Monday, 26 September 2016 00:00

ቶታል ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ዘመናዊ ዴፖ አስመረቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 ቶታል ኢትዮጵያ ለ66 ዓመታት በአገሪቷ ሲሰጥ የቆየውን የኢነርጂ ንግድ ለማሳደግና ለማዘመን ባለው ፍላጎትና ባደረገው ጥረት በአገሪቷ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነና ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው እጅግ ዘመናዊ የነዳጅና የጋዝ ዴፖ አሰርቶ ከትናንት በስቲያ አስመረቀ፡፡
ከአዲስ አበባ ከተማ በስተደቡብ ዱከም አካባቢ በ5.5 ሄክታር መሬት ላይ የተሰራው ዴፖ፤ 270 ሚሊዮን ብር የፈጀ ሲሆን 8 ሚሊዮን ሊትር ነዳጅና 200ሺህ ሊትር ፈሳሽ ቤንዚን የመያዝ አቅም እንዳለው ታውቋል። ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰራው ዴፖው፤ ዘመኑ ያፈራቸው እጅግ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተገጠሙለት ሲሆን በታንኩ ውስጥ ያለው ነዳጅ ምን ያህል እንደሆነ የሚያሳየው መሳሪያ አውቶማቲክ ነው፡፡ የፈሳሽ ነዳጅ መያዣው ታንከር ድርብ ከመሆኑም በላይ ዴፖው አንዳች እክል ቢገጥመው የሚጠቁም (የሚጮህ) እጅግ ዘመናዊ አላርም ተገጥሞለታል፡፡ አንድ ቦታ ላይ ኤሌክትሪክ ቢበላሽ፣ ጋዝ ቢፈስ፣ እሳት ቢነሳ፣ ጪስ ቢፈጠር፣ ፈሳሽ የሃይድሮጂንና ካቦርን (ሃይድሮካርቦን) ቢፈስ አደጋ ከማስከተሉ በፊት ወዲያውኑ የሚጠቁም የኤሌክትሪክ ሲስተም ስላለው ከአደጋ የተጠበቀ ነው፡፡
የአካባቢ ብክለትንና የአሰራሩን ደህንነት የሚያረጋግጥ የርቀት መቆጣጠሪያ መሳሪያ አለው፡፡ ፕሮግራም ተደርጎ እንቅስቃሴዎችን መቆጣጠር የዚህ ዴፖ ልዩ ባህሪው ሲሆን፣ ለአጠቃቀም ቀላልና የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ የሆኑትን ደረሰኝ አጠቃቀም፣ ያለውን የክምችት መጠን፣ ወጪ የሆኑ ምርቶችን ለማወቅና የአደጋ ጊዜ ሁኔታን ምቹ መቆጣጠሪያ መሳሪያ መሆኑን ያመለክታል፡፡  
የእነዚህ በጣም ውድ የሆኑ የደህንነት መጠበቂያና መቆጣጠሪያ መሳሪያዎች መገጠም፣ ቶታል ኢትዮጵያ ለደህንነትና አካባቢን ከብክለት ለመጠበቅ ያለውን ከፍተኛ ቁርጠኝነት እንደሚያመለክት ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

Read 1248 times