Monday, 20 April 2015 15:38

የጥረት ፍሬ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ወ/ሮ ውድነሽ መልከ መልካምና የደስደስ ያላት፤ ሳቂታና ተጫዋች ናት። በልጅነቷ ገበያ ላይ ከተዋወቀችዉ ጓደኛዋ ጋር ትዳር መስርታ አንድ ልጅ አፍርተዋል። ከእለታት በአንዱ ቀን ጨለማ ለብርሃን ስፍራዉን ሲለቅ ተነስታ ለባለቤቷ ቁርስ ታዘጋጃለች። ባለቤቷ ደግሞ ቀን ለሚሰራቸዉ ስራዎች የሚያስፈልጉትን ነገሮች ካዘጋጀች በኋላ ቁርሳቸዉን በፍቅር አብረዉ ተመገቡ። ከቁርስ በኋላ ባለቤቷ ሲለባብስ ይንን ልበስ፣ ይህንን ቀይር፤ እዚህ ጋር አስተካክል እያለች ካቆነጃጀችዉ በኋላ የግራ እጆቿን ጣቶች የቀኝ እጆቹ ጣቶች ውስጥ አሰካክታ ከቤት ይዛው ወጣችና እሱ ወደ መኪናው ሲሄድ ቆም ብላ እጆቿን ከእጆቹ በቀስታ አላቀቀች። መኪና ውስጥ ገብቶ ሲያስነሳ ሰራተኛዋን ጠርታ የግቢዉን በር እንድትከፍትለት ነገረቻት። ሰራተኛዋ በሩን ከፍታ ወደነሱ ስትመለከት ወ/ሮ ውድነሽ ጠጋ ብላ ባለቤቷ የለመደዉን የስንብት ሰላምታ ለማግኘት ዝቅ ባደረገዉ መስታወት በኩል ሳም አድርጋዉ በፍቅር ተሰናበተችዉ። ይህን የተመለከተችዉ ሰራተኛዋ በቀኝ እጇ አፏን እንደመሸፈን ብላ በማፈር መንፈስ ወደ መሬት አቀረቀረች።  ባለቤቷ አቶ ወርቅነህ ግቢውን ለቆ ሲወጣ ወ/ሮ ውድነሽ በሩን ዘግታ ከሰራተኛዋ ጋር ወደ ቤት ተመለሱ።
ሰራተኛዋ የተለመደውን አልጋ የማንጠፍ፣ ቤት የማጽዳት፣ እቃ የማጣጠብ ስራዋን ጨርሳ ወደሚቀጥለዉ ምግብ የማብሰል ስራዋ ልትሄድ ስትዘጋጅ ስትመለከታት የነበረችዉ ወ/ሮ ውድነሽ አንዳች ነገር ልቧን ደቃትና “ፈለጉሽ ነይ እሰኪ!” ብላ ወደራሷ ጠራቻት። ሰራተኛዋ ስራዎቹን የምትሰራዉ በግዴለሽነት ነዉ። በህይወቷ ለማሳካት የምትፈልገዉ ምንም አይነት ህልም የላትም። ያላትን መልካም አጋጣሚዎች ሁሉ ሳትጠቀምባቸው ታባክናለች። ገና ከገጠር ወደ ከተማ ስትመጣ  በአንዳንድ ጓደኞቿ እና አጉል ተስፋ በሚሰጡ ሰዎች ተገፋፍታ ትምህርቷን ቤተሰቧ ጋር ሆና በአግባቡ ትምህርቷን እየተማረች ካለችበት አቋርጣ የመጣችዉ። አሁን ደግሞ ያቋረጠችዉን ትምህርቷን ማታ ማታ እንድትቀጥል ወ/ሮ ውድነሽ ከስራ ነጻ በማድረግ ሁኔታዎችን ብታመቻችላትና ብትገፋፋትም ፈቃደኛ አልሆነችም። የምትሰራበትን ገንዘብ እንኳን አጠራቅማ እራሷን ለመለወጥ አትጥርም። ‘የማይረቡ ነገሮችን’ በመግዛት አበካክና ትጨርሳለች። እናም ወ/ሮ ውድነሽ ሁሌ ትመክራታለች፤ እሷ ግን መስማት እንጂ ወደተግባር ስትለውጥ አትታይም። በዚያን እለት ግን ትምህርት እንዲሆናት ብላ የራሷን የልጅነት ልፋት ኮስተር ባለ መንፈስ እንደተሞክሮ አካፈለቻት።
