ ሰርቷል፡፡ በዚሁ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በደረሰበት ጉዳት ግን ያለፉትን ወራት ሁኔታዎች ለሱ መልካም አልነበሩም፡፡ ከጉዳቱ ለማገገም ረጅም ጊዜ ቢፈጅበትም አሁን ግን ወደ ቀድሞ አቋሙ በመመለስ በጥሩ ብቃት ላይ እንደሚገኝ ይናገራል፡፡ የቡድኑ አዝናኝ እንደሆነ የተመሰከረለት አዳነ ጨዋታ አዋቂ ነው። በአጨዋወቱም በማንኛውም ቦታ በመሰለፍ ለቡድኑ አስተዋፅኦ ለማበርከት ቅሬታ የለውም፡፡ ከግብ ጠባቂ እስከ አጥቂ መስመር መጫወትን ለምዶታልና… በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ወቅት ዋልያዎቹ ደቡብ አፍሪካ ላይ መንገድ ሰይመውለት ነበር ፡፡ በዚያች አገር ብዙ ሰው ስለማውቅና ወንድሜም ስለሚገኝ አገር ምድሩን ሳሳያቸው ስለነበር ነው መንገድ የሰየሙልኝ ይላል፡፡ ወፍጮ በሚል በአሰልጣኝ ሰውነት የወጣለትን ቅጽል ስሙንም ይወደዋል። ስለ አሰልጣኝ ሰውነትን ሲናገር ደግሞ እንድትታዘዘው የሚያረግ አሰልጣኝ ነው ብሏል፡፡ ‹‹ተጋጣሚያችን በቁጥር ከኛ የተሻለ ነው ግን አሁን ጭንቀቱ ከኛ ይልቅ የእነሱ ነው›› በማለት በናይጄርያው የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ ዙርያ የተሰማውን ተናግሯል፡፡
ሰለሃዲን ሰኢድ አህመድ ለዋልያዎቹ ወሳኝ ጎሎችን በተለይም በመጀመሪያዎቹ የምድብ ማጣሪያዎች ላይ በተከታታይ በማስቆጠር ወሳኝነቱን አስመስክሯል። ሰለሀዲን ሰኢድ ለቡድን አጋሮቹ የህይወት ልምዱን በቅንነት ያካፍላል፤ ምክሩንም ይለግሳል፡፡ ብዙ ማውራት ባይሆንለትም ከሁለት ቋንቋዎች በላይ ተናጋሪ ነው፡፡ ላገኘው ሁሉ ተገቢውን አክብሮት ይሰጣል፡፡ ቀደም ሲል ስለ ልምምድ የነበረው ግንዛቤ ወጥቶ መጫወት ከጀመረ በኋላ ተቀይሮአል፡፡ በግብፁ ዋዲ ዳግላ ክለብ ስር የሚገኘው ሳላ ዝምታን ያበዛል፡፡ ስለ ናይጄርያው ትንቅንቅ ሃሳቡን ለሱፐር ስፖርት ሲሰጥ “እናከብራቸዋለን እንጂ አንፈራቸውም…እነሱም ለእኛ ንቀት ማሳየት የለባቸውም ጠንቅቀው ያውቁናል ስለዚህ በግባቡ ስራችንን ጠንክረን እየተዘጋጀን ነው›› ብሏል፡፡
ጌታነህ ከበደ ጊቤቶ የዲላው ተወላጅ …የእግር ኳስ ሂወቱ ፈጣን ነው በ2001 ዓ.ም እውቅና የሰጠው ሂደቱ አሁንም ወደ ማንዴላዋ ሀገር ደቡብ አፍሪካ አሻግሮት ቢድቪስት ዊትስ ለተባለ ክለብ እየተጫወተ ነው፡፡ጐሎችንም እያስቆጠረ ነው፡፡ ከመካከለኛው አፍሪካ ጋር በነበረው ጨዋታ ባጋጠመው ድንገተኛ ጉዳት ባለመሳተፉ ክፉኛ ማዘኑን ቢገልጽም ለውጤቱ መገኘት የቡድን አጋሮች ባደረጉት ርብርብ ኮርቷል፡፡ ከእሱ ጋር ረዘም ያለ ወሬ ለማውራት ጥሩ የርእስ ፈጠራ ክህሎት ያስፈልጋል፡፡ አይን አፋርነቱ ቀደም ሲል ያጠቃው ነበር አሁን ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተለወጠ መጥቷል፡፡ ልክ እንደ አይናለም ሁሉ እሱም ኳስ መጫወት ሲጀምር በግብ ጠባቂነት ነበር፡፡ በስብስቡ ውስጥ ግን የጨዋታ ፈጠራ ባይሆንለትም ቀልዱም ላይ ብቅ ይላል፡፡

ለቅርብ ወዳጆቹ ግልጽነቱ አንዱ መገለጫ ባህሪው ነው ፡፡
በሀይሉ አሰፋ ጐበዜ ዋልያዎቹ ገደኛው ይሉታል። ተቀይሮ በገባባቸው ግጥሚያዎች ጐል ባያስቆጥርም እንዲቆጠር ምክንያት ሲሆን በተደጋጋሚ በማጋጠሙ ነው። የበርካታ ቅጽል ስሞች ባለቤት ነው ቱሳና ዶክተር ከነዛ መካከል ይገኝበታል፡ ወደ ቀለም ትምህርቱ ያመዝናል። ነገርን አብራርቶ መግለጽ ይችልበታል፡፡ ማንም ለሚጠየቀው ጉዳይ ምላሹን ከነማብራሪያው ይሰጣል፤ ቁም ነገሩ ያመዝናል…ሰው አክባሪም ነው …በቡድኑ የዲፕሎማትነት ባህርይም አለው …ለተረቡም ጆሮው ክፍት ነው የማህበራዊ ህይወት ግንኙነቱ ጥሩ ነው፡፡ ስብሰባ ላይ ሃሳቡን በሚፈልገው መንገድ የመግለጽ ፍርሃት የለበትም፡፡ ለጠቅላላ እውቀት ግንዛቤም ቅርብ ነው፡፡
ሲሳይ ባንጫ ባሳ ለብሄራዊ ቡድኑ የሳቅ ምንጭ የሆነ ወሳኝ ሰው ነው፡፡ ደስታውንም መከፋቱንም ለመግለጽ ቦታ እና ጊዜ አይመርጥም፡፡ ሰው ምን ይለኛልም እሱ ጋር ቦታ የለውም፤ በቃ…ማድረግ ያለበትን ከማድረግ ወደኋላ አይልም፡፡ አንዳንዶች ስሜታዊ ይሉታል፡፡ ቶሎ መናደድ እንደገና መቀዝቀዝ ባህርይው ነው፡፡ በቡድኑ ጭፈራና ልዩ ድምጽ ሲያስፈልግ የሚጋበዘው እሱ ነው፡፡ መለያ ምት በማዳን ብቃቱም ይደነቃል፡፡
ብርሃኑ ቦጋለ ቦይዛ ለብሔራዊ ቡድን መጫወት የጀመረው በ1998 ዓ.ም ነበር፡፡ ዝምታን ያበዛል ረጋ ያለ ነው፤ በጣም ካልቀረቡት ላይረዱት ይችላሉ፡፡ የኳስ ሜዳው ልጅ የንግግር ችግር ባይኖርበትም ብዙ ከመናገር የተቆጠበ ነው፡፡ ቀለል ያለ ቀረቤታ ይስማማዋል፡፡ ተገቢውን አክብሮ መስጠቱ ላይ እሱም የተካነ ነው፡፡ የሚዲያ ሰው አይደለም ግን ከተጠየቀ ለትብብሩ ቀና ምላሹን ይሰጣል፡፡

         ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ከአፍሪካ የሚወከሉትን አምስት ቡድኖች ለመለየት አሥሩ ቡድኖች የጥሎ ማለፍ ትንቅንቃቸውን በመጀመርያ ጨዋታቸው ዛሬ እና ነገ ይጀምራሉ፡፡ በአፍሪካ ዞን ከሚደረጉት አምስት የጥሎ ማለፍ ትንቅንቆች በተለይ ኢትዮጵያ እና ናይጄርያ የሚገናኙበት ፍጥጫ ከፍተኛ ትኩረት እንደሳበ ነው፡፡ በሌሎች ጨዋታዎች ጋና ከግብፅ፤ አይቬሪኮስት ከሴኔጋል፤ ቡርኪናፋሶ ከአልጄርያ እንዲሁም ቱኒዚያ ከካሜሮን ይገናኛሉ፡፡ የኢትዮጵያ እና የናይጄርያ ጨዋታ ትኩረት የሳበው ያለምክንያት አይደለም፡፡ በሁለቱ አገራት ብሄራዊ ቡድኖች መካከል ያለው የእግር ኳስ ደረጃ ልዩነትን በማነፃፀር በሚሰጡ ግምቶች፤ የዓለም ዋንጫ ውድድር እንደኢትዮጵያ አይነት በእግር ኳስ ዝቅ ያለ ደረጃ የሚገኝ ቡድንን ለማሳተፍ በፈጠረው እድል አጓጊነት እና በሌሎች ምክንያቶች የሁለቱ ቡድኖች ግጥሚያ ዓለም አቀፍ ትኩረትን ስቧል፡፡

