ኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ የሰዓሊ ናኦድ ክፍሉ በርካታ የስዕል ስራዎች የተካተቱበትን “ትውስታ” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ ከትላንት በስቲያ ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ሙዚየም ለእይታ አበቃ፡፡“ትውስታ” የስዕል አውደ ርዕይ ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ የቀድሞ ባቡሮችን ወደ ሃሳብ ቀይሮ የሳለበትና ሌሎች 48 ያህል ስዕሎች የቀረቡበት እንደሆነ የኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ ባለቤት አቶ ኤፍሬም ለሚ ተናግረዋል፡፡ ሰዓሊው ከዚህ ቀደም ከሌሎች ሰዓሊያን ጋር በቡድን ለበርካታ ጊዜያት ስራዎቹን ለእይታ ማቅረቡን የገለፁት አቶ ኤፍሬም፤ “ትውስታ” በግሉ ያቀረበው የመጀመሪያው አውደ-ርዕይ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ኤፍሬም አርት ስቱዲዮና ጋለሪ ከዚህ በፊት ሦስት የቡድን አውደርዕዮችን ለተመልካች ያቀረበ ሲሆን የአንድ ሰዓሊ ስራዎችን ለብቻ ሲያቀርብ የአሁኑ የመጀመሪያው መሆኑን የጋለሪው ባለቤት ተናግረዋል፡፡ አውደ ርዕዩ እስከ ጥቅምት 3 ቀን 2008 ዓ.ም ለተመልካች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይም ታውቋል፡፡
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና