Monday, 27 January 2014 08:16

“ፉርሽ ባትሉኝ…”

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…እምጥ ይግቡ ስምጥ ያላወቅነው፣ በፊት የ‘አደባባይ ፊት’ የሚባሉ አይነት የነበሩ ሰዎች አሉ አይደል…ግዴላችሁም፣ ምን አለ በሉኝ ዘንድሮ ምሰው ከገቡበት ጉድጓድ ምስው ወጥተው ብቅ ሳይሉ አይቀሩም፡፡ ከየትም ይሁን ከየት ብቻ ብቅ ብለው ሳንጠራቸው “እዚህ ነኝ” የሚሉን ይመስለኛል፡፡፡ አሀ…የ“ፉርሽ ባትሉኝ…” ዘመን ነዋ! እናማ…እስከ ከርሞ ‘ኢሌክሽን’ ስንት “ፉርሽ ባትሉኝ…” ይኖራሉ የሚል የሪያሊቲ ቲቪ ሾው ይዘጋጅልንማ!
ስሙኝማ…የዚህ አገር ‘ቦተሊካ’ አንዳንዴ የሆነ አሪፍ ነገር አለው፡፡ “ፉርሽ ባትሉኝ…” ማለት ችግር የለውማ! ልክ ነዋ… “ፉርሽ ባትሉኝ…” እያለ ‘አጥር የዘለለውን’ (‘እየዘለለ ያለውን’ ብሎ ማስተካከልም ይቻላል) እስቲ አስቡት፡፡
እንግዲህ ባለችን ሚጢጢ ግንዛቤ በብዙ ሀገራት እንደምናየው ከ‘ቦተሊካው’ እልፍኝ የወጣ…በቃ “ወጣ” ነው፡፡  
ስሙኝማ… ሆሊዉድ አንድ እኛ “ቴክስ” ብለን የምንጠራቸውን፣ በስድስት ጎራሽ ሽጉጥ… አለ አይደል… መልሰው ጥይት ሳያጎርሱ አሥራ ሦስት ጊዜ ተኩሰው አሥራ አንድ የሚጥሉ አይነት ገጸ ባህሪያት አዘውትሮ የሚጫወት ተዋናይ ነበር፡፡ እናማ…ትንሽ ይቀሽምላችሁና ከትወናው መድረክ ይጠፋል፡፡ ጥቂት ዓመታት ቆይቶ ብቅ ይልና አንዱን ዳይሬክተር የሆነ ፊልም ላይ  አንድ ገጸ ባህሪይ እንዲሰጠው ይጠይቃል፡፡
ዳይሬክተሩም “ካው ቦይ ሆነህ ስትጫወት ፈረስ ብዙ ትጋልባለህ…” ይለዋል፡፡ ተዋናይም “እንዴታ!” ሲል ይመልሳል፡፡ ዳይሬክተሩም ምን አለው መሰላችሁ… “ተመልካቹ የሚፈልገውን ልንገርህ አይደል …ፈረስህ ላይ ተቀምጠህ ዘወር ብለህ ሳታይ እስከ ዘላለምህ እንድትጋልብ ይፈልጋል…” አለውና አረፈላችሁ፡፡
እናላችሁ… ዘንድሮ “ዘወር ብለህ ሳታይ እስከ ዘላለምህ እንድትጋልብ ይፈልጋል…” የሚባሉ “ፉርሽ ባትሉኝ…” ሰዎች እየበዙብን ነው፡፡
ታድያላችሁ…“አበቃለት፣ በቃው፣ የምናምን ዴሞክራሲ ማኒፌስቶውን ሰቀለ” (ቂ…ቂ…ቂ…) ምናምን የተባለ ‘ቦተሊከኛ’፣ ምናምነኛ… ድንገት ብቅ ይልና…ስንት ዓመት ፖውዝ ላይ የነበረችውን ቁልፍ ትቶ ፕሌይን ይጫናል፡፡ እኛ የፈረደብንም ‘ተቀባይና ሸኚዎችም’ ዜማና ግጥሙ ለ“ፉርሽ ባትሉኝ…” እንደሚመች ሆኖ የተዘጋጀውን ‘ቲሪሪም ታራራም እንሰማለን፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አንዳንዴ የሆኑ ዝግጅቶች ላይ ነገሬ ብላችሁ እንደሁ አስተናጋጁ፣ “ብሉልኝ፣ ጠጡልኝ” ባዩ አይበዛባችሁም! የዝግጀቱ ባለጉዳዮች መሆናቸውን የምታውቃቸው ሰዎች እኮ ሌሎች ናቸው! እናላችሁ…ሰዎቹ ዋና አጋፋሪ ሆነው ‘አዳራሹ ይጠባቸዋል’። ዋናው ሥራ ላይ፣ ዝግጅቱን እዛ ደረጃ ለማድረስ የጠየቀው ልፋት ላይ ግን ለደቂቃ ብቅ ብለው አያውቁም፡፡ “እሱ ሰውዬ ምነው ጠፋ፣ ውጭ አገር ሄደ እንዴ!” ምናምን ሲባልላቸው የከረሙ ናቸው። እናላችሁ… ሥራው ሁሉ አልቆ የ‘መታያው’ ጊዜ ሲመጣ ምን አለፋችሁ…ከየት ይሁን የት ዱብ ይሉና መድረኩን ይቆጣጠሩታል፡፡ ነገርዬው  “ፉርሽ ባትሉኝ…” ነዋ!
እናላችሁ… በ“ፉርሽ ባትሉኝ” ስትራቴጂ ‘በጨው ደንደስ በርበሬ ሲወደስ’ ይኖርላችኋል። ኮሚኩ ነገር ምን መሰላችሁ… አሁን፣ አሁን የሚሳካላቸው እንደነኚህ አይነት ሰዎች እየሆኑ መምሰሉ፡፡ አስመሳይ መሆን የሚያሳማው ‘ለአፍ’ ነው እንጂ በተግባር ነገርዬው ሌላ እየሆነ ነው፡፡
አባቶቻችን እኮ “ለጌሾ ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ፣ ለመጠጡ ብቻ ከየጎሬው ወጣ” የሚሉት…“ፉርሽ ባትሉኝ” ባይ ሲበዛባቸው ነው፡፡
ምን መሰላችሁ…አንድ ነገር ሲታሰብ መጀመሪያ ‘ሀይ፣ ሀይ’ ባዮች እነኚሁ “ፉርሽ ባትሉኝ…” ባይ ሰዎች ናቸው፡፡
“ፉርሽ ባትሉኝ…” አለ አይደል በብዙ መልኳ ትመጣለች፡፡ ለምሳሌ በአነጋገር ትመጣለች፡፡ ልክ ነዋ፣ ሥራው ቦታ ላይ “ይሄ ሰውዬ የተቀጠረው ቁጭ ብሎ እንትኑን ሲያሽ ሊውል ነው እንዴ!” የሚባልለት ሰው…አለ አይደል…የሆነ ስብሰባ ምናምን ላይ ምን ይላል መሰላችሁ… “አገራችን በተያያዘችው የልማት ጎዳና ሠራተኛው ደከመኝ ሳይል በንቃት…” ምናምን ብሎ የቦሶችን ቋንቋ ለ“ፉርሽ ባትሉኝ…” ስትራቴጂ ቋንቋ ይጠቀምባታል፡፡
የምር ግን… የሆነ የኃይማኖት ትምህርት የሚሰጣችሁ ሰው… “በተያያዝነው የዴሞክራሲ ጎዳና…” ምናምን ቢል “ይህንን ደግሞ ከየትኛው የኃይማኖት ድርሳን ላይ ነው ያገኘኸው…” ምናምን ማለት አያስፈልግም፡፡ አሀ…“ፉርሽ ባትሉኝ…” ስትራቴጂ ሊሆን ይችላላ! (እግረ መንገዴን…በሰላም በምንጓዝበት ጎዳና ‘የግድ’ ያህል እያስቆሙ “የመንግሥተ ሰማያት ቁልፍ እኛ ዘንድ ነው” አይነት ዕውቀት ሊሰጡን የሚሞክሩ ሰዎች መብታችንን እየታገፉ እንደሆነ ልብ ይባሉልንማ!) ስሙኝማ…መቼም ጨዋታ አይደል…አንዳንድ ጊዜ እኮ ሊሉ የፈለጉትን ነገር ብሎ “በሰላም ያውለን” ብሎ መለያየት አሪፍ ነው፡፡ ምን መሰላችሁ…አንዳንድ ጊዜ የዕቁብ ጸሀፊ ለመሰየምም፣ “የሹሮ ዕቃዬን አልመልስ አለችኝ፤ ልብ አድርጉኝ…” ለማለትም…አለ አይደል… “ዓለምን እያስቀና ያለው ልማታችን…” አይነት “ፉርሽ ባትሉኝ” ቀሺም ነው፡፡
ከዚህ በፊት ደጋግመን ያወራናት ነገር ነበረች። ያኔ ገና ‘ወንበሩም እንዳሁኑ ሳይሞቅ’፣ ‘ፊትና ኋላው ሳይለይ’… ሁሉም ሰልፍ ላይ የማትጠፋ መፈክር ነበረች... “የሽግግር መንግሥቱን ቻርተር እንደግፋለን፣” የምትል፡፡ ልክ ፖሊዮ በሽታን ለመከላከል የፖሊዮ ክትባት እንደሚሰጥ “የእነ እንትና ወገኖች ናቸው” ላለመባል አገልግሎት ላይ የምትውል ‘ክትባት’ በሏት፡፡ (ስኳር ይፈቀድልን ብለው የተሰለፉ ‘የማር ጠጅ’ ነጋዴዎች ሳይቀር ይቺን መፈክር ሳይዟት ቀሩ ብላችሁ ነው! ያኔ “ጠጁን የምንጥለው በማር ነው” እንዳላሉን በአደባባይ “የስኳር ያለህ” ሲሉ ሳቅን፡፡  በኋላ ‘ስኳር መላስ’ እንዲህ የአገር ጉዳይ ሊሆን!)
እናላችሁ…ዘንድሮም “በተያያዝነው ፈጣን የልማት ጎዳና…” ምናምን ማለት “የሽግግር መንግሥቱን ቻርተር እንደግፋለን፣” የ‘ክትባት’ አገልግሎት የምትሰጥ መፈክርን የተካች ትመስላለች። እዚህ አገር እኮ በማስመሰልና በመመሳሰል ‘ቅዝምዝሙን ዝቅ ብሎ ማሳለፍ’ ልዩ ጥበብ እየሆነ ነው፡፡ ደግነቱ ቦሶችንም ቢሆን በ“ፉርሽ ባትሉኝ…” ማስቀየሱ እስከዚህ የአይዛክ ኒውተን ጭንቅላት የሚጠይቅ መምሰሉ፡፡
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የቃላት አጠቃቀምን ካነሳን አይቀር ይሄ ለ‘አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች አስተያየት’ የሚያገለግለው ቃልና ሀረግ ውስጥ ሁሉ ነገር  እየገባላችሁ ነው፡፡
ደግሞላችሁ…በአጭሩ ማለቅ የሚችሉ ሀሳቦች እየረዘሙ “”ይህንን ላለመስማት የት አገር ልሰደድ ሊያሰኙ ምንም አይቀራቸውም፡፡
ስሙኝማ… ለምሳሌ…ሚዲያ ላይ ስለ ኳስ ሲወራ… አለ አይደል…“ይሄ ነገር ኳስ ነው ወይስ የሆነ የፖለቲካ ቡድን ማኒፌስቶ…” ምናምን የሚያሰኙ አቀራረቦች ይገጥሟችኋል፡፡ ልክ ነዋ… አሁን ለምሳሌ “የማን ዩናይትድ አሰልጣኝ ዴቪድ ሞይስ በደጋፊዎች ከፍተኛ ተቃውሞ እያስተናገዱ ያሉበት ሁኔታ ነው ያለው…” አይነት አቀራረብ አሪፍ ሚስቶ አይደለም፡፡ “ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸዋል…” አይነት እጥር ምጥን ያለ አባባል እያለ፡፡
እናላችሁ… “አሸንፏል” የምትል እጥር ምጥን ያለች አባባል እያለች “ባርሴሎና ሪል ቤቲስን በሜሲ ጎል ማሸነፍ ችሏል” አይነት ነገር ትንፋሽና ወረቀት መጨረስ እንዳይመስልብንማ፡፡
እናላችሁ…በዛ ሰሞን ኳሳችን ትንሽ አንቀሳቅሶን በነበረ ጊዜ…የዚህ አይነት አቀራረቦች በዝተው ነበር። (ስሙኝማ…እግረ መንገዴን ይሄ ኳሳችን አሁን እንግዲህ ያው የደረሰበት ስፍራ ደርሷል፡፡
እናላችሁ…መለስ ብሎ ከጥቂት ወራት በፊት የጭፈራው ሰሞን የነበረው ‘ፓትሪዮቲዝም’ ምናምን ያልተጫነው ውይይት ለማድረጊያ አሪፍ ጊዜ ነው፡፡ እናማ…ስፖርት ጋዜጠኞቻችን እውነት ቡድን ተመስርቶ ነበር ወይስ በአብዛኛው የግለሰብ ተጫዋቾች ችሎታ ነው ምናምን የሚለውን ተንትኑልንማ! በወቅቱ የነበረውን ‘እውነታውንና ህልሙን’ ለዩልን!)
እናላችሁ…እጥር ምጥን ማለትና ግልጽ መሆን እየተቻለ… “በትናንቱ ጨዋታ ቼልሲ በሜዳው ሽንፈት አስተናግዷል…” አይነት ነገር…አለ አይደል… ትንሽ ግራ ይገባል፡፡ “ተሸንፏል” የምትል እጥር ምጥን ያለች ቃል እያለች! ደግሞ ‘ሽንፈትን ማስተናገድ’ ምንም ማለት እንደሆነ እስቲ አጠያይቃለሁ፡፡
እናላችሁ…“ይቺ ያለበት ሁኔታ ነው ያለው…” ፣ “በተያያዝነው ፈጣን የልማት ጎዳና…” መንግሥት፣ የህብረተሰቡን ችግር ለመቅረፍ ባለው ከፍተኛ ቁርጠኝነት…” የሚሏቸው ጉደኛ ሀረጎች ለ“ፉርሽ ባትሉኝ” እየተጠቅምንባቸው ነው፡፡
እንትናዬ…ያቺ ‘ሳዮናራ’ ምናምን የተባለባት ቀን ስንት ዓመት ሆናት? ግዴለሽም…እሱን ተዪውና…“ፉርሽ ባትይኝ…”
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

