Administrator

Administrator

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ውስጥ ንብረትነታቸው የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የሆኑ ቤቶችን ለንግድ ሱቅ አገልግሎት ተከራይተው ሲጠቀሙ የነበሩ ነጋዴዎች ከኤጀንሲው ጋር የነበራቸው ውል ሣይቋረጥ የክፍለ ከተማው የመሬት አስተዳደር ቦታው ለቤተ አምልኮ እና ሁለገብ ህንፃ ግንባታ ስለሚፈለግ በአስቸኳይ ልቀቁ ማለቱ ውዝግብ አስነሣ፡፡
የክፍለ ከተማው የመሬት አስተዳደር አካላት በተደጋጋሚ የፖሊስ ግብረ ሃይል ይዘው በመመላለስ ንብረታችሁን አንሡና ቤቶቹን ልቀቁ የሚል ትዕዛዝ እንደሚያስተላልፉ የተናገሩት ባለ ንግድ ሱቆች፤ እኛ በውላችን የምናውቀው ያከራየንን አካል ስለሆነ እሡ ውላችሁን አቋርጫለሁ የሚል ትዕዛዝ ካላስተላለፈ አንለቅም ማለታቸውን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል። ስለ ጉዳዩ ያከራያቸውን የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲን ሲጠይቁ፤ “እኛ ከእናንተ ጋር ያለንን ውል እስካላቋረጥን ዝም ብላችሁ ስሩ” ማለቱን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ይናገራሉ። በቅርቡ ባደረጉት የውል ስምምነት እድሣትም፣ ከጥር 1 እስከ መጋቢት 30 የሚቆይ ስምምነት ከመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ጋር መፈራረማቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ሁለቱ የመንግስት አካላት ችግራቸውን ተነጋግረው መፍታት ሲገባቸው የክፍለ ከተማው አመራሮች በፖሊስ ግብረ ሃይል በመታገዝ ውክቢያ መፍጠራቸው ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡
ቀደም ሲል በቀበሌ ቤትነት ተመዝግበው የነበሩ አምስት ቤቶች ከአንድ አመት በፊት በተመሣሣይ አላማ እንዲፈርሡ ተደርጐ በቦታው ላይ ምንም ሣይሠራበት መቆየቱን የሚናገሩት ግለሠቦቹ፤ አካባቢው ሠፊ የንግድ እንቅስቃሴ ያለበት በመሆኑ የገቢ ምንጭ ፈጥረን ቤተሠቦቻችንን እያስተዳደርን ባለበት ወቅት አሣማኝ ባልሆነ ምክንያት እንድንለቅ መደረጉ አግባብ አይደለም ብለዋል፡፡ በአካባቢው መሪ ፕላን ላይ ቦታው ለልዩ ልዩ አገልግሎት የሚውል መሆኑ የተመለከተ ቢሆንም ከሊዝ ነፃ ተደርጐ ለኢትዮጵያ ህይወት ብርሃን ቤተክርስቲያን የቤተ አምልኮ ግንባታ መፈቀዱም የከተማው አስተዳደር መሪ ፕላኑን በማስፈፀም ረገድ ጉድለቶች እንዳሉበት አመላካች መሆኑን ቅሬታ አቅራቢዎቹ ገልፀዋል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርናቸው የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚኒኬሽን የስራ ሂደት ባለቤት አቶ አዲስ እጅጉ በበኩላቸው፤ ክፍለ ከተማው ጉዳዩን ከኤጀንሲው ጋር በመሆን መፈፀም ሲገባው ተከራዮቹን ማስጨነቁ አግባብ አለመሆኑን አመልክተው፣ የውዝግቡ መነሻ ቤተ ክርስቲያኗ ለግምት ካሣ ክፍያ የተተመነላትን 1.8 ሚሊዮን ብር ለኤጀንሲው ከፍላ በጊዜው ባለማጠናቀቋ መሆኑን ለዝግጅት ክፍላችን ገልፀዋል፡፡ አሁን ግን ቤተክርስቲያኗ የሚፈለግባትን ገንዘብ ከፍላ ባሣለፍነው ሣምንት በማጠናቀቋ፣ ለተከራዮቹ የውል ማቋረጫ ደብዳቤ ተፅፎላቸው በቀናት ውስጥ እንዲደርሣቸው ይደረጋል፤ ይህንንም ቅርንጫፍ መስሪያ ቤቱ እንዲያስፈፅም ትዕዛዝ ተላልፎለታል ብለዋል፡፡
ከተከራዮቹ ጋር የተዋዋላችሁት ስምምነት ግለሠቦቹ እስከ መጋቢት 30/2005 ዓ.ም ቤቱን እንዲገለገሉበት ይፈቅዳል፤ ይሄን እንዴት ልታስታርቁት ነው ብለናቸውም፤ መንግስት ቦታውን ለልማት ሲፈልገው በማንኛውም ጊዜ ውሉ ሊቋረጥ ይችላል የሚል ስምምነት በአከራይ ተከራይ ውላቸው ላይ መስፈሩን አቶ አዲስ አስታውቀዋል፡፡
በተመሣሣይ በአካባቢው በባለቤታቸው ስም የተመዘገበ የግል ይዞታ እንደነበራቸው የገለፁልን አቶ ወንድማገኝ መኮንን ካሣ፤ ተሠጥቷችሁ ትነሣላችሁ ሲሉን ቦታው ላይ ሠፍሮ የሚገኘው ግለሠብ አቅሙ ካለው ቅድሚያ የማልማት እድል ይሠጠዋል የሚለውን የህግ ድንጋጌ ዋቢ በማድረግ አቅሙ ስላለን ማልማት እንችላለን ብለናቸው፣ ብር በባንክ ዝግ የሂሣብ መዝገብ አስገቡ ካሉን በኋላ፣ ቦታው ለእናንተ አይፈቀድም ተሸጧል፣ ካሣችሁን ውሠዱ ብለውናል፡፡ እኛ ግን ካሣውን ለመውሠድ ፈቃደኛ ስላልሆን የሚመለከተው አካል ጉዳያችን በአንክሮ እንዲመለከት እንጠይቃለን ብለዋል፡፡
