በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕም ተሳታፊ ይሆናል፡፡ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በአህጉር ደረጃ በሚያደርጓቸው ጨዋታዎች በተለይ በሜዳቸው አዲስ አበባ ስታድዬም አስደናቂ ውጤት ሊያስመዘግቡ ይጠበቃሉ፡፡ ይህ ሊሳካ የሚችለው በክለቦቹ የሚደረግ ጠንካራ የዝግጅት ትኩረት ሲሆን ዋናው ግን የሁለቱም ደጋፊዎች ህብረት ነው፡፡ ስታድዬሙ ለዚህ ሁኔታ ምን ያህል ተዘጋጅቷል፡ ባለፈው ሰሞን የተደረገው የአሸናፊዎች አሸናፊ የደርሶ መልስ ጨዋታዎች በታየው ሁለገብ ስርዓት አልበኝነት የጋራ ስምምነት ካልተደረገ ግን ያሳስባል፡፡
የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የውዝግብ ድራማ እሹሩሩ ማለት አያስፈልግም በማለት አንዳንድ ስፖርት አፍቃሪዎች አስተያየት እየሰጡ ናቸው፡፡ በሱፐር ካፑ የደርሶ መልስ ጨዋታዎች በአዲስ አበባ ስታድዬም የገቡ የሁለቱ ክለቦች ደጋፊዎችና በሜዳ ላይ የክለቦቹ ተጨዋቾች ያሳዩት ስርዓት አልበኝነት በገሃድ ያሳያው እግር ኳስ በእድገቱ ከመዳከም ሌላ በአሳሳቢ ችግር መውተብተቡን ነው ፡ ሁለቱ ጨዋታዎች ላይ ደጋፊዎች እርስ በራሳቸው ካደረጉት መዘላለፍ ባሻገር የተቃራኒ ክለብ አመራሮችና ተጨዋቾችን በመሳደብና አላግባብ በማንጓጠጥ ስታድዬሙን የስርዓት አልበኝነት መድረክ ሲያደርጉት ተስተውሏል፡፡ የሁለቱም ክለብ ደጋፊዎች በተለይ ጨዋታውን በሚመሩት ዳኞች ላይ የሚያዘንቡት ስድብ ብዙዎችን ያሳዘነ ሲሆን የክለቦቹ ተጨዋቾች በሜዳ ላይ በተደጋጋሚ ርስበራስ ለጠብ በመጋበዝ፤ ዳኛን ከቦ በማዋከብ እና በመሳደብ ያሳዩት ባህርይ ስታድዬም ለገባ ጨዋ ስፖርት አፍቃሪ ብቻ ሳይሆን ግጥሚያዎቹን በቀጥታ ስርጭት በቴሌቭዥን ለታደመ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ተስፋ መቁረጥን ፈጥሯል፡፡
በሁለቱ ቡድኖች ግጥሚያ ለ20 ዓመታት የዘለቀው ስርዓት አልበኝነት የአገራችንን እግር ኳስ ውድቀትን የሚያፋጥን መሆኑ የሁለቱን ክለቦች ባለድርሻ አካላት የሚያስጠይቅ ሊሆን ይገባል ። እነዚህ ሁለት አንጋፋ ክለቦችና ተጫዋቾች ሞያቸውን፣ ቡድናቸውን፣ እና ተመልካቹን አክብረው ለስፖርቱ እድገት የሚበጅ ጨዋታ እንዲያሳዩን እንጠይቃለን።