“ይኸዉልሽ ፈለጉሽ፣ ነገ የተሻለ ህይወት ለመኖር ዛሬን መጣጣር ያስፈልግሻል። እኔ ከወላጆቼ የወረስኩት ገንዘብና እውቀት አልነበረም። ስለዚህም ገና ትንሽ ልጅ እያለሁ ኑሮዬን የተሻለ ለማድረግ በሰፈር ውስጥ ድንች፣ ቃሪያ፣ ሽንኩርት፣ጎመን…የመሳሰሉትን እየቸረቸርኩ ለራሴ የሚያስፈልጉኝን አንዳንድ ነገሮች እገዛ ነበር። በዚያ ሂደት ከጊዜ በኋላ ትንሽ ብር ማጠራቀም ቻልኩኝ። ያጠራቀምኩትን ብር ይዤ የቻለልኝን ያክል እቃ ገዝቼ እያዞርኩ ሱቅ በደረቴ መስራት ጀመርኩኝ። ስራዉን እየሰራሁ የበለጠ ገንዘብም እያገኘሁ እያለ አንድ ቀን …” እንዳለች ትካዜ ውስጥ ገባችና ንግግሯን አቋረጠች።
“እንዴ እትዬ ምነው ቆዘሙሳ?” አለቻት ሰራተኛዋ።
ለሴኮንዶች ጸጥ ካለች በኋላ “አይ ምንም አይደለም” ብላ ጨዋታዋን ቀጠለች። “እ…በእለቱ የእግረኛ መንገድ ዘግተን እንዳንሸጥ ፖሊስ ሲያባርረን ለማምለጥ የመኪና መንገድ እያቋረጥኩ ስሮጥ ከባድ የመኪና አደጋ ደረሰብኝ። በዘመድ አዝማድ ድጋፍ ጭምር ህክምና ባገኝም ከልጅነቴ ጀምሮ ከግራ እጄ ጋር ጉዳት የነበረበት የቀኝ እግሬ ከአገልግሎት ውጪ ሆነ” ብላ እምባ እየተናነቃት በአውራ ጣቷ እና በአመልካች ጣቷ ሁለት ዓይኖቿን ከድና ይዛ ወደታች አቀረቀረች።
“አይዞት እትዬ፤ እግዚአብሄር ይማሮት” አለቻት ሰራተኛዋ በሀዘኔታ።
“አዎ ምሮኛል!” ብላ ቀና አለችና ጨዋታዋን ቀጠለች ወ/ሮ ውድነሽ። “ታዲያ ያን ጊዜ ተስፋዬ ጨልሞ ምን ማድረግ እንዳለብኝ ባላወኩበት ጊዜ የአማራ ክልል የሴቶች ጉዳይ ቢሮ ከባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር ፍላጎት ላላቸዉ ሴቶች መጠነኛ ብድርና የመስሪያ ቦታ እንደሚያመቻቹ ሰማሁ። በዚያ ሁኔታ ውስጥ ሆኜ ጉዳዩን ማጣራትና መከታተል ያዝኩኝ። በመጨረሻም በአካል ጉዳተኝነት ቅድሚያ እድሉን በማግኘቴ ተስፋዬ አንሰራርቶ  መደብ ይዤ እጉልት የንግድ ስረዬን መስራት ጀመርኩኝ። ከዚያ ጊዜ በኋላ የሚያጋጥሙኝን ፈተናዎች ሁሉ በጽናት በማለፍ ይኸዉ ለዚህ በቅቻለሁ። አንቺም ነገ ኑሮሽን ለመቀየር ዛሬ መጣጣር አለብሽ” ብላ አጠንክራ ነገረቻት።
“እሺ እትዬ፤ እጥራለሁ!” አለች ሰራተኛዋ።
እናትና አባት ወደ ባህር ዳር የመጡት የእድሜያቸውን እኩሌታ ካሳለፉበት የደቡብ ጎንደር ገጠራማ አካባቢ ሲሆን ወ/ሮ ውድነሽ ግን የተወለደችዉ ባህረ ዳር ነው። ከመጻፍና ማንበብ ያለፈ ምንም ትምህርት አልተማሩም። በሚያባትል የኑሮ ውጣውረድ ተጠምደዉ እላይ እታች ዱብዱብ ሲሉ የኖሩ ናቸው። አባቷ የቀን ስራና ያገኙትን ተባራሪ ስራ በመስራት ህይወትን ሲመሩ የኖሩ ሲሆን እናቷ ደግሞ የሰው ቤት በተመላላሽ ሰራተኝነት እና በሰፈር ውስጥ ልብስ በማጠብ በሚያገኟት ገቢ ኑሯቸዉን ሲደጉሙ የኖሩ ናቸው።