ሰሞኑን በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የፊፋ ታዛቢ ሆነው የተገኙት የታንዛኒያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት፤ የመካከለኛውና ምስራቅ አፍሪካ የእግር ኳስ ምክር ቤት ሴካፋ ፕሬዝዳንት እና የካፍ ስራ አስፈፃሚ አባል የሆኑት ሚስተር ሊዮዳር ቴንጋ ‹ ምስራቅን ብቻ ሳይሆን ደቡባዊውን የአፍሪካ ዞን የወከለችው ኢትዮጵያ ናይጄርያን በማሸነፍ ለዓለም ዋንጫ እንድታልፍ እየፀለይኩ ነው› በማለት ተናግረዋል፡፡ ሚስተር ሊዮዳር ቴንጋ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እያስመዘገበ ባለው ውጤት ልትኮሩ ይገባል በማለትም ለጠቅላላ ጉባኤው አባላት ማበረታቻ ሰጥተዋል፡፡ የወቅቱ የአፍሪካ ሻምፒዮን የሆነችው ናይጄርያ ለዓለም ዋንጫ የምታልፍበትን ትኬት ኢትዮጵያን በማሸነፍ ትቆርጣለች ብለው የተማመኑት የናይጄርያው ፕሬዝዳንት ጉድላክ ጆናታን በበኩላቸው ነገ ለሚደረገው የመጀመርያ ጨዋታ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲሰጡ ለ200 ደጋፊዎች ቻርተር በረራ መፍቀዳቸው ታውቋል፡፡
ታዋቂው የእግር ኳስ ድረገፅ ጎል ስፖርት እንደገለፀው ኢትዮጵያ ከናይጄርያ የሚገናኙበት የዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ትንቅንቅ በንፅፅር ሲታይ የዳዊት እና የጎልያድ ፍጥጫ ነው፡፡ ይህንንንም በተለያዩ ንፅፅሮች ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ በትራንስፈርማርኬት ድረገፅ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአጠቃላይ ስብስቡ 23 ተጨዋቾችን ከእነሱ መካከል 5 ፕሮፌሽናሎችን አስመዝግቦ በዝውውር ገበያ 775ሺ ፓውንድ ዋጋ እንዳለው ሲገመት የናይጄርያ አቻው በ24 ተጨዋቾች ስብስቡ 18 ፕሮፌሽናል ተጨዋቾችን አስመዝግቦ የተተመነው 58.5 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ውዱ ተጨዋች የተባለው ሰለሃዲን ሰኢድ በትራንስፈር ማርኬት የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 300ሺ ፓውንድ ሲሆን በአንፃሩ የናይጄያ ውድ ተጨዋች የሆነው ጆን ኦቢ ሚኬል 19.5 ሚሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በኢንተርናሽናል ውድድሮች የ321 ጨዋታዎች ልምድ ያለው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አማካይ እድሜው 25.20 ሲሆን ከ361 በላይ ጨዋታዎችን በማድረግ ልምድ ያስመዘገበው የናይጄርያ ብሄራዊ ቡድን ደግሞ 24.10 ነው፡፡
ኢትዮጵያና ከናይጄርያ ከነገው ጨዋታ በፊት በታሪካቸው በ7 ግጥሚያዎች ተገናኝተዋል፡፡ አምስቱን ያሸነፈችው ናይጄርያ ስትሆን ኢትዮጵያ አንድ ጊዜ አሸንፋ ፤ በአንድ ጨዋታ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ሁለቱ ቡድኖች በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ የተገናኙት በ1982 እኤአ ሊቢያ ባስተናገደችው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነበር፡፡ በወቅቱ ናይጄርያ 3ለ0 ስታሸንፍ ሁለቱን ጎሎች አሁኑ የብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ የሆነው ስቴፈን ኬሺ ሲያስቆጥር ሌላኛዋን ጎል ያስመዘገበው አዴሞላ አዴሺና የተባለ ተጨዋች ነበር፡፡

ሁለቱ ቡድኖች ለሁለተኛ ጊዜ የተገናኙት ደግሞ በወዳጅነት ጨዋታ በ1993 እኤአ አዲስ አበባ ላይ ሲሆን 1ለ0 ያሸነፈችው ናይጄርያ ነበረች። ከዚህ በኋላ ደግሞ በ1994 እኤአ ላይ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ የመጀመርያ ግጥሚያ ላይ በአዲስ አበባ ሲገናኙ ኢትዮጵያ በወቅቱ ከባድ የነበረውን የናይጄርያ ቡድን 1ለ0 አሸንፋለች፡፡ በመልሱ ጨዋታ ግን ለአራተኛ ጊዜ ሲገናኙ ናይጄርያ በሌጎስ 6ለ0 ማሸነፏ የሚታወስ ሲሆን ግዙፉ አጥቂ ራሺዲ ያኪኒ በዚያ ጨዋታ ሃትሪክ ሰርቶ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ እና ናይጄርያ ለአምስተኛ ጊዜ የተገናኙበት ጨዋታ በ2012 እኤአ ላይ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ አዲስ አበባ ላይ ሲደረግ ነበር፡፡
በዚህ ጨዋታ ላይ 2ለ2 አቻ ሲለያዩ ለኢትዮጵያ ሁለት ጎሎችን ሳላዲን ሰኢድ አስቆጥሮ እንደነበር ሲታወስ ለናይጄርያቸ ደግሞ ኡቼ እና አምበሉ ጆሴፍ ዮቦ አስቆጥረዋል፡፡ በዚሁ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ የመልስ ጨዋታ በአቡጃ ለስድስተኛ ጊዜ በተገናኙበት ወቅት ደግሞ በሳምሶን ሲያ ሲያ የሚሰለጥነው የናይጄርያ ቡድን 4ለ0 በሆነ ውጤት ኢትዮጵያን አሸንፎ ነበር፡፡በወቅቱ በኢትዮጵያ ላይ አራቱን ጎሎች ያስቆጠሩት እያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ጎሎች ያስቆጠሩት ፒተር ኡታካ እና ኢኬ ኡቼ ናቸው፡፡

ይሁንና በመጀመርያው ጨዋታ በአዲስ አበባ አቻ የተለያየበት ጨዋታ ዋጋ አስከፍሎት ለአፍሪካ ዋንጫ ሳያልፍ ቀርቶ ለአሰልጣኙ መባረር ምክንያት የነበረ ውጤት እንደነበር ይታወሳል። ኢትዮጵያ እና ናይጄርያ ነገ በታሪክ ለስምንተኛ ጊዜ ከመገናኘታቸው በፊት በሰባተኛ ጨዋታቸው ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት ኢትዮጵያ ከ31 ዓመታት መራቅ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ተሳትፏዋን ባገኘችበት የደቡብ አፍሪካው 29ኛው አፍሪካ ዋንጫ ላይ ነበር፡፡
በደቡብ አፍሪካ ከተማ ሩስተንበርግ ተደርጎ በነበረው የ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ 3 የመጨረሻ ጨዋታ ላይ የሁለቱ ቡድኖች ትንቅንቅ እስከ 81ኛው ደቂቃ ያለምንም ግብ አቻ ነበር። ነገር ግን በመጨረሻዎቹ የጨዋታ ክፍለጊዜዎች በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች በተሰሩ ሁለት ጥፋቶች ሁለት የፍፁም ቅጣት ምቶች ለናይጄርያ ተገኙ፡፡ ሁለቱንም ኢሊጎሬዎች ቪክተር ሞሰስ አግብቶ 2ለ0 ድል በማድረግ ናይጄርያ እስከ ሻምፒዮናነት ለመገስገስ ችለዋል፡፡