በቂርቆስ ክፍለ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማት ማናጅመንት ፅ/ቤት ሃላፊ አቶ ተገኝ ጦፎ፤ ጉዳዩ ለሠባት አመታት የዘለቀ መሆኑን፣ ለቤተክርስቲያኗ የሊዝ ቦርዱ ቀደም ብሎ በ2003 ያስተላለፈውን ውሣኔ እስከ ዛሬ ባለማስፈፀማቸው ቅሬታ እንደቀረበባቸው፣ ለዚህም ሲባል ክፍለ ከተማው የማስፈፀም ሃላፊነቱን ለመወጣት ግለሠቦቹን ማንሣት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ እርምጃውን ሊወሠድ መቻሉን ገልፀዋል፡፡ “እኛ ከተከራዮቹ ጋር ምንም ግንኙነት የለንም፤ የተላለፈውን ትዕዛዝ በአግባቡ ማስፈፀም ነው ሃላፊነታችን፤ በዚህ ሂደት ነው ችግሩ የተፈጠረው” ያሉት አቶ ተገኝ፤ በቦታው ላይ ቤት ያላቸው ግለሠቦች እና የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ካሣ ተከፍሏቸው፣ የቀበሌ ቤቶቹ ደግሞ ምትክ ቤት ተሠጥቷቸው እንዲነሡ ይደረጋል ብለዋል፡፡ በዚህ ሂደት አግባብነት የሌለው እርምጃ ተወስዷል የሚል አካል ካለ በህግ መጠየቅ እንደሚችል የሚናገሩት ሃላፊው፤ “እኛ በደንቡ መሠረት ከቤተክርስቲያኗ ካሣውን ተቀብለን በመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ አካውንት እናስገባለን፣ ሂሣቡ መግባቱን ስናረጋግጥ አካባቢውን ወደ ማፅዳት እርምጃ እንገባለን፤ በዚህ አግባብ ነው ቦታው እንዲፀዳ እየተደረገ ያለው ብለዋል፡፡

Monday, 04 March 2013 00:00

እናት ባንክ ሥራ ጀመረ

የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ሁለንተናዊ አቅም የሚያሻሽሉና ከዚህ ቀደም በኢንዱስትሪው ትኩረት ያልተሰጣቸውን አገልግሎቶች ይዞ ሥራ መጀመሩን እናት ባንክ አስታወቀ፡፡ 

ባንኩ አገልግሎት የሚጀምርባቸው የመጀመሪያዎቹ ቅርንጫፎች ባንቢስ አካባቢ ከዮርዳኖስ ሆቴል ፊት ለፊት በሚገኘው ዋና መ/ቤቱና ቦሌ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን አካባቢ መሆኑ ታውቋል፡፡ የባንቢስ አካባቢው ዓቢይ ቅርንጫፍ በእቴጌ ጣይቱ ስም የተሰየመ ሲሆን የቦሌ መድኃኒዓለሙ በንግሥተ ሳባ እንዲሁም የሰንጋ ተራው በወ/ሮ አበበች ጎበና ስም መሰየማቸውን ገልጸዋል፡፡ 

እናት ባንክ የሴቶችን አቅም በማጐልበትና በመጠቀም በኢንዱስትሪው ፈጣን ዕድገት ለማምጣትና የአገሪቱን ዕድገት ቀጣይ ለማድረግ የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ አስታውቋል፡፡

የዱር አራዊት ተሰብስበው ግብረ - ገብነታችንንና ሥነ-ምግባራችንን የሚያርቅ፣ መሠረታችንን የሚያበጅ፣ ደህና ጠባይ ያለው እንስሳ እንምረጥ ይባባላሉ፡፡
አንበሳ፤ የአራዊቱ ሁሉ ንጉሥ ነውና “ምርጫው ይሳካ ዘንድ ጦጣን፣ አህያንና ነብርን ስጡኝና የአመራረጡን ሥነ ስርዓት አስቀድመን እናበጃጀው!” ይላል፡፡
አራዊቱ፤ “መልካም ሀሳብ ነው፡፡ እነዚህን ሶስቱን ወስደህ ምከሩበት፡፡ አስቀድመህ ግን፤ ለምን እነሱን እንደመረጥክ ምክንያቱን አስረዳ” አሉት፡፡
አንበሳም፤
“መልካም፡፡ በአዘጋጅ ኮሚቴነት ሶስቱን ስመርጥ ሶስት ዋና ዋና ምክንያቶች አሉኝ፡፡ እጅግ አስፈላጊ የሆነው የሥራ ሀላፊነት፡-
አንደኛ - ብልሃተኛ መሆን ነው፡፡ ለዚህ ጦጣን መረጥኩ፡፡
ሁለተኛ - ሸክም የሚችል ትከሻ ያስፈልጋል፡፡ እንደምታውቁት ለዚህ ከአህያ የተሻለ መሸከም የሚችል አይገኝም፡፡
ሦስተኛ - ፈጣን መሆን ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ እንደነብር ጥይት የለም፡፡
ምክንያቴ ይሄ ነው፤ አለ፡፡ ጭብጨባው ቀለጠ፡፡
“ጥሩ፡፡ በሉ ምርጫውን አሳኩት” ተባሉ፡፡
አንበሳ አስመራጮችን ሰብስቦ “እህስ? እንዴት እናድርግ ትላላችሁ?” አለ፡፡
አህያ፤ “ማናቸውንም በሸክም ዙሪያ ያለ ሥራ ለእኔ ይሰጠኝ” አለች፡፡
ነብር፤ “በፈጣንነቴ የትኛውም የጫካው ድንበር ድረስ ሮጬ የተሰጠኝን መልዕክት አደርሳለሁ” አለ፡፡
አያ አንበሶም፤ “እሺ እመት ጦጣስ? ምን እናድርግ ትያለሽ? መቼም መላ የሚጠበቀው ካንቺ ነው?!” አላት፡፡ ጦጣም፤ “መቼም አያ አንበሶ! የአህያም ሥራ ሸክም መሆኑ በሙያዋ ነው፡፡ የነብርም ሩጫ የተፈጥሮ ክህሎቱ ነው፡፡ እጅግ ከባዱ ጥያቄ ግን በእኔና በእርሶ በጌታዬ በአያ አንበሶ ጫንቃ ላይ ነው የወደቀው፡፡”
ይሄኔ ነብሮ፤ “ምን አዲስ ነገር አለ አንቺ የምትጨምሪልን?” አለና ጠየቃት፡፡
አህያም፤ “ነገሩን ከማስተባበርና ምርጫው በሰላም እንዲያልቅ ከማድረግ በስተቀር ምን የምታከናውኑት ተግባር ይኖራል?” ሲል ጦጣን ጠየቃት፡፡ አያ አንበሶም፤ “እስቲ አትቸኩሉ! የጦጣን ብልህነት አጥታችሁት ነው አሁን? የምትለውን በጥሞና እናዳምጣት” አለ፡፡
ጦጢትም፤ “መልካም እኔ ልል የፈለግሁት፤ ምንም ዓይነት ምርጫ ቢካሄድ አንድ ወሳኝ ቁምነገር መኖሩን አንርሳ ነው”
ነብሮ፤ “እኮ ቁምነገሩ ምንድን ነው?”
አህያ፤ “እኮ ቁም ነገሩን ንገሪና?”
ጦጢት “ታገሡኛ! ዓመት አላወራ! ይሄውላችሁ፤ ወሳኙ ቁም ነገር - የሚመረጠው እንስሳ ማንም ይሁን ማ ለአያ አንበሶ አገዛዝ የሚመች መሆን አለበት!”
ነብሮ፤ “እሱማ ጥርጥር የለውም!”
ጦጢት ቀበል አድርጋ፤ “ስለዚህ” አለችና ቀጠለች፤ “ስለዚህ አሁኑኑ ማን መሆን እንዳለበት እንወስን”
ነብሮ፤ “ለምን እኛ እንወስናለን?”
