Saturday, 30 August 2014 11:01

“ጳጉሜን ለጤና” የነፃ ምርመራ ለ5 ቀናት ይካሄዳል

Written by 
Rate this item
(4 votes)

እናት ልጃቸው ያለቅጥ ማምሸቱ አስግቷቸዋል፡፡ ይወጣሉ ይወርዳሉ፡፡ የ26 ዓመት ልጃቸው መጠጥ አይቀምስም፣ ብዙ ጓደኞችም የሉትም፡፡ ሁሌም በጊዜ ወደቤቱ የመግባት ዓመል ነበረው፤ዛሬ ግን የበላው ጅብ አልጮህ አለ፡፡ (የዛሬ 2 ዓመት ገደማ ነው) እናት ወገባቸውን በነጠላቸው አስረው እያቃሰቱ፣ ወደ አራዳ ክ/ከተማ ፖሊስ በመሄድ፣ ልጃቸው እንደጠፋባቸውና የሞባይል ስልኩም እንደማይሰራ እንባ በጉንጫቸው እየፈሰሰ ለፖሊስ ተናገሩ፡፡ ስሙንና መልኩንም በደንብ አብራሩ፡፡
ፖሊስ ይሄኔ የልጁ ማንነት ገባው፡፡ ወጣቱ የመኪና አደጋ ደርሶበት፣ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ድንገተኛ ክፍል ገብቶ፣ ሃኪሞች አስቸኳይ የሲቲስካን ምርመራ እንዲያደርግና ውጤቱን ፖሊሶች ይዘው እንዲመጡ አዘው ነበር፡፡ ፖሊሶችም አደጋው የደረሰበትን ወጣት፣ ወደ “ውዳሴ ዲያግኖስቲክ የምርመራ ማዕከል” በመውሰድ ምርመራው በነፃ እንዲያገኝ አደረጉ
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአራዳ ክ/ከተማ ትራፊክ ጽ/ቤት የሥራ ኃላፊ ስለውዳሴ ዲያግኖስቲክ በሰጡት አስተያየት፤ “ምንም እንኳን ወጣቱ በደረሰበት ከባድ የመኪና አደጋ ከሞት ባይተርፍም ማዕከሉ ግን አስቸኳይ ምላሽ ሰጥቶት ነበር፤ ከእኛ ጋር በመተባበር በሚሰሩት ስራ ከፍተኛ አድናቆት አለን” ብለዋል፡፡
እንደዚህ መሰል አደጋዎች፣ አሊያም በተፈጥሮ በህመም ምክንያት በሃኪም የሲቲስካን ምርመራ ሲታዘዝ ዋጋው ከሌሎች ምርመራዎች ስለሚወደድ ብዙ ሰዎች እድሉን ሳያገኙ ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡ በዚህ ረገድ ያለውን የሰዎች ችግር ለመቅረፍ የሚሰራው “ውዳሴ ዲያግኖስቲክ የምርመራ ማዕከል”፤ ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መርህ፤ ከ500 በላይ ለሆኑ ሰዎች ነፃ የሲቲስካን ምርመራ እንደሚያደርግ የማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት ሃይሉ አስታወቁ፡፡ ማዕከሉ በ2001 ዓ.ም ተቋቁሞ 65 ያህል ሰራተኞችን እንደሚያስተዳድር የገለፁት ስራ አስኪያጁ፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት መርህ ከ5ሺህ በላይ ለሆኑ የሲቲስካን ምርመራ ፈላጊዎችና በራሳቸው ለመመርመር አቅም ለሌላቸው ሰዎች አገልግሎቱን እንደሰጠ አብራርተዋል፡፡
“አንድ ለትርፍ የተቋቋመ ድርጅት ከሚያገኘው ነገር ላይ አቅም የሌላቸውን መርዳትና ማህበራዊ ኃላፊነቱን መወጣት አለበት” ያሉት አቶ ዳዊት፤ በየአመቱ በጳጉሜ ወር በዘመቻ መልክ ነፃ የምርመራ አገልግሎት እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡ የማዕከሉ የማርኬቲንግ እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሮ ሰብለ ኃይሉ እንደገለፁት፤ ከአራዳ ክ/ከተማ ትራፊክ ፅ/ቤት ጋር በመተባበር የመኪና አደጋ ደርሶባቸው የሲቲስካን ምርመራ ለሚስፈልጋቸው ሰዎች፣ በየትኛውም ሰዓትና ቀን ነፃ የምርመራ አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ “ዓመቱን ሙሉ ቢያንስ ከ4-5 ሰው በየቀኑ በተለያየ ምክንያት ምርመራው አስፈልጎት ሲመጣ ነፃ ምርመራ ያገኛል” ያሉት ወ/ሮ ሰብለ፤ ጳጉሜ ላይ በዘመቻ መልክ ለብዙ ሰዎች አገልግሎቱን የምንሰጠው ሌላውም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ምሳሌ ለመሆን ነው ብለዋል፡፡
“ምንም እንኳ ለትርፍ የተቋቋምን ብንሆንም መልካም ስራ ኪሳራ የለውም” ያሉት ወ/ሮ ሰብለ፤ ሰውን ማትረፍ መቻል በራሱ ትርፍ ነው ብለዋል፡፡ ማዕከሉ ባለፈው ዓመት ጳጉሜ ለ500 ሰዎች ነፃ ምርመራ ለማድረግ ጥሪ አቅርቦ፣ 950 ሰዎች መመዝገባቸውንና ሁሉም ነፃ ምርመራውን እንዳገኙ ተናግረዋል፡፡ የማዕከሉ ዋና ስራ አስፈፃሚ ቃለክርስቶስ ሃይሉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫም፤ ማንኛውም የአገልግሎቱ ፈላጊ የሚመለከተው የመንግስት አካል በግሉ ለመርመር እንደማይችል ጠቅሶ ደብዳቤ ከፃፈለትና ሃኪም ምርመራው ያስፈልገዋል ብሎ ከመሰከረ፣ 500 ቢባልም የመጣው ሁሉ መመርመሩ አይቀርም ብለዋል፡፡
“ውዳሴ ዲያግኖስቲክ” በዚህ የበጎ አድራጎትና ማህበራዊ ኃላፊነትን የመወጣት እንቅስቃሴው እንደሚቀጥል የገለፁት ስራ አስኪያጁ፤ ማዕከሉ በሚገኝበት አራዳ ክ/ከተማ  ነዋሪ ለሆኑ ታካሚዎች 20 በመቶ የክፍያ ቅናሽ እንደሚደረግላቸው ተናግረዋል፡፡ ማዕከሉ ከዚህም በተጨማሪ ለክ/ከተማው ነፃ የአምቡላንስ አገልግሎት ይሰጣልም ተብሏል፡፡
ለነፃ ምርመራ ጳጉሜን ለምን መረጣችሁ በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ ዳዊት ሲመልሱ፤ “ጳጉሜ አሮጌው አመት አልቆ ወደ አዲስ አመት መሸጋገሪያ እንደመሆኑ መጠን፣ ሰዎች ነፃ ምርመራ አግኝተው በተስፋና በደስታ አዲሱን ዓመት እንዲቀበሉ የበኩላችንን ለማድረግ አስበን ነው” ብለዋል፡፡

Read 2741 times