Monday, 06 April 2015 09:53

ኢትዮጵያ በሊዲያ ታፈሰ ለዓለም ዋንጫን በቃች

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(1 Vote)

    ከ2 ወራት በኋላ ካናዳ በምታዘጋጀው 7ኛው የሴቶች የዓለም ዋንጫ ኢትዮጵያዊቷ ኢንተርናሽናል ዳኛ ሊዲያ ታፈሰ በዋና ዳኝነት እንድትሳተፍ ተመረጠች። ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋ ለሴቶች ዓለም ዋንጫው በዋናና በረዳት ዳኝነት ከ49 አገራት የተውጣጡ 73 ያህል ዳኞችን ሹመት ከሳምንት በፊት አሳውቋል፡፡ በዋና ዳኝነት ከተሾሙ 22 ዳኞች መካከል አፍሪካን የወከሉት ሦስት ዳኞች ብቻ ሲሆኑ ከኢትዮጵያዊቷ ሊድያ ሌሎቹ ከዛምቢያና ከካሜሮን የተመረጡት ናቸው፡፡
የጅማ ልጅ የሆነችው ሊድያ ወደ ስፖርቱ የገባችው በቅርጫት ኳስ ተጨዋችነት ነበር፡፡ ለኦሮምያ ምርጥ ቡድን ስትጫወት ቆይታ ከዚያም በክለብ ደረጃ ለኪራይ ቤቶች ተጫውታለች፡፡  በ1989 ዓ.ም ላይ ወደ እግር ኳስ ዳኝነት መግባቷን ለስፖርት አድማስ የገለፀችው ሊዲያ ታፈሰ፤ ታዋቂው የዳኝነት ኢንስትራክተር ሽፈራው እሸቱ በጅማ ከተማ በቅርጫት ኳስ ለተመለከቷቸው ሴቶች የመጀመርያውን የዳኝነት ኮርስ በመስጠት መነሻ እንደሆኑላት ታስታውሳለች፡፡ የመጀመርያውን የዳኝነት ስራም በ1992 ዓ.ም በተደረገ የታዳጊ ውድድሮች ላይ በስኬት አከናውናለች፡፡ ከዚያ በኋላ በርካታ የዳኝነት ኮርሶችን እየወሰደችና በተለያዩ ውድድሮች በዋና ዳኝነት እየተመደበች ለ15 አመታት አገልግላለች፡፡ ከ1993 እስከ 2005 ዓ.ም ባሉት የውድድር ዘመናት በኢትዮጵያ የክለብ ውድድሮች በዋና ዳኝነት ያገለገለችው ሊድያ፤ በስፖርት ቤተሰቡ በልባምነት በምትመራቸው ጨዋታዎች እና ውሳኔዎቿ አድናቆት አትርፋለች፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ደረጃ በርካታ ትልልቅ ጨዋታዎችን በዋና ዳኝነት በመምራት ከፍተኛ ልምድ ማግኘቷን ለስፖርት አድማስ ስትገልፅም፤ ፌደሬሽን የፕሪሚዬር ሊግ ዳኞችን የመምረጫ መስፈርት ለሴቶች ዳኞች እንደ ወንዶች  150 ሜትርን በ30 ሰከንዶች መሮጥን በመመርያ ማውጣቱ እንድትቀጥል አላደረጋትም፡፡ ብዙዎቹ ሴት ዳኞች 150 ሜትርን በ35 ሰከንድ በአማካይ መሸፈን ይችላሉ ያለችው ሊድያ፤ እንደ ወንድ ዳኞች በ30 ሰከንዶች ፍጥነታቸውን ለሚያስመዘግቡ ሃላፊነቱ እንደሚሰጥ ተናግራለች፡፡
በፊፋ ኢንተርናሽናል ዳኝነት  ተመዝግባ በመስራት 10 ዓመታትን ያሳለፈችው ሊድያ በአፍሪካ ውድድሮች ያካበተችው ልምድም አለ፡፡ በናሚቢያ በተደረገው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች እና ከዚያም በኢኳቶርያል ጊኒ በተካሄደው የአፍሪካ ሴቶች የእግር ኳስ ዋንጫ እስከ ግማሽ ፍፃሜ ውድድሮችን መምራት ችላለች፡፡ በቅርቡ በፖርቱጋል በፊፋ የተሰጠውን የ1 ሳምንት ስልጠና ተከታትላ ወደ አገሯ የተመለሰችው ሊድያ፤ ኢትዮጵያን በዓለም ዋንጫ  ዋንጫ ለመወከል በመቻሏ ከፍተኛ ክብር እንደተሰማት ለስፖርት አድማስ ገልፃለች፡፡
ከወራት በፊት ኢኳቶሪያል ጊኒ ባስተናገደችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያዊው ኢንተርናሽናል አልቢትር ባምላከ ተሰማ በዋና ዳኝነት ተመርጠው እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት የኢትዮጵያ እግር ኳስ  በፊፋ የተሾሙ ኢንተርናሽናል ዳኞች ቁጥር እያደገ መምጣቱን ለመገንዘብ ይቻላል። በትልልቅ ዓለም አቀፍ ውድድሮች በዳኝነት መስራት በተለያዩ አህጉራዊና ዓለምአቀፍ ውድድሮች፣ ሥልጠናዎች ላይ ልምድ ለማግኘትና ለመካፈል የሚያስችል ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የኢንተርናሽናል ዳኞች ቁጥር በሁለቱም ፆታዎች 22 እንደደረሰ በፊፋ ድረገፅ ከቀረበው መረጃ ሲታወቅ 8ቱ ሴቶች ናቸው ፡፡ በፊፋ ፈቃድ ከተሰጣቸው 22 የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል አልቢተሮች መካከል 11 ያህሉ ዋና ዳኞች ሲሆኑ ሰባቱ ወንድ እንዲሁም አራት ደግሞ ሴት ዋና ዳኞች ናቸው፡፡ ከዚህ በታች በሁለቱም ፆታዎች በፊፋ ፈቃድ የተሰጣቸው የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ዳኞች ዝርዝር   ቀርቧል፡፡
    በወንዶች
      ዋና ዳኞች                       የትውልድ ዘመን         ኢንተርናሽናል ከጀምሮ
----------------------------------------------------------------------------------------
ሃይለየሱስ በለጠ ባዘዘው                1985                        2012
ግርማ ፊጋ ዘካርያስ                     1979                        2015
የማነብርሃን ካሳሁን ብሩክ              1983                        2015
ለማ ንጉሴ                                  1983                        2014
በላይ ታደሰ                                 1986                        2014
ባምላክ ተሰማ ወይሳ                      1980                         2009
ሃይለስላሴ አማኑኤል ወርቁ             1984                         2015

