Saturday, 21 March 2015 10:12

አፍሪካዊው የፖላንድ ፓርላማ አባል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

“የዛምቢያን ባህል ሳልረሳ የፖላንድን ባህል ተምሬአለሁ”

በትውልድ ዛምቢያዊ የሆኑት ፕሮፌሰር ኪለን ሙንያማ፤ የፖላንድ የፓርላማ አባል ሲሆኑ በተለያዩ ጊዜያት በፖላንድ በተካሄዱ ምርጫዎች ተወዳድረው በከፍተኛ ድምፅ በማሸነፍ ለመመረጥ በቅተዋል፡፡ የዩኒቨርስቲ ትምህርታቸውን እዚያው ፖላንድ የተከታተሉ ሲሆን በኢኮኖሚክስ የማስትሬትና የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ከፐዝናን ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኢኮኖሚክስ አግኝተዋል፡፡ ፕሮፌሰን ኪለን ባለፈው ሳምንት ከኢትዮ - ፖላንድ የፓርላማ ቡድን ጋር ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ጉብኝት አድርገዋል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት እቁባይ ከፕሮፌሰሩ ጋር በነበራት ቆይታ በጉብኝታቸው፣ በፖለቲካ ህይወታቸው፣ በአውሮፓ የኢኮኖሚ ቀውስና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ አነጋግራቸዋለች፡፡

     የኢትዮጵያ ጉብኝታችሁ በምን ላይ ያተኮረ ነው?
ጉብኝታችን ለኢትዮ-ፖላንድ የፓርላማ ቡድን በተደረገው ግብዣ መነሻነት የተከናወነ ነው፡፡ ግብዣው የተላከው በ2013 ዓ.ም ሲሆን ለጉዞው የሚያስፈልጉ ቅድመ ሁኔታዎችን በማሟላት አሁን ልንመጣ ችለናል፡፡ በጉብኝቱ የሚሳተፈው የልኡካን ቡድን በፓርላማ አባላቱ ብቻ ከሚወሰን ከኢትዮጵውያን ጋር በትብብር ለመስራት የሚፈልጉ   የተለያዩ የፖላንድ የቢዝነስ ኩባንያዎችን እንዲያካትት ባደረግነው ጥረት ስድስት ትላልቅ ኩባንያዎችን ይዘን ነው የመጣነው፡፡ የአፍሪካ ፖላንድ የንግድ ምክር ቤት ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት የሚፈልጉትን ኩባንያዎች በማደራጀት በኩል አግዞናል፡፡ ስለዚህ የጉብኝቱ አላማ ፖለቲካዊም ኢኮኖሚያዊም ነው ማለት ይቻላል፡፡
የኢትዮ - ፖላንድ የፓርላማ ቡድን ዓላማ ምንድን ነው?
ፓርላማዎች የሚመሳሰሉባቸውና የሚለያዩባቸው ነገሮች ይኖራሉ፡፡ የፖላንድ ፓርላማ የራሱ አወቃቀር አለው፡፡ ፓርላማው የተለያዩ ኮሚቴዎችና የፓርላማ ቡድኖች አሉት፡፡ የፓርላማው ቡድኖች ከተለያዩ አገሮች ፓርላማዎች ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ይሰራሉ፡፡ የፓርላማ አባላቱም የሚፈልጉትን አገር የፓርላማ ቡድን ይቀላቀላሉ፡፡ የቡድኖቹ አላማ በአገሮቹ መካከል ያለውን ግንኙነት በማጠናከር ላይ ያለመ ነው፡፡ ፓርላማችን ከአስራ አምስት የአፍሪካ አገሮች ጋር የፓርላማ ቡድን ግንኙነት አለው፡፡ የኢትዮ-ፖላንድ የፓርላማ ቡድንም አንዱ ነው፡፡ እኔ የኢትዮ-ፖላንድ፣ የዛምቢያ - ፖላንድ እና የኬኒያ - ፖላንድ የፓርላማ ቡድኖችን በሊቀመንበርነት እመራለሁ፡፡ በሌሎች በተለይ ከአፍሪካ ጋር የተገናኙና በፖላንድ አሜሪካን ቡድን፣ በብሪቲሽ ፖላንድ፣ በፖርቹጋል ፖላንድ የፓርላማ ቡድኖች ውስጥ በአባልነት እሳተፋለሁ። የፓርላማ ቡድኖቹ  ሊቀመንበር ወይም አባል ከሆኑባቸው አገሮች የሚመጡ ልኡካንን ተቀብሎ ያነጋግራል፣ በተለያዩ የጋራ ጉዳዮች ላይ በትብብር ይሰራል፡፡ የኢትዮ ፖላንድ የፓርላማ ቡድን አላማም ይኸው ነው፡፡
በብረታብረትና ኢንጂኒየሪንግ ኮርፖሬሽን ያደረጋችሁት ጉብኝት አላማ ምን ነበር?