            ዶ/ር ዎድሮስ አድሀኖም በኢፊድሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባለፈው ሳምንት የተጠናቀቀውን የፊጎ አፍሪካ የመጀመሪያ አህጉራዊ ስብሰባ በዘጉበት ወቅት የተናገሩትን አባባል ነበር ለርእስነት የመረጥነው፡፡ ከ67/ አገራት የተውጣጡ ወደ ስምንት መቶ የሚሆኑ ተሳታፊዎች የታደሙበት ስብሰባ ሲጠናቀቅ ዶ/ር ዎድሮስ የስብሰባውን በስኬት መጠናቀቅና የአባላቱን ጥረት ካደነቁ በሁዋላ ወደምእተ አመቱ የልማት ግብ ስኬት ነበር ንግግራቸው ያመራው፡፡
እ.ኤ.አ እስከ 2015/ዓም አለም እንድትከውናቸው የሚፈለጉ ግቦች በስምንት የተከፈሉ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ቁጥር 4/ ከአምስት አመት በታች ያሉትን ልጆች ሞት መቀነስ ሲሆን ቁጥር 5/ ደግሞ የእናቶችን ጤና ማሻሻል የሚል ነው። የልጆችን ሞት መቀነስ የሚለው ስሌት 2/3ኛ ያህል ሲሆን በዚህም በኢትዮጵያ ጥሩ ውጤት እንደተመዘገበና የእናቶች ሞት ደግሞ በ3/4ኛ እንዲቀንስ ጥረት በመደረግ ላይ ቢሆንም እስከአሁን ግን ከትክክለኛው መስመር ላይ አለመደረሱን ዶ/ር ዎድሮስ አድሀኖም ተናግረዋል፡፡
የኢትዮያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበርመሑሀ ፣የአፍሪካ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህራት ፌደሬሽንሑሀ፣ የአለም አቀፉ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበራት ፌደሬሽንህሀሑ እና የመሳሰሉት የህክምና ባለሙያዎች ማህበራት ሐገር እንዲሁም ህብረተሰቡ ብዙ እንደሚጠብቅ አውቀው በቀረው ጊዜ አስፈላጊውን እርብርብ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል ዶ/ር ዎድሮስ አድሀኖም፡፡
የምእተ አመቱን ግብ ለመምታት እንደ ዶ/ር ዎድሮስ ማብራሪያ ሙያው ሊተገበር የሚችልበትን ዘዴ አሟጦ መጠቀም ተገቢ ነው፡፡ የህክምናው አገልግሎት እና እርዳታ ፈላጊ እናቶች የሚገናኙበ ትን ዘዴ በተገቢው መቀየስና በቅያሱ መሰረት እዚህ ቀረሽ ሳይባል ማከናወን ከተቻለ ከሚጠበቀው ግብ መድረስ ቀላል ነው፡፡
በኢትዮጵያ የእናቶችን ሞት ከመቀነስ አኩዋያ እንደጥሩ ምሳሌ የሚቆጠረው በትብብር የመስራት አቅምን ማጎልበት ነው፡፡ ከዚህም አኩዋያ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር ከፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስር ጋር በመተባበር በተለይም ከዋና ከተሞች ራቅ ባሉ ስፍራዎች የሚገኙ ሐኪሞችን የማሰልጠን ስራ እየሰራ መሆኑ ብዙ ችግሮ ችን ለማቃለል አስችሎአል፡፡ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያዎች ቁጥር ከተጠቃሚው ሕብረተ ሰብ ቁጥር ጋር የማይነጻጸር ቢሆንም የጠቅላላ ሐኪሞችን እና በተመሳሳይ በገጠር ሆስ ፒታሎች የሚገኙ የህክምና ባለሙያዎች ትምህርቱን በስልጠና በማግኘታቸው አፋ ጣኝ የሆነ ውን የማዋለድ ስራ በቀዶ ሕክምና ጭምር እያገዙ ውጤ ታማ የሆነ ስራ እንዲሰራ በማስቻሉ የሚበረታታ እና የሚመሰገን ተግባር ነው ብለዋል ዶ/ር ዎድሮስ አድሀኖም የኢፊድሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፡፡
በስተመጨረሻም ዶ/ር ዎሮስ እንደአሉት አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን የመላው አፍሪካም ጭምር ከተማ በመሆንዋ የአፍሪካ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህራት ፌደሬሽን ጽ/ቤቱን በአዲስ አበባ ለመክፈት ቢፈልግ የኢትዮጵያ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ሊያደርግ ይችላል ፡፡
የፊጎ አፍሪካ የመጀመሪያው ስብሰባ በተካሄደባቸው ቀናት ከመስከረም 22-25 ድረስ የስብ ሰባው ተሳታፊዎች በከተማዋ በተለያዩ ቦታዎች ለጉብኝትና ለግብይት የተንቀሳቀሱ ሲሆን ከእነዚህም መሀከል ሐምሊን ኢትዮጵያ ፊስቱላ ሆስፒታል አንዱ ነበር፡፡ ጎብኝዎች በየቀኑ በአንድ ጊዜ አርባ ያህል እየሆኑ እንደፍላጎታቸው ይጎበኙ የነበረ ሲሆን የአንዱን ቡድን ጉብኝት የዚህ አምድ አዘጋጅ ተሳትፋለች፡፡ በጉብኝቱ ወቅት ሐምሊን ኢትዮጵያ ፊስቱላ ሆስፒታል ማለት ማን እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን አንባቢ ዎችም እንዲያስታውሱት ያህል በመጠኑ ቀንጨብ እናደርጋለን፡፡
ሐምሊን ኢትዮያ ፊስቱላ ሆስፒታል የተቋቋመው የዛሬ 53/ አመት ገደማ ባልና ሚስቱ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ዶ/ር ሄግ እና ካትሪን ሐምሊን በቀየሱት ዘዴ መነሻ ነት ነው፡፡ እነዚህ ባልና ሚስት ወደኢትዮጵያ ለስራ በመጡበት ወቅት ከስራቸው ጎን ለጎን ሁኔታዎችን ሲመለከቱ በኢትዮያ ብዙ በፊስቱል የተጎዱ ሴቶች በቂ ሕክምና እና ድጋፍ ሳያገኙ እንደሚቀሩ እና ምን ያክል በቤተሰቦቻቸው መገለል እንደሚደርስባቸው በመመልከታቸው እነዚህን ሴቶች መደገፍ ይገባናል ሲሉ ይወስናሉ፡፡ ከዚህም መነሻነት ሆስፒታሉ አገልግሎቱን እያስፋፋ በአሁኑ ወቅት በአምስት መስተዳድሮች ቅርንጫፎችን በመክፈት እናቶች በአቅራቢያቸው ሳይንገላቱ እንዲታከሙ ማድረግ ችሎአል።

