ደረቅ ቼክ ክስ ላይ የሚጠቀሱት የህግ አንቀፆች ባይለወጡም ከ2002 ዓ.ም ወዲህ የእስር ቅጣቱ በብዙ እጥፍ እየከበደ መምጣቱን የሚናገሩት ነጋዴዎች፣ ሆን ብለው ባልፈፀሙት ስህተት መፀፀታቸውን በመግለጽ ሐሙስ ዕለት ለፕሬዚዳንቱ የይቅርታ ጥያቄ አቀረቡ፡፡
“የደረቅ ቼክ” ክስ ደረጃውና አይነቱ እንደሚለያይ የሚገልፁት ነጋዴዎች፤ በደረቅ ቼክ አጭበርብሮ ለመጥፋት ወይም ክህደት ለመፈፀም የሚሞክር ባይጠፋም፣ በአብዛኛው ነጋዴ ላይ የሚከሰተው ችግር ግን በጊዜ የመክፈልና የማዘግየት ጉዳይ መሆኑን ይገልፃሉ፡፡ በተለያዩ ስህተቶች ሳቢያ እንጂ ሰውን ለማጭበርበር አስበን የፈፀምነው ተግባር አይደም የሚሉት እነዚሁ ነጋዴዎች፣ እዳችንን ከፍለን፣ ተበዳይን ክሰን እርቅ ብንፈጥርም፤ ለበርካታ አመታት ከመታሰር አለመዳናችን ያሳዝናል ብለዋል፡፡ ቼክ ከቆረጡ በኋላ በኪሳራ ወይም በሌላ ምክንያት የባንክ ሂሳባቸው ተራቁቶ እዳቸውን መክፈልና ከተበዳይ ጋር እርቅ መፍጠር ያልቻሉ ጥቂት ሰዎች መኖራቸው ግን ይታወቃል፡፡ እንዲያም ሆኖ ሰውን ለማጭበርበር አስበው ድርጊቱን እንደፈፀሙት ካልተረጋገጠ በቀር በበርካታ አገራት የገንዘብ ቅጣት እንጂ የእስር ቅጣት እንደማይፈረድባቸው የህግ ባለሙያዎች ይጠቁማሉ፡፡ በኢትዮጵያም ለተወሰነ ጊዜ  የደረቅ ቼክ ክሶች አያያዝ ደህና እንደነበር ሲያስረዱ፤ በ2001 ዓ.ም ለተለያዩ አምስት ሰዎች በድምሩ የ1.2 ሚሊዮን ብር ደረቅ ቼክ በመስጠት የተከሰሰ ነጋዴ፣ ከተበዳዮች ጋር እርቅ ባይፈጥርም የአንድ አመት እስር እንደተፈረደበት ይጠቅሳሉ፡፡
የእስር ቅጣቱ እየከበደ የመጣው ግንቦት 2002 ስራ ላይ በዋለው አዲስ መመሪያ መሆኑን ነጋዴዎቹ ገልፀው፤ በ2003 ዓ.ም ለአምስት ሰዎች በድምሩ የ540ሺ ብር ቼኮችን ቆርጦ የሰጠ ነጋዴ፤ ለጊዜው በቂ የባንክ ሂሳብ ስላልነበረው መከሰሱንና የተወሰነበት ቅጣት እጅግ ከባድ መሆኑን በማነፃፀሪያነት አቅርበዋል፡፡ በጊዜያዊ ስህተት ምክንያት የተፈጠረበት ችግር እንጂ ደንበኞቹን ለማጭበርበር የፈፀመው ድርጊት እንዳልሆነ ነጋዴው ሲያስረዳ፣ እዳውን ከፍሎ ተበዳዮችን ክሶ እርቅ መፍጠሩን ይገልፃል፡፡ እንዲያውም፤ ደንበኞቹ ፍርድ ቤት ፊት ቀርበው፣ ገንዘባቸው እንደተከፈላቸውና እንደታረቁ በመግለጽ የክስ ሂደቱ እንዲቀረጥ በተደጋጋሚ ጠይቀዋል፡፡ ነገር ግን፤ የተበዳዮቹ ምስክርነት፣ የእስር ቅጣቱን በ6 ወር ወይም በአንድ አመት ከማስቀነስ ያለፈ ውጤት አያስገኝም፡፡ በዚህም ምክንያት፤ ተከሳሹ የ15 አመት እስር ተፈርዶበታል፡፡
በርካታ ነጋዴዎች ባላሰቡት አጋጣሚ ለችግር እንደሚጋለጡ የተናገረው ሌላው ታሳሪ በበኩሉ፣ ከውጭ አገራት የሚያሰመጣቸውን ሸቀጦች በማከፋፈል ይተዳደር እንደነበር ይገልፃል፡፡
ያስመጣቸው እቃዎች የጉምሩክ ጣጣ እስኪጨርሱ ድረስ ያለ ስራ ላለመቀመጥ ሲልም፤ ከደንበኞቹ ጋር ተስማምቶ የቅድሚያ ሂሳብ እየቀበለ ተጨማሪ ሸቀጦችን ያስመጣል፡፡ ነገር ግን፤ ቀብድ የከፈሉ ደንበኞቹ ከጉምሩክ የሚወጡትን ሸቀጦች እስኪረከቡ ድረስ መተማመኛ ስለሚየስፈልጋቸው፣ በከፈሉት የገንዘብ መጠን በድምር የ850ሺ ብር ሰባት ቼኮችን ቆርጦ እንደሰጣቸው ይሄው ታሳሪ ገልጿል፡፡
ሸቀጦቹን ከጉምሩክ አውጥቶ ሲያስረክባቸው፣ ለመተማመኛ የቆረጠላቸውን ቼክ ይመልሱለታል ማለት ነው፡፡ ነገር ግን እንዳሰበው አልሆነም፡፡ በተለመደው ጊዜ ውስጥ የጉምሩክን ሂደት አጠናቅቆ ሸቀጦቹን ማስወጣት አልቻለም፡፡
ደንበኞቹ ለመተማመኛ የሰጣቸውን ቼክ ይዘው ወደ ባንክ ቢሄዱ ደግሞ፣ በቂ የባንክ ሂሳብ አልነበረውም፡፡
ስለሆነም፤ አቤቱታ ቀርቦበት ታሰረ፡፡ እንደአጋጣሚ ሆኖ ለበርካታ ቀናት ሲደክምበት የነበረው የጉምሩክ ሂደት ተጠናቅቆ እቃዎቹ የተለቀቁት በታሰረ ማግስት እንደሆነ የሚገልፀውም ይሄው እስረኛ፣ ቤተሰቦቼ ወዲያውኑ እቃዎቹን ለደንበኞቼ አስረክበዋል ብሏል፡፡
ነገር ግን፤ እሱ አልተፈታም፤ ሰባት ደረቅ ቼኮችን ቆርጠሃል ተብሎ ሰባት ክስ ቀረበበት፡፡ በእርግጥ፤ አቤቱታ አቅርበው የነበሩት ደንበኞቹ ፍ/ቤት ፊት ቀርበው፣ ስለታማኝነቱ በመመስከር ክሱ እንዲቋረጥ ጠይቀዋል፡፡ ቢሆንም፤ በ2002 ዓ.ም በወጣው መመሪያ መሰረት 16 ዓመት እስር ተፈረደበት፡፡
እስር ቤት ልትጠይቀው የመጣች ህፃን ልጁ፣ የሀዘን ስሜቱን እንዳታይበት እየተጨነቀ ሃሳቡን ሲናገር፤ ሆን ብዬ የፈፀምኩት ስህተት ባይሆንም ይፀጽተኛል፤ ነገር ግን አጭበርብሬ የወሰድኩት የሰው ንብረት ወይም ሳንቲም የለም፤ ሚሊዮን ብር የሰረቀ ወንጀለኛ እንኳ እንደኔ የ16 ዓመት ከባድ ቅጣት የሚፈረድበት አይመስለኝም ብሏል፡፡

Published in ዜና

ቤት ያገኘላቸው የኮሚሽን ሠራተኛ  360ሺ ብር አልተከፈለውም
ውል ፈርሶብኛል ያሉ ሌላ አከራይ የ2.4 ሚሊዮን ብር ካሣ ጠይቀዋል
የፕሬዚዳንቱ ፅ/ቤት የሚከራከርለት የህግ ባለሙያ የለውም
ለቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፤ የመኖሪያ ቤት አፈላልጐ ያከራያቸው የኮሚሽን ባለሙያ አቶ አንተነህ አሰፋ፤ 360 ሺ ብር የአገልግሎት ክፍያ አልተከፈለኝም ሲል በፕሬዚዳንቱና ልጃቸው ላይ ክስ መሠረተ፡፡
ክሱ፤ ከፕሬዚዳንቱ በተጨማሪ የፕሬዚዳንቱን ጽ/ቤትና የጽ/ቤቱ ሃላፊ ወ/ሮ አማረች በካሎን፣ የጽ/ቤቱ ባልደረባ ወ/ሮ አምሣለ ፋንታሁንንና የፕሬዚዳንቱን ልጅ ወ/ሮ መና ግርማን እንደሚያካትት ታውቋል፡፡
ከሣሽ አቶ አንተነህ፤ ታህሳስ 15 ቀን 2006 ዓ.ም ለፍ/ቤት  በጽሑፍ ባቀረበው ማመልከቻ፤ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ባለፈው መስከረም ወር ከስልጣን ሲወርዱ የገቡበትን ባለ 3 ፎቅ መኖሪያ ቤት አፈላልጐ በወር 400 ሺህ ብር እንዲከራዩ ማድረጉን ጠቅሶ፤ ለእሱ የሚገባው 360ሺ ብር የኮሚሽን ክፍያ እንዳልተከፈለው ገልጿል፡፡ የአገልግሎት ክፍያውን የመክፈል ሃላፊነት የማን እንደሆነ ለማወቅ መቸገሩን የጠቆመው ከሳሹ፤ ከ5ቱ ተከሣሾች ውስጥ ሃላፊነት ወስዶ ክፍያውን የሚፈጽመው ማን እንደሆነ ፍ/ቤቱ እንዲያጣራለት ጠይቋል፡፡ አስር በመቶ የኮሚሽን ክፍያው ከመስከረም ወር ጀምሮ ከሚታሰብ የ9 በመቶ ወለድና የክስ ሂደት ወጪዎች ጋር ተደምሮ ይከፈለው ዘንድም ለፍ/ቤቱ አመልክቷል፡፡
ክሱ የደረሰው የፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት በበኩሉ፤ የህግ ድጋፍ ለመጠየቅ ለፍትህ ሚኒስቴር በፃፈው ደብዳቤ፤ ለኮሚሽን ባለሙያው ሊከፈል የሚገባው ገንዘብ፣ የመንግስትን ጥቅም ስለሚጐዳና ጽ/ቤቱም በራሱ ለመከራከር የህግ ባለሙያ ስለሌለው፣ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ወክሎ እንዲከራከርለት ጠይቋል፡፡
የመኖሪያ ቤት ፍለጋውን ከመጀመሩ በፊት የፕሬዚዳንቱ ወኪል ከሆነችው ከልጃቸው ወ/ሮ መና ግርማ ጋር የኮሚሽን ክፍያ ውል መፈራረሙን የጠቀሰው ከሳሹ፤ ክፍያውን በወቅቱ ባለማግኘቱ  ህዳር 16 ቀን 2006 ዓ.ም ለፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት በፃፈው ደብዳቤ፤ በ5 ቀን ውስጥ ክፍያው ካልተፈፀመ ክስ እንደሚመሰርት ማስጠንቀቁን አስታውሷል፡፡ ጉዳዩ የቀረበለት ፍ/ቤትም፤ ተከሣሾች መልሳቸውን የፊታችን ረቡዕ በጽሑፍ እንዲያቀርቡ በማዘዝ የክሱን ቀጣይ ሂደት ለመስማት ለጥር 27 ቀጥሯል። በሌላ በኩል ቀደም ሲል በ530 ሺ ብር ቤታቸውን ለፕሬዚዳንቱ መኖሪያነት ለማከራየት ከተስማሙ በኋላ፣ ውል ፈርሶብኛል ያሉት አቶ ኤልያስ አረጋ፤ ቤቱን ለማሳደስና ለተያያዥ ጉዳዮች ያወጧቸውን የተለያዩ ወጪዎች በመጥቀስ፣ የ2.4 ሚሊዮን ብር ካሣ እንዲከፈላቸው ለፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት በደብዳቤ ያሳሰቡ ሲሆን ይህ ካልተፈፀመ ግን መብታቸውን በህግ ለማስከበር እንደሚገደዱ  ገልፀዋል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስ፤ በአሁኑ ሰዓት በኃይሌ ገ/ስላሴ ጐዳና፣ ከአክሱም ሆቴል ጀርባ መንግስት በተከራየላቸው ባለሦስት ፎቅ መኖርያ ቤት ውስጥ የሚኖሩ ሲሆን ቤቱ የመዋኛ ገንዳ ያለውና ባለብዙ ክፍሎች እንደሆነ ታውቋል፡፡ ቤቱ ከእሳቸው በፊት ለኬንያ ኤምባሲ ተከራይቶ ነበር፡፡  የመንግስት ባለስልጣናት በጡረታ ሲገለሉ የሚኖራቸውን መብት የሚደነግገው አዋጅ፤ ፕሬዚዳንቱ ከ4-5 መኝታ ክፍሎች ያሉት መኖርያ  ቤት እንደሚያገኝ ቢገልጽም የፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት ለቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፤ በጣም ውድና ከ20 ክፍሎች በላይ ያሉት መኖርያ ቤት መከራየቱ ሲያነጋግር መቆየቱ ይታወሳል፡፡  
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ልዩ አማካሪ አቶ አሰፋ ከሲቶን በጉዳዩ ዙርያ አስተያየት እንዲሰጡን ጠይቀናቸው “ጉዳዩ በፍርድ ሂደት ላይ ስለሆነ ምላሽ ልሰጣችሁ አልችልም” ብለዋል፡፡

Published in ዜና

በዚህ ጽሑፌ በፍቅር ተጀምረው በአሰቃቂ የግድያ ወንጀሎች የተቋጩ የትዳር (ፍቅር) ህይወቶችን ለማስቃኘት እሞክራለሁ፡፡ ከፖሊስ የሰበሰብኳቸው መረጃዎች በርካታ ቢሆኑም ጥቂቶቹን ብቻ መርጬ ለማሳያነት አቅርቤአለሁ፡፡ አንባቢያን መረጃዎቹን አንብበው የራሳቸውን ግንዛቤ ይወስዳሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ ከዚያም ባሻገር ግን በጉዳዩ ላይ ጥናትና ምርምር የማካሄድ ፍላጐቱ ላላቸው ባለሙያዎች እንደመነሻ ሊያገለግል ይችላል ብዬ አስባለሁ፡፡ ታሪኮቹ የቱንም ያህል አስከፊና አሳዛኝ ቢሆኑም ይፋ መሆናቸው በተለያየ መልኩ ጠቀሜታ እንጂ ጉዳት የላቸውም በሚል እንዲህ ተጠናቅረዋል፡፡  