በቅርቡ ለዕይታ የበቃውን ቀሚስ የለበስኩ ‘ለት የተሰኘ ‹‹ፊልም›› ከጓደኞቼ ጋር አይተን ስንወጣ በጭብጡ ብዙ ተወያየን፡፡ ለጥበብ እንዲህ መወያየት ምንኛ መታደል ነው፡፡ ከውይይትም ባሻገር ፊልሙን የሰሩትን ባለሙያዎች ልናደንቅና ስለፊልሙ የተሰማንን በጽሑፍ  ልናስቀምጥ ወደድን፡፡
ፊልሙ ሲጀምር ያልተለመደና ቀላል የሚመስል፣ ነገር ግን መሰረታዊ የሆነ ለውጥ አስተውለናል፡፡ የፊልሙ አቅራቢ፣ አዘጋጅ፣ ደራሲ፣ ስምና የስራ ድርሻ ቁልጭ ባለ አማርኛ ቀርቧል፡፡ በአብዛኞቹ ፊልሞቻችን እነዚህ ነገሮች በእንግሊዝኛ እንደሚቀርቡ ልብ ይሏል፡፡
የፊልም ኢንዱስትሪያችን እጅጉን ወደኋላ እንደቀረ አንክድም፡፡  ከመቶ አመታት በላይ ታሪክ ቢኖረውም ወደ ኋላ 100 አመት መጐተቱን ብንናገር ጨለምተኛ አያስብለንም፡፡  ወደ ኋላ የመቅረታችንን ምክንያት፣ ብንነጋገርበት፣ ብናውቀውና ውሉን ብንፈታው፤ በዕምቅ የታሪክ ሃብትና የጥበብ ክምችታችን ተጠቅመን በፊልም ዘርፍ ዓለምን ማስደመም እንችላለን፡፡
ፊልሙ ተጀመረ… እየታየ ነው፡፡
ወጣ ገባ እያለ የሚፈሰው ታሪክ፤ የፊልሙን ገጸ- ባሕርያት ከጭብጡ አንፃር በቅጡ እንዳንፈትሻቸው፣ አድርጐናል፡፡ ለምን ቢሉ? የተቆራረጡ ትዕይንቶች (ሲኖች) በጣም በዝተዋል፡፡
አንደኛው ጓደኛችን “እኔ ፊልሙን የወደድኩት ሙሉአለም እና ሰራዊት ባለመኖራቸው ነው” ብሎ የተለመደ አስቂኝ ትዝብቱን ጣል አደረገልን፡፡ ይሄ ጓደኛችን እንዲህ ያለው ሁለቱ አርቲስቶች ላይ የግል ጥላቻ ኖሮበት አይደለም፡፡ ፊልሙ እንደነሱ ያሉ ለዓመታት  ገንነው የዘለቁ ባለሙያዎች ሳይሳተፉበት፣ አሪፍ ሆኖ መሰራቱን ለማድነቅ ነው፡፡  በእርግጥም አዳዲስ እና ወጣት ፊቶች ማየት በራሱ ዕድልም ድልም ነው፡፡ በአንድ ብቻ እንዳይቀሩብን እንጂ!?
በፊልሙ ወደተሳተፉት ተዋንያን እንምጣ። የኢትዮጵያ ንግድ ም/ቤት ኘሬዚዳንት ወ/ሮ ሙሉ ሰለሞን በፊልሙ ውስጥ መሳተፋቸው ለጥበቡ ያላቸውን ክብር ቢያሳይም የተሰጣቸውን ሚና በብቃት ተጫውተውታል ለማለት ግን አያስደፍርም፡፡ የፊልሙ ዋና ገጸ ባሕርይ ሳምራዊት/ዘሪቱ፤ በከፍተኛ የኑሮ ውጣ ውረድ ውስጥ የምታልፍ ጠንካራ ሴት ሆና ብትቀረጽም  ያንን ስሜት በትክክል አንፀባርቃለች ለማለት ያዳግታል።  ዘሪቱ በከፍተኛ ዝምታ ውስጥ ሆና የዝምታዋን ጥንካሬ፤ ውበትና ሕይወት አላሳየችንም፡፡ ስሜት… ህይወት… እስትንፋስ…ያንሳታል፡፡ ነገሮችን አመዛዝና ከፍተኛ የሕይወት ውሳኔ የምትሰጥ ገጸ-ባሕርይ መሆኗን በብቃት አላሳየችንም፡፡ ስሜቷን ልታጋባብን አልቻለችም፡፡
ሔኖክ አየለ፤ መጀመሪያ ላይ  አስተማሪ ገጸ ባህርይ ተላብሶ ቢተውንም  በፊልሙ መገባደጃ ላይ ግን ድራሹ ይጠፋል፡፡ የገባበት አይታወቅም፡፡ በፊልሙ ውስጥ ለምን ተወለደ…? ለምንስ ድንገት ፊልሙ ሳያልቅ ጠፋ? የትስ ነው የገባው? አይዳ የተሰጣትን ገፀ ባህርይ ውብ አድርጋ ተጫውተዋለች፡፡ መሳይም ግሩም ነው፡፡ የሳምራዊት ጸሎት ጠንካራ ነበር! ሳምራዊት እና ዲበኩሉ፤ ከምትጠልቀዋ ፀሐይ ስር፣ መኪና ተደግፈው የሚታየው ትዕይንት  እጅግ ማራኪ ነው፡፡ ተመስገን ለተፈጥሮአችንና ዘመኑ ለፈጠረው ቴክኖሎጂ! በካሜራ ጥበብ  ይሄን ያህል ለውጥና መሻሻል ማየትም መታደል ነው፡፡ (ገና ብዙ ቢቀርም)
በዚህ ፊልም ተመልካቹ ሳይወድ በግድ ከ1 ሰዓት በላይ በዝምታ እንዲታደም መደረጉን ብዙዎች የወደዱት አይመስልም፡፡ ሳቅ የለም፤ ጭብጨባ የለም፡፡ ዝም ብሎ መመልከት ብቻ፡፡ ዝም ብሎ ማሰብ ብቻ፡፡ ዝም ብሎ መጠየቅ ብቻ፡፡ ዝም ብሎ መመራመር ብቻ፡፡ እንዲህ ነው የሚያደርገው የእነዘሪቱ ፊልም!
እርግጥ ነው በዘመነኛ አገራዊ ፊልሞቻችን  እንዲህ ዝም ብለን እያዳመጥን፤ እያሰብን… ሳንስቅ፣ ሳናጨበጭብ ፊልም አይቶ መጨረስ አልተለመደም፡፡ ለማሰብና ለመመራመር የሚገፋፉ ፊልም ሲኖር አይደል፡፡ ግን ለየትኛው ነው ክብርና ዋጋ የምንሰጠው? የፊልሙ ዋና ጭብጥም “ክብር ለማን እንስጥ” የሚል ነው፡፡
የሁሉንም የልብ ትርታ ማወቅ ባልችልም ለኔ እና ለወዳጆቼ ግን ከፊልሙ ያገኘነው መልዕክት ወደር የለሽ ነው፡፡ በተለይ የፊልሙ መጨረሻ አካባቢ ከመቀመጫ አስነስቶ የሚያስጨበጭብ ታላቅ መልዕክት ይተላለፋል፡፡  ፊልሙ ሲታይ ማንም ያጨበጨበ ባይኖርም፤ አንዳንዱ ቤቱ ሄዶ የሚያጨበጭብ ይመስለናል፡፡ አሊያም ዘመንን ተሻግሮ፤ ‹‹ለሰው ክብር ዋጋ›› የሚሰጥ ትውልድ ሲፈጠር በደንብ የሚጨበጨብለት ፊልም እንደሆነ የእነዘሪቱ ፊልም በሁሉም ነገር የበቃና የተሳካለት ነው ሊባል አይችልም፡፡ ግን በፊልም ዘርፍ ብሩህ ዘመን እየመጣ እንደሆነ አመላካች ነው - በፍቅርና በትጋት ከተሰራ፡፡
የጥበብ ስራ በተለይ ፊልም ተሰርቶ ሲጠናቀቅ፣ በዘርፉ ባለሙያዎች ሊፈተሽና አስተያየት ሊሰጥበት እንደሚገባው አያከራክረንም - ለተመልካች ከመቅረቡ በፊት፡፡  እነ ዘሪቱ ይህን አድርገው ይሆን?
በሕይወት ዘመናችን አንድ ጊዜ የሰራነው ስሕተት ምን ዋጋ አስከፈለን? ስህተቱን ከመስራታችን በፊት ምን ያህል ተጠነቀቅን? ስህተቱን ከሰራን በኋላስ ምን አይነት መፍትሔ ወሰድን? ከስህተታችንስ ምን ተማርን? ከፍተኛ መስዋዕትነት፣ዋጋ እና ክብር ሊሰጥ የሚገባው ለማን ነው? ለምንስ ነው?…. እነዚህን ሃሳቦች በውስጣችን ይቀሰቅሳል - ፊልሙ፡፡
የሰው መንፈስ በኦና ምድር እየተንሳፈፈች በምትገኝበት ዘመን፤ የሰው ክብር ዋጋ-ቢስ በሆነበት በዛሬው ጊዜ፣ ከንዋይ በልጦ ሊዘከር የሚችል ምንድን ነው?... የሚል ጥያቄም ይፈጥርብናል፡፡
ጥያቄና ፍተሻውን ወደ አገር ደረጃም ከፍ ማድረግ ይቻላል፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ ‹‹ቀሚስ የለበሰች ዕለት›› ምን አይነት ስህተት ሰራች…? ምን አይነት ውሳኔስ ወሰነች…? ምን አይነት መፍትሔ አማጠች…?  ውሳኔዋ የሰውን ክብር አመጣ ወይስ አሳጣ? በተደጋጋሚ ቀሚስ መልበስ… በተደጋጋሚ ስህተት መስራት… እናም… ከስህተት አለመማር… ግን በጥበብ ከስህተት መቆጠብ እንችላለን፡፡ በጥበብ ከስህተት መማር እንችላለን፡፡ የእነዘሪቱ ፊልም ይሄን ያስተምረናል፡፡ ወደነዋል፤ አድንቀነዋል፡፡ በርቱም ብለናል - ባለሙያዎቹን፡፡