ጦጢት፤ “1ኛ/ ጊዜ እንቆጥባለን
2ኛ/ አራዊቱ ማንን እንምረጥ እያሉ ግራ እንዳይጋቡ እናግዛቸዋለን
3ኛ/ ተመራጩ ብቁ ነኝ ብቁ አደለሁም፤ ተዘጋጅቻለሁ አልተዘጋጀሁም? እያለ ራሱን እንዳያስጨንቅና በፍርሃት ኃላፊነቱን አልቀበልም እንዳይል፤ ከወዲሁ እናመቻቸዋለን” ስትል አስረዳች፡፡
አያ አንበሶም፤
“ድንቅ ነው! እኔ ጦጢት አስመራጭ ትሁን ያልኩት ይሄንን ጭንቅላቷን አመዛዝኜ ነው! በእኔ እምነት መመረጥ ያለበት ዝንጀሮ ነው፡፡ በሰውና በእንስሳ መካከል ያለ እሱ በመሆኑ እሱ ይመረጥ! በቃ ተመካከሩና ማንን እንደምናስመርጥ ንገሩኝ፡፡ እኔ ትንሽ አረፍ ልበል” ብሎ እየተጐማለለ ወደ ማረፊያው ሄደ፡፡
***
“ንጉሡ የወደዱትን ሁሉ ህዝብ መውደድ አለበት” ከሚል አስተሳሰብ ይሰውረን፡፡ ካህኑ የወደደውን ምዕመኑ ሊወድድ ግን ግድ ሊሆን ይችላልና ጥኑ ጥንቃቄ ይፈልጋል፡፡ አንድም፤ የዓለምን - የዓለምን ቢሉም የኃያላንን ፍላጐት - እናሙዋላ ዘንድ ግዴታችን ነውን? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ የሃይማኖት ውዝግባችን የኃያላንን ፍቃድ ማሟላት ነውን? ብሎ በጥሞና ለመመርመር ወቅቱ አሁን ነው፡፡ የእኛ ባህል፣ የእኛ ሃይማኖት ብሎም የእኛ ሰላም መኖርና መሰንበት፤ ዐይናቸውን የሚያቀላው ሃያላን መንግሥታት፤ እንደልብ የሚያሽከረክሩን አሻንጉሊቶች እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡ የተራቀቀውን የኑክሊየር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ከመዋጀት፤ “በአንድ መርፌ አናት ላይ ስንት መላዕክት ይቀመጣሉ?” የሚለው መንፈሳዊ ምላሽ የሚሻ ምርምር የተሻለ ዋጋ እንዳለው አንዘንጋ! ከፈረሱ ጋሪው የሚቀድምበትን ሁኔታ ማስተዋል የዲሞክራሲን፣ የምርጫንና የፍትህን ነገረ-ሥራ እንድናይ በእጅጉ ይረዳናል፡፡ ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ ስለ ዮፍታሄ ንጉሤ ሲፅፍ “ቅኔ የንባብና የፀዋትወ ዜማ፣ ደጀን የትርጓሜ መፃህፍት ፊታውራሪ ነው… ቅኔን ከፀዋትወ ዜማ በፊት፣ ከትርጓሜ ወፃህፍት በኋላ ለመማር በፍፁም አይቻልም፡፡ ይኸውም ከዘር በፊት ቡቃያ፣ ከባል በፊት ልጅ ይሆናል” ይለናል፡፡ ዲሞክራሲም እንደዚያው፡፡ ከምርጫ በፊት መከበር ያለበት ዲሞክራሲ ነው፡፡ ዲሞክራሲን ሳይዙ እኩልነት የሰፈነበት፣ ፍትሐ ርትዕ የበለፀገበት ሥርዓት እገነባለሁ ማለት “እንሥራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” እንደሚባለው ይሆናል፡፡
በአገራችን አንዳች ነገር ምን ስለመሆኑ ከመፃፍ ምን ስለአለመሆኑ መፃፍ ይቀላል፡፡ የሚገባንም አሉታዊ ዘዴ እንጂ አዎንታዊ ገፅታ አይደለም፡፡ ኑሮአችንም ጉዞአችንም አድካሚ አቀበት የሚሆንብን ለዚህ ነው፡፡ ለምሳሌ ዲሞክራሲ ቀናውና ግልፁ ጉዞ ሆኖ ሳለ ሚስጥራዊ ወይም ምትሃታዊ ብናደርገው እንመርጣለን፡፡ የቅኔ ትምህርትን ማወቅ የምንደክመውን ያህል ዲሞክራሲን ማወቅም የዚያኑ ያህል አድካሚ ነው፡፡ ባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ በዚያው መፅሐፉ የዲሞክራሲንና የቅኔን ቁርኝት እንድናፀኸይ እድል ይሰጠናል፡፡ “የቅኔ ትምህርት… የትውልድ አገርን ትቶ፣ ጋራ ዙሮ ወንዝ ተሻግሮ፣ ወጥቶ ወርዶ፣ ከውሻ ተከላክሎ፣ ቁራሽ እንጀራ ለምኖ፣ ደበሎና ማቅ ለብሶ፣ ተዋርዶ ተንከራትቶ፣ ብዙ ፈተና ተቀብሎ፣ አይመስሉ መስሎ፣ ቀይ የነበረው ጠቁሮ፣ ረዥም የነበረው አጥሮ፣ ተርቦ ተጠምቶ፣ ፀዋትወ መከራውን ሁሉ ታግሶ የሚማሩት የተባሕት ትምህርት ነው” ይላል፡፡ ስለዲሞክራሲም የምንናገረው ይሄንኑ ያህል ነው፡፡ እንደምን ቢሉ፤ ዲሞክራሲም እንደቅኔ ትምህርት ጋራ ዙሮ ወንዝ ተሻግሮ የሚገኝ እንጂ የምቾትና የቅንጦት ባለመሆኑና፣ ብዙ መከራ የታቀፈ ስለሆነ፤ ብዙ ፈተና በማስከፈሉ፣ እንዲሁም፤ እንደ ቁራሽ እንጀራ ሁሉ ኢኮኖሚን በመንተራሱ ነው! “እኔ እምሻውን ብቻ እስከፈፀምክ ድረስ ዲሞክራሲ ማለት ያ ነው” ብለን መንገዳችንን ማስተካከል ከቶም አይቻልም፡፡ ያ ከሆነ ስህተቱንና ህፀፁን እንገነዘብ ዘንድ፤ “ጥቁር ይሁን እንጂ ማንኛውን ቀለም መቀባት ትችላላችሁ” ያለውን፤ ሀብታም መኪና - አስቀቢ መርሳት ነው፡፡ You can paint it any colour; provided it is black.

