ዋናው መፀዳጃ ቤት በመፍረሱና በአጠቃቀም ችግር የተከሰተ ነው (የፍ/ቤቱ ፕሬዚዳንት)
      ልደታ አካባቢ የሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የመፀዳጃ ቤት የንፅህና ችግር እንዳማረራቸውና ለበሽታ እንደዳረጋቸው የቃሊቲ ማረሚያ ቤት የታራሚ አጃቢ ፖሊሶች ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ ላለፉት ሶስት ዓመታት አቤቱታ አቅርበው እስካሁን መፍትሄ አለመገኘቱ አሳዝኖናል ብለዋል ፖሊሶች፡፡
የከፍተኛው ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ውብሸት ሽፈራው በበኩላቸው፤ በባቡር መንገድ ዝርጋታው ምክንያት ዋናው መፀዳጃ ቤት በመፍረሱ የታራሚዎች ማረፊያ አጠገብ ያለው አነስተኛና ጊዜያዊ መፀዳጃ ቤት መገንባቱን አስታውሰው፣ የተጠቃሚው ቁጥር ከመጸዳጃ ቤቱ ጋር ባለመመጣጠኑና በአጠቃቀም ጉድለት ችግሩ ሊከሰት መቻሉን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ የመጸዳጃ ቤት የፅዳት ችግር ብቻ ሳይሆን እጥረትም እንዳለ በፍ/ቤቱ ግቢ ውስጥ ያነጋገርናቸው ባለጉዳዮች ገልፀውልናል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በግቢው ውስጥ ካፍቴሪያ ባለመኖሩ ጠዋት ፍ/ቤት  መጥቶ ለከሰዓት የተቀጠረ ባለጉዳይ አረፍ ብሎ የሚጠብቅበት ስለማያገኝ ለእንግልት እንደሚዳረግ ባለጉዳዮች ይናገራሉ፡፡
 “ላለፉት ሶስት ዓመታት ቢያንስ በሁለት ቀን አንዴ ታራሚዎችን ወደ ፍ/ቤት ይዤ እመጣለሁ” ያለው የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ፖሊስ፤ በዚህም ሳቢያ ለአስም በሽታ መዳረጉን ለአዲስ አድማስ ተናግሯል፡፡ ከመፀዳጃ ቤቱ ፊት ለፊት በገንዳ መልክ የተሰራው የወንዶች ሽንት ቤት እስከ አፉ ድረስ በሽንት የተሞላ ሲሆን ሽታው የሚሰነጥፍጥ እንደሆነ በአካል ተገኝተን ታዝበናል፡፡ በሁኔታው የተማረሩት የታራሚዎች አጃቢ ፖሊሶች ችግሩ እንደማይቀረፍ እናውቀዋለን ይላሉ፡፡ ለየትኛውም ሚዲያ ብንናገር ችግሩ እንደማይቀረፍ ብናውቅም ከመናገር ግን ወደ ኋላ አንልም ያሉት ፖሊሶቹ፤ እነሱ ብቻ ሳይሆኑ ታራሚዎችም የችግሩ ሰለባ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ችግሩ ከአቅም በላይ ሆኗል የምትለው የፍ/ቤቱ የፅዳት ሰራተኛ፤ በተለይ የውሃ እጥረት ለፅዳት ሰራተኞችም ሆነ ለተጠቃሚው ትልቅ ፈተና እንደሆነ በመጥቀስ አስቸኳይ እልባት ያሻዋል ብላለች፡፡
የፍ/ቤቱ ፕሬዚዳንት አቶ ውብሸት ሽፈራው በበኩላቸው፤ የችግሩን ስፋት ግምት ውስጥ በማስገባት ፍ/ቤቱ ካሉት ቋሚ የፅዳት ሰራተኞች በተጨማሪ ጊዜያዊ ሰራተኞችን በመቅጠር የፅዳት ስራው ሳይቋረጥ እንደሚሰራ ጠቁመው፤ በአጠቃቀም ችግርና በተጠቃሚው ብዛት የተነሳ መጸዳጃው ቶሎ ቶሎ እንደሚሞላና የውሃ እጥረቱ ተደምሮ ችግሩን እንዳባባሰው ገልፀዋል፡፡ ሆኖም እነዚህ ችግሮች በቅርቡ መፍትሄ ያገኛሉ ይላሉ - ፕሬዚዳንቱ፡፡ በፍ/ቤቱ ዋናው ህንፃ ስር አገልግሎት ሳይሰጡ የቆዩ ከ16 በላይ መቀመጫ ያላቸው መፀዳጃ ቤቶች መኖራቸውን  ጠቁመው፤ እነዚህ መፀዳጃ ቤቶች በቀን ከ400 እስከ 500 ሰው ማስተናገድ እንደሚችሉ፣ አስፈላጊው ጥገናም እንደተደረገላቸውና በቅርቡ ስራ ሲጀምሩ ችግሩ እንደሚፈታ አስረድተዋል፡፡ የውሃ እጥረቱንም ለመቅረፍ ሮቶ የውሃ ታንከሮች ግዢ ለመፈጸም ጨረታ እንደወጣ ጨምረው ገልጸዋል፡፡