አብረውን የመጡት ኩባንያዎች ስለ ስራቸው አስተዋውቀዋል፡፡ የድርጅታቸውን የሥራ ታሪክና በትብብር መስራት የሚፈልጉባቸውን መስኮችም ለብረታብረትና ኢንጂኒየሪንግ ኮርፖሬሽን ሰጥተዋል፡፡ አንዳንዶቹ መስኮች ኮርፖሬሽኑ  በጣም ትብብር የሚፈልግባቸው እንደሆኑ ተገንዝበናል፡፡ ጉብኝታችንና የተደረጉት ውይይቶች ጥሩ ውጤት ያመጣሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ ምክንያቱም አብዛኞቹ አብረውን የመጡት ኩባንያዎች የብረታብረትና ኢንጂኒየሪንግ ኮርፖሬሽን ከሚሰራቸው ስራዎች ጋር የሚገናኝ ስራ ላይ የተሰማሩ ናቸው፡፡
እንዴት ነው ወደ ፖለቲካው የገቡት? አፍሪካዊ ሆነው እንዴት የፖላንድ የፓርላማ አባል ለመሆን ቻሉ?
ሁሉም ነገር የሆነው የፖላንድ ዜግነት ካገኘሁ በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያ ወደ ፖላንድ የሄድኩት እ.ኤ.አ በ1981 ዓ.ም ለትምህርት ነበር። ከኔ ጋር አራት ዛምቢያውያን ስንሆን፣ አስራ አራት ኢትዮጵያውያንም አብረውን ነበሩ፡፡ አንድ አመት የቋንቋ ኮርስ ከወሰድኩ በኋላ  ትምህርቴን በመቀጠል በ1987 ነበር ያጠናቀቅሁት፡፡ በነገራችን ላይ ሁላችንም አገራችንን ስንለቅ የመጀመሪያ ዲግሪያችንን ይዘን ለመመለስ በሚል ነበር፡፡ ወደ አገራችን የተመለስነው ግን የማስተርስ ዲግሪያችንን ሰርተን ነበር፡፡ ትምህርቴን እንደጨረስኩ እዚያው ፖላንድ ስልጠና የማግኘት እድል ስለተሰጠኝ ስልጠናዬን ጨርሼ ነው ወደ ዛምቢያ የተመለስኩት። ለሶስት ወራት ያህል በዛምቢያ ንግድ እና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ውስጥ ከሰራሁ በኋላ እንደገና የዶክትሬት ዲግሪዬን ለመስራት እዚያው ፖላንድ ስኮላርሺፕ በማግኘቴ፣ በ1988 ዓ.ም ወደዚያው ሄድኩ፡
ኮሙኒዝም እየከሰመ የነበረበት ወቅት ነው። በዚህ የተነሳ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ሁኔታዎች እየተለወጡ ነበር፡፡ በመጨረሻም ኮሙኒዝም ሙሉ በሙሉ ሲወድቅ በሰዎች ህይወት ላይ ለውጥ መጣ። የዶክትሬት ዲግሪ የመመረቂያ ፅሁፌን ከማቅረቤ በፊት የዩኒቨርሲቲ መምህር ሆኜ ተመደብኩ፡፡ በ1999 ዓ.ም ደግሞ የፖላንድ ዜግነት አገኘሁ፡፡
ይኼኔ ነው ወደ ፖለቲካው የገቡት?