በቅናት ባሏን ጋዝ አርከፍክፋ ያቃጠለች ሚስት…
“ከወንድ ጋር አየሁሽ” ብሎ ፍቅረኛውን በጩቤ የወጋ ወዳጅ--
የልጆቹ እናት ላይ 18 ጥይቶች አርከፍክፎ የገደለ ባል…

          በሸዋሮቢት ካራቆሬ ከተማ የተወለደችው ምንትዋብ ጌታቸው፤ በትውልድ አገሯና በአዲስ አበባ እስከ 9ኛ ክፍል ተምራለች፡፡ በ1989 ዓ.ም በ16 ዓመቷ ትዳር መስርታ አንድ ልጅ ብትወልድም ከባሏ ጋር መስማማት ባለመቻሏ ባገባች በሁለተኛ ዓመቷ ፍቺ ለመፈፀም ተገደደች፡፡
ሻይ አፍልታ እየነገደች ልጇን በማሳደግ ላይ ሳለች ነበር ሽታዬ ሙሉ ከተባለ ሰው ጋር እዛው ሸዋሮቢት የተዋወቀችው - ፍቺ ከፈፀመች ከሁለት ዓመት በኋላ፡፡ የትዳር ጥያቄ ሲያቀርብላት ግን በአንዴ በጄ አላለችውም፡፡ “ሌላ ለትዳር የጠየቀኝ ሰው አለ” በማለት አሻፈረኝ ብላ ነበር፡፡ በኋላ ግን “እህትሽ እኮ ፈቅዳለች” ብሎ በማግባባት የጋብቻ ጥያቄውን እንድትቀበል አደረጋት፡፡ ይሄን ጊዜ ነው ለሁለተኛ ጊዜ ወደ አዲስ አበባ የመጣችው። ከመጀመሪያ ባሏ የወለደችውን ልጇን ይዛ ኮተቤ አካባቢ ቤት በመከራየት አዲስ የትዳር ህይወት ጀመረች- ከአዲሱ ባለቤቷ ጋር፡፡ ብዙም ሳትቆይ ከሁለተኛ ባሏ ሁለተኛ ሴት ልጅ የወለደችው ምንትዋብ፤ በትዳሯ ግን ደስተኛ እንዳልነበረች ከፖሊስ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡ ባሏ ሰክሮ እየገባ ይደበድባት ስለነበር በተደጋጋሚ ከቤት እየወጣች በሽምግልና ታርቃ መመለሷን ትናገራለች።
ሆኖም በዚህ መቀጠሉን ባለመፈለጓ፣ ልጆቿን ለእናቷ ሰጥታ በቤት ሠራተኝነት ተቀጥራ ወደ ኩዌት  ተጓዘች፡፡ ለዘጠኝ ወራት ያህል ከሰራች በኋላ ግን ችግር ገጠማት - ከኩዌት አሰሪዎቿ ሳይሆን ከአዲስ አበባ፡፡ ባለቤቷ “ሚስቴን አረብ አገር የላካችኋት እናንተ ናችሁ” በማለት ቤተሰቧን እንደሚበጠብጥና እንደሚያስፈራራ ስለሰማች፣ ሥራዋን ጥላ ወደ አገሯ መመለሷን ተናግራለች፡፡ ከዚያም ልጆቿን ከእናቷ ቤት አምጥታ  ከባሏ ጋር እንደገና መኖር ጀመረች፡፡ በኩዌት ሰርታ ባጠራቀመችው ከ20ሺ ብር በላይ ቤት ገዝታ  ከኪራይ ቤት ወጡ፡፡ በ2002 ዓ.ም ሁለተኛ ሴት ልጅ ደገሙ፡፡ ሆኖም ባለቤቷ ከእሷ በፊት ጐጃም ከነበረው ትዳሩ ሦስት ልጆች መውለዱን የሰማችው ምንትዋብ፤ “ለምን ደበቅኸኝ” በሚል ሰበብ ጭቅጭቅ ማንሳቷ አልቀረም፡፡ ባለቤቷ አንዱን ልጁን ክረምቱን አብሯቸው እንዲያሳልፍ ከጐጃም ማምጣቱ ደግሞ ጭቅጭቁን  አባባሰው፡፡ በመሃላቸው ሽማግሌዎች ገብተው፣ ሁለቱም ከሌላ የወለዱትን በውጭ እየረዱ በጋራ የወለዷቸውን አብረው እንዲያሳድጉ በመወሰናቸው ችግሩ በዚሁ እልባት አገኘ፡፡
ጥንዶቹ፤ የከፋ ጠብ ውስጥ የገቡት ሽታዬ የጤና እክል ገጥሞት ምንትዋብን ገንዘብ እንድትሰጠው በጠየቃት ጊዜ ነው፡፡ ሚስት ገንዘብ እንደሌላት ስትነግረው “ገንዘቡን ካላመጣሽ እዚህች ቤት አትገቢያትም” ብሎ እንደዛተባት ምንትዋብ ለፖሊስ በሰጠችው ቃል ገልፃለች፡፡ መጀመሪያ ላይ ወርቋን አስይዛ ገንዘቡን ከሰው ለመበደር አስባ እንደነበር ትናገራለች፡፡ በኋላ ግን ወደ ክፉ ሃሳብ ዞረች፡፡
ጥቅምት 21 ቀን 2004 ዓ.ም ምንትዋብ ከጐረቤት በተዋሰችው መጥረቢያ፤ ባለቤቷን በተኛበት  ሁለት ጊዜ ጭንቅላቱ ላይ “እንካ ቅመስ” በማለት እንደገደለችው የፖሊስ መረጃ ይጠቁማል። አሁን ምንትዋብ በከባድ ሰው የመግደል ወንጀል ተከስሳ፣ ፍርዷን በማረምያ ቤት ሆና በመጠባበቅ ላይ ትገኛለች፡፡
ወታደር እዮብ ጌታቸው ናዝሬት ነው የተወለደው፤ በ1982 ዓ.ም፡፡ እስከ ስምንተኛ ክፍል ድረስ ከተማረ በኋላ ሁርሶ ማሠልጠኛ በመግባት፣ ለሦስት ወር በእግረኛ ወታደርነት ሰልጥኖ በትግራይ ክልል ዲንሻ አካባቢ ተመድቦ መሥራት ጀመረ፡፡ በሀምሌ ወር አጋማሽ 2004 ዓ.ም ላይ ታሞ ለህክምና ወደ አዲስ አበባ ጦር ሀይሎች ሪፈራል ሆስፒታል የተላከ ሲሆን “ወባ አለብህ” ተብሎ በተመላላሽ ሲታከም ከቆየ በኋላ፣ ስላልተሻለው የአመት ዕረፍት ወስዶ አዲስ አበባ ተቀመጠ፡፡
በዚህ መሃል ነበር ከዚህ ቀደም አጠና ተራ አካባቢ በ200 ብር አብሯት ያደረውንና በሴተኛ አዳሪነት የምትተዳደረውን “ሰላማዊት” የተባለች ሴት ያገኘው፡፡ መስከረም 3 ቀን 2005 ዓ.ም ሌሊቱን አብረው ለማደር 200 ብር ሊከፍላት ተስማማ፡፡ እሷ መጠጥ ስለማትጠጣ አስፈቅዷት ሌላ ቦታ ሲጠጣ ይቆይና ከሌሊቱ 6፡00 ገደማ ወደ መኝታ ክፍሉ ይመለሳል፡፡ “ሰላማዊት” አኩርፋ እንደጠበቀችው የሚናገረው እዮብ፤ “ከሌላ ሴት ጋር ተኝተህ ነው የመጣኸው፤ ድሮም ወታደሮች ስትባሉ ሸርሙጦች ናችሁ” በማለት እንደሰደበችውና ተደባድበው መተኛታቸውን ተናግሯል፡፡ ከሌሊቱ 11፡00 ሰአት ላይ ትንሽ በረድ ብሎላታል በሚል ግንኙነት እንዲፈጽሙ ሲጠይቃት ግን የማታውን ዓይነት ስድብ ደግማ እንደሰደበችው የገለፀው ወታደር ኢዮብ፤ ይሄኔ ተናዶ አንገቷን አንቆ እንደገደላት ለፖሊስ የሰጠው ቃል ይጠቁማል፡፡ ወታደር ኢዮብ በከባድ ሰው የመግደል ወንጀል ተከስሶ፣ በማረምያ ቤት ፍርዱን እየተጠባበቀ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡
በሰሜን ወሎ ላስታ ላሊበላ የተወለደው በሪሁን መብሬ፤ ወደ አዲስ አበባ የመጣው የአባቱን ሞት ተከትሎ  ከእናቱ ጋር ነበር - በ1997 ዓ.ም ፡፡ በ16 ዓመት የታዳጊነት ለጋ ዕድሜው ከአዲስ አበባ ጋር የተዋወቀው በሪሁን፤ ቀን እየሰራና ማታ እየተማረ እናቱንና እህቱን ይረዳ ነበር፡፡ ከሦስት ዓመት በኋላ ትዕግስት አበራ ከተባለች ወጣት ጋር ተዋወቀ፡፡ ለአራት አመታት በፍቅር ከቆዩ በኋላ ግን ትዕግስት አብራው በፍቅር  መቀጠል እንደትማፈልግ ነገረችው፡፡ በሪሁንም፤ “እኔ ወደ ክ/ሀገር እስክሄድ ድረስ ከማንም ወንድ ጋር እንዳላይሽ” ሲል እንዳስጠነቀቃት ለፖሊስ ከሰጠው ቃል መረዳት ተችሏል፡፡ ሆኖም ሐምሌ 25 ቀን 2004 ዓ.ም በቦሌ ክ/ከተማ  ልዩ ቦታው ጐሮ ገብርኤል በተባለ ስፍራ ከምሽቱ 1፡00 ሰአት ገደማ ላይ ሙልዬ ከተባለ ወንድ ጋር ቆማ ያያታል፡፡ ይሄኔ ነው ጠጋ በሎ “ከወንድ ጋር እንዳላይሽ ብዬ አልነበረም?” ሲል በኃይለቃል የጠየቃት፡፡  “ምን አገባህ!” ስትል እሷም በቁጣ እንደመለሰችለት በሪሁን ያስታውሳል፡፡ ወዲያው መለስ ይልናም አብሯት የቆመውን ሙሉዬ የተባለ ወጣት፤ “አብረሃት እንዳላይህ አላልኩህም” ብሎ ያፈጥበታል፡፡ “እኔ አይደለሁም የጠራኋት፤ እሷ ናት የጠራችኝ” በማለት ይመልሳል - ወጣቱ፡፡ በሪሁን እንደገና ወደ ትዕግስት ዞሮ “ከማንም ወንድ ጋር እንዳላይሽ አላልኩሽም ወይ?” ሲላት አሁንም ደግማ “አያገባህም!” ትለውና አብሯት የነበረውን ወጣት ጠርታ ይዛው ትሄዳለች፡፡
በሪሁን በድርጊቷ በግኖ ወደ ቤቱ በመሄድ፣ ከወሎ ያመጣውን ብረት ለበስ ስለት ይዞ እንደወጣ ይናገራል፡፡ ትዕግስትን ለብቻዋ አግኝቷት ሊያነጋግራት ቢሞክርም “አትንካኝ” በማለት እንዳመናጨቀችው  የገለፀው በሪሁን፤በያዘው ስለት ጡቷና ጀርባዋ ላይ ወግቶ ገድሏታል፤ የክስ መዝገቡ እንደሚጠቁመው፡፡  በሪሁን በፈፀመው ከባድ የሰው መግደል ወንጀል ተከሶ ፍርዱን እየተጠባበቀ ይገኛል፡፡
በአዲስ አበባ የተወለደው የወንደሰን ይልማ፤ በ1998 ዓ.ም መስከረም ወር ላይ ነበር ከሁለት ዓመት ፍቅረኛው ፍሬህይወት ታደሰ ጋር በቤተክርስቲያን ውስጥ ጋብቻውን  የፈፀመው፡፡
ሁለት ልጆች ወልደው በሠላም እየኖሩ ሳለ በመሃል በሚከሰቱ ጠቦች ባለቤቱ ከቤት እየወጣች ቤተሰቧ ጋር ትሄድ እንደነበር የሚናገረው የወንድወሰን፤ “በዚህም የተነሳ ታምሜ እተኛ ነበር” ሲል ለፖሊስ ቃሉን ሰጥቷል፡፡ ጠባቸው እያየለ በመጣበት በ2003 ዓ.ም ግን ፍሬህይወት ቤተሰቧ ጋ አልነበረም የሄደችው፡፡ ቦሌ አካባቢ ቤት ተከራይታ ከሁለት ልጆቿ ጋር መኖር ጀመረች፡፡ በተደጋጋሚ ሽምግልና ብልክባትም አሻፈረኝ አለች ይላል - የወንደሰን። ለአንድ ዓመት ተለያይተው ለየብቻ ቢኖሩም ታርቀው አብረው እንደሚኖሩ ተስፋ ያደርግ እንደነበረ የሚናገረው የወንደሰን፤ ባለቤቱ ግን የፍቺ ማመልከቻና የንብረት ማሳገጃ ወረቀት ከፍ/ቤት እንዳመጣችለት ይገልፃል።
በዚህ መሃል ልጆቹ ማየት እንዳልቻለ የሚያስታውሰው የወንደሰን፤ ለፍ/ቤት አመልክቶ ልጆቹን ቅዳሜ ቅዳሜ እንዲያያቸው ተወስኖለት ነበር፡፡ ልጆቹን ሲያገኛቸው ግን “ለምን መጣህ? አንተ አባታችን አይደለህም? አባታችን ጋሼ ነው” በማለት የጥላቻ ስሜት ያንፀባርቁበት እንደነበር ገልፆ በዚህም በእጅጉ ስሜቱ እንደተጐዳ ለፖሊስ ገልጿል፡፡ በዚህም የተነሳ ጥቅምት 10 ቀን 2005 ዓ.ም በ10ሺህ ብር ከሰው ላይ በገዛው ክላሽ  የልጆቹ እናት ላይ 18 ጥይቶችን በማርከፍከፍ ህይወቷን ያጠፋ ሲሆን፤ ፍርዱን በማረምያ ቤት ሆኖ በመጠባበቅ ላይ ይገኛል፡፡
በጐንደር አምባጊዮርጊስ የተወለደችው አማረች አቸናፊ፤ እናትና አባቷ ከሞቱ በኋላ ነበር በ14 ዓመቷ ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በሰው ቤት ሰራተኝነት ተቀጥራ መስራት የጀመረችው፡፡  በ2002 ዓ.ም ግን ፍቅረኛዋ ከነበረው ዳንኤል የተባለ ግለሰብ ጋር በአንድ ጐጆ ውስጥ የጋራ ኑሮ ይጀምራሉ፡፡ አማረች እንደምትለው፤ ፍቅረኛዋ አምሽቶ እየመጣና ከተለያዩ ሴቶች ጋር በስልክ እያወራ ያበሳጫት ነበር። የከፋ ነገር የተፈጠረው ግን ሰኔ 10 ቀን 2004 ዓ.ም ነበር፡፡ ከምሽቱ 4፡00 ላይ ቤታቸው ደጃፍ ላይ የባሏን ድምፅ ሰምታ መውጣቷን የተናገረችው አማረች፤ ባለቤቷ ከጐረቤት ሴት ጋር ቆሞ ሲያወራ እንዳየችው ለፖሊስ ገልፃለች፡፡ ቤት ከገባም በኋላ ስልክ ደውሎ “ገብቻለሁ… አታስቢ” ብሎ ሲያወራ መስማቷንና  ይሄም በመካከላቸው የከረረ ጭቅጭቅ መፍጠሩን አስታወሳ፤ጐረቤቶቻቸው እሱን ጠርተው  “አትረብሹን” እንዳሉት ትናገራለች፡፡ በጐረቤቶቹ ንግግር የተበሳጨው ባለቤቷም፤ “አዋረድሽኝ” በማለት ልብሱን በፌስታል ሸክፎ ይተኛል። “ሁልጊዜም ጩቤ ከኪሱ ስለማይጠፋ ልብሱን የሰበሰበው ገድሎኝ ሊጠፋ ነው” የሚል ስጋት ያደረባት አማረች፤ ባለቤቷ እንቅልፍ እስኪወስደው ጠብቃ ሶስት ሊትር ጋዝ ሰውነቱ ላይ በማርከፍከፍ ክብሪት እንደለኮሰችበት ጠቁማ፤ ጭንቅላቱ አካባቢ እሳቱ ሲሰማው እንደነቃና “አድኑኝ” እያለ ሲሮጥ በዱላ ጭንቅላቱን ደጋግማ እንደመታችው ተናግራለች፡፡ ተጐጂው ባለቤቷ በየካቲት 12 ሆስፒታል ህክምና ቢያገኝም  ህይወቱ ሊተርፍ አልቻለም፡፡ አማረችም በማረሚያ ቤት ሆና ፍርዷን እየተጠባበቀች ነው፡፡  

