Saturday, 16 March 2024 19:54

የባህር-ዳርቻ ወፍና የባህር አሣ ሲታገሉ አሣ አጥማጅ ይጠቀማል

Written by 
Rate this item
(7 votes)

 ከሊዮ ቶልስይ ተረቶች ውስጥ እንዲህ የሚል ይገኝበታል።
አንድ ንሥር በዛፍ ላይ ጎጆትሠራለች። እዚያ ውስጥ ጫጩት ትፈለፍላች። አንዲት አሣማ ደግሞ ግልገሎቿን ይዛ ዛፉ ሥር ትመጣለች። ንሥሩዋ ሩቅ በርራ አድን  ልጆቿን ትቀልባለች። አሣማዋ ዛፉ ሥር እየኖረች እጫካው ውስጥ እየገባች እያደነች ውላ ማታ ለልጆቿ ምግብ ታመጣላቸዋለች። በዚህ ዓይነት ንሥርና አሣማ እንደ ጥሩ ጎረቤት እየተማመኑ፣ እየተዋረዱ፣ አንዳቸው ባንዳቸው ላይ ክፉ ላያስ ተስማምተው መኖራቸውን ቀጥላ። በመሰረቱ ንሥርና አሳማ ባንዳቸው ላይ ክፉ ላያስቡ ተስማምተው መኖራቸውን ይቀጥላሉ። በመሠረቱ ንሥርና አሣማ በተፈጥሯቸው አንዳቸው ያንዳቸውን ግልገል ካገኙ የማይምሩ ተፃራሪ ፀባይ ያላቸውና ሊጠፋፉ የሚችሉ ናቸው። አንድ ቀን አንዲት አሮጊት ድመት ወደ ሁለተሩ ሰፈር መጣች። የንስሯንም ጫጩቶች ጡት የሚጠቡትንም የአሳማዋን ግልገሎች፣ ልትበላቸው አሰበች።
ወደ ንሥሯ ሄዳ፤
“ንሥር ሆይ! ለምግና ለአደን ብለሽ ከእንግዲህ ሩቅ መንገድ እንዳትሄጂ። ይቺ አሣማ የምትተኛሽ አይምሰልሽ። መጥፎ ተንኮል እያሰበችብሽ ነው። የዛፉን ሥር እየበጣጠሰችው ነው። እንደምታይው በየቀኑ የሥሩን አፈር እየማሰች ነው” አለቻት። ንስርም ስለምክሯ አመስግናት ተለያዩ
ቀጥላ ደግሞ ወደ አሳማዋ ዘንድ ሄዳ፤
“አሣማ ሆይ! ዘንድሮ ጥሩ ጎረቤት አልተዋጣልሽም። ትላንት ማታ ንሥሯ ለጫጭቶቿ እንዲህ ስትል ሰማኋት፡- ወዳጄ ስለሆንሽ ሆዴ አልችል ብኝ ልነግርሽ መጣሁ” አለች። አሣማም፤ “ምን አለችኝ እባክሽ?” ብላ በጉጉት ጠየቀች።
ድመትም፤ “ምን ስትል ሰማኋት መሰለሽ፡-” ‘ልጆቼ፤ ከእንግዲህ አትራቡም። እንዲያውም ጥሩ ጥሩ ግልገል አሣሞች እያመታሁ እቀልባችኋለሁ። አይዟችሁ፤ ይቺ አሳማ የምትኖርበት ድረስ መጥታ ግልገሎቿን መሬት ላይ አፍስሳልናለች። እናታቸው ራቅ ብላ ስትሄድ ቆንጆ ቆንጆ ግልገሎቿን እያመጣሁ አበላኋቸው’” አለች።
ከዚህ ቀን ጀምሮ ንስር ወደ ሩቅ ቦታ እየሄደች ማደኗን አቆመች።
አሳማዋም ከዚህ ቀን ጀምሮ ወደ ጫካ መሄዷን አቆመች።
የንስርም ቻጩቶች፣ የአሳማም ግልገሎች ከቀን ወደ ቀን ለረሃብ እየተጋለጡ ሄዱ። ውሎ አድሮ፤ የንስር ልጆች አንድ በአንድ ከዛፍ ላይ እየተፈነቸሩ ይወድቁ ጀመር። የአሳማም ግልገሎች እናታቸው ለመኖሪያ ወደማሰችው ጉድጓድ ውስጥ ሞተው ይገኙ ጀመር።
አሮጊቷ ድመት የሞቱትን ጫጩቶችና ግልገሎች እያፈራረቀች “ተመጣጠነ ምግብ ማለት ይሄ ነው!”፤ እየተመገበች፤ ፌሽታ ስታደርግ ከረመች።
ንስርና አሳማ ሲያለቅሱ ሰነበቱ።
***
 ከላይ ዛፍ ከታች መሬት ለመኖሪያ ካተመቸ አገር አማን አትሆንም።
የህዝቡ ኑሮ አስተማማኝ አይንም። በዜጎች መካከል መተማመን አይኖርም። አንድም ፍትሃዊት እየጠፋ “በጨው ደንደስ በርበሬ ተወደስ ይሆናል”። አንድም ደግሞ ቃልኪዳን ፈርሶ፣ የተደላደሉበት ተንሸራቶ “ያመኑት ፈረስ ጣለው በደንደስ” ይሆናል። ከላይ በተረቱ እንዳየነው፤ ተቻችለውና ተስማምተው ለመኖር የሚችሉትን በማቆር፤ እንጠቀማለን ለሚሉ አለመመቸት ተገቢ ነው።
