Saturday, 27 July 2013 14:29

ጥልቅና አንኳር አስተያየት ስለ “የተረሳ ወራሽ”

Written by  ነቢይ መኰንን
Rate this item
(7 votes)

ጥልቅና አንኳር አስተያየት ስለ
“የተረሳ ወራሽ”

“መጽሐፉ የእናቴ ስለሆነ የግድ አሪፍ
ነው ማለት አይደለም፡፡ እናንተ
ባለሙያዎቹ አስተያየት ስጡበት፡፡”
የመጽሐፉ ደራሲ ሴት ልጅ አዜብ መርሻ

የመጽሐፉ ምርቃት
ቅዳሜ ሐምሌ 13 ቀን 2005 ዓ.ም
የተመረቀበት ቦታ
በቤተመጻሕፍት ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ
መጽሐፉ - የተረሳ ወራሽ
ደራሲ - መሰሉ መዝለቂያ
አርታዒ - አሊ መሀመድ አሊ
አስተያየት - ነቢይ መኮንን
እንደ መሽከንተሪያ (አንዳንዶች መስከንተሪያ ይሉታል) – (መሽከንተሪያን፤ ዘርጋው መዝገበ ቃላት ደግሞ “በመሬት ውስጥ የተሰራውን መመርመሪያ አርሶጦላብ” - ይለዋል)
መሽከንተሪያ ማለት፡- ዱሮ ልጅ ሆነን ስንጫወት፣ የባህር -ዛፍ ፍሬ እንለቅምና ሊሾ ሲሚንቶ ወለል ላይ ዙሪያ ተቀምጠን በሁለት ጣታችን ፍሬዋን ስናሾራት እዚያ ሲሚንቶ ላይ ፉርር እያለች ዙሪያውን ትሽከነተራለች፡፡ ቶሎ አትቆምም፡፡ ትዞራለች፡፡ መሽከንተሪያ እንግዲህ ማሾሪያ፣ ማሽከንተሪያ፣ ማዞሪያ፣ የመነሻ ጉልበት መስጫ (Starter እንደሚባለው በመካኒክ ቋንቋ - “ማስነሻ” መሆኑ ነው)
እንደገና፤ ዱሮ ልጅ ሆነን እናቶቻችን በእንዝርት ጥጥ ሲያጠነጥኑ እንዝርቷን በሁለት ጣታቸው መካከል አስገብተው ሲያሾሯት እንዝርቷ በጣም ትሽከረከራለች። ትሽከነተራለች፡፡ ከላይ በባህር - ዛፏ ፍሬ ስንጫወት ያደረግነውና የእናታችን የእንዝርት እሽክርክሪት ያው መሽከንተር ማለት ነው፡፡ እንግዲህ መሽከንተሪያን በጽሑፌ ውስጥ እንደመነሻ ኃይል፣ የጀርባ ታሪክ (Background) ወዘተ. ተጠቀምኩበት፡፡
በ“የተረሳ ውርስ” መጽሐፍ ላይ ይህን አስተያየት እንድሰጥ ያነሳሳኝ፣ መሽከንተሪያዬ ምንድን ነው? እነሆ፡-
ስልክ ይደወልልኛል፡፡
“ሃሎ?” አልኩ
“ሰላም ነቢይ፤ ታስታውሰኝ ይሆን?” አለች ከዚያኛው ጫፍ ያለችው ልጅ፡፡
“ማን ነሽ?” አልኩ በግርታ፡፡
“የመሰሉ መዝለቂያ ልጅ ነኝ…”
“መሰሉ? መሰሉ መዝለቂያ?...ትዝ ትዝ ይለኛል ስሟ…” አሁንም በግርታ፡፡
“ያኔ በእናንተ ጋዜጣ በነጋ - መዝለቂያ መጽሐፍ ላይ አስተያየት ትሰጥ የነበረችው እንኳን” በትሑት - አስረጂ መንፈስ መግለጽ ጀመረች፡፡
“ኣ! በደንብ አስታወስኩ!” አልኳት፡፡
“መሰሉ መዝለቂያ እናቴ ናት፡፡ ያኔ የሷን ጽሑፍ ይዤልህ የምመጣው እኔ ነበርኩ፡፡”
“ኦ! በትክክል ገብተሽኛል፡፡ ደህና ነሽ? ምን ላግዝሽ?”