Published in ህብረተሰብ

                 ባለፈው ሳምንት፣ “ወደ ፍቅር ጉዞ” በተሰኘው የሙዚቃ ኮንሰርቶች ዝግጅት ላይ በተፈጠረው ችግር ዙሪያ ከድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ጋር ያደረግነውን ቃለምልልስ ያቀረብን ሲሆን፤ ስላለፈው ዘመን ታሪክና ስለአዲሱ ትውልድ ፍላጎት ያለውን አስተሳሰብ መግለፁ ይታወሳል። ሁለተኛውን ክፍል እነሆ፡-
የአገሪቱን የሩቅና የቅርብ ጊዜ ታሪክ እየጠቀስክ፣ ታሪካዊ ሰዎችንም እያነሳህ የሰራሃቸው ዘፈኖች፣ ኢትዮጵያውያንን በፍቅር የሚያቀራርቡ ናቸው ብለህ ታምን ይሆናል። ነገር ግን፤ ብዙውን ጊዜ የምናየው ከዚህ የተለየ ነው። የተለያዩ ወገኖች ጎራ ለይተው፣ ታሪክን እየጠቀሱ ሲወዛገቡ ነው የምናየው። እንደማጥቂያ መሳሪያ ይጠቀሙበታል። የውዝግብ ማራገቢያ ከሚሆን፣ ቢቀር አይሻልም?    
ታሪክን የፖለቲካ መጠቀሚያ ማድረግ ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን ታሪክ ጥቅም የለውም ማለትም አይደለም፡፡ ከታሪክ ውስጥ በአድናቆት አክብረን የምንወስደውና የምናሳድገው ነገር እንዳለ ሁሉ፣ ከታሪክ ውስጥ እንዳይደገም አድርገን የምናስተካክለውና የምናሻሽለው ነገር ይኖራል፡፡ ዛሬ በህይወት የሌሉ ሰዎች በጊዜያቸው ካሰቡት፤ ከተናገሩት፣ ከሰሩትና ከፈፀሙት ነገር የምንወርሰውና የምንማረው ብዙ ነገር አለ። ነገር ግን፤ ሁሉንም ነገር መውረስ የለብንም። ከሞቱ ሰዎች ላይ፣ ህይወት ያለው መልካም ስራቸውን መውሰድ እንጂ፤ ከነሱ ጋር አብሯቸው የሞተ መጥፎ ነገርን ማውጣትና ማግዘፍ ምን ይጠቅመናል? በጎ በጎውን እንጂ፣ ክፉ ክፉውን ማጉላት ጥቅም የለውም።
በጨላለመው አቅጣጫ ላይ ካተኮርክና ከተጓዝክ ጨለማ ይውጥሃል፡፡ ወደ ብርሃናማው አቅጣጫ አተኩረህ ስትንቀሳቀስ ደግሞ፣ ትንሿ ጭላንጭ እንኳ እየፈካች እየሰፋች ትመጣለች፡፡ የወደድከው ነገር ወዳንተ ይመጣል የሚባለው ለዚህ ነው፡፡ አንተ ስትቅርበው ወዳንተ ይመጣል፡፡
ታሪክ አበላሽቷል ብለን የምናስበውንና ከብዙ አመታት በፊት የሞተውን ሰው እያነሳን፤ አፈር የተጫነው አፅሙ ላይ ክፉኛ እንጨክናለን። የሞተ ሰው ላይ እንዲያ ከጨከንን፣ በሕይወት ባሉ ሰዎች ላይ ጭካኔያችን ምን ሊሆን እንደሚችል ስታስበው ያስፈራል፡፡ ይሄ ጥሩ አይደለም፡፡
ከምንም በላይ፣ ለሚቀጥለው ትውልድ፣ ለሚቀጥሉት ልጆች ማሰብ ያስፈለጋል፡፡ ሲሆን ሲሆን፣ ታላላቆቻችን የድሮ ቅሬታና አስወግደው፣ ‘አዲሱ ትውልድ የራሱን ታሪክ እንዲሰራ መልካም ነገር እናውርሰው’ ብለው ሲያስቡልን ብናይ እንወዳለን፡፡ ታላላቆቻችን ይህ ካልሆነላቸው፣ ቢያንስ ቢያንስ ብሩህ ዘመን እንዲፈጠር መመኘት አለባቸው ብዬ አስባለሁ፡፡
ፈጣሪ ፍቅር ነው ስለሆነም ከፍቅር ማምለጥ አንችልም። የእለት ተእለት ኑሮ ላይ የማያግባቡን ጥቃቅን ነገሮች ይኖራሉ። ግን የጥላቻ አጥር አናድርጋቸው። ከፈጣሪ ጋር እንግባባለን የምንል ከሆነ፤ ፈጣሪ ሁሉንም የሚያቅፍ ስለሆነ፤ ሁላችንንም የሚያግባባ ፍቅር አለን ማለት ነው፡፡
ሰው መሆንን አሳንሰን፣ ታሪክንም አሳንሰን፣ ፈጣሪንም እንዲሁ ወደ እለታዊ ስሜት አውርደን፣ ወደ ፖለቲካ ንትርክ ደረጃ አጥብበን ማየታችንን ማቆም አለብን። የትኛው ሃይማኖት ነው ፍቅርን የማይሰብከው? የትኛው ሃይማኖት ነው እርቅን የማይደግፈው?
የገብረክርስቶስ ግጥም ላይ አንዲት ጥንቸል አለች፡፡ ጥንቸሏ ከመሬት ጋር የተዋዋለችው ብድር ነበረ፡፡ መሬት የተጠየቀችውን ሰጠች፡፡ ጥንቸሏ አቅም ስላላገኘች ይሁን ፍላጐት ስላጣች አይታወቅም፡፡ ቃሏን አላከበረችም፡፡ እና ለማምለጥ ትሮጣለች፡፡ አሁንም ትሮጣለች፡፡ ከመኖሪያዋ ከመሬት ነው ለማምለጥ የምትሮጠው፡፡ እኛስ እንዴት ነው ከፈጣሪ ፍቅር ለማምለጥ የምንሮጠው? ማን በዘረጋው መሬት ማን ባሰፋው ሰማይ ነው፤ ቂም እያወረስን አሳዳጅና ባለዕዳ ለመሆን የምንሞክረው? በታላላቆቻችን አለመግባባት ምክንያት የመጣ አውድ መሃል የተፈጠረ ትውልድ ሆነን፣ በፍቅርና በመግባባት መቀጠል ስንፈልግ እንዴት በክፉ ይታያል? እንዴት ታናናሾች ይህንን ለታላላቆች ይነግራሉ? እንዴት ታናናሾች ታላላቆችን ይሸከማሉ? ይሄ ከባድ ጥያቄ አለብን፡፡ በየአጋጣሚውና በሰበቡ በሚፈጠር ንትርክ ላይ ሳይሆን፤ ያንን ከባድ ጥያቄ ለመፍታት ነው መነጋገር ያለብን፡፡ ታላላቆቻችንን፤ አለመግባባት እንዲወገድና ፍቅር እንዲሆን፣ አዲሱ ትውልድ በተስፋ አይን፣ አይናቸውን እየተመለከተ ይጠይቃቸዋል፡፡
እስቲ ተዋደዱ ይያያዝ እጃችሁ
አለበለዚያማ በምን ያስታውቃል እኛን መውደዳችሁ?
ቂምን ተሸክሞ አለመግባባትን የሙጢኝ ማለት ውጤቱ ምን እንደሆነ አብረን እያየነው፤ ለምን ወደሚቀጥሉት ልጆች እንዲሸጋገር እናደርጋለን? አንዳንዴ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ቀና ትውልድ የድርሻውን እንዳይሞክር ማወክ፣ የፍቅር ሃሳቡንም ማፍረስ የለብንም፡፡ መድሃኒት አይገፊም፡፡ ፍቅር መድሃኒት ነው፤ ረዥም ጊዜ ከተማመንበት በሽታ የሚያድነን፤ ፈውስ ነው፡፡
የድሮ ሰዎችን ትልቅ ታሪክና ጀግንነት እየጠቀስን የምንኮራ ከሆነ፤ በስህተታቸው ማፈርና የጥፋታቸው ባለዕዳ መሆን የግድ ነው፡፡ ሁለት ወዶ ይሆናል? ከወላጆቼና ከታላላቆቼ ያኛውን ትቼ ይህኛውን ብቻ ልውረስ ማለት ያስኬዳል?
በፍቅር ተገናኝተው ልጆችን ለማፍራት የበቁ ወላጆች፣ የአያቶችን አለመግባባትና ቂም አስታውሰው ሲለያዩ፤ ለልጆቻቸው የሚያወርሱትን አስበው፡፡
የቅርብ ጊዜ ታሪካችን ላይ’ኮ አይተናል፡፡ ለዚህም አይደለም እንዴ፤ ዳህላክ ላይ ያለው ሰውዬ፤ ለተለያትና ለተለየችው ባለቤቱ፤ አለመግባባትና ፀብ በኛ ላይ ያቁም፤ ቅሬታን ለልጃችን አናውርሰው፤ ጥላቻንና ቂምን አናስተምረው የሚላት፡፡ ፍቅርንና መግባባትን ብናስተምረውና መልካም ችግኝ ብናደርገው፤ እኛን መልሶ የሚያቀራርብና የሚያስታርቅ ታላቅ ሰው ይሆናል ይላታል፡፡ አለመግባባት ሊያጋጥማቸው አይገባም ነበር በለን ታላላቆችን ሁሉ መውቀስ ስህተት የመሆኑን ያህል፤ አለመግባባትን ማውረስ ስህተት ነው፡፡ አለበለዚያማ፤ መሻሻልና ማደግ አይኖርም፡፡ እንደ ዳህላኩ ሰውዬ ታላላቆች ለአዲሱ ትውልድ መልካም ሲጨነቁ፣ ከወረሱት ቂም ይልቅ የሚያወርሱት ፍቅር እንደሚበልጥ አስበው መልካም ነገር ሲያስተምሩ፤ የታናናሾች እና የልጆች ስሜት ብሩህ፤ የአገሬው መልክና መንፈስ ያማረ ይሆናል፡፡ የአገር ታሪክ፣ ፖለቲካና መንግስትም ደግሞ፣ የአገሬውን ሕዝብ መምሰሉ የማይቀር ነው፡፡ በቅንነት የወደድከው ሳይመጣ አይቀርም፡፡ አዲሱ ትውልድ ቅን ስለሆነ፤ መልካም ዘመን፣ ድንቅ ታሪክ እየመጣ ነው፤ እድል እንስጠው፡፡
ወደ ፍቅር ጉዞ አይቆምም ብለሃል። ኮንሰርቶቹ ይዘጋጃሉ ማለት ነው?
የትውልድ ድምጽ፤ የትውልድ ራዕይ ነው። ራዕይ ደግሞ አስቀድሞ የተፈፀመ ነገር ግን አሁን የሚገለጥ ነው፡፡ ፍቅር እጅግ ሃያል ስለሆነም ጉዞውን ይቀጥላል፡፡ አገራችን በታሪክም በህዝብም ሰፊ ነች፡፡ አለመግባባት አይፈጠርም ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡ ሰው፤ እንደተገነዘበውና እንዳወቀው መጠን፤ እንደመጣበትና እንደመረጠው መንገድ፤ በመሰለውና በኮረኮረው መጠን ያስባል፡፡ ይሄ ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ፍቅር ይህንን ሰፊ ተፈጥሮ ስለሚያቅፍ፣ በየአጋጣሚው የሚያደነቃቅፍ ነገር ያጋጥመዋል ግን ይጓዛል፡፡
ወደ ፍቅር ጉዞ ተጀምሯል ትላለህ። ግን፣ ዙሪያችንን ስናየው፤ ብዙም ለውጥ የለም። በየምክንያቱ ግጭት፣ በየሰበቡ ውዝግብ ነው፤ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ...። ጉዞው ቢጀመር እንኳ ስንዝር መራመድ የሚችል አይመስልም።
ወደ ፍቅር የምትጓዘው መንገዱ ተመቻችቶ ሲዘጋጅ ብቻ አይደለም፡፡ መንገድ ከጠበበ እያሰፋህ መንገዱ ካልተመቸ እያስተካከልክ ነው የምትጓዘው። በአለም ደረጃም ልታስበው ትችላለህ፡፡ ከባድ አለም ውስጥ ነው የምንኖረው፡፡ በየአገሩ ለጦር መሳሪያ የሚውለው ሃብት፣ ለጦርነት የሚወጣው የገንዘብ ሲታይ፣ ሰላምን ማጣጣም ወይም መፍትሔ ማግኘት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ይነግርሃል። ፍቅር ያሸንፋል ሲባል፤ ክብደት የለውም ብሎ ለማቃለል አይደለም፡፡ ብዙ ነገር የመሸከም ሃይል ስላለው ነው። “ቀላል ይሆናል” የሚለው ዘፈንም’ኮ የተራራው ጫፍ እያለ ከባድነቱን ያሳያል፡፡
ደቂቀ ተስፋን ካየናት አርቀን
ነገ ሌላ ይሆናል ጥሩ ቀን
የተስፋ ጭላንጭሏ ማነስ፣ የተራራው አናት ርቀት፣ የመንገዱ አለመደላደልና አስቸጋሪነት ባይካድም፤ በብርሃን የተሞላው መስክና የተራራው ጫፍ ላይ ለመድረስ መጓዝ አለበት፡፡ ለምን ብትል፤ “ፍቅር ያሸንፋል” ካልን፤ “ለፍቅር እንሸነፋለን” ማለት ነው፡፡ ወደ ወደድከው ነገር ትጓዛለህ፡፡ ለፍቅር ብለህ፡፡
ሁላችንም አሸናፊ ለመሆን እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን አሸናፊነት ማለት የመጨረሻው ውጤት ብቻ አይደለም፡፡ ጉዞውም ጭምር ነው፡፡ “ገዳዩ፣ ገዳዩ” የሚሉ ብዙ ዘፈኖች አሉን፡፡ አሸናፊነን ለመግለጽ ነው፡፡ ግን መተውም ቢሆን የሚያሸንፉ አሉ፡፡ ኢየሱስ ይህንን ያስተማረን ይመስለኛል፡፡ ጥላቻን በይቅር ባይነት ድል በሚያደርግ ቀና የፍቅር መንገድ መጓዝ አሸናፊነት ነው፡፡ “ፍቅር ያሸንፋል” እና “ፍቅር አሸንፏል” ብሎ መናገር ልዩነት የለውም፡፡ ገና ከጅምሩ ጉዞው ውስጥ አሸናፊነት አለ፡፡
አንድ በጣም ስሜትን የሚነካ ታሪክ ላስታውስህ። በእስራኤልና በፍልስጥኤም መካከል ለዘመናት ያላበራው ግጭት፣ ጥፋት እና ሃዘን አሁንም ከየእለቱ ዜና ጠፍቶ አያውቅም፡፡ ነገሩ፤ የሙስሊሞች በዓል የሚከበርበት ቀን ላይ ያጋጠመ ነው፡፡ የታሪካቸው ቅርበት ያህል የብዙዎቹ ኑሮም ቅርብ ለቅርብ ነው፡፡ ከመንገዱ ወዲህ ፍልስጤኤማውያን፣ ከመንገዱ ወዲያ ደግሞ እስራኤላዊያን ይኖራሉ፡፡ ጥዋትም ከሰዓትም በኋላም ማዶ ለማዶ ይተያያሉ። ፋታ የሌለው ጥርጣሬ ግን በሰላም እንዲተያዩ አላደረጋቸውም፡፡
እና በዚያ የበዓል ቀን፤ አባት ለልጁ አዲስ ልብስ ገዝቶለታል፤ አዲስ መጫወቻም አምጥቶለታል፡ በተገዛለት መጫወቻ የተደሰተው ህፃን፣ አዲስ ልብሱን እንዳደረገ ከቤት ውጭ ይጫወታል፡፡ ቦታው ትንሽ ከፍ የለ ነው፡፡ ወደ ታች ብዙም ሳይርቅ የእስራኤላዊያን መንደር አለ፡፡
ከመሃል ባለው መንገድ ላይ ለጥበቃ የተመደቡ የእስራኤል ወታደሮች አካባቢውን ይቃኛሉ። እና ከወታደሮቹ አንዱ፣ ከጉብታው አካባቢ የሰው እንቅስቃሴ ሲመለከት፤ አደጋ ተሰማው፡፡ የተነጣጠረ መሳሪያ ታየው፡፡ ሳይቀድመኝ ልቅደም ብሎ ይተኩሳል፡፡
አባቱ የገዙለትን ውሃ የሚረጭ ሽጉጥ ይዞ ሲጫወት የነበረው ህፃን በጥይት ተመታ፡፡ አባት የተኩስ ድምጽ ሰምቶ በድንጋጤ ከቤት ወጥቶ ይመጣል፡፡ ልጁ ወድቋል፡፡
የእስራኤል ወታደሮችም ተጠግተው አይተዋል፡፡ የተነጣጠረ መሣሪያ የመሰላቸው ነገር ውሃ የሚረጭ ሽጉጥ መሆኑን ሲያዩ ደነገጡ፡፡ ህፃን መጉዳታቸውን ሲያዩ አዘኑ፡፡
በአስቸኳይ ሄሊኮፕተር ተጠርቶ ልጁ ወደ ሆስፒታል እንዲወሰድ አደረጉ፡፡ ነገር ግን ወደ ሆስፒታል የተወሰደውን ህፃን ለማዳን ሃኪሞች ቢጣጣሩም አልተሳካላቸውም፤ ህይወቱ አለፈ፡፡ ይሄ አባት፣ ከዚያች ቅጽበት በኋላ ምን አይነት ሰው እንደሚሆን አስበው፡፡
በሀዘን የተመታው አባት፤ ሃኪሞቹን ጠየቃቸው። “የልጄ ልብ ንፁህ ነው ወይ” አላቸው፡፡ ያልጠበቁት ጥያቄ ነው፡፡ “አዎ ጤናማ ነው” አሉት፡፡
“እንግዲያውስ፣ በልብ ህመም ለሚሰቃዩ እስራኤላዊ ሕፃን አስተላልፉለት” አላቸው፡፡ ያልተለመደ በጣም አስገራሚ ታሪክ ነው፡፡ ሁሉም ሰው ውስጥ ይበዛም ይነስ በጐ ነገር አለ፡፡ አደገኛነት ብቻ ሳይሆን ታላቅነትም የሚወለደው እንዲህ ካለ ጥልቅ ጉዳት ውስጥ ነው፤ ምክንያቱም ፍቅር ሳይሰቃይ አያሸንፍምና፡፡

ለ46 ዓመታት በፖለቲካ ትግል ውስጥ እንደቆዩ የሚናገሩት የ70 ዓመቱ አዛውንት የቀድሞ የኢፌዲሪ ኘሬዚዳንት ኋላም

የተቃዋሚው አንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፤ በቅርቡ ከፓርቲ-ፖለቲካ ራሳቸውን አግልለዋል።
ዶ/ር ነጋሶ፤ ለምን ከአንድነት ፓርቲ ለቀቁ? ስለተቃዋሚዎችና ስለኢህአዴግ ምን ይላሉ? በስጋት ስለሚኖሩበት

የመንግስት ቤት ጉዳይስ?
በእነዚህና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ብሥራተ ገብርኤል በሚገኘው መኖሪያ

ቤታቸው አግኝቶ  በስፋት አነጋግሯቸዋል፡፡


በስጋት ነው የምኖረው መውደቂያዬን አላውቀውም
እኔ የታገልኩት ቁስ ለመሰብሰብ አይደለም
ታጋይ እንጂ ዲኘሎማት አይደለሁም


ለ46 ዓመታት በፖለቲካ ትግል ውስጥ እንደቆዩ የሚናገሩት የ70 ዓመቱ አዛውንት የቀድሞ የኢፌዲሪ ኘሬዚዳንት ኋላም የተቃዋሚው አንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፤ በቅርቡ ከፓርቲ-ፖለቲካ ራሳቸውን አግልለዋል። ዶ/ር ነጋሶ፤ ለምን ከአንድነት ፓርቲ ለቀቁ? ስለተቃዋሚዎችና ስለኢህአዴግ ምን ይላሉ? በስጋት ስለሚኖሩበት የመንግስት ቤት ጉዳይስ? በእነዚህና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ብሥራተ ገብርኤል በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው አግኝቶ በስፋት አነጋግሯቸዋል፡፡ በስጋት ነው የምኖረው መውደቂያዬን አላውቀውም እኔ የታገልኩት ቁስ ለመሰብሰብ አይደለም ታጋይ እንጂ ዲኘሎማት አይደለሁም ለምንድነው የፓርቲ-ፖለቲካ በቃኝ ያሉት? አንደኛው፤ የእድሜ ጉዳይ ነው፡፡ ጳጉሜ 3 ቀን 2005 ዓ.ም 70 ዓመት ሞልቻለሁ፡፡ ለ46 ዓመት ያህል በቀጥታ ህይወቴን ከፖለቲካ እንቅስቃሴ ጋር አቆራኝቼ ኖሬያለሁ፡፡ አሁን ይበቃል የሚል ስሜት አደረብኝ፡፡ ከአሁን በኋላ ለወጣቶች ቦታውን መልቀቅ አስፈላጊ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ በኔ በኩል የተቻለኝን ያህል በፓርቲ-ፖለቲካ ውስጥ አገልግያለሁ፡፡