በ2002 ዓ.ም የአካባቢ ምርጫ ይደረግ ነበር፡፡ የዲስትሪክት (አውራጃ) ሀላፊው ለዲስትሪክት ምክር ቤቱ እጩ ሆኜ እንድቀርብ ጥያቄ ሲያቀርብልኝ በጣም ነበር ያስገረመኝ፡፡ ፖለቲካ ውስጥ የመግባት ምንም አይነት ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ እዚያ ብዙ አመታትን ያሳለፍኩ ብሆንም ምርጫ ተወዳድሬ አሸንፋለሁ ብዬም አስቤ አላውቅም፡፡ ለሃላፊው  “ምርጫ እኮ የመራጮች ድምፅ ነው” ስለው፤ “ምርጫውን ተወዳድረህ ማሸነፍ ትችላለህ፤ ስለዚህ መወዳደር አለብህ” ብሎ ገፋፋኝ፡፡ እንግዲህ የሚሆነውን እናያለን ብዬው ተስማማሁ፡፡ ምንም አይነት የምረጡኝ ቅስቀሳ አላደረግሁም፣ ድምፅ የማገኝ ከሆነ የራሴንና የባለቤቴን ሁለት ድምፅ ብቻ እንደሚሆን በመገመት ወደ ምርጫው ገባሁ። ግምቴ ግን በጣም የተሳሳተ ነበር፤ አብላጫ ድምፅ በማግኘት ምርጫውን አሸነፍኩ፡፡ ያልጠበቅሁት ውጤት ስለነበር በጣም አስገረመኝም አስደሰተኝም።
ከዚያ በኋላ መራጮች ከኔ የሚፈልጉትን መስጠት እችላለሁ ወይ የሚለው ነገር የሚያሳስበኝ ሰው ሆንኩ፡፡ የተመረጥኩት ለአራት አመት ስለነበር የስራ ዘመኑ ሲያበቃ፣ ራሴን ለአውራጃ ምክር ቤት  ሳይሆን ከሱ ከፍ ወዳለው የክልል ፓርላማ እጩ አድርጌ አቀረብኩ፡፡ የክልል ፓርላማው ተመራጭ ለመሆን ደግሞ የፖለቲካ ፓርቲ አባል መሆን ያስፈልጋል፡፡
ስለዚህ “ሲቪክ ፕላትፎርም” የተባለውን የሊበራል ዲሞክራቲክ ፓርቲ ተቀላቀልኩና በ2006 ዓ.ም በተደረገው ምርጫ አሸንፌ የክልል ፓርላማ ገባሁ፡፡ ከአራት  አመት በኋላ እንደገና በክልል ምርጫ አሸነፍኩ፡፡ በ2011 ዓ.ም በተደረገው አገራዊ የፓርላማ ምርጫ ፓርቲዬ እንድወዳደር እጩ አድርጎ ሲያቀርበኝ “ተወዳድሮ ማሸነፍ ይችላል ብላችሁ ካመናችሁ እወዳደራለሁ” ብዬ ተስማማሁ፡፡ የፖላንድ የፓርላማ ስርአት ተመጣጣኝ ውክልና (ፕሮፖርሽናል ሪፕረሰንቴሽን) ስለሆነ እኔ በምወዳደርበት የምርጫ ጣቢያ አራት የኔን የፓርቲ ወኪሎች ጨምሮ ዘጠኝ ተወዳዳሪዎች ነበርን፡፡ ከኔ ፓርቲ አባላት ውስጥ እኔ በማሸነፌ ፓርላማውን ተቀላቀልኩ፡፡
መራጩ ህዝብ ከእርስዎ የሚፈልገውን አሟልቻለሁ ብለው ያስባሉ?
