ዙምራ እና እኔ (የመጨረሻው ክፍል)

ከትንሿ የኤግዚቢሽን አዳራሽ ተቀምጨ ዙምራን ስጠብቅ ብዙ ጥያቄዎች በህሊናዬ ተመላልሰዋል፡፡ ዕውን በህጻንነቴ የአዋቂ አብራሄ - ህሊና /Enlightenment/ ነበረኝ ያለው ልጅ ከወሎ ጐጃም ጐንደር ሄዶ ማስተማር የፈለገው? ፈጣሪ አስመልክቶት ነውን ወይስ የአእምሮው ፍጥረት ነው አስተሳሰቡን የሰረፀበት? የሚለው ጥያቄ በአዕምሮዬ ግዘፍ - ነስቷል፡፡ ከአምስት አስተሳሰቦች /አስተምሮት/ በላይ እንዲሰፋ ይፈልጋል ወይስ አይፈልግም? መማር ለምን አልፈለገም? 6 ሚስቶች መፍታት ለምን አስፈለገው? የአካባቢው ህዝብ በጥላቻ ዓይን እንደሚያያቸው ካወቁ ለምን ግንኙነታቸውን ለማሻሻል አልፈለጉም? ከ8 በላይ ኮምፒዩተሮች አንድ ኤን ጂ ኦ የተሰጣቸው ካሉ፣ ከዓለም ጋር ያላቸው ግንኙነት ሊሰፋ መሆኑ ነው፡፡

ይህን እንዴት ያዩታል? … ወዘተ እያልኩ ከራሴ ጋር እጠያየቃለሁ… በመጨረሻ ዙምራ መጣ፡፡ ከገመትኩት በታች አጭር ነው፡፡ ቆፍጠን ያለ ነው፡፡ በልቤ በተለያየ አጋጣሚ ያወቅኋቸውን አዋቂዎችና ፈላስፋዎች፤ የሀይማኖት ፈጣሪዎች፣ በፈረንጂኛ Great Avatars የሚባሉትን ለምሳሌ:- እየሱስ ክርስቶስን፣ ቡድሃን፣ ዘሮስተርን እና ክሪሽናን ወዘተ ሌላው ቀርቶ፤ የአርሲ ፈረቀሳ መሪ የሆኑትን እሥር ቤት አግኝቻቸው የነበሩትን ቀኛዝማች ታየ መሸሻን ሳይቀር፤ ሃሣቤ ውስጥ አስገብቼ አውጠነጥናለሁ፡፡ አሁን የማየው የዙምራ ቁመት ከሁሉም ያጥራል፡፡ “እስቲ ስለልጅነትህ ንገረኝ?” አልኩት ሰላምታ ከተለዋወጥን በኋላ፡፡ በ64 ነው የጀመርኩት፡፡ በ4 ዓመት ዕድሜዬ ስለ ሰው ልጅ ማህበራዊ ኑሮ እንዳነሳሁ ከእኔ ቀድመው ያወቁት ይነግሩኛል፡፡ እናቴ ናት ዋናዋ፡፡ በልጅነቴ ያን ሁሉ ነገር ሳደርግ ለእኔ አትገልጥልኝም፡፡ “ሃሣቡ ከሰው ተለይቶ፣ ታሞ ነው” ትላለች፡፡ በየመድሀኒት ቤቱ ስትወስደኝ ነው የማውቀው፡፡ ግን አልዳንኩላትም፡፡

ከዚህ በ64 ዓ.ም እነሱን ሳገኝ ነው የረጋሁት፡፡ በ6 ወሩ ቆሞ ይሄድ ነበር ነው የምትለው፡፡ እኔ ቆሜ መሄዴን አውቃለሁ? አላውቅም፡፡ “ወደዚያ ሄደህ ያው የታወቁ ትላልቅ ሰዎች ማግኘትህን መቼም ታስታውሰዋለህ ብዬ ነው?” ሙሉውን ነው እማውቀው ሙሉውን! ተህጻንነቴ ጀምሮ ሃሣቡን ይዤው የምሄድ ስለሆነ አሁን የሚመራኝ ያው ሃሣብ ነው!፡፡ ተሃይማኖት አባቶች ቦታ እሄዳለሁ፡፡ ቤተክርስቲያንም መስኪድም … ሰው በተሰበሰበበት አደባባይ እሄዳለሁ … ሄጄ ግን ሁለት ሶስት አራት ጥያቄዎችን ነው የማነሳው፡፡ መቼም ተማያቸው እየተነሳሁ ነው ሰዎች ከሚሠሩዋቸው፣ ከሚናገሯቸው ….. ስላልተማርኩም ነው፤ ያስተማረኝ ባካባቢ የሚሠራው ህዝብ ነው፡፡ መጀመሪያ 4 ሀሣቦችን ነበር አንስቼ የነበረው፡፡ ኋላ ላይ ወደ 5 ሄደዋል። ይሄ በዙረት ነው፤ በ13 ዓመቴ፡፡ ውጪ በወጣሁ ጊዜ ግን አንድ ቦታ ላይ አንተ አንቺ ሲሉ አያለሁ። ሌላ ቦታ ላይ እርስዎ ሲሉ እሰማለሁ፡፡ አንቱታና አንተታ፤ አንድ ቦታ አንዱን ሽማግሌ ሰውዬ አንተ ሲሉ እሰማለሁ፤ እድሜ የማይመለከተውን ሰው ደግሞ አንቱ ሲሉ እሰማለሁ፡፡ አንቱታ ሥራው ምንድን ነው የሚል ጥያቄ አመጣሁ፡፡ ለክብር ነው ይሉኛል፤ ለክብርማ አይደለም፡፡ የላይና የታች ሰው መምረጥ የለበትም፡፡

ለክብር ቢሆን የመጀመሪያውን እድል እናትና አባት ይወስዱት ነበር፡፡ ከዚያም ቀጥሎ ዘመድ ይጋራው ነበር፡፡ ይሄ ከመነሻው ላይ ራሳችን በሰው ልጅ ላይ ልዩነት የፈጠርንበት ነው፡፡ ተሰባት ትውልድ በኋላ ባዕድ፣ ተሰባት ትውልድ በፊት ዘመድ፤ ብለን የፈጠርን ጊዜ፤ ለክብር ከሆነ ዘመድ ለምን ክብር አጣ? ነው ጥያቄዬ፡፡ “የራቀውን ባዕድ ሄደን አንተ ብንል ቀድሞ የጣልከኝን አሁን የት ታውቀኛለህ? የሚል ቁጣ ነው የሚያስነሳው፡፡ ዘመድ ዘንድ መጥተህ ደግሞ፤ አንቱ ብትል ያዝናል፡፡ እኔ ወንድምህ አደለሁ ወይ እንዴት አንተ ትለኛለህ ይልሃል፡፡” “እነዚያ ታላላቅ የተባሉት ሰዎች ካንተ ጋር ስለሃሳብህ ሲወያዩ የጨመሩት የለም፣ የቀነሱት የለም? የተለዩበት የለም?” “እነሱ ባይሰጡኝም እኔ እመልስላቸዋለሁ፡፡ የትኛው ነው ልኩ እላቸዋለሁ፡፡ ይህ ልክ ነው፤ “ግን ሰው አልሄደበትም የሚል ምላሽ ነው የሚሰጡኝ፡፡ አብሮ መሄድ አይቻልም፡፡ አንተ ግን ትክክክል ነህ” ነው እሚሉኝ፡፡ ስለዚህ ሁኔታውን ያዙት ብያቸው እሄዳለሁ … በ13 ዓመቴ ነው የሄድኩት … ዕብድ ነው ታሟል ተብሎ ነበር እሚባል በእናቴ በኩል፡፡ ከ4-13 ዓመት ተቤተሰቤ፣ ተዚያም ከህ/ሰቡ ጋር ነበርኩ፡፡” “በ13 ዓመቱ ኬት አመጣው ?ብለው ነዋ የማይሰሙት” አልኩ ለማስረገጥ፡፡ “ዕብድን ማን ያደምጣል? እሃይማኖት አባቶች ጋ ሄጃለሁ፡፡

ግን ብዙ ነገር አለ፤ መግለፅ የማልችለው እዚህ ውስጥ .. /በእስልምና በኩል ትንሽ ቅር የሚለኝ አለ/ በኦርቶዶክስ በኩል ግን በ13 ዓመቴ ነው እሚሉት እስከ 15 ዓመት ድረስ፡፡ ሁሉን ነገር ጨርሼ ተስፋ ቆርጨ፣ ጠይቄ አብቅቻለሁ፤ እሆነውን ሆኛለሁ። በኦርቶዶክስ በኩል ያገኘኋቸው ሊቅ አዋቂዎች ማን ይሄኮ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ነው የሚሉት እንዴት አመጣሽው? ከምን አገኘሽው አዕምሮው ባልፈቀደው ልጅ እንዴት መጣ? እና ሲያዩኝ ምግብ የለም፤ ምን የለም ዝም ብዬ ነው እምሄደው፡፡ ከሣምንት ከአሥራምስት ቀን ምግብ ባገኝ ነው ዝም ብዬ ነው እምሄደው፡፡ አሁንም እኔ የፈጣሪ ስዕል ነው ብዬ ነው እምሄደው … የእኔ ስዕል አይደለም። ያን ኩሉ ተቋቁሜ መሄድ አልችልም ነበር የእሱ ስዕል ባይሆን! ባንድ በኩል አሳዝናቸዋለሁ፡፡ ባንድ በኩል ደግሞ “እንዴት እቺ ልጅ በፈጣሪ ሥራ እንዴት ገብታ ትቸገራለች” ይላሉ፡፡ በእዝነት ነው እሚያዩት፡፡ በክብር ነው እሚያዩት! በጣም ይገርማቸዋል! በሙስሊሙ በኩል ግን ከነቢዩ መሃመድ ጋር ነው እሚያይዙትም፤ ብዙም አይደለም ፍላጐታቸው አንዳንዶች ኦርቶዶክሶች እንዲያውም “በሕዝብ ያላወረድነውን የመጽሃፍ ቃል ነውኮ እምትናገረው” ይላሉ /አንቺ ነው የሚሉኝ/ … እሷ ይዛ ያለችው፡፡ “የእናትህ ማ/ሰብ ግን በሽተኛ ነው ነው የሚልህ?” “ስሙንም ያወጡልኝ እነሱ ናቸው፡፡...እና…” “ደህና ቤ/ሰብ ነበር ግን ቤተሰብህ? ሀብት ነበረው?” “እናቴ ካባቴ ጋር ሳለv ሀብት ነበራት፡፡ በጊዜው ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡አባቴ በህጻንነቴ በ4 ዓመቴ ነው የሞተ፡፡

እስከ 13 ዓመቴ ድረስ እናቴ ጋ ነው የቆየሁ፡፡ ለእናቴ እኔ አራተኛ ልጅ ነኝ፡፡ ከበታችም ከበላዬም አሉ… ብቻዋን ነበረች እሷ ሀብት ቢኖርም!” “ወንድም እህት አለህ?” “እህት የለኝም ወንድሞች አሉ፡፡ እናቴ ሴት ልጅ አልወለደችም፡፡” “እነሱስ ስላንተ ምን ይላሉ?” “ታሁን በፊት ታሟል ይሉ የነበሩ፣ “ለካ አንተ አልታመምክም፤ የታመምነው እኛ ነን” የታመምን እኛ ነው! ሚሉ፡፡” “ወደ አውራምባ ታዲያ እንዴት መጣህ? ከዚህ እስቴ አደል የተመለስክ?” “እስቴ ላይ ተመለስኩ፡፡ እስቴ ሆኜ ወደ ትዳር ዓለም ገባሁ፡፡ በትዳር ዓለም እያለሁ እርሻ አርሼ፤ በጋ በጋ ላይ-ብቻዬን መኖር ስለማልችል፤ ሰው ፍለጋ እዞራለሁ፡፡ ለብዙ ዓመታት ከዞርኩ በኋላ እዚህ አካባቢ ሃሣቤን የሚያደምጥ ሰው ሳገኝ፣ በተደጋጋሚ መጥቼ ካስረዳሁ በኋላ እዚሁ መጥቼ ብቀመጥስ አልኩኝ፡፡” የተሻለ ህይወትም አገኛለሁ አልኩ” “ሚስትህንስ እንዴት አገባሀት ታዲያ!? አስተሳሰብህን ተቀብላህ ነው፤ ወይስ እንዲሁ መፈቃቀድ ነው?” “መጀመሪያ ገበሬ ስሆን አጋቡኝ፡፡ ባመቱ ምርቱ የደረሰ ጊዜ እኔ ያገኘሁትን ምርት በአካባቢ ላሉ ችግርተኞች ማካፈል፡፡ የእኔ ደስታዬ እሱ ነው፡፡ እሱን በማደርግ ጊዜ ሚስቴ መስጠቴን የማትፈልግ ሆነች፡፡ “አዬ ዕብድ ነው እያሉኝ ገብቼ! ዕብደቱ የእኔ ነው እያወኩ የገባሁት፤ ራሴ ነኝ እያለች እምቢ አለች፡፡ እሷን ተውሁና እኔ ወደዚህ ማህበረሰብ መምጣት ፈልግሁ፡፡ አሁን እዚሁ አድጋ የተወለደች ልጅ አገኘሁ፡፡