አሁን ይበቃኛል፡፡ ይህን ስል ትግሉን አቆማለሁ ማለቴ አይደለም፡፡ ሁለተኛ፤ የጤንነት ጉዳይ ነው፡፡ የስኳር ህመምተኛ ነኝ፡፡ በክኒን ነው የምኖረው፡፡ የደም ግፊትም አለብኝ፡፡ እንደልቤ መንቀሣቀስ አልችልም፡፡ በሊቀመንበርነት ከመሩት “አንድነት” ፓርቲ ጋር ስላለዎት የአመለካከት ልዩነት ይንገሩን? ለእኔ ከፓርቲ-ፖለቲካ መገለል ከላይ ከጠቀስኳቸው ምክንያቶች በበለጠ ይሄኛው ዋናው ምክንያቴ ነው፡፡ ጠቅላላ ጉባኤው ሊደረግ በታቀደ ጊዜ፣ በአመራር ውስጥ መግባት የሚፈልጉ እንዲወዳደሩ ብለን ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ ለሊቀመንበርነትም ሆነ ለብሔራዊ ምክር ቤት ለመወዳደር አልፈለግሁም። ያልፈለግሁበት ምክንያት ደግሞ እኔ ወደ አንድነት የመጣሁት በመድረክ ምክንያት ነው፡፡ ከአንድ ዓመት በላይ በፈጀ ውይይት ነው መድረክ የተመሠረተው፡፡ መጀመሪያ መድረክ ወደ ጥምረት ሲሸጋገር ድርጅቶች ናቸው ተስማምተው ጥምረቱን ያቋቋሙት፡፡ እኔ ደግሞ በወቅቱ በየትኛውም ድርጅት ያልታቀፍኩ ስለነበርኩ ሁለት ምርጫ ብቻ ነበረኝ፡፡

ወይ ከመድረክ ጋር ያለኝን ግንኙነት ማቆም አለያም በፓርቲ ጥላ ስር ሆኜ መንቀሣቀስ፡፡ ተሣትፎዬ እንዲቀጥል ስለፈለኩ፣ የግድ ወደ አንድ ፓርቲ መግባት ነበረብኝ። ኘሮግራሙን በማዘጋጀት ብዙ ረድቻለሁ፤ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በጋራ ሊሠሩ የሚችሉበት ጠንካራ ኘሮግራም ነው፣ በጣምም ደስ ስለሚለኝ ተሣትፎዬን መቀጠል ፍላጐቴ ነበር፡፡ ስለዚህ በፓርቲ ለመታቀፍ ከስድስቱ የመድረክ ተጣማሪ ፓርቲዎች የትኛው ኘሮግራም የበለጠ ለኔ ይስማማኛል መምረጥ ነበረብኝ፡፡ እናም አንድነትን መረጥኩ፡፡ በዚህ መልኩ ነበር ወደ አንድነት የመጣሁት፡፡ ከመጣሁ በኋላም መድረክ ራሱን አሣድጐ ወደ ግንባር ተሸጋገርን፡፡ ይህን ስናደርግ በሥራ አስፈጻሚ ደረጃ ብዙ ውይይቶች ነበሩ፡፡ ከየድርጅቱ ሁለት ሰዎች የተወከሉበት የሥራ አስፈጻሚ አለ፡፡ የዚያም አባል ነበርኩ፡፡ የአንድነት ፓርቲ ኘሮግራም ያስቀመጠው አቅጣጫ፤ ሁሉም ፓርቲዎች ቢዋሃዱ ለዚህች ሀገር ጠቀሜታ እንዳለው የሚገልጽ ነው፡፡ ህዝቡም ተመሣሣይ ግፊት ያደርግ ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ነው መድረኩ ከጥምረት ወደ ግንባር የተሸጋገረው። የመድረኩ ሥራ አስፈጻሚ፤ የግንባሩን ኘሮግራም እና የወደፊት አቅጣጫዎች ሠርቶ ለየፓርቲዎቹ ሥራ አስፈጻሚዎች አቀረበ፡፡ የድርጅቶቹ ሥራ አስፈጻሚዎች ከተወያዩበት በኋላ በኘሮግራሙ ተስማሙ፣ አንድነትም ተስማማ፡፡ የአንድነት ሥራ አስፈጻሚ ከተስማማ በኋላ፣ የመጨረሻ ወሣኝ የሆኑት ሁለት አካላት ውሣኔ ይጠበቅ ነበር፡፡ አንደኛው፤ ብሔራዊ ምክር ቤት ሲሆን ሁለተኛው ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡

በዚህ ተዋረድ መሠረት፣ ሥራ አስፈጻሚው የተስማማበትን የግንባሩን ኘሮግራም ወደ ብሔራዊ ምክር ቤት አወረደ፡፡ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ተቀበለው፡፡ ከዚህ በኋላ የመጨረሻ ወሣኙ ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ ጠራንና፣ ጠቅላላ ጉባኤው በበጐ ተቀበለው፡፡ ይሄን አካሄድ እንግዲህ ሁሉም የመድረክ ተጣማሪ ድርጅቶች ናቸው የተገበሩት፡፡ አንድነትን ጨምሮ ሁሉም ድርጅቶች በዚህ ሂደት “ግንባሩ ይፈጠር” የሚለውን ከወሰኑ በኋላ የመድረክ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠራ፡፡ ከእያንዳንዱ ድርጅት በደንቡ መሠረት 10 ሰው ተወከለ፡፡ 10 የአንድነት ወኪሎችም በመድረኩ ጉባኤ ተገኙ፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ አንዳንድ ችግሮች ነበሩ፡፡ አንደኛ፤ መድረክ የገንዘብ ችግር ነበረበት፡፡ ሁለተኛ፤ ደግሞ ሰዎች በትርፍ ጊዜያቸው ነበር የሚሠሩት፡፡ እነዚህ የስራ መጓተቶች ፈጠሩ፡፡ በዚህ የተነሳም አንዳንድ ጭቅጭቆች ተነሱ፡፡ ለምሣሌ ኘ/ር በየነ፤ በግርማ ሠይፉ ላይ ሲሠጡ የነበረው አስተያየት፣ ግርማም ሲሰጠው የነበረው ምላሽ፤ አቶ ቡልቻም በአንድነት ላይ ሲሰነዝሩት የነበረው አሉታዊ አስተያየት…፤ እነዚህ ሁኔታዎች በአንድነት አባላት ላይ ቀላል የማይባል ተጽዕኖ ፈጥረዋል፡፡ እንዴት የመድረክ አባል ሆነን አሉታዊ አስተያየት ይሰነዘርብናል የሚሉ ቅሬታዎች ነበሩ፡፡ ይሄ አሉታዊ ሁኔታ እያለ ከአንድነት አባላት አንድ ሃሣብ መጣ፡፡ “የመድረክን ሂደት እንገምግም” የሚል፡፡ በብሔራዊ ምክር ቤቱም ሂደቱን ገምግመን ማጠናከር አለብን የሚል ውሣኔ ላይ ተደረሰ፡፡ አንድ ኮሚቴም ተቋቋመ፡፡ ድጋሚ የተቋቋመው ኮሚቴ፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ ግምገማውን አጠናቆ፣ ውጤቱን ለብሔራዊ ምክር ቤቱ አቀረበ፡፡ እዚያ ላይ ነው እንግዲህ ችግሮች መፈጠር የጀመሩት፡፡

ገምጋሚ ኮሚቴ ያመጣው አንደኛው የግምገማ ውጤት፤ የመድረክ አባል ድርጅቶች ከአንድነት ኘሮግራም ጋር የማይስማሙ አቋሞችና አላማዎች አሉት፤ በዚህ ሁኔታ ግንባር ፈጥሮ አብሮ መሥራት አይቻልም የሚል ነው፡፡ሁለተኛው ደግሞ ግንባር እንዲሆን የተወሰነው በደንብ ጥናት ተደርጐበትና በቂ ውይይት ተካሂዶበት ሳይሆን አመራሩ ብቻ ያደረገው ነው የሚል ሆነ፡፡ ይሄ ነው በእኔና በአንድነት አባላት መካከል ልዩነት የተፈጠረው፡፡ በእርግጥ ቀድሞም ቢሆን መድረክ እና አንድነት የሚለያዩባቸው አንዳንድ ነጥቦች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ለምሣሌ የህገ-መንግስቱ አንቀጽ 39 ጉዳይ፣ የግለሰብና የቡድን መብት ጉዳይ፣ የመሬት ጥያቄ አፈታት፣ የፌዴራሊዝም ጥያቄ የመሣሠሉት ላይ ልዩነት ነበረው፡፡ እንዴት እነዚህ ልዩነቶች እያሉ ግንባር እናቋቁማለን የሚል ጉዳይም ተነስቷል፡፡ በወቅቱ እኔያቀረብኩት አስተያየት “እነዚህ ልዩነቶች ሊኖሩ ይችላሉ፤ ዋናው በዴሞክራሲያዊ አካሄድ ወደፊት ልዩነቶቹ የሚፈቱበት ሁኔታ በኘሮግራሙ መቀመጡ ነው” የሚል ነበር፡፡ በመድረክ ያሉ ፓርቲዎች ፌዴራሊዝምን የሚደግፉ ቢሆንም በኢትዮጵያ አንድነት እምነት አላቸው፡፡ በኘሮግራሙም መገንጠልን አንደግፍም የሚል አቋም ላይ ተደርሷል። “ልዩነቶች ሊያለያዩን አይገባም፤ አብረን እየሠራን ከምርጫው በፊት ዴሞክራሲያዊ የምርጫ ምህዳር እንዲፈጠር በማድረግ፣ የጋራ ማኒፊስቶ አዘጋጅተን፣ ወደ ፓርላማ እንገባለን ነበር የተስማማነው፤ እኛ ብቻ ሣንሆን ኢህአዴግን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶችም ፓርላማ ይገባሉ፣ ይህን መነሻ አድርገን የጋራ መንግስት እናቋቁማለን፡፡ ዴሞክራሲያዊ የመንግስት መዋቅር ከተፈጠረ በኋላ፣ የመድረኩ ግንባር ተጣማሪዎች የየራሣቸውን ኘሮግራም ይዘው ወጥተው አሊያም አንድ ሆነው የመሠላቸውን ትግል” ይቀጥላሉ በሚል ይሄን ስምምነት የፓርቲው ግምገማ አፈረሰው። በዚህ የተነሣ በሃሣብ ተለያየን፡፡ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ግምገማውን ተቀበለው እኔ ተቃወምኩኝ፡፡

ይሄ የሆነው በ2005 ሚያዚያ ወር ነው፡፡ ሁለተኛው ልዩነት የተፈጠረው ደግሞ የግምገማው ውጤት ምን ይሁን በሚለው ላይ ነው፡፡ የግምገማው ውጤት ወደ መድረክ ይሂድና ለውይይት ይቅረብ፤ በሌላ በኩል ወደ ሚዲያ ወጥቶ ህዝቡ ይወያይበት፤ ይሄ በሁለት ሣምንት ጊዜ ውስጥ ተግባራዊ ይደረግ በሚል ብሔራዊ ምክር ቤቱ ወሰነ። ነገር ግን ጉዳዩ በማግስቱ ከውሣኔው ውጪ ሚዲያ ላይ ቀድሞ ወጣ፡፡ አንድ ግለሰብ ጋዜጣ ላይ በስፋት አወጣው፡፡ ይሄን የመድረክ ሰዎች ሲያዩት ትልቅ ቁጣ አስነሣ፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ አንድነት ራሱን ሂስ ያድርግና ማስተባበያውን በጋዜጣ ያውጣ ወይም ይሄን ባደረገው ሰው ላይ እርምጃ ውሰዱ የሚል ማስጠንቀቂያ ከመድረክ ቀረበ፡፡ የእኔ አቋም “በሚዲያ ቢወጣ ምናለበት፣ ሂስም ማድረጉ ክፋት የለውም” የሚል ነበር፡፡ ሌሎች ግን አልተስማሙም። እንግዲህ በዚህ ላይም በእኔና በሌሎች የፓርቲው አመራሮች መካከል ልዩነት ተፈጠረ ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ በመድረኩ ስብሰባዎች ላይ በሙሉ ህሊናዬ ሆኜ አንድነትን ለመወከል አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ገባሁ፡፡ እንደ ሊቀመንበር የግድ አንድነትን መወከልና የፓርቲውን ሃሣብ ማስተጋባት አለብኝ በሌላ በኩል ደግሞ ህሊናዬ ይሞግተኛል፡፡ በዚህ ምክንያት ዘንድሮ የመድረክ ሥራ አስፈጻሚ ውስጥ ከመግባት ተቆጠብኩ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ደግሞ የውህደት ጉዳይ ተጀመረ፡፡ መኢአድ እና አንድነት ይዋሃዱ ተብሎ ድርድር ተጀመረ፡፡ የቅድመ ውህደት ሠነድም ተዘጋጀ፡፡ በዚያ ሰነድ ላይ እኔና ብሔራዊ ምክር ቤቱ አሁንም ተለያየን፡፡ ብዙ የልዩነት ነጥቦች ናቸው፡፡ እነሱን አሁን መዘርዘር አልፈልግም፡፡ እርስዎ ውህደቱን አይደግፉም ማለት ነው? ውህደት እደግፋለሁ፤ ነገር ግን ሲዋሃዱ በምን ላይ ነው የተመሠረቱት፤ የውህደት ስምምነቱስ ምንድን ነው? በሚለው ላይ አንዳንድ ጥልቀት ያለው ውይይት ሊካሄድባቸው የሚገቡ ጉዳዮች ነበሩ፡፡ የአንድነት ብሔራዊ ምክር ቤት ግን እነዚህን ውይይት የሚያስፈልጋቸውን ጉዳዮች እንዳለ ተቀብሏል። ለምሣሌ የህገ-መንግስቱ አንቀጽ 39 ጉዳይ አለ። አንቀጹ የመገንጠል መብትንም ያካትታል፡፡ ይሄን አንቀጽ የውህደቱ ተደራዳሪ ኮሚቴ አይደግፍም፤ ከህገ መንግስቱም መሰረዝ አለበት ሲል ተስማምቶበታል፡፡ በእኔ በኩል ደግሞ ይሄ የማይቻል ነው፡፡ አንቀጽ 39ን ይደግፋሉ? አዎ! እደግፋለሁ፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው የመብት ነው፡፡ መብቱ ይከበር ነው እንጂ መገንጠል ይኖራል ማለት አይደለም፡፡

ስለዚህ እኔ አንቀጽ 39 ከህገ መንግስቱ ይሠረዝ የሚለውን አልደግፍም፡፡ ይህን ተቃውሞዬን በማሠማበት ጊዜ፣ እኛ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ አንደራደርም የምትል ማሻሻያ በድርድር ሰነድ ላይ ቀረበች፡፡ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ይሄን ሙሉ ለሙሉ ተቀበለው፡፡ በእኔ በኩል አሁንም ይሄ አባባል አስቸጋሪ ነው አልኩ፡፡ መብት አክብረህም አንድ ክፍለ ህዝብ መብቴ አልተከበረም፤ እገነጠላለሁ ካለ ምንድነው የሚሆነው? ወደ ጦርነት ነው የሚኬደው ወይስ ሌላ አማራጭ አለ? እዚህ ላይ ልዩነቶች ተፈጠሩ፡፡ አሁን መጨረሻ ላይ ደግሞ በአንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የምረጡኝ ቅስቀሣ ሲካሄድ ነበር። እዚያ ላይ ጠቅላላ ጉባኤው፤”ውህደቱ ያስፈልጋል በማለት በ3 ወር ጊዜ ውስጥ ከመኢአድ፣ ከአረና እና ከመሣሠሉት ፓርቲዎች ጋር ውህደት እንዲፈጸም” ብሎ የወሰነውን ውሣኔ ኢ/ር ግዛቸው ወሰደና፣ “እንዲያውም ለውህደቱ የተሰጠው ጊዜ ዘግይቷል በአጭር ቀናት ውስጥ እንዲጠናቀቅ አደርጋለሁ” ሲል ቅስቀሣ ማካሄድ ጀመረ፡፡ በተጨማሪም “ከአሁን ጀምሮ በጥምረት፣ በግንባር በመሣሠሉት ጊዜ ማጥፋት አያስፈልግም፤ ውህደት ብቻ ነው የሚያስፈልገው፤ በዚህ አካሄድ ነው የምሠራው” ሲል አቋሙን ገለፀ ፤ በዚህም በከፍተኛ ድምጽ ተመረጠ፡፡ ይሄ ለኔ ሌላ ትርጉም አለው፡፡ የእኔ ግልጽ አቋም ምን መሠለህ? ከተቻለ ውህደት ጥሩ ነው፤ ወደ ውህደት የምትደርሰው ግን ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ ነው እንጂ አድርጉ ስለተባለ መሆን የለበትም፡፡ ውህደት ላይ ሁሉም በአንድ እጅ ማጨብጨብ አለበት፤ በኘሮግራም ሙሉ ለሙሉ መስማማት አለበት፡፡ ይሄን ለማድረግ ደግሞ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ብዙ ውይይት ያስፈልጋል፡፡ እንግዲህ ይሄ የመጨረሻው ውሣኔ ላይ እንድደርስ እና ከፓርቲው እንድወጣ ያደረገኝ ጉዳይ ነው፡፡

