Monday, 27 May 2013 14:39

“አፍሪካ የሀብቷ አዛዥ መሆን መጀመር አለባት”

Written by  ኤልሳቤት ዕቁባይ
Rate this item
(0 votes)

ዊኒ ባይናይማ የመጀመሪያዋ የዩጋንዳ ሴት የአውሮፕላን ኢንጂኒየር ናት፡፡ ሙሴቬኒ የሚልተን ኦቦቴን አገዛዝ ለመጣል ባደረጉት የአምስት አመታት ትግል ጫካ በመግባት ዊኒ፤ ከድል በኋላም የፓርላማ አባል ሆናለች። በአሁኑ ወቅት የኦክስፋም ኢንተርናሽናል ዳይሬክተር በመሆን እየሰራች ትገኛለች። ከሙሴቬኒ ጋር በአንድ የትውልድ ቀዬ የልጅነት ጊዜዋን ያሳለፈችው ዊኒ፤ ጫካ ሳሉ የፍቅር ግንኙነት ነበራቸው፡፡ መንግስት ተመስርቶ ሙሴቬኒ ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላ በተፈጠረ አለመግባባት ከፓርቲው ወጥታ በዓለም አቀፍ ድርጅቶች መስራት ጀመረች፡፡ በትጥቅ ትግሉ ወቅት የሙሴቬኒ የግል ሀኪም ከነበረውና ከትግሉ በኋላ የተቃዋሚ ፓርቲ ከመሰረተው ኪሳ ቢሲጂ ጋር ጋብቻ መስርታለች፡፡ ዊኒ ከትጥቅ ትግል በኋላ ውጤታማ ከሆኑ ጥቂት አፍሪካውያን ሴቶች አንዷ ናት። ሰሞኑን በአዲስ አበባ በነበራት ቆይታ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ኤልሳቤት ዕቁባይ ጋር ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

እስቲ ራስሽን አስተዋውቂ… ዊኒ ባይናይሚ እባላለሁ፡፡ የተወለድኩት እ.ኤ.አ በ1959 ዓ.ም በምስራቃዊ ኡጋንዳ በሚገኘው ምባራራ የተባለ ሥፍራ ነው። በኤሮኒውቲካል ኢንጂነሪንግ የመጀመርያ ዲግሪዬን አግኝቻለሁ፡፡ አሁን ከገበያ በወጣው ኤየር ዩጋንዳ በኢንጂነርነት አገልግያለሁ፡፡ የኢኒጂነርነት ስራሽን የተውሽው ያኔ በዩዌሪ ሙሴቪኒ የተጀመረውንና የሚልተን አቦቴን አገዛዝ ለመጣል በተደረገው የትጥቅ ትግል ውስጥ ለመሳተፍ ነው፡፡ ወደ ጫካ ለመግባት እንዴት ወሰንሽ? ዩጋንዳ በኤዲ አሚን እና በሚልተን አቦቴ አምባገነን አገዛዞች ብዙ ስቃይ አሳልፋለች፡፡ በወቅቱ እኔ እንግሊዝ አገር ነበርኩ፡፡ ይህን አስከፊ ስርአት ለማስወገድ ሙሴቪኒ የትጥቅ ትግል ሲጀምር እርምጃው ጥሩ ነው ብዬ ተቀብዬ ነበር። ከዛም ባለፈ የድርሻዬን ማበርከት እንዳለብኝ ስላመንኩ ትግሉን ተቀላቀልኩ፡፡ መጀመሪያ ላይ ሴቶች ጫካ ገብተን አልነበረም የምንታገለው፡፡

እኔና በለንደን ይኖሩ የነበሩ ሌሎች ሴቶች ለትግሉ የሚሆን ድጋፍ በማሳባሰብ እናግዛቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ከሩቅ ሆኖ መታገሉ ራሱ አገልግሎት ቢሆንም ጫካ መግባት እንዳለብኝ በመወሰን በ22 አመቴ ጫካ ገባሁ፡፡ ውሳኔዬን ግን ሙሴቪኒ አልተቀበለውም ነበር፡፡ ለምን ነበር ያልተቀበሉት? በጫካ ያለው ሁኔታ ለሴቶች ጥሩ አይደለም በሚል ምክንያት ነው፡፡ ጫካ ከምትገቢ ዚምባቡዌ ወይም ዩጋንዳ ውስጥ ሆነሽ ለትግሉ የሚያስፈልጉ ነገሮችን በሚስጥር አድርጊ ብሎ መከረኝ፡፡ እኔ ግን ፈቃደኛ አልሆንኩም፤ እዛው ጫካ ውስጥ ሆኖ መታገልን መረጥኩ፡፡ የትግል ህይወት እንዴት ነበር? እጅግ አስቸጋሪና ፈታኝ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ ለሴቶች ከባድ ነበር፡፡ ግን እወጣዋለሁ ብዬ ስለገባሁ ተቋቁሜዋለሁ፡፡ የሚልተን አቦቴን አገዛዝ ለመጣል የተደረገው የትጥቅ ትግል አምስት አመት ፈጅቷል፡፡ የትጥቅ ትግሉ ካበቃ በኋላስ? እ.ኤ.አ በ1995 ዓ.ም የዩጋንዳ ህገመንግስት ሲፀድቅ የአርቃቂ ቡድኑ አባል ነበርኩ፡፡