የፊስቱላ ሆስፒታል ቅርንጫፍ የሚገኝባቸው አካባቢዎችም መቀሌ ፣ይርጋለም ፣ሐረር ፣ባህርዳር እና መቱ ናቸው፡፡
ሐምሊን ፊስቱላ ሆስፒታል ሕመማቸው ለጠናባቸው እና ታክመው ወደቤተ ሰቦቻቸው መመለስ ለማይችሉት እንዲሁም ከህክምናው መራቅ የሌለባቸውን ሴቶች የተለያየ ስልጠና እየሰጠ ስራ ሰርተው እንዲተዳደሩ የሚችሉበት ከአዲስ አበባ 17/ኪሎ ሜትር ታጠቅ ከሚባለው አካባቢ የደስታ መንደር በሚል ስያሜ አንድ ትልቅ መንደር ከፍቶ እንዲያገግሙ የማገገሚያ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡
የፊስቱላን ሕመም ለመከላከል እንዲቻልም እያንዳንዱዋ እናት በተማረ የሰው ኃይል አማካኝነት ካለችበት አካባቢ ሳትርቅ በሕክምና እየተረዳች ልጅ እንድትወልድ ለማስቻል የሚረዳ አንድ ኮሌጅ በመክፈት አዋላጅ ነርሶችን በማስተማር በዲግሪ እያስመረቀ ይገኛል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሌሎች ባለሙያዎችንም በስልጠና ያግዛል፡፡
ከጎብኝዎች የተገኘውን አስተያየት ወደ አማርኛ መልሰን ለአንባቢዎች እንላለን፡፡
“...እኔ ታቦኒ እባላለሁ፡፡ የመጣሁት ከኒውዝላንድ ነው። ዜግነ ግን ዚምባቡዌ ነው፡፡ እንደሐምሊን ኢትዮጵያ ፊስቱላ ሆስፒታል አይነት አገልግሎት የትም ሐገር ሄጄ አላጋጠመኝም፡፡ እንደዚህ አይነት አገልግሎት የሚሰጥበት ተቋም እስከአሁን ድረስ አላየሁም፡፡ እጅግ አስደሳች ነው፡፡ ልክ በታሪክ የማዳምጠው እንጂ በዚህ ጊዜ በአይኔ የምመለከተው አልመሰለኝም፡፡ ለእኔ ብዙ ሀሳብ ሰጥቶኛል፡፡ የጽንስና ማህጸን ሕክምና ባለሙያ እንደመሆኔ ይህ አይነት አገልግሎት በሀገሬ ዚምባቡዌ እንዲሰጥ የበኩሌን እጥራለሁ...”
                                            -----///------
“...እኔ ኢማን አቡጋጃ እባላለሁ፡፡ በዜግነት ሱዳናዊት ስሆን የምሰራው ግን በዩኬ ነው፡፡ እኔ በሕይወ ካየሁዋቸው ተቋማት የሚበልጥ በጣም አርኪ የሆነ ስራ የሚሰራበት ግሩም ሆስፒታል ነው፡፡ ለእናቶች አገልግሎት የሚሰጡ እንደዚህ ያሉ የህክምና ተቋማት በአፍሪካ በብዛት ቢኖሩ ኖሮ ለብዙዎች መፍትሔ በሆነ ነበር፡፡ የእናቶችን ጤና ከማሻሻል አንጻርም ብዙ ውጤት በተመዘገበ ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ አላየሁም፡፡ ዶ/ር ሐምሊንን አግኝቻቸው ነበር፡፡ ያልኩዋቸው ነገር ቢኖር... እርግጠኛ ነኝ እስከአሁን ከታካሚዎችዎም ሆነ ከጎብኝዎችዎ ብዙ ምስጋናና ሙገሳን አግኝተዋል ፡፡ እኔ የምጨምረው ብዙም ላይኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን እድለኛ የሆኑ ታላቅ ሴት ነዎት ማለት እፈልጋለሁ፡፡ እራስዎን ለሌ ሎች አሳልፈው የሰጡ እና ትልቅ መስዋእትነትን የከፈሉ ነዎት ፡፡ ልዩ ክብር እና ምስጋና ይገባዎታል፡፡ አምሳያም የለዎትም ነበር ያልኩዋቸው። ከዚህ ሆስፒታል ብዙ ተምሬአለሁ፡፡ እኔን ጨምሮ ሌሎቹም ምሳሌነቱን ለመከተል ለራሳችን ቃል ገብተናል...”
                                                   -----///------
“...እኔ ናይጄሪያዊ ነኝ ፡፡ በሙያዬም የጽንስና ማህጸን ሐኪም ነኝ፡፡ በቃ... እኔ ለዚህ የምሰጠው አስተያየት ...እራስን መርሳት ...ብዬ ነው፡፡ በዚህ ሆስፒታል የሚሰሩት በተለይም ዶ/ር ካትሪን ሐምሊን በጭራሽ እራሳቸውን እረስተው ብዙ ዜጎቻችሁን ከሞት ወደ ሕይወት መልሰዋል፡፡ እጅግ ያስደንቃል። በአሁኑ ሰአት ሆስፒታሉን በመጎብኘት ላይ ያለነው ሁላችንም በአንድ መንፈስ ነው እርካታችንን የገለጽነው፡፡ እሳቸውንና የሆስፒታሉን ሰራተኞች በሙሉ እግዚአብሄር ይባር ካቸው እላለሁ ፡፡ ይህ ለሁላችንም ጥሩ ምሳሌ ነው፡፡ እናቶችን ለማዳን ይህንን አይነት ከባድ ስራ ሲሰራ ከማየት በላይ ምንም የሚያስደስት ነገር የለም፡፡ “
                                                             ------///------
ከላይ ያነበባችሁት የጎብኝዎች አስተያየት ነበር፡፡ የሀምሊን ኢትዮጵያ ፊስቱላ ሆስፒታል ወደ 150/ አልጋ ያለው ሲሆን በመላው ቅርንጫፎች ከሚሰጠው አገልግሎት ጋር ተዳምሮ በአመት ወደ 3/ ሶስት ሺህ ለሚሆኑ ሴቶች የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ዶ/ር ካትሪን ሐምሊን ባለቤታቸው በህይወት ባይኖሩም እሳቸው ግን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እስከአሁን ድረስ ሕመምተኞችን የማከምና የማዳን ስራቸውን ቀጥለዋል፡፡
የፊጎ አፍሪካ የመጀመሪያው አህጉራዊ ስብሰባ ላይ የተለያዩ ሳይንሳዊ መረጃዎች ለውይይት ቀርበው ነበር፡፡

Published in ላንተና ላንቺ
Saturday, 12 October 2013 13:28

ግዴለሹ የአሜሪካ ኮንግረስ!