በዚህና ከላይ ባስቀመጥኳቸው ምክንያት አቅጣጫው የተለወጠ ይመስለኛል፡፡ እኔ ደግሞ ከአቅጣጫ ለውጡ ጋር ህሊናዬ ተስማምቶ ሊሠራ አልቻለም፡፡ በዚህ ምክንያት ከአንድነት ልወጣ ችያለሁ፡፡ ከፓርቲው ከወጣሁ በኋላ ምን ማድረግ አለብኝ ብዬ ሣስብም የደረስኩበት ድምዳሜ የፓርቲ-ፖለቲካ ይበቃኛል የሚለው ሆነ፡፡ አብዛኞቹ ፖለቲከኞች ከፓርቲ ፖለቲካ ሲገለሉ መጽሀፍ ይጽፋሉ፣ልምዳቸውን ያካፍላሉ፡፡ እርስዎ ምን አሰቡ? ርዕሱንና ይዘቱን መግለጽ አልፈልግም እንጂ መጽሃፍ እየጻፍኩ ነው፡፡ በሌላ በኩል የፖለቲካ ምክር መስጠትና ልምድ ማካፈልም አለ፡፡ እኔ እንዲታወቅልኝ የምፈልገው በአንድነትም ሆነ በመድረክ ላይ “ትክክል አይደሉም” ብዬ ጫና ለመፍጠር አልፈልግም፡፡ እንዲጐዱም አልፈልግም፡፡ ለዚህች ሀገር ፖለቲካ አስፈላጊ ኃይሎች መሆናቸውን በሚገባ አምናለሁ፡፡ ከአንድነት የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ ከነበሩት ኢንጂነር ዘለቀ ረዲ ጋርም አለመግባባቶች ተፈጥረው እንደነበር ይታወቃል፡፡ መነሻው ምን ነበር? ኢ/ር ዘለቀ የድርጅት ኮሚቴ ሰብሳቢ ነበር፡፡ የፓርቲውን የድርጅት ስራ ማንቀሣቀስ ነበረበት፡፡ ግን እንደታሰበው ሣይሆን ድክመት ተፈጠረ፡፡ ኃላፊነቱን እንዲወጣ የተቻለውን ያህል መከርን፤ ግን አልሆነም፡፡ እኔ ነበርኩ ኃላፊነቱን የሠጠሁት፡፡ ሥራው ከተዳከመ አልንና ኃላፊነቱን እንዲለቅ አደረግን፡፡ እሱ ግን ደብዳቤ አልደረሰኝም ብሎ ጋዜጣ ላይ አወጀ፡፡ ይሄ ግን አይደለም፤ በወቅቱ ደብዳቤውን ሰጥቼዋለሁ፡፡ ይሄ ነው የግል ፀብ ያስመሰለው እንጂ የአለመግባባቱ መንስኤ የአሠራር ጉዳይ ነው፡፡ ብሔራዊ ምክር ቤቱ ራሱ በአንዳንድ የዲስፒሊን ግድፈቶች የተነሳ በአባልነቱ ላይ ጥያቄ አንስቶ ነበር፡፡ በእኔና በአሥራት ላይም በየጋዜጦቹ ያወጣቸው ጉዳዮች ነበሩ፡፡

አሁን ደግሞ ኢ/ር ግዛቸው በሥራ አስፈጻሚነት መልምሎታል፡፡ እኔ በዚህ ምንም ቅር አይለኝም፡፡ በግል ግን እኔና እሱ ፀብ የለንም፤ እንቀራረባለን፡፡ በ46 ዓመታት የፖለቲካ ህይወትዎ ለኢትዮጵያ ህዝብ አበርክቻለሁ የሚሉት ጉልህ አስተዋጽኦ ምንድን ነው? ዴሞክራሲና ፍትህ ከሌለ፣ ጭቆናና የሰብአዊ መብት ጥሰት ከተንሰራፋ፣ ሰው ሁሉ መታገል አለበት የሚል እምነት አለኝ፡፡ እኔም በዚህ መርህ መሠረት፣ የራሴን ድርሻ ህሊናዬ በፈቀደው መንገድ እየተጓዝኩ አበርክቻለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ ዴሞክራሲ እንዲኖር፣ የሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ አነቃቅቻለሁ ለማለት እችላለሁ፡፡ ለህሊና መኖር እንደሚቻል ያሣየሁም ይመስለኛል፡፡ ዋናው ነገር ሰው ሁልጊዜ መብቶቹ ካልተከበሩ መታገል አለበት፡፡ ባላደርግሁት ብለው የሚቆጩበት ፖለቲካዊ ውሣኔ ይኖርዎት ይሆን? አየህ… አሁን ለምሣሌ ሶሻሊዝምን እደግፍ ነበር። ደርግ ሶሻሊስት ነኝ ባለ ጊዜ ልደግፈው እችል ነበር፤ ነገር ግን አምባገነን ነው፡፡ ወጣቶችን የሚገድልና መብቶችን የሚደፈጥጥ ነበር፤ በዚያ ሶሻሊስት ስለሆነ ብቻ ሁሉን ሃጢያቶቹን ትቼ እሱን ለመደገፍ ህሊናዬ አይፈቅድልኝም ነበር፡፡ ኦነግን ረድቻለሁ፤ ነገር ግን ኋላ ላይ ተጣላን፤ የተጣላንበት ምክንያት ተበታትኖ በየጐጡ እየተደራጁ የሚደረጉ ትግሎችን ተቃውሜ፣ ወደ አንድ መድረክ መሰባሰብ ይገባል የሚል አቋም በመያዜ ነበር፡፡ በአውሮፓ ይገኙ የነበሩ ሁለት የኦሮሞ ድርጅቶችን ለማቀራረብ ስንቀሣቀስ አንደኛው ድርጅት፤ “ይሄ ጐበና ዳጩ /የሚኒልክ ጦር አዝማች የነበሩት/ ነው “አለኝና አገለለኝ፡፡ ከዚያ በኋላ ኦፒኤልኤፍ ከሚባል ድርጅት ጋር እየሠራን እያለ፣ በ1983 “ዱለ ወልቂጡማ ቢሊሱማ” /ዘመቻ ለነጻነትና ለእኩልነት/ ሲታወጅና ጦሩ ከጐጃም ተነስቶ ወደ ወለጋ ሲጓዝ “ይሄ ደግሞ ቅኝ ግዛት ነው” አሉ፡፡ እኔ በወቅቱ “ይሄ ዳግም ቅኝ ግዛት ሊሆን አይችልም።

ምክንያቱም ደርግ ሌላ ቦታ ተሸንፎ መሠረት ያደረገው ኦሮሚያ ውስጥ ነው፤ ስለዚህ ይህን ኃይል ለመደምሰስ የሚደረግን ዘመቻ ዳግም ቅኝ ግዛት ነው ብሎ ያለመደገፍ ደርግ እንዲቀጥል ማድረግ ነው ብዬ አቋም በመያዝ ከእነሱ ጋር ተለያየን፡፡ እንደገና ወደ ኦህዴድ ከመጣሁ በኋላ በ1993 ዓ.ም ከኢህአዴግ የተለየሁት በአቅጣጫ ልዩነት ነው፡፡ ሶሻሊስት ነን ብዬ አብሬ ስሰራ እነሱ ነጭ ካፒታሊዝምን ነው የምንከተለው ብለው በድንገት አወጁ፤ እኔ ደግሞ በካፒታሊዝም አላምንም፡፡ ምክንያቴም ካፒታሊዝምን እንከተላለን ሲባል እንዲሁ የውሸት በመሆኑ ነው፡፡ ፓርቲዎች በነጻነት መንቀሣቀስ ባልቻሉበት እና የብሔር ጥያቄ ባልተፈታበት ሁኔታ ካፒታሊዝምን እንከተላለን ማለት ሌላ ችግር ያመጣል ብዬ ተለያየን ፡፡ ከዚህ አንጻር ህሊናዬ በሚፈቅደው መንገድ ነው ስሄድ የነበረው ማለት ነው፡፡ ህሊናህ በፈቀደው መንገድ ስትጓዝ ደግሞ የሚቆጭህ ነገር የለም፡፡ ስለዚህ እኔ አንዳችም የሚቆጨኝ ነገር የለም በውሣኔዎቼ ሁሉ ደስተኛ ነኝ፤ የራስን ሃሣብና የህሊና ጥያቄ ገፍቶ ለድርጅታዊ ውሣኔ ብቻ መገዛት በእኔ በኩል ትክክል አይደለም፡፡ አንዳንድ ሰዎች “ልዩነት ቢኖርህም ልዩነትህን ውጠህ እዚያው ብትቆይ ይሻልህ ነበር” የሚል ሃሣብ ያመጣሉ፤ ለኔ ግን ይሄ ትክክል አይደለም፡፡ አንዳንዶች እርስዎ ዶ/ር ነጋሶ፤ “ቀጥተኛ ሁሉን ነገር በግልጽ የሚናገሩ ስለሆኑ ለፖለቲካው የሚሆኑ ሰው አይደሉም ይላሉ…. አዎ! እኔ ዲኘሎማት አይደለሁም፡፡ ቀጥተኛ ታጋይ ነኝ፡፡ ፖለቲካው ወደዞረበት እየዞረ የሚሄድ ፖለቲከኛ ዲኘሎማት አይደለሁም፡፡ ዲኘሎማት የሆኑ ሰዎች ብዙ ጊዜ በዚህም በዚያም ብለው ግባቸው ላይ ለመድረስ ነው የሚጥሩት፡፡ እኔ ያንን አልችልበትም ፡፡ ቀጥተኛ መሆንዎ ያሣጣዎት ነገር አለ? ምን ያሣጣኝ ነገር አለ? /ረጅም ሣቅ/ ምናልባት በቁሣቁስ አሣጥቶኝ ሊሆን ይችላል፡፡ ማቴሪያል ደግሞ ድሮም አልነበረኝም፤ አሁንም የለኝም፡፡ ሰዎች ከኢህአዴግ ጋር ባትጣላ ኖሮ ቢያንስ እንደ መቶ አለቃ ግርማ ትኖር ነበር ይሉኛል፡፡

ያንን ካየህ በቁስ ደረጃ ያጣሁት ነገር አለ ተብሎ ሊታሠብ ይችላል፡፡ ይሄ ያለሁበት ቤትም የኔ አይደለም፤ ከዚህም ውጣ ከተባልኩ ቆይቷል፡፡ መውደቂያ ስለሌለኝ እምቢ ብዬ ነው እንጂ፡፡ አበል የለኝም፣ ከአንድነት ትሠጠኝ የነበረች 3 ሺ 800 ብር አበልም ከበቀደም ጀምሮ ቆማለች፡፡ የምኖረው እንግዲህ ከቀበሌ በማገኛት 1300 ብር ጡረታዬ ነው፡፡ ባለቤቴም መጠነኛ ገቢ የምታገኝባት ሥራ አላት፡፡ እንግዲህ አሁን ያለሁበትን የኑሮ ደረጃ ካየህ፣ አጥተሃል የሚሉኝ ሰዎች ሃሣብ ትክክል ነው ልትል ትችላለህ፤ ነገር ግን ይሄ ለኔ አይቆጨኝም፤ ስሜትም አይሰጠኝም፤ ምክንያቱም እኔ በዚህ አይደለም የታገልኩት ቁስ ለመሰብሰብ አይደለም ፡፡ እስቲ ስለፖለቲካ ፓርቲዎች ደግሞ አናውራ…. በአሁኑ ወቅት ለህዝብ መብትና ጥቅም በሃቀኝነት የሚታገሉ ፓርቲዎች አሉ? በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ሃቀኛ ናቸው አይደሉም የሚለው ግምገማ አስቸጋሪ ነው፡፡ ሁሉም በመሠለው መንገድ እየታገለ ነው፡፡ ለኔ ግን ካየኋቸው ተሞክሮዎች፣ በእርግጥም ሃቀኛ ድርጅት ነው ብዬ የማምነው የህዝብን ሉአላዊ የስልጣን ባለቤትነትን የሚቀበል ፓርቲ ነው፡፡

ለዚህ ተግባራዊነት የሚንቀሣቀስ መሆን አለበት እንጂ ለፓርቲ ኘሮግራም እና ዓላማ ብቻ የሚሠራ መሆን የለበትም፡፡ እዚህ አገር ሁሉም ፓርቲዎች ለህዝብ ነው የሚታገሉት ይባላል። ግን ከገዥው ፓርቲ ጀምሮ በሁሉም ላይ ችግር አያለሁ፡፡ ኢህአዴግ ለስሙ መልካም አስተዳደር፣ ዴሞክራሲ ምናምን ይላል፤ የሚሠራው ግን ሌላ ነው፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችም የምንታገለው ለህዝብ የስልጣን ባለቤትነትና ለዴሞክራሲ ነው ይላሉ፤ ያ ከሆነ በጋራ መሥራትን ለምን ይፈሩታል? ከዚህ አኳያ ከተመለከትነው ሁሉም ፓርቲዎች ላይ የሃቀኝነት ጥያቄ ይነሣባቸዋል ማለት ነው፡፡ እርሶ ሲመሩት የነበረው አንድነት፤ “ገዥው ፓርቲ ሀገሪቱን በብሔር ከፋፍሎ ኢትዮጵያዊነትን ሸርሽሯል” የሚል አመለካከት አለው፣ በሌላ በኩል ደግሞ በቅርቡ “የቁጫ ብሔረሰብ ማንነቱ ለምን አይከበርም ሲል የብሔር መብት ጥያቄ ያነሣል፡፡ እነዚህ ነገሮች እርስ በእርሣቸው አይጋጩም? በአንድነት ኘሮግራም ላይ አንድ አንቀጽ አለ። የኘሮግራሙ 3.1.5 አንቀጽ፤ “አብይ የፖለቲካ ጥያቄዎች በፖለቲካዊ መንገድ ነው የሚመለሱት፤ ይሄም በህጋዊና በዲሞክራሲያዊ መንገድ፤ በውይይት እና በድርድር ነው፤ በዚህ መንገድ አብይ ጥያቄዎች ካልተፈቱ ወደ ህዝብ ነው የሚሄደው” ይላል፡፡ ይሄ አንቀጽ እውነት ይታመንበታል ወይ የሚለው ለኔ ጥያቄ ነው፤ ለእኔ ከፖለቲካ ጥያቄዎች አንዱ የብሔር ጥያቄ ነው፡፡ አብይ የፖለቲካ ጥያቄ እንደሚኖር የምታምን ከሆነ፣ አንቀጽ 39ን መቃወም የለብህም ማለት ነው፡፡ የብሔር ጥያቄ የምታምንበት ከሆነ “በኢትዮጵያ አንድነት አልደራደርም” አትልም ማለት ነው፡፡ እኔ ተቃርኖውን በዚህ መንገድ ነው የማየው፡፡የቁጫን ህዝብ በተመለከተ ግን የአንድነት ኘሮግራም ላይ የግለሰብ እና የቡድን መብት መከበር እንዳለበት ተቀምጧል፡፡ የቁጫ ህዝብ አንድ ቡድን ነው፤ አንድነት የማንነት ጥያቄ ሣይሆን የመብት ጥያቄውን ነው የደገፈው፡፡