የካፍቴሪያውን ጉዳይ በተመለከተም ጨረታ ወጥቶ ውል ለመፈራረም በዝግጅት ላይ እንደሆነ የጠቆሙት የፍ/ቤቱ ፕሬዚዳንት፣ ካፍቴሪያው በቅርቡ ተከፍቶ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምርም ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ከወራት በፊት የ15 ዓመቷን ታዳጊ ሃና ላላንጎን ከት/ቤት ስትመለስ በታክሲ አሳፍረው በመውሰድና በተደጋጋሚ አስገድደው በመድፈር ለሞት ዳርገዋል በሚል ተጠርጥረው ክስ የተመሰረተባቸው አምስት ወጣቶች እንዲከላከሉ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 3ኛ ወንጀል ችሎት ባለፈው ረቡዕ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
በከባድ የሰው ግድያና አስገድዶ መድፈር ወንጀል የተከሰሱት አምስቱ ወጣቶች ላይ አቃቤ ህግ ምስክሮቹን አሰምቶ የጨረሰ ሲሆን ፍ/ቤቱ የምስክሮችን ቃልና ክሱን መርምሮ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ይዞ ነበር፡፡  ባለፈው ረቡዕም ፍ/ቤቱ ተጠርጣሪዎቹ ወጣቶች ክሱን እንዲከላከሉ ብይን የሰጠ ሲሆን መከላከያቸውን ለመስማትም ለፊታችን አርብ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና

    በሽብርተኝነት ወንጀል ተጠርጥረው ከሚያዚያ ወር 2006 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኙት ሶስቱ ጋዜጠኞችና ስድስቱ ጦማሪያን የፊታችን ማክሰኞ የእምነት ክህደት ቃላቸውን መስጠት ይጀምራሉ፡፡ ፍ/ቤቱ ከዚህ ቀደም አቃቤ ህግ እንዲያሻሽል ካዘዘው አራት ክሶች ውስጥ ባለፈው ረቡዕ ሶስቱን ሲቀበል፣ የተጠርጣሪዎቹን የስራ ክፍፍል በተመለከተ አቃቤ ህግ አሻሽሎ ያቀረበውን ክስ ፍ/ቤቱ ውድቅ አድርጎታል፡፡
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት፤ አቃቤ ህግ አሻሽል የተባለውን አራት ክሶች ያሻሻለው በፍ/ቤቱ ትዕዛዝ መሰረት ነው ወይስ አይደለም የሚለውን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለባለፈው ረቡዕ ቀጠሮ መያዙ የሚታወስ ሲሆን የአቃቤ ህግን የክስ ማሻሻል ሂደት መርምሮ ሶስቱን ሲቀበል አንዱን ውድቅ ማድረጉን ፍ/ቤቱ ገልፆ፤ ተከሳሾች በእለቱ የእምነት ክህደት ቃል መስጠት ይችሉ እንደሆነ ጠይቋል፡፡