“ደህና ነኝ ነቢይ…ለምን ደወልኩ መሰለህ? አሁን ደግሞ እናቴ መጽሐፍ ጽፋለች፡፡ እና እንድታይላት ከማተሚያ ቤት ሲወጣ ይዤልህ ልመጣ ፈልጌ ነበር። ጊዜ ካለህ…ከተመቸህ…”
ደስ አለኝ፡፡ “Great! መጽሐፍ መፃፏ በጣም ያስደስታል፡፡ ዱሮም ወደዚያው ነበር አዝማሚያዋ…ጊዜው ሲደርስ ደውይልኝ፡፡ ምንም ችግር የለም…አየዋለሁ” አልኳት፡፡
“በጣም አመሰግናለሁ ነቢይ”
ከአፏ ላይ “ነቢይ” የሚለው ቃል አይለይም። ያ ደግሞ ቀረቤታን፣ ዝምድናን ነው የሚያሳየው። አንድም፣ ፈረንጆቹ እንደሚሉት “To a man, the sweetest word in any language is his own name” (ለሰው፤ በማንኛውም ቋንቋ ቢነገር እጅግ ጣፋጩ ቃል፤ የራሱ ስም ነው፤ እንደማለት ነው) ስለዚህ ሞቅ የማለት ስሜት አለው!
በኋላ ስታጫውተኝ “ለጓደኞቼ ዘመዳችን ነው” እላቸው ነበር ማለቷ ከአንደበቷ “ነቢይ” የሚለው ቃል ላለመለየቱ፣ ለቀረቤታው፣ ማፀህያ (verification) ወይም ማጠየቂያ (Justification) ይሆነናል፡፡
ለመሆኑ ደራሲዋ መሰሉ መዝለቂያ ማናት?
ነጋ መዝለቂያ ከኢትዮጵያ ውጪ የሚገኝ ሲሆን፤ የመሰሉ መዝለቂያ ወንድም ነው፡፡
የመሰሉ ወንድም ነጋ መዝለቂያ በ1994 ዓ.ም በእንግሊዝኛ “Notes from The Hyenas Belly” የሚል መጽሐፍ ይጽፋል፡፡ በዚሁም መጽሐፍ ዙሪያ “ዘ ፖኤትስ ኤንድ ራይተርስ” ለተባለ መጽሔት የሰጠው ቃለ - ምልልስ ጥር 18 ቀን 1994 በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ተተርጉሞ ወጥቶ ነበር፡፡ እህቱ መሰሉ መዝለቂያ “ነጋ ከዕውነተኛ ታሪኩ አልተነሳም፡፡ አባይ ነው፡፡ ለዚህም እኔ እማኝ ነኝ” በሚል መንፈስ ትጽፍልናለች። የነጋ መጽሐፍ በደራሲው - በነጋ መዝለቂያ በደርግ ዘመን፣ የጅጅጋና የሐረር ግለ - ታሪክ ዙሪያ የተጠነጠነ ነው ይባል እንጂ የደራሲው እህት መሰሉ መዝለቂያ፤ “ዕውነተኛ ታሪክ” ነው ተብሎ የተፃፈው የወንድሟ መጽሐፍ አልተዋጠላትም፡፡
ስለዚህም ምርርና ክርር ያለ ሒሳዊ አስተያየት በሐተታ (article) መልክ ትጽፍና በሴት ልጇ በኩል፤ ለአዲስ አድማስ ትልካለች፡፡ እናነበዋለን፡፡ መሰሉ እጇ፣ ቀለም አጣጣሏ፣ የሃሳብ ውርዷ፣ አመክንዮዋ (reasoning)፣ አወዛጋቢነቷ (Controversy) እና ለታሪክ መቆርቆሩዋ ቁልጭ ብሎ ይታያል፡፡ “ግለሰቡ በግሌ ከጐዳኝ የበለጠ በወገን ታሪክ ላይ የፈፀመው ደባ የከበደ ስለመሰለኝ፣ ይህን የተጋነነና የገዘፈ ውሸት ቸል ብዬ ማለፍ አልሆነልኝም” ትላለች፡፡
ደሞ ሌላ ምሳሌ ለአብነት ጠቅሼ በምን ሁኔታ ልትጋተረው እንደሞከረች ላሳይ፤ (አዲስ አድማስ 1994 ግንቦት 10)