እያሉ ጥለውኝ ሄዱ፤ እነዚያ በዕብደቴ ጥለውኝ ሄዱ፡፡ እነሱ ሀብት ማካበት የሚፈልጉ ይመስለኛል። ምርት እስከሚመጣማ ደህና ነኝ፡፡ ምርቱን የምሰጥበት ጊዜ ነው እምንጣላ! እኔ ደግሞ ማካበት እምፈልገው ሰውን ነው፡፡ ለዕለት የምትለብሰውን ካገኘህ ሌላው ትርፍ ነው፡፡ እሚፈለገው ለጥቂቱ ነው፡፡” “ምን ይሉ ይሆን እነዚህ የፈታሃቸው ሴቶች?” “ዛሬ ላይ ነው?” “አዎ፡፡” “እንግዲህ አላገኘኋቸውም” “እኔ ባገኛቸው ጥሩ ነበር እጠይቃቸው ነበር?” “እኔም አላገኘኋቸው” “ለየት ያለ ባህሪ ነው እንግዲህ አኗኗራችሁ ነገሩ ማ/ሰቡ ባህሉ ለየት ያለ እንዲሆን አድርጐታል ይመስለኛል፡፡” “አዎ፡፡ እኔኮ በሰዎቹ አልፈርድም፡፡ እነሱ’ኮ አደሉም የገቡብኝ፡፡ እኔ ነኝ የተውኳቸው። እየተውኳቸው እሄዳለሁ፡፡ ተመልሼ መጥቼ ይሄ መሆን ነበረበት እላለሁ የምትለው፤ መሆን ያለበትማ አንተ እምትለው ነው፡፡ ግን እንዴት ይቻላል ነው” እሚሉኝ:: “ታዲያ ለምን ለማስፋፋት አልሞከርክም? ይሄ ነገር ከአውራምባ ለምን አልወጣም?” “ዕብድ ነው ተብያለሁ፡፡ ከ93 ወዲህኮ ነው መስፋፋት የጀመርነው፡፡ ተሰደን እኮ ነበር፡፡ የማህበሩ አባል በቁጥር የማይገኝ ነው፡፡ የማ/ሰቡ አባል የማህበሩ አባል ነው፡፡

እየበዛ ነው፡፡ የሃሣቡ ተካፋይ ነው ማ/ሰቡ፡፡” “ከአራቱ ሃሣቦች አምስተኛ ስድስተኛ ሰባተኛ እያልክ ለምን አልቀጠልክም ነው? አልመጣልህም?” “ሃሣቦቼ እንደሱ ሆኖ የተፈቀደልኝ ነው፤ እነሱኮ ብዙ ናቸው?” “ ሲመነዘሩ?” “አንደኛው የሴቶች እኩልነት ነው፡፡ ሴት በሴትነቷ እናት ናት፤ ወንድ በወንድነቱ አባት ነው፡፡ እኩል ናቸው፡፡ እሱ በቤቱ ገዢ ሆኖ አዛዥ ቢፈልግ እሚረግማት፣ ቢፈልግ እሚሰድባት፣ ቢፈልግ እሚደበድባት፣ ሲፈልግ ውጪልኝ ከቤቴ ብሎ አስወጥቷት እሚቀመጥ ለምን? ነው ጥያቄው፡፡ እናት በሌለችበት አባት የለም፡፡ አባት በሌለበት እናት የለችም፡፡ እኩል ናቸው ግን እሷን እንደሞግዚት ያደረግነው ለምንድነው?! በጉልበት ነው? አይደለም፡፡ አፈጣጠሩ እኩል ነው፡፡ ሌላው ህጻናቶችን በሚመለከት ነው ሥራ ሲሰጣቸው አያለሁ ያ ሥራ ሲጠፋባቸው ለምን አጠፋህ ለምን አበላሸህ? አርጩሜ ይከተላል፡፡ ለምን ይሆናል? ነው፡፡” “ከመግረፍ ይልቅ ታዲያ በምን መለወጥ ይቻላል? በነሱ አቅም ምን ይደረጋል?” “በአቅማቸው የሚሆን ነገር መስጠት፡፡ ከዚያም ምክር መስጠት ነው፡፡ እኛ ያልቻልነውን እነሱ አይችሉም፡፡ ተማርን ያልነው ዱላ ስናነሳ ምን ይዘው ያድጋሉ? እሱን ይዘው ነው ሚያድጉት፡፡ እና ለምን? ምን ዘርተን ምን ልናመርት እንፈልጋለን? ምርታችንን ከፍ እያደረግን ነው ከእኛ ይበልጥ እነሱ ይሸከማሉ ለምን ነው?” 3ኛው/ ባካባቢው የወደቁ አረጋውያን አሉ በእርጅና ጠንካራው ደካሞቹን እንዲያስተዳድራቸው፣ በልተው ጠጥተው አርፈው እንዲኖሩ ነው፡፡ እንደኛው ሰው ናቸው እኛ ትተናቸው ከሄድን ማን አላቸው፡፡

ለሰው ደራሹ ሰው ነው፡፡ እኛም አንድ ቀን እንወድቃለን፡፡ የሚረዳን የሚያስጠጋን እንፈልጋለን? እኛ እንደምንፈልገው ሁሉ እነሱም ያስፈልጋቸዋል፡፡ 4ኛው/ ሰውን ሰው ሲዋሸው፣ ሲሰርቀው፣ ሲዘርፈው፣ ሲደበድበው ይታያል፡፡ ለምን? ለራሳችን ሊደረግብን የማይገባ ነገር ለምን በሰው ልጆች ላይ እናደርጋለን ነው፡፡ ከሌሎች እንስሳት የተለየ ከሌለን ለሰውነታችን ምን መኖር አተረፍን? እሄን ባልኩ ሰው እንደሚያስበው አታስብም ይሉኛል የማይወጣ ጥጃ ከማሠሪያው ይታወቃል። ዕውነት አይደለም ወይ? “ዕውነትማ ዕውነታ ነው፤ ግን መሸከም አይቻልም” ይላሉ፡፡ 5ኛ/ ሌላው ቅድም ያልኩህ ነው የአንቱታና ያንተታ ጉዳይ፡፡ ትልቁ ሀብት ሰው መሆን አለበት ሌላው ሁለተኛ ነው፡፡ ሌላው ጠብ እስከናካቴው ተምድረ-ገጽ መወገድ አለበት፡፡ ሰላምን መስርተን ገነትን ፈጥረን መሄድ አለብን፡፡ ጠብ እንዴት ይኖራል? ትላለህ ነው ጥያቄው፡፡ ጠብን የምንሠራው እኛ ነን ከዚያ ይልቅ ፍቅርን ብንሠራ!” “ግን ተገንብቷል? ማህበረሰቦች የተገነባ ሥርዓት አላቸው በዚያ ውስጥ ጠብም ተገንብቷል፡፡ አሁን ጠብ አይኑር ብትለው ማንም እሺ አይል ፡፡ውስጡ ተገንብቷልና ልጆች ግን እንደ አዲስ ማስተማር ከያዝክ ቀላል ነው እሚሆነው፡፡ ምክንያቱም ልጆች ናቸው ጠብ እንደማይኖርና እንዳይኖር አድርገው ያድጋሉ፡፡

ጥሩ አርገህ ከተንከባከብካቸው ያን ይዘው ያድጋሉ፡፡ ህ/ሰቡ አንዴ የያዘውን ይዞ ታንጿል፡፡ ስለዚህ ለመለወጥ ሳይከብድ አይቀርም። አሁን ለምሳሌ አንተ ሄደህ ከፈላስፎች ጋር አትነጋገርም፡፡ የነሱ ሃሣብ ላንተ ያንተም ለነሱ ሆኖ ምናልባት ልትለውጣቸውም ከቻልክ ለምን አትለውጣቸውም? እዚህ አውራአምባ ውስጥ ብቻ በመኖር ተከልሎ መቆየቱ፣ ብዙ እድሜ እዚሁ እንዲቀር አያረገውም ወይ? አላስፋፋኸውም ማለቴ ነው፡፡ ወደ ህ/ሰቡ ማስተማር ለማደግ…” እያልኩ አቋረጠኝና ትንሽ ቆጣ ብሎ “የተማርነውን ይዘን ከዚህ ብንገባስ የአገኘነውን ይዘን ብንገባስ? እኔ ብቻ ሳልሆን ከኔ ብቻ ሳትጠብቁ የአገኘነውን ይዘን ብንሄድ ቤታችን ብንገባስ?” “እኔኮ እዚህ ድረስ መጥቼ ነው ያገኘሁህ? አንተ ወደህብረተሰባችን አልመጣህም!” “የእኔ እግር ተጠብቆ ነው ታዲያ?! ዓለም እምትድነው የእኔ እግር ተጠብቆ አይደለም፡፡ በአንድ አካባቢ በአንድ ሰው አንድ ሃሣብ ሲመነጭ የግለሰቡ ድካም ብቻ መሆን የለበትም፡፡ ያገሪቱ ንብረት ነው መሆን ያለበት! ያገሪቱ ንብረት ይሁን ታልን ደሞ ምሁሮች ናችሁ መረከብ ያለባችሁ፡፡ “ምሁሮች እንዲረከቡ መማር አለባቸዋ ፍልስፍናህን?” አዎ ምሁሮች ናቸው መረከብ ያለባቸው ምሁሮች ቁጣው እየጋለ ነው፡፡ “አዎ ምሁሮች ናቸው፣ ወደዱም ጠሉም መረከብ ያለባቸው፡፡ እነማናቸው? የሃይማኖት አባቶችም ይሁኑ፣ የቀለም ምሁሮች መረከብ አለባቸው! ተረክበው ወደ ሀገሪቱ እንዲሰርጥ ማድረግ የምሁሮች ፋንታ ነው! እንደመነጨህ አገሪቱን እየሄድክ አልብስ እሚሉት ፈሊጥ ነው ችግሩ! ከተገኘ አባይን አሁን በአገሪቱ እንውሰደው ብንል ማንም መውሰድ አይችልም፡፡ በራሱ መሄድ አይችልም፡፡ ቅብብሎሽ ካረግነው ግን ይቻላል፡፡ ምሁሮቹ ደሞ ጥሪውን አግኝተው ወደ ህዝብ የማያሰርጡ ከሆነ ያገኙትን ዕውቀት ያገራቸው ሀብት ለራሳቸው ብቻ ለምን ይሆናል ነው፡፡

ሀብት ጥሪት ሳይያዝ ምሁርነታቸው ምንድነው ነው? ተጠያቂ ናቸው! አይደለም በሉኝ አስረዱኝ ምሁርነታቸው ምንድነው? ስተት ነው በሉኝ ተምኑ ላይ? እኔም መማር አለብኝ፡፡ ነው ካልነ ለማን እንተወው ?መቼ ላደርሰው ነው ለህ/ሰቡ ማለት አለባቸው… አሁን ደርሷል በቴሌቪዥን፣ በራዲዮ፣ በመጽሔት፣ በጋዜጣ፣ በኢንተርኔት… ዓለምንም ሞልቷል፡፡ ንብረታችን ነው እንውሰደው። አለበለዚያ አንተ እየሄድክ እየተንቆረቆርክ አድርስ ከሆነ እምትሉ እኔ ቀጠልኩ፤ ስንፈት ወይም ቂመት ወይም ቅጥፈት ወይም ሽንፈት ነው ብዬ ነው እማስበው ሽንፈት ነው!!” በጣም ተቆጣ አሁን፡፡ “አሁን ሰዎች ተቀበሉት በኢንተርኔት እንበል። የራሳቸውን ጨመሩበት እንበል አንተ እሥሩ ከሌለህ፤ ኦርጅናሌው ሰው ከሌለህ፣ ነገ እየተዛባ ቢሄድ ማንም ሊከላከለው አይችልም፡፡ ስለዚህ፤ ወይ አንተ የማሳወቂያ መንገድ መፍጠር አለብህ ማለት ነው፡፡ እኔ ሳስበው ግን አንተ መጣጣር አለብህ። ሁልጊዜ እምለው፤ ለምን አይሰፋም? ለምን አዲስ ሃሣብ አልመጣለትም? ለምን አልጨመረም ዙምራ? እላለሁ፡፡ ከሰማሁ ቆይቻለሁ፤ እንደው ዕድሉን ባገኝና ባገኘው ይሄን እለዋለሁ ስል ነበር።” “እንዳንተው ለመፈለግ ያልፈለገ ሁኖ ነው። እንዳንተው፡፡ ከሰማህ ጀምረህ አልመጣህል፡፡” “ያለሁበት አይፈቅድልኝም ነበር፡፡ ፈቃደኛ ሳልሆን ቀርቼ ሳይሆን ሁኔታው አልፈቀደልኝም ነው የምለው፡፡” ዙምራ እየተቆጣኝ እየገነፈለብኝ ነው አሁን፡፡ “ማነው ተጠያቂ እሺ?” “ካልመጣሁ አዎ ተጠያቂ ራሴ ነኝ፡፡ አንተ አትሆንም… ግን ፈቃደኛ ስላልሆንኩ አይደለም… አሁን ለምሣሌ አንተ አውሮፖ ሂድ ብልህ አቅም ላይኖርህ ይችላል.. ግን አውሮጳ አንድ ፈላስፋ ይኖራል ያንተ አይነት አስተሳሰብ ያለው፡፡

ይህን ሰውዬ ባገኝ ጥሩ ነበር የማለት ሃሣብ ካለህ ብቻ ነው በጐ ፈቃደኛ የምትባለው፡፡ ግን… እሱም ለራሱ ነው እኔም የራሴ ነኝ ከሆነ መደጋገፋችን ቀርቷል፡፡ አንዱን ዓላማ ስተነዋል ማለት ነው፡፡ እኔ እምለው አንተ የምታውቀውን ካላካፈልክ ይጐዳል ሰው ላገርህ ነውና ጥቅሙ፡፡ ስለዚህ ወዳንተ መምጣት የሚችለው ይምጣ፡፡ አንተም ደግሞ የምትችለውን መንገድ ፍጠር! ያንተ አስተሳሰብ ቢሰፋ ማ/ሰቡ ይጠቀማል እንጂ አይጐዳም፡፡ ጥሩ አስተሳሰብ አለበትና፡፡ ዋናው ግን ማድረግ መሞከር አለብህ ነው ምልህ!” “በእኔነቴ ስዞር ስዞር ብዙ ቆይቻለሁ፡፡ ወይም እሚሰማኝ ባገኝ ብዬ ወይ የሚጠይቀኝ ብዬ … “ልክ ነው” “አሁን አይደለም፡፡ ኢትÄጵያ አፍሪካ ብናንኳኳ አውቃለሁ የሚል ብቻ ነው ያለው! ‘አውቆ የተደበቀ ቢጠሩት ወይ አይልም’ ነው፡፡ “ልክ ነው” “ተሰማ በኋላ ግን ይህ ነገር ንብረት ነው ብለን ለንብረት መቆርቆር ያለብን ሁላችንም ነን፡፡ ተቆርቁሮ ያልበረረ ሰው ነገር ብትግተው አይዋጠውም፡፡ ዛሬ ብዙ ቀጣፊ አሳማኞች ያሉበት ጊዜ ነው! በየደጃፉ እየቆረቆርክ ይሄ ምንድን ነው ብትለው፤ ሊሰማህ አይሻም፡፡ ምነው ብትል አውቆ…. “አውቆ የተኛ ነው!” “ሊክ! ‘አውቆ የተኛ ቢቀሰቅሱት አይነቃ’ ነው፡፡ የሆኑ ፈረንጆች ገቡ፡፡ ሰላም አልኳቸው፡፡ “አሁን አውራምባ ታውቋል፡፡ እነዚህ ሁሉ እሚመጡት ኢንተርኔት አስተዋወቀን እያሉ ነው…” “እኔም ስሄድ ላስተዋውቅ እሞክራለሁ” “እየጣፍክ በየሼልፉ ብታስቀምጥም ገልጠህ ዕቃውን ካሳየህ ዋጋ የለውም… መውሰድ አለብህ። ወስደህለት ካልወሰደ አይወሰድም … ይሄ ዕንቁ ነው ሀብታችን ነው ካልነው ግን ወደፈለቀበት ወደ ምንጩ ይመጣል፡፡ ወደቦታው ስንመጣ ነው እውነት የሚሆነው፡፡ ኑሮ እኖራለሁ ብዬ ባሰብኩ ኑሮዬን በሰው ልጆች ላይ ባደረኩ ነበር፡፡ የለም። አይሆንም፡፡ እና የእኔ ሃሣብ ይሄ ነው፡፡ ሌላው በኢንተርኔት እየታወቀ ነው፡፡ ገለጻዬን መስጠት ነው፡፡

