Saturday, 17 August 2013 11:07

“ሆራይዘን ቢዩቲፉል” ፊልም ውዝግብ አስነሳ

Written by  ማህሌት ፋሲል
Rate this item
(0 votes)

የብሉ ናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚ ተማሪዎች ክፍያ ተከለከልን አሉ
በብሉ ናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚና በስዊዘርላንዱ ቴሌ ፊልም ጂኤምቢኤች ትብብር የተሰራው “ሆራይዘን ቢዩቲፉል” የተሰኘ ፊልም ውዝግብ አስነሳ፡፡ በፊልሙ ላይ የተሳተፉ ተማሪዎች አካዳሚው የሚገባንን ክፍያ ከልክሎናል ብለዋል፡፡ ብሉ ናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚ በበኩሉ፤ ፊልሙ ትምህርታዊ እንጂ ለገበያ የተሰራ እንዳልሆነ ጠቁሞ፤ ወደፊት ገቢ ከተገኘበት ለፀሐፊዎች አስር በመቶ ይከፈላል ብሏል፡፡ 

የ90 ደቂቃ ርዝማኔ ያለው “ሆራይዘን ቢዩቲፉል” ፊልም በአንድ የውጪ ዜጋና በሶስት የብሉ ናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚ ተማሪዎች የተፃፈ ሲሆን በተፈጠረው ውዝግብ እስካሁን ለእይታ እንዳልበቃ ተማሪዎቹ ተናግረዋል፡፡
“የፊልሙን ፅሁፍ ስናዘጋጅ ከሶስት ወር በላይ ወስዶብናል፤ የተከፈለን ግን ለእያንዳንዳችን 2500 ብር ብቻ ነው” ያሉት ተማሪዎቹ፤ ሥራውን ስንጀምር ትምህርታዊ ፊልም ነው ተብለን ነው፤ መጨረሻ ላይ የቴሌ ፊልም ተወካይ እስቴፈን ጃገር 14500 ዩሮ (364ሺ276 ብር ገደማ) ለተማሪዎች ክፍያ ብሎ ቢሰጥም የብሉ ናይል ትምህርት ቤት ባለቤት አቶ አብርሃም ሃይሌ ገንዘቡ ሌላ ትምህርታዊ ፊልም ይሰራበታል በማለት ከልክለውናል ብለዋል፡፡ ፊልሙን ስንፅፍ ለትራንስፖርትና ሌሎች ወጪዎችን ከኪሳችን ገንዘብ ስናወጣ ነበር ይላሉ - ተማሪዎቹ፡፡
የብሉ ናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚ ምክትል ስራ አስኪያጅና የአቶ አብርሀም ሀይሌ ህጋዊ ወኪል ወ/ሮ ፅጌሬዳ ታፈሰ በበኩላቸው፤ “ፊልሙ ትምህርታዊ እንጂ ለገበያ የሚቀርብ አይደለም፤ ፊልሙ እንዲሰራ የፈለግነው ተማሪዎች የእውቀት ልውውጥ እንዲያደርጉ ነው” ብለዋል፡፡ ምንአልባት በቲቪ ወይም ፕሮጀክቶች ላይ ታይቶ ገቢ ካስገኘ 10በመቶ ለፀሀፊዎች ይሰጣል፤ ለዚህ ነው ውል የተፈራረምነው ሲሉም አብራርተዋል፡፡ የስዊዘርላንዱ ቴሌ ፊልም ተወካይ ለተማሪዎቹ እንዲከፈል ሰጥቷል ስለተባለው ገንዘብ የተጠየቁት ወ/ሮ ጽጌረዳ፤ የቴሌ ፊልም ተወካይ እስቴፌን ጃገር በመሄጃው ቀን ለተማሪ ክፍያ ብሎ 14500 ዩሮ (364ሺ 276 ብር ገደማ) መስጠቱን አምነዋል፡፡
ይሁን እንጂ ት/ቤቱ ገንዘቡን ለተማሪዎቹ ከማከፋፈል ይልቅ ለሌላ ትምህርታዊ ፊልም እንዲውል በመወሰን ብሩ ባንክ ተቀምጧል ብለዋል፡፡ “ሆራይዘን ቢዩቲፉል” ከስድስት ማሊዮን ብር በላይ በሆነ በጀት በአካዳሚውና በስዊዘርላንዱ ቴሌ ፊልም ትብብር የተሰራ ፊልም ነው፡፡ በሌላ በኩል እነዚሁ ተማሪዎች ለአንድ ዓመት የተማሩበት ሰርተፊኬት አልተሰጠንም ማለታቸውን በተመለከተ ወ/ሮ ፅጌረዳ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ “ሰርተፊኬት የተከለከሉት ያላሟሉት ነገር ቢኖር ነው፤ አልያም የስምንት ደቂቃ የመመረቂያ ፕሮጀክት አላጠናቀቁ ይሆናል፤ ይሄ እንዳይከሰት ብለን ብዙ ጊዜ ማስታወቂያ አውጥተናል፤ ለእያንዳንዱ ተማሪ ደውለናል፤ ከአሁን በኋላ ግን አመት ስላለፋቸው ፈፅሞ አናስተናግዳቸውም” ብለዋል - ወ/ሮ ፅጌረዳ ታፈሰ፡፡

Read 17754 times Last modified on Saturday, 17 August 2013 11:10