Sunday, 13 November 2016 00:00

የአሜሪካ ምርጫ ለእኔ ምኔ ነው?!

Written by 
Rate this item
(8 votes)

“እውነተኛ ለውጥ ነው የማመጣው … የኦባማ አይነት እንዳይመስላችሁ”

ማክሰኞ ማታ ወደ እንቅልፌ የሄድኩት ሄላሪ ክሊንተን እንደምትመረጥ እርግጠኛ ሆኜ ነበር። ጠዋት ባለቤቴ ትራምፕ እየመራ ነው ስትለኝ ደንብሬ ተነሳሁኝ፡፡ የደነበርኩት ጆሮዬን ማመን ስለተሳነኝ ነው፡፡ የምርጫውን ሂደት ስከታተል ነው የከረምኩት፡፡ ምንም እንደማይመለከተኝ አውቃለሁ፡፡ እኔ አፍሪካ ውስጥ እንጂ አሜሪካ ያለሁ ሰው አይደለሁም፡፡ በራሴ ሜዳ የምወክለው ሰው ስለሌለኝ በሌላ ሀገር ገብቼ እንደ መቀላወጥ ነው፡፡ ግን ህልም አለኝ፡፡ ሰው ነኝ፡፡ እንደ ማንኛውም ሰው ምርጫ አለኝ፡፡
ወደ ቴሌቪዥኑ ሄጄ ከቁርስ በፊት ተቀመጥኩኘ። ትራምፕ ድምፁን እየሰበሰበው ነው፡፡ ከእሱ ምርጫ ጣቢያና ከሂላሪ ምርጫ ጣቢያ ዘገባው እየተለዋወጠ ይሰራጫል፡፡ ከዘገባው ይበልጥ በሁለቱም ምርጫ ጣቢያ የተሰበሰቡ የደጋፊ ፊቶች፣ እየተከሰተ ስላለው ነገር እውነቱን ይናገራሉ፡፡ የሂላሪ ደጋፊዎች በማዘን ላይ ናቸው፡፡ በዲሞክራቶቹ ሀዘን እኔ መደሰት ጀመርኩኝ፡፡ ከዚህ ቀደም ሪፐብሊካንም ዲሞክራትም ሲመረጥ የምደግፈው አልነበረኝም። ግን ደግሞ ኦባማ ከዛሬ ስምንት ዓመት በፊት ሲመረጥ ደስተኛ ነበርኩኝ፡፡
ለኦባማ ስደግፍ ምክንያቴ ምን ነበር? … ግልፅ ነው፤ ጥቁር በመሆኑ ምክኒያት ብቻ ነበር፡፡ በብቃቱ አይደለም፡፡ ብቃቱ ለእኔ የቆዳ ቀለሙ ላይ የሚገኝ ይመስለኝ ነበር፤ መሳሳቴ እስኪገባኝ ስምንት ዓመት ማለፍ ነበረበት፡፡ የቀለም ዘረኛ ነበርኩኝ፤ ያኔ። ግን ፕሬዚዳንትነት ከቀለምም ሆነ ከድጋፍ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፡፡ እውነት ነው፤ ለምርጫ ምክኒያቱ፡፡ ኦባማ ታላቅ የንግግር ጥበብ አዋቂ ነው። ስምንት ዓመት በተለያየ መድረክ ላይ ሲናገር ተሰምቷል፡፡ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶም ረጅም ንግግር ሲያደርግ ሰምቼዋለሁ፡፡ ግን ማውራት ነው እንጂ ሌላ ለውጥ አላመጣም፡፡
“Change we can” - የምርጫ መቀስቀሻው ሃረግ ነበረች፡፡ ለውጡ ወደ ምን እንደሆነ ግን አልታወቀም ነበር፡፡ አሁን ለይቷል፡፡ ቴሌቪዥኑ ላይ ማፍጠጤን ቀጠልኩኝ፡፡ የሂላሪ የምርጫ ውጤት 208 ላይ ቆሟል፡፡ የትራምፕ 245 ደረሰ። በጉጉት እየተጠበቀ ያለው የፔንስልቫኒያ እስቴት የምርጫ ድምፅ ነው፡፡ የሂላሪ የእድገት ግዛት ነው፡፡