          ከሁለት ሣምንት በፊት ከአንድ ወዳጄ ጋር ቀጠሮ ነበረኝ፡፡ ለወትሮው የቀጠሮ ሰዓት መሸራረፍ የማይወደው ወዳጄ፣ በ “የሀበሻ ቀጠሮ” ልማድ ላይ አዘውትሮ ጣቱን የሚቀስረው ባልንጀራዬ ከተቀጣጠርንበት ቦታ በሰዓቱ መድረስ አልቻለም፡፡
በርግጥ እኔም አሥር ደቂቃ አሣልፌ ነበር ከቦታው የደረስኩት፡፡ በቀጠሮ ሰዓት የማያወላዳው ባልንጀራዬ እንደዓመሉ፣ በኋላቀር የቀጠሮ ሰዓት ልማዴና አመለካከቴ እያላገጠ፣ የወግ መጀመሪያ ያደርገኛል ብዬ እራሴን እያዘጋጀሁ ብመጣም፣ ከቀጠሮው ቦታ አላገኘሁትም። ቀድሜ በመድረሴ ከፉተታው ብድንም ባልተለመደ መልኩ መኪናውን በአካባቢው ሳጣት ሃሳብ ውስጥ መግባቴ አልቀረም፡፡ ተንቀሳቃሽ ሥልኬን አውጥቼ ልደውልለት አልኩና “አሁን እየነዳ ሊሆን ይችላል” ብዬ ለተጨማሪ አሥር ደቂቃዎች መታገስ ግድ አለኝ፡፡
አስር ደቂቃዎች አለፉ፡፡ ስልክ ደወልኩ - አይነሣም። አሁን ትንሽ መደናገጥ ጀመርኩ፡፡ ባልንጀራዬ በጤናው ከግማሽ ሰዓት በላይ አይዘገይም፡፡ የስልኩ በተደጋጋሚ አለመነሳት ደግሞ ድንጋጤዬን እየጨመረው መጣ፡፡ ምንም እንኳ የትራፊኩ መጨናነቅ የመዲናችን የየዕለት ግብር ቢሆንም፣ ባልንጀራዬ ወደቀጠሮ ቦታው የመምጫ ጊዜውን አስረዝሞ፣ ቀድሞ ለመነሳት ይሞክራል እንጂ በምንም መልኩ የመዘግየት ልማድ የለውም፡፡ እርሱም፣ በቀጠሮ ሰዓት ላለመገኘት የሚቀርብን ምንም አይነት ሰበብ አይቀበልም፡፡
በትራፊክ መጨናነቅ፣ በታክሲ ወረፋ ወይም በሌሎች ማኅበራዊ እክሎች ጦስ ሳቢያ የሚፈጠር  የቀጠሮ መዘግየት እንዳለ ቢያምንም፣ “ቀድሞ በመነሳት ማካካስ ይቻላል” የሚል ቆራጥ “አብዮታዊ”ም በሉት “ልማታዊ” አቋም ነው የሚያራምደው፡፡ በተለያዩ የፊልም፣ የመጻሕፍት፣… … ምረቃ ላይ በተለይ የክብር እንግዳ በመጠበቅ የምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ከተባለው ጊዜ ሲዘገይ፣ አሥር ደቂቃ ጠብቆ ጥሎ ሲሄድ በተደጋጋሚ ስላየሁ፣ ይህን የቀጠሮ ሰዓት አስከባሪ አርበኛ  በድንገት ያውም ከግማሽ ሰዓት በላይ ሲዘገይ፣ ብደነግጥ ይፈረድብኛል?
ከክብደቴ ላይ ኪሎ ሥጋ ቀንሼ ከወዲያ ወዲህ ሥንቆራጠጥ፣ የባልንጀራዬን መኪና የምትመስል ተሽከርካሪ በርቀት ስትመጣ አየሁ፡፡ መኪናዋ እኔ ወዳለሁበት አካባቢ ስትቀርብ ሌላ እንደሆነች አረጋገጥኩ። ለአሥረኛ ጊዜ ይመስለኛል እየደወልኩ አልነሳ ያለው ስልክ፣ በመጨረሻ ተነሣና ምላሽ ሣይሰማ ተዘጋ። ባልንጀራዬ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንደሆነ ወይም እየነዳ እንዳለ ጠረጠርኩ፡፡ ቀጠሮ የያዝንበት ጉዳይ ብርቱ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ ባለ ጉዳዩም በዋናነት እርሱ ስለነበረ እንደማይቀር አውቃለሁ፡፡ የባልንጀራዬን  መጥፎ ዜና እንዳያሰማኝ ከአምላኬ ጋር መደራደሬ አልቀረም፡፡ በሰላም ያገናኘን እንጂ፣ ሥዘገይበት እርሡ የሚፈጥረውን ቡራከረዮ እኔ እንደማልደግመው፣ ለአምላኬም ለራሴም ቃል እስከመግባት ደረስኩ፡፡ “የጨነቀው እርጉዝ ያገባል” የሚባለው ምሣሌያዊ አነጋገር እንደዛሬ በተግባር ተተርጉሞብኝ የሚያውቅ አልመሰለኝም፡፡
በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለሁ፣ የባልንጀራዬ መኪና አጠገቤ መድረሷን ልብ ሳልል ብቀርም፣ ከኋላዬ ሲጠራኝ ግን አልደነገጥኩም፡፡ እንደውም ያላሰብኩት ንዴት ተናነቀኝ፡፡ “አንተ በአሥር ደቂቃ እያበድክ እንዴት ከአንድ ሰዓት በላይ ዘግይተህ ትመጣለህ? ለምንስ ስልክ አታነሣም?” እያልኩ ሳቅራራ፣ ባልንጀራዬ መኪናውን  ቦታ ለማስያዝ ወደ ኋላ እየነዳ ነበረ፡፡ እርሱ አይቶኛል ቦታ ይለቅልኛል ሲል፣ እኔም አይቶኛል ብዬ ዞሬ ስሳደብ መኪናዋ ለካ ወደ ቆምኩበት አቅጣጫ እየመጣች አጠገቤ ደርሳለች፤ በአካባቢው ያሉ ሰዎች ሲጮሁ፣ መኪናዋ እግሬ ሥር ስትቆም አንድ ሆነ፡፡
ከዚህ በኋላ ምን ሊፈጠር እንደሚችል የምትገምቱ ይመስለኛል፡፡ እኔ ከመበሳጨቴ የተነሣ የምናገረውን ሁሉ አላውቅም ነበረ፡፡ ባልንጀራዬ ከመዘግየቱ፣ ሊገጨኝ መቃተቱ የበለጠ አሳፈረው፤ ሲናደድና ሲደንግጥ ምንም መናገር የማይችል “ዝጋታም” የሚባል አይነት ሰው ነው፡፡ እንደምንም ተረጋግተን ስንነጋገር፣ ባልንጀራዬ ለመዘግየት ያበቃውን ምክንያት እየመረረውም ቢሆን ያስረዳኝ ጀመር። ምሣ ለመብላት መኪናውን ውጭ ላይ አቁሞ ወደ ሆቴል አመራ፡፡ ሰዓቱ 7፡30 ላይ እንደነበር ያስታውሳል፡፡ ሆቴሉ ከአንድ ዋና መንገድ ተገንጥሎ በሚገባ አገናኝ መንገድ ዳር የሚገኝ ቢሆንም፣ መንደር ውስጥ ሊባል የሚችል ነው፤ ሰፈሩ ደግሞ፤ ቦሌ ሩዋንዳ አካባቢ፡፡ ባልንጀራዬ 9፡00 ካዛንቺስ ላይ ቀጠሮ እንዳለው ስላወቀ፣ በእርሱ አገላለጽ ምሣውን፣ “ቷቷ…አድርጐ” ሒሣብ ከፍሎ፣ ከሆቴሉ ወጣና  ወደ መኪናው አመራ፡፡ መኪናውን ተዟዙሮ ገላመጣት፡፡ በሰላም ነበር የጠበቀችው፡፡ አስነስቶ ወደ ዋናው መንገድ የሚያወጣውን ብቸኛ የውስጥ ለውስጥ መንገድ ተያያዘው፡፡ ከዋናው መንገድ ጋ ሊደርስ ሲል ሰዓት ተመለከተ፡፡ ግማሽ ሰዓት ብቻ ነው የፈጀው፡፡ ኮራ ብሎ፣ ቀስ ብሎ እየነዳ 9፡00 ቀጠሮው ቦታ መድረስ እንደሚችል እያሰበ ወደፊት ሲመለከት፣  ብቸኛው የየውስጥ ለውስጥ መንገድ ጫፉ ላይ “በግሬደር” ገደል ሆኖ አገኘው፡፡  
መኪናውን ወደ ዳር አቁሞ፣ ምን እየተሠራ እንዳለ የሚመለከተውን ለማነጋገር በእግሩ ሄደ፡፡ ከፊት ለፊቱ ያለው ቱቦ ከተቀበረ በኋላ ጉዱጓዱ ተደፍኖ እንደሚያልፍ ተነገረው፡፡ “አሁን ሣልፍ እኮ ደህና ነበረ፤ ቢያንስ የመኪና ማለፊያ ከጫፍ በኩል ትንሽ ቦታ ለምን አልተዋችሁም?” ለሚለው አሳዛኝ ጥያቄ የቀረበለት የማስተዛዘኛ ማስመስል አልነበረም፡፡ አንድ በወጉ የማይናገር ሃላፊ ነገር፣ “ሰውዬ እንሥራበት አትረብሽ! ሁለት ሰዓት መታገሥ ያቅትሃል?...እንዴት እንደምንሠራ አንተ አትነግረንም…መኪናህን ትተሀት ሂድ፤ ያንተን መኪና ማን ይነካል…” የሚሉ የሚያበሣጩ የቃላት ጥይቶች አዘነበበት፡፡
ባልንጀራዬ በወጉ ከማያውቀው ሰፈር መኪናውን አቁሞ፣ ከግማሽ ሰዓት በላይ ሲከራከር ከቆየ በኋላ 8፡30 አካባቢ በታክሲ ወደ ቀጠሮው ለመምጣት እንደሞከረ ነገረኝ፡፡ ሁኔታውን ለማሳወቅ ተንቀሳቃሽ ሥልኩን ከኪሦቹ ውስጥ ሲፈልግ አጣው፡፡ መኪና ውስጥ አስቀምጦት መውረዱ ትዝ አለውና ወደ ቆመችው መኪናው አመራ፡፡ የመኪናው በር አልተዘጋም፤ ሣይዘጋው ይውረድ ወይም በአንዳች ተአምር ይከፈት እስከ ዛሬም አልታወቀም፡፡ ብቻ ተንቀሣቃሽ ስልኩ ከመኪናው ውስጥ ተሠወረ፡፡ ሲጨንቀው ወደ ሆቴሉ ሄደ፡፡ የእርሡን ሞባይል የበላ ጅብ እንዳላዩ አረዱት፡፡ ሥልኩ ላይ እንዲደውሉለት አደረገ፡፡ ሞባይሉ ይጠራል። ሞባይሉ ከጅብ አፍ እንዳልገባ ተሥፋ ተደረገ፡፡ መኪናውን አገለብጦ እንዲፈትሽም ተመከረ። የተባለውን ሁሉ አደረገ፡፡ ሞባይሉ ግን እስከ ዛሬም እንዳልተገኘ አውቃለሁ፡፡
ከአንድ ሰዓት በኋላ የተቆፈረው መንገድ ቱቦው ተቀብሮ ተጠናቀቀና በጐን በኩል እንዲያልፍ ተነገረው። መኪናው፣ አዲስ የተደፈነውን ጉድጓድ በማለፍ ታሪክ ብትሠራም፣ በቀጠሮው ሰዓት መድረስ አልቻለችም፡፡ ይኼን ሁሉ ጉድ አሣልፎ የመጣው ቀጠሮ አስከባሪው አርበኛ ባልንጀራዬ፣ ቀጠሮ ቦታው ከመድረሱ እኔንም ወደ ሞት አፋፍ ሊያደርሠኝ ነበር፡፡
በመጨረሻ፣ ጓደኛዬና እኔ ተረጋግተን ወሬ ሥንጀምር፣ ያጋጠመውን ነገር ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻ ሣይደብቅ ሊነግረኝ ቃል ገባ፡፡ ወዲያው ትንሽ እረፍት ወሠደና ፈገግ አለ፡፡ የነበርንበትን ቀዝቃዛ ድባብ የቀየረው ግን በድንገት “እንቆቅልሽ?” ሲለኝ ነበረ፡፡ በሁኔታው ተገርሜ ሣቅሁ፡፡ እየሣቀ “እንቆቅልሽ?” አለኝ በድጋሚ፡፡ “የጨነቀው እርጉዝ ያገባል ማለትስ አሁን ነው … ምን አውቅልህ?” በማለት መለስኩለት፡፡ “ጧት ታይቶ ማታ የሚጠፋ ምንድን ነው?” አለኝ፤ ኮስተር ብዬ፡፡ “ቀሽም? አሪፍ እንቆቅልሽ እንኳን ብትጠይቀኝ ምን አለ?” ብዬ ከተኩራራሁ በኋላ፣ “ለመሆኑ ቀልዱን ብትተው ምን አለ? … ለማንኛውም ጤዛ” በማለት መለስኩለት፡፡ አገር እንድሠጠው ሲጠይቀኝ፣ “ምን አገር አለህን? አገር ቢኖረን መቼ እንዲህ እንሆን ነበረ …” ስለው ከትከት ብሎ ሣቀና፣ “ጧት ታይቶ ከሰዓት በኋላ የሚጠፋ … የአዲስ አበባ መንገድ ነው!” አለኝ፡፡
እውነትም ጧት ታይተው ከሰዓት የሚጠፉ መንገዶች…! የመንገዶች ባለሥልጣን በፊታውራሪነት፣ ቴሌኮም በቀኝ አዝማችነት፣ መብራት ኃይል በግራ አዝማችነት፣ ውኃና ፍሳሽ ደግሞ በደጅ አዝማችነት የአዲስ አበባን መንገዶች ወይም አስፋልቶች እንዳሻቸው ያሣርሷቸዋል፤ በፈረቃ ይቆፍሯቸዋል፤ በተናጠል ያፈርሷቸዋል … ለአዲስ አበባ መንገዶች ሠቆቃና ብሶት ሲባል፣ ፍሬ ሣይዘሩ የሚያርሷቸውን ተቋማት፣ ቅርስ ሣያውቁ የሚያፈርሷቸውን አካላት 1ለ4 “የሚያደራጃቸው” አርቆ አሣቢ መሪ እንዴት ይጥፋ!?