ጥያቄያቸው ይሰማ ነው ያለው። እነሱ የጠየቁት ይሰማ ከሚለው አኳያ ነው እንጂ ማንነታቸው ይታወቅ የሚል አይደለም፡፡ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል ጥሩ አቅጣጫ ይዟል፤ በቀጣይ ምርጫም የስልጣን ባለቤት ሊሆን ይችላል ብለው ተስፋ የጣሉበት ፓርቲ አለ? አሁን ይህን ማለት ጥሩ አይደለም፡፡ ይሄኛው ከዚህ የተሻለ ነው ብዬ መወሰንም አልችልም፡፡ ፓርቲዎች ይደራጁ፣ ይሞክሩ፤ ከተመረጡ ይመረጡ፤ አሁን አለ ወይም የለም የሉም ብዬ ከደመደምኩኝ ጥሩ አይሆንም ነገር ግን ሁሉም በተቻለ መጠን ከልባቸው ለህዝብ የስልጣን ባለቤትነት ይታገሉ፡፡ በኢህአዴግ በኩልም የፖለቲካ ምህዳሩን መክፈትና ሁሉንም ፓርቲዎች በእኩል ማስተናገድ አለበት፡፡ ፓርቲዎች ከአሁን ጀምረው ተሰባስበው፣ ለዲሞክራሲ መሥራት አለባቸው፡፡ አሁን ጥሩ እየሠሩ ነው የሚሏቸው ፓርቲዎች የሉም? እየሞከሩ ነው ሶስተኛ አማራጭ አለ። አክትቪዝምን የሚከተሉ አሉ፣ አንድነትም፣ መድረክም…. ሌሎችም አሉ፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ግን ይሄኛው ይሻላል ያኛው አይሻልም ወይም ሁሉም አይረቡም በሚለው ላይ ግን አስተያየት መስጠት አልፈልግም፡፡ ከፓርቲ ፖለቲካ ራስዎን ቢያገሉም በግልዎ የፖለቲካ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል፡፡ በግልዎ ለፓርላማ መወዳደርስ? የለም ይበቃኛል፡፡ ወደ ፓርላማው መግባትም አልፈልግም፡፡ ምናልባት በፓርቲዎች መካከል ስምምነት ለመፍጠር፣ በኢህአዴግና በተቃዋሚዎች መካከል መቻቻል እንዲኖር፤ ሁሉም በብሔራዊ ጉዳይ እንዲስማማ የማድረግ እንቅስቃሴዎች ለመሳተፍ እሞክራለሁ፡፡ ምናልባት ኢህአዴግ፤ ለሁለተኛ ጊዜ አብረውት እንዲሰሩ ወይም በማማከር እንዲያግዙት ቢጠይቅዎ ፈቃደኛ ይሆናሉ? ምክር ከፈለገ አብሬ ብሠራ ምንም ችግር የለብኝም፡፡

ስብሰባዎች ካሉ እሣተፋለሁ፡፡ በቅርቡ አቶ ስብሃት ነጋ በሂልተን ሆቴል አንድ ሴሚናር አዘጋጅቶ ጋብዞኝ ነበር፡፡ እዚያ ላይ ተሣትፌያለሁ፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጆርናሊዝምና ኮሚኒኬሽን ኢንስቲትዩት የፌዴራሊዝም ጥያቄ ላይ በተደረገ ውይይት ጋብዞኝ አስተያየቴን ሰጥቻለሁ፡፡ በቅርቡም ሌላ ውይይት ላይ እንድገኝ ጠይቀውኛል፡፡ የዚህ ዓይነት ሁኔታ ከተፈጠረ ለምን እምቢ እላለሁ፡፡ የመድረክ ሰዎች ብዙዎቹ እኮ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ናቸው፡፡ ዩኒቨርሲቲ ከቀጠረኝ የመንግስት ስለሆነ አልፈልግም አልልም፡፡ ኢህአዴግም በምክር ከፈለገኝ አማክረዋለሁ፤ “ይሄን ብታደርግ ይሻላል፤ ይሄ ጥሩ አይደለም” ለሚለው ሃሣብ በሩን ከከፈተ ጥሩ ነው፡፡ ድሮ የትግል አጋርዎ የነበሩት የቀድሞ የኦነግ አመራር አቶ ሌንጮ ለታ “ወደ ሠላማዊ ትግል ተመልሻለሁ አዲስ ፓርቲም አቋቁሜያለሁ” ማለታቸው ለኢትዮጵያ ፋይዳው ምንድን ነው? ተቀባይነትስ ያገኛሉ ብለው ያስባሉ? በአገር ውስጥ 72 ፓርቲዎች ስላሉ የእነሱ አዲስ ፓርቲ ይዞ መምጣት ብዙም ፋይዳ የለውም፡፡ ከሌሎች ጋር ቢቀናጁ ይሻላል የሚል ሃሣብ አለኝ። ምክንያቱም በኦሮሞ ስም የተደራጁ ብዙ አሉ፡፡ “በኢትዮጵያ ጥላ ስር መኖር ይቻላል” ከሚለው አኳያ ስንመለከተው የእነ ሌንጮ መምጣት የሚጨምረው እሴት ይኖራል፡፡

በሌላ በኩል በአጠቃላይ በኦሮሚያ ውስጥ የሚንቀሣቀሱ ፖርቲዎች ሁለት አቅጣጫ ነው የያዙት፡፡ አንዱ እንገንጠል፣ ሌላው በኢትዮጵያ ጥላ ስር ሆነን እንኑር የሚሉ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ጥላ ሥር እንኑር ለሚሉት የእነ ሌንጮ መመለስ ድጋፍ ሲሆን እንገንጠል ለሚሉት ደግሞ ድጋፉን ያጐድልባቸዋል፡፡ አገር ውስጥ በሠላማዊ መንገድ ሲታገሉ የቆዩትን የኦሮሞ ድርጅቶችና የእነ ሌንጮ ፓርቲ ውዝግብ ውስጥ እንዳይገቡ እፈራለሁ፡፡ በሌላ በኩል ኦነግ በእነ ሌንጮ ላይ ትግሉን ገድለውታል የሚል ሃሣብ የሚያነሣ ይመስለኛል፡፡ በተለይ ለኦሮሚያ “ህዝብ በኢትዮጵያ ማዕቀፍ እንኑር” የሚለውን አስተሣሠብ የበለጠ ያጠናክራል፡፡ በእኔ እይታም የኦሮሞ ህዝብ ይሄንን ነው የሚፈልገው፡፡ የዳያስፓራውን ፖለቲካ እንዴት ይገመገሙታል? አንዳንዶች የሃይማኖት ተቋማትን በዘር እስከ መከፋፈል ደርሰዋል በሚል ይተቻሉ… ጨለምተኛነት አለ፣ አክራሪነት አለ፣ በሀይማኖትና በጐሣ መከፋፈል የእነ ሌንጮ ፓርቲ ተቀባይነት ያገኛል ወይ የሚለው አስቸጋሪ ጥያቄ ነው፡፡ እኔ 17 ዓመት ጀርመን ሀገር ስለኖርኩ አውቀዋለሁ፤ ከአንዳንድ የኦሮሞ ጓደኞቼ ጋር የምጣላው ለዚህ ነበር፡፡ ለምሣሌ እኔ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ “አዲስ ዘመን” ጋዜጣ አስመጥቼ ሳነብ ሲያዩ፡፡ “እንዴት ይሄን የአማራ ጋዜጣ ታነባለህ?” ይሉኛል ወይም መንገድ ላይ ሰውን በአማርኛ ሰላም ስል ደስ አይላቸውም ነበር፡፡ እንዲህ ያሉ ሁኔታዎች ዛሬም አሉ፡፡ እዚያ ነጻነት አለ፤ ግን ነጻነት በዚህን ያህል ደረጃ መከፋፈላቸው፤ በአገር ቤቱ ፖለቲካ ላይ ተጽዕኖ አለው፡፡ ከኢህአዴንም ከአንድነትም የወጡት በአቅጣጫና በአመለካከት ልዩነት ነው፡፡ ከሁለቱ የበለጠ ያልተመቾት የቱ ነው? በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡

የኢህአዴጉ በአንድ በኩል “የህወኃት አንጃ” ያላቸውን ሰዎች ያስተናገደበት መንገድ አስከፊ ነው፡፡ ያኔ እኔ ምርጫ ቦርድ ብሆን ኖሮ፣ ኢህአዴግን ሠርተፊኬቱን እሠርዝበት ነበር። ምክንያቱም ሰዎቹ ህገ-መንግስቱና የምርጫ ህጉ በሚፈቅደው መንገድ አይደለም የተባረሩት፡፡ ዴሞክራሲያዊ መብታቸው አልተጠበቀም ያ ለኔ ብዙ ራስ ምታት ፈጥሮብኛል፡፡ ከዚያ በኋላ ደግሞ በሰኔ ላይ አቅጣጫ መቀየር መጣ፡፡ እንግዲህ እሱ እና አሁን በአንድነት ያጋጠመኝ ይመሣሠላል፡፡ እኔ ላይ ጭቅጭቅና አለመግባባት በመፍጠር ረገድ ግን የኢህአዴጉ ነው የሚበዛው፡፡ ከአንድነት ስወጣ በእድሜ መግፋት እና በጤና እንደምለቅ አስቀድሜ ስለገለፀኩ ከጭቅጭቅ ያመለጥኩ ይመስለኛል። አንድነት በዚህ በኩል ሊበራል ነው፡፡ ሃሣብን ያከብራል፤ ያለ ቅሬታ ነው የተለያየነው፡፡ የኢህአዴጉ ግን የልብ ድካም ሁሉ ያመጣብኝ ነበር፡፡ አዲሱን የኢፌዲሪ ኘሬዚዳንት በተመለከተ አስተያየት አለዎት? የኘሬዚዳንት ተቋም ኃላፊነትና ተግባር እንዲሆን የተፈለገው የእንግሊዙ ሲስተም ነው፡፡ በእንግሊዝ ንግስቲቱ ሀገርን ትወክላለች፤ ሆኖም ግን እዚያ ብዙ ጥንቃቄ አለ ንግስቲቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ትደግፋለች፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፊናው እያንዳንዷን ነገር ማማከር፣ ሪፖርት ማድረግና የውሣኔ ሃሣቦችን መቀበል አለበት፡፡

እዚህ ያ የለም፤ አሁን ተፈጥሮ እንደሆነ አላውቅም፡፡ እኔ ባለሁበት ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አማክሮኝ አያውቅም፡፡ እኔም ብዙ ጊዜ የኦህዴድን የድርጅት ሥራ በመሥራት ላይ ተጠምጄ ስለነበር በሌሎቹ ሥራዎች ላይ አልተንቀሣቀስኩም። ኘሬዘዳንት ግርማም በህመም ምክንያት አልተንቀሣቀሱም፡፡ የአሁኑ እንግዲህ እየተንቀሣቀሱ እንደሆነ አላውቅሁም፡፡ ሆኖም ግን በእድሜም በጤናም ደህና ናቸው፡፡ በትምህርትም ደህና ናቸው፤ በግርማ ሞገስም ገጽታቸው ለኘሬዚዳንትነት አይከፋም፡፡ ነገር ግን የኛ ህገ መንግስት ለኘሬዚዳንቱ ስልጣን አይሠጥም፡፡ በግል ቂም አለው ወይ እንዳትለኝ እንጂ የአሁኑ ኘሬዘዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ እና ዳዊት ዮሐንስ ነበሩ ያኔ በእኔ ላይ የፈረዱት። ሁሉን ነገር እንዳጣ የወሰኑት እነሱ ናቸው፡፡ በ97 ዓ.ም ምርጫ ጊዜ ምርጫ ውስጥ ገብተሃል፤ ብሎ አዋጅ ጥሰሃል ስለዚህ ጥቅማ ጥቅሞችህንና መብትህን ታጣለህ” ብለው የወሰኑት እነሱ ናቸው፡፡ ዶ/ር ሙላቱ ያኔ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ነበር፡፡ አሁን የሚኖሩበት ቤት ከኘሬዚዳንትነት ሲለቁ የተሰጥዎ ነው? ከኘሬዚዳንትነት የለቀቅሁ እለት የት እንደሚያስገቡኝ ጨንቋቸው፣ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አጠገብ ካለች አንዲት ቤት ነበር ያስገቡኝ፡፡ እዚያ 6 ወር ከኖርን በኋላ ወደ ቦሌ ወሰዱን፤ ጥሩ ቤት ነበረች፤ 3 መኝታ ቤት አላት፣ ቢሮ ግን የላትም፡፡ ግድግዳውና መስታወቱ ተሠነጣጥቆ በጋዜጣ ነበር እየሸፈንን ሁለት አመት ቆየን፡፡ ከዚያ አሁን ያለሁበት ቤት አመጡን፡፡ አሁን ከፓርቲ ፖለቲካ ሲገለሉ ጥቅማ ጥቅሜን መለሼ ላገኝ እችላለሁ የሚል ተስፋ የሎትም? የቀድሞ ኘሬዚዳንት ከወገንተኛ የፖለቲካ እንቅስቃሴ መገለል አለበት ይላል፡፡ አተረጓጐሙ እንግዲህ በኢህአዴግ እይታ አፍህን ዘግተህ ተቀመጥ ነው፡፡ የመጀመሪያው ማስጠንቀቂያ የደረሰኝ አዳማ ላይ የሮያል ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በክብር እንግድነት ጋብዞኝ ባደረግሁት ንግግር ነው በወቅቱ ኢህአዴግ እንደሚለው “ልማት ያስፈልገናል፣ ልማት እንዲመጣ ዴሞክራሲ ያስፈልገናል፣ ዴሞክራሲ እንዲመጣ የመብት ጥያቄዎች መልስ ያስፈልጋቸዋል” አልኩ። አክዬም፤ “በኦሮሚያ ሠላም ስለሌለ እንደሌሎች አካባቢዎች ልማት እየተፋጠነ አይደለም፣ ይህ የሆነው ደግሞ ዲሞክራሲ ስለሌለ ነው” ብዬ ተናገርኩ፡፡ ከሁለት ሣምንት በኋላ ዳዊት ዮሐንስ ጠራኝና የኦሮሚያ ክልል ከሶሃል አለኝ፡፡ “ፖለቲካ ውስጥ እየገባህ ነው፤ ከአሁን ሰዓት ጀምሮ በዚህ ሁኔታ የምትቀጥል ከሆነ ጥቅማ ጥቅምህን ታጣለህ” አለኝ፡፡ “የፈለከውን አድርግ፤ እኔ አቋሜን ከማራመድ ወደ ኋላ አልልም” አልኩትና ሄድኩ፡፡ በዚያው ውሣኔያቸውን ተግባራዊ ማድረግ ጀመሩ እኔም ክስ መስርቼ፣ ከስሼ ሰበር ደርሶ ለእነሱ ተወሰነ፡፡