ለእኔ የትራምፕ መመረጥ ምንድነው የሚፈይደው? ከሚለው ጥያቄ ጋር ተፋጠጥኩኝ። የሚፈይደው ነገርማ አለ፡፡ የአሜሪካ ፖለቲካ በአናቱ ከተዘቀዘቀ፣ የሀገሬም ፖለቲካ ቢያንስ ጥርሱ መውለቁ አይቀርም፡፡ የሀገሬ ፖለቲካ ከሂላሪ ፖለቲካ ጋር ብዙ ዝምድና አለው፡፡ የሂላሪ ፖለቲካ ከማንነት ፖለቲካ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ለሴቶች፣ ለብሄር ብሔረሰቦች፣ ለማይኖሪቲዎች .. ወደሚል አዝማሚያ ያጋደለ ነው፡፡ ክፍልፋይን የሚያበረታታ እንጂ ወደ አንድነት የሚያመራ አይደለም፡፡
በሂደት እንደተረዳሁት ሁሉም ፖለቲካ፣ ከኢኮኖሚ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የፈለገ አይነት የፖለቲካ ጥያቄ ከማንነት ጥያቄ ይበልጥ የኢኮኖሚ መንስኤ ያለው ነው፡፡ ፍትሐዊ ሀብት የማፍራትና ፍትሀዊ የመከፋፈል ጉዳይ ነው … ሁሉም ጥያቄ ሲጠቃለል፡፡
ኦባማ ጥቁር መሆኑ ወይንም ሄላሪ ሴት መሆኑዋ ለኢኮኖሚ ኢ-ፍትሃዊነቱ መፍትሄ መሆን እስካልቻለ ድረስ የማንነት ጥያቄ አስፈላጊ አይደለም፡፡ መጀመሪያ የሰውነት ጥያቄ ነው፡፡
እንዲህ እያልኩ በማሰብ ውጤቱን መከታተል ቀጠልኩኝ፡፡ የሂላሪ ደጋፊዎች ከተቋም ጋር የተጋጩና ተቋሞችን በአጠቃላይ የሚጠሉ ስለመሆናቸው አንድ የኢኮኖሚ ባለሙያ ቀርቦ ሲናገር ሰማሁት፡፡ ባለሙያውን አውቀዋለሁ፡፡ በክሊንተን መንግስት ውስጥ የኢኮኖሚ አማካሪ ሆኖ ይሰራ የነበረ ሰው ነው፡፡
ሮበርት ራይሽ ይባላል። ለሮበርት ራይሽ መሰረታዊና ጤናማ ኢኮኖሚ፣ የመካከለኛ ገቢ የህብረተሰብ ክፍልን የሚያሳድግ ነው፡፡ መካከለኛ ገቢ ያላቸውን የሚፈጥር፣ የሚያጠነክርና የሚጠብቅ ስርዓት “ቅዱስ” ነው ብሎ ያምናል፡፡ ስለዚህ ምናልባት ህዝቡ ከተቋማቱ ጋር የተጣላው እነዚህ መብቶቹን የሚያስጠብቁ ስላልሆኑ ነው ብሎ ሀሳቡን ሰነዘረ፡፡ ሌሎችም ተራ በተራ እየተለዋወጡ የተለያዩ አስተያቶችን ይሰጣሉ። በአጠቃላይ ግን በቴሌቪዥን መስኮት የሚታዩት ሁሉ የደስታ ድባብ ውስጥ አልነበሩም፡፡  
በተለይ ምሁራኑ በተለያየ አቅጣጫ መበሳጨታቸውን እየገለፁ ነው፡፡ በቴሌቪዥን የሚታዩ ተንታኞች ግን ከህዝቡ ጋር ናቸው ወይንስ አይደሉም? አልኩኝ፡፡ ህዝብ ከተጣላው ተቋም ጋር ነው የሚሰሩት? … እሺ ምሁራንና ተንታኞቹስ ከተቋማቱ ጋር ያብሩ፤ ጋዜጠኞቹ ግን ምን ነክቷቸው ነው? … ለካ በፋውንዴሽን ታቅፈው ነው መረጃ የሚያጠናቅሩት፡፡ ከህዝቡ ጋር የቆመ ታዲያ ማነው? እንግዲህ ለህዝቡ የቆመው ማን እንደሆነ በግልፅ እየታየ ነው፡፡ ከህዝብ ፍላጎት ጋር የቆመው የምርጫ ሳጥኑ ብቻ ነበር፡፡ በምርጫ ሳጥኑ ውስጥ የተከማቸው ድምፅ ደግሞ የዶናልድ ትራምፕን ስም አጭቆ ይዟል፡፡
“Popular Vote” የሚል ነገር በቴሌቪዥኑ አንድ ጫፍ ተፅፏል፡፡ በ Popular Vote ላይ ያለው ቁጥር በሳጥኑ ውስጥ ካለው ይለያል፡፡ በጎዳና ላይ ወሬ ሂላሪ ተመርጣለች፡፡ በተጨባጩ የድምፅ መስጫ ሳጥን ውስጥ ግን የሴትየዋ ድምፅ ጎድሏል፡፡ በፕሮፓጋንዳ ምርጫ እሷ አሸንፋለች፡፡ እውነትና ፕሮፓጋንዳ ግን በህዝብና በተቋማት መሀል ያለውን ርቀት መልሰው ማንፀባረቃቸው የሚደንቅ አይደለም?