ይህን ሊመልሱ የሚችሉት የመረጡኝ ሰዎች ናቸው፡፡ በመጪው ጥቅምት ወር በሚካሄደው ምርጫ ላይም ለመወዳደር አስቤያለሁ፡፡ ያኔ የማገኘውን ድምፅ አይቼ መናገር እችላለሁ፡፡ በእኔ በኩል ለተመረጥኩበት ቦታ ብቻ ሳይሆን ለአገሪቱ ማድረግ የምችለውን ሁሉ አድርጌያለሁ ባይ ነኝ፡፡
በአሁኑ ወቅት በአውሮፓ  ያለውን የኢኮኖሚ ቀውስ እንዴት ይገልፁታል?
አውሮፓን በአራት መክፈል እንችላለን፡፡  38 አገሮችን የሚያካትተው የአውሮፓ ህብረት፣ 19 አገሮችን ያቀፈው ዩሮላንድ የሚባለው የአውሮፓ ሞኒተሪ ህብረት፣ የአውሮፓ የነፃ ገበያ ቀጠና አገሮች እና የአውሮፓ ህብረት አገሮች ያልሆኑት የምስራቅ አውሮፓ አገሮች እነ ራሺያ፣ ዩክሬይን፣ቤላሩስ፣ ሰርቢያ፣ሞንቴኔግሮ፣ ቦስኒያሄርዞጎቪኒያ  የሚገኙበት ምድብ አለ፡፡ ከኢኮኖሚ ጋር በተያያዘ በዋነኛነት የማተኩረው ዩሮን በመገበያያ ገንዘብ በሚጠቀሙ  ዩሮላንድ ወይም የአውሮፓ ሞኒተሪ ህብረት በሚባለው ምድብ ላይ ባሉ አገሮች ነው። የኢኮኖሚ ቀውሱ የተፈጠረው ገንዘብ በአግባቡ ካለመጠቀም ጋር በተያያዘ ሳይሆን በአባል አገሮቹ በተለይ በግሪክ፣ ስፔን ፣ ፖርቹጋል፣ ጣሊያንና  አየርላንድ ውስጥ በተከሰቱ ውጣውረዶች ሳቢያ ነው፡ አገራቱ የኢኮኖሚ እድገታቸው መሻሻልን ቢያሳይም አሁንም ችግሮች አሉባቸው፡፡  ለምሳሌ ግሪክ  የበጀት እጥረትና ከፍተኛ የዕዳ ጫና አለባት፡፡ የነዚህ አገሮች እጣ ፈንታ የሚወሰነው በዩሮ ጥንካሬ ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ የዩሮ የመግዛት አቅም ማጣት ይበልጥ ችግሩን ያወሳስበዋል፡፡ አንድ ሰው ከሰውነት ክፍሉ የተጎዳ ቦታ ካለ፣ ያንን ክፍል መቆጣጠር መከታተል ይጠበቅበታል፡ ግሪክ በአሁኑ ወቅት ልዩ ክትትል የሚያስፈልጋት የህብረቱ አገር ሆናለች። አዲሱ የግሪክ መንግስት አገሪቱ በህብረቱ ውስጥ የሚጠበቅባትን ግዴታ ለመፈፀም ጊዜ እንዲሰጣት እየተደራደረ ነው፡፡ ከዩሮላንድ ውጪ ያሉ አገሮችን ስናይ ለምሳሌ ፖላንድ፣ ሀንጋሪ፣ ቼክ ሪፐብሊክ፣ ስዊድንና ብሪቴይን አፈፃፀማቸው የከፋ አይደለም። እኛን (ፖላንድን) ብታይ እያደግን ነው፡፡
የአውሮፓ ህብረትና አይኤምኤፍ፤  ስፔይንና  ግሪክ የፖሊሲ ማሻሻያዎችን በማድረግ ብድር እንዲያገኙ ቢጥሩም በተለይ በግሪክ ስልጣን የያዘው አክራሪው ግራ ፓርቲ ለማሻሻያዎቹ ዝግጁ አይደለም፡፡ አይኤምኤፍና የአውሮፓ ህብረት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ብድር እንዲለቁ ይፈልጋል። በፍላጐቱ መሰረት ምላሽ ቢያገኝ ዕዳውን የሚከፍለው ማነው?