ባለፈው ሳምንት በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ ላይ ከሜዳ ውጭ የተጫወቱት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በሰፊ የግብ ልዩነት ተጋጣሚዎቻቸውን አሸንፈው ወደ መጀመርያ ዙር ማጣርያ የሚገቡበትን እድል አሰፉ፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ቅዱስ ጊዮርጊስ ካዛንዚባሩ ጃምሁሪ ጋር ተገናኝቶ 3ለ0 ሲያሸንፍ ጎሎቹን ፍፁም ገብረማርያም፤ ኡመድ ኡክሪ እና ጆሴፍ ከመረብ አዋህደዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ ደደቢት የሴንትራል አፍሪካውን አንጌስ ዴፋቲማ 4ለ0 ሲረታ ግቦቹን ያስቆጠሩት ጌታነህ ከበደ፤ አዲስ ህንፃ፤ በሃይሉ አሰፋ እና ዳዊት ፍቃደ ናቸው፡፡ በቀጣይ ሳምንት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በቅድመ ማጣርያው የመልስ ጨዋታቸው ተጋጣሚዎቻቸውን በአዲስ አበባ ያስተናግዳሉ፡፡ ሁለቱም ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሩ ወደ የሚቀጥለው የመጀመርያ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር በመልስ ጨዋታቸው በቀላሉ አቻ መውጣት እና ማሸነፍ ይበቃቸዋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ የዛንዚባሩን ጃምሁሪ በቅድመ ማጣርያው ጥሎ ሲያልፍ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ ቀጣይ ተጋጣሚው የማሊው ክለብ ዲ ጆሊባ ይሆናል፡፡ ደደቢት ደግሞ አንጌስ ዲ ፋቲማን ጥሎ ካለፈ በኮንፌደሬሽን ካፑ የመጀመርያ ዙር ማጣርያ የሚያገኘው የሱዳኑን ክለብ አሊሂላል ሼንዲ ነው፡፡
በአፍሪካ ሁለት ትልልቅ የክለብ ውድድሮች ቅዱስ ጊዮርጊስና ደደቢት ኢትዮጵያን በመወከል በነበራቸው ተሳትፎ ከሜዳቸው ውጭ ብዙ ጎል አግብቶ በማሸነፍ ያስመዘገቡት ውጤት በአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ በአገሪቱ እግር ኳስ የተፈጠረውን መነቃቃት አስቀጥሏል፡፡ በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለተሳተፈው ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ሁለቱ ክለቦች በጋራ 17 ተጨዋቾችን በማስመረጥ ግንባር ቀደም ነበሩ፡፡ በእነዚህ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾቻቸው በአፍሪካ ዋንጫው ያገኙት ልምድ ደግሞ በአህጉራዊው የክለቦች ውድድር ከቀድሞው የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ምክንያት ሆኖላቸዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ እና ኮንፌደሬሽን ካፑ አጀማመር ላይበሁለቱ ክለቦች ከተመዘገቡት 7 ግቦች አራቱን ለብሄራዊ ቡድን ያስመረጧቸው ተጨዋቾች ከመረብ አዋህደዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊግ በሚወዳደረው ቅዱስ ጊዮርጊስ ውስጥ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የሆኑት አምበሉ ደጉ ደበበ ፤ ግብ ያስቆጠረው ኡመድ ኡክሪ እና አማካዩ ሽመልስ በቀለ በዛንዚባሩ ጨዋታ ምርጥ ብቃት እንደነበራቸው ተገልጿል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ተሳታፊ የሆነው ደደቢት የሴንተራል አፍሪካውን አንጌስ ዴፋቲማ በሰፊ የግብ ልዩነት ሲያሸንፍ 3 ጎሎችን ያስመዘገቡት የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾቹ ነበሩ፡፡ ሌሎቹ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች አዲስ ህንፃ የጨዋታው ኮከብ እንደነበረና ግብ ጠባቂው ሲሳይ ባጫ በርካታ ግብ ሊሆኑ የሚችሉ ኳሶችን በማዳን ምርጥ ብቃት ማሳየታቸው ታውቋል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሻምፒዮንስ ሊግ
ለዘንድሮው የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከ1 ወር በላይ የተዘጋጀው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከቅድመ ማጣርያው አንስቶ በሶስት ዙር የሚደረጉትን የማጣርያ ምእራፎች በማለፍ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ ሻምፒዮንስ ሊጉ የምድብ ድልድል ውስጥ ለመገባት አቅዷል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ዛንዚባር ሲያቀና ወሳኙን የግብ አዳኝ አዳነ ግርማን ከደረሰበት ጉዳት ባለማገገሙ አልያዘም ነበር፡፡ አዳነ በአዲስ አበባ ለሚደረገው የመልስ ጨዋታ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ መሰለፉ ቢጠበቅም ጨዋታው ያን ያህል አስጨናቂ ባለመሆኑ ካለበት ጉዳት በተሟላ ሁኔታ እንዲያገግም ሊደረግ ይችላል፡፡
በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን ለ25 ጊዜያት ሻምፒዮን በመሆን ክብረወሰን የያዘው ቅዱስ ጊዮርጊስ የዘንድሮው የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎው ለ10ኛ ጊዜ ሲሆን ውድድሩ አፍሪካን ካፕ ኦፍ ሻምፒዮንስ ክለብስ እየተባለ ደግሞ 10 የውድድር ዘመኖችን ተካፍሎበታል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን ደግሞ ጊዮርጊስ በካፍ ኮንፌደሬሽን ካፕ ለመጀመርያ ጊዜ መሳተፉ አይዘነጋም፡፡በወቅቱ በቅድመ ማጣርያው የተገናኘው ከኤስ ማንጋ ስፖርት ጋር ነበር፡፡ በዚሁ የደርሶ መልስ ፍልሚያ በመጀመርያው ጨዋታ ከሜዳ ውጭ 1ለ0 አሸንፎ ከተመለሰ በኋላ በመልሱ ጨዋታ እዚህ አዲስ አበባ ላይ ማንጋ ስፖርት 4ለ0 በመርታት ወደ መጀመርያው ዙር ገብቶ ነበር፡፡ በመጀመርያው ዙር የተገናኘው ከቱኒዚያው ክለብ አፍሪካን ነበር፡፡ የመጀመርያውን ጨዋታ በሜዳው ሲያደርግ 1ለ1 ተለያየ ከዚያም በመልስ ጨዋታው በክለብ አፍሪካን 2ለ0 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሆኗል፡፡
በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የኢትዮጵያው ቅዱስ ጊዮርጊስ ተጋጣሚ የሆነው የዛንዚባሩ ክለብ ጃምሁሪ በአፍሪካ ክለቦች ውድድር ብዙም ልምድ የለውም፡፡ ጃምሁሪ አምና በኮንፌደሬሽን ካፕ ለመጀመርያ ጊዜ የተሳተፈ ሲሆን በዛንዚባር ሊግ ሻምፒዮን ሆኖ የሚያውቀው አንዴ ብቻ ነው፡፡ የ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ በታሪኩ ለ47ኛ ጊዜ በአዲስ የውድድር ስርዓት መካሄድ ከጀመረ ደግሞ ለ17ኛ ጊዜ የሚከናወን ነው፡፡ በዘንድሮው ውድድር ከ45 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች የተወከሉ 56 ክለቦች ይሳተፉበታል፡፡
