Monday, 09 March 2015 11:22

“ሁሉም የጋዜጣው ኮፒዎች አሉኝ”

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

   በሙያዬ የፅንስና የማህፀን ሀኪም ነኝ፡፡ ለመፅሀፍና ለጋዜጣ ልዩ ፍቅር ስላለኝ ላለፉት በርካታ ዓመታት አያሌ መፅሀፍትን እንዲሁም ጋዜጦችን አንብቤአለሁ፡፡ ጋዜጣ ሳነብ አልመርጥም፡፡ በተለይ አዲስ አድማስን አንብቤ ለአዟሪው መልሼ አላውቅም፡፡ መጀመሪያውኑም አዲስ አድማስን ስገዛ ርዕስ እና የፊት ገፅ አልመለከትም፡፡ መግዛት ግዴታዬ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ፡፡ ገና ብርቱካናማውን የጋዜጣውን ሎጐ ስመለከት የሆነ ደስ የሚል ነገር ይሰማኛል፡
አዲስ አድማስ ባለፉት 15 ዓመታት እጅግ በርካታ ቁም ነገሮችን፣ አስተማሪና አዝናኝ ጉዳዮችን ሲያስኮመኩመን ኖሯል፡፡ “የእኛ ሰው በአሜሪካ”፣ “እንጨዋወት”---የመሳሰሉት አምዶች አይረሱኝም፡፡ መስራቹን አቶ አሰፋ ጐሳዬን ነፍሱን በገነት ያኑራት እላለሁ፡፡ እሱ ካለፈም በኋላ የጋዜጣው ህልውና እንዲቀጥል ያደረጉትን ቤተሰቦቹን ማመስገን እወዳለሁ፡  ጋዜጣው ከመነሻው ጀምሮ ቢታይ፤ በዘርፉ ጥናትና ምርምር ለሚያደርጉ፣ ወደ ጋዜጣ አሳታሚነት ለሚገቡ፣ በጋዜጠኝነት በተለይ በህትመት ሚዲያ ላይ ትምህርት ለሚከታተሉ ሁሉ አይነተኛ ግብአት ነው ባይ ነኝ፡፡
የእኛም ማህበር (ኢሶግ) በጋዜጣው ላይ “ላንቺና ላንተ” የተሰኘ ቋሚ አምድ አለው፡ በዚህ ዓምድ በሚወጣ ፅሁፍ በርካቶችን ማስተማር ተችሏል፡፡ በአገራችን እንደ ልብ ጋዜጣ በማይገኝበትና እንደ ልብ መፃፍ በማይቻልበት ሁኔታ እንኳን አዲስ አድማስ ሁሉን ተቋቁሞ፣ ሁሉን እንዳመሉ ችሎ መረጃ ያቀብለናል፡፡ በውስጡ ደግሞ እንደ ገጣሚና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ እንደነ አብደላ ዕዝራ፣ እንደነ ኤፍሬም እንዳለ እና መሰል ሳተና ብዕረኞች አሉት፡፡ ቀድሞም በርካታ ብርቱ ብርቱ ፀሐፊዎች ነበሩ፡ ያን ጊዜም አሁንም ጋዜጣውን አነበዋለሁ፡፡ ወንዱ ልጄ ሶፍትዌር ኢንጂነር ቢሆንም የእኔው ዓመል ተጋብቶበት፣ ቅዳሜ ቅዳሜ አዲስ አድማስን ብብቱ ስር ሸጉጦ መምጣት ከጀመረ ረዘም ያለ ጊዜ ሆኖታል፡፡ ታዲያ እሱ ገዛ ብዬ እኔ መግዛቴን አልተውም፡፡ በዚህ ምክንያት ከመጀመሪያው እትም አንስቶ  የአድማስ ኮፒ አለኝ፡፡
አዲስ አድማስ ጋዜጣን ተውሶ የማይመልስልኝ ጠላቴ ነው፡፡ ለስራ ብዙ ጊዜ ወደተለያዩ የአፍሪካና የአውሮፓ አገራት ስሄድ፣ ደንበኛዬ ጋዜጦቹን በጥንቃቄ ያስቀምጥልኛል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ ከአገር ስወጣ ዌብሳይቱ ላይ ማንበብ መቻሌ ያስደስተኛል፡፡ ብቻ… በአዲስ አድማስ ደስተኛ ነኝ፡፡ ከአዲስ አድማስ ቀጥሎ የማንበብ ጥሜን የሚያረካልኝ የነበረውና እንደ ሃምሌ ፀሐይ ብልጭ ብሎ የጠፋው “አዲስ ነገር” የተባለ ጋዜጣ ነበር፡፡ ጋዜጣውም ተዘጋ፤ አዘጋጆቹም ኮበለሉ፡፡
ለዚህ ነው ከላይ እንደ ልብ መናገርና መፃፍ በማይቻልባት ኢትዮጵያ፤ ትችቱንም፣ ትዝብቱንም፣ ወቅታዊ ትኩሳቶችንም አለዝቦ በማቅረብና ማህበረሰቡን በማስተማር ሲተጋ 15 አመት መጓዙ አድማስን ያስመሰግነዋል የምለው፡ አሁንም በርካታ 15 ዓመቶችን ያክብር፡ አዘጋጆቹንም ፀሐፊዎቹንም ኢትዮጵያንም ፈጣሪ ይባርክ፡፡
(ስማቸው እንዲገለፅ ያልፈለጉ)

Read 2011 times