“ይህ ግለሰብ…(ከገጽ 134 የመጨረሻው አንቀጽ ጀምሮ) “አባቴ ቀብሪደሀር በሥራ ላይ እያለ በደርግ ካድሬዎች ተገደለብኝ፡፡ አንድ መኮንን መርዶውን ባያመጣልን እንደማንኛውም ወጥቶ የቀረ ዜጋ የደረሰበትን ሳናውቅ እንቀር ነበር” እያለ የቀብር ወግ ሳያገኙ ሜዳ ተጥለው ከቀሩት ዜጐች ጋር አብሮ መውደቁን ያረዳናል፡፡ በተጨማሪም የአባቱ የባንክ ተቀማጭና ሀብት ንብረት ውሃ በልቶት እንደቀረ ያዋየናል፡፡ ሃቁ ግን የሁለታችንም አባት የሆነው አቶ መዝለቂያ አልታዩ በ1966 ዓ.ም በጡረታ ተገልሎ ቀብሪደሀርን የለቀቀና ጅጅጋ ከሚገኘው ቤተሰብ ጋር ተቀላቅሎ በ95 ብር የጡረታ አበል መተዳደር የጀመረ ሲሆን፤ በ1967 ዓ.ም በጉበት በሽታ በመያዙ በህክምና ሲረዳ ቆይቶ በ1968 ዓ.ም ሚያዚያ 2 ቀን ማረፉ ነው፡፡ የቀብር ሥነስርዓቱም የተፈፀመው ጅጅጋ በቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ነው”
ነብሱን ይማረውና አሰፋ ጐሣዬ (የአዲስ አድማስ ሥራ አስኪያጅ) እንዲያነበው ሰጠሁት፡፡ አነበበው፡፡ ተደሰተ፡፡ “ልብ ያላት ፀሐፊ ናት!” አለ፡፡
እኔም፤ “አዎ፡፡ ወደፊት ጐበዝ ደራሲ ይወጣታል!” አልኩት፡፡
ተከታታይ ጽሑፍ አቀረበች፡፡
ይሄው ዛሬ መጽሐፍ ይዛ ብቅ አለች፡፡ እኔ እስከማውቃት ድረስ መሰሉ መዝለቂያ ይቺ ናት!
አንድም የጋዜጣችን ጽሑፍ አቅራቢ የነበረች በመሆኗ፣ አንድም የገባትና የሚገባት (“ገ”፣ “ባ” ይጠብቃል) ደራሲ በመሆኗ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ፤ ገና ታሪኩ ወደፊት የበለጠ፣ በጠለቀና በሰፋ መልኩ ይፃፋል ብዬ በማምነው በ1960ዎቹ ትውልድ ላይ በማተኮሯ፤ በያገባኛልና - በይገባኛል ባይነት፤ አስተያየት ልሰጥ አሰብኩ፡፡
የመሰሉ መዝለቂያ ልጅ ዛሬ መጽሐፉን ይዛልኝ ስትመጣ ያኔ ትንሽ ተላላኪ የነበረችው ትልቅ ሆና አገኘኋት፡፡ የጊዜው ሩጫ!- እኛን ለማስረጀት ያለው ችኰላ፤ ገረመኝ፡፡ “ጊዜ በረርክ በረርክ … ግና ምን ተጠቀምክ ምንም አላተረፍክ” የሚለው የደበበ ሰይፉ ግጥም ጥቂት መስመር ነው ትዝ ያለኝ፡፡
“መጽሐፉ የእናቴ ስለሆነ የግድ አሪፍ ነው ማለት አይደለም፡፡ እናንተ ባለሙያዎቹ አስተያየት ስጡበት” ብላ ነው የሰጠችኝ፡፡
ሌላ ቀን የመሰሉ ልጅ ስለራሷ ስታጫውተኝ፤
“በሲቪል ኢንጂነሪንግ በመጀመሪያ ዲግሪ ተመረቅሁ፡፡ ቀጥዬ ኔዘርላንድስ ሄጄ ማስተርሴን ሰራሁ…ዩኒቨርሲቲ ሌክቸረር ሆኛለሁ አሁን፡፡ (እናቷ ግቧን መታለች!) ስለሥነጽሑፍ ግን ምንም አላውቅም” ትለኛለች፡፡
“ምንም ምንም?” ብዬ ጠየኳት
“ምንም!” አለች ፍርጥም ብላ፡፡
“ወይ ጉድ ‘ምንም!” ለማለት ድፍረት ያላት ልጅ ናት! እንዲህ ያለ ልጅ ብዙ አይገኝም በአሁኑ ዘመን!” አልኩኝ በሆዴ፡፡ ያሁኑ ትውልድ…የእኛ ትውልድ…እያልኩ ብዙ አውጠነጠንኩ፡፡
