Sunday, 11 February 2018 00:00

የተረጎምኩት መፅሃፍ ተመሳስሎ ተተርጉሞብኛል ያሉት ደራሲ 194 ሺ ብር ካሣ ተፈረደላቸው

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  እኔ ቀድሜ የተረጎምኩትን “The power of Now” የተሰኘ መጽሐፍ ተርጉመው፣ የ100 ሺህ ብር ኪሣራ አድርሠውብኛል ያሉት ተርጓሚ በፍ/ቤት የ194 ሺ ብር ካሣ እንዲከፈላቸው ተወሠነ፡፡
ከሳሽ ደራሲና ተርጓሚ አፈወርቅ በቀለ ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ፍትሃ ብሄር ችሎት ሚያዚያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ባቀረቡት የክስ አቤቱታ፤ በኤክርሃቶ ቶል፣ “The power of Now” በሚል የተፃፈውን መፅሐፍ “የአሁንነት ሃይል” በሚል ወደ አማርኛ ተርጉመው ለአንባቢያን ማቅረባቸውን ይሁን አንጂ እሳቸው በማያውቁትና ፍቃዳቸው ሳይጠየቅ አቶ ብስራት እውነቱ የተባሉ ደራሲ “የአሁኑ ሃይልነት” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ቋንቋ በመመለስ ኪሣራና ጉዳት እንዳደረሰባቸው ጠቁመዋል፡፡
በዚህ የክስ አቤቱታ፤ አቶ መኮንን ፋንታሁን መፅሃፉን እንዲተረጉም በማድረግና በአሣታሚነት እንዲሁም ፋር ኢስት ትሬዲን ኃላ/የተ/የግ/ማህበር ደግሞ በአታሚነትና በመሸጥ፣ ከፍተኛ ጥቅም ማግኘታቸውና ጉዳት አድራሽ መሆናቸው ተመልክቷል፡፡
ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ፣ የራሳቸውን መልስ ለፍ/ቤት ያቀረቡ ሲሆን አንደኛ ተከሣሽ የሆኑት አቶ ብስራት እውነቱ፤ የመፅሃፍ ባለመብትና ደራሲ ሄክሃርት ቶል እንጂ ከሣሽ አይደሉም ስለዚህ የፈጠራ ባለመብት አይደሉም፤ የሚል መልስ የሠጡ ሲሆን ሁለተኛ ተከሳሽ በበኩላቸው፤ ከሣሽ ራሳቸው የዋና ደራሲውን ፈቃድ ሣያገኙ ነው የተረጎሙት፤ በዚህም የመፅሃፍ ባለመብት ሆነው ክስ ማቅረብ አይችሉም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ 3ኛ ተከሳሽ (ማተሚያ ቤቱ በበኩሉ፤ እኔ ስራዬን የመፅሐፉን ይዘት ማንበብ ሣይሆን ማተም ብቻ ነው የሚል ምላሽ ሠጥተዋል፡፡
ከሣሽ በበኩላቸው፤ በፍሬ ጉዳይ ላይ ባቀረቡት መከራከሪያ፤ የትርጉም ስራ እራሱን የቻለ ፈጠራ በመሆኑ በቅጅና ተዛማጅ አዋጅ ቁጥር 410/96 መሠረት ጥበቃ አለው፤ ሲሉ አንቀፅ ጠቅሠው ተከራክረዋል፡፡
የግራ ቀኙን ክርክር የመረመረው ፍ/ቤቱ፤ ከሣሽ “መፅሃፉን እኔ ስለተረጎምኩት ሌላ ሠው ሊተረጉመው አይችልም” ብለው አንቀፅ በመጥቀስ ያቀረቡትን መከራከሪያ ተቀባይነት እንደሌለው፤ ነገር ግን ተከሣሾችም ከሳሽ መፅሀፉን በመጀመሪያ መተርጎማቸውን ማመናቸውንና ይዘቱም ተመሣሣይነት እንዳለው ከግምት በማስገባት፣ በጉዳዩ ላይ ውሣኔ ሠጥቷል፡፡
ፍ/ቤቱ ባሣለፈው ውሣኔ፣ 1ኛ እና 2ኛ ተከሣሽ ጥፋተኛ በመሆናቸው፣ በከሳሽ ደራሲና ተርጓሚ አፈወርቅ በቀለ ላይ ላደረሡት ቁሣዊ ጉዳት 94 ሺህ አንድ መቶ አርባ ብር (94,140) እንዲሁም በከሳሽ ላይ ለደረሰው የሞራል ጉዳት ብር አንድ መቶ ሺህ (1000,000) በድምሩ አንድ መቶ ዘጠና አራት ሺህ አንድ መቶ አርባ ብር (194,140) ብር እንዲከፍሉ ወስኗል፡፡ 3ኛ ተከሳሽ (ማተሚያ ቤቱ) በከሳሽ ላይ ላደረሠው ቁሣዊም ሆኖ ሞራላዊ ጉዳት ሃላፊነት የለባቸውም ብሏል - ፍ/ቤቱ፡፡

Read 2448 times