Saturday, 19 September 2015 09:11

የዞን 9 ጦማርያን የዘንድሮ የፕሬስ ነፃነት ተሸላሚ ሆኑ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(9 votes)

    በሽብር ተከሰው ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታየ የሚገኘው የዞን 9 ጦማሪያንና በስደት ላይ የሚገኙ  የጦማሪያኑ ቡድን አባላት፤ የዓለም አቀፉ ጋዜጠኞች ጥበቃ ኮሚቴ (CPJ) የ2015 አለማቀፍ የፕሬስ ነፃነት ሽልማት አሸናፊ ሆኑ፡፡
ሲፒጄ፤ የማሌዥያ፣ ፓራጓይና ሶሪያ ጋዜጠኞችም የዘንድሮ ዓለም አቀፍ የፕሬስ ነፃነት ሽልማት አሸናፊ መሆናቸውን ይፋ አድርጓል፡፡ እኒህ ጋዜጠኞች በሥራቸው ሂደት የሞት ማስፈራሪያና ዛቻ እንደረሰባቸው የጠቆመው ኮሚቴው፤ በአካላዊ ጥቃት፣ በህጋዊ እርምጃ፣ በእስር ወይም በስደት ክፉኛ መሰቃየታቸውንም በመግለጫው ጠቁሟል፡፡  
“የዞን 9 ጦማሪያን በሀገሪቱ ያሉ ነፃ ፕሬሶችና መገናኛ ብዙሃን በመንግስት ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ ተፅዕኖዎች እንዲሁም በገንዘብ አቅም መዳከም የማህበረሰቡን ችግር አጉልተው ማውጣት በተሳናቸው ሰዓት፣ የማህበራዊ ሚዲያን በመጠቀም ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል” ሲል ሲፒጄ በሪፖርቱ አወድሷቸዋል፡፡
የዞን 9 ጦማሪያን ከሦስት ዓመት በፊት በ9 ወጣት ፀሐፊያን የተመሰረተ የጡመራ መድረክ መሆኑን የገለፀው ሲፒጄ፤ 4ቱ ጦማሪያን በእስር ላይ እንደሚገኙና ሁለቱ በቅርቡ ከእስር መለቀቃቸውን እንዲሁም 3ቱ የጦማሪያኑ አባላት በስደት ከሀገራቸው ውጪ እንደሚገኙ ጠቁሟል፡፡
አራቱ በእስር ላይ የሚገኙት የዞን 9 አባላት አቤል ዋበላ፣ በፍቃዱ ኃይሉ፣ አጥናፍ ብርሃኔና  ናትናኤል ፈለቀ ሲሆኑ ማህሌት ፋንታሁንና ዘላለም ክብረት ከወራት በፊት ከእስር መለቀቃቸው ይታወሳል፡፡ በሌለችበት በሽብር የተከሰሰችውን ሶሊያና ሽመልስን ጨምሮ እንዳልክ ጫላና ጆማኔክስ ካሳዬ በስደት ላይ ይገኛሉ ተብሏል፡፡
መንግስት በ2007 ዓ.ም 6 ያህል ጋዜጠኞችን ከእስር መልቀቁን የጠቀሰው ሲፒጄ፤ ዛሬም ግን በርካታ ጋዜጠኞች ከስራቸው ጋር በተያያዘ በእስር ላይ እንደሚገኙ ጠቁሞ፣ ኢትዮጵያ ከዓለም ጋዜጠኛ አሳሪ 10 አገራት መካከል በ4ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ አመልክቷል፡፡
የሲፒጄን ሪፖርቶች እንደማይቀበል በተደጋጋሚ የገለፀው የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ በፃፈው ፅሁፍ ምክንያት አሊያም ከሙያው ጋር በተያያዘ የታሰረ አንድም ጋዜጠኛ አለመኖሩን መግለፁ ይታወሳል፡፡ 

Read 2552 times