ወ/ሮ ውድነሽ ታዲያ በልጅነቷ ወደ ትምህርት ቤት እንድትገባ ከወላጆቿ ሁኔታዎችን የማመቻቸትም ሆነ የመገፋፋት እድል አልገጠማትም። ‘ከጓደኞቼ አልቀርም’ እያለች በማልቀስ  እና ብሶ ሲመጣም ‘ከጓደኖቿ በታች አታድርጓት’ እያስባለች በጎረቤቶቻቸው በማስነገር የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቷን አጠናቃለች። ከቤት ሳትወጣ የቤት ውስጥ ስራ ብቻ እንድትሰራ ነበር የቤተሰቦቿ ፍላጎት። ‘ሴት ልጅ በማጀት ውላ የቤት ዉስጥ ስራ ብቻ ስትሰራ ተፈላጊነቷ ይጨምራል፤ ከቤት ወጥታ አደባባይ ከዋለች ግን እሷ አለሌ ናት እየተባለች ተፈላጊነቷ ይቀንስና ቆማ ትቀራለች’ የሚለው ለዘመናት በህብረተሰቡ ውስጥ ሰርጾ የቆየ አባባል በወ/ሮ ውድነሽ ቤተሰቦችም ዘንድ የጸና ነበር። ከዚህ ሌላ ደግሞ አካል ጉዳተኛ በመሆኗ ብዙ የእድሜ እኩዮቿ ይርቋት ስለነበርና የአካባቢዉ ሰዎችም በተለየ ሁኔታ ያይዋት ስለነበር ‘የተረገመ ዘር አለባቸዉ’ ብሎ ህብረተሰቡ እንዳያገላቸዉ በመስጋትም ጭምር ነበር ከቤት እንዳትወጣ ጥረት ያደርጉ የነበረዉ። ሌላው ቀርቶ እንግዳ ወደ ቤታቸዉ ሲመጣ እንኳን ፊት ለፊት እንዳትታይ ወደጓዳ እንድትገባ ያደርጓት ነበር።
ሰራተኛዋን ለመምከር ካደረገችዉ ጥረት በኋላ ያለፈዉ መጥፎ ትዝታ መንፈሷን ስለረበሸዉ ወ/ሮ ውድነሽ ትንሽ እረፍት ለማግኘት ባለ አንድ ፎቅ የሆነው ቤታቸው አናት ላይ ወዳለዉ ክፍት ቦታ ወጥታ አረፍ አለች። ባለችበት ሆና ግቢዉን በዓይኗ መቃኘት ጀመረች። ግቢያቸዉ በጣም ሰፊና የተዋበ ነው። በልዩ ልዩ አበባ እና በተፈጥሮ ሳር ፈርጅ ፈርጅ ባለው መልኩ የተሸፈነ ነው። እጸዋቱ ለዓይን ከመማረካቸዉ ባሻገር ግቢውን ነፋሻማ አድርገዉታል። ከውሻ ቤት ጀምሮ በግቢዉ ውስጥ ያሉ ክፍሎች በንጽህና የተያዙ ናቸዉ።  
በዓይኗ ግቢዉን እየቃኘች ሆዷ ውስጥ የሆነ ስሜት ተሰማት። ወዲያዉ በኋላ ባለቤቷ አቶ ወርቅነህ ትዝ ላት እና ለራሷ ፈገግ አለች። አንድ ቀን ከዋለበት የንግድ ስራዉ ሲመጣ ወ/ሮ ወድነሽን አልጋ ላይ አገኛት። በቀስታ ወደ እሷ ካመራ በኋላ፤
“የኔ ውድ፤ ስላም ዋልሽ?” ብሎ በፍቅር ሳም አደረጋት።
“ደህና ነኝ” አለችዉ በደንብ እየነቃች።
ወደታች ወረድ ብሎ ሆዷን ዳበስ እያደረገ “እንዴት ነው ይህ ጎረምሳ?” አላት።
ሳቅ እንደማለት ብላ “ጎረምሳ መሆኑን እንዴት አወቅክ? ጎረመሲት ናት!” አለችዉ እና ሁለቱም ተያይተዉ ተሳሳቁ።