ደደቢት በኮንፌደሬሽን ካፕ
ላይ ደደቢት በአፍሪካ የክለቦች ውድድር ካለው የአጭር ጊዜ ልምድ የተሻለ ታሪክ ለማስመዝገብ የሚያስችለውን የአሸናፊነት ስነልቦና መያዙን ወደ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ሲጓዝ በተደረገለት ሽኝት እንደተገለፀ የሚታወስ ነው፡፡ በቅድመ ማጣርያው ከሜዳው ውጭ 4ለ0 በማሸነፍ የተመዘገበው ውጤት ይህን ያረጋገጠ ነበር፡፡ ደደቢት ከሁለት የውድድር ዘመን በፊት በኮንፌደሬሽን ካፕ ተሳታፊ ነበር፡፡በቅድመ ማጣርያው ከታንዛኒያው ያንግ አፍሪካንስ ጋር ተገናኝቶ በመጀመርያው ጨዋታ ከሜዳው ውጭ 4ለ4 ተለያይቶ በመመለስ በመልሱ ጨዋታ እዚህ አዲስ አበባ ላይ 2ለ0 አሸንፎ ጥሎ ማለፍ ችሏል፡፡ ከዚያይ በመጀምርያ ዙር ማጣርያ ከግብፁ ሃራስ ኤልሁዳድ ጋር ነበር የተገናኘው፡፡ በመጀመርያ ዙር ከሜዳው ውጭ በሃራስ ኤልሁዳድ 4ለ0 ተሸንፎ በመልሱ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ አንድ እኩል አቻ በመውጣት ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡
በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የደደቢት ተጋጣሚ የሆነው የመካከለኛው አፍሪካ ክለብ አንጌስ ዴፋቲማ በአገሩ የሊግ ውድድር 5 ጊዜ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን ስታድዬሙ በዋና ከተማው ባንጉዊ የሚገኝ ነው፡፡ በአፍሪካ ሻምፒዮን ክለቦች ውድድር 5 ጊዜ፤ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ 2 ጊዜ፤ እንዲሁም በካፍ ኮንፌደሬሽን ካፕ 1 ጊዜ ተሳትፎ ከመጀመርያ ዙር አላለፈም፡፡ በታሪኩ ለ10ኛ ጊዜ በሚደረገው የ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ ከ41 ፌደሬሽኖች የተውጣጡ በአጠቃላይ 59 ክለቦችን ያሳትፋል፡፡
የሁለቱ ክለቦች አርዓያነት
ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ በአርዓያነት ሊወሰድ የሚገባ አስተዳደርን ይከተላሉ፡፡ ሁለቱ ክለቦች ለዋና ቡድኖቻቸው መሰረት የሆኑ የቢ እና የሲ ቡድኖችን በመያዝ፤ ለተጨዋቾች ጠቀም ያለ የፊርማ ክፍያ በመስጠት እና ከፍተኛ ደሞዝ በመክፈል፤ ከተለያዩ የውጭ አገራት ተጨዋቾችን በመቅጠር፤ ስለክለባቸው የተሟላ መረጃ ማግኘት የሚቻልባቸውን ድረገፆች በማንቀሳቀስ፤ የሴት እግር ኳስ ክለቦችን በመዋቅራቸው በማካተት ይሰራሉ፡፡ ሁለቱም ክለቦች በዙርያቸው ድጋፍ ሰጭ ስፖንሰሮችን በማሰባሰብም ብዙ ርቀት ተጉዘዋል፡፡
ፈረሰኞቹ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሁለት ዓመት በፊት የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመቱን ሲያከብር በኦፊሴላዊ ድረገፅ የክለቡ ፕሬዝዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀል ባሰፈሩት መልእክት ክለባቸው ለኢትዮጵያ እግር ኳስ በሚጫወተው ፈርቀዳጅ ሚና እንደሚቀጥል ገልፀው ነበር፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ደጋፊዎቹን በአባልነት በመመዝገብ እና ባለድርሻ አካል እንዲሆኑ በማድረግ ፤ የውጭ አገር ተጨዋቾችን በመቅጠር እንዲሁም የውጭ አገር አሰልጣኝ በሃላፊነት በማሰራት ቅዱስ ጊዮርጊስ አርዓያ መሆኑን ፕሬዝዳንቱ በኩራት ይገልፃሉ፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ከ20 ዓመታት በፊት የራሱ ቢሮ እንዳልነበረው በመልእክታቸው የጠቀሱት አቶ አብነት አሁን ክለቡ የራሱን ስታድዬም በመገንባት ላይ እንደሚገኝ፤ የወጣቶች አካዳሚ ገንብቶ ስራ እንደጀመረ ገልፀው ክለቡን በአውሮፓ ሞዴል ለማስተዳደር በተቃና መንገድ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ የአርሰናል ክለብ እና የአሰልጣኝ አርሰን ቬንገር አድናቂ መሆናቸውን በዚሁ መልእክታቸው የገለፁት አቶ አብነት ክለባቸው ቅዱስ ጊዮርጊስ በሁሉም ረገድ እንደአርሰናል ቢሆን ፍላጎቴ ነው ይላሉ፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ የራሱን ስታድዬም በመገንባት የያዘው ጅምር ለሁሉም የኢትዮጵያ ክለቦች አርዓያነቱን ያጎላዋል፡፡ ክለቡ ለስታድዬም ግንባታው የሚኖረውን ወጭ 80 በመቶ ከክቡር ሼህ መሃመድ አላሙዲ ያገኛል፡፡ የክለቡን ደጋፊዎች ባለድርሻ አካል ያደረገውና የአባልነት መታወቂያ ይዘው ክለቡን በወርሃዊ መዋጮ እንዲደግፉ በማድረግ የተሳካለት የቅዱስ ጊዮርጊስ አስተዳደር ትልልቅ ኩባንያዎችን በስፖንሰርሺፕ አብረውት እንዲሰሩ በማድረግም አርዓያ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖንሰርሺፕ ድጋፉን ከቢጂአይ፤ ከዳሸን ባንክ እና ከፔፕሲ ኢትዮጵያም ይሰበስባል፡፡
በቅፅል ስሙ ሰማያዊው ጦር የሚባለው ደደቢት ከተመሰረተ 15 ዓመት ሲሆነው የእግር ኳስ ክለቡ ፕሬዝዳንት ኮለኔል አዎል አብድራሂም ናቸው፡፡ ‹‹ህልማችን እውን ይሆናል›› የሚለውን ያነገበው ክለቡ የልምምድ ሜዳውን በአበበ ቢቂላ ስታድዬም ያደረገ ሲሆን ሳርቤት አካባቢ በተሟላ የመዝናኛ አገልግሎት የሚሰጥበት የተጨዋቾች ካምፕን ይጠቀማል፡፡ የደደቢት እግር ኳስ ክለብ ስፖንሰሮችን በማስተባበር ይሰራል፡፡ ለክለቡ በመጀመርያ ደረጃ ስፖንሰርነት ድጋፍ የሚያደርገው የብረታብረት እና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሲሆን፤ በ2ኛ ደረጃ ስፖንሰር የሚያደርገው ደግሞ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ነው፡፡ በ3ኛ ደረጃ ስፖንሰርነት የመከላከያ የኮንስትራክሽን ግብዓቶች ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ እንዲሁም በ4ኛ ደረጃ ስፖንሰርነት የአርሚ ፋውንዴሽን ክለቡን እየደገፉ እንደሆነ ከድረገፁ የተገኘ መረጃ ይገልፃል፡፡ የክለቡ የማልያ ስፖንሰር ደግሞ ሳምሰንግ ነው፡፡

ዶ/ር እስክንድር ከበደ
እርግዝና ሲታሰብ ብዙ ጥንቃቄዎችን ማድረግ እንደሚገባ በተለያዩ ጥናታዊ ስራዎች ተጠቁሞአል፡፡ የስነተዋልዶ ጤና ጠበብት የሚመክሩት በማንኛውም ወቅት እናቶች የህኪም ምክር እንደሚያስፈልጋቸው ሲሆን በተለይም ወደ እርግዝናው ከመገባቱ በፊት አስቀድሞውኑ የጤና ክትትል ማድረግ ተገቢ መሆኑንም ነው፡፡ አንድ ችግር ከመከሰቱ አስቀድሞ ከጤና ተቋማት በመገኘት ሁኔታውን በማማከር መፍትሔ ማግኘት ይቻላል ፡፡ በዚህ እትም ለንባብ ያቀረብነው በእርግዝና ወቅት ችግር ሊያስከትሉ ስለሚችሉ እጢዎች ጉዳይ ነው፡፡ ዶ/ር እስክንድር ከበደ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ክፍል ኃላፊ ለጥያቄዎች መልስ ሰጥተዋል፡፡
ኢሶግ፡ የማህጸን እጢ ሲባል አይነቱ እንዴት ይገለጻል?