የፍ/ቤቱ ጥያቄ ድንገተኛ የሆነባቸው ተከሳሾችና ጠበቆቻቸው በጉዳዩ መክረንበት ከሰዓት በኋላ እንገናኝ በማለት ለፍ/ቤቱ ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ ሆኖም ከሰዓት በኋላ የተከሳሽ ጠበቆች ጉዳዩን በውል ለማጤን በቂ ጊዜና ምቹ ቦታ አለማግኘታቸውን፣ የ9ኛ ተከሳሽ የጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ ጠበቃ ችሎት የቀረቡት በዚያን ሰዓት በመሆኑ ዝግጁ አለመሆናቸውን፣ ሌላ አንድ ጠበቃም በደረሰባቸው የመኪና አደጋ የተነሳ በችሎት ባለመገኘታቸውና በተያያዥ ምክንያቶች ከደንበኞቻቸው ጋር መመካከር ባለመቻላቸው ፍ/ቤቱ አጭር ተለዋጭ ቀጠሮ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍ/ቤቱም ጠበቆችና ተከሳሾች ያቀረቡትን ምክንያት ካደመጠ በኋላ የተከሳሾችን የእምነት ክህደት ቃል ለመቀበል ለፊታችን ማክሰኞ ሶስት ሰዓት ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

Published in ዜና

      የዘንድሮው የኢፌድሪ የመከላከያ ሠራዊት ቀን በብሔራዊ ደረጃ በምዕራብ እዝ ከዛሬ ጀምሮ እስከ የካቲት 7 ቀን 2007 ዓ.ም የሚከበር ሲሆን የመክፈቻና የማጠቃለያ ስነስርዓቱ በባህር ዳር ይከናወናል ተብሏል፡፡
ለ3ኛ ጊዜ የሚከበረው የዘንድሮው የመከላከያ ሠራዊት ቀን በእዝ ደረጃ የሚከበር መሆኑን የጠቀሱት የመከላከያ ሚኒስትሩ አቶ ሲራጅ ፈጌሣ; በዋናነት ከየካቲት 1 እስከ 6 ቀን 2007 ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ የሠራዊቱን ተግባራት የሚዘክሩ ኤግዚቢሽኖች በማቅረብ የሚከበር ሲሆን የማጠቃለያ በአሉም የካቲት 7 በድምቀት ይከበራል ብለዋል፡፡  የዘንድሮው በአል “ህዝባዊ ባህሪያችንን ጠብቀን ከዘመኑ ጋር እየታደስን ተመራጭ የሰላም ሃይል ሆነን እንቀጥላለን” በሚል መርህ የሚከበር ሲሆን መሪ ቃሉም ሠራዊቱ የቴክኖሎጂ ለውጥ ማዕከል መሆን ህዝባዊ መሠረት ይዞ በአለማቀፍ ደረጃ በሠላም ማስከበር ያለውን ተመራጭነት አጠናክሮ ይቀጥላል የሚለውን መልዕክት እንደሚያስተላልፍ ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡
የመከላከያ ሠራዊት ቀንን ማክበር ያስፈለገበትን ምክንያት ያብራሩት ሚኒስትሩ፤ ሠራዊቱ ህገ መንግስቱንና ህገመንግስታዊ ስርአቱን ለማስከበር ያለውን ዝግጁነት ለማረጋገጥ፣ ሠራዊቱ እርስበእርሱ ያለውን ዲሞክራሲያዊ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንዲሁም የሠማዕታትን ክብር ለማስጠበቅና እነሱን ለመዘከር በማሰብ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ህብረተሰቡ በየአካባቢው ከሚገኙ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ጋር በጋራ በአሉን በድምቀት እንዲያከብርና ለሠራዊቱ ተገቢውን ክብርና ምስጋና እንዲያቀርብ ሚኒስትር ሲራጅ ፈጌሣ ጥሪ አቅርበዋል፡፡  

Published in ዜና
  • የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች ሽልማቱን አወድሰዋል
  • በግጥምና በስዕል 1ኛ የወጡ 100ሺ ብር ይሸለማሉ

    ዳሸን ቢራ የአገሪቱን የኪነ ጥበብ ዘርፍ ለማሳደግ ያግዛል በሚል ያዘጋጀው የኪነ ጥበባት ውድድር ሽልማት (Dashen Arts Award) ግማሽ ሚሊዮን ብር በነገው ዕለት ለአሸናፊዎች ያከፋፍላል፡፡ በግጥምና በስዕል ዘርፍ ከ1-3  የወጡ ተወዳዳሪዎች ከ100 ሺ ብር እስከ 50 ሺ ብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡
