Saturday, 07 May 2016 12:22

የመዝገቡ ተሰማ ሥዕሎች ለዕይታ ይቀርባሉ

Written by 
Rate this item
(7 votes)

      ታዋቂው ሰዓሊ መዝገቡ ተሰማ የሰራቸው ትልልቅና አዳዲስ ስዕሎች፣ “የአዲስ አባ ልጅ” በሚል ስያሜ፣ ሐሙስ  በብሔራዊ ሙዚየም ለተመልካቾች ይታያሉ፡፡ምናባዊ ፈጠራንና ተዓማኒነትን ባጣጣመ ድንቅ የስዕል እውቀትና ክህሎት የላቀ የጥበብ ደረጃ ያሳየ አርቲስት እንደሆነ የሚነገርለት ሰዓሊ መዝገቡ፤ “ንግስ” በተሰጥኦ ትርኢት ያቀረባቸው  ስዕሎች ከፍተኛ አድናቆት አትርፈውለታል፡፡ በታሪክ ተጠቃሽ የሆኑ የስዕል ስራዎቹንና ምርጥ ችሎታውን ማሳየት የጀመረው ከ20 ዓመታት በፊት ቢሆንም፤ በየጊዜው የፈጠራና የችሎታ ምጥቀትን የሚመሰክሩ ስራዎች በማበርከት ይታወቃል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት “ንግስ” በሚል ስያሜ ያቀረባቸው ስዕሎች በበርካታ የሚዲያ ተቋማት መነጋገሪያ  ርዕስ ለመሆን የበቁትም፤ ስዕሎቹ በፈጠራ ሃሳብና በስዕል ችሎታ አዲስ ደረጃን ያሳያሉ በሚል ነበር፡፡ በርካታ ተመልካቾችን የማረከው ይሄው “ንግስ” የስዕል ትርዒት፣ እንደገና ለእይታ እንዲከፈት በተደጋጋሚ ሲጠየቅ የነበረ ሲሆን፤ የተወሰኑት ስዕሎች በአሁኑ ትርዒት እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡ “የአዲስ አባ ልጅ” ለተሰኘው ትርዒት የተሰሩ  አዳዲስ የመዝገቡ ስዕሎች፤ ከወትሮው የተለዩ አይደሉም፤ እንደ ወትሮው በአዳዲስ የፈጠራ ሃሳቦችና በጥበብ ክህሎት  የተሰሩ ስዕሎች ናቸው፡፡ የፊታችን ረቡዕ ምሽት ተመርቆ ሐሙስ ለተመልካች የሚከፈተው ትርኢት 20 ስዕሎችን የያዘ ነው፡፡


Read 2930 times