አንድ አውቶቢስ ሰው እዚህ ቢመጣ አሁን፤ ብዙ ገንዘብ ይቀበላቸዋል፡፡ ያን ከማድረግ ይልቅ፤ እኔን ወደዚያ ወስደውኝ ሃሣቤን ብሰጥ መልካም ይሆን ነበር!” “ትክክል ነው አሁን ተግባባን!” “እሱ ነው መሆን ያለበት፡፡ ምንጩ እስከሚታወቅ ድረስ የለፋሁትን ልፋት ብታስብ፣ ይሄ ደጅ እንዴት ይታለፋል ሲሉ፣ አልፌ ሄጃለሁ፡፡ የእኔ ስዕል ሳይሆን የፈጣሪ ስዕል ነው፡፡ እዚያ ድረስ ሄጃለሁ፡፡ አሁን ላይ ግን ተጣቧል፡፡ ከጠበበ በኋላ ዝም ብለን እምናይ ከሆነ ተኝተናል፡፡ ምሁሮች ራሳችንን እያታለልን ነው የምንኖረው፡፡ ባናታልል ጥሩ ነበር፡፡ እኔ አንድ ነገር የማስበው አለኝ፡፡ እኔ ገበሬ ነኝ፡፡ ያንድ ገበሬ ሃሣብ ነው፡፡ በታሪክ ስናይ እየሱስ ክርስቶስንም እንውሰድ ነብዩ መሃመድንም እንውሰድ፤ ብዙ መማርና ትምህርት መውሰድ የነበረባቸው ሰዎች ጥላቻቸውን ተከናንበው ተኝተው ነበር፡፡ በዚያን ጊዜ በነበራቸው ሰዓት ጠይቀው ተረድተው ቢኖር ኖሮ ይሄ ሁሉ መከፋፈል ባልነበረ! ከራሳቸው ከባለቤቶቹ አንደበት ሰምተው ቢሆን ኖሮ ይሄ ሁሉ መከፋፈል ባልነበረ እነሱን አርቀን አርቀን ከገፋናቸው በኋላ፤ ጊዜያቸውን ሳይጠቀሙበት ካለፉ በኋላ መጽሐፍ ተጽፎ በስማ በለው አይሆንም፡፡ ….ነገር ሁሉ እሚበላሸው እንደዚህ እየሆነ ነው፡፡ …. እንዲያው ከሰማሁት ታሪኩን ልንገርህ ብዬ ነው፡፡ እኔ በየኢትÄጵያ ይሄን ምንጭ ይዘን ቁጭ እንበል፣ እንኑር ከሆነ ራስን መተቸት ነው…” “ግን የመማር ዕድል አልነበረህም? ለምን አልተማርክም?” “እስካሁን የተማርኩትስ “ፊደል ቆጠራውን ማለቴ ነው… “እውነት ካልከኝማ አለመማሬ ይቆጨኛል አንዳንዴ! አንደዜ ደግሞ አይቆጨኝም፡፡ “አንደዜ እሚቆጨኝ ምንድነው? መጣፍ ማሠራጨት ጥሩ ነበር…” “ልክ ነው” “ለራሴ መጣፍ አልችልም፡፡

ማንበብ አልችልም። ስላልተማርኩ ማለት ነው፡፡ እንግሊዝኛ ሲናገሩ እኔ ደንቆር ነኝ፡፡ አውቅላቸው ነበር እሚፈልጉትን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ አይቆጨኝም። ለምን? አገራችን ምሁር አላጣችም፡፡ የት ነው የደረስነው ብዬ ሳስብ የትም አልደረስንም! አድቀናታል፡፡ ትልቅ ዳቦ ያማራቸው ሰዎች ሠርተው ያሳደጓት አገር ናት ኢትÄጵያ፡፡ እኔም ብማር ኖሮ አገሬን አደቃት ነበር እላለሁ፡፡” “ሌላ ጥያቄ አለህ?” “ጨርሻለሁ?” እኔ እምለው ነገር ነው እምለው ነው፡፡ ካልክ ምሁር ነህ ውሰደው፡፡ አይደለም ካልክ እምኑጋ እኔም ልማር!” “አመሰግናለሁ!” በልቤ አውራምባ ደግሜ መምጣት አለብኝ - አልኩ፡፡ የቀረኝ ነገር አለ፡፡ “ሰዎች ከሚሠሩት እያየሁ ነው የተማርኩት፤ በ4 ዓመቴ ነው አስተሳሰቡን የጀመርኩት፤ በላቸው አለ ዙምራ ለአስተርጓሚው፤ ለፈረንጆች እንዲነገርለት፡፡ ዕውነትም እንግሊዝኛ አለማወቁ፣ መቆጨቱ ልክ ነው እያልኩ በሆዴ፤ ወጣሁ፡፡ * * * እነሆ ለብዙ ሣምንታት፣ ከእየሩሣሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (ኢህማልድ - JECCDO) ጋር ከአመሠራረታቸው ጀምሮ ልማታዊ ትሥሥር ያላቸውን ማህበረሰብ ተኮና ድርጅቶች (CBOs) (ማህበራትና እድሮች) ስጐበኝ ቆይቻለሁ፡፡ በዚህ ጉዞ ከደብረ ዘይት ጀምሬ፣ በናዝሬት አድርጌ፣ በአዋሳ አቋርጬ፣ ደብረ ብርሃንን አካልዬ በመካያው ባህርዳር ከትሜ፣ የአውራምባን ማህበረሰብ አይቼ አበቃሁ፡፡ የሀገር ልማትና ጥንካሬ በማህበረሰቦች ድርጅታዊና ማህበራዊ አቅም ላይ መመሥረቱን፣ ህዝብን መሠረት አድርጐ የሚጓዝ ልማታዊ እንቅስቃሴ ምንጊዜም ዘላቂነት አንዳለው፣ አስተውያለሁ፡፡

የከተማ ግብርና የህፃናት ትምህርት፣ የአረጋውያን እንክብካቤ፣ የጽዳትና የጤና አጠባበቅ ስልቶች፣ የሴቶች ልባዊ ተሳትፎ የአምራቾች የኅብረት ሥራ ቅስቃሴ በማህበረሰብ ቁጥጥር የሚመራ የገቢ ምንጭ ሀብቶች ጥራት በማህበረሰቡ በራሱ ይዞታዬ፣ ጉዳዬ ተብሎ ሲያዝ ምን ያህል ዘላቂና ለሀገር ልማት ልዩ ፍኖት ሊሆን እንደሚችል ተገንዝቤአለሁ፡፡ ይህን መሰል እንቅስቃ እንደአስፈላጊነቱና እንደአግባቡ ከመንግሥት ጋር እንዴት ተደጋግፎ ለመሥራት እንደሚቻልም ልብ ብያለሁ፡፡ እንደእየሩሳሌመ ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅትና ሌሎች መሰል ድርጅቶች ህብረተሰብን በማስተባበር፣ በማገዝና ራሱን እንዲችለና እንዲበቃ ከማቴሪያል ጀምሮ እስከ ከፋይናንስና ሥልጠና ድጋፍ በመስጠት፤ ማህበረሰቡ በሁለት እግሩ ሲቆምና ራሱን በራሱ ለማዝለቅ ሲችል፤ ጉዳያቸውን ጨርሰው በመውጣት (Phase – out በማድረግ) ዕድገትን ለማጠናከር እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ያየሁበትን ጉዞ አብቅቻለሁ፡፡ ምናልባት በቦታና በጊዜ ጥበት ምክንያት የተውኳቸውን አያሌ አስገራማ ዝርዝር ሰዋዊ አሻራዎች፤ ሌላ ጊዜ በሌላ መልክ እጽፍላችሁ ይሆናል፡፡

Published in ባህል

“በቤተክርስትያናችን ሽፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል”
ሰንበት ት/ቤቶቹ የአማሳኝ አስተዳዳሪዎችን ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ ተዘጋጅተዋል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተንሰራፋው ሙስናና ሸፍጥ ላይ በተጠናከረ ኃይል በመዝመት የተጀመረውን የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ከዳር እንዲያደርሱ አዘዙ፡፡ አቡነ ማትያስ ትእዛዙን የሰጡት ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በሥር ነቀል የእርማት ርምጃዎች ለማስተካከል ያስተላለፉትን መግለጫ ለመደገፍና የፓትርያርኩ ልዩ ሀ/ስብከት የኾነው የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ያዘጋጀው የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ተግባራዊ እንዲኾን ለመጠየቅ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ፣ ጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ለተሰበሰቡት በሺሕ ለሚቆጠሩ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሰጡት መመሪያ፣ ቃለ ምዕዳንና የበዓለ ጥምቀት ቡራኬ ነው፡፡

ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት 160 ገዳማትና አድባራት የተሰበሰቡት 1800 ያህል የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች በሀ/ስብከቱ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አማካይነት ባወጡት መግለጫ፤ ፓትርያርኩ ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በማውገዝ ለማስተካከል አበክረው ሥራ በመጀመራቸው ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ ብዙኃን የሰንበት ት/ቤት አባላት አይነኬ ኾኖ ቤተ ክርስቲያኒቱን ሲያስተቻት የቆየውን ሙስናና ብልሹ አስተዳደር ስከ እስር ደርሰው ሲታገሉት እንደቆዩም ተናግረዋል፡፡ የሙስናና ብልሹ አስተዳደር ተጠቂ እየኾኑ በማደጋቸው አስከፊነቱን በሚገባ እንደሚያውቁ በመግለጫቸው ያተቱት የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ፤ ፓትርያርኩ በየጊዜው ያስተላለፏቸውን መመሪያዎች በመከታተልና የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ስለ ሚያደርገው እንቅስቃሴ በመወያየት ችግሩ ከመሠረቱ እንደሚወገድና በዘመናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ትንሣኤ እንደቀረበ መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ ሙስናንና ብልሹ አስተዳደርን ለማረም የሚካሔደው እንቅስቃሴ በእነርሱም በወላጆቻቸውም ጽኑ እምነትና አቋም እንደተያዘበት የጠቀሱት ወጣቶቹ፤ ጥረቱን ከግቡ ለማድረስ ከፓትርያርኩ ጎን ቆመው በታዘዙበት መሥመር ለመሰለፍ ዝግጁ መኾናቸውን አስታውቀዋል፡፡

‹‹የፀረ ሙስና እንቅስቃሴውን እንደግፋለን ብላችኁኛል፤ እኔም እንደምትደግፉኝ አምናለኹ፤›› በማለት ተስፋቸውን የገለጹት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው÷ ‹‹ዘመኑ የእምነት ጉድለትና የኑፋቄ ነው፤ ሐቅ፣ መልካም አስተዳደር፣ እውነተኝነትና ሓላፊነት ጠፍቷል፤ በቤተ ክርስቲያናችን ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል፤›› ሲሉ አምርረው ተናግረዋል፡፡ ስለሙስናና ብክነት ከሚሰጧቸው ተደጋጋሚ መግለጫዎች ጋር ተያይዞ ‹‹ኹላችንም ሌቦች ተብለናል›› የሚል ቅሬታ ያቀረቡላቸው ወገኖች መኖራቸውን ያልሸሸጉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹የሚያመው ያመው ይኾናል፤ ሁላችኁም አማሳኞች ናችሁ የሚል አልወጣኝም፤ የሚያማስኑ እንዳሉ ግን ሐቅ ነው፤›› ሲሉ የችግሩ አስከፊነት ሊካድ እንደማይገባው አረጋግጠዋል፡፡ ሙስና ማለት ጥፋት ነው ሲሉ የቃሉን ትክክለኛ ንባብና ገላጭነት ያብራሩት ፓትርያርኩ፣ ‹‹በቤተ ክርስቲያን ያለው የሙስና ሙስና›› መኾኑን በመግለጽ፣ በፀረ ሙስና ቅስቀሳው የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ በይበልጥ እንዲዘምቱበት አሳስበዋቸዋል፡፡ ‹‹ተይዞ ባለው የፀረ ሙስና ቅስቀሳ እናንት የሰንበት ት/ቤት አባላት በይበልጥ ብትዘምቱበት፤ በተጠናከረ ኃይል ይህን ብትረዱኝና ከዳር ብናደርሰው አመሰግናችኋለሁ፡፡›› በተያያዘ ዜና÷ የአዲስ አበባ ሀ/ስብከትን የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ እንቅስቃሴ የሚበዙት የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የጽ/ቤት ሠራተኞች፣ ማኅበረ ካህናት፣ ማኅበረ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች እንደሚደግፉት እየተገለጸ ቢሰነብትም ‹‹ምእመናን በእኛ ሕግ ምን ያገባቸዋል፤›› የሚሉ አንዳንድ አስተዳዳሪዎች ቅሬታቸውን ለፓትርያርኩ ማቅረባቸውን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