በግጥም፣ በስዕልና ቅርፃ ቅርፅ ሲካሄድ በቆየው ውድድር 356 ተወዳዳሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ከኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር፣ ከኢትዮጵያ ሰዓሊያንና ቀራ    ፂያን ማኅበር፣ ከዜማ ብዕር ሴቶች የሥነ-ፅሑፍ ማኅበርና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-ጥበባት ኮሌጅ የተውጣጡ ዳኞች በሰጡት ዳኝነት ያሸነፉ ተወዳዳሪዎች ነገ ከ10 ሰዓት ጀምሮ በሚሌኒየም አዳራሽ እንደሚሸለሙ ድርጅቱ አስታውቋል፡፡
በግጥም ዘርፍ ከተወዳደሩት 157 ተሳታፊዎች መካከል 29 ተወዳዳሪዎች በስራቸው ብቃት ተመርጠው፣ ከእነዚህ ውስጥ ሦስት አሸናፊዎች የታወቁ ሲሆን 1ኛ የወጣው ተወዳዳሪ 100ሺ ብር፣ 2ኛ የሆነው 75ሺ ብር፣ 3ኛ ደረጃ ያገኘው 50 ሺ ብር ይሸለማሉ፡፡
በሥዕልና ቅርፃ ቅርፅ 198 ተወዳዳሪዎች ቀርበው 10 አሸናፊዎች የተመረጡ ሲሆን፣ 1ኛ የወጣው 100 ሺ ብር፣ 2ኛው 75 ሺ ብር፣ 3ኛው 50 ሺ ብር የሚሸለሙ ሲሆን ከ4ኛ እስከ 10ኛ የወጡትም የማበረታቻ ሽልማት እንደሚያገኙ ታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ በሰጡት አስተያየት፤ ዳሸን ቢራ በራሱ ተነሣሽነት ስነጽሑፍን ለመደገፍ እንዲህ ያለውን ሽልማት ማዘጋጀቱ የሚያስመሰግነው መሆኑን ጠቅሰው ሌሎቹም የኩባንያውን አርአያ ሊከተሉ እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡ “ስነጽሑፍን እያወዳደሩ ሽልማት መስጠት በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎችን ያበረታታል” ሲሉም አክለዋል ዶ/ር ሙሴ፡፡
ዳኞቹ ከደራሲያን ማህበርም እንደተመረጡ የጠቆሙት ፕሬዚዳንቱ፤ የፀሃፊዎቹ ማንነት በማይታወቅ መልኩ ስነጽሑፉ ብቻ እንዲገመገም መደረጉን ጠቅሰው፤ ፋና ወጊ የሆነው የዳሸን ቢራ የኪነጥበብና ስነጽሑፍ አጋርነት በሌሎችም ኩባንያዎች መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡
የሥነፅሁፍ ምሩቁና የ “የኛ ድራማ ፀሐፊ እስክንድር ሃይሉ በበኩሉ፤ “ዳሸን ቢራ ለግጥም ዘርፍ የሰጠው ክብር፣ ከአለም የጥበብ መድረክ ሊጠፋ ለተቃረበውና በሀገራችንም የመጽሐፍት መደርደሪያ ማድመቂያ ሆኖ ለቀረው የግጥም ዘውግ ትንሣኤ ነው” ሲል አስተያየቱን ለአዲስ አድማስ ሰጥቷል፡፡
ሠአሊ ዘሪሁን የትምጌታ ደግሞ “ሽልማቱ በዚህ ዘመን እንደ እንጉዳይ የፈላውን አርቲስት ሞራል የመስጠት ፋይዳ አለው” ብለዋል፡፡ ሽልማቱ የወጣት ሰአሊያንን መንፈስ የሚያጠናክር በመሆኑ በዳሸን ቢራ ብቻ ሣይሆን በሌሎች ኩባንያዎችም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ያሉት ሰአሊ ዘሪሁን፤ የሽልማት ፕሮግራሙ በአዲስ አበባ ብቻ ሣይሆን ወደ ክልሎችም መስፋፋት እንደሚገባው ገልፀዋል፡፡ የሽልማቱ መጠን ለተሸላሚዎች ቁምነገር ያለው መሆኑን አስተያየት ሰጪው አክለው ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