ከአንድ ወዳጄ ጋር ስለ ምርጫ ስናወራ የነገረኝ ቀልድ ትዝ አለኝ፡፡ በሰዎች መሀል ትራምፕን እንደሚደግፍ አንዱ የአሜሪካ ዜጋ ሲያወራ፣በዙሪያው ያሉ ሁሉ “እንትን የነካው እንጨት አደረጉት፡፡ “እንዴት እንደዚህ አይነት መሀይም፣ ዘረኛና ተሳዳቢ ሰው ትመርጣለህ?!” ብለው አዋከቡት፡፡ ግራ አጋቡት፡፡ ከከበበው ነቀፋ ለመራቅ ወጥቶ ሊሄድ ሲል ከታቃወሙት መሀል መሪ ሆኖ ሲጮህ የነበረው ከኋላው ተከትሎ በጆሮው፣ “እኔም ትራምፕን ነው የምመርጠው … ግን ሰው ፊት እንደዛ ብዬ አልናገርም … ሊያጠቁህ ይችላሉ” ብሎ ሹክ አለው፤ሲል አጫወተኝ፡፡ ከዚህች ቀልድ በላይ “Popular Vote”ን የገለጠልኝ ማስረጃ የለም፡፡ በቴሌቪዥኑ መስኮት የሪፐብሊካን የምርጫ ዘመቻ ዋና አቀናጁ፣ ጆን ፓዴስታ ብቅ ብሎ፣የሂላሪን ደጋፊዎች፤“ወደ ቤታችሁ ተመልሳችሁ ተኙ” ሲል ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ ደጋፊዎቿ እያለቀሱ  ተበታተኑ፡፡
አሁን ትኩረት ሁሉ ወደ ሪፐብሊካኑ ጎራ ሆነ። እኔም የታሪክ አንድ አካል የመሆን ስሜት ለምን እንደተሰማኝ ማወቅ ፈልጌያለሁኝ፡፡ … ለምንድነው እኔም ፖለቲከኛ የምጠላው፡፡ ትራምፕ የቢዝነስ ሰው እንጂ ፖለቲከኛ አለመሆኑ ደጋግሞ ሲገለፅ ይሰማል። እንዲያውም ልሂቃን ከሚባሉት ጋር እንደማይቆም ይነገራል፡፡ “የአሜሪካ ህዝብ በአብዛኛው እኮ መሀይም ነው … ትራምፕን ቢደግፉ አይግረምህ፤ እንደ አውሮፓ ህዝብ ጥልቅ ነገር አይገባውም” ያለኝ አንድ ምሁር ትዝ አለኝ፡፡ አሁን ትራምፕ ሊመረጥ መሆኑን ሲሰማ ምን ይል ይሆን? ስል አሰብኩኝ፡፡
በእርግጥ ግን ዲሞክራሲና እውቀት ምንና ምን ናቸው፡፡ መሀይም ህዝብ፤ የሚፈልገውን መሪ አያቅም ማለት ነው? … አንድን ብቁ የሚለውን ሰው ለመምረጥ ሰው መሆን ብቻ በቂ አይደለም እንዴ? የፖለቲካ ውድድር በእርግጥ የኦሎምፒክ ውድድር አይደለም፡፡ አንድ ማራቶን ውድድር ላይ ተካፍሎ ያሸነፈውን ለማወቅ፣ ምርጫና ክርክር አያስፈልገውም፡፡ ግልፅ ነው፡፡ የሰው ብቃት በአካል ተገልፆ ሲታይ ክርክር አይፈጥርም፡፡
አንድ የምርጫ እጩ ለህዝቡ የሚሆን እውነትን ሲያቀርብስ? … አዎ ያከራክራል፡፡ ስለሚያከራክር ነው የድምፅ ብልጫ ያስፈለገው፡፡ ድምፁን በምርጫ ሳጥን ከቶ መቁጠር ያስፈለገው ክርክሩን ለመክፈል ነው፡፡ ህዝብ የሚመርጠውን አያውቅም ከተባለ ዲሞክራሲ የማይሰራ ፅንሰ ሀሳብ ነው እንደ ማለት ነው፡፡