ዞሮ ዞሮ እናቷ ስለራሷ ትውልድ ነው የፃፈችው፡፡
በዚያ በደርግ ዘመን ባሏ ወደ ስደት፣ እሷ ወደ እሥር ቤት፣ የወንድሞች ስደት፣ ልጅ ይዞ ዩኒቨርሲቲ መግባት፣ የሌላ ልጇ ወደ ቤት ሥራ መሰማራት ወዘተ ተገፍታ፣ ተሰቃይታ፣ ልጅ አሳድጋ…ልጆቿን ለወግ ለማዕረግ ለማብቃት ብዙ አበሳ አየች፡፡ የገዛ ታሪኳ ራሱ አስገራሚ ነው፡፡ “እያንዳንዱ ደራሲ በዚህም ሆነ በዚያ መንገድ፣ የፃፈው ታሪክ ውስጥ እራሱ አለበት” (Each writer, this way or the other, is part of the story he wrote እንደተባለው ነው፡፡) አንዳንዴ ሳስባት፣ ለዋሸ፣ ለቀጠፈ፣ የትውልዷ አካል (ወንድሟን ጨምሮ) በመጽሐፍ መልክ መልስ መስጠቷ ይሆን እላለሁ፡፡
እንግዲህ ይቺን ደራሲ ከማድነቅ አልፌ ባበረታታት ሁሉ ፈቃዴ ሆነ!
መሽከንተሪያዬ እናቱም አባቱም ይሄው ነው! በሁለት ተከታታይ ክፍል ቢቀርብ ነው ክጃሎቴ፡፡ መጀመሪያ በዐይኑ በሰበከቱ በኩል እናያለን፡፡ ቀጥሎ በመልኩም በገበሩም፤ ብልት ብልቱን እናያለን፡፡
***
መጽሐፉ በተመረቀበት ወቅት በቦታው ተገኝቻለሁ፡፡ ትንሽ ንግግር አድርጌአለሁ፡፡ የዚያችንም ንግግሬን መንፈስ እዚህ አስተያየቴ ውስጥ ዶየዋለሁ፡፡ “ከአፍ ከወጣ አፋፍ” ነውና፤
መወራቱ ላይቀር በጽሑፍ ቢቀመጥ ምን ይገደዋል? ብዬ ነው፡፡
***
የተረሳ ወራሽ
የመጽሐፉ ርዕስ ደስ የሚል መስህብ አለው፡፡ የታመቀ ሃሳብ ያዘለ ይመስላል፡፡
የሽፋን ስዕሉ፣ በዕርበትም ሆነ በጀምበር ስርቂያ ስሜት፣ ደብዛዛ ከመሆኑና ህትመት ያጐሳቆለው ከመምሰሉ በስተቀር፤ ውስጡ ያለውን ይዘት ለመግለጥ አቅም አላነሰውም፡፡
የገፁ ብዛት - በንግግሬም ላይ እንደገለጥኩት፤ ለዛሬው የንባብ ውርጭ ለመታው አንባቢ 506 ገጽ ነውና ሳያስፈራው አይቀርም፡፡ ሆኖም እንቅልፍ ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም፡፡ በተለይ በረዥም ልብ ወለድ መልክ በሚፃፍ መፅሃፍ ፣ለአንባቢ ወይም ለገበያ ተብሎ ፤በጥቂት ገፆች ቀንብቦ ማቅረብ ፍትሃዊነት የጎደለው ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ደራሲው ሀሳቡን ያቆረበትን ያህል ገጽ መቀበሉ መልካም ነው፤ እላለሁ፡፡
በእርግጥ “ግጥሜን ባሳጥረው” በሚለው ግጥሜ ውስጥ (ለግጥም ሆነ እንጂ) ተቃራኒ ሀሳብ ተንፀባርቆ ይሆናል፡፡
ግጥሜን ባሳጥረው
ጊዜ አጣሁኝ ብዬ ፣ ከቁመቱ በታች
ግጥሜን ባሳጥረው
“አይምሰልህ” አለኝ-
“ዕድሜ ሲያጥር እንጂ፣
ቁመት ሲያጥር አደለም፣ ግጥም የሚሞተው”
ብሎ መለሰልኝ፡፡
አንጀቴን አርሶ፣ ዕድሜ ጨመረልኝ!!