አለማችን በመጪዎቹ 10 አመታት 28 ስጋቶች ይጠብቋታል

በመጪዎቹ አስር አመታት አለማችንን ይፈታተኗታል ተብለው ከሚጠበቁ ስጋቶች መካከል አለማቀፍ የእርስ በእርስ ግጭቶችና ከውሃ ጋር ተያያዥ የሆኑ ቀውሶች ቀዳሚውን ስፍራ እንደሚይዙ በመካሄድ ላይ በሚገኘው የ2015 የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ጉባኤ ላይ ተገለጸ፡፡የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ሪፖርት እንደሚለው፣ አለማቀፍ ግጭቶች የመከሰት ዕድላቸው ከአየር ንብረት ጋር ተያያዥ ከሆኑ የተፈጥሮ አደጋዎች፣ ከአገራት የአስተዳደር ችግሮች፣ ከመንግስታት ቀውሶችና ከስራ አጥነት የበለጠ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡የህዝቦችን ህልውና አደጋ ላይ በመጣልና ጉዳት በማድረስ ረገድም፣ ከሌሎች አደጋዎች የበለጠ ተጽዕኖ ይፈጥራል ተብሎ የሚሰጋው የውሃ እጥረት እንደሆነ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ በአገራት ውስጥ የሚፈጠሩ የእርስ በእርስ ግጭቶች፣ የተላላፊ በሽታዎች መዛመት፣ አውዳሚ የጦር መሳሪያዎችና ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያያዥ የሆኑ ቀውሶችም ጉዳት ያደርሳሉ ተብለው የሚጠበቁ ሌሎች የአለማችን ቀዳሚ ስጋቶች ናቸው፡፡
በዘንድሮው የአለም የኢኮኖሚ ፎረም በመጪዎቹ አስር አመታት አለማችንን ይገጥሟታል በሚል ያስቀመጣቸው ስጋቶች 28 ያህል ሲሆኑ፣ ስጋቶቹም ኢኮኖሚያዊ፣ አካባቢያዊ፣ ጂኦፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ከቴክኖሎጂ ጋር ተያያዥ ናቸው፡፡
በያዝነው የፈረንጆች አመት 2015 አለማችንን በከፋ ሁኔታ ያሰጓታል ተብለው የተቀመጡት ስጋቶች ጂኦፖለቲካዊ እንደሆኑ የጠቀሰው ሪፖርቱ፣ እነዚህ ስጋቶች በአገራት ውስጥ የሚከሰቱና ክልላዊ ተጽዕኖ የሚያደርሱ የእርስ በእርስ ግጭቶችን ያጠቃልላሉ ብሏል፡፡
በስዊዘርላንድ ዴቮስ በመካሄድ ላይ በሚገኘውና ዛሬ በሚጠናቀቀው 45ኛው የ2015 የአለም የኢኮኖሚ ፎረም አመታዊ ጉባኤ ላይ ከ100 የአለማችን አገራት የተወከሉ ከ2ሺህ በላይ የአገር መሪዎች፣ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች፣ የኩባንያ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈውበታል፡፡
በተያያዘ ዜና ኦክስፋም ኢንተርናሽናል በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ ያወጣው የጥናት ውጤት፣ ካለፉት ስድስት አመታት ወዲህ በአለማችን የሃብት ክፍፍል ኢ -ፍትሃዊነት እየጨመረ መምጣቱን ይጠቁማል፡፡
በመጪው አመት ከአለማችን አጠቃላይ ህዝብ 1 በመቶ የሚሆነው፣ ቀሪው 99 በመቶ ህዝብ ከሚኖረው ድምር የሃብት መጠን የሚበልጥ ሃብት ይኖረዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ ይህ 1 በመቶ ህዝብ በመጪው አመት የዓለማችንን ሃብት ከግማሽ በላይ ጠቅልሎ ይይዛል ተብሎ እንደሚገመት ገልጿል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