መሀይም ቢሆንም ተመረጠ፡፡ የተሰበሰበው ህዝብ በጩኸት ደስታውን ገለፀ፡፡ የሚዲያ ተቋማቱ “የተከሰተው የፖለቲካ ስርዓት መሬት መንቀጥቀጥ ነው” ይላሉ ደጋግመው፡፡ ልክ ፀሐይ በምዕራብ የወጣች ይመስላል እንዲህ ሲሉ። መገረማቸው የመነጨው ከትምክህታቸው መሰለኝ። የማያውቁትን ህዝብ እናውቀዋለን ብለው ደመደሙ፡፡ ድምዳሜው ስህተት መሆኑ ሲገለፅ የሚሰጥ ትንታኔ ማቅረብ ጀመሩ፡፡
ከዚህ ቀደም መሀይምነትን ከሀይማኖተኛ ፅንፈኝነት ጋር በማያያዝ ነበር ትንታኔ የሚሰጡት፡፡ ወይንም “ካፒታሊዝምን ሊያፈርስ የመጣ ኮሚኒስት ነው” በማለት ነበር የሚወነጅሉት፡፡ ግን ንግድን የሚያበረታታ ፅንፈኛ ወይንም ታክስን እቀንሳለሁ የሚል ኮሚኒስት ለሀሜት አይመችም፡፡ ከዚህ ቀደም የቡሽ አስተዳደር ያማረራቸው ሪፐብሊካኖች (ያውም ቀይ አንገት ነጮች) ጥቁሩን ኦባማን በአንድ ድምፅ መርጠውታል፡፡ አሁን ደግሞ ጥቁሩ ሰው የሚፈልጉትን አልሰማ ሲል ለወጡት፡፡ ምንም ፍረጃ አያስፈልገውም፡፡ ከፑቲን ጋር ለመስራት መፈለጉም የህዝቡን ድምጽ አላሳጣውም፡፡  
… ብቻ ውጤቱ ታወቀ፡፡ ትራምፕ በከፍተኛ (278) ድምጽ ተመረጠ፡፡ ሂላሪ ስታለቅስ ቆይታ ደጋፊዎቿን ለማሰናበት መጣች፤ “ዋናው አሜሪካ ናት … ከትራምፕ ጋር መስራት አለብን” አለች፡፡ ዶናልድ ማሸነፉን ሲያውቅ ለደጋፊዎቹ ያደረገውን ንግግር ተሸናፊዋም ደገመችው፡፡ ልዩነትን መግጠም ላይ አተኮሩ፡፡ ስንጥቁ ግን በቀላሉ የሚገጥም አይመስልም፡፡ ኦባማም ብቅ ብሎ፣ከወዲሁ የሽግግር ሂደቱን አቀላጥፎ፣ ለዶናልድ ስልጣኑን ለማስረከብ እንደጓጓ ተናገረ፡፡
ቀኑን ሙሉ ቴሌቪዥን ላይ የተከልኩትን አይኔን ነቀልኩኝ፡፡ ትራምፕን ከክርክሩ ጀምሮ እደግፈው ነበር፡፡ ድጋፌ የመነጨው እውነትን የሚናገር መስሎ ስለተሰማኝ ነው፡፡ የሚመስል ሁሉ አይሆንም የሚሉኝ ብዙ ናቸው፡፡ መምሰል መጀመር ራሱ ትልቅ ነገር ነው፡፡ ወደ መሆን እና ወደ ለውጥ የመጓዣ ብቸኛው መንገድ ነው፡፡
“እውነተኛ ለውጥ ነው የማመጣው … የኦባማ አይነት ለውጥ እንዳይመስላችሁ” ብሏል፤ ሰውየው።
የምርጫ ውድድሩ የመጀመሪያ ሂደት ላይ … ገና የሪፐብሊካን እጩ ለመሆን በመወዳደር ላይ ሳሉ አንድ የጋዜጣ አምደኛ፤ “ትራምፕ የሪፐብሊካን ፓርቲ እጩ ሆኖ ከተመረጠ የምፅፍበትን የጋዜጣ አምድ እበላዋለሁ …” ብሎ ፎክሮ ነበር፡፡
እንግዲህ ከእጩነት አልፎ ሰውየው ፕሬዚዳንት ሆነ፡፡ የጋዜጣ አምዱን ቀርቶ የህገ መንግስቱን ድርሳን በአጠቃላይ እየቀደደ ቢበላውም ይህ ሁነት የሚለወጥ አይሆንም፡፡

Read 4342 times