Published in ህብረተሰብ

           “ይኼ የመስኖ ውሃ ከመምጣቱ በፊት ዝናብ ጠብቀን ነበር የምናርሰው። ስለዚህ ቤተሰብ ለማስተዳደር ብዙ እንቸገር ነበር፡፡ ከሦስት ዓመት በፊት የማደርገው ባጣና ግራ ቢገባኝ ከአካባቢው ጠፍቼ ልሰደድ ነበር፡፡፡ አክሽን ኤድና-ፓዴት የመስኖ ውሃ አምጥተው ከስደት አዳኑኝ” ያለችው ዙሪያሽ መኮንን ናት፡፡ በአንኮበር ወረዳ የእንዶዴ ጐጥ ነዋሪ የሆነችው ዙሪያሽ፤ የ28 ዓመት ወጣት ብትሆንም የሦስት ልጆች እናት ናት፡፡
“መሬቴ ትንሽ ብትሆንም የመስኖ ውሃ በመጠቀም ሽንኩርት፤ ቀይ ስር፣ ካሮት፣ ቃሪያ፣ ድንች ጐመን አለማለሁ፡፡ አትክልቱን እየወሰድኩ በመሸጥ ለችግሬ አውላለሁ፤ ቤቴንም ለውጫለሁ። ልጆቼንም አስተምራለሁ፣ ትልቋ ልጄ 9ኛ ክፍል ናት፡፡ ሕይወቴም ተለውጧል፣ እንለብሳለን፣ በልተን እናድራለን፣ እየቆጠብን ወደ ባንክም መወርወር ጀምረናል፡፡ በወር 50 ብር ባንክ እከታለሁ፤ አሁን 3ሺህ ብር ቆጥቤአለሁ፡፡ በወር ደግሞ 180 ብር እቁብ እጥላለሁ፤ ቆርቆሮ ቤትም ለመሥራት እያሰብኩ ነው፡፡ ተለውጫለሁ ብዬ አስባለሁ፤ ፓዴት አክሽንን አመሰግናለሁ” ብላለች፡፡
አክሽን ኤድና ፓዴት (የባለሙያዎች ኅብረት ለልማት) እ.ኤ.አ ከ2006 ጀምሮ እስካሁን ድረስ በአንኮበር ወረዳ፣ ከሕዝቡና ከአስተዳደሩ ጋር በመተባበር፣ በርካታ የልማት ሥራዎች እያከናወኑ ይገኛሉ፡፡ ሁለቱ ድርጅቶች፣ ባከናወኑት ጠቃሚ ሥራ የልማቱ ተጠቃሚ የሆነው ሕዝብ ሕይወታቸው መለወጡን ይናገራሉ፤ አስተዳደሩም ይመሰክራል፡፡ ለመሆኑ ምን ቢያከናውኑ ነው አመኔታና አክብሮት የተቸራቸው?
አሁን መሻሻል አሳይተዋል እንጂ የኅብረተሰቡ ዋነኛ ችግሮች በነበሩት፣ በምግብ ዋስትና፣ በሴቶች ልማት፣ በጤናና ኤች አይቪ ኤድስ ዙርያ ከሕዝቡና ከአስተዳደሩ ጋር በመመካከርና በመግባባት መሥራታቸውን ቀደም ሲል የአንኮበር ፕሮግራም አስተባባሪና መሥራች፣ አሁን ደግሞ በፓዴት ዋና መ/ቤት የፕሮግራም ማስተባበሪያ ኃላፊ የሆኑት አቶ ብርቅነህ ተዋቸው ይናገራሉ፡፡
አቶ ብርቅነህ፣ በምግብ ዋስትና ዘርፍ፣ የተፈጥሮ ደን ጥበቃ፣ መስኖ ልማት፣ የገበሬውና የመንግሥት ባለሥልጣናት አቅም ማጐልበት ሥልጠና መስጠታቸውን፣ ለሴቶችና ወጣቶች ደግሞ የገቢ ማስገኛ መፍጠራቸውን ይናገራሉ፡፡ በጤና ዘርፍ፣ ንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማሟላት 29 ምንጮች አጐልብተው ከ7ሺህ ሕዝብ በላይ ተጠቃሚ ማድረጋቸውን፣ 1,200 ሰዎች ውሃ የሚያገኙበትንና በአራት ከተሞች በሴቶች የሚመራ የውሃ ማኅበር ከመንግሥት ጋር ሲያቋቁሙ፣ የሴቶች የአመራር አቅም እንዲጐለብት ድጋፍ ማድረጋቸውንና የሴቶች ማኅበር ማቋቋማቸውን፣ ከመንግሥት ጋር በመሆን ኤች.አይ.ቪ ቫይረስ በደማቸው ውስጥ ያለባቸው ሰዎች ማኅበር እንዲቋቋምና የገቢ ማስገኛ እንዲፈጠርላቸው ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
በትምህርት ዘርፍ፣ የአንደኛና 2ኛ ደረጃ ት/ቤቶች አቅም እንዲጐለብት ድጋፍ ከማድረጋቸውም በላይ በወረዳው ያልነበረ ቅድመ መደበኛ ት/ቤት (መዋለ ሕፃናት) እንዲከፈት አድርገዋል፡፡ መደበኛ ት/ቤት የውስጥ ቁሳቁስ እንዲሟላና ክበባት እንዲቋቋሙ፣ የክፍል ጥበትን ለማስወገድ አራት ክፍሎች ያላቸው ስድስት ብሎኮች መሥራታቸውን፣ በ2ኛ ደረጃ ት/ቤት ደግሞ የቤተመጻሕፍት ብሎክ በመሥራት ተማሪዎች መጻሕፍት እንዲያገኙና አንድ የአስተዳደር ብሎክ መሥራታቸውን ተናግረዋል፡፡  
ከከተማ ራቅ ባሉ የገጠር መንደሮች ንፁህ የመጠጥ ውሃን ለማቅረብ፣ ምንጮች አጐልብተው ሰዎችና እንስሳት ለየብቻ እንዲጠጡ፣ ልብስ ማጠቢያ ገንዳና የገላ መታጠቢያ ሻወር ሠርተው ሕዝቡ ንፅህናውን እንዲጠብቅ ማድረጋቸውን ይናገራሉ፡፡ የደጋና የወይና ደጋ ከብቶች ውሃ ሲጠጡ አልቂት በአፋቸው እየገባ ለጉዳትና ለሞት ያደርሳቸው ነበር። ይህን የገበሬውን ችግር ለመቅረፍ፣ የከብቶች ውሃ መጠጫ ሠርተው እልቂት እንዳይገባ በሽቦ ወንፊት ከድነው እንዳስረከቡ ገልጸዋል፡፡
የወጣቶችን ሥራ አጥነት ለመቀነስ፣ አስተዳደሩ፣ አክሽን ኤድና ፓዴት ወጣቶችን በማኅበር አደራጅተው የመሥሪያ ቦታና ቁሳቁስ አሟልተው ሰጥተዋል፡፡ ኤችአይቪ በደማቸው ውስጥ የሚገኝ ሰዎችን በማኅበር አደራጅተው፣ የገቢ ማግኛ እንዲፈጠርላቸው ሙቅና ቀዝቃዛ ሻወር ያላቸው 10 ክፍሎች ፔንሲዮን ሠርተው ሰጥተዋል፡፡
ሌላው የልማት ሥራ፣ የተጐዳ አካባቢ መልሶ እንዲያገግም ማድረግ ነው፡፡ አፋጀኸኝ በተባለው ጐጥ ጥሩ የእርሻ መሬት የነበረው ስፍራ ከተራራው በሚፈሰው ውሃ ተቦርቡሮ የተፈጠረው ገደል ሰውም ሆነ እንስሳ አያሻግርም ነበር፡፡
ያንን 3 ሜትር ያህል ጥልቀት የነበረውን ገደል፣ አክሽንኤድ ፓዴት ሕዝቡን በማሳመን አፈሩ እንዳይሸረሸር ሦስት ጊዜ በጋቢዮን በመሙላትና የተለያዩ ዛፎች በመትከል፣ አካባቢው ሊድንና እንደገና ሊያገግም ችሏል፡፡ በዚሁ ጐጥ ነዋሪ የሆነው የ32 ዓመቱ ዲያቆን ዘነበ ወርቅነህ፤ የእርሻ ማሳ የነበረው መሬት በጐርፍ ተገምሶ ገደል ሲሆን እያየ እንደነበር ጠቅሶ፣ ያ መሬት አገግሞ በማየቱ ሰው ማጥፋትም ሆነ ማልማት ይችላል በማለት አግራሞቱን ገልጿል፡፡
አክሽን ኤድ-ፓዴት በፈጠረላቸው የመስኖ ውሃ ሕይወታቸው መለወጡን የሚናገሩት ሌላው ገበሬ አቶ ወንዳፈራው ጌጤ ናቸው፡፡ የጐልጐ ዙሪያ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ወንዳፈራው፤ የ45 ዓመት ጐልማሳ ሲሆኑ የ5 ወንዶችና የሁለት ሴት ልጆች አባት ናቸው፡፡ አቶ ወንዳፈራው የመስኖውን ውሃ ካገኙ በኋላ፣ ሸንኮራ አገዳ፣ ሙዝ፣ ቲማቲም፣ ጥቅል ጐመን፣ ሽንኩርት፣ ቃሪያ፣ ካሮት፣ … የመሳሰሉ የጓሮ አትክልቶች እያመረቱ ነው፡፡
“መስኖ ባልነበረ ጊዜ ሁለቴ ነበር የምናመርተው። ዛሬ ዕድሜ ለፓዴት አክሽን ኤድ በየሦስትና አራት ወሩ እያመረትን እንሸጣለን፡፡ ጐመኑ ሲደርስ ነቅለን ሽንኩርት እንተክላለን፡፡ ጐርጐ ገበያ እየወጣን በመሸጥ ለልጆቻችን ደብተርና ሌላም ነገር ለማሟላት ብዙ ረድቶናል፡፡ አሁን ስለመስኖ አጠቃቀም በየጊዜው ሥልጠና እየሰጡን ልምድ አዳብረናል፡፡ ድሮ ሽንኩርትና ቃሪያ ከገበያ እየገዛን ነበር የምንበላው፡፡ ዛሬ ግን ተክለን እየተጠቀምን ነው። ሸንኮራውም ሙዙም ተሸጦለታል፡፡ ከዚህ በታች 1,500 ብር ሸጬለታለሁ፡፡ ከዚያ በላይ ያለው ደግሞ 800 ብር ያወጣል ብያለሁ፡፡ በአሁኑ ሰዓት ሕይወታችን ተለውጧል፡፡ በተለይ ተማሪዎች ሳይጨነቁና ትምህርት ሳያቋርጡ ነው የሚማሩት” በማለት መስኖ ያስገኘላቸውን ጥቅም አስረድተዋል።
አክሽን ኤድ-ፓዴት በአንኮበር ወረዳ የተሳካ ሥራ እያከናወነ መሆኑን ተጠቃሚ አርሶ አደሮች ብቻ ሳይሆኑ፣ የወረዳው አስተዳደርም ይመሰክራል። አቶ ዋሲሁን ብርሃኑ የአንኮበር ወረዳ ም/አስተዳዳሪ፣ የአካባቢ ጥበቃና መሬት አስተዳደር ኃላፊ፣ አቶ ታዲዎስ እሸቴ የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊ፣ አቶ ዮሐንስ ላቀው የገንዘብና ኢኮኖሚ ጽ/ቤት ኃላፊና ወ/ት ሜሮን አበበ የሴቶች ሕፃናትና ወጣቶች ጽ/ቤት ኃላፊ በጋራ በሰጡት መግለጫ፣ አክሽን ኤድ-ፓዴት፣ የመንግሥትን ክፍተት ለመሙላት አብሮን የሚሠራ አጋራችን ነው ብለዋል፡፡
የድርጅቶቹን ሥራ በአራት ዘርፍ በመክፈል ማየት ይቻላል ያሉት አቶ ዋሲሁን፤ በግብርና፣ በትምህርት፣ በጤና፣ ሴቶችና ወጣቶችን ጠቃሚ ያደረጉ ተግባራትን ፈጽሟል፡፡ በግብርና ዘርፍ በምግብ ዋስትና፣ በተቀናጀ የተፈጥሮ ሀብት፣ የተፈጥሮ ተፋሰስ ጥበቃና በመስኖ ልማት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ያደረጉ ብዙ ሥራዎች አከናውኗል ብለዋል፡፡
የትምህርት ጥራትን ለማሳደግና ት/ቤቶችን ምቹና ሳቢ ለማድረግ፣ ብሎኮችን በመስራትና የውስጥ ቁሳቁስ በማሟላት ከፍተኛ ድጋፍ አድርጓል። በጐልማሶች ትምህርት ዘርፍ ማንበብና መጻፍ የማይችሉ 37 ሺህ ዜጐች ከመሃይምነት እንዲወጡ ለአምስት ዓመት ድጋፍ ሲያደርግልን ቆይቷል፡፡
በጤና ዘርፍ ደግሞ 29 ምንጮች አጐልብቶ አርሶ አደሩ ንፁህ የመጠጥ ውሃ እንዲያገኝ ረድቷል። ምንም ለሌላቸው ሴቶችና ወጣቶች በተዘዋዋሪ ብድር በግ ገዝቶ እየሰጠ ተጠቃሚ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ በእኛ ወረዳ ከድርጅቱ ጋር ለሦስትና ለአራት ዓመታት ተከታታይ የሆነ ሰፊ ሥራ ሠርተናል፡፡ አሠራራቸው ግልፅ ነው፤ የፋይናንስ አጠቃቀማቸው በእኛ ሲስተም የሚተላለፍ በመሆኑ እንከን የለውም። ለሌሎች ድርጅቶችም አርአያ የሚሆን ነው፡፡ መጀመሪያ ያሉ ችግሮችን አጥንቶ፣ ከመንግሥት አካላትና ከአርሶ አደሩ ጋር በመወያየት፣ አርሶ አደሩና መንግሥት በባለቤትነት፤ አክሽን ኤድ-ፓዴት በድጋፍ ሰጪነት ይሠራል።
ማንኛውንም አርሶ አደርና ልጆች ብትጠይቁ “ፓዴት ይኑርልን፣ ሕይወታችንን ለወጠልን” ይላችኋል በማለት ለድርጅቶቹ ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል። የሌሎችም ጽ/ቤት ኃላፊዎችም አስተያየት ተመሳሳይና በሙገሳ የታጀበ ነበር፡፡   