ዘመን አይሽሬ የሙዚቃ ስራዎቹን ለአለም ያበረከተው ጀርመናዊ የሙዚቃ ሊቅ ሉድዊንግ ቫን ቤትሆቨን ከፍተኛ ተወዳጅነት ያተረፉ ምርጥ ስራዎቹን የቀመረው፣ የልብ ምቱን መነሻ በማድረግ እንደሆነ በሙዚቃዎቹ ዙሪያ የተሰራ አንድ ጥናት ማስታወቁን ሃፊንግተን ፖስት ዘገበ፡፡ሰሞኑን የወጣው የዋሽንግተንና የሚቺጋን ዩኒቨርሲቲዎች የጋራ ጥናት እንዳለው፣ በአብዛኞቹ ተወዳጅ የሙዚቃ ስራዎቹ ውስጥ የሚደመጡት ያልተለመዱ ምቶች ቤትሆቨንን ለሞት እንዳበቃው የሚገመተው ካርዲያክ አሪዝሚያ የተባለ የልብ ህመም ከሚፈጥረው የልብ ምት መዛባት ጋር የተያያዘ ሊሆን ይችላል፡
ዩኒቨርሲቲዎቹ በጋራ ያሰሩትና የልብ ህክምና ዶክተሮች፣ የህክምና ታሪክ አጥኝዎችና የሙዚቃ ተመራማሪዎች የተሳተፉበት ይህ ጥናት፣ በቤትሆቨን የልብ ጤንነትና በሙዚቃዎቹ መካከል ያለውን ግንኙነት በተመለከተ ጥልቅ ፍተሻ እንዳደረገ ተነግሯል፡፡
ቤትሆቨን መስማት የተሳነው መሆኑ፣ ለልብ ምቱ ትኩረት የሚሰጥበትን ዕድል እንደፈጠረለትና፣ የልብ ምቱ በሙዚቃ ስራዎቹ ላይ ተጽዕኖ ሳይፈጥርበት እንዳልቀረ ተመራማሪዎቹ ገልጸዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በቅርቡ በሁለት ፈረንሳውያን ሙስሊም ወንድማማቾች ፓሪስ ውስጥ የተፈፀመውን የሽብር ጥቃት ተከትሎ በአውሮፓ በተለይም በፈረንሳይና በጀርመን የሚኖሩ አናሳ ሙስሊሞች ጫና በርክቶባቸው ውጥረት ውስጥ ገብተዋል፡፡
ከትላንት በስቲያ በሺዎች የሚቆጠሩ ጀርመናውያን የምዕራቡን አለም “እስላማዊነት” በመቃወም አደባባይ ወጥተው ድምፃቸውን አሰምተዋል፡፡ የነገርየው አያያዝ አላምራቸው ያለ ሙስሊሞችም የገባቸውን ስጋት ለመግለጽ በፊናቸው አደባባይ በመውጣት አቤት ብለዋል፡
ጉዳዩ መገረምን የፈጠረባቸው እጅግ በርካታ ሰዎች ታዲያ አውሮፓውያን አብረዋቸው በሚኖሩት ሙስሊሞች ይህን ያህል ስጋት የገባቸው ቁጥራቸው ምን ያህል ቢሆን ነው የሚል ጥያቄ ማንሳታቸው አልቀረም፡፡
በአውሮፓ የሚገኙ ሙስሊሞች ቁጥር ከተቀሩት ጋር ሲወዳደር አናሳ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ በፈረንሳይና በጀርመን አተካራው ያየለበት ዋነኛው ምክንያት ሌላ ሳይሆን በምዕራብ አውሮፓ ከሚገኙት ሙስሊሞች አብዛኞቹ የሚገኙት በሁለቱ አገራት በመሆኑ ነው፡፡ በሁለቱ ሀገራት ብቻ 4.7 ሚሊዮን ሙስሊሞች ይኖራሉ፡፡
63 ሚሊዮን ከሚሆኑት ፈረንሳውያን ውስጥ 7.5 በመቶ የሚሆኑት ሙስሊም ናቸው፡፡ ይህ ቁጥር ደግሞ በምዕራብ አውሮፓ ከፍተኛው ነው፡፡ 82 ሚሊዮን ከሚሆኑት ጀርመናውያን መካከል ደግሞ የሙስሊሞቹ ቁጥር 5.8 በመቶ ነው፡፡ በፈረንሳይ ከሚኖሩት ሙስሊሞች እጅግ አብዛኞቹ የሰሜን አፍሪካ ተወላጆች ሲሆኑ በጀርመን ከሚገኙት ሙስሊሞች ውስጥ ደግሞ እጅግ የሚበዙት ትውልዳቸውን ከቱርክ የሚቆጥሩ ናቸው፡፡
በእንግሊዝ 2.7 ሚሊዮን ሙስሊሞች ይኖራሉ፡፡ ይህም ከጠቅላላው የእንግሊዝ ህዝብ 4.8 በመቶ የሚሆነውን ይወክላል፡፡ ከነዚህ ሙስሊሞች ውስጥ በጣም የሚበዙት የዘር ሀረጋቸውን የሚመዙት የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ከነበሩት ፓኪስታንና ናይጄሪያ ነው፡፡