                የዲሞክራሲ ስርአትን በሚከተሉ ሀገራት ፓርላማ ከፍተኛው የህግ አውጭ አካል ነው፡፡ ፓርላማው በሚያወጣቸው ህግና ደንቦች መሠረት ሀገርና ህዝብ ይመራሉ፡፡ የፓርላማ አባላትም፣ በፓርላማው ውስጥ ተቀምጠው ህግ የሚያወጡበትን ወንበር የሚያገኙት በህዝብ ምርጫ መሠረት በመሆኑ፣ ውክልናቸው ወይም ተጠሪነታቸው ለመረጣቸው ህዝብ ነው፡፡
ህዝቡም፤ በነፃ ምርጫው አማካኝነት ወደ ፓርላማው የሚልካቸው ተመራጮች፣ ፓርላማው በሚያወጣቸው ህግና ደንቦች እሱን መስለው፣ እሱን ወክለው፣ ለሱ ጥቅም መጠበቅ እንዲከራከሩለት ወይም እንዲሰሩለት ማድረግ እንጂ ሌላ ጉዳይ የለውም፡፡
ካለፈው ሁለት ሳምንት ጀምሮ፤ የመገናኛ አውታሮችን ብቻ ሳይሆን የድፍን አለሙን ቀልብ ስቦ የሚገኝ አንድ ክስተት አለ፡፡ ይኸውም፤ የአሜሪካ የመንግስት መስሪያ ቤቶች (ከመላከያውና ደህንነት ክፍሉ በስተቀር) መዘጋት ጉዳይ ነው፡፡
ይህ የሆነው እንደሳበ የሚገኝ አንድ ክስተት የአሜሪካ የመንግስት መስሪያ ቤቶች (ከመከላከያውና ደህንነት ክፍሉ በስተቀር) መዘጋት ጉዳይ ነው፡፡
ጉዳዩ ተአምር በፈጠሩ ወይም በሸባሪዎች ጥቃት አሊያም በአስማት የተከሰተ ሳይሆን፤ የመንግስት በጀት እስካሁን ሊለቀቅ ባለመቻሉ ብቻ ነው፡፡ “እኔ ያልኩት ካልሆነ ወይም እኔ በምፈልገው አይነት ቀመር ካልተዘጋጀ በቀር … ሁሉም ነገር እስከወዲያኛው ጥንቅር ብሎ ይከረቸማታል እንጂ እኔ በጀቱን አጽድቄ አለቅም” ያለው ደግሞ፤ ፕሬዚዳንቱ ባራክ ኦባማ፣ ወይም የገንዘብ ምኒስትሩ አሊያም የፌደራል ባንኩ ገዢ አይደሉም፡፡ ይህን ያደረገው በህገንግስቱ አማካኝነት የሀገሪቱን አመታዊ በጀት መርምሮ የማጽደቅ ስልጣን የተሰጠው የአሜሪካ ኮንግረስ ነው፡፡
ይህን የመሰለው የአሜሪካ ኮንግረስ ድርጊት፤ አንድ ሚሊዮን የሚሆኑ አሜካውያንን ስራ ፈት አድርጓቸዋል፡፡ ላልታሰበ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ችግርም ዳርጓቸዋል፡፡
ይህም ብቻም አይደለም፡፡ በስንት ፍዳ ተገንዞቦት የነበረውን የኢኮኖሚ አቡጀዲ ቀድዶ፣ አንገቱን ቀና ማድረግ የጀመረውን የአሜካንን ድውይ ኢኮኖሚ እንደገና ወደ ግንዝ አልጋው ሳይሆን ወደ ቀብር ሳጥኑ ሊከተው ይችላል የሚል ስጋት እንደ አዲስ ቀስቅሷል፡፡ ማርያም ማርያም እንዲባልለት አድርጐታል፡፡
ይህ ሁሉ ክስተት ግን ለአሜሪካ ኮንግረስ ግድ አልሰጠውም፡፡ ለስራ አጥነት የተዳረጉት አሜካውያንን እግዚኦታም ሆነ የፕሬዚዳንት ኦባማን ውትወታ ጉዳዬ ብሎ ከቁም ነገር አልጣፈውም፡፡
እንግዲህ፤ የአሜሪካ መንግስት ነገር እንዲህ ከሆነ መቸም … ማንም ሰው ቢሆን ሊጠይቀው የሚገባ አንድ ጥያቄ የሚከተለው ለመሆኑ ጥርጥር የለኝም፡፡ የአሜካንን ኮንግረስ (ለወከለው ህዝብና ለሀገሪቱ) እስከዚህ ድረስ ግዴለሽ ያደረገው ከቶ ምን አይነት አውሊያ ነው?” የሚለው ጥያቄ ነው መልስ የሚያሻው፡፡
የሆኖ ሆኖ፤ ከስራ ውጪ ያደረጋቸው አንድ ሚሊዮን የሚሆኑ አሜሪካውያን ለሚያሰሙት የችግር ጩኸት የዝሆን ጆሮ ይስጠኝ ማለቱ ብዙም አስገራሚ ላይሆን ይችላል፡፡ የአሜሪካንን ኮንግረስ ጓዳ - ጐድጓዳ ጠጋ ብሎ መመርመር የቻለ) ለዚህ መልስ ሊሆኑ የሚችሉ በርካታ ማስረጃዎችን ማግኘት ይችላል፡፡
ለምሳሌ፤ አሁን ካሉት አምስት መቶ ሠላሳ አምስት የኮንግረስ አባላት ውስጥ፤ አስራ ሠባቱ፤ እያንዳንዳቸው በአማካይ ሀምሳ ሚሊዮን ዶላር ሀብት ባለቤት ናቸው፡፡ አሁን ካሉት የኮንግረስ አባላት መካከል ግንባር ቀደም ቱጃር የሆኑት፤ የቴክሳስ ግዛት የአስረኛው ወረዳ ተመራጭ የሆኑት፣ ሪፐብሊካኑ ማይክል ማካውል ናቸው፡፡ እኒህ የኮንግረስ አባል፤ በባንክ ያላቸው ተቀማጭ ሀብት ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡ እኒህን የኮንግረስ አባል በሀብት ብዛት በቅርብ ርቀት የሚከተሏቸው የአራት መቶ ሰማኒያ ሚሊዮን ዶላር ባለቤት የሆኑት የካሊፎርኒያው ተመራጭ ዳረል ኢሳ ናቸው፡፡
የአስራት ሠባቱ ባለፀጋ የኮንግረስ አባላት ሀብት አንድ ላይ ሲሠላ፤ ሁለት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር ይሆናል፡፡ መቼም … ሁላችሁም እንደምታውቁት፤ የላይኛው የአሜሪካ ምክር ቤት ወይም “ሴኔት” የአባላቱ ቁጥር (ሳፊ) … አንድ መቶ ነው፡፡ ከነዚህ አንድ መቶ የአሜሪካ ሴናተሮች ውስጥ ታዲያ ስልሳ አንድ የሚሆኑት፤ የገንዘብ ካዝናቸው ባሻው ቀን ተከፍቶ ቢታይ ቢያንስ ከአንድ ሚሊዮን ዶላር በላይ ከውስጡ ይገኛል፡፡
ከአሜሪካ ሴናተሮች ውስጥ፤ የቁጥር አንድ ሀብታምነቱን ደረጃ ሁለት መቶ ሀያ ስምንት ሚሊዮን ዶላር በባለቤትነት በማስመዝገብ የሚመሩት የቨርጂኒያው ሴናተር (ዲሞክራቱ) ማርክ ዋርነር ናቸው፡፡ በሁለተኝነት የሚከተሏቸው፤ የምዕራብ ቨርጂኒያው ሴናተር ዲሞክራቱ ጄይ ሮክፌለር ናቸው፡፡ ሴናተር ጄይ ሮክፌለር የስታንዳርድ ኦይል ኩባንያ መስራች ሲሆኑ በአሜሪካ ታሪክ የመጀመሪያው ቢሊየነር የነበሩት የጆን ፎክፌለር የልጅ ልጅ ናቸው፡፡
የአሜሪካንን ኮንግረስ አብላጫውን መቀመጫ የያዙት የሪፐብሊካን ፓርቲ አባላት ናቸው፡፡ ልክ የአሜሪካ የሴኔት ምክር ቤት አብላጫው መቀመጫ የተያዘው በዲሞክራቲክ ፓርቲ አባላት እንደሆነው …
እነዚህን የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባላት የሆኑ ሴናተሮችን የሚመሩት ደግሞ፤ የኔቫዳ ግዛቱ ሴናተር ሀሪ ሪድ ናቸው፡፡ የአራት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ዶላር ጌታ ናቸው፡፡ ሴናተር ሀሪ ሪድ ከሀብታም ሴናተሮች ተራ ውስጥ ተመዝግበው የሚገኙት ሰላሳኛው ተራ ቁጥር ላይ ነው፡፡
የሚገርመው ደግሞ፤ በፌደራል መንግስቱ ሥራ ማቆም ምክንያት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሠራተኞች ያለ ደሞዝ ባዶ እጃቸውን ሲይጨበጭቡ፣ ሚሊዬነሮቹ የኮንግረስ አባላት ግን ደሞዝ ይከፈላቸዋል፡፡ ግዴለሽ ቢሆኑ ታዲያ ምን ይገርማል?!

 

 