እንደምንጮቹ መረጃ፣ ቅሬታ አቅራቢ አስተዳዳሪዎቹ የመዋቅር ለውጡን የሚቃወሙ ሲኾኑ ከእነርሱም መካከል ለአደረጃጀትና አሠራር ለውጡ በተከታታይ የተካሔዱት የድጋፍ መግለጫ ስብሰባዎች ምእመናኑን በእነርሱ ላይ ኾነ ተብሎ ለማነሣሣት የታለሙ ናቸው ብለው ያምናሉ፡፡ ሰንበት ት/ቤቶቹ ከፓትርያርኩ ጋር ባካሔዱት ውይይት፣ ሙስናና ብልሹ አስተዳደርን በግልጽ በመቃወማቸውና በማጋለጣቸው ያሳሰሯቸውና ያስደበደቧቸው አስተዳዳሪዎች እንዳሉ ተገልጧል፡፡ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶቹ የቤተ ክርስቲያንን ሀብትና ንብረት ለግል ጥቅም በማዋልና ለባዕድ አሳልፎ በመስጠት አላግባብ በልጽገዋል የሚሏቸውን አማሳኝ አስተዳዳሪዎች ዶሴ ለፓትርያርኩ ለማቅረብ፣ እንደ ሕጉ አግባብም ለፀረ ሙስና ኮሚሽን ለማመልከትም ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ከአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሥራ አመራር አባላት ተጠቁሟል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ የጥቅምት ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ÷ ቤተ ክርስቲያኒቱ ‹‹የሃይማኖት ዕንከን ሳይኖርባት፣ ሞያ ሳያንሳትና ተቆርቋሪ ምእመናን እያሏት›› በመልካም አስተዳደርና በፋይናንስ አያያዝ ምክንያት የምትወቀስበትና ልጆቿን የምታጣበት ታሪክ መገታት እንዳለበት የገለጸ ሲሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን የአገልግሎት አፈጻጸም እሴቶችና መርሖዎች የሚገልጸው መሪ ዕቅድ ከገመገመ በኋላ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ከሥሩ ለመቅረፍ በሚያስችል አኳኋን ተዘጋጅቶ እንዲቀርብለት መመሪያ መስጠቱ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና
Saturday, 18 January 2014 12:10

ክፍል አራት

ከባለፈው እትም የቀጠለ
የግል ንግድ ተቋማት ማህበራዊ ሃላፊነትና የህጻናት ጥቅም

ቀደም ባሉት ክፍሎች እንዳየነው የግል ንግድ ተቋማት በማንኛውም የንግድ እንቅስቃሴያቸውና አቅርቦታቸው ውስጥ የህጻናትን ደህንነት የማረጋገጥ ብሎም ምርትና አገልግሎታቸው የህጻናትን ጥቅምና ፍላጎት ያማከለ ስለመሆኑ የማረጋገጥ ሃላፊነት እንዳለባቸው ያስረዳሉ ፡፡ ስድስተኛው መርህ ሽያጭና ማስታወቂያዎች የህጻናትን ደህንነት ማክበርና መደገፍ እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ እንደሚታወቀው ሽያጭና ማስታወቂያ ለማንኛውም ንግድ የደም ስር መሆናቸው ይታወቃል፤ ሆኖም እነዚህ ሁለት እንቅስቃሴዎች ሲካሄዱ በልጆች ላይ ለያደርሱ የሚችሉት ተጽእኖ ብዙም ቦታ ላይሰጠውና ላይተኮርበት ይችላል፡፡ ስለዚህም በማንኛውም መንገድ ምርታቸውን በሚሸጡበት አልያም በሚያስተዋውቁበት ወቅት በህጻናት ላይ ምን ሊያስከትል ይችላል የሚለውን ቅደሚያ ከግምት ማስገባት ያለባቸው ጉዳይ ስለመሆኑ ያስረዳል፡፡

መርሁ የሽያጭ ሂደትም አድልዎ ሊኖርበት እንደማይገባና@ ለተጠቃሚዎች ውሳኔ ይረዳ ዘንድም የምርቶችን ደረጃ በይፋ የማሳወቅ ሃላፊነት እንዳለባቸውም ያስረዳል፡፡ምንም ያህል የጠበቀ ቢሆን፤ የምርት ማስተዋወቅ ሂደትና ማስታወቂያ የአለም አቀፍ የጤና ድርጅትን እንዲሁም ከአገር አቀፍ ደረጃዎች ጋር የሚስማሙ መሆን አንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ እንደ መርሁ አገላለጽ የንግድ ድርጅቶቹ በሽያጭ ወይም በማስታወቂያቸው በጎ አመለካከቶችን(አስተሳሰቦችን) ፣ጥቃትን መቃወም እና ጤነኛ የአኗኗር ዘዴን በማንጸባረቅ በተለይም የህጻናት ጥቅሞችን የሚደግፉ መሆን እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡

ሰባተኛው መርህ ህጻናት ከአከባቢያቸው፣ ከመሬት ይዞታና አጠቃቀም ጋር ያለቸውን መብቶች ስለማክበርና ስለመደገፍ ይመለከታል፡፡ ህጻናት ከአከባቢያቸው ጋር በተያያዘ ያሏቸው ፍላጎቶች ከግምት ውስጥ ሊገቡ ይገባቸዋል፡፡ አከባቢን አስመልክቶ የሚወጡ ማናቸውም እቅዶችና ሰትራቴጂዎች የህጻናትን፣የቤተሰቦቻቸውን አንዲሁም የማህበረሰቡን ፍላጎት ያማከሉ መሆን እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ በተጨማሪም እነዚሁ እቅዶች በአከባቢና በጤና ላይ ለሚደርሱ ጉዳቶች፣በስራ አጋጣሚ ለሚከሰቱ ጉዳቶች የሚሆኑ የካሳ አከፋፈል ስርአትን የማካተት ሃላፊነት ለነዚህ ተቋማት ይሰጣል፡፡ እንደ መርሁ አገላለጽ በመሬት ይዞታና አጠቃቀም ዙሪያም እነዚህ የንግድ ተቋማት@ ከመኖሪያ ቦታ የመፈናቀል አጋጣሚን በመቀነስና ህብረተሰቡን አሳታፊ በሆነ መልኩ የህጻናትን ጥቅም መከበርን ከግምት ማስገባት ይኖርባቸዋል፡፡ በተጨማሪም ከአከባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ የህጻናት የመማር፣የደህንነት፣የጤና፣በቂ ምግብ የማግኘት፣ በጥሩ ሁኔታ የመኖር እንዲሁም የተሳትፎ ፍላጎቶቻቸው ሊከበሩ እነደሚገባም ያስረዳል፡፡ ስለዚህም የንግድ ተቋማት ከአከባቢ እንዲሁም ከመሬት ይዞታ ጋር በተያያዘ የሚያከናውኗቸው ተግባራት@ ለአከባቢ ደህንነት ብሎም ለቀጣዩ ትወልድ አሉታዊ ተጽእኖዎችን ሊያስከትሉ እንደሚችሉ በመገመት ከወዲሁ ለዘላቂ ልማት አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡

Published in ጥበብ

“ግጥም እግሮቹ ሳይጠኑ ወረቀት ላይ አይራመድ”

ስለዘመናችን ስናስብ፣ ዘመኑ ስላበቀላቸው ግጥሞች ስናሰላስል ሣቅ ይርቀናል፣አይናችን እንባ ያቀርራል፡፡ ግጥም ታላቅ ጥበብ መሆኑን ታላላቅ የዓለማችን ጠቢባን በብርቱ ብዕራቸው ድርሣን ሞልተው ቢያልፉም ብዙዎች ግን እንደፌንጣ እየዘለሉ አጉድፈውታል፡፡ በኛ ሀገር የግጥም ነገር መላቅጡን እያጣ መምጣቱን ደጋግሜ መለፈፌ ይታወቃል፡፡ “ግጥም ሞቷል” ብሎ አንድ የተባ ብዕር ያለው ጋዜጠኛ ከጻፈ በኋላ፣ ነገሩ እውነት እየሆነ መምጣቱ ሲገርመን አሁን ደግሞ አስከሬኑን ለመጎተት ልባቸው የጠና ምድሩን ሞልተውት እያየን ነው፡፡ ለአቅመ ንባብ ያልበቁትን ግጥሞች በወረቀት ገንዘው ሲያቀርቡ፣ በየአዳራሹ ውስጥ ለማስመረቅ ሳይሆን ለማስቀበር እንደነፍስ አባት ለፍትሀት የሚወዛወዙ ከየሙያው ዘርፉ ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡ የኮሎምቢያ ዩኒቨርስቲዋ መምህርት ሊዎራሮ ስፔየር፤ ግጥም እግሮቹ ሣይጠኑ ወረቀት ላይ አይራመድ ትላለች፡፡ ታላቁ የግጥም ምሁርና ተመራማሪ ሂሊየር ደግሞ ግጥማችሁን ደጋግማችሁ አብስሉት ይላል፡፡ እንግሊዛዊው ገጣሚና የዩኒቨርስቲ ምሁር ሮበርት ፍሮስትም፤ “ግጥም በዘይቤያዊ ቃላት ካልተከሸነ አይን አይገባም፤ ልብም አይደርስ” ይላል፡፡

የእኛ ሀገር ዋና ዋና ችግሮች አሁን የተጠቀሱት ይመስሉኛል፡፡ ጥሩ የምንላቸው እንኳ ዘመን የማይሻገሩ፣ ፈንጠዝያ ፈጣሪ የምጣድ ላይ ተልባዎች ሆነዋል፡፡ አንዴ ዘልለው መሬት የሚቀሩም አሉ። አንዳንዶቹም አክንባሎ እንዳልተከደነ እንጀራ መስለው አይን አውጥተው አይን ሳይጠቅሱ የሚቀሩ እንጥልጥሎች ሆነዋል፡፡ ለዚሁ ሁሉ ችግር ተጠያቂው ደግሞ የእኛ ግብዝነትና አስመሳይነት ይመስለኛል፡፡ የግጥሙንና የገጣሚውን ትክክለኛ አቅምና ብቃት ከመናገር ይልቅ ተለሳልሰን ርካሽ ውዴታና ውዳሴ መቀበል እንመርጣለን፡፡ እጅግ የምወዳቸውና የማከብራቸው የግጥም ጓዳ ፈታሽ ለውረንስ ፔረኒ ግን በዓለማችን ላይ ማን በየትኛው ደረጃ እንደሚቀመጥ በስም ለይተው እስከ መጻፍ ደፍረዋል፡፡ ሂሊየርም ቢሆኑ ሎንግፌሎውን ሲያደንቁ፣ ዲከንሰንን ሲያወድሱ፣ አላንፖን ሲገመግሙ ድክመቱን እየጠቆሙ ነው - መረጃ እየጠቀሱ፡፡ ለምሣሌ የአሜሪካን የ19ኛው ክፍለ ዘመን አራት ምርጥ ገጣሚያን ይደረድሩና አንዱ ግን ወደ ሃያኛው ክፍለ ዘመን መሻገር እንዳቃተው ይጠቁማሉ - ያውም ኤመርሰንን! እኛ ግን ለዚህ አልታደልንም፣ እየዋሸን፣ እያስመሠልን የሀገራችንን ጥበብ እንቀጫለን። ለዚያውም አስተያየት ስንሰጥ “በኔ አመለካከት” እያልን ነው፡፡ የእኛ አመለካከት ስሜት ነው። ለራሳችን ማጣጣሚያ ብቻ የሚሆን ነው። ስለ ግጥም የተጻፉ በርካታ መጽሐፈት እያሉ፣ ለምን በስሜት መዳኘትና ማሣሣት እንዳማረን ባላውቅም፣ አዝናለሁ! ….ፍቅር ካለን በቅጡ መገምገም ነው፡፡

ለምሣሌ ባለፈው ሰሞን አንድ ነጋዴና ሌላ አትሌት የግጥም መጽሐፍ ላይ አስተያየት እንደሰጡ ጠቁሜ ነበር፡፡ ጥፋቱ ግን የነርሱ አይደለም፡፡ የአስተያየት ጠያቂዎቹ ነው፡፡ እውነት ለመናገር ከየትኛውም የጥበብ ዘርፍ በእኛ አገር ሁሉም ተነስቶ እንደፈለገ የሚፈነጭበት የግጥም ሠፈር ብቻ ነው፡፡ በተለይ አጫጭር ግጥም የሚለውን ሰበብ ተጠቅሞ እንደልቡ ያልሆነበት የለም፡፡ አንብበናል የሚሉትን ሰዎች እንጀራቸውን ሲያሣድዱ ጥበቡ ገደል ይገባ ብለው ትተውት “ሃይ!” የሚል ጠፍቷል፡፡ በዚህም የተነሳ በጓደኝነትና በቡድን የማይረባውን ሥራ ከፍ ከፍ ለማድረግ ሲሞክር ይታያል፡፡ ባለፉት አሥር ዓመታት ካነበብኳቸው የግጥም መጽሐፍት ሁለንተናዊ የግጥም አላባውያንን ያሟሉና ብቃት ያላቸው መጽሐፍ አሥር እንኳ አይሞሉም፡፡ አንዳንዶቹ ለጊዜው ቢጣፍጡም እንደእለት መና ለአንድ ቀን ጣፍጠው በማግስቱ ትዝ የማይሉና የሚረሱ ናቸው። ምናልባት በቋንቋ ልቀትና በአሠኛኘት፣ በሥርዐተ-ነጥብ፣ በዜማና ምት ከፍ ያሉ ናቸው የምንላቸው የዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ የታገል ሰይፉ (የመጨረሻ መጽሐፍ) የዮሐንስ ሞላ ጥቂቱ ናቸው። ለምሣሌ በቅርብ ከታተሙት “ቀብድ የበላች ሀገር” በቋንቋው የተሻለ ስፍራ የያዘ ነው። እንደዚሁ የላቀ ሃሣብ ይዘው እንደ ዱባ ሀረግ ሃሣብ መሸከም የሚችል ቃላት አጥተው መሬት ለመሬት የሚሳቡም አሉ፡፡ ሰሞኑን ከታተሙት የግጥም መፃሕፍት… የገጣሚ አብርሃም ስዩም መድበል ጥሩ አተያይ፣ ሩቅ ያለ ሕልም በውስጧ ይዛለች ለማለት ያስደፍራል፡፡