በምዕራብ አውሮፓ ከሚኖሩት ሙስሊሞች ውስጥ በብዛት አራተኛ ደረጃ የያዙት መኖሪያቸውን ያደረጉት ጣሊያን ነው፡፡ 2.2 ሚሊዮን የሚሆኑት ሙስሊሞች ከጠቅላላው የጣሊያን ህዝብ ብዛት 3.7 በመቶ የሚሆነውን ይወክላሉ፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በሳኡዲ አረቢያ አንድን ውሻ በከፍተኛ ሁኔታ አሰቃይተው ገድለዋል በሚል ተከሰው ፍርድ ቤት የቀረቡ ሁለት ወጣቶች የ5 አመት እስር ወይም የ500 ሺህ የሳኡዲ ሪያል መቀጣታቸውን አረብ ኒውስ ዘገበ፡፡
ወጣቶቹ ከሳምንታት በፊት ውሻውን በከፍተኛ ሁኔታ ሲደበድቡና ሲያሰቃዩ ቆይተው ለሞት እንደዳረጉት የሚያሳየውና በአንደኛው ወጣት ሞባይል የተቀረጸው አስር ደቂቃ ያህል የሚረዝም የቪዲዮ ፊልም በማህበራዊ ድረገጾች አማካይነት በስፋት መሰራጨቱን ተከትሎ፣ ድርጊቱ ከፍተኛ ተቃውሞ ማስነሳቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ፖሊስ ወንጀለኞቹን ተከታትሎ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጿል፡፡
ፖሊስ ወንጀለኞቹ መኪና እያሽከረከሩ ውሻውን በመሬት ላይ በመጎተት ሲያሰቃዩት እንደነበር በሚያሳየው በዚህ ቪዲዮ ላይ የታየውን የመኪናዋን ታርጋ ቁጥር በመመዝገብ የድርጊቱን ፈጻሚዎች ተከታትሎ በሪያድ በቁጥጥር ስር ማዋሉንም ዘገባው አስረድቷል፡፡
የአገሪቱ የግብርና ሚኒስትር ጃቢር አል ሸሪ፤ ወጣቶቹ በውሻው ላይ የማሰቃየት ወንጀል መፈጸማቸው በመረጋገጡ፣ በአገሪቱ ህግ እና የባህረ ሰላጤው አገራት ባወጡት እንስሳትን የማሰቃየት ወንጀል ህግ መሰረት፣ ፍርድ ቤት ቀርበው ቅጣት እንደተጣለባቸው አስታውቀዋል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

በእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ላይ የደረሰውን የቃጠሎ አደጋ ለመታደግ በተደረገው ርብርብ ላይ ተሳታፊ ለነበሩ አካላት “ምስጋና” የሚቀርብበት ምስጋና የተሰኘ ልዩ የኪነ ጥበብ ዝግጅት በጣይቱ ሆቴል ግቢ ውስጥ ተከፈተ፡፡ ከጥር 14 እስከ ጥር 17 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ ይቆያል በተባለው በዚሁ የኪነ ጥበብ ፕሮግራም ላይ የተለያዩ ሰዓሊያን የስዕል ስራዎች ለዕይታ ቀርበዋል፡፡ ከስዕል ኤግዚቢሽኑ በተጨማሪ ልዩ የሰርከስ፣ የሙዚቃ ትርኢትና ሥነ ግጥሞች የሚቀርቡ ሲሆን ለህፃናት የታሪክ ነገራ እና የስዕል ስራዎች ስልጠናም እንደሚሰጥ አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ገብረፃዲቅ ሀጎሽ ፕሮግራሙን መርቀው በከፈቱበት  ወቅት እንደተናገሩት፤ ታሪካዊውንና ጥንታዊውን ሆቴል ከቃጠሎው አደጋ ለመታደግና የህዝብ ሀብት የሆነውን ሆቴል  ለማዳን ህብረተሰቡ ያደረገውን ተጋድሎ እናደንቃለን ብለዋል፡፡ ሆቴሉ በቋሚነት የቀድሞ ይዘቱንና ታሪካዊነቱን በጠበቀ መንገድ እንዲታደስ የሚደረግበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ጥረት በመደረግ ላይ መሆኑንና ሆቴሉን ከፀሐይና ከዝናብ ለመከላከል የሚያስችል ጊዜያዊ ጥገናው በሆቴል አስተዳደሩ መጀመሩን አመልክተዋል፡፡

Page 4 of 18