የሚሠጠኝ አበል፣ መኪና፣ ሠራተኞች፣ ቤት የመሣሠለውን አጣሁ እኔ አሁን ከፓርቲ ፖለቲካ በመውጣቴ በድጋሚ ጥቅማ ጥቅሜን አገኛለሁ የሚል ተስፋ የለኝም፡፡ ኢህአዴግ ይህን ካደረገ ተለውጧል ማለት ነው፡፡ እኔ ግን አሁንም አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ መተቸቴንና መቃወሜን እቀጥላለሁ፡፡ ለኘሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ በ4ዐዐሺህ ብር መኖሪያ ቤት መከራየቱን የሚተቹ ወገኖች አሉ? እርስዎ ምን ይላሉ? እኔም ከሚቃወሙት ወገን ነኝ፡፡ በዚህች ድሃ ሀገር ለምን ይሄ አስፈለገ? አንደኛ እኔ እንደሠማሁት ቤቱ 2ዐ ክፍሎች ነው ያሉት፡፡ አሁን በተሻሻለው ህግ ደግሞ ኘሬዚዳንቱ ከ3 እስከ 4 ክፍል ቤት ይሠጠዋል ነው የሚለው፡፡ በሀገራችን የድህነት ሁኔታ በ4ዐዐ ሺህ ብር ቤት መከራየት ያስፈልጋል ወይ?” የሚለውን ጥያቄ ከሚያቀርቡት ወገን ነኝ፡፡ አሁን እርስዎ የሚተዳደሩት በምንድነው? እስከአሁን ድረስ ለኢኮኖሚ የሚጠቅመኝን ሥራ አልሠራሁም፡፡ ለፒኤችዲ የጻፍኳት መጽሃፍ አለች ከዚያች ትንሽ ገንዘብ አግኝቻለሁ፡፡ ከዚያ “ዳንዲ የነጋሶ መንገድ” ከሚለው መጽሃፌ ደግሞ ሩብ ያህሉን አግኝቻለሁ፡፡ ሌላው ኦሮሚያ ኢንተርናሽናል ባንክ ሲቋቋም፣ ዘመዶች አክስዮን ግዛ ብለውኝ በ4 ሺህ ብር የገዛሁት አለኝ፡፡ ከዚያ በስተቀር ምንም የኔ የምለው ሃብት የለኝም፡፡ ደምቢዶሎ ያለው የወላጆቻችን ቦታ ተወስዷል፡፡ እዚህም የራሴ የምለው ቤትም ሆነ ቦታ የለኝም፡፡ ከዚህ ከምኖርበት ቤትም ውጣ ብለውኝ ነበር፡፡ ነገር ግን አቤቱታ በማቅረቤ እስከአሁን ድረስ ዝም ብለውኛል፡፡ ግን በፈለጉ ጊዜ እንደሚወስዱት አውቃለሁ፡፡ ዋስትና የለኝም፤ በስጋት ነው የምኖረው፤ ቀጣይ መውደቂያዬንም አላውቀውም፡፡ ልጆችዎ የት ናቸው? ልጃችን አሁን የፊልም ትምህርቷን ጨርሳ ሎስአንጀለስ ውስጥ ሥራ እያፈላለገች ነው፡፡ ከቀድሞዋ ባለቤቴ የወለድኳቸው ደግሞ አንደኛው ጀርመን ሀገር ይሠራል፤ ሴቷ ደግሞ ለንደን ነው ያለችው፡፡

ልጅ ወልዳለች አሁን የእነሱ ጉዳይ አያሣስበኝም፡፡ እኔ አንድ ነገር ብሆን ባለቤቴ ምን ትሆናለች የሚለው ነው የሚያስበኝ፡፡ በቅርቡ በኢቲቪ በተላለፈ ዶክመንተሪ ላይ እርስዎና ሌሎች የአንድነት አመራሮች በ“ኢሳት” ጣቢያ ላይ ቃለ ምልልስ መስጠታችሁ ተተችቷል... ዶክመንተሪውን ተከታትየዋለሁ፡፡ የመጀመሪያው ላይ አሥራት ጣሴ፣ እኔ እና ዳንኤልን ነበር የሚያሳዩት ሁለተኛው ላይ እኔና ዳንኤል ኢንተርቪው ሰጥተዋል የሚል ትችት አቀረቡ ያቀረቡት፡፡ በቃለ ምልልሱ ምን እንዳልን ግን አላቀረቡም፡፡ ይህ እንግዲህ እነ ነጋሶ ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት አላቸው ለማለት ተፈልጐ እንደሆነ ይገባኛል፡፡ ይህ የአሁኑ ሌላ የኘሮፖጋንዳ ሥራ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ጨዋታ ጥሩ አይደለም፡፡ የትም አያደርሣቸውም፡፡ ቢተውት ጥሩ ነው፡፡ ለወደፊት እርሶ ምን ዓይነቷን ኢትዮጵያ ለማየት ይመኛሉ? መብትና ነጻነት የተከበረባት፣ ሁሉም የፈለገውን የሚያስብባትና ያሻውን አቋም የሚገልጽባት ኢትዮጵያን ባይ ደስ ይለኛል፡፡ ሰው በፈለገው መንገድ እየተደራጀ የፈለገውን ተቃውሞ በመንግስት ላይ የሚያቀርብባት፣ የፈለገውን ግለሰብ እና ፓርቲ የሚመርጥባት፣ዜጐች በሁሉም ጉዳዮች ላይ ወሣኝ የሚሆኑባት ኢትዮጵያን ማየት ምኞቴ ነው፡፡ የሰው ልጅ ሙሉ ነጻነቱ ከተከበረለት፣ አቅሙን መጠቀም ይችላል፤ ያኔም ልማት ይመጣል፡፡ ይች ሀገር በተፈጥሮ ሀብት እግዚአብሔር የባረካት ነች፣ ይህን ተጠቅመን ድህነትን የምንቀርፍባትን ኢትዮጵያ እመኛለሁ፡፡

መንግስት፤ ተቋሙ የተቃዋሚዎች የፕሮፖጋንዳ ማስፈፀሚያ ነው
“በኢትዮጵያ የነፃ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ ነው”
“በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሳት ነውር ሆኗል” ብሏል

የኢትዮጵያ መንግስት የዜጐችን  ሰብአዊ መብት በስፋት ይጥሳል በማለት ተደጋጋሚ ወቀሳና ስሞታ የሚያቀርበው ሂውማን ራይትስ ዎች የተሰኘው አለማቀፍ የመብት ተቋም፤  ሰሞኑን ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ፣ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ነፃነት ይበልጥ መጥበቡንና የነጻ ሚዲያ ህልውና አደጋ ላይ መውደቁን ገለፀ፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ የተቋሙን ሪፖርት ያጣጥላል፡፡ በአገሪቱ ውስጥ የፖለቲካ ነፃነትና የፖለቲካ እንቅስቃሴ የማካሄድ እድል (የፖለቲካ ምህዳር) እየጠበበ የመጣው ከምርጫ 97 በኋላ መሆኑን የገለፀው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ከዚያ ወዲህ በመንግስት የፀደቁትን የፀረ - ሽብር እና የበጐ አድራጐት ማህበራት አዋጆችን በምሳሌነት ጠቅሷል፡፡ በፀረ - ሽብር አዋጁ መነሻነት ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ሽብርተኛ ተብለው እንደታሠሩና እንደተፈረደባቸው የተቋሙ ሪፖርት ጠቅሶ፣ በህጋዊና ሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በፍርሃት እንዲሸበቡ ተደርገዋል ብሏል፡፡
ጋዜጠኞች የፀረ-ሽብር አዋጁን በመፍራት የሙያ ተግባራቸውን እንዳያከናውኑ መታፈናቸውን ሲገልጽም፤ የአዋጁ አንቀፅ እየተጠቀሰ እሥራት የተፈረደባቸው ጋዜጠኞች መኖራቸውንም አውስቷል፡፡
በኢትዮጵያ ጐልተው የሚታዩት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የፖለቲካ ምህዳር መጥበብና የኘሬሶች አፈና ቢሆኑም፤ ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችም መሻሻል አላሣዩም ብሏል ሪፖርቱ፡፡
በማረሚያ ቤት ያሉ እሥረኞች በገለልተኛ አካላት እንዳይጐበኙ መከልከል፣ ያልተፈረደባቸው ግለሰቦችን አስሮ ማቆየትና ለፍርድ ቤት አቤቱታ እንዳይቀርቡ ማገድ፤ ያልተፈረደባቸውን ሰዎች በብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ በሚሠራጩ ፕሮግራሞች ላይ እንደ ወንጀለኛ መፈረጅ… በአገሪቱ ከሚታዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ውስጥ የሚካተቱ መሆናቸውን ሪፖርቱ ዘርዝሯል፡፡  
ሠላማዊ ሠልፍ የማካሄድ፣ የመብት ጥያቄ የማቅረብና ተቃውሞን የማሰማት መብቶችንም ፈትሼያለሁ የሚለው ሂውማን ራይትስ ዎች፤ ጥያቄ ባቀረቡና ሰላማዊ ሰልፍ ባካሄዱ ሙስሊሞች ላይ እንግልት፣ ድብደባና እሥር ተፈጽሟል ብሏል፡፡ በተቃዋሚ ፓርቲዎች የተጠሩ ሠላማዊ ሠልፎችም  በአፈና ውስጥ የተካሄዱ መሆናቸው በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡
በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ የመብት ጥሰት ይፈጸምባቸዋል ከተባሉት አገራት መካከል ኤርትራ በቀዳሚዎቹ ተርታ ውስጥ እንደምትመደብ ተቋሙ ገልፆ፤ ጋዜጠኞች ለእሥራት እና ለእንግልት፤ ብዙ ዜጐችም ለስደት መዳረጋቸውን ዘርዝሯል፡፡
በኤርትራ የመብት ጥያቄ ማንሣት ነውር ሆኗል ያለው ይሄው ሪፖርት፤ የኤርትራ ሁኔታ ከሁሉም የአፍሪካ ሀገራት እጅግ በጣም አሣሣቢ ነው ብሏል፡፡
ሃሣብን በነጻነት መግለጽ፣ መደራጀትና የፈለጉትን አቋም መያዝ ለኤርትራውያን እንደማይፈቀድ በመጥቀስም፤ ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ ውጪ ሰዎች እየተያዙ ይታሠራሉ፤ እስር ቤት የታጐሩ  ጋዜጠኞች፣ ፖለቲከኞችና ሌሎች ዜጐች  ያለምንም ፍርድ ከ10 ዓመት በላይ ሆኗቸዋል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች ሙሉ ለሙሉ እንደማይቀበል በተደጋጋሚ ያስታወቀ ሲሆን፤ ተቋሙ ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት የሚሠራ ነው፤  የተቃዋሚ ሃይሎች የኘሮፖጋንዳ ማስፈጸሚያ ነው ሲል ይከሳል፡፡
ሰሞኑን የተሰራጨውን አመታዊ ሪፖርት በተመለከተ የጠየቅናቸው የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል፤ “ሂውማን ራይትስ ዎች የሚያወጣው ሪፖርት ተአማኒነት የሌለውና ገጽታን ለማጠልሸት ያለመ ነው” ብለዋል፡፡
ተቋሙ ሀገር ውስጥ ሣይገኝ ወይም መርማሪዎቹን ሣይልክ፣ ኬንያናና ሌላ ሀገር ተቀምጦ ከተቃዋሚዎች በሚቃርመው ያልተጣራ ተባራሪ ወሬ ላይ ተመስርቶ፣ ከመንግስት ምላሽ ሳይጠይቅ የሚያወጣው መናኛ ሪፖርት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ፈጽሞ አይገልጽም ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው፡፡
ተቋሙ የኢትዮጵያን መንግስት ለማጥላላት  አቅዶ የሚሠራ ነው ያሉት አቶ ሽመልስ፤ የተቋሙ የምስራቅ አፍሪካ ወኪል አቶ ዳንኤል በቀለ፣ ህገ-መንግስቱን የማፍረስ ነውጥ በማስነሳት የተከሰሱና የተፈረደባቸው፣ ይቅርታ ጠይቀው ቢለቀቁም በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ቂም የቋጠሩ በመሆናቸው ሪፖርታቸው ገለልተኛ ሊሆን አይችልም ብለዋል። ይህ ሲባል ግን ሀገራችን ታዳጊ ሀገር እንደመሆኗ ችግሮች አይኖሩም ማለት አይደለም ያሉት ኃላፊው፤ የኘሬስ ነጻነትና የጋዜጠኞች መብት ሙሉ ለሙሉ ተጠብቆ ኘሬሱ እንዲጠናከርና  እንዲስፋፋ እየተደረገ ነው፣ ከባለሙያዎች ጋርም እየተመካከርን በጋራ እየሠራን ነው ብለዋል፡፡

Published in ዜና

አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ “በልማት ጋዜጠኝነት” ዙሪያ የፓርቲና የመንግስት ተወካዮች አቋማቸውን የሚገልፁበት ውይይት ለዛሬ ያዘጋጀ ሲሆን፤ ሰማያዊ ፓርቲ የኢትዮ ሱዳን ድንበር በተመለከተ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም ሃሳብ የሚያቀርቡበት ውይይት ያካሂዳል፡፡
‹‹ልማታዊ ጋዜጠኝነት›› በሚለው ርዕሰ ጉዳይ የተለያዩ ሃገሮችን ልምድ የሚያሳይና በኢትዮጵያ የሚኖረውን ቦታ የሚፈትሽ ውይይት በኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል እንደሚካሄድ የገለፀው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒዩኬሽን ትምህርት ክፍል፤ የፓርቲ እና የመንግስት ተወካዮች አቋማቸውን እንደሚያቀርቡ ጠቁሟል፡፡
“ልማታዊ ጋዜጠኝነት” ለድሃ አገራት የሚጠቅምና የሚስማማ ነው በማለት የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ፤ በተቃራኒው ጋዜጠኝነት የመንግስት ጥገኛና አፈቀላጤ እንዲሆን ያደርጋል በማለት የሚተቹ መኖራቸው ይታወቃል፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮ-ሱዳን ድንበርን በተመለከተ ዛሬ በዘጠኝ ሰዓት በጽ/ቤቱ ውይይት የሚያዘጋጀው ሰማያዊ ፓርቲ፤ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያም በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ልምድ እንዳላቸውና ሃሳባቸውን እንደሚያቀርቡ ገልጿል፡፡ መንግስት፣ ከሁመራ እስከ ቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል ድረስ ባለፉት ሁለት ወራት ድንበር እያካለለ መሆኑን በሱዳን የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች እንደተሰራጨ የገለፀው የፓርቲው የወጣቶች ጉዳይ ሃላፊ ዮናታን ተስፋዬ፤ መንግስት ጉዳዩን ደብቆ ይዟል ብሏል፡፡
መንግስት በድንበር ጉዳይ የሚሰነዘሩ ትችቶች መሰረት የለሽ ናቸው ብሎ ማስተባበሉ ይታወሳል።

