Saturday, 17 August 2013 11:07

የቅድስት ሥላሴ ኮሌጅ መምሕራን አላግባብ ከመኖርያ ተባረርን አሉ

Written by  መልካሙ ተክሌ
Rate this item
(0 votes)

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ መምህራን በተማሪዎችና በአስተዳደር መካከል የነበረው ውጥረት እንዲረግብ ጥረት በማድረጋችን በኮሌጁ ቅጽር ግቢ ከሚገኙ መኖርያዎቻችን አለአገባብ ልቀቁ ተብለናል አሉ፡፡ በኮሌጁ አስተዳደር እና በተማሪዎች መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የመማር ማስተማር ሂደቱ ዘንድሮ ብቻ ሁለት ጊዜ ተቋርጦ የቆየ ሲሆን ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ ተማሪዎች ባሰሙት ተቃውሞ ከመንበረ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት በተጻፈ ደብዳቤ መደበኛ ትምሕርት እስከ መስከረም 2006ዓ.ም እንዲቋረጥ ተደርጓል፡፡ ይሁንም እንጂ የኮሌጁ መምህራን እና ሌሎች ግለሰቦች ባደረጉት ጥረት የዘንድሮ ተመራቂ ተማሪዎች ምረቃ ባለፈው ሐምሌ 27 የተከናወነ ሲሆን መምህራኑ ልዩነት ለማጥበብ መሞከራችን የተማሪዎቹ ወገንተኛ ተደርገን በመቆጠር አላግባብ ከመኖርያ ቤታችን እንድንለቅ ተደርገናል ብለዋል፡፡
ስለ ጉዳዩ የጠየቅናቸው ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አንድ የኮሌጁ መምሕር ራሳቸውን ጨምሮ ከ5 እስከ 15 ዓመት በኮሌጁ ቅጽር ግቢ የኖሩ መምህራን እንዳሉ ገልፀው ነሀሴ 8 ተጽፎ ነሀሴ 9 ለመምህራኑ በተሰጠ ደብዳቤ ቤቶቹን በ20 ቀናት ልቀሉ ተብለናል ብለዋል፡፡
ሌላው ለአዲስ አድማስ አስተያየት የሰጡ መምሕር በበኩላቸው ቤቶቹ ለእድሳት ይፈለጋሉ ቢባልም ምትክ መኖርያ ሳይዘጋጅልን በተለይ በጾምና በክረምት ልቀቁ መባላችን አግባብነት የለውም ብለዋል፡፡
የኮሌጁን አስተዳደርም ሆነ የበላይ ጠባቂውን ብፁዕ ዶክተር አቡነ ጢሞቴዎስን ለማግኘት ያደግነው ጥረት ባይሳካም ለኮሌጁ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ለመምህራኑ የቤት አበል ተሰጥቶ ግቢውን እንዲለቁ ቀደም ብሎ ብሎ የታሰበበት እንደሆነ ገልፀው በድንገት ውጡ መባላቸው አግባብነት የለውም ብለዋል፡፡

Read 18129 times