Published in ከአለም ዙሪያ

“ልብ የሚያሳርፍ ምርጫ ነው” የቀድሞው የማህበሩ ፕሬዚዳንት
በ97 ዓ.ም 30ሺ ብር የነበረው ካፒታል 2.7ሚ. ብር ደርሷል
ባለፈው ቅዳሜ የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር በቅርስ ጥናትና ምርምር አዳራሽ የጠራውን ጠቅላላ ጉባኤ የጀመረው በመርሃ ግብሩ ላይ ከተቀመጠው በአንድ ሰዓት ዘግይቶ ነው፡፡ ቀን ሙሉ ለሚካሄደው ጉባኤ አምስት ያህል አጀንዳዎች ተይዘው ነበር። ከሁሉም በላይ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ግን የማህበሩን አዲስ አመራር የመምረጥ ሂደት ነው፡፡
በኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር የግማሽ ክፍለ ዘመን ጉዞ፣ ከተከናወኑት ተግባራት ሁሉ ባለፉት ስምንት ዓመታት የተሰሩ ሥራዎች ላቅ ያሉ እንደሆኑ ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ ሆኖም ማህበሩን ለስምንት ዓመታት የመራውን አመራር የሚተካው ማነው? የሚለው ጥያቄ ብዙ ሲያነጋግር ቆይቷል። በህዳር ወር 2005 ዓ.ም ማህበሩ በጠራው ጠቅላላ ጉባኤ፣ ጥያቄው መልስ ባለማግኘቱ የነባሩ አመራር የስራ ጊዜ ለወራት እንዲራዘም መወሰኑ ይታወሳል፡፡ የመስከረም 25ቱ (ያለፈው ቅዳሜ) የምርጫ አጀንዳም ትኩረት የሳበውና ያጓጓው ብዙ ስላስጠበቀ ይመስላል፡፡
የማህበሩ ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው በለጠ በስብሰባው መጀመሪያ ላይ ያደረጉት ንግግር፣ ባለፉት ስምንት ዓመታት እሳቸውና አመራሩ ያከናወኗቸውን ሥራዎች ውጤት የሚዳስስ ነበር፡፡ በመጋቢት 1997 ዓ.ም የተቀበልነው እጅግ የተጎሳቆለ “ስመ ማህበር”ን ነበር ያሉት አቶ ጌታቸው በለጠ፤ ከዚያ በኋላ ባሉ ጊዜያት ብዙ ውጣ ውረዶችን የጠየቀ ቢሆንም፣ ስኬታማ ስራዎች ማከናወን እንደተቻለ ተናግረዋል፡፡ ይሄም የሆነው በሥራ አመራሩ ጥንካሬ ብቻ ሳይሆን መንግሥታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ የተለያዩ አካላት ያደረጉት አስተዋጽኦ ታክሎበት ነው ብለዋል - አቶ ጌታቸው፡፡
ማህበሩ ባለፉት ዓመታት የተለያዩ መጻሕፍትና መጽሔቶች ማሳተሙን የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፤ አባላቱ የነፃ ትምህርት ዕድል እንዲያገኙ ማድረጉንና የአባላት ቁጥር እንዲጨምር መትጋቱን ገልፀዋል፡፡ ከዚህም ሌላ የመታሰቢያ ቴምብሮችን ማሳተሙን፣ ቅርንጫፍ ቢሮዎችን መክፈቱን፣ የጥበብ ጉዞዎችን ማዘጋጀቱን፣ የመፃሕፍት አውደ ርዕዮችን ማሰናዳቱን፣ የሬዲዮ ፕሮግራም መጀመሩን፣ የሥነ ጽሑፍ ስልጠናዎች መስጠቱንና ማህበሩ ለሚያሰራው የጥበብ እልፍኝ ሕንፃ ከመንግሥት ቦታ መጠየቁን አቶ ጌታቸው ዘርዝረዋል፡፡
የዕለቱ የክብር እንግዳ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሙሉጌታ ሰኢድ በበኩላቸው፤ “አንድ ማህበር በአመራሩ ጥንካሬ ለውጤታማ ተግባራት አፈፃፀም የሚጠቅም መስመር ይዞ መጓዝ ቢችልም ለጥንካሬው የማዕዘን ድንጋይ የሚሆኑት በማህበሩ ስር የተደራጁ አባላት ትጋት፣ ቁርጠኝነትና ጥንካሬ ሲኖራቸው ነው፡፡ አምዱ የላላበትና የአባላት መሰረቱ የተሸረሸረበት ማህበር “አለ” ከመባል ውጭ መኖሩን የሚያመለክቱ ተግባራት ሲፈጽም አይታይም” በማለት፣ በኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር የታየው ስኬት የመተባበር፣ የጥረትና የድካም ውጤት መሆኑን መስክረዋል፡፡ በማህበሩ የተጀመሩ ሥራዎችን ለማሳደግም በዚሁ ዕለት ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈርሟል፡፡
የማህበሩን ያለፉት ስምንት ዓመታት የሥራ እንቅስቃሴ የሚቃኝ የጥናት ጽሑፍ ያቀረበው ደራሲ አንዱዓለም አባተ፤ “ከተዘጋጀሁበት ርዕሰ ጉዳዮች ብዙዎቹ በአቶ ጌታቸው በለጠ ስለተገለፀ አሳጥሬ አቀርብላችኋለሁ” በማለት በፕሬዚዳንቱ ያልተነሱ ጉዳዮችን ዳስሷል፡፡
የደራሲ ተመስገን ገብሬ የሕይወት ታሪክና የደራሲ በዓሉ ግርማ የድርሰት ሥራዎች እንዲታተሙ ትልቁን ሚና የተጫወተው ደራስያን ማህበሩ፤ ከዚህም በላይ ታላላቅ ተግባራትን ማከናወን ይችል እንደነበር የጠቆመው ጽሑፍ አቅራቢው፤ የመግባቢያ ሰነዱ ቀደም ብሎ ተፈርሞ ቢሆን ኖሮ ማህበሩ አባላቱን ለማስተማር ዩኒቨርሲዎችን ደጅ አይጠናም ነበር ብሏል፡፡ በደርግ ዘመን ማህበሩ አባላቱን ወደ ውጭ አገራት እየላከ ያስተምር እንደነበርም በማስታወስ፡፡
ማህበሩ አባላቱን የሚያበረታታበትና ዕውቅና የሚሰጥበት ዓመታዊ የሽልማት ፕሮግራም ማዘጋጀት ነበረበት ያለው ደራሲ አንዱዓለም፤ የራሱ ማተሚያ ድርጅትና የመፃሕፍት መሸጫ መደብሮች ቢኖሩት ጥሩ ነው ብሏል፡፡ ለጥበባዊ ጉዞዎች የሚመረጡ አባላት የሚመለመሉበት አካሄድ ግልጽ አለመሆኑን በመጠቆም፤ ጉዳዩ ቅሬታ እያስነሳ ስለሆነ ወጥ የሆነ መስፈርት ሊቀመጥለት ይገባል ሲልም አሳስቧል፡፡
ሌላው የጥናት ጽሑፍ አቅራቢ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በፎክሎር የዶክትሬት ተማሪ የሆነው ገዛኸኝ ፀጋው በበኩሉ፤ ማህበሩ ያሳተማቸውን መፃሕፍትና መጽሔቶች የተመለከተ ዳሰሳ አቅርቧል፡፡ በማህበሩ የግማሽ ክፍለ ዘመን ታሪክ ማህበሩን ከመሩት አምስት የተለያዩ ኮሚቴዎች ውስጥ በአንደኛው፣ በሦስተኛውና አምስተኛው የሥራ አስፈፃሚ ዘመናት ስለታተሙት መፃሕፍትና መጽሔቶች ዝርዝር ያቀረበው ገዛኸኝ፤ የአምስተኛውን ዘመን ሥራ “ወርቃማ” ነበር ብሎታል።
ሩብ ጉዳይ፣ የበዓሉ ግርማ ድርሰቶች፣ ከቁጥር 2 በኋላ የታተሙት ብሌን መጽሔቶች፣ በቁጥር 1 እና 2 የታተሙት የዘመን ቀለማት፣ መድብለ ጉባኤ፣ የጥላሁን ገሠሠ የሕይወት ታሪክ፣ ከአርቲስቲክና ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤቶች ጋር በመተባበር የታተሙ 14 መፃሕፍትና መሰል ሥራዎችን በማሳያነት ያቀረበው የጥናት ጽሑፍ አቅራቢ፤ በሥራው ሂደት የታዩ ግድፈቶችና ስሕተቶችን ነቅሶ በማውጣት ልንማርበት ይገባል ብሏል፡፡
በማህበሩ ፀሐፊ በደራሲ እንዳለጌታ ከበደ በቀረበው የሒሳብ ሪፖርት፤ ለጥበብ እልፍኝ ማሰሪያ በዝግ አካውንት የተቀመጠውን 2 ሚሊዮን ብርና በተዘዋዋሪ ፈንድ የሚንቀሳቀሰው ገንዘብ፤ እንዲሁም ያልተሸጡ መፃሕፍትና መጽሔቶችን ዋጋ ጨምሮ ማህበሩ 2.7 ሚሊዮን ብር ካፒታል እንዳለው ተገልጿል፡፡ አመራሩ ማህበሩን በ1997 ዓ.ም ሲቀበል ካፒታሉ 30ሺ ብር እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
ከቀኑ 10 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ላይ ነበር በጉጉት ወደሚጠበቀው ትልቅ አጀንዳ የተገባው፡፡ በደራሲና ሐያሲ አስፋው ዳምጤ የሚመራ ሦስት የአስመራጭ ኮሚቴ ከተሰየመ በኋላ “የማሕበሩ ሕገ ደንብ ላይ አለ የተባለው ክፍተት ተሻሽሎ ምርጫው ይካሄድ፤ ከነባሮቹ ሥራ አመራሮች የተወሰኑት ወደ አዲሱ ሥራ አመራር እንዲገቡ ይደረግ፤ ሙሉ ለሙሉ አዲስ የሥራ አመራር ከመምረጥ ውጭ የሚያስኬድ ምንም ሕጋዊ መሠረት የለም” የሚሉና የሥነ ስርዓት ጥያቄዎች ላይ የሚያተኩሩ ሐሳቦች መንሸራሸር ጀመሩ፡፡ በመጨረሻም “ያለ ነባሩ አመራር ማህበሩ ሊቀጥል አይችልም በሚል ስጋት አይግባን፤ በዚህ አዳራሽ ውስጥ ማህበሩን ሊመሩ የሚችሉ አባላት አሉ” በሚል በቀረበው ሀሳብ መግባባት በመቻሉ፤ ለውድድር የሚቀርቡ አባላትን የመጠቆሙ ኃላፊነት ለነባሩ ሥራ አመራር ተሰጠ፡፡ 10 እጩዎች ለውድድር ቀርበውም ሰባቱን አሸናፊዎች ለመለየት ድምጽ መስጠት ተጀመረ።
ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ ፕሬዚዳንት፣ ገጣሚ አያልነህ ሙላቱ ምክትል ፕሬዚዳንት፣ ደራሲ አንዱዓለም አባተ ዋና ፀሐፊ ሆነው ሲመረጡ፤ ገጣሚ ገዛኸኝ ፀጋው በሂሳብ ሹምነት፣ ደራሲ አብርሃም መለሰ ደግሞ በኦዲተርነት ተመረጡ፡፡
በስልጣን ሽግግሩ ማጠናቀቂያ የቀድሞው ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው በለጠ ባደረጉት ንግግር፤ “ልብ የሚያሳርፍ ምርጫ ነው፤ ተመራጮቹ ለሥራው የተሰጡ ሰዎች ናቸው” ካሉ በኋላ በማህበሩ የተጀመሩ ሥራዎች በተሻለ መልኩ ተግባራዊ እንዲሆኑ ለአዲሱ አመራር አደራ ሰጥተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር አዲሱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ በበኩላቸዉ፤ እምነት ጥለውባቸው የመረጧቸውን የማህሩን አባላት አመስግነው፤ “ማህበሩ ለዛሬ የደረሰው ብዙ ውጣ ውረዶችን አሳልፎ ነው፤ ተከታታይ ትውልዶች ማህበራችንን ከዘመን ወደ ዘመን አሸጋግረው ለዛሬ አድርሰውልናል፡፡ ያለፉትን አመራሮች ጥንካሬ፣ ትጋትና ሐቀኝነት በእኛም ውስጥ ለማስቀጠል እንሰራለን፡፡
የመረጣችሁን አባላት ትተባበሩናላችሁ፣ አብራችሁን ትቆማላችሁ ብለን ስለምናምን ኃይልና አቅም ሆናችሁን ታላቅ ሥራ እንሰራለን” በማለት ንግግራቸውን ሲያጠቃልሉ የአዳራሹ የግድግዳ ሰዓት 12፡45 ላይ ያመለክት ነበር፡፡