ደግሞ በሌላ በኩል የዜማ ስብራት፣ የአሠኛኘት ልልነት ይታይባታል… ቢሆንም ብሩህ ተስፋ ያረገዘች መፅሃፍ ናት፡፡ እስቲ ጥቂት ግጥሞች እንይ… መርሺያ የለኝምና! እርሽኝ አታስታውሽኝ እስከ መፈጠሬ! እርሳኝ ግን አትበይኝ እባክሽን ፍቅሬ! ይህች “መንቶ” ግጥም ትልቅ ሃሣብ፣ ጥልቅ ስሜት ተሸክማለች፡፡ ግዙፍም ናት፡፡ “ያገር ነሽ!” በሚል ስንኝ የተቋጠረለትን ግጥም ደግሞ እንያት፡፡ የሕዝብ ቅኝት ናት የሕዝብ ሁሉ ዜማ፣ የኔ ነሽ አይሆን መቼም ቢሆን ስሟ! እንደባቲ ቅኝት ደግሞ እንደ ትዝታ ማንም ይቃኛታል ሲመሽ ወደ ማታ! ትራፊክ የለበት መንገድ ሚቆጣጠር ፈቃድ አይጠይቅም እሷን ለመዘወር ልቤን ወስዳው ነበር ድንገት እንዳየኋት ያገር ብትሆንብኝ አፍቅሬ ሸሸኋት!! ይህች ግጥም በጭብጥዋ የዘመናችን ችግር ናት፡፡ አንድ ሰው ልቡን ስንት ቦታ እንደሚቸረችር መቁጠር ያዳግታል፡፡ ብዙ ጊዜ ስለ ሴቶች ይወራል እንጂ የወንዱ ይብሣል፣ ባህላችን ግን ብልግናን ለወንድ የፈቀደ ስለሆነ ሴቶች ላይ ጥቂቱ ይገዝፋል። ይህንን አሮጌ ባህል መዋጋትና ማስወገድ የጥበቡ ዓለም ሰዎች ይመስለኛል፡፡ “አንድ እኩል” የሚለው ግጥምም እንዲህ ይላል፡- በሎሚ ጋጋታ … አነጣጠርኩና ደረቷን ብመታ፣ እኔም አላመለጥኩ ደረቴ ተመታ፣ ከባሏ ጠመንጃ በተሳበ ቃታ!! ሃሣቡ ጥሩ፣ አተያዩ የተለየ ነበር፡፡

ግን ቤት መምቻውና መድፊያው ሥሩ አንድ ግስ ነው፡፡ ሀብትን ማን ይጠላል? የሚለው ግጥም፡- ያማረ መኝታ የተንደላቀቀ የማይቆጠር ሃብት ስፍሩ ያልታወቀ ጮማና ወይን ጠጅ እንኳንስ ቀምሰውት ሲያዩት የሚያስጐመጅ ይህን ሁሉ ሰጥቶ ፍላጐት ከማጣ ቁርበት የለበሰ የጭቃ መደብ ላይ ድንጋይ ተንተርሼ ጣሪያ ሆኖኝ ሰማይ አንድ ቅርጫት ሙሉ ቦሎቄ ከክቼ እየፈሳሁ ልደር ጧ ብዬ ተኝቼ ግጥሙ እርካታ በገንዘብና ምቾት እንደማይገኙ ይተርካል፡፡ በቁሳዊ ነገር ጥሩ እንቅልፍ፣ ዘንባባ የተጐዘጐዘበት ሕይወት እንደማይመጣ ያሣያል። ርዕሰ ጉዳዩ የዘመኑ የሥነ ልቡና ምሁራን መከራከራያና ጥያቄም ነው፡፡ አብርሃም ጥሩ አይቶታል፣…. ቤት ለመምታት ሲል ግን አራተኛውን ስንኝ ለጥጦ ውበት አሣጥቶታል እንጂ፡፡ የአብርሃም ግጥሞችን ስቃኝ አርታኢ ቢኖረው ኖሮ ያሰኙኝ ግጥሞች ብዙ ናቸው። ለምሳሌ ግጥሙን ያነበበለትና አስተያየት የሰጠው አርቲስት “ስሞት አትቅበሪኝ” ከሚለው ግጥም ላይ የመጨረሻዎቹን ስድስት ስንኞች ማስወገድ ነበረበት፡፡ ግጥሙን ከወገብ በላይ ጠንካራ፣ ከወገብ በታች እግሮቹን የሚጐትት ሽባ አድርጐታል፡፡ ይልቅ፡- ተስማሚ በቃሌ ፍቅሬ እሺ በይኛ፣ ሞቼም አልለይሽ አብሬሽ ልተኛ --- ብሎ ቢያቆም ሙሉና የፈረጠመ ውበት በነበረው፡፡ የዘመን ጣር የሚለው ግጥር ላይ ጳጉሜን “ዘመን” ብሎ በዚያው አንድ መስመር “ዘመናት” ሲል የሁለትዮሹን ሥብራት ማቅናት ይቻል ነበር፡፡

ገጽ 8 ላይ ያለው “ነበር” በሚል ርዕስ የተጻፈ ግጥም፣ ከሠናይት አበራ “የጨረቃ ሳቆች” መድበል ገጽ 15 ላይ ካለው “እባብ የሞት ምግብ” ጋር ተመሳሳይነቱን ልብ ይሏል፡፡ እስቲ እናስተያያቸው፡- እባብ የሞት ምግብ አዳምና ሄዋን ቻይናዊ በሆኑ የሩቅ ምስራቅ ሰዎች ጃፓን በነበሩ ይቺን ፍሬ ብሏት ብሎ የነገራት ይሆን ነበር ሾርባ ከእፀበለስ በፊት፡፡ ይህ ግጥም በ1996 ዓ.ም የታተመ ነው፡፡ “ነበር” ሕንዳዊ ነው አዳም አባቴ! ማለቴ፤ አዳም ቻይናዊ ሆኖ ቢፈጠር በለሱን ትቶ እባቡን ከትፎ ይበላው ነበር፡፡ ይህ መመሣሠል አንዳንዴ ሣይታወቅ፣ በአአምሮ ውስጥ ቆይቶ ከራስ ሃሣብ ጋር ሊፈስ ስለሚችል ያጋጥማል ብሎ መጠበቅ ይቻላል፡፡ ግን ይህንን አርታኢ ሊያስታውሰውና ሊያቀናው ይችላል፡፡ ግን በአጠቃላይ ግጥም፣ የብዙ ነገሮች ቅንብርና የብዙ መዋቅር ውጤት እንጂ እንደ ኦ ሔነሪ ልቦለዶች ያልታሰቡ ነገሮችን ብቅ ማድረግ ብቻ አይደለም። የላቀ ቋንቋ ለግጥም የግድ ነው። እንደፍጥርጥሩ ካላልን በስተቀር ኦና ቃላትን መደርደር ምንም ፋይዳ የለውም፡፡ ከሰሞኑ ለንባብ የበቃው የአብርሃም ስዩም “ወደ ብርሃን የተሰኘ” መጽሐፍ ግን ብዙ ውበት፣ ጥሩ አተያይ የተስተዋለበት ነው፡፡ የአሠኛኘት ጥንካሬ ለማግኘት ግን ንባብ የሚያስፈልግ ይመስለኛል። እጅግ ለተሻለ ሥራ የሚጠበቅ ወጣት መሆኑን ከሥራዎቹ ማየት ይቻላል፡፡ ግን ሳያነቡ መጻፍ በጐ አይመስለኝም፡፡ አቅምን በንባብ ማገዝ ለሁሉም ወጣት ገጣሚያን ፍቱን መድሃኒት ነው። የግጥማችንን ሬሳ ከመጐተት ያድናልና፡፡ አብርሃም በርታ…. ጥሩ ሃሣብ፣ጥሩ ድፍረት ይዘሃል፡፡

የፍልስፍና ጥያቄዎችህም የሚያመራምሩ ናቸው፡፡ ሌላው በቅርቡ ገበያ ላይ የዋለው መጽሐፍ የቴዎድሮስ ሞገስ “የኔው እኔ” የተባሉ የግጥሞችና ጭውውቶች መድበል ነው፡፡ መጽሐፉ ፀሐፌ ተውኔት ኃይሉ ፀጋዬ የጀርባ አስተያየት ሰጥቶበታል። መድበሉ በአሠኛኘትና በዜማና ምት ጣዕም ፈቀቅ ያሉ ግጥሞችን ያካተተ ነው፡፡ እንደጉሽ ጠላ እንትፍትፍ የሚያሰኙ ግሣንግሶች የሉበትም። ጥቂት ቢሆኑም ጥልል ያሉ ግጥሞች ይዟል፡፡ ለምሣሌ “ጥበብ” የሚለው ግጥሙን እንይ፡- ውርጭ የመታው ጥጥ ፈርቅጠው በወጥ አባዝተውት በቅጥ በብሳና ደጋን ብን አርገው ሳይነድፉት፣ በ ከማን አንሼ እኔ ከማን ብሼ ከእነ እድፍ ጉድፍ አሸምነው ጥበብ ጥልፍ ቢያስጠልፉት፣ እንኳን ልብ ሰርቆ ስም በሩቅ ሊያስጠራ ቢለብሱትም አይሞቅ ቢያጥቡትም አይጠራ፡፡ ጥበብን ትንሽ ለየት ባለና ከሀገራችን የሸማ ሥራ ጥበብ ጋር አዛምዶ ወይም አነጻጽሮ ተምሣሌታዊ በሆነ መንገድ አቅርቦታል፡፡ የነቶሎ ቶሎ ቤት ካደረጉት ደግመው ሊያበጁት አይችሉም፡፡ ሊያቀኑት አይቀልልም ይላሉ፡፡ “እንኳን ትርፍ ሊያገኝ” የሚለው ግጥም እንዲህ ተጽፏል፡- እንደ ዕድሉ እንደገዱ ጠመመም ተቃና የሕይወት መንገዱ እንደተጻፈለት መኖር ላይቀርለት ቅናት ሎሌው አርጐት አጉል ሲያቀናጣው እንኳን ትርፍ ሊያገኝ ያለውን ሊያሳጣው አምጦ ላይወልደው ወይ ነጥቆ ላይወስደው የባልንጀራውን አጥብቆ አስወደደው፡፡

የተሻለ ርዕስ ሊመርጥለት ሲችል ለምን ይህን እንዳደረገው ባይገባኝም፣ ቅናትን ትርፍ የለሽ አድርጐ የሚጐሽም ግጥም ነው፡፡ የጠለቀ ሃሣብ የተደበቀ ዓይን የለውም፣ ያው በኛው አይን ነው ያየው፡፡ ገጣሚ ግን የማይታይ አይን አለው ብለን እናምናለን፡፡ ሌላው “የእኔው እኔ” መድበል ግጥሞች ፀባይ ባብዛኛው የግጥሙ ተራኪ ተቺ መሆኑ ነው- አውጋዥ ነው፡፡ “ሰው መሳይ” እንዲህ ይላል፡- ሰው ሲል የሰማውን ደጋግሞ ዘማሪ ልብስ ተማሪ በቁም ከፈን እንደቃሪያ ተሰንጐ ሳመኝ ስሙኝ ይላል ሰው መሳይ በሸንጐ “ቅቤ እንኳንስ ሆዱን” የሚለውም ግጥም ተራኪው ሌላኛውን ወገን የሚተችበት ነው፡፡ በአጠቃላይ ከላይ እንዳልኩት ጥሩ የተገመዱ ሰንኞች አሉት፣ ሀዲዱ ግን በአብዛኛው ወደ አንድ አቅጣጫ ያመራል፡፡ ቋንቋው የላቀ ባይባልም አሁን ከምናያቸው አብዛኞቹ ግጥሞች የተሻለ ነው፡፡ የሃሣብ ልቀት ግን ያንሰዋል፡፡ ቢሆንም አንዴ ተነብቦ የሚጣል አይደለም፡፡ ጥሩ ነገሮች አሉት፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 18 January 2014 12:08

አዲስ አባ

ቀለበት አስሮ እንደያዘው
እንደደለለው ጋብቻ
ግብሩን ከቶ ሳላገኘው
ተጃጅዬ በስም ብቻ
በምኞት ህልም
በአጉል ተስፋ
እስትንፋሴ እየራቀ
አኗኗሬ እየከፋ
ውስጤ ላዬ እያደፈ
ብዙ አበቅቴ ተታለፈ፤
ቱር…ሳልል ብርር ….ሳልል
እዚህ እዚያ ሳላዳርስ
ጭብጥ ጥሬ እንኳ ይዤ
ባልጠግበውም ላመል ሳልቀምስ
ባይሞቀኝም እንዳይበርደኝ
ጐጆ ይዤ ጭስ ሳላጨስ
“እልፍ ካሉ - እ - ልፍ” እንዲሉ
ዞር ማለቱን ሰንፌ
እንዳኖሩት ግዑዝ ድንጋይ
ቀረሁብሽ ተወዝፌ፤
ውሃ እንደተጠማ ኩታ
ልዋጭ እንደሌለው ጨርቅ
ገምቼ ገልምቼ ስቼ
ከእድፌ ጋር ስጨቃጨቅ
ስትገፊኝ እምቢኝ እያልኩ .
ዛሬም አለሁ አንቺን ሳለቅ፤
አዲስ አባ
ውሃሽ በመዘውር አልፎ
ዙሪያ ገባሽን ቢሞላ
ለኔ በባሊ ነፍጐ
ለረጠበው እያደላ
“ዝናብ ቢዘንብ በባህሩ…”
ብሎ እንዳለው መምህሩ
ገበሬ እንኳ ዓመት ለፍቶ
ለጐተራሽ ቢዘረግፍ
እጀ ረጅሙ ደርሶ
አግበስብሶ ነው… እሚልፍ
እናም አዋጅ ልንገር ጐረቤት ሁሉ ይስማ
ርስቴን ለቀቅሁ ወጣሁ ወደ ሌላ ከተማ፡፡
አውላቸው ለማ   

Published in የግጥም ጥግ

ጃኖ ባንድ ለዓመቱ የመጀመሪያ የሆነውን የሙዚቃ ኮንሰርት ዛሬ ምሽት በትሮፒካል ጋርደን ያቀርባሉ፡፡ ኮንሰርቱን ከአምስት ሺ በላይ ሙዚቃ አፍቃሪዎች ይታደሙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የመግቢያ ዋጋ 200 ብር እና ለቪአይፒ 400 ብር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ጃኖ ባንድ በመቀጠል በቀጣይነት ተመሳሳይ የሙዚቃ ድግሶች በጐንደር፣ ባህርዳር፣ ድሬዳዋ እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡

የሥነፅሁፍ ምሁሩን ዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳን የሚዘክር የኪነጥበብ ዝግጅት ዛሬ ከ3 ሰዓት እስከ 6 ሰዓት በብሄራዊ ቲያትር ቤት ይቀርባል፡፡ ከ40 ዓመት በላይ በኢትዮጵያ ስነፅሁፍ ዘርፍ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረከቱት ዶ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ፤ በአሜሪካ ሎስአንጀለስ ዩኒቨርስቲ ውስጥ መምህር ናቸው፡፡ ምሁሩን ለመዘከር በተሰናዳው የኪነጥበብ ዝግጅት፤ የስነፅሁፍ ባለሙያዎች ግጥሞችን፤ ተውኔቶችንና መነባንቦችን እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጅ አብርሃ ግዛው ኢንተርቴይንመንትና ፕሬስ ሥራዎች ገልጿል፡፡

በእርቅይሁን በላይነህ የተዘጋጀው “የኢትዮጵያ ታሪክ - ከኢማም አሕመድ እስከ አጤ ቴዎድሮስ” የተሰኘ የታሪክ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ፣ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም የታሪክ ተመራማሪ ዶ/ር ተፈሪ መኮንን በመፅሃፉ ጀርባ ላይ በሰጡት አስተያየት፤ “ይህ መፅሃፍ በታሪክ ተመራማሪዎች ብዙም ትኩረት ያልተሰጠውን፣ ነገር ግን ምናልባትም ወሳኝ የሆነውን የኢትዮጵያን ታሪክ በአማርኛ ቋንቋ ስለሚዳስስ፣ ለአብዛኛው ኢትዮጵያዊ አንባቢ ተመራጭ እንዲሁም ወደፊት ለሚደረጉ የታሪክ ምርምሮች በመነሻነት የሚኖረው ድርሻ ከፍተኛ ነው” ብለዋል፡፡ በ364 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ ስድስት ምዕራፎች ያሉት ሲሆን በ79.99 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የኒዮሊበራሊዝም ኃይሎች በአሸባሪነት ተፈርጀዋል እንዴ?
የኢኮኖሚ ዕድገቱን መካድ “ከሃዲነት” ነው!
“የመንግስት ሚዲያዎች በባህርያቸው የአውራው ፓርቲ ልሳን ሆነዋል”

<እውነቱን ለመናገር በአሁኑ ወቅት “ማጥራት” የሚፈልጉ “ብዥታዎች” እንደ ጉድ ተበራክተዋል (የቃላቱ ኮፒራይት የኢህአዴግ መሆኑ ልብ ይባልልኝ!) እናላችሁ ….. የዛሬ ፖለቲካዊ ወጌ በእነዚህ “ብዥታዎች” ዙርያ ያጠነጥናል፡፡ (ብዥታዎች ሳይጠሩ ልማትም ዲሞክራሲም ቅዠት ነው!) በነገራችሁ ላይ… ያለማንም ስፖንሰርሺፕ ባካሄድኩት መጠነኛ ጥናት፤ ብዥታዎቹ ኢህአዴግ ተቃዋሚዎች ሳይል በሁሉም ላይ የሚታዩ መሆናቸውን ያረጋገጥኩ ሲሆን ብዥታዎቹን በመፍጠር ረገድ ግን አውራው ፓርቲና የመንግስት ሚዲያዎች የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ (የእኔ ሳይሆን የጥናቱ ውጤት ነው!) አሁን በቀጥታ ወደ “ብዥታዎቹ” እንግባ፡፡ ባለፈው ሳምንት በዚሁ ጋዜጣ ላይ በወጣ ዘገባ ሰማያዊ ፓርቲ “የምናገርበትን ሚዲያ ማንም እንዲመርጥልኝ አልፈቅድም” ማለቱን አንብቤ ቆራጥነቱን አድንቄለታለሁ፡፡ እዚሁ ቆራጥነት ውስጥ ግን ያሸመቀ “ብዥታ” አስተውያለሁ። ብዥታውን የፈጠረው ኢህአዴግ ቢሆንም። ነገርዬው…. ኢቴቪ በቅርቡ ካስተላለፈው የሽብርተኝነት ዶክመንተሪ ጋር በቀጥታ የተገናኘ ነው ተብሏል፡፡ /ፓርቲው ነው ያለው!/ እኔ የምለው ግን …ኢቴቪ በቅርቡ ለግሉ ሴክተር ያቀረበውን “ዶክመንተሪ ፊልሞች በጋራ እንስራ” የሚል ፕሮፖዛል ወይም የግብዣ ጥሪ ሰምታችኋል? (አቅሙና ፍላጐቱ ያላችሁ እንዳያመልጣችሁ ብዬ ነው!) ግን የ“ሰው ለሰው” ዓይነት ድራማ እንዳይመስላችሁ፡፡

በአብዛኛው ለውዝግብና ለፍ/ቤት ማስረጃነት የሚቀርቡ ዶክመንተሪ ፊልሞች ናቸው፡፡ (ማዝናናትና ትግል ለየቅል ናቸው!) እኔ መጀመሪያ ግብዣውን እንደሰማሁ “አደጋ አለው!” ብዬ ነበር፡፡ በኋላ ረጋ ብዬ ሳስበው ግን የወደደ የሚገባበት ስለሆነ ችግር የለውም ብዬ ተፅናናሁ፡፡ (የቱ ነበር ክስ የቀረበበት ዶክመንታሪ?) ለዚህ ነው መሰለኝ የኢቴቪን ግብዣ እንደሰማሁ “አደጋ አለው!” ያልኩት፡፡ ያለዚያማ ኢቴቪ ያለበትን የአቅም ውሱንነት ከግምት ውስጥ አስገብቶ፣ ከግል ሴክተሩ ጋር ለመስራት ያቀረበው ሃሳብ ወርቅ እኮ ነው፡፡ (ኧረ እንደውም ዘግይቷል!) እዚህ ጋ ግን አንዲት “ብዥታ” ጥርተን ማለፍ ይኖርብናል፡፡ ዶክመንታሪውን ከኢቴቪ ጋር ለመስራት የኢህአዴግ ደጋፊ፣ አባል፣ ምናምን መሆን ያስፈልጋል እንዴ? (መጥራት ያለበት “ብዥታ” ስለሆነ ነው!) አያችሁ …. ብዙዎቹ የኢቴቪ ዶክመንታሪዎች የአውራውን ፓርቲ ፖለቲካዊ ውሣኔና አቋምን የሚያንፀባርቁ ስለሆኑ አውቀን እንድንገባበት ነው፡፡ በነገራችን ላይ …. ኢቴቪ በሚዲያ ዳሰሳ ፕሮግራሙ የግሉን ፕሬስ ጋዜጠኞች እየጋበዘ በተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ማወያየቱን ወድጄለታለሁ፡፡

(ከመራራቅ መቀራረብ፣ ከመነቃቀፍ መወያየት ይሻላል!) አያችሁ…የእኔን ነገር! ሳላውቀው እኮ ሌላ አጀንዳ ውስጥ ራሴን ዶልኩት፡፡ (የእኛው ጉዳይ ስለሆነ አትታዘቡኝ!) ሰማያዊ ፓርቲ “የምናገርበትን ሚዲያ ማንም እንዲመርጥልኝ አልፈቅድም” ብሏል ብዬ ነበር - ባለፈው ሳምንት። ፓርቲው ይሄን ያለው በኢቴቪ በቀረበው ዶክመንታሪ ላይ ከ “ኢሳት” ጋር ግንኙነት ያላቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱን ጠቅሶ ነው። ማስጠንቀቂያው የመንግስት ባለስልጣኖችን ዝም ብሎ ማለፉ ያስቆጣው ይመስላል - ፓርቲው፡፡ (“የመንግስት ባለስልጣኖችም ለኢሳት ቃለምልልስ ሰጥተዋል” ባይ ነው!) “ኢሳት” በኢትዮጵያ መንግስት በአሸባሪነት ከፈረጃቸው ድርጅቶች አንዱ በሆነው ግንቦት 7 ድጋፍ የሚንቀሳቀስ እንደሆነ በዶክመንተሪው ላይ ቢገለጽም ሰማያዊ ፓርቲ ግን አጣጥሎታል (ውሃ አያነሳም ብሎ!) አሸባሪዎችን የመፈረጅ ብቸኛ ስልጣን ያለው የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው ያለው ፓርቲው፤ “እስካሁን ም/ቤቱ በአሸባሪነት ስላልፈረጀው በጣቢያው ቃለምልልስ ማድረጌን፣ ፕሮግራሜን ማስተዋወቄን፣ የአባላቶቼን ቁጥር ማሳደጌን እቀጥላለሁ” ብሏል፡፡ (በቁርጠኝነት!) ይሄውላችሁ… “መጥራት” የሚያስፈልገው “ብዥታ” ማለት እንዲህ ያለው ነው፡፡

“ኢሳት አሸባሪ ነው አይደለም?” የሚለው “ያልጠራ ብዥታ” በመሆኑ የውዝግብ መነሻ ሆኗል፡፡ እኔ የምላችሁ…በዶክመንታሪው እንደተገለፀው በኢሳት ቃለምልልስ ማድረግ ከአሸባሪ ጋር እንደመተባበር የሚቆጠር ከሆነ፣ ኢሳትን መመልከትስ? ይሄን ለመግለጽ ሌላ ዶክመንታሪ መስራት የሚያስፈልግ አይመስለኝም፡፡ በአጭሩና በግልጽ መናገር በቂ ነው፡፡ (ህጉን ተከትሎ ማለቴ ነው!) አሁን ደግሞ ወደ ሌሎች ብዥታዎች እንለፍ። “አዲስ ዘመን” ጋዜጣ ባለፈው ረቡዕ በፊት ለፊት ገፁ ላይ ያወጣውን ዜና አይታችሁልኛል? “መጽሔቶቹ በብዙ ባህሪያቸው የጽንፈኛ ፖለቲካ ፓርቲ ልሳናት ሆነዋል” ይላል፤ የጥናት ሰነድ በመጥቀስ የወጣው ዘገባ፡፡ ጥናቱን ያሰሩት የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደሆኑ የገለፀው ዘገባው፤ ጥናቱ የተካሄደው በሰባት የግል መጽሔቶች ላይ መሆኑን በመጠቆም ዘርዝሯቸዋል፡፡ ይሄን የጥናት ሪፖርት ያመጣሁት መጥራት ባለባቸው በርካታ “ብዥታዎች” የተሞላ በመሆኑ እንጂ በሌላ አይደለም፡፡

(ፖለቲካዊ አቋም ልይዝበት እንዳይመስላችሁ!) እንግዲህ ሁለቱ የመንግስት ተቋማት ከመስከረም እስከ ህዳር መጨረሻ ድረስ (ለ3 ወራት ማለት ነው!) ስለመጽሔቶቹ እንዲጠናላቸው የፈለጉት ምን መሰላችሁ? መጽሔቶቹ በህትመቶቻቸው ያነሷቸው ስድስት ርዕሰ ጉዳዮችን ነው፡፡ (ማን ይሆን ያጠናው?) በሌላ አነጋገር የአዝማሚያ ጥናቱ ዋና ዋና ግኝቶች ያተኮሩት… ሀ) የመንግስት ኃላፊዎችን የግል ስብዕና የሚነኩ ለ) የአመጽ ጥሪዎችን የሚጠሩ ሐ) ሽብርተኝነትን የሚያበረታቱ መ) የፖለቲካ ስርዓቱን የሚያጨልሙ ሠ) የኢኮኖሚ ዕድገቱን የሚክዱ ረ) ህገመንግስቱን የሚያጣጥሉ… በሚሉት ዙሪያ ነው፡፡ እናም እነዚህን ሲያጠኑና ሲያስተነትኑ ቆይተው ነው “መጽሔቶቹ በብዙ ባህሪያቸው የጽንፈኛ ፖለቲካ ፓርቲ ልሳናት ሆነዋል” የሚለው ድምዳሜ ላይ የደረሱት፡፡

(አይ “ብዥታ”!) በመጀመሪያ ደረጃ እኔ ይሄን ጉዳይ ያነሳሁበት ምክንያት አንዳችም “ብዥታ” እንዲፈጥር አልፈልግም፡፡ (ብዥታን ለማጥራት ብዥታ መፍጠር ተገቢ አይደለም!) እናም… የፕሬስ ድርጅትና ኢዜአ ለሶስት ወር ውድ ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን ሰውተውና ከስክሰው የግል ፕሬሱ ላይ (ጋዜጦችን ባይመለክትም!) ጥናት በማድረጋቸው ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ (ምስጋናው ጥናቱ ፋይዳ እንዳለው አይጠቁምም!) በነገራችሁ ላይ የመጽሔቶቹ አዘጋጆችና ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ የጥናት ሪፖርቱን በጽኑ ተቃውመውታል፡፡ (አደራ አንተስ እንዳትሉኝ!) የእኔ ዓላማ ለጊዜው ብዥታዎችን መንቀስ ብቻ ነው፡፡ በጥናቱ ውስጥ ሳይገቡኝ ዝም ብለው የገረሙኝ በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ መጥቀስ ሳይኖርብኝ አይቀርም፡፡ ከአመጽና ሽብርተኝነት ጋር የተያያዙትን ትቼ ገራገሮቹን ብቻ አነሳለሁ፡፡ (ብዥታን ለማስቀረት እኮ ነው!) አሁን ለምሳሌ “የኢኮኖሚ ዕድገቱን የሚክዱ ዘገባዎች” የሚለው ነገር አሁንም ድረስ (ሳምንት ሙሉ ማለት ነው!) ይገርመኛል እንጂ ፈጽሞ ሊገባኝ አልቻለም፡፡ (በብዥታ የተሞላ ነዋ!) መንግስት ባለሁለት ዲጂት የኢኮኖሚ እድገት አስመዝግቤአለሁ ሲል ቆይቷል፡፡ መጽሔቶቹ ደግሞ ይሄ የመንግስት ቃል አላሳመናቸውም (ዕድገትን በቃል ማሳመን ከባድ ነው!) እናም ዕድገት የለም ብለው ፃፉ፤ ዘገቡ፡፡ ምንድነው ችግሩ? ያላመኑበትን መግለጽ ሃጢያት ወይም ክህደት ሊሆን አይችልም፡፡