     ረዳት ዳኞች                     የትውልድ ዘመን            ኢንተርናሽናል ከጀምሮ
------------------------------------------------------------
ግዛው በላቸው ትግሌ                       1980                          2012
ክንዴ ሙሴ                                 1976                            2007
ተመስገን ሳሙኤል አታንጎ               1984                           2013
ተባበል ታደሰ ሸዋንግዛው                1978                           2012
ሃይለራጉኤል ወልዳይ                    1978                           2007
በላቸው ይታየው                         1971                             2004
ክንፈ ይልማ                                1977                           2011
-----------------------------------------------
በሴቶች
      ዋና ዳኞች                         የትውልድ ዘመን          ኢንተርናሽናል ከጀምሮ
አስማይኔ ፍቅረገነት አነሳሽ                    1989                             2015
ከተማ ኪዳኔ ጌራወርቅ                          1986                             2015
ፅጌ ሲሳይ                                         1975                             2005
ሊድያ ታፈሰ                                     1980                             2005

   ረዳት ዳኞች                            የትውልድ ዘመን            ኢንተርናሽናል ከጀምሮ
ትርሃስ ገብረዮሃንስ                             1982                              2007
ወይንሸት ካሳዬ አበራ                           1986                              2013
ወጋየሁ ዘውዱ ብዙአየሁ                       1985                               2013

Read 2526 times