 

Published in ጥበብ

             መውለድ ሁሉንም ይቀድማል፡፡ ይበልጣል፡፡ መውለድ ባይኖር (የሚያድግ ነገር ስለሌለ) ስለ ማሳደግ በፍፁም ማውራት ባልቻልን ነበር፡፡ የእንጀራ አባት ወይንም ጉዲፈቻ ለተወለደው ነገር ባለ ውለታም ቢሆንም ወላጁ ግን አይደለም፡፡
ስለ ሰው ልጅ የአካል ውልደት ሳይሆን ስለ መንፈስ ውልዱ ነው ማውራት የፈለግሁት፡፡ ስለ ጥበብ፡፡ ስለ ጥበብ የተዋልዶ ጤና መዛባት በመጨነቄ ይሄንን መረጃ ፍላጐቱ ላለው ሁሉ ለመንገር ፈለግሁ፡፡ ጤናማ ተዋልዶ እንዴት እንደሚካሄድ በተደጋጋሚ ከመዘብዘብ፣ ተዋልዶውን ጤና የሚያሳጡት ዋነኛ በሽታዎቹ የትኞቹ እንደሆነ ባሳብቅ ይሻላል ብዬ ስላሰብኩ ወደ አላማዬ በቀጥታ ላምራ፡፡
እንደ ማንኛውም ውልደት ጥበብም መወለዱን እርግጠኛ እንድንሆን የምንተማመንባቸው ምልክቶች አሉት፡፡

አንደኛው ምልክት ሞት ነው። አዲስ ጥበብ ሲፈጠር ከፈጠራው በፊት የነበሩ ትውልዶችን ወይንም የጥበብ የግንዛቤ ንቃቶችን ያፈራርሳል፡፡ አዲስ ፈጠራ እንደተከወነ እርግጠኛ ከሆንን፣ አዲስ አመለካከትም አብሮት መወለዱ ሊያጠራጥረን አይችልም፡፡ ምንም እንኳን አዲሱ አመለካከት ገና ቁልጭ ብሎ ባይታየንም። ምሳሌዎችን ልጥቀስ - በ1948 እ.ኤ.አ በጀርመን ሀገር የቅዱስ ማሪን የቤተመቅደስ ውስጥ ጥበባዊ ምስሎችን ለማደስ የተቀጠረው ጀርመናዊ፣ አንድ አስደናቂ ግኝት በቤተመቅደሱ ግድግዳዎች ላይ አገኘ፡፡ ያገኘው የጥንታዊ ጐቲክ የግድግዳ ስዕሎችን ነበር፡፡
እነዚህን መሰሎች አዋቂዎቹ ሲመረምሯቸው የጥንታዊ የጐቲክ ዘመን የጥበብ ጉልላት የሚወክሉ በመሆናቸው በአንድ አቋም ተስማሙ፡፡ “የጠፋ ቅርስ ተገኘ” ተባለ፡፡ ግኝቱ በቅርስ ጠባቂዎች ተመዘገበ፡፡ ቤተክርስቲያኑም ጐብኚን መሳብ ጀመረ፡፡ ማንኛውም ተመራማሪ የስራውን ኦርጅናልነት አልጠረጠረም፡፡ አዲስ የተወለደ ነገር ነው፡፡ አዲስ የተወለደ ሳይሆን የተገኘ ነገር ቢሆንም ከአዲስ የጥበብ ፈጠራ ተለይቶ አልታየም፡፡ እነዚህን ስዕሎች ከተደበቁበት ያገኘው ዲትሪች ፌይ የሚባል ሰው ነበር፡፡ የተገኙትን ስዕሎች በዘመናት ውስጥ ያለፉበትን እንግልት መልሶ እንዲያድስ የተቀጠረው ባለሞያ ግን ሉተር ማስካልት ነው ስሙ፡፡ የጥበብ ግኝቱ በመደነቅ እና ተመልካች እየሳበ ብዙ ጊዜ ከቆየ በኋላ (ከእለታት አንድ ቀን) ይኼው የእድሳቱን ስራ ያከናወነው ባለሞያ ህሊናው እረፍት ነሳው መሰለኝ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሄዶ እጁን ይሰጣል። ጥፋቱንም ይናዘዛል፡፡ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ የተገኙት የጥንታዊ ጐቲክ ልጥፍ የግድግዳ ስዕሎች የተሰሩት በእኔ እጅ ነው፤ የሚል ነው ኑዛዜው። ኑዛዜውን ተመርኩዘው አሁንም የጥበብ ባለ እውቀቶች ስራውን በጥልቀት መረመሩ፤ “ሰውየው የሚለው ስህተት ነው፤ ስዕሎቹ ኦርጅናል ናቸው” አሉ፤ በድጋሚ፡፡
ወንጀለኛ ነኝ በሚል የፀናው ሉተር ማስካልት፤ ቤቱን እንዲፈትሹ ይገፋፋቸዋል፡፡ ወደ ገፋፋቸው ቦታ ሲገቡ የሉተር ስቱዲዮ በተለያዩ ታላላቅ ጥበበኞች የተሳሉ፤ ነገር ግን አለም የማያውቃቸው ማስተር ፒሶች ተሞልቶ ያገኙታል፡፡ የሬምብራት፣ የፒካሶ፣ የካጋል፣ የሉትሪክ ወዘተ፡፡
ከራሳቸው ከጥበበኞቹ በስተቀር ማንም ሊደግማቸውም ሊያስመስላቸውም የማይችሉ የፈጠራ ስራዎች ናቸው፡፡ ላለማመን አንገራገሩ። ግን ለማመን ተገደዱ፡፡ የስእሎቹ ብዛት ራሱ ከተሸሸጉበት ፈልጐ ነው ያገኛቸው ሊያስብሉ የሚችሉ አይደሉም። የእያንዳንዱ አርቲስት አዲስ ስራ በመቶዎች ብዛት ነው በሉተር ማስካልት እስቱዲዮ ውስጥ የሚገኘው።
ውልደት ናቸው ብለው ደምድመው የነበሩዋቸው ስራዎች፤ ከተወለዱ በኋላ በሉተር አስመስሎ ሰሪው ጉዲፈቻነት ያደጉ ናቸው፡፡ ግን ችግሩ ጥበብ መወለዱ ብቻ በቂ ነው፡፡ ሲወለድም ራሱን ችሎ ነው፡፡ አሳዳጊ ወይንም ጉዲፈቻ አይፈልግም፡፡ የጥበብ ኦሪጅናል ስራ በአስመሳይ ሲደጋገም ጉዲፈቻ እያሳደገው ነው ስል እኔ ሰይሜዋለሁ፡፡ ጥበብ ተወልዶ ከነበረ ለማደግ የማንንም እንክብካቤ አይፈልግም፡፡ ጉዲፈቻ ሊኖረው አይችልም፡፡ በአስመሳይ ጥበበኛ የተሰራ ፈጠራ የሚያሳድገው ጥበቡን ሳይሆን ጉዲፈቻውን ነው፡፡ (ከዚህ በፊት በዚሁ ጋዜጣ ላይ እኔ እና ሌሎች ተጠንጠልጣይ ቁልፍ፤ ተገንዳሽ እና የመሳሰሉትን ስንባባል እንደነበር ትዝ ይለኛል) ትክክለኛው ተንጠልጣይ ግን የጉዲፈቻ አርቲስቱ ነው፡፡
የተንጠልጣይነትን ስነልቦና ለማወቅ ትንሽ ጠለቅ ብሎ መመልከት ያስፈልጋል፡፡ ይኼንኑ የተንጠልጣይነት ስነልቦና የሚወክልልኝ የአንግሊዝኛ ቃል ስፈልግ “Snobbery” የሚለው ልክክ አለልኝ፡፡ በፈረንጆቹ ትንተና መንጠልጠልን አስቲ ለመረዳት ልጣር-
“Snobbery is the result of a mix up between two frames of reference. “A” and “B” with different standards of value; and the consequent misapplication of standard “A” to value judgment referring to “B”
ለምሳሌ የቅድሙ ምሳሌዬ የነበረው (ራሱን እንደ ወንጀለኛ የቆጠረው) ሉተር ማስካልት የታላላቆቹን አርቲስት ዘይቤ እና ክህሎት በማያሻማ መልኩ እንዲያውም እነሱ ፈጥረው በማያውቁት አዳዲስ አርዕስተ ነገር ላይ እየተጠቀመ የጥበብ ስራ ሰርቷል፡፡ የጥበቡ ስራ በእነዛ ታላላቅ ሰዎች እጅ እንደተሰራ አዋቂ ነን ብለው የሚያምኑትም መስክረዋል፡፡ በስራዎቹ ወጥነት እርግጠኛ ሆነው ሳለ በስንት ምርመራ አስመስሎ ፈጣሪው ሉተር ማስካልት፤ የስራዎቹ ወላጅ መሆኑ ሲደረስበት ተመሳስለው የተሰሩት የፈጠራ ውጤቶች ድንገት ከጥበብ ካታሎጐቹ ላይ ተፋቁ፡፡
መንጠልጠል ወይንም እስኖበሪ ያልኩት በሽታ እዚህ ላይ ቁልጭ ብሎ ሊታየን ይገባል፡፡ ያንኑ ስዕል ተመልክተው ሰአሊውን (ሉተር ማስካልት) ታላቅ፤ ከተጋለጠ ወይንም ራሱን ካጋለጠ በኋላ ደግሞ ያንኑ ፈጠራ ውዳቂ የሚያደርግ ሰውኛ አተያይ የሚገልፀው የቅድሙን ሃሊዮት (ቲዎሪ) ነው፡፡ በሉተርም ይሰራ በፒካሶ ስዕሉ ፊት ለፊታችን ቁጭ ብሏል፤ ብለን እናስብ፡፡ ስዕሉን “A” እንበለው። የሰው አስተያየት ደግሞ አለ፤ ማለትም ስዕሉ የአንድ በጣም የታወቀ ሰው ስራ ነው ስንባል “A” አሪፍ የሚሆን ከሆነና …የአንድ ውዳቂ “ስም” ስራ ነው ስንባል “A” አስቀያሚ የሚሆን ከሆነ፤ “A” የሚባለው ነገር ውበቱን የሚለዋውጠው አሊያም በምትሀታዊነት እና አምታችነት መሀል የሚዋልለው በ“B” የሚባል ሌላ ነገር ምክንያት ነው፡፡
ይህ ነገርየውን ከነገርየው ጋር ምንም ግንኙነት በሌለው መለኪያ የሚያስለካን ነገር …”ተንጠልጣይነት” ወይንም “Snobbery” ብዬ ጠርቼዋለሁ፡፡
የዛሬ መቶ ሃምሳ አመታት በፊት በፈረንጆቹ የምግብ ዝርዝር “ኦይስተር” የሚባል የባህር እንቁ ፈጣሪ ቀንዳውጣ መሰል ነገር “የደሀ” ምግብ ነበር። በሀብት በናጠጡት መሀል ምግቡ “ቄስ ይጥራው” የሚባል ነውር እንደነበር ይታወቃል፡፡ ከመቶ ሃምሳ አመታት በኋላ ተገላቢጦሽ ሆነ፡፡ ደሀ ሳይመገበው ኖሮ ይሞታታል፡፡ ኦይስተር “ፐርል” የተባለውን የባህር እንቁ በውስጡ የሚሰራ ፍጥረት ብቻ ሳይሆን …“የምግብ ብሔሮች”ም እንቁ ሆነ፡፡
ሂትለር የሚባለው ሰውዬ በጀርመን ላይ ከመነሳቱ በፊት ትኖር ስለነበረች አንዲት ፀሃፊ ሴትዮ የሚባለውም የቅድሙን ሃሊዮት የሚያጠናክር ነው፡፡ ፀሃፊዋ ከተለያዩ ወንዶች ጋር የፍቅር ግንኙነት ማድረግ አመሏ ነው ይባልላታል፡፡ ወንዶቹን ለወሲብ ብትመርጣቸውም ለምርጫዋ ዋናው ምክንያት የወንዱ እድሜ፣ ደም ግባት ወይንም የፍቅር አያያዝ ዘይቤው አይደለም፡፡ ከወንዱ ጋር ግንኙነት እንድታደርግ የሚያነሳሳት እንደኛ ሰውዬው ደራሲ መሆን አለበት፡፡ ሁለተኛ የደረሰውን መጽሐፍ ከ20.000 ኮፒዎች በላይ የሸጠ መሆን አለበት፡፡ “ከዚህ ሽያጭ በታች ያሽቆለቆሉት ጋር ለመተኛት ስሞክር ሰውነቴ አልታዘዝ ይለኛል” ብላ እርግጡን ተናግራለች ይባልላታል፡፡
በዚህ በሁለተኛው የፀሃፊዋ ምሳሌ ረገድ “A” የፆታ ግንኙነት እና በወንድና ሴት መሀል ያለው መፈላለግ ልንለው እንችላለን፡፡ “B” ደግሞ ደራሲነት እና የመጽሐፍ ሽያጭ ነው፡፡ በሁለተኛው አማካኝነት የመጀመሪያው “A” የሚንጋደድ ከሆነ፤ የመጀመሪያው ድሮውኑ ብቻውን ትርጉም የለውም ማለት ነው፡፡
የፈጠራ ስራ ብርሐን ነው፡፡ ራሱን የቻለ ነው፡፡ ውልደት ነው፡፡ አሳዳጊም አያስፈልገውም፡፡ የፈጠራ ስራን (ብርሐን) የማፍለቅ አቅምና የፈጠራ ሰውነት ያለው ሰው፤ የጥንቱንም የፈጠራ ውጤት አይታከክም፡፡ ስሙንም በማስተዋወቅ ስራውን ለማስወደድ አይሞክርም፡፡
ስለዚህም ጥበቡ የጉዲፈቻ ወይንም በሌላ ከጥበቡ ውጭ በሆነ ነገር ላይ በመመርኮዝ ጥበቡ እንደተወለደ ሊያረጋግጥልን አይችልም፡፡ ውልድ (ጤነኛ ስነ ተዋልዶ መንገድ) መገኘቱን የሚገልፀው የተፈጠረው ጥበብ ብቻ ነው፡፡ “A” is “A” or “A” is Non “A” but it can’t be “A” and Non “A” at the same time የሚለውን የአሪስጣጢለስ የማንነት ህግ፤ ለጥበብ ማንነትም እንደ መለኪያ መጠቀም እንችላለን፡፡ ግን … ጥበብ ምን ማለት እንደሆነ በማያሻማ መንገድ መግለፅ እስካልቻልን … መወለድም ሆነ መሞት፣ ብርሐንም ሆነ ጨለማ፣ ፈጠራ እና ኢ-ፈጠራ … የቱ የት እንደሆነ መለየት ሳንችል መሳከር ነው የሚሆነው፡፡
(እዚህ መጣጥፍ ላይ ስሜን ፅፌ እንድታነቡት ባደርጋችሁ … የስሜ ማንነት የፅሁፉን ማንነት ከጥሩ ወደ መጥፎ … ሊቀይረው ስለሚችል … ሲችልም ከተፃፈው አስተሳሰብ ጋር እንድታነፃፅሩት ስሜን አድምቄ እፅፈዋለሁ!)