(“ዕድገቱን በግድ እመኑ” ይባላል እንዴ?!) ለዚህ እኮ መድሃኒቱ ሌላ ሳይሆን አለ የተባለውን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ወዳላመኑት ወገኖች ማዳረስ ነው፡፡ ( “ሳያዩ የሚያምኑ ብፁአን ናቸው” ለዕድገት አይሰራም!) እናም… የግል ሚዲያዎች መንግስት የሚገልፀውን የኢኮኖሚ ዕድገት አልተቀበሉም ማለት ሌላ አንደምታ ያለው ነው የመሰለኝ (በጥናቱ መሰረት!) አንደምታው በግልጽ ይነገረን። ይከሰሳሉ? በአሸባሪነት ይፈረጃሉ? ይዘጋሉ? ወይስ ምን? መጥራት ያለበት “ብዥታ” ነው። በዚህ ጥናት ውስጥ ሌላው ሳይገባኝ የገረመኝ ደግሞ “የፖለቲካ ስርዓቱን የሚያጨልሙ” በሚል የቀረበው ነው፡፡ ያጨለሙት በብዕር ነው በትጥቅ ትግል? በመፃፍ ነው ጦርነት በመክፈት? በሃሳብ ነው በሃይል? ነገርዬው አልጠራም!! በነገራችሁ ላይ የፕሬስ ድርጅትና ኢዜአ ይሄ ጉዳይ እንዴት እንዳሳሰባቸውና የጥናት ትኩረት እንዳደረጉት ፈጽሞ አልገባኝም፡፡ የግል መጽሔቶቹ የፖለቲካ ስርዓቱን “አጨልመውታል” ብለው ካሰቡ እኮ እነሱም በሚዲያቸው “ማፍካት” ይችላሉ፡፡ (የሚዲያ ችግር የለባቸውማ!) ከሁሉም ግን የጠጠረብኝና በ“ብዥታ” የተሞላው የቱ መሰላችሁ? ሁሉም መጽሔቶች የጋራ የመረጃ ምንጮች ይከተላሉ ተብሎ “የኒኦሊበራል አክራሪ ኃይሎች፣ ድርጅቶች፣ ተቋማትና ግለሰቦች…” በሚል የተጠቀሰው ነው፡፡

እውነቴን እኮ ነው… ይሄ ኒኦሊበራል የሚለው ነገር ላይ ፈጽሞ የተግባባን አይመስለኝም። ከቃሉ ፍቺ ውጭ የተሰጠው አዲስ ብያኔ ካለ ይነገረን እንጂ አልሆነም፡፡ (እንደ ባቢሎን ግንብ ሆንን እኮ!) እኔማ ምን አስብ ነበር መሰላችሁ? ኢህአዴግ የኒኦሊበራል ኃይሎች ምናምን ሲል…ከተቃዋሚዎች ጋር ለመበሻሸቂያ እንጂ የምሩን አይመስለኝም ነበር፡፡ (በጥናት ውጤቱ ተገለጠልኝ!) እናላችሁ የኒኦሊበራል ሃይሎች አሸባሪ ተብለው ተፈርጀው እንደሆነ በግልጽ ይነገረን (ብዥታው እንዲጠራ!) በነገራችሁ ላይ… የጥናት ውጤቱ በመጽሔቶቹ ላይ የደረሰበት ድምዳሜም እኮ “ብዥታ” የሞላበት ነው፡፡ “መጽሔቶቹ በብዙ ባህሪያቸው የጽንፈኛ ፖለቲካ ፓርቲ ልሳናት ሆነዋል” ይላል፡፡ ምን ማለት ነው? ለማንኛውም ግን በኢህአዴግ ሳቢያ የሚፈጠሩ በርካታ “ብዥታዎች” በጊዜ ካልጠሩ ለአደጋ ያጋልጡናል (ጐጂ ልማድም ናቸው!) እኔም እንግዲህ የበኩሌን አንዲት “ብዥታ” ጣል አድርጌ ልሰናበት፡፡ (ለሙከራ ያህል እኮ ነው!) “የመንግስት ሚዲያዎች በብዙ ባህሪያቸው የአውራው ፓርቲ ልሳናት ሆነዋል” (ለአቅመ “ብዥታ” በቅቶ ይሆን?)

Saturday, 18 January 2014 11:44

የሦስት ፎቅ ሰማይ

           “ሳምሶን ወደ ጥንቅሹ እንዴት ተቀየረ?” ሳምሶንን ድሮ ለሚያውቁት ሁሉ አስገራሚ ጥያቄ ነው፡፡ እንደ ሳምሶን አይነት ከይሲ …. ቂጡን በእግሩ የጠረገ ዱርዬ …. አንገቱን የሰበረውን፣ ሰው ቀና ብሎ የማያየውን … ከቤቱ የማይወጣውን ጥንቅሹን እንዴት በቅጽበት ሆነ? መልሱ ሳይሆን ጥያቄው ነው አስገራሚ፡፡ መልሱማ፤ ግልጽ ነው፡፡ ጌታን አገኘ ወይንም ጌታ አገኘው፡፡ ፀጉሩን ላጭቶ እማኝ አደረገው፡፡ ልቡን እና ትዕቢቱን ሰበረለት፡፡ ጌታ ጥንቅሹን፣ፍልስጤማዊያኑ ሳምሶንን በእጃቸው ያስገቡበት መንገድ አንድ ነው፡፡ መንገዱ ሴት ናት፡፡ ደሊላ፡፡

ጥንቅሹን ግን ለጌታ አሳልፋ የሰጠችው የኤሮናዛ ፋርማሲ ባለቤት ናት፡፡ ወደ ፋርማሲው የሄደው ኮንዶም ለመግዛት ነበር፡፡ ፋርማሲስቷን ሲያይ ሌላ በሽታ ያዘው፡፡ መድሐኒት ሻጯን እንደ መድሐኒት መዋጥ ፈለገ፡፡ ከእነ ሁሉ ነገሯ፤ ከእነ ወጣትነቷ፣ ከእነ መድሐኒት መደብሯ፣ መድሐኒት መደብሩ ደጃፍ ከነአቆመችው መኪና…እሷን ከነሁሉ ነገሯ ቢውጥ ህይወቱን የመታው የእጦት ደዌ እንደሚፈወስ አመነ፡፡ እሷን ለመዋጥ ግን መጀመሪያ በእሷ መዋጥ እንዳለበት አውቋል። ግን የሚዋጥ ነገር የለውም፡፡ ከይሲ ነው፣ ቂጡን በእግሩ የጠረገ ዱርዬ፡፡

ኮንዶም መግዛቱን ትቶ የባጥ የቆጡን አወራላት፡፡ መጥበሱ ነው በሱ ቤት፡፡ ያወራላት ነገር ለእሥረኛ የሚበቃ በመሆኑ መረቧን ጣለችበት፡፡ ወደ ቤተክርስቲያኗ የእግዚአብሔርን ቃል እንዲሰማ ጋበዘችው፡፡ ግብዣዋን ተቀብሎ ሊወጣ ሲል በህክምና ሳሙና በታጠበ እጇ ጨበጠችው፡፡ ወደ ተጋበዘበት ጉባኤው ሲገባ ጀምሮ ሳምሶንነቱ አጠረው፡፡ እውነተኛ ስሙን ለመናገር አፈረ፡፡ ስሙን ስትጠይቀው “ጥንቅሹ” አላት። እውነተኛ ስሙን በደንብ ከተግባቡ በኋላ ሲገልጽላትም መጀመሪያ የተነገራትን ይዛ ቀረች፡፡ ጥሪዋን አልለውጥ አለች፡፡ የዋጠችው በፍጥነት ነው፡፡ ከተዋወቁበት እለት ወደ ቤተክርስቲያኗ እስክትጋብዘው በመሃል ተለያይተው ከቆዩበት ጥቂት ቀናት በስተቀር ግንኙነታችሁ በየእለቱ እንዲሆን አደረገች፡፡ ወደ ሳምሶንነት የሚመለስባቸውን መንገዶች ነፈገችው፡፡ በሦስተኛው ወር አጋማሽ ላይ ከአባቷ ጋር አስተዋወቀችው፡፡ ወደ ወላጆቹዋ ቤት ወስዳ ከአባትና ከእናቷ ፊት ፈትታ ለቀቀችው፡፡ አባት እና እናትየው በዛ እለት የተዋወቁት ጥንቅሹን ብቻ ሳይሆን የታናሽዋይቱን ልጃቸውንም እጮኛ (እስረኛ) ነው፡፡ ታላቂቱ ጥንቅሹን፣ ታናሽቱ ለምቦጫሙን አጥምደው ወላጆቻቸው ፊት ፈትተው ለቀቁዋቸው፡፡ አባትየው ተይዘው የመጡትን ሁለት ወንድ በጐች ወገባቸውን ጨበጥ ጨበጥ እንደማድረግ በተለያዩ የአይን እና የንግግር መመዘኛዎች ለኳቸው፡፡ ጥርስ መሽረፍ እና አለመሽረፋቸውን አረጋገጡ፡፡ እኛም ወደናል ይሁን አሉ፡፡

የጥንቅሹ እጮኛ ወላጆች የሚኖሩት ፎቅ ቤት ሰርተው ነው፡፡ የቤቱ ሶስተኛው ፎቅ ላይ አባትና እናት፣ ሁለተኛው ፎቅ ላይ ኤልሻዳይ/የጥንቅሹ እጮኛ/፣ አንደኛው ፎቅ ላይ ህይወት (የመጨረሻ ልጃቸው) ይኖራሉ፡፡ ከትውውቁ በኋላ ጥንቅሹ ሁለተኛው ፎቅ ላይ ከኤልሻዳይ ጋር መኖር ጀመረ፡፡ በዘመቻ ፍጥነት ህይወትም ለምቦጫሙን አስገብታ መኖር ጀምራለች፡፡ ለምቦጫሙ የክርስቲያን ግንባር ነው ያለው፡፡ ስሙ ግንባሩን አይመስልም፡፡ “አቡ” ብለው የእጮኛው ወላጆች ጠሩት። የሴቶቹ ወላጆች ወንዶቹን የሚጠሩት በመጥሪያ ነው፡፡ ሶስተኛ ፎቅ ሞቅ ካለው ሳሎን ቤት ውስጥ ያለውን የመጥሪያ ደወል ለአንደኛው ወይም ሁለተኛ ፎቅ አነጣጥረው ይደውላሉ፡፡ በተነጣጠረው ደወል የተመታ ምላሽ ለመስጠት ወደ ሶስተኛ ፎቅ ይሮጣል፡፡ የፎቁ ምድር ቤት ለአገልግሎት ሰጪ ሠራተኞች የተዘጋጀ ነው፡፡ ሦስተኛ ፎቅ ሁለተኛ እና አንደኛ ፎቅን ያዝዛል፡፡ ሁለት እና አንድ ደግሞ ምድር ቤትን ያዛሉ፡፡ ምድር ቤቱ ውስጥ ብዙ አይነት አገልግሎት ሰጪዎች አንድ አንድ ክፍል ተሰጥቷቸው ይኖራሉ፡፡ ምግብ የሚቀቅሉ፣ የሚያፀዱ፣ ጥበቃ የሚሰሩ፣ አትክልት የሚቆፍሩ …ወዘተ፡፡

የሰራተኞቹ ብዛት እንደሁኔታው በአምስት እና አሥር መሃል ከፍ ዝቅ ይላል፡፡ የጋብቻ ሥነ ሥርዓቱ የታቀደው በወላጆቹ ነው። ከሦስተኛ ፎቅ እቅዱ ወደ ተግባር የተቀየረው በሁለቱ ሴት ልጆች፡፡ ሴቶቹ ልጆች ለራሳቸው ሰርግ ሚዜ ነበሩ፡፡ ወንዶቹ፤ ጥንቅሹ እና አቡበከር ለኩ የተባሉትን ሱፍ መለካት…ቁሙ በተባሉበት ቦታ መቆም ብቻ ነው የሚጠበቅባቸው፡፡ አድርጉ የተባሉትን እስካደረጉ ድረስ፣ የሚስቶቻቸው ወላጆች በእነሱ ደስተኛ ይሆናሉ፡፡ ወላጆች ህግ አውጪ ናቸው፣ ሚስቶች ህግ አስፈጻሚ ናቸው …ባሎች ህግ ተወጪ፡፡ ጥንቅሹ ለሰርጉ ዕለት የሚጠራቸውን ዘመዶቹን በጥንቃቄ በማጥናት የይለፍ ካርድ የሰጡት አባትየው ናቸው፡፡ ከሶስተኛ ፎቅ ሆነው በየዕለቱ ማታ ማታ፤ ልጆች የወላጆችን እግር የማጠብ ሥነ ሥርዓት ያከናውናሉ፡፡ ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጠበበትን ሥነ ሥርዓት ለማስታወስ፡፡ ወንዶቹ ልጆች የሴቶቹን ወላጆች እግር ያጥባሉ፡፡ አንዱ የአባትን፣ ሌላው የእናትን፡፡ ጥንቅሹ የአባትን እግር የማጠብ ተራ ሲደርሰው ደረቱን የሚያፍን ስሜት ይሰማዋል፡፡ አስም ስለጀመረው መድሐኒት እንድትፈልግለት ለሚስቱ ኤልሻዳይ ነግሮአት ነበር፡፡ አፈናው በመድሃኒት እንደማይቆም ግን ቀልቡ ነግሮታል፡፡ ሴቶቹ ልጆች ደግሞ በተዋረድ የባሎቻቸውን እግር በወላጆቻቸው ፊት ያጥባሉ፡፡