ለሁለት ተከታታይ የስራ ዘመኖች የፓርላማ አባል በመሆን አገልግያለሁ፡፡ በፈረንሳይ የዩጋንዳ የዩኔስኮ አምባሳደርም ነበርኩ፡፡ የአፍሪካ ህብረት የስነፆታ እና የልማት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በመሆን በህብረቱ መቀመጫ አዲስ አበባ ሠርቻለሁ፡፡ ባለፈው ሚያዝያ ወር የኦክስፋም ኢንተርናሽናል ዳይሬክተር ሆኜ ከመሾሜ በፊት፣ በተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የልማት ፖሊሲ ቢሮ የስነፆታ ዳይሬክተር በመሆን አገልግያለሁ፡፡ ከታገልሽበትና የትጥቅ ትግሉን ከመራው “ናሽናል ሬዚስታንስ ሙቭመንት” የወጣሽው በሰላም እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡ እስኪ ስለሱ አጫውቺኝ… እ.ኤ.አ በ1999 ዓ.ም ከንቅናቄው የኢንፎርሜሽን ዳሬክተርነት እንድነሳ ተደረግሁ። ምክንያቱ ደግሞ ለፓርቲው ውሳኔ እና ፖሊሲ ታዛዥ አይደለችም የሚል ነው፡፡ በፓርላማ ቆይታዬም በተለይ ከሙስና ጋር በተያያዘ የማነሳቸው ጉዳዮች ብዙም ተቀባይነት ሊያገኙ አልቻሉም ነበር፡፡ በዚህ የተነሳ ነው የወጣሁት፡፡

የታገላችሁለትን አላማ አሁን ካለው አጠቃላይ የዩጋንዳ ሁኔታ ጋር ስታይው ምን አስተያየት ትሰጫለሽ? አሁን የማወራሽ የአለምአቀፍ ድርጅት ተወካይ ሆኜ ስለሆነ ስለዩጋንዳ ፖለቲካ አላወራም፡፡ በአጠቃላይ ግን ዩጋንዳ ልክ እንደብዙዎቹ በማደግ ላይ ያሉ አገሮች በብዙ ችግሮች የተተበተበች አገር ናት፡፡ ድህነት፣ ኋላቀርነት… ሁሉም መፍትሔ የሚፈልጉ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በትጥቅ ትግሉ ወቅት የማልረሳው የምትይው መጥፎ ትዝታ ምንድን ነው? ለምን መጥፎውን ትጠይቂኛለሽ፡፡ እኔ የማልረሳውን ጥሩ ትዝታዬን ነው የምነግርሽ። ከጫካ መጥተን ዋና ከተማዋን ካምፓላን እንደተቆጣጠርን አንድ ሚሽን ተሠጥቶኝ ወደ አንድ ጣቢያ ሄድኩ። እንደደረስኩ በሩ ላይ ያለው ጥበቃ አንዳንድ የሴኩሪቲ ጥያቄዎችን ጠየቀኝ፡፡ መለስኩለትና ውስጥ ልገባ ስል ቆይ ሃላፊዬን አግኚ አለኝ፡፡ ቆሜ ጠበቅሁ፡፡ አንዲት ሴት ወታደር ወደ እኔ መጥታ ሠላምታ ሰጠችኝ፡፡

ሴትየዋ ከአራተኛ ክፍል በላይ የዘለለ ትምህርት አልተማረችም፡፡ በሀላፊነት የያዛቸው ጣቢያ ግን በወቅቱ በአገሪቱ ብቸኛ የነበረውንና ብዙ ምሁራን የሚወጡበትን የማካሬሬ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ ይሄን እንቆቅልሽ ሁልጊዜ ሳስበው ይገርመኛል፡፡ ከዛ ወጣ ብዬ ሳስበው ደግሞ እነዚህ ሴቶች ያለ እንቅልፍ ያሳለፏቸው ሌሊቶች፣ መስዋዕትነቶች፣ ከማህበረሰቡ አስተሳሰብ ጋር ተያይዞ የሚደርስባቸው ችግር አሁንም ድረስ እንደቀጠለ ነው፡፡

የኢንጂነርነት ትምህርትሽ ምን ላይ ደረሰ? የትጥቅ ትግሉ እንዳበቃ በክሬንፊልድ ዩኒቨርሲቲ በሜካኒካል ኢንጂኒሪንግ፣ “ኢነርጂ ኮንሰርቬሽን” ላይ የማስተርስ ዲግሪዬን ሰርቻለሁ። የአፍሪካ ህብረት የ50ኛ አመቱን የወርቅ ኢዮቤልዩ እያከበረ ነው፡፡ በአሉ ሲከበር መረሳት የሌለበት የምትይው ዋነኛ ጉዳይ ምንድን ነው? የአፍሪካ ህብረት የአባል አገሮች ስብሰባ ነው፡፡ እያንዳንዱ አገር የህዝቡን ጥያቄዎች የሚመልስበት፣ የአፍሪካውያንን ሰቆቃ፣ ስደት እና ረሀብ ለማስቆም በቁርጠኝነት ቃል የሚገባበት ወቅት መሆን አለበት። አፍሪካ የሀብቷ አዛዥ መሆን መጀመር አለባት። ህዝቦቿ የማይጨበጥ ተስፋ ሊሰጣቸው ሳይሆን የሚጨበጥ ተስፋ ሊኖራቸው ይገባል፡፡

Read 1979 times