እጅግ የከረሩ አቋሞች ሚያመጡትን ጉዳት አንዳንዴ ከህዝብና ከሀገር ጥቅም ጋር ማየት ተገቢ ነው። በፓርቲዎች ደረጃ ሲታሰብ የኔ ልማት የሌላው ጥፋት የሚል እሳቤ ብዙ አያራምድም። በአገርኛ አባባል፤ “ሞትሽ እውነት በሆነና ልጅሽን ማሳደጉ እኔ በቸገረኝ፤ አለች አሉት” እንደተባለው ማለት ነው።
በዓለም ላይ እንደታየው ብዙ ለሥልጣን ሚታገሉ የፖለቲካ ሃይሎች ሁኔታዎች በውጥረት ሲሞሉ ምክንያታዊ መሆናቸው እየላላ በአጭር ጊዜ መፍትሄ ላይ ይተማመናሉ።
ይኸውም በአብዛኛው ስሜታዊና ጉልበተኛነት የሞላ ሆኖ ነው የሚገኘው። ይሄ በፈንታው ሰላም ያሳጣናል። በሀገራችን በተካሄደው ምርጫ ህዝቡበነቂስ ቀጥቶ ድምጹን ለፈለገው ወኪሉ መስጠቱ ለዲሞክራሲዊ ጎዳና ጥርጊያውን የማመቻቸቱን ያህል፤ በቸልተኝነት በማንአለብኝም በሚሰሩ ስህተቶች መካከል ፍጻሜ እንዳናይ ከተደረግን፤ በዲሞክራሲያዊነት ስም ሀሳዊ- ዲሞክራሲ ይጫነናል።
አንድ ጸሐፊ ስለተሳትፎአዊ ዲሞክራሲ ሲጽፍ፤ “በጥረት ህዝብን ማሳተፍ የመቻሉን ያህል በጉልበት የተሳትፎውን ፍሬ መከልከል ከቶ አይቻልም” እንዳለው በሀገራችን ዲሞክራሲያዊ ንፍቀ-ክበብ እንዳይጨልም ማድረግ ወሳኝ ነገር ነው።
በየትኛውም መልኩ ሰላምንም፣ ዲሞክራሲንም ማጣት ሀገራችን ዛሬ ልትቋቋመው የማትችለው እዳ ነው። የተረገመን እግር፤ በቅሎም ጫማም ይነሳዋል እንደሚባለው ሲሆን ነው። ማለት ነው።
“ከቶውንም ትላንት የነበረውን ምርጫ ሆነ ፖለቲካዊ አካሄድ ዛሬ ለምንሰራው ስህተት፤ መሸፈኛ አልያም መጸጸቻ እስከመቼ ነው? ግትርነት፣ ጉልበትና ስሜታዊነት ባላንጣ ላይ ብቻ ሳይሆን የራስንም ወገን እንደሚያሳጣህ ቀደምት ጸሀፍት ይናገራሉ። ሸክስፒር እንዲህ ይጠይቀናል፡- “… እልህ እስከምን ይዘልቃል።”
የት ድረስ ነው ግትር ጽንፉ
በባላንጣ ሰበብ ምክንያት፣
የራሱን ወገን ማርገፉ?...”
ዲሞክራሲ ስንል በህዝብ መወከል፣ በፖለቲካ ጉልበት የሆነበት ግን የህዝብ ተአማኒ አገልጋይ የሚኮንበት አትበጀኝም ሲል ህዝብ በቃኸኝ፣ አትወክለኝም ሊል የሚችልበት፤ የሲቪልና የፖለቲካ መብት እንዲከበር የሚደረግበት፤ ህዝብ ህጋዊና ህገ-ወጥ የሆነውን ነገር በውል አውቆና መብቱን ተረድቶ ሊያስከብር የሚነሳበት መነሳቱን እንደወንጀል የሚቆጠርበት፣ የማይሰጥ-የማይነጠቅ ነጻነት የሚቀዳጅበት ማለት ነው።
ይህንን ስንልም ዲሞክራሲ ምሉዕ ይሆን ዘንድ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መብቶቹንም ያካተተ መሆኑን ከቶም ሳንዘነጋ ነው።
ወደ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ የሚያራምደንን ምርጫ አንድ እርምጃ ብለን ለመጓዝ የምርጫውን ዘላቂ ውጤት፣ የድጋሚ ምርቸውን ወሳኝ ቁጥርና አግባብ ያለው ቆጠራ እንዲኖር ታዛቢዎች እውነተኛ ውሳኔ፣ የስሞታዎች የተጣራ ውጤት ወዘተ ተደምረው ነው ፍሬ የሚገኘው፤ ሁሉም ተፎካካሪ ወገኖች ትልቁን የሀገር ስብእና ዘላቂውን የህዝብ ጥቅም ቀዳሚ አድርገው ካስተዋሉ ነው። አለበለዚያ ቻይናውያን እንደሚሉት “የባህር-ዳርቻ የወፍና የባህር አሣ ሲታገሉ አሣ-አጥማጅ አይቀማውም።”

Read 1030 times