Tuesday, 24 May 2016 08:49

የመንግሥት መ/ቤቶች የተሽከርካሪዎች አያያዝ ላይ ከፍተኛ ችግር እንዳላቸው ተገለፀ

Written by  መታሰቢያ ካሣዬ
Rate this item
(3 votes)

 በአንድ የመንግሥት መ/ቤት 10 ተሽከርካሪዎች ሊብሬአቸው ሲገኝ መኪኖቹ የገቡበት አልታወቀም
     በፌደራል መንግስት መ/ቤቶች ውስጥ ያለው የተሽከርካሪዎች አያያዝና አጠቃቀም ከፍተኛ ችግሮች እንዳሉበትና አፋጣኝ የእርምት እርምጃ እንደሚያስፈልገው ተገለፀ፡፡
የፌደራል ዋና ኦዲተር፤ የመንግስት መ/ቤቶች የ2007 በጀት ዓመት ሂሳብ ኦዲት ሪፖርትን ሰሞኑን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበበት ወቅት እንደተገለፀው፤ በፌደራል መንግስት ሥር በሚተዳደሩት የመንግስት መ/ቤቶች ላይ በተደረገ ፍተሻና ምርመራ በ32 መ/ቤቶች ውስጥ የሚገኙ 313 ተሽከርካሪዎች የባለቤትነት ሊብሬ አልቀረበባቸውም፡፡ በ21 መ/ቤቶች ውስጥ የሚገኙ 218 መኪኖች በብልሽት ምክንያት ቆመዋል፡፡ በአንድ መንግስታዊ ተቋም ውስጥ የሚገኙ 10 ተሽከርካሪዎች ሊብሬአቸው ብቻ ሲገኝ መኪኖቹ የገቡበት አለመታወቁም ተገልጿል፡፡
በስድስት መ/ቤቶች ውስጥ የሚገኙ 15 ተሽከርካሪዎች የሰሌዳ ቁጥር የሌላቸው መሆኑንና በ2 መ/ቤቶች ውስጥ የተገኙ 3 ተሽከርካሪዎች ደግሞ ሞተራቸው ተቀይሮ መገኘታቸው ተጠቁሟል፡፡
በፌደራል መንግስት መ/ቤቶች ላይ ያለውን የተሽከርካሪዎች አያያዝና አጠቃቀም ለማየት በተወሰኑ መንግስታዊ ተቋማት ላይ ፍተሻ ማካሄዱን የገለፀው የጠቅላይ ኦዲት ሪፖርቱ በአያያዝና አጠቃቀማቸው ላይ ጉድለት የተገኘባቸው መ/ቤቶች የእርምት እርምጃ መውሰድ እንዳለባቸው፣ በብልሽት ምክንያት የቆሙትም ተጠግነው አገልግሎት እንዲሰጡ፣ የማያገለግሉት በመንግስት መመሪያ መሰረት እንዲወገዱ፣ ሊብሬ ያልቀረበላቸው መኪኖች እንዲመጣላቸው፣ በአካል ያልተገኙት ተሽከርካሪዎች ያሉበት ሁኔታ ተጣርቶ ተገቢው እርምጃ እንዲወሰድ አሳስቧል፡፡

Read 1245 times