Published in ህብረተሰብ
Sunday, 05 January 2014 00:00

“ሓቅ ሓቁን ለህፃናት”

በጥላቻና በእርግማን የተሞላ “መጽሐፍ”
ባለፈው ሳምንት ከቆምንበት እንቀጥል፡፡ የኢትዮጵያን አንድነት በማስጠበቅ ረገድ ከቴዎድሮስ ይልቅ ዮሐንስ የተሻሉ እንደነበሩ ጸሐፊው የገለጡበት መንገድ የተሳሳተ መሆኑን አመልክቼ ነበር የተሰነባበትነው፡፡
“የእንግሊዝ ተንኮል ያቅለሸለሻቸው አፄ ዮሐንስ ይህ ሃሳብ ይዞ ለመጣ የእንግሊዝ ልኡክ ተቀብለው ከሃገሬ መሬት ቅንጣት ታክል ቆርሶ የመስጠት ስልጣን የለኝም፡፡ ብለው መለሱት፡፡ አፄ ዮሐንስ የሰሩዋቸው ስራዎች ከሳቸው በፊት የነበሩት ንጉስ አፄ ቴዎድሮስ አልተገበሩትም፡፡ በአፄ ምኒልክም አልተደገመም” (ገጽ 37) ይሉናል፤ ጸሐፊው ዮሐንስን ከቴዎድሮስና ከምኒልክ የግድ የተለዩ የአገር ተቆርቆሪ ለማድረግ፡፡
ሃገርን በመውደድ ረገድ ሶስቱም መሪዎች የሚታሙ አልነበሩም፡፡ ሆኖም ከቴዎድሮስም ሆነ ከምኒልክ ለእንግሉዞች በጣም ቅርብ የነበሩት ዮሐንስ መሆናቸው ደግሞ መካድ የለበትም፡፡ የእንግሊዞችን ከፍተኛ የጦር መሳሪያና የፖለቲካ ድጋፍ ባያገኙ ኖሮ በዝብዝ ካሳ ከደጃዝማችነት የዘለለ ሥልጣን ላይኖራቸው ይችል እንደነበር የታሪክ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡
ለሥልጣን የናወዙ መኳንንትና መሳፍንት ከእንግሊዞች ጐራ ተሰልፈው ባያጨናግፉባቸው ኖሮ ቴዎድሮስ እንኳንስ አገራቸውን ኢየሩሳሌምንም ከቱርኮች አገዛዝ ነፃ የማውጣት ህልም ነበራቸው፡፡ ምኒልክም ቢሆኑ የፈረንጆችን ተንኮል በመቋቋም ረገድ ከሁሉም የተሻለ የሠሩ ለመሆናቸው የአድዋ ድል ብቻ በቂ ነው። ሐረርን ከግብፆች ግዛት ነፃ ያወጧትም ምኒልክ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
የምኒልክን ጭካኔ ሲገልፁም ፀሐፊው እንዲህ ብለዋል “ግፍ ከመፈጸም አኳያ ግን በትግራይ ህዝብ የፈጸሙት ዘመነሸ(ሸ) እየተባለ የሚታወቅ አሰቃቂ ያ የግፍ ዘመን አልፎዋል፡፡ ሲከተሉት የነበረ ፖሊሲ ከፋፍለህ ግዛ መሆኑ ተደጋግሞ የተነሳ ጉዳይ ነው፡፡ የአፄ ምኒሊክ ለሁለት ከፍለህ መግዛት የስልጣን ስስታምነት የፈጠረው ነው። ይህም እውን የሆነው ትግራይን ለማዳከም ትግራይ ትግርኝን ለሁለት ከፍሎ የኢትዮጵያ ድንበር በመረብ እንዲወሰን ማድረጋቸው ለአሁን ትውልድ ጦስ መሆን አስተዋጽኦ አለው” (ገፅ 59)
የፀሐፊው ሃሳብ “የእምየን እከክ ወደ አብየ” መሆኑ ነው፡፡ እዚህ ነጥብ ላይ በድፍረት፣ በእውነትና በማስረጃ መከራከር ያስፈልጋል፡፡ የጸሐፊው ስሜታዊነት ጐልቶ ከወጣባቸው አጋጣሚዎች አንዱም ይህ ይመስለኛል፡፡ ኤርትራን ከትግራይ ሳይሆን ከመላው ኢትዮጵያ የነጠላት የምኒልክ ከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ አይደለም፡፡ አፍሪካዊው ጀግና ቱርክ ፓሻ አሉላ አባ ነጋ ዶጋሊ ላይ በአንድ ቀን ጦርነት 500 ጣሊያኖችን ድባቅ ሲመቱ፣ አጤ ዮሐንስ ጀግናቸውን በመሾምና በመሸለም ፋንታ “ሳታስፈቅደኝ ለምን የሃገር ጠላት ወጋህ” ብለው ወቅሰዋቸዋልኮ፡፡ ለኤርትራ ከቀረው የኢትዮጵያ ከፍል መነጠል የተለያዩ ምክንያቶች መኖራቸው እውነት ቢሆንም ዋናው ግን እንግሊዞች አጤ ዮሐንስን ማታለላቸውና በግብፆችና በደርቡሾች ጦርነት ምክንያት አሉላን ከአስመራ ማንሳታቸው ነው፡፡
የፀሐፊው መከራከሪያ “ምኒሊክ ኤርትራን በጉልበት አላስመለሱም፤ ውስጥ ውስጡንም ከጣሊያን ጋር ተስማምተዋል” የሚል ነው፡፡ ፖለቲካዊ ድጋፍ ለማግኘትና ዘውድ ለመቀዳጀት ሲል ወገኑን እየከዳ ውስጥ ውስጡን ከፈረንጅ ጋር ያልተዋዋለ ማን አለ? ዮሐንስም’ኮ ሊቋቋሙት ያልቻሉትን ቴዎድሮስን እንዲጥሉላቸው እንግሊዞቹን ከምጽዋ መቅደላ ድረስ መርተው አምጥተዋል፤ ለዚህ ወሮታም በርካታ የጦር መሳሪያ ከጀኔራል ናፒር ተበርክቶላቸዋል፡፡ ለጦር መሳሪያና ለሥልጣን ሲሉ ያገራቸውን ዳር ድንበር በጠላት ያስደፈሩትም ያኔ ነው፡፡ ምኒልክም ከጣሊያኖች ያውም በግዥ የጦር መሳሪያ ማግኘታቸው እውነት ነው፡፡ ግን ጣሊያንን  በራሱ መሳሪያ አላጄ፣ መቀሌና አድዋ ላይ ድባቅ መቱበት እንጂ ለወገናቸው መቅጫ አልተጠቀሙበትም፡፡
በመሠረቱ ኤርትራ የሄደችው ከላይ በገለጽሁትና ማዕከላዊ መንግስት ባለመጠናከሩ ምክንያት ሆኖ ሳለ የምኒሊክን ስም እያነሱ በከንቱ ማጉደፍ ዕርባና ያለው አይመስለኝም፡፡ የሩቁን እንተወውና እስከ 1983 ግንቦት ድረስ’ኮ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር ነበረች፡፡
እዚህ ላይ ፀሐፊውን አንድ ጥያቄ ልጠይቅ፡፡ አቶ አታክልቲ ታጋይ የነበሩ መሆንዎን በ”መጽሐፍዎ” ነግረውናል፡፡ እኒያ አምርረው የሚጠሏቸውና “ደቂቀ ምኒሊክ” የሚሏቸው ኃይሎች’ኮ ኤርትራን ከእናት ሀገሯ ቀላቅለዋት ነበር፡፡ ኤርትራን ከእናትዋ የለያት ማን እንደሆነ ያውቁት የለም እንዴ!
በ1974 ዓ.ም በተካሄደው መጠነ ሰፊ የቀይ ኮከብ ዘመቻ’ኮ ሻዕቢያ “እግሬ አውጭኝ” እያለ ወደ ሱዳንና ፈጣሪዎቹ ወደሆኑት የአረብ አገሮች እየፈረጠጠ ነበር፡፡ ለሀገሩ አንድነት ሲዋደቅ በነበረው የኢትዮጵያ ሠራዊት ላይ የተኮሰው ማነው? “ከሃዲው” ምኒልክ ይሆን? እባክዎ አቶ አታኸልቲ ቀልድዎን ያቁሙ፡፡ ይህንን ሐቅ’ኮ ባልደረቦችዎ በኩራት በየመድረኩ የሚናገሩት ነው፡፡ “ደቂቀ ምኒሊክ” በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ ኤርትራን ከመለሷት ብዙ ጊዜ ነበር፡፡ እናም ኤርትራን ለማስገንጠል ወገኑን ከጀርባ ሆኖ ሲወጋ የኖረና በ1983 ዓ.ም ለሻዕቢያ አሳልፎ የሰጣት፣ የእርስዎን “ትግራይ ትግርኝ” ለሁለት የሰነጠቃት ምኒልክ ሳይሆን እርስዎ በደንብ የሚያውቋቸው የልጆች ፖለቲካ (child politics) አራማጆችና አለአዋቂዎች ናቸው፡፡
“የኤርትራ ህዝብ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው” የሚል አቋም ያራመደውም እርስዎ የታገሉለት ድርጅት እንጂ ምኒልክና ሸዋዎች አይደሉም፡፡ ከሰባ ሺህ በላይ ወጣቶችን ከበላ በኋላ እልባት ባላገኘው የባድመ ጦርነት ላይስ “ድንበሩ የቅኝ ግዛት ጊዜ ውል መሆን አለበት” ብሎ የተከራከረ ማነው? ምንስ ለማግኘት ታስቦ ነው? እና ወዳጄ ታሪክና ስሜት የተለያዩ በመሆናቸው ጥንቃቄ ያስፈልግ ይመስለኛል፡፡
የምኒልክን ዘረኝነት ሲገልፁም “መጀመሪያ ለከፍተኛ ሹመት የሚመረጡት ከራሳቸው ዘር ሸዋዎች ናቸው፡፡ ከሸዋዎቹም በኋላ የግድ ሆኖ ከሌላ ከተመረጠ አንዳንዱን በዓይነቁራኛነት በሚኖሩበት ሁኔታ ይሆናል፡፡ እንደዚህ ዕድል ሲታጣ የአንዱ አካባቢ የሆነ ታማኝ ሹመኛ ለሌላው እንዲቆጣጠረው በማድረግ ውስብስብ ያደርጉታል” ይሉናል (ገጽ 60) ጸሐፊው፡፡
እዚህ ላይም አቶ አታኸልቲን እየተገረምሁም ቢሆን መጠየቅ ግድ ሆኖብኛል፡፡ ምኒልክ ዘረኛ ነበር ካሉ ለምን የታገሉለት ስርዓት በዘር ላይ የተመሠረተ የአስተዳደር ዘይቤ ተከተለ? ለምንስ ምደባ ላይ ሁሉ (በተለይ በፌደራል መ/ቤቶች) የአንድ ዘር ሹመኞች አለመጠን እንዲበዙ ተደረገ? የምኒሊክን ከሸዋ ብቻ መሾም የምትኮንኑ ከሆነ ለምን ዛሬ ትደግሙታላችሁ? ከምኒልክ የተማራችሁት ከሆነ ለምን ምኒልክን መወንጀል አስፈለገ? ምኒልክ ሲመድቡ ወይም ሸዋዎችን ሲሾሙ ወንጀል ይሆናል፤ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ላይ እርስዎና ድርጅትዎ ሲፈጽሙት ግን ጽድቅ ነው ማለት ነው?
“ራስ አሉላን የአድዋ፤ ራስ ሐጐስን ደግሞ የሽሬ አስተዳዳሪ አርገው በመሾማቸውና የስልጣን አቀማመጡ ያልነበረ በመኖሩ አገዳደሏቸው” ያሉት ማጣቀሻም የምኒልክን ተንኮልና ከፋፋይነት ወይም ዘረኝነት  ሳይሆን ለጋስነታቸውን የሚያሳይ ይመስለኛል፡፡ ሁለቱ ታላላቅ ራሶች ራስ በራሳቸው የተገዳደሉትም በዘመኑ በነበረው የስልጣን መስፋፋት እንጂ ምኒልክ የሸዋን ሰው አድዋ ወይም ሽሬ ላይ ስለሾሙ አይደለም፡፡ ሲወነጅሉም በአግባቡ እንጂ አቶ ጸሐፊ፡፡
“ቴሌፎን ወደ ኢትዮጵያ የገባ ለጣሊያን መንግስት የስለላ ሥራ ለማቀላጠፍ እንደነበር ከነ ዝርዝር ማስረጃው ሮማ ውስጥ እንዳለ አይረዱትም” ብለውናል ጸሐፊው፤ ምኒልክ ስልክ በማስገባታቸው የሚያመሰግኗቸውን ሰዎች ሲወቅሱ (ገፅ 63)
ይህ አስተሳሰብ በመሠረቱ ፍጹም የተሳሳተ ብቻ ሳይሆን ፀረ ስልጣኔም ይመስለኛል፡፡ በኢህአዴግ ዘመን ተንቀሳቃሽ ስልክ እስከ አርሶ አደሩ መንደር እንዲደርስ የተደረገው ለስለላ ነው ማለት ነው? ለነገሩ ምኑን ይሰለላል? ተሰልሎ፣ ተሰልቦ አልቋልኮ፡፡ ስልኩ የገባው ለስለላ ከነበረ ውሃ፣ መብራት፣ ባቡር፣ መኪና፣ ፖስታ ወዘተ ለምን አገልግሎት ነበር የገባው? አቶ አታኽልቲ! ለጣሊያን ወይስ ለፈረንሳይ ጥቅም? ይህም ያልበሰለ አስተያየት ውጤት ነው፡፡
“የአፄ ዮሐንስ ሂዎት የምኒሊክ ክዳትና ተንኮል እንጂ ሌላ ከአገር ውስጥ ያጋጠመው የሚጋነን ችግር አልነበረም-(ገፅ 75)” የሚለው አገላለጽም ለብቻዬ ፈገግ አሰኝቶኛል፡፡ ምኒልክና ዮሐንስ’ኮ ወዳጄ በክህደት ሊወቃቀ አይችሉም፡፡ ምኒሊክ ክህደትን ከማን ተማሩ ነው ጥያቄው፡፡ የመጀመሪየው የክህደት ሰለባ ቴዎድሮስ ናቸው፡፡ ዮሐንስን ጨምሮ የወቅቱ መኳንንትና መሳፍንት ከዷቸውና ለእንግሊዝ ወራሪ ሰራዊት ብቻቸውን አጋፈጧቸው፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ራስዎ “ማስረጃ” ብለው ካያያዟቸው ደብዳቤዎች ውስጥ ካሳ ምራጭ (በኋላ ዮሐንስ) ከንጉሠ ነገሥቱ ፈቃድ ውጭ ከአውሮፓ ነገሥታት ጋር የተላላኳቸው የምሥጢር ደብዳቤዎች የክህደት ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ለጣሊያኖች ደብዳቤ መጻፍ ክህደት ከሆነ የመጀመሪያው የክህደት መምህር ማን እንደ ነበረ ከ“መጽሐፍዎ” መገንዘብ ይችላሉ። ቴዎድሮስንስ ማን አስገደላቸው? “ሓቅ”ማለት ይህን እውነት ሲደፍሩ ነው ወዳጄ!
“ድሮውንም አፄ ምኒሊክ ስለወደብ ሳያውቁ በድንቁርናቸው ትግራይ አደካምኩኝ ዘውዴንም አለመለምኩ ሲሉ ነው ለጣሊያን የሰጡት” (ገፅ 165) ሲሉ ስለ ወደብ የገለጹበት መንገድ ሊያስማማ ይችላል፡፡ የሚያስማማን ታዲያ ምኒሊክ ስለ ወደብ አለማወቃቸው “ደንቆሮ” ስለሆኑ ነው ባሉት ብቻ ነው፡፡ የዛሬዎቹ መሪዎቻችንስ “ወደብ አንፈልግም የአሰብ ጉዳይም የተዘጋ ፋይል ነው” የሚሉን በምን ምክንያት  ይሆን? ዕውቀት ወይስ ድንቁርና?
ለማጠቃለል ያህል “መጽሐፉ” በሩጫና በይድረስ ይድረስ የተጻፈ መሆኑን ከቋንቋው፣ ከመዋቅር እና ከማስረጃ አጠቃቀስ ድክመቱ መረዳት ይቻላል፡፡ በጥድፊያ እንዲጻፍ ሰበብ የሆነውም የ1997 ዓ.ም ምርጫን ተከትሎ የግል ጋዜጦች ይጽፉት የነበረው አስተያየትና ዜና ሁሉ በምኒልክ ደጋፊዎችና በሸዋዎች  እንደ ተፈጸመ በማመንዎ ይመስላል፡፡ ለዚህም ነው ተጀምሮ እስከሚያልቅ ድረስ ምኒልክንና ሸዋን በከሃዲነት በመፈረጅ በማውገዝና እውነቱን በማውገርገር የሚጠቃለለው፡፡
በመሠረቱ ይህ ታላቅ ድፍረት ብቻ ሳይሆን ወንጀልም ነው፡፡ ዛሬ ዓለም በሉላዊነት (ግሎባላይዜሽን) ወደ አንድ መንደር እየተቀየረች ባለችበት ዘመን፣ አውሮፓን የሚያህል ታላቅ አህጉር ወደ አንድ አገርነት እየተቀየረ ባለበት ጊዜ፣ አፍሪካን አንድ አገር ለማድረግ ወይም በህብረት ለማጣመር ከፍተኛ ትግል በሚደረግበት አገር ላይ ሆነን፣ እነ ማንዴላን የመሰሉ የይቅርታ እና ሰላም አባቶችን አሰልጥነን ለፍሬ ያበቃን ዜጐች፤ ያለቀ፣ የደቀቀ ነገር እየጐተቱ ህዝብን በዘረኝነት መርዝ ለመበከል የሚደረገው የቀን ከሌት ሩጫ ሁሉ ከንቱ የዋህነት ስለሆነ በተለይ “ደራሲ ነኝ፤ ጋዜጠኛ ነኝ፤ ወዘተ” የምንል ሁሉ ነገ ተጠያቂነት እንዳለብን መገንዘብ ይኖርብናል። በአጠቃላይ “መጽሐፉ” በቋንቋም ሆነ በይዘቱ እጅግ ደካማ በመሆኑ ባይታተም ኖሮ  በተለይ ለጸሐፊው የተሻለ ጥቅም ያስገኝ እንደነበር መግለፅ እፈልጋለሁ፡፡    