 

Published in ጥበብ

ቀደም ሲል ለንባብ የበቃው “በአራጣ የተያዘ ጭን” የተሰኘ የአጭር ልብወለድ መድበል፣ እንደገና ታትሞ ለገበያ ቀረበ፡፡ 19 አጫጭር ልብወለዶችን የያዘው መጽሐፍ የዮፍታሔ ካሳ ድርሰት ሲሆን፣ ተወዳጅነት በማግኘቱ ሁለተኛ ዙር 10ሺ ኮፒ እንደታተመ ተነግሯል፡፡ የመጀመሪያው እትም 5ሺ ኮፒ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በ233 ገጽ የቀረበው መጽሐፍ ዋጋው 47 ብር ነው፡፡ 

ሃያ ሰባተኛው ግጥም በጃዝ በመጪው ረቡዕ ምሽት እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታወቁ። በራስ ሆቴል አዳራሽ በሚቀርበው ዝግጅት ገጣሚ ነቢይ መኮንንን ጨምሮ ምንተስኖት ማሞ፣ በረከት በላይነህ፣ ባየልኝ አያሌውና ምስራቅ ተረፈ ግጥሞቻቸውን ሲያነቡ፤ ሀብታሙ ስዩም ወግ፣ ዶ/ር አሉላ ፓንክረስት ዲስኩር ያቀርባሉ ተብሏል፡፡ 

በቀሲስ ሰሎሞን ሙሉጌታ የተዘጋጁ አስራ ሦስት የልጆች መጻሕፍት ዛሬ በካፒታል ሆቴል እንደሚመረቁ አዘጋጁ አስታወቁ፡፡
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን አስተምሕሮ መሠረት የተዘጋጁት መጻሕፍት ከሙዓለ ሕጻናት እስከ 12ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች የተዘጋጁ ናቸው።
ከመጻሕፍቱ ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ለበጐ አድራጐት ይውላል ተብሏል፡፡