ወ/ሮ ውድነሽ ድርስ ናት። ካረገዘችበት ጊዜ ጀምሮ የምታሳያቸዉ በየጊዜዉ ስሜቶቿ ይቀያየራሉ። እርግዝናዉ ከአካል ጉዳተኝነቷም ጋር ተዳምሮ ጫና እንዳይፈጥርባት አቶ ወርቅነህ አጥብቆ ከጎኗ በመሆን የምትፈልገዉን ሁሉ አቅሙ በፈቀደዉ መጠን በማሟላትና በመንከባከብ የድረሻዉን ይወጣል።
በዚያች ቅጽበት በሃሳብ ሰረገላ እየጋለበች ከባለቤቷ ጋር ያሳለፈቻቸውን መልካም ጊዜ በዓይነ ህሊናዋ መቃኘት ጀመረች።
ሁለቱም አብረዉ ብዙ ጊዜ በእግር ጉዞ የደርጉ ነበር። ከእለታት በአንዱ ቀን አመሻሽ ላይ የእግር መንገድ ለማድረግ ተያይዘዉ ወጡ። በእለቱ የእግር ጉዞውን ለማድረግ የወሰኑት ለቤታቸዉ ቅርብ ወደሆነው ጣና ሃይቅ ዳርቻ በመሆኑ ወደዚያዉ ተጓዙ። የሃይቁ ዳርቻ ሸክላማ ድንጋይ የተነጠፈ በመሆኑ ለአግር ጉዞ በጣም ተመችቷቸዋል። ከመንገዱ በቀኝ በኩል ሃይቁን ተንተርሰዉ በተሰሩ የሃይቅ ዳርቻ መዝናኛዎችና ለምለም እጸዋት አይናቸዉ ተማርኳል። ወደ ግራ ዞር ሲሉ ደግሞ  ሃይቁና ሰማዩ የተገናኙበት የሚመስል ቦታ ላይ በግማሽ የጠለቀችው ፀሐይ በቀረዉ አካሏ በምትለቀዉ ፍም እሳት በሚመስለዉ ብርሃኗ የውሃው ገጽ ላይ የተለየ ማራኪ ሁኔታን ፈጥራላቸዋለች። በስፍራዉ በሚታየዉ ነገር በሙሉ መንፈሳቸዉ ታድሷል። ለእግር ጉዞዉ ከተነጠፈዉ ሸክላማ ድንጋይ መጨረሻ ሲደርሱ ከመመለሳቸው በፊት ሀይቁ ዳር አረፍ ብለው የዱሯቸዉን ማውጋት ጀመሩ።
አረፍ ብለዉ ትንሽ እንደቆዩ  “ፍቅሬ! ጉልት ሰፈርን ታሰታውሰዋለህ?” ብላ ጠየቀችዉ ወ/ሮ ውድነሽ።   


“እሱማ እንዴት ይረሳል የኔ ፍቅር። ለዛሬዉ ማንነታችን መሰረቱ እሱ አይደል?” አላት በፈገግታ በተሞላ ፊት አይን አይኗን እያየ።
“እሰኪ ከዚያ የማትረሳዉን ነገር ንገረኝ!” አለችዉ የጉንጩን ጺም እየደባበሰችና አይኑን በቆረጣ እያየች እያየች።
“እ…እዛማ የሚፈራረቅብን ፀሃይና ዝናቡ፣ እቃ አልሸጥ ሲለን ሌላ እቃ ማምጣት ሲያቅተንና በጣም ስንቸገር፣…ከሁሉም በላይ የማልረሳዉ ደግሞ ከንግድ ቢሮ ነዉ የመጣነዉ ያሉ ግለሰቦች የንግድ ፈቃድ ሳይኖራችሁ መስራት አትችሉም ብለዉ መደባችን ፈራርሶ ከቦታችን ተፈናቅለን የተንገላታነዉ ነዉ” አላት።
“ኡ…ያን ጊዜማ አታንሳዉ!” አለችዉ ወ/ሮ ውድነሽ እጆቹን ጥብቅ አድርጋ እየያዘችና ትኩር ብላ እየተመለከተችዉ።
“አይዞሽ ውዴ! አሁንኮ አልፏል” አላት ዘና ባለ መንፈስ።
ቀጠል አደረገችና “ያኔ እኮ እኔ ተስፋ ቆርጬ በህይወቴ ወደኋላ የተመለሰኩበት ጊዜ ነበር” አለችው አዘኔታ በተሞላበት ድምጸት።
ወደራሱ እቅፍ እያደረገ “አዎ! ግን ያው የተለያዩ አካላት…” ሲል ሳታሰጨርሰዉ ቀበል ብላ፤
