Saturday, 23 June 2012 08:32

የአፄ ቴዎድሮስና የዓለማየሁ መፃህፍት በድጋሚ ታተሙ

Written by  መልካሙ ተክሌ (melkamutekele@gmail.com)
Rate this item
(0 votes)

በህንዳዊው መምህር ጆሴፍ ፍራንሲስ የተዘጋጁት “አፄ ቴዎድሮስ” እና “ዓለማየሁ ቴዎድሮስ የኢትዮጵያ ልኡል” የተሰኙ ሁለት መፃህፍት ለሁለተኛ ጊዜ የታተሙ ሲሆን በሚቀጥለው ሳምንት ለገበያ ይቀርባሉ፡፡ ሁለቱም መፃህፍት የመጀመርያ ዕትማቸው የወጣው የዛሬ አምስት ዓመት ሲሆን በወቅቱ የመፃህፍቱ ቅጂ አነስተኛ ስለነበረ አሁን ማሳተሙ አስፈልጎዋል ብሉዋል - ጆሴፍ ፍራንሲስ፡፡ መፃህፍቱ በተለይ ልጆችና ወጣቶች ስለአገራቸው ታሪክ እንዲያውቁ ታልመው የተዘጋጁ ሲሆኑ በእንግሊዝኛና በአማርኛ ቋንቋዎች የቀረቡ ናቸው፡፡

የመፃህፍቱ አዘጋጅ ጆሴፍ ፍራንሲስ በዓለማየሁ መፅሃፍ ምስጋና ላይ ባሰፈረው ማስታወሻ “የልኡል ዓለማየሁን አሳዛኝ ታሪክ የሚያብራሩ ምንም ሰነዶች በሌሉበት፤ በተለያዩ ገጠመኞች የተሞላውን የልኡሉን ሕይወት ለመተረክ መነሳቴን እጅግ ፈታኝ ሆኖ አግኝቼዋለሁ” ብሏል፡፡

በሁለቱም መፃህፍት ላይ የሰፈረውን የጀርባ አስተያየት (Blurb) የፃፉት ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት “አፄ ቴዎድሮስ” የተሰኘው መፅሃፍ ላይ በሰጡት ምስክርነት “ከኢትዮጵያ ታላላቅ ነገስታት አንዱ የሆኑት አፄ ቴዎድሮስ ከሀገሪቱ አስደናቂና ተወዳጅ መሪዎች አንዱ ናቸው ቢባል ተገቢ ነው፡፡ የማያጠያይቅ ጀግንነት ያላቸውና የዘመናዊ ሥልጣኔ አቀንቃኝነታቸው ልዩ የሚያደርጋቸው ንጉስ ናቸው፡፡ ጆሴፍ ፍራንሲስ ስለዚህ ስለ አፄ ቴዎድሮስ ፅሁፍ ሊደነቅ ይገባዋል” ሲሉ አወድሰውታል፡፡ የአሁኑ “ልኡል አለማየሁ” መፅሃፍ በመጀመርያው እትም ላይ ያልተካተቱ መረጃዎችና ምስሎችን እንዳካተተ ለአዲስ አድማስ የተናገረው አዘጋጁ፤ “አማራ አቀፍ ልማት ማህበር” ለመፃህፍቱ ህትመት ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሶ ለማህበሩ ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ መፃህፍቱ በ“ቡክ ዎርልድ” ሁሉም ቅርንጫፎቹ የሚገኙ ሲሆን የእያንዳንዱ ዋጋ 50 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡ ጆሴፍ ፍራንሲስ “የአድዋ ጦርነት” የሚል መፅሃፍም አዘጋጅቶ ለንባብ ማቅረቡ የሚታወቅ ሲሆን የኢትዮጵያን መልካም ገፅታ በመገንባት ረገድ የላቀ አስተዋፅኦ ሊያበረክት የሚችል “የኢትዮጵያ ድንቃድንቆች” የተሰኘ መፅሃፍ በቅርቡ ለገበያ እንደሚያቀርብ አስታውቆዋል፡፡ ጆሴፍ በአሁኑ ጊዜ በግሪክ ኮሙኒቲ ስኩል በማህበራዊ ሳይንስ መምህርነት እያስተማረ የሚገኝ ሲሆን ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ 29 ዓመት ገደማ አስቆጥሮዋል፡፡

 

 

Read 1777 times Last modified on Saturday, 23 June 2012 08:36