Saturday, 16 April 2016 10:42

“ለሕዳሴ ግድብ ቦንድ ያዋጣነው 400ሺ ብር የገባበትን አናውቅም” የቦሌ መድኃኔዓለም ካህናት

Written by  ማህሌት ኪዳነወልድ
Rate this item
(16 votes)

ቦንድ ሳይሆን ስጦታ ነው፤ ተብሏል
    የቦሌ ደብረ ሳ ሌም መድኃኔዓለም ካቴድራል ካህናትና ሠራተኞች፤ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ያዋጣነው
ከ400ሺሕ ብር በላይ ገንዘብ የገባበትን አናውቅም፤ አሉ፡፡ ገንዘቡ ከ4 ዓመት በፊት 160 ከሚሆኑ
ሠራተኞች ደመወዝ የተሰበሰበ መሆኑን ምንጮች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡ እንደ ምንጮቹ ገለፃ፤ ካህናቱ በወቅቱ በተደጋጋሚ ለካቴድራሉ አስተዳደር የቦንድ ግዢ የተፈፀመበት ሰርተፍኬት እንዲሰጣቸው ጠይቀው የነበረ ቢሆንም አስተዳደሩ ግን፣ “ገና ከባንክ ቤት አልመጣም”፣ “ይደርሳል” እና መሰል ምክንያቶችን እየሰጠ ቆይቷል፡፡ ከ4 ዓመታት በኋላም  ግን፣ ሰርተፊኬቱ ይሄው አልደረሰም ይላሉ ምንጮች፡፡ በመጨረሻም ካህናትና ሠራተኞቹ ወደ ንግድ ባንክ በመሄድ ጉዳዩን ለማጣራት እንደሞከሩ የጠቆሙት የካቴድራሉ ምንጮች፤ ባንኩም  ብሩ ከእነርሱ ስለመሰብሰቡ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ እንደገለጸላቸው ተናግረዋል፡፡ኹሉም የካቴድራሉ ካህናትና ሠራተኞች የዓመት ደመወዛቸውን በሁለት ዙር ማበርከታቸውን የሚናገሩት አስተዳዳሪው መልአከ ሰላም አባ መንግሥተ ኣብ ገብረ እግዚአብሔር፤ ለሁለተኛው ዙር መዋጮ የቦንድ ሰርተፊኬት መስጠታቸውንና የመጀመሪያውን ዙር በተመለከተ ግን የወቅቱ  ሒሳብ ሹም ተከታትለው እንዲያስጨርሱ መወከላቸውን ገልፀዋል፡፡ በወቅቱ የካቴድራሉ ሒሳብ
ሹም የነበሩትና ከወራት በፊት ወደ ደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል የተዛወሩት እማሆይ  እሕተ ማርያም ገብረ ሥላሴ በበኩላቸው፣ ከካቴድራሉ ውክልና እንደተሰጣቸው በአስተዳዳሪው የተጠቀሰውን አስተባብለዋል፡፡ አያያይዘውም ጊዜው በመራቁ የገንዘቡን ትክክለኛ መጠን እንደማያስታውሱት ሒሳብ ሹሟ ገልጸው፤ ይኹንና 4 ኪሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሥላሴ ቅርንጫፍ በካቴድራሉ ስም ገቢ ማድረጋቸውንና የገባበትንም ኮፒ ለሀገረ ስብከቱ መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለ ቦንድ ሰርተፊኬቱ ከሦስት የካቴድራሉ ሠራተኞች ጋር በመሆን የባንኩን ቦሌ መድኃኔዓለም ቅርንጫፍ መጠየቃቸውን የጠቆሙት ሒሳብ ሹሟ፤ “መጀመሪያ የተሰበሰበው ገንዘብ እንደ ስጦታ፣ የሚቆጠር ነው፤” የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው ጠቅሰዋል፡፡

Read 4904 times