Sunday, 04 September 2016 00:00

በአማራ ክልል በ1 ወር ውስጥ ከ80 ሰዎች በላይ ሞተዋል - መኢአድ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(58 votes)

“በመተማ ከ1ሺህ በላይ ሰው ተፈናቅሏል” አረና ፓርቲ
- ከሠኔ ወዲህ በአማራና በኦሮሚያ ከ500 በላይ ሰዎች ሞተዋል” የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች

በአማራ ክልል ከተፈጠረው ተቃውሞና ግጭት ጋር በተያያዘ በሁለት ሳምንት ውስጥ የ51 ሰዎች ህይወት ማለፉንና 63 ሰዎች በፅኑ መቁሠላቸውን የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ያስታወቀ ሲሆን የክልሉ መንግስት በበኩሉ፤ በአሁን ሰዓት ህግ የማስከበር ስራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁሞ በሰዎች ህይወት ላይ የደረሰው ጉዳት በኋላ ይገልጻል ብሏል፡፡
ከነሐሴ 8 እስከ ረቡዕ ነሐሴ 25 ቀን 2008 ዓ.ም በጎንደርና በጎጃም ከተሞች የተካሄዱ ተቃውሞዎችን ተከትሎ በተከሰቱ ግጭቶች የ51 ሰዎች ህይወት ማለፉን የገለፀው መኢአድ፤ ከሐምሌ 29-ነሐሴ 1 በነበረው ተቃውሞ የ30 ሰዎች ህይወት ማለፉንና በድምሩ 81 ሰዎች መሞታቸውን አመልክቷል፡፡
የመኢአድ ዋና ፀሐፊ አቶ ኪዳነ ጥላሁን ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ የአማራ ክልል ከተሞች በሆኑት፤ ማጀቴ-ሠሜን ሸዋ 1 ሰው ሞቶ 2 ሠው ቆስሏል፣ ጎንደር  8 ሠው ሞቷል፣ ኮሶ በር (እንድባራ) 3 ሠው ሲሞት፣ 8 ሠው ቆስሏል፣ ዱርቤቴ 6 ሠው ሞቷል፣ ፍኖተ ሰላም 1 ሠው ሞቷል፣ ደብረታቦር 3 ሠው ሞቷል፣ 8 ሠው ቆስሏል፤ ስማዳ 10 ሠው ሞቷል፣ 20 ሰው ቆስሏል፣ ባህርዳር 4 ሠው ሞቷል፣ አዴት ከተማ 2 ሠው ሞቷል፣ ወረታ 11 ሠው ሲሞት ከነዚህ ውስጥ 8ቱ የፀጥታ አካላት ናቸው፣ ክምር ድንጋይ 1 ሠው ሞቶ፣ 1 ሠው ቆስሏል፣ ጌዶ 7 ሠው ቆስሏል፣ አዘዞ 2 ሠው ቆስሏል፣ ዳንግላ 3 ሠው ቆስሏል እንዲሁም ወሎ- መቄት 3 ሠው ቆስሏል፡፡ በድምሩ በነዚህ 17 ቀናት ውስጥ 51 ሠዎች ሲሞቱ፣ 63 ሰዎች ቆስለዋል ብለዋል፤ አቶ አዳነ፡፡ ግጭቶች በተነሱባቸው አብዛኞቹ የክልሉ ከተሞች እስከ ትናንት በስቲያ የፀጥታ ሃይሎች በስፋት መሰማራታቸውንና የተለመደው የእለት ተለት እንቅስቃሴ የተገደበ መሆኑን ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ በርካቶች እየታሰሩ መሆኑንም መኢአድ አስታውቋል፡፡
በተጨማሪም ከትናንት በስቲያ ደብረታቦር ማረሚያ ቤት ተቃጥሏል፡፡ የማረሚያ ቤቱ ዙሪያ በታጠቁ የፀጥታ አካላት ተከቦ እንደነበርና በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት ስለመኖሩ ማጣራት እንዳልተቻለ አቶ አዳነ የጠቆሙ ሲሆን፣ በመተማና በጎንደር አምባ ጊዮርጊስ አካባቢዎች ቁጥራቸው በውል ላልታወቀ     ሰዎች ህይወት መጥፋት ምክንያት የሆነ ግጭት መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡
በደብረ ታቦርና ደብረ ማርቆስ ከተሞች የሶስት ቀናት የስራ ማቆምና ቤት ውስጥ የመዋል አድማ ተደርጎ እስከ ትናንት መቆየቱን መረጃ አግኝተናል ያሉት የመኢአድ ዋና ፀሐፊ፤ በአብዛኞቹ የጎንደርና የጎጃም ከተሞች አገር አቋራጭ ትራንስፖርት አገልግሎት ተስተጓጉሏል ብለዋል፡፡
መተማ ላይ ከትናንት በስቲያ ተኩስ እንደነበርና የሟቾች ቁጥር በውል ማወቅ እንዳልተቻሉለ አቶ አዳነ የጠቆሙ ሲሆን አረና ፓርቲ ለቪኦኤ በሰጠው መረጃ በተፈጠረው ግጭት ከ1ሺህ በላይ የትግራይ ተወላጆች፣ ከቤታቸው መፈናቀላቸውንና ወደ ሱዳን መሰደዳቸውን ጠቁመዋል፡፡
ብሉምበርግ የተሰኘው የዜና አውታር በበኩሉ፤ ከሰኔ ወር 2008 ዓ.ም ጀምሮ በኦሮሚያና በአማራ ክልል በተፈጠሩ ተቃውሞና ግጭቶች፤ ከ500 በላይ ሰዎች መሞታቸውን የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ሪፖርት ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
በጎንደር ከተማ እስከ ባለፈው ረቡዕ ድረስ አብዛኞቹ ንግድ ቤቶች ሳይከፈቱ የሰነበቱ ሲሆን የትራንስፖርት አገልግሎትም ተገድቦ መክረሙንና ከትናንት በስቲያ የተሻለ መረጋጋት እንደነበር ተናግረዋል፡፡
በባህር ዳር ከተማ ከእሁድ ጀምሮ እስከ ትናንት ድረስ ቤት የመዋል አድማ መደረጉን፣ ሠኞና ማክሰኞ እለት ግጭቶች ተፈጥረው ሰዎች መጎዳታቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የስራ ማቆም አድማው በከተማዋ ለሁለተኛ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን ቀደም ሲል ከነሐሴ 8 ቀን እስከ ነሐሴ 12 ለ4 ቀን 2008  ዓ.ም ከተካሄደ በኋላ ፣ለ4 ቀናት ወደተለመደው እንቅስቃሴ የጠመለሰ ሲሆን በድጋሚ አድማ መደረጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በአድማው ማንኛውም የከተማ ትራንስፖርትም ሆነ ከባህርዳር ወደተለያዩ አካባቢዎች የትራንስፖርት አገልግሎት መቆሙን ምንጮች የጠቆሙ ሲሆን ሰኞና ማክሰኞ እለት በከተማዋ የተኩስ ድምፅ ይሰማ እንደነበርና በርካታ ወጣቶችም በፀጥታ ኃይሎች መታሰራቸውን አመልክተዋል፡፡

Read 9443 times