አገሮቹ ኢኮኖሚያቸው የሚያገግምበትን መንገድ መፈለግ አለባቸው፡፡ የገንዘብ ብድርን በተመለከተ ቅድመ ሁኔታ አስፈላጊ ነው፡፡ የግሪክን ሁኔታ ስናይ አክራሪነት ብቸኛ መፍትሄ አይደለም፤ ለስለስ ማለት ያስፈልጋል፡፡ የአለምአቀፍ የገንዘብ ተቋም አባል ለመሆን ተቋሙ ለሚያስቀምጠው ህግ ተገዢ መሆን ይገባል፡፡ ዕዳውን ማነው የሚከፍለው ላልሽው… ከፋዮቹ ዜጎች ናቸው፡፡ እንግዲህ ግሪክ አትሸጥ፡፡ በዚህም የተነሳ ከፍተኛ ታክስ በመጣልና በመሳሰሉት መንገዶች ዜጎች ዕዳውን ይከፍላሉ፡፡ አፍሪካ እንደ አህጉር 300 ቢሊዮን ዩሮ ቢሰጣት ምን ያህል መሰረተ ልማት ሊገነባ እንደሚችል መገመት አያቅትም፡፡ ግሪክ 10 ሚሊዮን የማይሞላ ህዝብ ይዛ ይህን ያህል ገንዘብ ነው የጠየቀችው፡፡  ከዚህ አንፃር በአገሪቱ ጠንካራ የሆነ የሀላፊነት ስሜት፣  የተጠያቂነት ስርአት ሊኖር ይገባል፡፡
በአሁኑ ወቅት የአውሮፓ ፖለቲካ እየተለወጠ ነው፡ አክራሪ የግራ ፓርቲዎች በግሪክና በስፔይን እንዲሁም አክራሪ የቀኝ ኃይሎች በፈረንሳይና በእንግሊዝ፤ ብሔርተኞች ደግሞ በሀንጋሪ እየተጠናከሩና ምርጫዎችንም እያሸነፉ ነው፡፡ የዚህ አንደምታው ምንድን ነው?
አክራሪ ሀይሎች በአውሮፓ እየተጠናከሩ የመምጣታቸው ጉዳይ ምቾት የሚሰጥ አይደለም። ለዚህ ሁኔታ መከሰት  ብዙ ምክንያቶች አስተዋፅኦ አድርገዋል፡፡ አውሮፓ ለአውሮፓውያን ብቻ እንድትሆን እንዲሁም የአውሮፓ የመገበያያ ገንዘብ አውሮፓ ውስጥ ብቻ በስራ ላይ እንዲውል የሚፈልጉ ወገኖች አሉ፡፡  አውሮፓውያን ብቻ ሳይሆኑ ከተለያዩ ባህሎች እንዲሁም  ከሀይማኖት ጋር በተያያዘ ደስተኞች ያልሆኑ  ወገኖችም አሉ። በኔ አስተያየት አለም አንድ እየሆነ በመጣበት በግሎባላይዜሽን ዘመን የራሴ በሚል ተከልሎ መኖር አይቻልም፡፡ አሁን የሚያስፈልገው የራስን ከልሎ መያዝ ወይም ሌሎችን አግልሎ መኖር ሳይሆን ውህደት ነው፡፡