ዶ/ር፡ የማህጸን እጢ ሲባል የተለያዩ አይነት ናቸው በብዛት በሴቶች ላይ የሚገኘው ግን በህክምናው አጠራር ማዮማ ወይም ፋይብሮይድ ወይም ላማዮማ የሚባለው አይነት ነው፡፡ ማዮማ ከማህጸን ግድግዳ በመነሳት ወደውጭ ወይንም ወደውስጥ በማደግ የማህጸንን ግድግዳ መጠኑን ከፍ በማድረግ ወይንም ቅርጽን በማበላሸት እንደእጢ ሆኖ ችግር የሚፈጥር ነው፡፡ ሁለተኛው አይነት እጢ ከእንቁላል ማፍሪያው ወይንም ኦቫሪ ከሚባለው ክፍል የሚነሳ የእጢ አይነት ነው፡፡ እንደዚህ አይነቱ እጢ ውሀ የቋጠረ ትንሽ ነገር ሲሆን እየዋለ እያደረ ግን መጠኑም እያደገ ሄዶ ከፍተኛ ክብደት ሊኖረው የሚችል ነው፡፡
ከእንቁላል ማመንጫው የሚፈጠረው እጢ አንዳንድ ጊዜ ችግር የማያመጣ ሊሆን ሲችል ሁለተኛው ክፍል ግን ወደካንሰር ተለውጦ ወደሌላው የሰውነት ክፍልም በመሰራጨት በሕይወት ላይ አደጋ ሊያስከትል የሚችል ነው፡፡
ኢሶግ፡ በእርግዝና ወቅት ችግር ሊያስከትል የሚችለው እጢ የትኛው ነው?
ዶ/ር፡ አንዲት ሴት እርጉዝ ሆና ማዮማ የተሰኘው የማህጸን እጢ በተመሳሳይ ጊዜ ሊኖራት ይችላል፡፡ ነገር ግን እጢው የተለያየ ችግር ሊያስከትል ይችላል፡፡ ለምሳሌ...
የመጀመሪያው ሶስት ወር ከመሙላቱ በፊት ተከታታይ ውርጃ ሊኖር ይችላል፡፡
ቀኑ ሳይደርስ ምጥ እንዲጀመር ሊያደርግ ይችላልልጁ ከመወለዱ በፊት የእንግዴ ልጅ ከማህጸን ግድግዳው አንዲላቀቅና ደም እንዲፈስ ሊያደርግ ይችላል፡፡
እጢው ከማህጸን አፍ አካባቢ ከሆነ ምጥ በሚኖርበት ጊዜ ልጁ እንዳይወለድ ሊያውክ ይችላል፡፡
ስለዚህም በእንደዚህ ያለ አጋጣሚ እጢ ያለባቸው ሴቶች ከሌሎች በተለየ መልኩ በስድስት እጥፍ በኦፕራሲዮን የመውለድ እድል ይኖራቸዋል፡፡ በተጨማሪም ከወለዱ በሁዋላም የደም መፍሰስ ከሌሎች ሴቶች በተለየ ሊያጋጥም እና ለጉዳት ሊዳርጋቸው ይችላል፡፡
ኢሶግ፡ ማዮማ ከተሰኘው እጢ ሌላ እርግዝናን የሚያውክ እጢ ይኖራልን?
ዶ/ር፡ ሌላው አይነት እጢ ከማህጸን ፍሬ የሚነሳው ነው፡፡ እንደዚህ አይነቱ እጢ በእርጉዝ ሴት ላይም ሊያጋጥም የሚችል ሲሆን በተለያዩ ጊዜ በተሰሩ ጥናቶች ለማወቅ እንደተቻለውም እንደቦታው እና በተለይም በመጀመሪያው ሶስት ወር ላይ በአልትራሳውንድ የመጠቀምን ባህል ተከትሎ እጢው ከመቶ እርግዝናዎች በአንድ ወይንም ከሁለት ሺህ እርግዝናዎች አንድዋ ሴት ላይ እንደሚከሰት ተገምቶአል፡፡ ይህ እጢ ከማህጸን እንቁላል ማቀፊያ የሚነሳ ሲሆን የሚያረግዙት ሴቶችም በእድሜያቸው ወጣት ስለሚሆኑ ብዙ ጊዜ ወደካንሰር ተለውጦ አይገኝም፡፡ በተሰሩት ጥናቶችም ወደካንሰር ተለውጦ የሚገኝባቸው ሴቶች ከአንድ ፐርሰንት በታች የሆኑት ናቸው፡፡ ብዙ ጊዜ እጢው ወደ ካንሰር ተለውጦ የሚገኘው የመውለድ እድሜ ካበቃ ማለትም ከሀምሳ እና ስድሳ አመት በሁዋላ ነው፡፡
ኢሶግ፡ አንዲት ሴት ማዮማ የተሰኘው እጢ በማህጸንዋ ኖሮአት ብታረግዝና ጉዳት ቢገጥማት እርግዝናው በምን መልክ ይቀጥላል?