(የካቲት 1999ዓ.ም)
እርግጥ ነው፡፡ ሰንሰለቱ ሲረዝም እያንዳንዱ ቀለበት ይላላል፡፡ ይህም ዳተኛ አንባቢያንን የበለጠ ማሳነፉ አይቀሬ ነው፡፡ ሆኖም ትጉውን አንባቢ ማበረታታቱን ነው እኛ እምንመኘው፡፡ ዕይታችን ከአፍንጫችን ስር እንዳይሆን፣ሩቅ-አሳቢነቱን ረዥም-ተጓዥነትን እንለምድ ዘንድ ይረዳናልና ነው፡፡ ደግሞም ደራሲዋ ለምን ረዥሙን ሀሳቧን ትሸምልለው፣ ያፈተታትን ያህል እንድትፅፍ ነፃነቷን ማጎናፀፍ አንድም ለጋስነት ነው!!
የተረሳ ወራሽ- 506 ገፅ ነው ብያለሁ፡፡ ያውም ጥቅጥቅ ባለ ቀለም፡፡ ውስጡ ሲገቡ ግን የታሪኩ ፍሰት ገፁን ያሳጥረዋል ለማለት ይቻላል፡፡
የታሪኩ መቼት -በ1966 አካባቢ ጅጅጋን ፣ ድሬድዋን፣ ደሴን፣ አዲሳባንና አሰበ ተፈሪን ያካለለ ነው፡፡
ታሪኩ - እስከ ሶስተኛው ሚሊንየም መባቻ የሚዘልቅ ነው፡፡
ድርጊቱ- ዘመኑን ፊትና ኋላ የሚያስቃኝ ነው፡፡
በሴራውና በግጭት አፈጣጠር ረገድ፤
የትውልድን አለመተዋወቅ፣ በማንነት አለመረዳዳት (አባት-ልጅን፣ልጅ አባትን፣ዘመድ ዘመድን፣ ዘመነኛ ዘመነኛን ፣… ከሀገር ውስጥ እስከ ዳያስፖራ ወዘተ..) የሚያጠነጥን ነው፡፡ በጅጅጋና አሰበ ተፈሪ ወጣቶች እልቂት ውስጥ የተከሰተውን፤ ስደት፣ ያለ ወላጅ መቅረት፣ አድራሻ መጥፋት፣ ትዳርና ቤተሰብ መፍረስ፣ በትውልድ ላይ የደረሰ ድቀት፣ የሙያና የስራ ስሜት - ዕጦት (frustration) ወዘተ ያካተተ ነው፡፡ በአጠቃላይ ትውልዱ የከፈለውን መስዋዕትነት የሚነግረን ነው፡፡
ደራሲዋ ገፀ-ባህሪያቷን፤ከዚያ ምስቅልቅል ዘመን በተረፉ ባለታሪኮች መልክ ስላ፤ ከተሪፈ - ህይወታቸው ጋር አሰናስላ ነው ያቀረበቻቸው፡፡ ይሆናል የተባለው ሳይሆን፣ አይሆንም የተባለው ሆኖ ያለበት ዘመን የጣለባቸውን አሻራ የሚያሳዩ ገፀባህሪያት ናቸው፡፡ በዝርዝር ወደኋላ ላይ እናያቸዋለን፡፡
መፅሃፉ አንኳር ጭብጡ ፍለጋ ነው፡፡ የልጅ ፍለጋ፣የአባት ፍለጋ፣የስራ ፍለጋ፡፡ የትውልድ ፍለጋ፡፡ የማንነት ፍለጋ፡፡ በዋናነትም የትምህርት ፍለጋ፡፡
