የኢራኑ አብዮታዊ ጦር አዛዥ የሆኑት ብርጋዴር ጄነራል ጎላም ሪዳ ጃላሊ፣ እስራኤል ከሜዲትራኒያን ባህር ተነስቶ ወደ ኢራን የሚጓዘውን ዳመና ከአየር ላይ በመጥለፍና ዝናባችንን በመዝረፍ፣ በአገራችን የተከሰተውን የውሃ እጥረት እያባባሰች ነው ሲሉ መክሰሳቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ሰሞኑን በመዲናዋ ቴራን በተካሄደ የግብርና አውደጥናት ላይ ንግግር ያደረጉት ብርጋዴር ጄነራል ጎላም ሪዳ ጃላሊ፣ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያሳድራቸው ተጽዕኖዎችና የሚያደርሷቸው ጉዳቶች፣ ተፈጥሯዊ ሳይሆኑ የውጭ አገራት ሴራዎች መሆናቸውን የአገራችን ሳይንቲስቶች በጥናት ደርሰውበታል ብለዋል፡፡
እስራኤልና ሌሎች አገሮች በትብብር በድብቅ በሚያደርጉት ሴራ፣ በሜዲትራኒያን ባህር ላይ ከሚያልፈው አየር ላይ ቅዝቃዜን በመምጠጥና ዝናብና በረዶን በመመንተፍ፣ ኢራን ዝናብ እንዳታገኝ ሲያደርጉ ቆይተዋል ሲሉም ተናግረዋል፡፡
እስራኤልን በዝናብ ዝርፊያ የሚወነጅለው የብርጋዴር ጄነራል ጎላም ሪዳ ጃላሊ ንግግር፤ በተለያዩ የኢራን መገናኛ ብዙሃን በስፋት መዘገቡን ተከትሎ፣ የአገሪቱ የሜትሪዮሎጂ ኤጀንሲ ዳይሬክተር አሃድ ቫዚፌ በጉዳዩ ዙሪያ አስተያየታቸውን የሰጡ ሲሆን፣ “ዝናብ ወይም ዳመና መዝረፍ ለማንኛውም አገር የማይቻል ነው” በማለት የጄኔራሉን ውንጀላ አጣጥለውታል፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