እኔ “ዘ ፓርላሜንታሪ አሴምብሊ ፎር ዘ ካውንስል ኦፍ ዩሮፕ” አባል ነኝ፡፡ 47 አገሮች በአባልነት ይገኙበታል፡፡ በስደተኞች ጉዳይና በተፈናቀሉ ሰዎች ዙሪያ እንወያያለን፡፡ አክራሪዎቹ እየጠነከሩ ነው፡፡ በግሌ ከባህልና ከሀይማኖት ጋር የተያያዙ  ግጭቶች መቀነስ አለባቸው ብዬ አምናለሁ፡፡ “ሮም ስትኖር ሮምን ምሰል” ይላል ተረቱ፡፡  የራስ ባህል ይረሳ ማለት አይደለም፡፡ እኔ የዛምቢያን ባህሌን ሳልረሳ የፖላንድን ባህል  ተምሬያለሁ፡፡ ፖላንድ ውስጥ በተካሄደ ጥናት፤ አክራሪዎች ከ7 በመቶ በታች ናቸው፡፡ ሁሉም ነገር ሚዛን ሲኖረው ነው ጥሩ የሚሆነው፡፡
በምስራቅ አውሮፓ በዘረኝነት ስማቸው በቀዳሚነት ከሚጠሩ አገሮች ውስጥ ፖላንድ አንዷ ናት፡፡ እንዲያውም ፖላንዳውያን ጥቁሮችን “ሙዢን” ብለው ነው የሚጠሩት፡፡ እርስዎ ደግሞ በፖላንድ ፓርላማ ውስጥ እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ እስቲ ስለዘረኝነቱ ጉዳይ ይንገሩኝ?
ሙዚን ማለት ኒገር ማለት ነው፡፡ ቃሉ እንደ አጠቃቀሙ ሁኔታ ነው ትርጉም የሚሰጠው። የሚቀርብሽ ሰው ሙዢን ሲልና እንደ ስድብ የሚጠቀምበት ሰው ሲያጋጥም ትርጉሙ ይለያያል። ሙዚን ማለት ቆዳው የጠቆረ ማለት ነው፡፡ ፖላንዳውያን እርስ በርስ ሲጠቀሙበት ችግር የለውም፤ ጥቁር የሆኑ ሰዎች ሙዢን ሲባሉ ግን የሚያስቀይም  ይሆናል፡፡  ይህ ቃል ጥቅም ላይ እንዳይውል የምንፈልገው አሉታዊ ነገር ስላለው ነው፡፡ እኛ ከሙዚኖች በአንድ መቶ አመት ያህል እንደምንርቅ ይነገራል፡፡ ይህ አባባል ሌሎችን ስለሚያስቀይም ጥቅም ላይ ባይውል እንመርጣለን፡፡ እኔ ተማሪ ሆኜ በመጣሁበት ጊዜ ከዚህ ጋር በተያያዘ እንደማንኛውም ወጣት ተበሳጭቼና ግብግብ ገጥሜ አውቃለሁ፡፡ ያ ማለት ግን ፖላንዳውያን ዘረኞች ናቸው ማለት አይደለም። በመጀመሪያ ምርጫ ተወዳድሬ  እንዳሸነፍኩ ከዋርሶ ድረስ  እኔን ኢንተርቪው ለማድረግ የመጣ ጋዜጠኛ ነበር፡፡ ሰዎችን ቃለመጠይቅ ሲያደርግ፤ “ምን ያስገርምሀል? ከዋርሶ ድረስ መጥተህስ ለምን ቃለ መጠይቅ ልታደርግልን ፈለግህ? እሱ ከኛ ጋር የኖረ የኛ ሰው ነው፤ ስለዚህ  መረጥነው” በማለት መልሰውለታል። “እኛ የመረጥነው ኬለንን እንጂ ነጭ ወይም ጥቁር ብለን አይደለም” ብለውታል፡፡ አንቺ እንዳልሽው ስለ ፖላንድ ከዘረኝነት ጋር ተያይዘው ብዙ ነገሮች ይፃፋሉ፤ ነገር ግን የፖላንድ ፓርላማ እኔና አንድ ናይጄሪያዊን በፓርላማ አባልነት ይዟል።  ይህን ምን ትይዋለሽ?

Read 2458 times