Published in ህብረተሰብ
Sunday, 05 January 2014 00:00

ፅርሀ አርያማዊ የገና ዛፍ

         ደራሲ ነኝ፡፡ ይህ ታሪክ ከእኔው ምናብ የፈለቀ ይመስለኛል፡፡ ይመስለኛል ብልም እኔው እንደፈጠርኩት በእርግጠኝነት አውቃለሁ፡፡ ምናልባትም በሆነ ስፍራ ፣ ወቅት በገሃዱ ዓለም የተከሰተ ሊሆን ይችላል፡፡ ያውም በገና ዋዜማ …በአንድ ሞቅ ደመቅ ባለ ከተማ፡፡ ውርጩ እና ቁሩ በበረቱበት ወቅት፡፡…በእዝነ ሕሊናዬ አንድ ልጅ ይታየኛል፡፡ 6 ዓመት ያልበለጠው ብላቴና፡፡ እንደ በረዶ ከቀዘቀዘ የምድር ስር ቤት በማለዳ ከእንቅልፉ ነቃ፡፡ ብን ብላ የሳሳች ጨርቅ ቢጤ ትከሻው ላይ ጣል ቢያደርግም ብርዱ እያንዘፈዘፈው ነው፡፡ በዚያ ላይ ርሀብ እየሞረሞረው፡፡ የሳሳ ፍራሽ ላይ ከተኛችው በሽተኛ እናቱ ዘንድ መለስ ቀለስ አለ…ግን እናቱ እንዴት? ከየት? እዚህ መጣች፡፡ ከሌላ ቦታ መጥታ ድንገተኛ በሽታ ጥሏት ይሆን፡፡
አብዛኛዎቹ ተከራዮች ከበዓሉ ቀደም ብለው ቤቱን ለቀዋል፡፡ ቤቱ ውስጥ የቀሩት ለ2 ሰዓት ቀምቅሞ አቅሉን ስቶ የተዘረረ ሰካራም ሰውዬ እና አንዲት የጨረጨሱ አሮጊት፡፡ እኚህ የ80 ዓመት አሮጊት ቀድሞ ሞግዚት ነበሩ….ልጅ ጠባቂ…አሁን ግን ከሞት ሌላ የሚጠብቁት ምንም የለም…ያውም ያለ አስታዋሽ፡፡ በቁርጥማት በሽታ በፅኑ እያቃሰቱ ነው፡፡ ልጁ ላይ እያልጎመጎሙ በጥልቅ ጥላቻ አፍጥጠውበታል፡፡
ጨለማው እየበረታ ነው፡፡ ፍርሃት ህይወት ዘርግቶ ውስጡ ተላወሰ፡፡ በሽተኛ እናቱን ልቀስቅሳት አልቀስቅሳት በሚል ወላወለ፡፡ ከቆይታ በኋላ የእናቱን ፊት ሲነካ እንቅስቃሴ አልባ በድን የመሆኗ ነገር ገርሞት “እዚህ ይቀዘቅዛል” ሲል አሰበ፡፡ ሳያስበው እጆቹን የሟች እናቱ ትከሻ ላይ አሳረፈ፡፡
……ጣቶቹን እርስ በእርስ እየሰበቀ በትንፋሹ ሞቅ አድርጎ፣ ከዚያች የጨለማ ማኅፀን የምድር ስር አብራክ ወጣ፡፡ ወደ ጎዳናው አመራ፡፡ እንዴት ያለ የሞቀ የደመቀ ከተማ ነው! በፊት የነበረበት ከተማ ከመሸ በኋላ በጨለማ አዘቅት የሚዋጥ ነው፡፡ ደንገዝገዝ ሲል መንገድ ላይ ዝር የሚል ሰው የለም። ሁሉም ወደቤቱ ይገባል፡፡ ጎዳናው ሌሊቱን የውሾች ማላዘኛ ሆኖ ያርፈዋል፡፡ ቢሆንም እዚያ እንደዚህ አይበርድም፡፡ ሙቀት አለ፡፡ ምግብ አለ፡፡ እዚህ የሚላስ የሚቀመስ የለም፡፡ ትርምስና ግርግሩ ግን ሌላ ነው፡፡ ከአፉ የሚያኖረው የሚቀመስ ነገር ለማግኘት ተንሰፍስፏል፡፡ ጠኔ ሊጥለው ነው፡፡ በማለፍ ላይ የነበረ ፖሊስ መኮንን፣ ልጁን ላለማየት ፊቱን አዞረ፡፡
ወደ ሌላ ሰፊ ማራኪ ጎዳና አቀና፡፡ ሰው ሁሉ ይጯጯኃል፡፡ በዚያ ላይ ግርግሩ….በብርሃን የተሽቆጠቆጠ፡፡ በአንድ ሰፊ የመስታወት መስኮት፣ጣሪያ ሊነካ የደረሰ ድምቅ ያለ የገና ዛፍ ይታያል፡፡ ሙሉ በሙሉ በመብራት፣በወርቃማ ወረቀቶች፣በአሻንጉሊቶች ያሸበረቀ…..የገና ዛፍ። ፍፁም ፅዱ የሆኑ ልጆች ክፍሉ ውስጥ ላይ እታች ይራወጣሉ …… እየተሳሳቁ እየፈነደቁ….. እየበሉ እየጠጡ፡፡ አንዲት ትንሽዬ ውብ ልጅ ከአንዱ ጋር መደነስ ጀመረች፡፡ እንዴት የምታምር ውብ ልጅ ናት፡፡ ሙዚቃው ውጪ ድረስ ያስተጋባል፡፡ የእጅና የእግር ጣቶቹ በቆፈኑ ተቆራምደው ፅኑ ስቃይ ውስጥ ቢሆንም በተመለከተው ነገር በመደነቅ ከት ብሎ ይስቃል፡፡
የጣቶቹ ህመም በረታበትና ማልቀስ ጀመረ፣እንደ መሮጥም አለ…. ደግሞ ከሌላ የመስታወት መስኮት የገና ዛፍ ተመለከተ፡፡ ጠረጴዛው ላይ የኬክ አይነት በገፍ ተደርድሯል፡፡ ሶስት ሴቶችም ተቀምጠዋል፡፡ ለሚገባው ሁሉ ኬክ እያነሱ ይሰጣሉ፡፡ ልጁም በቀስታ ወደ በሩ ተጠጋ፡፡ በሩን ከፍቶ ሰተት ብሎ ወደ ውስጥ ዘለቀ፡፡ ውስጥ የነበሩት አንድ ላይ አምባረቁበት፣ አዋከቡት፡፡ አንዷ ወደ እሱ መጥታ ሳንቲም እጁ ላይ አኖረችና እንዲወጣ በሩን ከፈተችለት፡፡ እንዴት በፍርሃት እርዶ ነበር፡፡ የገነተሩ ቀይ ጣቶቹ በቅጡ ሳንቲሙን በቅጡ መጨበጥ ስላልቻሉ ወደቁበት፡፡ ወዴት እንደሚሄድ ባያውቅም ከዚያ ቦታ በፍጥነት ሸሸ፡፡
….አልቅስ አልቅስ ብሎታል፡፡ ደግሞም ፍርቷል። እናም እሮጠ…እሮጠ…የባይተዋርነት፣ የብቸኝነት ስሜት ተሰማውና በሀዘን ተዋጠ፡፡
ደግሞ ሌላ ባለ መስታወት መስኮት ውስጥ ሶስት አሻንጉሊቶች ተደርድረዋል፡፡ ቀይና አረንጓዴ የለበሱ፡፡ ሽማግሌው ትልቅ ቫዮሊን ይዞ ይጫወታል። ሁለቱ ደግሞ እራሳቸውን ነቅነቅ …ነቅነቅ…. እያደረጉ ከንፈራቸውን እያንቀሳቀሱ የሚያወሩ ይመስላሉ። ልጁ አሻንጉሊቶቹ ህይወት ያላቸው ፍጡራን መስለውት ነበር፡፡ ቆየት ብሎ ግዑዝ አሻንጉሊቶች መሆናቸውን ሲረዳ፣ ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም…ከት ብሎ ሳቀ፡፡ እንዲህ አይነት አሻንጉሊቶች ይኖራሉ ብሎ አላሰበም፡፡
በድንገት አልቅስ አልቅስ አለው፡፡ አሻንጉሊቶቹ የፈጠሩበት ግርምት ግን አለቀቀውም፡፡ የሆነ ሰው ከኋላው ሲጎነትለው ተሰማው፡፡ አንድ እርኩስ ልጅ ነበር፡፡ በኩርኩም ብሎት ኮፍያውን ላፍ አድርጎ ገፈተረው፡፡ ልጁ ከመሬት ላይ ተዘረረ፡፡ ግርግር ሆነ፡፡ ዙሪያውን ሰዎች ከበቡት፡፡ ልጁ በፍርሀት ተብረከረከ። ከወደቀበት ተነስቶ እብስ አለ፡፡  የት እንደደረሰ ሳያውቀው አንድ ግቢ ጓሮ ገብቶ ከእንጨት ክምር ጀርባ ተደበቀ፡፡ “እዚህ በፍፁም ማንም አያገኘኝም፤ ደግሞ ጨለማ ነው”….
ኩርምት ብሎ ቁጢጥ አለ፡፡ በተፀናወተው ፍርሐት ትንፋሹ እየተቆራረጠ ከመቅፅበት የደስተኝነት ስሜት በውስጡ ናኘ፡፡ የእግርና የእጁ ህመም ለቀቀው፡፡ ፍፁም ፈውስ በውስጡ እንደ ጠል ፈሰሰ፡፡ ምድጃ ዳር እሳት እንደሚሞቅ ሰውነቱ ዘና አለ፡፡
በመሀል ብንን አለ….ተኝቶ ነበር ማለት ነው፡፡ “እዚህ መተኛት እንዴት አስደሳች ነው…ትንሽ ቆይቼ እንደገና አሻንጉሊቶቹን ሄጄ አያቸዋለሁ፡፡” ብሎ በውስጡ አብሰለሰለ እናም ስለ አሻንጉሊቶቹ አስቦ ሳቅ አለ፡፡ “ልክ የእውነት እኮ ነው የሚመስሉት”፡፡ ….እናቱ ከላይ ሆና ስታንጎራጉር ሰማት፡፡
“እማዬ ተኝቻለሁ፤ እዚህ ማንቀላፋት እንዴት ደስ ይላል”
“ና ወደ ገና ዛፌ …ማሙዬ” በርህራሔ የተነከረ ለስለስ ያለ ድምፅ አንሾካሾከበት፡፡ የእናቱ መስሎት ነበር፡፡ ግን አይደለም፡፡ ሊያየው አልቻለም፡፡ የሆነ ሰው ከጨለማው አብራክ ወጥቶ በርከክ ብሎ እቅፍ አደረገው፡፡ እሱም በደስታ ሲቃ እጁን ዘረጋለት…ሁሉም ነገር ከመቅፅበት ብርሀን በብርሃን ሆነ….አስደናቂ የገና ዛፍ፡፡ ብሩህ አንፀባራቂ ምትሀታዊ የገና ዛፍ…. የተለመደው የፅድ ዛፍ አልነበረም፡፡ እንዲህ ያለ የገና ዛፍ ፈፅሞ አይቶ አያውቅም፡፡ የት ነው ያለው? ምትሀታዊ የገና ዛፍ በአሻንጉሊቶቹ ተሽቆጥቁጦ…. የለም የለም አሻንጉሊቶች አይደሉም….አንፀባራቂ የሚያማምሩ ትናንሽ ልጆች ናቸው፡፡ እንደ መላዕክት እየበረሩ መጥተው በልጁ ዙሪያ ሾሩ፡፡ ሁሉም ሳሙት። ተሸክመው ይዘውት ነጎዱ፡፡ እርሱም እየበረረ ነበር፡፡
እርሱን እያየች በመሳቅ ላይ የነበረችው እናቱን አያትና “እማምዬ እንዴት ደስ ይላል እዚህ” …ልጆቹን በየተራ ሳመና ….በሱቁ መስኮት ስላያቸው አሻንጉሊቶች ሊነግራቸው አሰበ፡፡ “እነ ማሙሽ…እነ ሚሚ እነማን ናችሁ?” ግርም ብሎት ጠየቀ፡፡
“ይህ የክርስቶስ የገና ዛፍ ነው” ሲሉ መለሱለት፡፡ …. “ክርስቶስ በዛሬው እለት የገና ዛፍ ያዘጋጃል…የገና ዛፍ ለሌላቸው ምስኪን ልጆች…”
እነዚያ ሁሉ ልጆች ልክ የእርሱ ቢጤ ምንዱባን መሆናቸውን አወቀ…የግፍ ብካይ ሰለባዎች፡፡ አንዳንዶቹ በጨቅላነታቸው በቅርጫ ተደርገው ከሀብታሞቹ የፒተርስበርግ ነዋሪዎች ቤት ደጃፍ ተጥለው በረዶ ሆነው የቀሩ …በየማሳደሪያው በጭስ ታፍነው የሞቱ ወላጅ አልባ ህፃናት…አንዳንዶቹም ጠኔ ከያዛት እናታቸው ጡት ላይ የሞቱ…ሌሎቹም በተግማማው በሚቀረናው ሶስተኛ ማዕረግ ባቡር ውስጥ ታጅለው ታፍነው የሞቱ…እነሆ አሁን ግን ሁሉም እዚህ ናቸው፡፡ ኢየሱስን የከበቡ መላዕክት መስለው፡፡ ክርስቶስ መሀላቸው ሆኖ እጆቹን ዘርግቶላቸዋል፡፡ እጆቹን ከፍ አድርጎ ሀጥያተኛ እናቶቻቸውን ይቅር አላቸው፡፡ ባረካቸውም፡፡ የህፃናቱ እናቶች በአንድ በኩል ቆመዋል….እንባቸው ኩልል ብሎ እየፈሰሰ፡፡ ልጆቻቸውም ለይተው አውቀዋቸዋል፡፡ ህፃናቱም ወደእየ እናቶቻቸው በመሄድ ሳሟቸው፡፡ በሚጢጢዬ ፀአዳ እጆቻቸው የእናቶቻቸውን እንባ አበሱ፡፡ ዛሬ የሀሴት ቀን በመሆኑ እንዳያለቅሱ ተማፀኗቸው፡፡
ማለዳ የቤቱ ዘበኛ፤ እንደበረዶ የተጋገረውን የህፃኑን አስክሬን ከእንጨት ክምሩ ጋ አገኘው፡፡ እናቱ ከልጇ ቀደም ብላ ነበር የሞተችው…በሰማይ ግን በጌታ ፊት ተገናኙ፡፡
በምድር ቤቱ እና ከእንጨቱ ክምር ስር የሆነው በገሀዱ አለም ተከስቶ ሊሆን ይችላል…. የክርስቶስ የገና ዛፍ ተከስቶ ይሆናል ወይም አይሆንም የሚለውን ግን ለማወቅ አልችልም፡፡