“እሱማ ነዉ።  በሴቶች ዙሪያ የሚሰሩ የተለያዩ አካላት ተቀናጅተዉ የመስሪያ ቦታችን ከበፊቱ በተሻለ መልኩ መጠለያም እንዲሰራለት፣ ለመንቀሳቀሻ ብድር እንዲመቻችልን እንዲሁም የንግድ ስራችንን እንዴት መስራትና ውጤታማ መሆን እንደምንችል ስልጠና እንድናገኝ ድጋፍ ካደረጉልን በኋላ እኮ ነዉ ወደራሴ ተመልሼ እንደገና በወኔ መንቀሳቀስ የጀመርኩት” አለችዉ።
“ከዚያ በኋላ እኮ በቃ እንደ ጥይት ተተኮስሽ” አላት ፈገግ እያለ።
“ታዲያስ! ከዚያማ ብርታት አግኝቼ ወደኋላ ላልመለስና በህይወቴ ውደፊት ብቻ ለመጓዘዝ አመረርኩኝ” ብላ እንደ መቀለድ አለችና ሳም አደረገችዉ።
ወዲያው ዞር ብሎ ተመለከተና፤ “ጨለማ እየመጣ ነዉ፤ ሰው ሁሉ ሄዶ ጭር ብሏል። እንነሳ” ብሏት እነሱም ወደ ቤታቸዉ ጉዞ ቀጠሉ። በመንገድ ላይ እሷ በግራ እጇ እሱ ደግሞ በቀኝ እጁ አንዱ የሌላኛው ወገብ ላይ በማሳረፍ ተቃቅፈዉ ነበር የሚጓዙት። ወደ ቤታቸዉ አቅራቢያ ሲደርሱ ወ/ሮ ውድነሸ ድንገት “ያዝ!” ብላ ክራንቿን ለአቶ ወርቅነህ ሰጠችው። “እንዴ ኧረ እንዳትወድቂ!” ብሎ ጮኸባት። “አይዞህ አታስብ ሌላ ምረኩዝ አለኝ። የጉልት ንግዴ በተቃወሰበት ጊዜ እንድጠነክር በማበረታታት፣ የገበያ አማራጮችን በማፈላለግ፣ የተሻለ ገቢ እንድናገኝ እና ከጉልት ወደ መደበኛ ሱቅ በመሸጋገር የንግድ ስራችን እዚህ ደረጃ እንዲደርሰ ከጎኔ ሆኖ ያበረታታኝና መቻሌን ይመሰክርልኝ የነበረ ምረኩዝ አለኝ።” አለችዉ ጭንቅላቷን በራስ መተማመን መንፈስ ወደላይ እና ወደታች እያንቀሳቀሰች።
“ምን እያልሸሀ ነዉ? ማንን ነዉ?” ብሎ ጠየቃት በአግራሞት መንፈስ እያያት።
ሳቅ እያለች በአመልካች ጣቷ ወደሱ ጠቆመች። እሱም እየሳቀ ወደራሱ አሰጠግቶ እቅፍ አደረጋት እና “ ይህንን እኮ በማድረጌ አንቺ ብቻ ሳትሆኚ እኔም ነኝ የተጠቀምኩት” አላት።
“እሱስ ልክ ነህ። መቼም ሁሉም ወንዶች እንዲህ የሚያስቡበት ጊዜ መምጣቱ አይርም” አለችዉ።
ሁለታቸዉም ተያይተዉ ተሳሳቁ። በወ/ሮ ውድነሽ በዚህ ትዝታ ውስጥ እያለች፤
“እትዬ!” የሚል ድምጽ አባነናት።
“ወይ” አለች በሃሳብ በነጎደችበት ሰረገላ ወደገሃዱ ዓለም እየተመለሰች።
ሰራተኛዋ ነበረች ምሳ እያቀራረበች የተጣራችው።