Published in ዜና

በቅስቀሳ ላይ የነበሩ አባሎቼ ታስረውብኛል ብሏል

ዓረና ፓርቲ በዓዲግራት ከተማ ነገ እሁድ የድርጅቱን ፕሮግራምና ወቅታዊ የፖለቲካ አጀንዳዎቹን ለማስተዋወቅ ህዝባዊ ስብሰባ ጠራ፡፡ በትግራይ ክልል በየከተማውና በየአካባቢው በመዘዋወር ፕሮግራሙንና የወደፊት ራዕዩን ለህዝብ እያስተዋወቀ መሆኑን ፓርቲው ጠቅሶ፤ በዓዲግራት ለጠራው ህዝባዊ ስብሰባ ቅስቀሳ እንዲያካሂዱ ያሰማራቸው አቶ ዓምዶምና መምህር ገብረጨርቆስ የተባሉ አባላት እንደታሰሩበት ገልጿል፡፡
ሰላማዊ የፖለቲካ ስብሰባ ማካሄድና መሳተፍ የሁሉም ዜጋ መብት መሆኑን የተናገሩት የፓርቲው ተወካይ፤ ሁለቱ አባላት የታሰሩት “ህዝብ በስብሰባ እንዲሳተፍ ቀስቅሳችኋል፣ ህጋዊ አይደላችሁም›› በሚል እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ስብሰባ ተፈቅዶ አትቀስቅሱ ብሎ ማሰር አስገራሚ ህገወጥነት ነው ያሉት የፓርቲው ተወካይ፤ ዓረና ፓርቲ አማራጭ ፖሊሲውን ለህዝብ እያስተዋወቀ ይቀጥላል፤ በቀጣዩ እሁድም ሁመራ ላይ ህዝባዊ ስብሰባ ያደርጋል ብለዋል፡፡  

Published in ዜና

            በአዲስ አበባ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ፤ ባሏ በነዳጅ ቃጠሎ ያደረሰባት ወ/ሮ ብዙነሽ ነጋ ከአራት ሳምንት ስቃይ በኋላ ማክሰኞ እለት የሞተች ሲሆን፤ ድርጊቱን ፈጽሟል የተባለው አቶ ሽታው ሁሴን በፖሊስ ተይዞ ምርመራ እየተካሄደ ነው፡፡
ለ12 አመታት በትዳር የቆዩት ባልና ሚስት አንድ ልጅ ማፍራታቸውን የገለፁት ዘመዶች እንደሚሉት፤ በሟቿ ላይ የደረሰው ጥቃት ያልታሰበ ዱብዕዳ አይደለም፡፡ ለበርካታ ጊዜ ባለትዳሮቹ እየተጋጩ፤ ወ/ሮ ብዙነሽ በተደጋጋሚ ጥቃት ይደርስባት ነበር ብለዋል፡፡
አቶ ሽታው ባለቤቱን ከቤተሰብና ከጐረቤት ጋር እንዳትቀራረብ ብቻ ሳይሆን ከቤት ውጭ እንዳትንቀሳቀስ እያስፈራራ፣ በተደጋጋሚ ጉዳት እንዳደረሰባት የሚናገሩት የሟች እህት ወ/ሮ አበባ ነጋ፤ ባለፈው ወር ታህሳስ 17 ቀን እኔ ቤት ቆይታ አመሻሽ ላይ ወደ ቤቷ ከሄደች በኋላ ነው ጥቃት የፈፀመባት ይላሉ፡፡ እህታቸው መጐዳቷን ሰምተው ወዲያውኑ መሄዳቸውን እና አሰቃቂነቱ ለማመን እንደሚከብድ የገለፁት ወ/ሮ አበባ፤ “ህይወቷ አላለፈም፤ ግን በቃጠሎው ቆዳዋ እንደጨርቅ ከላይዋ ላይ የወለቀ ይመስል ነበር” ብለዋል፡፡
ከምሽቱ 3 ሰዓት ገደማ በቃጠሎ ክፉኛ የተጐዳችው ወ/ሮ ብዙነሽ፤ በአካባቢው በሚገኝ ጤና ጣቢያ የመጀመሪያ ደረጃ እርዳታ ተደርጐላት፣ ወደ ጥሩነሽ ቤጂንግ ሆስፒታል የተላከችው ከሌሊቱ 7 ሰዓት እንደሆነ ቤተሰቦቿ ገልፀዋል፡፡
ለከፍተኛ ስቃይ የተዳረገችው ወ/ሮ ብዙነሽ ጥቃቱ እንዴት እንደደረሰባት ሆስፒታል ውስጥ በቆየችባቸው ቀናት እንደነገረቻቸው የገለፁት ቤተሰቦቿ፤ ቤት ውስጥ በነጭ ጋዝ ምድጃ ወጥ እየሠራች ነበር ብለዋል፡፡ ባለቤቷ የቤቱን በር ቆልፊው ብሏት ከቆለፈችው በኋላ እራት እንድትሰጠው አዘዛት፡፡ ወጡ ውስጥ ጨው ጨምራ እራት ልትሰጠው ስትል ነው ከመቀመጫው ተነስቶ፣ ምድጃውን እስከነድስቱ አንስቶ የደፋባት፡፡ ከእሳቱ ጋር የምድጃው ጋዝ እላይዋ ላይ የተከለበሰባት ወ/ሮ ብዙነሽ፤ መላ አካሏ በእሣት ነደደ፡፡  “ሰላም ሳታገኝ ስትኖር የቆየች እናት ላይ ነው አሰቃቂው ኢ- ሰብአዊ ድርጊት የተፈፀመባት” የሚሉት ቤተሰቦቿ ሟች ከሁለት አመት በፊት አንገቷን በገመድ ሊያንቃት ሲሞክር ጐረቤት ነበር ያስጣላት ብለዋል፡፡
ለጊዜው በህይወት የተረፈችው ወ/ሮ ብዙነሽ ከነልጇ ሸሽታ በታላቅ እህቷ ቤት ቤት ተጠግታ ብትቆይም ኑሮን ለማሸነፍ ወደ አረብ ሃገር ስራ ፍለጋ ሄዳለች፡፡ ግን አረብ ሀገርም አልተሳካላትም፡፡ 11 ወር ቆይታ የተመለሰችው ወ/ሮ ብዙነሽ፤ ከባለቤቷ ጋር እርቅ ተፈጽሞ አብራው መኖር ብትጀምርም፤ ከቀድሞው ጥቃት አልተገላገለችም፡፡ አንድ አመት ሳይቆይም የባሏ ጥቃት ህይወቷን የሚያጠፋ አሰቃቂ ደረጃ ላይ ደረሰ ብለዋል - ቤተሰቦች፡፡
 ከአንገቷ በታች በስተቀር መላ ሰውነቷ በእሣት ቃጠሎ እንደነደደና ያለማቋረጥ እያበጠ በሚፈነዳ ቁስል እንደተሸፈነ የገለፁት የሟች ቤተሰቦች፤ የተኛችበት አንሶላ ከአንድ ሰዓት በላይ ያስቸግር ነበር ብለዋል፡፡
ከአራት ሳምንት በኋላ ህይወቷ አለፈ፤ የቀብር ስነ ስርአቱም በአካባቢው በሚገኘው ሳሎ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ጥር 14 ቀን 2006 ተፈጽሟል፡፡
የአቃቂ - ቃሊቲ ገብርኤል አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ የምርመራ ክፍል ሃላፊ ሳጅን ጐሽሜ አገኘሁ፣ ተጠርጣሪው በእለቱ ተራ በሆነ ቅናት ተነሳስቶ ሟች ወደ ቤቷ ስትመለስ ጠብቆ “የት ቆይተሽ ነው የመጣሽው፣ “አልኮል ጠጥተሻል” በሚል ፀብ አንስቶ፣ የተቀጣጠለውን ምድጃ ሰውነቷ ላይ በመወርወር ቃጠሎውን እንዳደረሰ ገልፀዋል፡፡ ፖሊስም ጥቆማው እንደደረሰው ወዲያው ግለሰቡን በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ ማድረጉን የገለፁት ሳጅን ጐሽሜ አገኘው፤ ተጠርጣሪው በአካባቢው በሚገኘው የከተማ ነክ ጉዳዮች ፍ/ቤት ቀርቦ ፣ ፍ/ቤቱ በ2ሺህ ብር ዋስ እንዲለቀቅ ትዕዛዝ ሲያስተላልፍ  ፖሊስ ለፍ/ቤቱ በህይወት እና በሞት መካከል ያለችውን ተጐጂ የጉዳት መጠን የሚያሳይ ፎቶግራፍ በማቅረብ ጭምር ዋስትናው እንዳይፈቀድ ቢያመለክትም ፍ/ቤቱ በአቋሙ ፀንቷል ብለዋል፡፡ ነገር ግን ፖሊስ ጉዳዩን ለከፍተኛው ፍ/ቤት በድጋሚ አቅርቦ ተጠርጣሪው በማረፊያ ቤት እንዲቆይ በተደረገበት ሁኔታ ተጐጂዋ ህይወቷ ማለፉን  ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ የምርመራ መዝገቡ ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ተልኮ በምርመራ ላይ መሆኑን ሃላፊው ገልፀዋል፡፡  

Published in ዜና

ዋና አዘጋጁ በ5ሺህ ብር ዋስ ተለቋል

 “ሰንደቅ” ጋዜጣ ስለ ጉዲፈቻ በሰራው ሰፊ ዘገባ ላይ የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር  በስም ማጥፋት አቤቱታ እንዳቀረበበት የገለፀው ዋና አዘጋጁ ፍሬው አበበ፤ ባለፈው ሀሙስ ጠዋት ማዕከላዊ ምርመራ ቀርቦ ቃሉን ከሰጠ በኋላ በ5ሺህ ብር ዋስ መለቀቁን ተናገረ፡፡
ጋዜጣው ታህሣሥ 23 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም ‹‹የጉዲፈቻ ዘመቻ በተጠያቂነት መጀመር አለበት›› ርዕስ አንቀጽና በሕግ አምዱ ላይ ‹‹ጉዲፈቻና የሕጎቻችን ክፍተቶች›› በሚል ዘገባ ማውጣቱን ዋና አዘጋጁ ተናግራል፡፡ የሴቶች፣ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር በጋዜጣው የአገርን ገፅታ የሚያበላሽ፣ የፍትህ ስርዓቱን ተዓማኒነት የሚያሳጣና የሚኒስትሯን ክብር የሚያዋርድ ዘገባ አውጥቷል ሲል ለፓሊስ አቤቱታ ማቅረቡን የተናገረው ዋና አዘጋጁ፤ ከትላንት በስቲያ በፌደራል ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ቀርቦ ቃሉን ከሰጠ በኋላ፣ በ5ሺህ ብር ዋስ መለቀቁን ገልጿል፡፡
በጉዲፈቻ ዙሪያ ባወጡት ዘገባ ስም በማጥፋት በመንጀላቸው እንዳሳዘነው የገለጸው ዋና አዘጋጁ ፍሬው፤ “የተፈለገው ሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነትን እንዳናጋልጥ ቢሆንም ፈርተን ወደ ኋላ አንልም፤ ሞያው የሚጠይቀውን  መስዋዕትነት ሁሉ እንከፍላለን” ብሏል፡፡ 

Published in ዜና

አደራዳሪው አምባሳደር ስዩም የተኩስ አቁም ስምምነቱን ይቆጣጠራሉ
በመንግስት የታሰሩ ተቃዋሚዎች ይለቀቃሉ ተብሏል


የደቡብ ሱዳንን ገዢ ፓርቲ ለሁለት በመሰንጠቅ፣ አንጋፋ መሪዎች በሁለት ጐራ የሚያካሂዱትን ጦርነት ለመሸምገል በአካባቢው አገራት ይሁንታ የተመደቡት አምባሳደር ስዩም መስፍን፣ ሁለቱ ባላንጣዎች ተኩስ እንዲያቆሙ በማስማማት ሐሙስ ማታ አፈራረሙ፡፡
በፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ከስልጣን የተባረሩት የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንት ሬክ ማቻር የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ካካሄዱ በኋላ፣ መንግስት አፈንጋጭ የገዢው ፓርቲ አመራሮችንና ባለስልጣናትን ያሰረ ሲሆን አፈንጋጮቹ በበኩላቸው፤ በወታደራዊ ጥቃት በርካታ ከተሞችና የነዳጅ ማውጫ ቦታዎች ላይ መዝመታቸው ይታወቃል፡፡
በምስራቅ አፍሪካ የኢጋድ አባል አገራት፣ አምባሳደር ስዩም መስፍንን ከቻይና በመጥራትና ሁለት ተጨማሪ ልዑካንን በማከል ተቀናቃኝ የደቡብ ሱዳን ባላንጦችን እንዲሸመግሉ ቢመድብም፣ ተቀናቃኞቹ ያቀረቡት የድርድር ቅድመ ሁኔታ ፈታኝ ሆኖባቸው እንደቆየ ተነግሯል። ድርድሩ ያለ ውጤት ሊራዘም ይችላል ተብሎ ቢገመትም ፤ መንግስት ለሰላም ድርድር ሲል ተቃዋሚዎችን ከእስር እንዲለቅ፤ ተቃዋሚዎች ደግሞ በሃይል ስልጣን ለመያዝ ከመሞከር እንዲቆጠቡ በማሳመን ሐሙስ እለት የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲፈራረሙ ተደርጓል፡፡
ተቀናቃኞቹ ወገኖች ከወታደራዊ ጥቃትና ከፕሮፖጋንዳ ዘመቻ ለመቆጠብ የተፈራረሙትን ስምምነት ማክበራቸውን ለመቆጣጠር አምባሳደር ስዩም እና ሁለቱ ተጨማሪ የኢጋድ ልዑኮች ሃላፊነት ተሰጥቷቸዋል፡፡
ከዚህ አስቸጋሪ ሃላፊነት በተጨማሪ፤ ተቀናቃኞቹ ዘላቂ መፍትሔ ላይ ለመድረስ የሚያካሂዱት የሰላም ድርድር ብዙ ፈተናዎች ስለሚጠብቁት፤ የደቡብ ሱዳን ጉዳይ አሳሳቢ እንደሆነ ይቆያል ተብሏል፡፡
በሚቀጥለው ሣምንት በአዲስ አበባ የሚካሄደው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤም በግብርናና በምግብ ዋስትና ዙሪያ እንዲያተኩር ታስቦ የነበረ ቢሆንም፤ የጉባኤው ትኩረት ወደ ደቡብ ሱዳንና ወደ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ የፀጥታ አደጋዎች ይዞራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከሃይማኖት ጋር የተነካካው የማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ቀውስ እና የእርስ በርስ ግጭት ሰሞኑን ረገብ ያለ ቢመስልም አገሪቱ አሁንም ከቀውስ አልወጣችም፡፡ የዋና ከተማዋ የባንጉዊይ ከንቲባ የአገሪቱ ኘሬዚዳንት እንዲሆኑ ተመርጠው ስልጣን ቢረከቡም የፀጥታ ሁኔታው አሁንም እንዳልተረጋጋና አፋጣኝ ሁነኛ መፍትሄ ካልተገኘ ግጭቱ ወደ እርስ በርስ እልቂት ሊያመራ እንደሚችል ከአገሪቱ የሚወጡ መረጃዎች እየጠቆሙ ነው፡፡
ከመሪዎቹ ጉባኤ አስቀድሞ የአፍሪካ የሚኒስትሮች ጉባኤ በባህርዳር ከተማ እየተካሄደ ሲሆን፤ በሠላምና መረጋጋት ችግሮች ላይ ተወያይቶ የውሳኔ ሃሣቦችን ለመሪዎቹ ጉባኤ ያቀርባል፡፡
በህብረቱ ጉባኤ ላይም ሆነ ጣና ላይ እየተካሄደ ባለው የሚኒስትሮች ስብሰባ ላይ ግብጽ አትሳተፍም። የመሀመድ ሙርሲን መንግስት ተክቶ ያለው ወታደራዊ መንግስት ስልጣኑን በህዝብ ለተመረጠው መንግስት እስኪያስረክብ ድረስ ግብጽ በአፍሪካ ህብረት እንዳትሳተፍ ማዕቀብ ተጥሎባታል፡፡

Published in ዜና
Page 3 of 14