Published in ልብ-ወለድ

በእናቱ ኢትዮጵያዊ፣ በአባቱ ሆላንዳዊ በሆነው ዳንኤል ጁፕሁክ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “አመፀኛው ክልስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ ደራሲው በ12 ዓመት የእስር ቤት ቆይታው ያሳለፈውን ህይወት ከወህኒ ቤት ከወጣ በኋላ በደች ቋንቋ እንደፃፈው፣ ከዚያም ወደ አማርኛ በመተርጎም እንዳሳተመው ታውቋል፡፡
በአማርኛ ቋንቋ የተተረጐመው መጽሐፍ፤ በአገር ውስጥ በ70 ብር እየተሸጠ ሲሆን በደች ቋንቋ የተዘጋጀው ደግሞ በደቡብ አፍሪካና በአውሮፓ በመሸጥ ላይ እንደሆነ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡

አንዳንድ ተረቶች በሂደት የዕውነታ ትንቢት ይሆናሉ፡፡ ቻይናዎች ዛሬ የደረሱበት ሁኔታ በሚከተለው ተረታቸው ላይ የተመሠረተ ሳይሆን አልቀረም፡፡
እነሆ፡-  
አንድ የቻይና ሊቅ-አዋቂ፣ አንድ ቀን በተከሰተለት ራዕይ ላይ ተመሥርቶ እንዲህ የሚል ሀሳብ ለህ/ሰቡ ያቀርባል፡-  
“ጐበዝ በመጪው ዘመን የሚመጣው ውሃ የተበከለ ነው የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ካሁኑ በእጃችሁ ያለውን ንፁህ ውሃ ብታከማቹ ደግ ነው፡፡ መጪው ውሃ ከቶም ጥራት ያለው ስለማይሆን በጊዜ ውሃችሁን አጠራቅሙ፡፡”
ይህን በየቦታው እየዞረ መስበኩን ቀጠለ፡፡
ከፊሉ፤
“አጭበርባሪ ነው፡፡ አዋቂ ነኝ በማለት አዲስ ነገር ለማስመሰል የቆመ ነው፡፡”
ግማሹ፤
“ጊዜው እያለፈ ሲሄድ ፈላስፋ ነን የሚሉ መምጣታቸው አይቀሬ ነው፤ ተውት አትስሙት” የሚል እሳቤ አቀረበ፡፡
አዋቂው ግን፤
“ግዴላችሁም እኔ እምላችሁን ስሙ፡፡ ስለ ውሃ የወደፊት ሁናቴ የሚጠቅማችሁ ይሄ እኔ የምላችሁ ነገር ነው” ማለቱን ቀጠሉ፡፡
ሰው ሁሉ አዋቂውን ናቀ፡፡ ዘለፈ፡፡
ስለሆነም፤ አሮጌውን ውሃ ትቶ አዲስ ውሃ መጠጣት ፈቀደ፡፡ ጠጣ ጠጣና ሰው ሁሉ አበደ!
ከማ/ሰቡ መካከል አንድ ሰው ግን፤ አዋቂው ያለውን ተቀብሎ ውሃ ማጠራቀም ጀመረ፡፡ ሆኖም፤ የሰው ሁሉ መሳቂያ መሳለቂያ ሆነ፡፡ “ዕብድ ነው!” ተባለ፡፡ ይብስ ብሎ ተቃዋሚ አፈራ፡፡ ተቃዋሚው በዛ በዛና አገሩ ሁሉ ተቃዋሚው ሆነ፡፡ በዚህም ምክንያት ሰው ሁሉ፤
“ይሄ ሰው ጤና ቢጐለው ነው እንጂ የዱሮ ውሃ አያጠራቅምም ነበር፤ እያለ ክፉኛ ወሬውን ነዛው”
ሰውዬው፤ ከነጭራሹ በህብረተሰቡ ተተፋ፡፡ ንክ ነው፣ ዕብድ ነው ተባለ! የሚጠጋውም ሆነ የሚያወራው ወዳጅ በማጣቱ ይጨነቅ፣ ይጠበብ ጀመር፡፡ ያበደ አገር፤ እሱን ዕብድ ነው እያለ አገለለው!
ስለዚህ ዋለ አደረና ተስፋ ሲቆርጥ ያጠራቀመውን ውሃ ሁሉ ደፋው፡፡ ከዚያም እንደሰው አዲሱን ውሃ መጠጣት ጀመረ፡፡ ይሄኔ አገሬው፤ “ይሄ ዕብድ ጤናው ተመለሰ፡፡ ደህና ሰው ሆነ!” እያለ እያወደሰው፣ ቀርቦ ያጫውተው ጀመር፡፡ ያ ዕብድ የተባለ ሰው ከአገር ተደባለቀ፡፡ ከዕድር ተዋሃደ፡፡ ካበደው አበደ፡፡ ነባሩን ጽዱ ውሃ ያጠራቀመ ሰው በአገሩ ባለመኖሩ፤ ሰው ሁሉ የተመረዘው፣ አዲስ ውሃ ሰለባ ሆነ!!
*    *    *
ከመንገደኝነት አስተሳሰብ ካልወጣን ንፁህ ውሃ አንጠጣም፡፡ በአንድ አሸንዳ የመፍሰስ አባዜ ለለውጥ አያዘጋጅም፡፡ የተለየ አስተሳሰብ ያላቸውን ወገኖች እህ ብለን ካላዳመጥን ለውጥ አናመጣም። ምክንያቱም፤ አንቻቻልምና ሰላም አይኖረንም፡፡ አንተራረምምና ከስህተት ክብ ቀለበት ለመውጣት አይቻለንም፡፡
ሀገራችን፤ ሁለመናቸው ዓይን ብቻ የሆኑ (እለ ኩለንታሆሙ መሉዐነ ዓእይንት እንዲል ግዕዙ) ሰዎች የሚያስፈልጓት ሰዓት ላይ ናት፡፡ ደራሲ ብርሃኑ ድንቄ በ “አልቦ ዘመድ” እንደገለፁት፤ “የኢትዮጵያን ታሪካዊ ባህል አስፋፍቶ ለማሳደግና መሠረቱንም ለማጠንከር የደከሙት፤ “እብነ ማዕዘንት” የሚባሉት አባቶች ሁሉ አልቀው፤ ዛሬ ኮረቶቹና ጠጠሮቹ መሠረት ነን እያሉ ሲፎክሩ መስማት ‘ትራጀዲ’ ብቻ አይባልም፡፡ ‘ኮሜዲም’ መሆን አለበት፡፡ ይህን ዝብርቅርቅ ሳስብ በማልቀስ ፈንታ አንዳንድ ጊዜ ያስቀኛል፡፡ ‘እንዳላለቅስ ብዬ በመፍራት ሁልጊዜ እስቃለሁ’ ብሎ የተናገረው ማነው?” ይሉናል። ጥቅሱ የፀሐፌ-ተውኔቱ የቦማርሼ ነው፡፡ አፍንጫችን ሥር ያለውንና የፊት የፊታችንን ብቻ ስንመለከት መሠረታችንን እንዳንስት በቅጡ ማስተዋል ይገባናል፡፡ መሠረቱ የላላ ህብረተሰብ የኋላ ኋላ፤ ራሱንም አጥቶ የሌላውንም መቀበል ሳይችል አየር ላይ ተንገዋሎ ይቀራል፡፡ ለጊዜው የሥልጣኔ የሚመስሉን፣ ከነስውር - ደባቸው ማንነታችንን ሊያጨነግፉ የሚባትቱ አያሌ መጤ የካፒታሊዝም ሳልባጅ አስተሳሰቦችን በጥንቃቄ ማየት አለብን፡፡ እነዚህን ትውልድ ሳንገነባ ልንታገላቸው አንችልም። የሚከተለው ቃል ትውልዳችንን ለማየት ይጠቅማልና እነሆ፡- “ያለፈውን ትውልድ የሚያደንቁበት፣ የዛሬውን ትውልድ የሚፈርዱበት ዋናው ምክንያት ምንድን ነው? …” ተብለው አንደኛው ገፀ - ባህሪ ይጠየቃሉ፡፡ ሌላው ሲመልስ -  
“በነዚህ ሁለት ቃላቶች ላይ የእኔን ምክንያቶች ተንጠልጥለው ያገኙዋቸዋል፡-
፩ መስዋዕትነት ፪ ራስን መውደድ፡፡ ያለፈው ትውልድ መስዋዕትነት ምን እንደሆነ ደህና አድርጎ ያውቃል፡፡ የዛሬው ትውልድ ደህና አድርጎ የተማረው ራስን መውደድ ነው!!” (አልቦ ዘመድ)
አንድ ትውልድ መስዋዕትን ሳያቅ ጥቅም እንደሚያገኝ ሲያስብ ሐሳቡ እንደጧት ጤዛ እየተነነ፣ የጨበጠው የመሰለውና ያዝኩት የሚለው ነገር ሁሉ እየበነነ፣ መንፈሰ - ባዶነት ስለሚያጠቃው፣ መቦዘን፣ መንገዋለልና የማናቸውም አዲስ ሀሳብ፣ አዲስ ግጭት ሰለባ የመሆን ዕድሉ ሰፊ ነው፡፡ ስለሆነም በብሔር-ብሔረሰቡም፣ በሃይማኖቱም፣ በፍልስፍናውም፣ በማህበራዊ ቀውሱም፣ እንዲያው ባገኘው ክስተት ውስጥ ሁሉ ጠብ-ያለሽ-በዳቦ ማለትን፣ ተንኳሽነትን፤ ሽፋጭነትን፣ ዘራፊነትን ያስተናግዳል። ሰከን፣ ጠንፈፍ ብሎ ስለማይቀመጥ ትግሉ ሁሉ ብትን ይሆናል፡፡ የመደራጀት፣ የመሰባሰብ የመወያየት፤ መላ ይጠፋበታል! ጊዜ ወስዶ የመብሰል ነገር ይሳነዋል፡፡ ኑሮ ያራውጠዋልና መንፈሱ እየባዘነ ያገኘውን ሁሉ ቀጨም የማድረግ ፈሊጥን ብቻ ያዘወትራል፡፡ የበለጠ ከሥሩ ይነቀላል። ንቀትን እንደዕውቀት ምንጭ ስለሚይዝ፤ ሁሉን ነገር በቅድመ-ፍርድ (bias) ወስኖ፤ አዕምሮውን ዘግቶ፣ ፋይሉን ወደ መዝገብ ቤት መልሶ፣ ስለሚቀመጥ የመለወጥ ዝግጁነት ከቶ ያጣል፡፡ ስለሆነም ከጥቅም ማጋበስ ውጪ የሚታየው ነገር አይኖርም፡፡ በአፉ ይራገማል፣ ድርጊቱን ግን ራሱ ሲፈፅመው ይታያል፡፡ የህ/ሰብ ዝቅጠት (degeneration) ምልክት ነው፡፡ የንቅዘት (decadence) መገለጫው ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ባሻገር ደግሞ የአንጎላችን ባዶነት ሳያንስ፣ በድህነታችን ጥልቀት ሳቢያ ሆዳችን ባዶ ሆኖ ሲጮህብን፣ ጉሮሮአችን ደርቆ ሲሰነጣጠቅብን ዓመት በዓል ሲመጣብን፣ ሌማታችን ባዶ ሲሆን፣ ህይወት የምሬት ሬት ወደመሆን ያመራና፤ ዕቅዱ፣ ራዕዩ፣ ስትራቴጂው፣ ታክቲኩ፣ ፖለቲኩ፣ ምርምሩ ሁሉ፤ ይቀርና ከልቡናችንም ይፋቅና፣ ይጠፋና፤ “ነገ ነዳጅ ሊወጣ ነው”፣ “ተቆፍሮ ወርቅ ሊፈልቅ ነው” ቢባል፣ “ከሚመጣው ዓመት ዶሮ፣ ዕንቁላል ዘንድሮ!” ማለት ብቻ ይሆናል ቋንቋችን! ለማንኛውም መልካም የገና (“ገ” ጠብቆም ላልቶም) በዓል ይሁንልን!!
እንኳን ለልደት በዓል አደረሳችሁ!