ዶ/ር፡ የጉዳቱን መጠን የሚወስነው የማዮማው መጠን ማለትም ትልቅንተና ማነስ ሲሆን ሌላው ደግሞ ያለበት ቦታ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እጢዎቹ ምንም እንኩዋን ከማህጸን ግድግዳ ቢነሱም እድገታቸው ወደ ውጭ ይሆናል፡፡ እንደዚህ ያሉት በእርግዝናው ላይ የሚያስከትሉት ጫና በጣም ዝቅተኛ ስለሚሆን እርግዝናውን እስከመጨረሻው መጠበቅ ይቻላል፡፡ ነገር ግን ግን እጢው በጣም ትልቅ ከሆነና የማህጸንን ቅርጽም እስከማበላሸት እና በተከታታይ ውርጃን የሚያመጣ እንዲሁም እርግዝናን የሚከለክል ከሆነ እርግዝናው እንዲቋረጥ እና ምናልባት ቢቻልም ከእርግዝናው በፊትም እንዲወጣ ማድረግ ግድ ይሆናል፡፡ እጢው ያለበት ቦታ ችግር የማያስከትል ከሆነ ግን እርግዝናው እንዲኖር ይመከራል፡፡ ከዚህ ውጪ ማዮማው እያለ እርግዝና ከተከተለ ምናልባት በማህጸን እጢ ውስጥ ደም በመድማት እና መጠኑን በመጨመር ከፍተኛ ሕመምን ሊያስከትል ስለሚችል ወደህክምናው በመቅረብ መከላከል ይቻላል፡፡ እረፍት በማድረግም ማዮማው በተወሰነ ቀናት ውስጥ ሕመሙን ሊቀንስ ስለሚችል ጊዜውን ማሳለፍ የሚቻልበት መንገድ አለ፡፡
ኢሶግ፡ አንዲት ሴት እጢው በማህጸንዋ ይኑር አይኑር አስቀድማ ልታውቅ የምትችለበት መንገድ አለ?
ዶ/ር፡ ማዮማ የተሰኘው እጢ ያለባቸው ሴቶች ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ምንም አይነት የህመም ስሜት ስለማይኖራቸው ምንም አይነት ሕመም እንዳላቸው አያውቁም፡፡ በአብዛኛው የሚታየው ስሜት የወር አበባ መዛባት ፣የወር አበባ እረጅም ጊዜ መፍሰስ ፣የወር አበባ በብዛት መፍሰስ ፣ከሆድ በታች አካባቢ ሕመም መሰማት ፣ሽንት ቶሎ ቶሎ መሽናት፣ ወይንም ሽንትን መከልከል ፣የሆድ ድርቀት የመሳሰሉት ናቸው፡፡ በእርግጥ የእርግዝና ክትትል በሚደረግበት ጊዜ በመጀመሪያው ሶስት ወር አካባቢ ተገቢውን ምክር ከሐኪምዋ ልታገኝ ትችላለች፡፡
የህመም ስሜቱ ቢከሰትም እንኩዋን በህክምና የሚመ ከረው እርግዝናውን እንዲሞክሩት ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ ከመውለድ በፊት ማዮማውን ለማውጣት ሲባል ኦፕራሲዮን ቢደረግ ሊከሰት በሚችለው የጎንዮሽ ጉዳት ወደፊት ማርገዝን ሊያውክ ስለሚችል ነው፡፡
እርግዝና በእራሱም ማዮማው እድገቱን ወይንም መጠኑን እንዳይጨምር ሊያደርግ የሚችል ሲሆን በአብዛኛው እጢው የሚይዛቸው ሴቶችም ልጅ ያልወለዱ ናቸው፡፡ በተከታታይ ያረገዙ ሴቶች ባብዛኛው ማዮማ የተሰኘው እጢ አያጠቃቸውም፡፡ ስለዚህ እርግዝና እራሱ እንደእጢው መከላከያ ተደርጎም መቆጠር ይችላል፡፡
ኢሶግ፡ ሕክምናው ምን ይመስላል?
ዶ/ር፡ እጢው ሲታከም በአብዛኛው ካንሰር ካልሆነ እና ከአምስት ሴንቲሜትር በታች ከሆነ ምንም ጉዳት የማያስከትል ስለሆነ በአልትራሳውንድ እየተከታተሉ ተገቢውን ሕክምና ማድረግ ይቻላል፡፡ ከአስር ሴንቲሜትር በላይ የሆነው ግን ኦፕራሲዮን ቢሆን ይመረጣል፡፡ ምክንያቱም እያደገ በሄደ ቁጥር ካንሰር የመሆን እድሉ እየሰፋ የማህጸንን ቅርጽና መጠን ስለሚቀይር ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እጢው ካደገ ሆድ ውስጥ በመሽከርከር የደም ስሮችን የሚይዘውን ስጋ በራሱ ላይ ስለሚጠመለልበት ምናልባትም ለእጢው የሚደርሰው ደም በማነሱ ምክንያት ፈንድቶ ኢንፌክሽንን ሊያስትል ስለሚችል አደጋው ከመድረሱ አስቀድሞ በኦፕራሲዮን ማስወገድ ይመረጣል፡፡ ከአምስት እስከ አስር ሴንቲ ሜትር የሆነው እጢ ውስጡ ጠንካራ የሆነ ነገር ወይንም ክፍልፋይ የሆነ ነገር ካለው የካንሰር ምልክት ስለሆነ ማውጣት የሚመከር ሲሆን ውሀ ብቻ የቋጠረ ከሆነ ግን መታገስ ይቻላል፡፡
ኢሶግ፡ እጢው እያለ እርግዝና ከተከሰተ ኦፕራሲዮን ማድረግ የሚመከረው ምን ጊዜ ነው?
ዶ/ር፡ ኦፕራሲዮን ማድረግ የሚመረጠው ከአስራ አራት እስከ ሀያ ሳምንት ባለው ጊዜ ነው፡፡ የዚህም ምክንያቱ በመጀመሪያው ሶስት ወራት አካባቢ እንቁላልዋ ስትወጣ ውሀ የቋጠረ እጢ ከሆነ ከአስራ አራተኛው ሳምንት በሁዋላ ሊጠፋ ይችላል፡፡
ነገር ግን ሳይጠፋ ቀጥሎ ከሆነ ካንሰር ወደመሆን ሊለወጥ ስለሚችል ሕክምናውን ማድረግ ይመከራል፡፡ ኦፕራሲዮን ለማድረግ ሲባል ለእናትየው የሚሰጠው ማደንዘዠ ጉዳት ዝቅተኛ ነው ተብሎ የሚታመንበት ሰአት ከአስራ አራት እስከ ሀያ ሳምንት ባለው ጊዜ ነው፡፡ ጊዜው ከዚህ በታች ከሆነ ጽንሱን በውርጃ መልክ ማጣትን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ከዚህ በላይም ከሆነ ማደንዘዣው በጽንሱ ላይ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል፡፡
ኢሶግ፡ ማዮማን ለመከላከል ምን ማድረግ ይቻላል?