በየምሽቱ ተሰናብተው ወደ ራሳቸው መኖሪያ እንደ ደረጃቸው ሲወርዱ እና በፎቅ ፎቃቸው ሲከተቱ፣ ባሎች የሚስቶቻቸውን ጀርባ ያሻሉ፡፡ የሰርጉ እለት ጥንቅሹ ቀኑን ሙሉ ፈዞ ከዋለበት ድንገት ነቅቶ መለፍለፍ ማብዛቱ፣ በእስክስታ በጉባኤ መሃል የመግባቱ ሚስጥር የታወቀው ምንጣፉ ላይ ከማስመለሱ ጥቂት ቀደም ብሎ ነበር፡፡ መጠጥ ከየት እንዳገኘ ማንም ማስረዳት አልቻለም፡፡ ኤልሻዳይ የክርስቶስን ስም እየጠራች ስጋ ለባሽ ስድቦች ስትሰድበው ማንም አፏን ለማስጣል አልሞከረም፡፡ የሰርጉ ቀን አለፈ፡፡ ጥንቅሹም ተኝቶ ስካሩን አሳለፈ። ሲሰክር ሳምሶምነት ይጠናወተዋል፡፡ በሰርጉ እለት አባትየው ለሙሽሮች ለማበርከት ያቀዱትን ስጦታ ለጥንቅሹ እና ለ “አቡ” የሰጠዋቸው ቆየት ብለው ነው፡፡ ግምገማ እና ተግሳፅ መቅደም ስለበረበት፡፡ የሰርጉ ቀን ካለፈ ሁለት ሳምንት በኋላ የእግር ማጠብ ሥነ ሥርዓቱም በአዲስ መልክ ተጀመረ፡፡ ወላጆች ለሁለት ሳምንት ልጆቻቸውን እና ባሎቻቸውን አጣምረው አኮረፉ፡፡ ከሶስተኛ ፎቅ ላይ ሆነው፡፡ ስጦታው ለሙሽሮች በሚበረከትበት ቀን፤ ከማለዳ እስከ ቀትር የምክር እና የፀሎት ፕሮግራም በቅድሚያ ተካሂዷል፡፡ እጅ በጥንቅሹ ላይ ተጭኖ ተፀለየለት፡፡

ሳምሶም በኢየሱስ ስም እንዲባረር ሆነ፡፡ የአባትየውን እግር ሲያጥብ ብቻ ሳይሆን የአባትየው እጅ ሲጫንበትም ጥንቅሹን ያፍነዋል፡፡ የአባትየው ትንፋሽ ያለበት ቦታ የአስሙ ምክንያት እንደሆነ መቀበል ግን አልደፈረም፡፡ አስሙ ለቀቅ እያደረገው የመጣው ስጦታው ይፋ ሲሆን ነው፡፡ የጠበቀው ስጦታ ቤት ቢሆንም መኪናም ግን የሚያስከፋ አይደለም፡፡ ቢያንስ አስሙ ሲነሳበት ሞተር አስነስቶ ወደ ሶደሬ፣ ላንጋኖ ሊሄድ ይችላል፡፡ ከኤልሻዳይ ጠባብ ሱሪ እያፈነገጠ እንደ ጡት ብቅ የሚለው መቀመጫዋ ሲያቅለሸልሸው… የተስተካከለ የሰውነት ገበያ ወዳለባቸው ክለቦች በመኪና ሊደርስ ይችላል፡፡ መኪና ራሱ የሚንቀሳቀስ ቤት ነው፡፡ ወጣት ልጃገረዶች ሊፍት ሰጥቶ ዛፍ ጥላ ስር ሆኖ መጨዋወት አያቅተውም፡፡ ስጦታውን ሲያይ ያፈነው አስም ከደረቱ ወጥቶ እንደ ጉም በነነ፣ ንጹህ ትንፋሽ ሳንባው ያገኝ ጀመረ፡፡ ጥሩ ትንፋሽ ሳንባ ሲያገኝ፣ ጥሩ ደም ልቡን ነዘረው…. እንደ ጥንቱ ጥሩ ጥሩ ሃሣብ አእምሮው ውስጥ ተፍታታ፡፡ ሶምሶንነቱ ከተላጨው ጸጉር ውስጥ እንደ አዲስ ሽፍ ብሎ ሲበቅል ተሰማው፡፡ የሰርጉን ስጦታ ለማየት ባይችልም ዘመናዊ እና አዲስ መኪና መሆኑን አምኖ፣ በልበ ሙሉነት ወደ አልጋው ሄደ፡፡ የሚስቱን ኤልሻዳይን ጀርባ ሲያሽ… እንደ ቀድሞው በትህትና አልነበረም፡፡

በአፉ ጥንቅሹን ሆኖ ቢያወራም… በአስተሳሰቡ እና አኳኋኑ ግን ሳምሶምን ሆኗል፡፡ ኤልሻዳይ እየሰባበረ ከሚያሻት የባሏ መዳፍ ጋር ድምጿ እየተሰባበረ፣ የተገዛለት መኪና ምን አይነት እንደሆነች ነገረችው። ቀለሟንም በአፉዋ ቢጫ አድርጋ ቀባቻት፡፡ ማፈኑ እንዳይጀምረው ቢፈራም ለአስም እጁን አልሰጠም። አቶዝ የሴት መኪና ብትመስልም መኪና ናት፣ ቤንዚን መስጫውን እንደ ወንድ አድርጐ ከረገጠው ልታርቀው ትችላለች፡፡ ቀለሟ ቢጫ ቢሆንም እሱ ከውስጡ ሆኖ እስከ ነዳት ድረስ ውጪው አይታየውም፡፡ ከውጭ ሆነው የሚያዩዋት ሴቶች ስለሆኑ እንዲያውም ትስባቸዋለች፣ ብሎ ተጽናና፡፡ የሳምሶን ጸጉር በውስጡ አያደገ ሲመጣ ተሰማው፤ መጠጥ አማረው፡፡ ግን መኪናው እጁ እስክትገባ መታገስ አለበት፡፡ አቡ የተሰጠው መኪናም ከእሱ ጋር ተመሳሳይ አንደሆነ ኤልሻዳይ ታሽታ ከመጨረሷ በፊት ለባሏ አጫወተችው፡፡ በቀለምም ሆነ በብራንድ የእሱ እና የሚስቱ እህት ባል መኪኖች አንድ ናቸው፡፡ የታርጋ ቁጥር ነው የሚለያቸው፡፡ ከስም ታርጋ ልዩነት በስተቀር ተመሳሳይ እህቶች… አንዳገቡት፡፡ ተመሳሳይ መኪና ለባሎቻቸውም አባትየው ገዝተውላቸዋል፡፡

አባትየው ወንዶቹን ባሎች ከሴት ልጆቻቸው ሚስትነት አስበልጠውም ሆነ ለይተው ማየት አይፈልጉም፡፡ በእግዜር ፊት ሁሉም እኩል እንደሆነ፣ አባትየው ፊትም ልጆቻቸው እና ባሎቻቸው እኩል ናቸው፡፡ አባትየው ራሳቸውን የባለ ሦስት ፎቅ እግዜር አድርገው መቁጠራቸው ተገልጾላቸው የሚያውቅ አይመስልም፡፡ ጥንቅሹ በጠዋት ተነስቶ የመኪናውን ቁልፍ ሲፈልግ ኤልሻዳይ ወደ ፋርማሲዋ ለመሄድ እየተሰናዳች ነበር፡፡ ቁልፉ በአባቷ እጅ እንዳለ ነግራው ወጣች፡፡ በደወል ሳይጠራ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሶስተኛ ፎቅ ሮጠ፡፡ የእየሱስን ስም በእየ አረፍተ ነገሩ መሀል እየቀቡ ዳቦአቸውን በማርማላት ሲነክሩ ደረሰባቸው፡፡ አባትየው የበኩር ልጃቸውን ባል ግንባሩን ከሳሙት በኋላ፣ አብሮአቸው ቁርስ ለማድረግ ተቀመጠ፡፡ በብዙ ማባበል ቁልፉን እና መኪናዋ የት እንደሚገኙ ጠየቃቸው፡፡ መኪናዋ ግቢ ውስጥ መሆንዋን፤ ቁልፉ ግን የሚሰጠው ለምን ጉዳይ እንደሚሄድ፣ ምን ያህል ርቀት እንደሚሄድ እና መቼ እንደሚመለስ አስመዝግቦ መሆኑን አንደተራ ነገር ገለፁለት፡፡ ለዚሁ አገልግሎት ያዘጋጁትን ዶሴ መሰል ነገር አወጡ፡፡ በተዘረዘረው ተራ ቁጥር መሰረት መሄድ የፈለገበትን እንዲሞላ ጠየቁት፡፡ የተጠየቀውን ሞላ፡፡ አንድ አልባሌ ቦታ፡፡ ከእሱ ፍላጐት በጣመ የራቀ፣ ወደ አባትየው ፍላጐት በጣም የቀረበ ቦታ፡፡ ሱፐር ማርኬት፡፡ የሱፐር ማርኬቱን ስም ጠይቀው አሁንም አስሞሉት። ከባለሶስቱ ፎቅ እስከ ሱፐር ማርኬቱ ያለውን የደርሶ መልስ ርቀት አስልተው የቤንዚን ብር ወደሱ ዘረጉ። እያስጨበጡት አንድ ተጨማሪ ህግ ነገሩት፡፡

ከእንግዲህ የወላጅነት ድርሻን መወጣት ላይ ስለሆነክ የገንዘብ አወጣጥህ ላይ ጥንቃቄ ያስፈልጋል፤ ስለዚህ ኤልሻዳይ ፋርማሲ ሸጣ ከምታመጣው ትርፍ የምትሰጥህን ገንዘብ እኔ እየተቀበልኩ ልቆጥብልህ ወስኛለሁ፡፡ ገንዘብ ስትፈልግ እኔን ትጠይቀኛለህ፣ እኔም ጥያቄህን መርምሬ፣ ተገቢ ሆኖ ካገኘሁት፤ የጠየቅኸኝን አሟላለሁ፤ ህይወት በኘሮግራም መመራት አለበት፤ ትላንት ሳልሰጥህ የረሳሁት ነገር አለ፤ ብለው፤ ከጠረዼዛው ላይ ትራስ የሚያህል በላስቲክ የተቋጠረ ነገር አንስተው አቀበሉት፡፡ ለክተህ አሳየኝ አሉት፡፡ ደረጃውን እየወረደ ፌስታሉን ፈትቶ ተመለከተው፡፡ ብርቱካን አይነት ቲሸርት አና አረንጓዴ ቦላሌ የመሰለ ቁምጣ ከፌስታሉ ውስጥ ተከታትለው ተመዘዙ፡፡ ከቲሸርቱ እና ቁምጣው ስር ቢጫ የኤርጌንዶ ነጠላ ጫማ አለ፡፡ እንደ አዲስ ጐማ ይከረክራል፡፡ ወደ ሁለተኛ ፎቁ ገብቶ ልብሱን አውልቆ፣ ከአባትየው የተሰጠውን አጠለቀው፡፡ አያጐጠጐጠ ያለ ሳምሶምነቱ በቅጽበት ከለበሰው ቲሸርት፣ ቦላሌ እና ኤርገንዶ ጋር ረገፈ፡፡ ሲረግፍ ሁለተኛ እንደማይበቅል ሆኖ ነው፡፡ ከልብሱ ጋር የማይወልቅ ማንነቱ ጥንቅሽነቱን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አረጋገጠና ጸና፡፡ ከዚህ ቀደም የሚስቱን እህት ህይወትን እና ባሏን በልቡ ይጠላቸው ነበር፡፡ ኤርገንዶውን ሲጫማ ድንገት ወደዳቸው፡፡ የሚስቱን ባል “አቡ”ን በአዲስ መልክ ለመተዋወቅ፣ ሰላም ለማለት ወደ አንደኛ ፎቅ ቁልቁል ተንደረደረ፡፡ አቡም፤ ወደ ላይ ወደ አባትየው እየተንደረደረ መሀል መንገድ ተገናኙ፡፡ በግጭቱ ውስጥ ተቃቀፉ፡፡ አቡም ብርቱካን አይነት ቲሸርት በአረንጓዴ ቦላሌ አጥልቋል፡፡ ቢጫ ኤርገንዶውን ገርግዷል፡፡ ጫማው ትንሽ ሰፍቶታል፡፡ የአባትየውን ፈቃድ መሙላት ስላለበት ግን ቢሰፋውም ራሱን አሳድጐ የሰፋውን ጫማ ይሞላል፡፡ አቡ አመጹን ካስወገደ ቆይቷል፡፡ ወደ ሶስተኛው ፎቅ አብረው ከጥንቅሹ ጋር ተንደረደሩ፡፡

አባትየው የገዙላቸውን ልብስ ለማስመረቅ፡፡ እደጉ ለመባል፡፡ ጥንቅሹ እና አቡ በተመሳሳይ ጊዜ ውስጥ ከተመሳሳይ ሚስቶቻቸው ተመሳሳይ ሴት ልጆች ወለዱ፡፡ በተመሳሳይ ቀን፣ከሦስተኛው ፎቅ በተሰጣቸው ትዕዛዝ፡፡ በተመሳሳይ ጊዜ ክርስትና አስነሱ፡፡ ሴት ልጆቻቸው ሲያድጉ፣ አባትየው በፎቅ ቤቱ ላይ ሁለት ደረጃ ለመጨመር ይገደዳሉ፡፡ የልጅ ልጆቻቸው ባል ይዘው ለመምጣት ሲደርሱ የሚገቡበትን ስፍራ ለማመቻቸት፣ እሳቸው ወደ አምስተኛ ደረጃ ወጥተው አራቱን ከላይ ሆነው ያስተዳድራሉ፡፡ የፎቅ ቤቱን ደረጃ ከፍ ከማድረግ በተረፈ ሁለት ተጨማሪ ፋርማሲዎች ይከፍታሉ፡፡ ለሴቶቹ ልጅ ልጆቻቸው፡፡ ፋርማሲ ውስጥ እንደ ሸረሪት ድር ሰርተው የታመሙ ሰዎችን ያክማሉ… ከታመሙት መሀል አንድ አጥምደው ወደ አያቶቻቸው ዘንድ ወስደው ያስተዋውቃሉ፡፡ ፈቃድ ሲያገኙ ያገባሉ። የልጅ ልጆቻቸውን ህይወትም ለማስተዳደር የሚበቃ እድሜ አና አቅም በውስጣቸው አንዳለ ሰውየው እርግጠኛ ናቸው፡፡ በፊት ባል የነበሩት፣ በኋላ አባት፣ ቀጥለው አያት የሆኑት የሶስተኛ ፎቁ አምላክ፣ እርግጠኛ ናቸው፡፡ በአያትየው አይን ሁሉም የቤተሰቡ አባል እኩል ነው፡፡ ሁሉም ሴት ልጆቻቸው ናቸው፡፡

Published in ልብ-ወለድ
Page 6 of 14