Published in ርዕሰ አንቀፅ

ባሎች ለሚሰቶቻቸው ሊሉት የማይገባቸው ነጥቦች ምንድናቸው? በእርግጥ ይህ ሁሉንም አስፈላጊ ነገር ያንትታል ባይባልም በመጠኑ ለጠቅላላ እውቀት ስለሚረዳ ለንባብ ብለነዋል፡፡ፀሐፊዋ ጂሊ ስሞክለር ትባላለች፡፡  
ጂሊ ስሞክለር እንደምትለው ከባለቤትዋ ጋር ከአስር አመት ላላነሰ ጊዜ አብራ ኖራለች፡፡
ነገር ግን ከዚህ ሁሉ አመታት በሁዋላም ባልዋ ባህርይዋን ስላልተረዳው እኔ ምን መስማት እንዳለብኝና እንደሌለብኝ ብነግረው ብነግረው ሊሰማኝ አልቻለም፡፡ የተከበርክ ባለቤቴ እባክህን እኔን በሚመለከት እነዚህን አስር ነጥቦች አትናገራቸው... አልወዳቸውም ብዬ በፍሪጅ ላይ በግድግዳ ላይ ሁሉ ቦታ ለጠፍኩዋቸው፡፡ ነገር ግን ትላለች ጂሊ... እሱ ምን በወጣው ዞር ብሎም አያያቸውም፡፡ ስለዚህ ሌሎች ሚስቶችም ልክ እንደእኔ ተበሳጭተው ሊሆን ስለሚችል ለንባብ ብያቸዋለሁ ብላለች፡፡ ሰዎች  በአለም ዙሪያ በብዙ ጎናቸው ይመሳሰላሉ፡፡ እናም  ትዳሩ ...ወልዶ ማሳደጉ ... ፍቅሩ...ጸቡ...ብቻ ብዙው ነገር ይመሳሰላል፡፡ምናልባትም የአንዱ ሀገር ህዝብ ከሌላው ጋር የሚለያይባቸው ነገሮች ቢኖሩም ሰው በመሆናቸው ብቻ የሚጋሩዋቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ ለዚህም ነው መረጃዎች ከአለም አለም በተመሳሳይ ድህረ ገጽ ለንባብ የሚቀርቡት፡፡
                                                 -------////-------
ባሎች ለሚስቶች ወይንም ለፍቅረኞች ሊናገሩዋቸው የማይገባቸው ነጥቦች...
1/ መታጠቢያ ቤት አጠቃቀም፣
እኔ ወደ መታጠቢያ ቤት ስሔድ ትክክል ልሁን ወይንም አልሁን ባለቤቴ ሊነግረኝ አይገባም፡፡
የመታጠቢያ ቤት ጉዞ ለግለሰቡ የግል ጉዳይ ተደርጎ መተው ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ ወደ መታጠቢያ ቤት  መሔድሽ ልክነው ወይንም ልክ አይደለም የሚለው አስተያየት በሌላው ሰው ወይንም በባል  ቢሰነዘር የተጠቃሚውን  ሞራል ሊነካ ይችላል፡፡ ይሄንን በሚመለከት በባልና በሚስት ብቻም ሳይሆን በማንኛውም ሰው ቢሆን አስተያየት ሊሰጥበት የማይገባ ነው ትላለች ፀሐፊዋ፡፡ ስለዚህ ባሎችም ሆኑ ሚስቶች በእንደዚህ ያለው የግል ጉዳይ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ ካልተጋበዙ በስተቀር ጣልቃ በመግባት አስተያየት ባይሰጡ ይመከራል ትላለች ጂሊ።
እንደዚህ ያለው ጉዳይ ለዚህ አገር ሰዎች ይሆናል አይሆንም የሚባል ሳይሆን ለሁሉም የሰው ልጅ የሚሆን አስተያየት ነው፡፡
2/ ምግብ፣
እኔ ቀኑን ሙሉ ለፍቼ የሰራሁትን... ቀኑን ሙሉ የደከምኩበትን ምግብ ባሌ እንዲበላ ሳቀርብለት ... የምግብ ጠረኑን ማሽተት...ወይንም አሁን ይሄ ምግብ ነው? ብሎ መተቸት እጅግ ያማር ራል፡፡ በእርግጥ ምግቡ የጎደለው ነገር ቢኖር በግልጽ መነጋገር ይቻል ይሆናል። ነገር ግን በደፈናው መተቸት አይገባም ትላች ጂሊ... አንዳንድ ጊዜ ወንዶች ለቤት ወጪ የሚሰጡት ገንዘብ ምግብን አጣፍጦ ለመስራት አይበቃ ይሆናል ብለው ቢገምቱ ምናልባት አስከፊውን ነገር ያስወግድ ይሆናል፡፡
-------////-------
“...ባለቤቴ ለእኔ የሚሰጠው የቤት ወጪ እና እሱ በኪሱ የሚያስቀረው ገንዘብ አኩል ነው፡፡ ለቤት ወጪ የሚሰጠው ገንዘብ አራት ልጆችን እሱንና እኔን ጨምሮ የተተመነ ነው፡፡ በሱ ኪስ የሚቀረው ግን ለእሱ ብቻ ነው። እሱ ቁርሱን እራቱን ምሳውን የሚበላው ከቤቱ ነው፡፡ በኪሱ የሚቀረው ገንዘብ ግን ለመጠጥ ብቻ የሚሆን ነው፡፡ ታድያ ሁልጊዜ የሚናገረው ነገር ምግቡ እንደማይጣፍጥ ነው፡፡ አንድ ሊትር ዘይት ለአስራአምስት ቀን ካልበቃ ምን ኑሮ ነው? ይላል በሌላ በኩል ደግሞ ወጡ ዘይት የለውም አይጣፍጥም ይላል፡፡ ግራ የገባ ነገር ነው...”
    ኢትዮጵያዊት ሴት የሰጠችው አስተያየት
3/ የልጆች መስተንግዶ፣
ጂሊ እንደምትገልጸው...እኔ እናታቸው ቀኑን ሙሉ አብሬአቸው ውዬ ነገር ግን አመሻሹ ላይ እሱ ሲመጣ ሶስት ሴኮንድ ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የእሱ አድናቂዎች እንዲሆኑ...እሱ እንደሚ ወዳቸው... አንዳንድ ቀለብ ወይንም ልብስ የማይሆኑ ነገሮችን ይዞ መጥቶ በማባበል... ወይንም በማታለል ከእኔ ጋር ጭቅጭቅ መፍጠር አይገባም፡፡ እኔ እናታቸው ምግባቸውን አብስዬ አቅርቤ ልብሳቸውን አጥቤ ትምህርት ቤት እንዲሄዱ አድርጌ… እነዚህንና የመሳሰሉትን መሰረታዊ ስራዎች ሰርቼ ስለማሳድጋቸው አባትየው የበለጠ ተወዳጅ ለመሆን የማያስፈልግ ጥረት ማድረግ አይገውባም፡፡ ነገር ግን አለች... ጂሊ ...በትክክለኛው መንገድ ከእናትየው ጋር በመተባበር ልጆችን ማስተናገድ ከአባትየው ይጠበቃል፡፡ እናትየው አባታቸውን እንዲጠሉ ወይንም አባትየው እናታቸ ውን እንዲጠሉ ማድረግ ትክክል አይደለም፡፡
4/ አጉዋገል ቀልዶች፣
አንዳንድ ጊዜ በስራ ቦታ የሚቀለዱ ደርቲ ጆክ የሚባሉ አጉዋጉል ቀልዶችን በቀጥታ ወደቤት ማምጣት እና ከሚስት ጋር ለመቀለድ መሞከር ደግ አይደለም፡፡  ለእንደዚህ ያለው ጨዋታ እነዚያኑ ጉዋደኞችህን ጥራቸው ብላለች ጂሊ ለባልዋ ...ይሄንን የሚያደምጡ ሁሉ ቀልዶቹ ምን አይነት እንደሆኑ መገመት አያቅታቸውም። እውነትም ከሚስት እና ከባል ጋር የሚቀለዱ ቀልዶችን መለየት ይገባል፡፡
5/ ቅያሬ ካልሲ ማጣት፣
ምነው ካልሲዎቼ በሙሉ ቆሸሹ? ይሄ ጥያቄ በጭራሽ ሊነሳ አይገባም፡፡ ምክንያቱም ባል ካልሲ እንኩዋን በማጠብ እራሱን አይረዳም እንዴ? ስትል ትጠይቃለች ጂሊ ስሞክለር፡፡  ካልሲውን ባጥብ... ባጥብ ...ሁልጊዜ ችግር መሆኑ አይቀርም፡፡ እኔ ከአቅሜ በላይ ስለሆነ ብትፈልግ አንዱን ካልሲ ከአንዱ አዛምደህ አድርግ ...አረ ብትፈልግ አታድርግ ብዬ መልስ ሰጠሁ፡፡ በዚህ ብቻም አላቆምኩም ትላለች ጂሊ፡፡ እንዲያውም ከዚያ በሁዋላ ወደካልሲ ፊቴን ማዞር ትቻለሁ፡፡ በገዛ እጁ በቅንነት ማገልገሌን እንድተው አድርጎኛል ትላለች፡፡
በእርግጥ ይህ ብዙ ወንዶችን አይመለከትም፡፡ በዛሬ ጊዜ ወንዶች ከዚህም ባለፈ ቤታቸውን ልጆቻቸውን ሲረዱ ስለሚታዩ ለሚስቶቻቸው እንዲህ ያለ ጥያቄ ያቀርባሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ከሆነም ይታረም ይላሉ ሚስቶች፡፡
6/ የሰውነትን ቅርጽ በሚመለከት ፣
ምነው በየቀኑ ትወፍሪያለሽ? ይህ ጥያቄ በጣም ነው የሚያበሳጨኝ፡፡ ምናልባት ወፍሬም ቢሆን እኔ እንዲነገረኝ አልፈልግም፡፡ ይልቁንም ይህ አይነት ቀለም ልብስ  አይስማማሽም ወይንም ይሄኛውን ለውጠሸ ልበሽ ብባል እወዳለሁ፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ስለውፍረቴ መስማት ያበሳጨኛል፡፡ እኔ ወድጄ ያደረግሁት ስላልሆነ ልወቀስበት አልፈልግም ትላለች ጂሊ፡፡  
7/ የሰውነት ጠረን፣
በስራ እና በተለያዩ ምክንያቶች ጊዜ አጥቼ ልብሴን ለሁለት ቀን ወይንም ከዚያ በላይ አልለወጥኩ ይሆናል። እንግዲህ ልብስ ካልተለወጠ ሰውነት ምን ምን ሊሸት እንደሚችል የታወቀ ነው፡፡ይህንን እኔም አላጣሁትም፡፡ ግን ጊዜ አጥቼ ወይንም ሳይመቸኝ ቀርቶ ነው፡፡
የተከበረው ባለቤቴ በፍቅር መንገድም ሳይሆን በማጥላላት ኡፍ… ምን ምን ትሸቺያለሽ? አትታጠቢም እንዴ ቢለኝ እና ቢያጥላላኝ በጣም ነው የሚከፋኝ። ቢታገሰኝ ግን እኔ እራሴ ጥሩውን ነገር ለማድረግ ጭንቅላቴ ዝግጁ ስለሚሆን አርመዋለሁ፡፡
8/ ኩርፊያ፣
አንተ የሚያስገርም ኩርፊያ እያኮረፍክ ጥሩ እንቅልፍ ትተኛለህ፡፡ እኔ ግን በአንተ ኩርፊያ ምክንያት ቁጭ ብዬ አድራለሁ፡፡ እስቲ ምን ይባላል? ኩርፊያን የሚያመጡ ነገሮችን ለማረም ምንም ዝግጁ አይደለህም፡፡ አመጋገብ አስተኛኘት የመሳሰሉት ነገሮች ላይ ግድ የለህም፡፡ ታዲያ እንደዚህ ያለውን ጥፋት ለማረም ካልቻልክ ምናለበት ወደዚያችው ወደምትችልህ እናትህ ብትሄድ ወይንም እሱዋን ወደ አንተ ብትጠራት የወለደ እንግዲህ እዳ አለበት አይደል? ትላለች ሚስት...
...በአገራችንም ይብላኝ ለወለደህ ያገባህስ ይፈታሀል ተብሎ የለ?
9/ ሙድ፣
አንተን ደስ ባለህ ወይንም ሙድህ በተስተካከለ ጊዜ የሚስትህን መደሰትና አለመደሰት ወይንም ሙድ ሳትገነዘብ ምንም ነገር አትጠይቅ፡፡ የስዋ ስሜት እስኪስተካከል ጠብቅ፡፡ አለበለዚያ እንደመጣልህ የምትገልጸው ወይንም ስሜትህን የምታሳይ ከሆነ ሚስትህ ልታስቀይምህ ትችላለች፡፡ ምክንያቱም አልተዘጋጀችበትማ...
10/ ልጆን ማዝናናት፣
ልጆችህን ከቤት ውጭ የማዝናናት ስራ እንዳለብህ አትዘንጋ... ወደሲኒማ ቤት ወይንም መታጠ ቢያ ቦታ፣ ስፖርት ቦታ፣ ዋና ቦታ ፣ከውጭ ምሳ መጋበዝ የመሳሰሉትን ከሚስትህ ጋር አብረህ ማድረግ አለብህ። ምናልባትም ሚስትህ በአንዳንድ ስራዎች እንኩዋን ብትያዝ መስተንግዶው እንዳይቋረጥባቸው ልጆችህን መንከባከብ ትልቁ ስራህ መሆኑን እንዳትረሳ፡፡

Published in ላንተና ላንቺ
Page 11 of 14