ወ/ሮ ውድነሽ በጣም ጠንካራ፣ በተስፋ የተሞላች እና ፈተና እንኳን ሲገጥማት ከጨለማ ዛሬ በስተጀርባ ብርሃን የሆነ ነገ እንዳለ የምታስብ ናት። በችግር ውስጥ ሆና ጥቃቅን መልካም አጋጣሚዎችን በመጠቀም ባገኘችው ቀዳዳ ሾልካ በመውጣት በህይወት መንገድ ላይ ጉዞዋን የምትቀጥል ሴት ናት። እንኳንስ ሴትነት አካል ጉዳተኝነት ለስኬት እንቅፋት ያልሆነባት ብርቱ የሆነች ሴት ናት። በመሆኑም የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን ያከፋፍሉበት ከነበረዉ ሱቅ በማሻሻል ያለቀላቸዉ የቆዳ ምርቶችን ለአገልግሎት ዝግጁ በማድረግ ‘በኢትዮጵያ የተሰራ’ የሚል ጽሁፍ እያተሙበት ወደ ውጭ መላክ ደረጃ ላይ ደርሰዋል። ምርቶቻቸዉ የበረካታ አገራት ገበያን ሰብረዉ መግባት የቻሉ ናችው። ድርጅታቸውን እሷ በስራ አስኪያጅነት ባለቤቷ ደግሞ በምክትል ስራ አስኪያጅነት ይመሩታል። አሁን ግን እሷ ሁለተኛ ልጃቸውን እርጉዝ በመሆኗ ወልዳ እስክትነሳ ባለቤቷ እሷን ተክቶ ድርጅቱን ይመራል።
ዛሬ ላይ ወ/ሮ ውድነሽ ህይወቷ ተቀይሯል። እንደዚህ አይነት ኑሮ እኖራለሁ ብላ አስባም አታውቅም። ስታስበዉ ለራሷም በጣም ትገረማለች። እሷ የሚገጥማትን ፈተናና ጫና በማለፍ ለበለጠ ውጤት መትጋት ላይ ነበር ሁል ጊዜም ትኩረቷ። ጥረቷም ፍሬ አፍርቶ አሁን ላይ ከራሷና ከቤተሰቧ አልፋ በድርጅታቸዉ ውስጥ ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል መፍጠር ችላለች።ሴቶች ሁሉ እንደሷ ጠነክረው በመስራት ከራሳቸውና ከቤተሰባቸዉ አልፈዉ ለሃገራቸው እድገት አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አጥብቃ ትሻለች። በዘር፣ በጎሳ፣ በሃይማኖት፣ በቀለም እና በጾታ ሳትለያይ የሰውን ልጅ ሁሉ በምትችለዉ አቅም መርዳት ትፈልጋለች። በርካቶችንም ባገኘችው አጋጣሚ በገንዘብና በሃሳብ በመደገፍ በህይወታቸዉ አንድ እርምጃ ወደፊት እንዲጓዙ ምክንያት ሆናላቸዋለች። ለዚህ ስኬቷ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተደረገላትን ድጋፍ እንደ ምክንያት ብትጠቅሰውም የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበር ሚና ግን የጎላ እንደሆነ ትገልጻለች ወ/ሮ ውድነሽ። በዋናነትም በማደራጀት፣ ስልጠና በመስጠት፣ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ እና የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸዉ በማድረግ ለርካታ ሴቶች ለውጤት መብቃት ማህበሩ የተጫወተዉ ሚና አሌ የማይባል መሆኑን በመጥቀስ ሁሌም ታመሰግናለች። ኧረ እንዲያዉም አንዳንዴ የአማራ ክልል ነጋዴ ሴቶች ማህበርን ‘የህይወት ጉዞ ማርሽ አስቀያሪ’ ትለዋለች። ብዙ ሴቶች የጥረታቸዉን ፍሬ እንዲበሉ ከጐኗቸዉ በመሆን ደግፏቸዋልና።


Read 2602 times