መፅሃፉ በአንኳር መፍትሄ - ጭብጡ ይቅርታ መደራረግን አበክሮ ያሳያል፡፡ ደራሲዋ በአፃፃፍ ስልቷ አልፎ አልፎ በምልሰት-ዘዴ ትጠቀም እንጂ አንፃራዊ አውታር (parallel dimension) ማለትም ባለታሪኮቹ በየምዕራፋቸው የየራሳቸውን መንገድ እየተጓዙ ልብ እንዲያንጠለጥሉ የማድረግን ዘዴ መርጣለች። ትስስሩ፣ ግጭቱም ሆነ ፍፃሜ - ክረቱ ወደ ኋላ ምዕራፎቹን ስታዋህዳቸው የምናይበት ዓይነት ነው፡፡
ቋንቋዋ ቀላልና ግልፅ ነው፡፡
የታሪኩ መሪ ገፀ-ባህሪ አንዲት በስርዓቱ አሰቃቂ የግድያ ተግባር ወላጆቿን ያጣች ልጅ ናት፡፡ አያሌ፤ ስቃይ እንደደረሰባትና በጥንካሬና በፅናቷ ሁሉን ተቋቁማ እንዴት ለአዎንታዊ ፍሬ እንደምትበቃ እንገነዘባለን፡፡ የመከራ ዘመን ምርት ነውና የሀዘን ተውኔቱ ይበዛል፡፡ አልፎ አልፎ የድርጊቶች መወሳሰብና የገፀ-ባህሪያት ብዛት ቢኖር፤ ለአወዛጋቢነቱ አስተዋፅኦ በአረገበት አቅጣጫ ካየነው ገንቢ ውስብስብነት ነው፡፡
“የተረሳ ወራሽ” ከአማርኛ ትውልድ ተኮር መፃህፍት አንፃር ሳየው የቆንጂት ብርሃነን “ምርኮኛ” የሚያስታውሰኝ ሲሆን፤ ከእንግሊዝኛ ክላሲክ መፃህፍት ደግሞ the miserables (les miserables) ያስታውሰኛል፡፡
ቀጥሎ የመፅሃፉን ብልት ብልት አካላት እናስተውላለን፡፡
ሁለት ጥቅሶችን እንውሰድ፡-
“ልመና ከረሃብ የበለጠ እንደሚጠብስ አታውቅም?!...
ረሃብ የሚጠብሰው ወደን ነው፡፡ ልመና ግን የለማኙን ፊት ፣ህሊና፣ሰብዓዊ ክብርና ዜግነቱን ጭምር ነውኮ የሚለበልበው፡፡ እስቲ ከልብ ሆናችሁ አስቡት ልጆቼ! በእርዳታና በልመና መኖር በጠላት ተሸንፎ ከመማረክና ከመሞት የበለጠ ውርደት አይደለም? ጠላት፤ ተይዞ የማያውቅ እጃችንን ለምፅዋት መዘርጋት፤ ከውርደትም በላይ ሞት አይደለም? ልመናው በሚያሳድርብን ሃፍረት የሚቀጨው አንገታችን የፈረንጆች መርገጫ መደላድል መሆኑ አያስቆጫችሁም?...”
* * * (ገፅ 416)
… ስላለፈው መጥፎ ድርጊት ይቅር ተባብሎና ያለፈው አልፏል ብሎ፣ብሄራዊ ስሜት በውስጡ ማስረፅ የቻለ ትውልድ ነው አገሩንም ትውልዱንና እራሱንም ከድህነት ነፃ ማውጣት የሚችለው” ገፅ 382)
ይቀጥላል

Read 2608 times