ዶ/ር፡ በእርግጥ ማዮማ በአብዛኛው ወልደው በማያውቁ ሴቶች ላይ ይከሰታል ቢባልም አንዳንድ ጊዜ ግን በእድሜ ምክንያትም ይከሰታል፡፡ እርግዝና ማዮማ የተባለውን እጢ ሙሉ በሙሉ ባያጠፋም ግን የመከላከል አቅሙ ከፍተኛ ነው፡፡
ስለዚህ መውለድ በሚገባው የእድሜ ክልል አርግዞ መውለድ በጣም ይመከራል፡፡

“ሁላችንም የየራሳችንን ዳገት በየቀኑ እንወጣለን” እንደ በገና አውታር፣…ልብ የሚነዝሩ፣…ሆድ የሚያባቡ፣…ስሜት የሚነሽጡ ናቸው - የግርማ ተስፋው ግጥሞች፡፡ “መጀመሪያ” ብሎ መግቢያው ላይ ከተጠቀመበት የህይወት ማንጸሪያ ላይም የወደድኩለት ነገር አለ፡፡ “ሁላችንም የየራሳችንን ዳገት በየቀኑ እንወጣለን፡፡”
በማለት አንድ አዛውንት የራስ ዳሸንን ዳገት ሲወጡ ከተናገሩት የምሬት ንግግር ጋር ያነጸረበት መንገድ የሚመች ነው፡፡
“የጠፋችውን ከተማ ሃሰሳ” በሚል ግርማ መጽሃፍ ማውጣቱን ስሰማ ያው በግጥም ላይ ከሚቀልዱት አንዱ ይሆናል በሚል ችላ ብዬው ነበር፡፡ ምክንያቱም እኛ ሃገር መጣጥፍ የጻፈ ሁሉ ደራሲ፣ጋዜጣ ላይ ስንኞች ያስነበበ ሁሉ ገጣሚ ነው የሚል ዘውድ ሲደፋለት እያየን ነው፡፡ የፈጠራ ስራ ክብር ከመጣጥፍ እኩል እስከመታየት ደርሷል፡፡

ግና ኤድጋር ስፔየርን ጨምሮ የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ ታላላቅ መምህራንን ለጥበብ የመወለድ እውነትን ማጣጣም ያቃታቸው ብዙ ናቸውና ግርማንም ከዚሁ ተርታ መድቤው ነበር፡፡ ምክንያቱም ግጥም ይዞ ወዲያ-ወዲህ ሲል አላየሁትም ነበርና!! ይሁንና ለግርማ የነበረኝን ግምት ከገጽ-ገጽ ስሻገር እየቀየርኩ ሄጃለሁ፡፡ግርማ የ“አዲስ ነገር” ጋዜጣ አዘጋጅ የነበረ ሲሆን አሁን ውጭ ሀገር በስደት የሚኖር ኢትዮጵያዊ ነው፡፡
ከግርማ ግጥሞች ብዙዎቹን ወድጃቸዋለሁ፤ያ ብቻ አይደለም ተመስጨባቸዋለሁ፡፡ በተለይ ተፈጥሮን ለማንጸሪያነት እየተጠቀመ በፈጠረው ውበት ተደምሜያለሁ፡፡ ሰማይን….ደመናን…ትዝታን…ክዋክብትን ወዘተ ወደ ምደር አውርዶ እንደ መጽሃፍ ገልጦ፣አቅርቦ አሳይቶናል፡፡ ስሜታችንን እንደ ድስት ገልብጦ ሽንኩርት አቁላልቶበታል፡፡
በባለሁለት መስመርዋ ግጥም ብጀምር ደስ ይለኛል፡፡ እነዚህን ግጥሞች ያነበብኩት ጎልፍ ክለብ ያሬድ ከሚባል የግጥም፣የንባብ ወዳጅ ጋር ነበረና፤”በናትህ ስማ!” እያልኩ ድምጽ እያወጣሁ ነበር ያነበብኩት፡፡ በግጥም የመጀመሪያ ንባብ የሚፈጠር ስሜት አይታመንም ይላሉ የዘርፉ ሊቆች፡፡ እኔ ግን ደግሜ ደጋግሜ አንብቤዋለሁ፡፡ ግሩም ነው - እፁብ ድንቅ!
ቀጣዩ ግጥም “ነገረ እስር” በሚለው ግጥሙ ስር ካሉት ግጥሞች ቁጥር አምስት ላይ ያለ ነው፡፡
አገሩ ታሠረ
እስር ቤት መቀለስ እንደድሮው ቀረ፡፡
እጅግ የገረመኝ - አንገቴን ያስነቀነቀኝ ግጥም ነው፡፡ በሁለት ስንኞች አገር ማነቃነቅ!!...በጣም ልብ ይነካል፡፡ ግርማ ይህችን ግጥም ብቻ እንኳ ጽፎ በቃኝ ቢል ትልቅ ገጣሚ ነው፡፡ በጣም ትልቅ የምናብ ኃይል የታየበት ግጥሙ ነው፡፡ ትልቅ አይን!...እያንዳንዱ ሰው በየራሱ ቤት ከታሰረ ወህኒ ቤት ምን ይሰራል?…ሃሳቡ ከተጠፈነገ የሰው ልጅ ሌላ እስር ቤት ለምን ያስፈልገዋል?ኦ ግርማ!... ጀፈርሰን 3ኛ የአሜሪካ ፕሬዚደንት ሆኖ ሲመረጥ እንዲህ ብሎ ነበር፡-“I have sworn upon the altar of God eternal hostility against any form of tyranny over the mind of man.” በሰዎች አእምሮ ላይ የሚጫን የአምባገነኖች ጫና የሚያስጠላ ነገር ነው፡፡ከመግደልም አይተናነስምና መሰዊያ ላይ ባልምልም ግርማና ጀፈርሰንን እደግፋለሁ!!
ብቻ ይህቺ የግርማ ግጥም እንደ እንቁላል ተፈልፍላ በሰማይ ሊያበር የሚችል አቅም ያላት ናት፡፡ ልብ ብሎ ላነበባት፡፡ሰንሰለት የማይታይበት፣ሰሚ ያጣ አልቃሽ ከሆንን ቆየን፤የቁም እስረኛ ሆነን ይሆን? መንግስታችንም ገጣሚ ዳዊት ጸጋዬ እንዳለው መናገር እንጂ መስማት አልችልም ስላለ ይለወጣል ብለን በጉጉትና በተስፋ የምንጠብቀውን እንኳ አስከፍቶናል፡፡
“ተራራ እናትና በር” (ርዕሱ ለግጥም የማይመች ቀውላላ ቢሆንም)
በር በሌለው ጎጆ፤በተራራው ጫፍ ላይ
አለች ምስኪን እናት፤ማዶ ማዶ እምታይ፡፡
ከተራራው ቆርባ፤ከጋራው ተላምዳ
እያማከረችው የዘመንዋን ፍዳ፤
ምስክር ማን አለ? የተመለከተ
ሳይዘጋ ሲኖር የጎጆዋ በሩ እንደተከፈተ፤
ምልዔል ደረሰ መመለስ ወግ ሳይኾን
በሄዱት ልጆቿ ሃሳብዋ ሳይሰክን፤
ልጆቿም አልመጡ፣በሩም አልተዘጋ
እንባዋም አልቆመ፣ሌሊቱም አልነጋ፡፡
ይህ ግጥም ተምሳሌታዊ መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ግን ሆድ ያባባል፤እንደ ሁዳዴ የበገና ዜማ አንጀት ያላውሳል፤በተለይ ለስደተኞች፡፡ እግር ላላቸው ሳይሆን ሃገር ከሆድ ያለፈ ትርጉም እንዳለው ለሚገባቸው፡፡ ለመቃጠል…ለማሰብም…ሆድ ሳይሆን ህሊና ያስፈልጋል፡፡ ግርማ ለኔ ከአድማስ ባሻገር የሚያማትር ዓይናማ፣በሳል፣ስል ነፍስ ያለው ያገር ልጅ ነው፡፡ሃሳቦቹ የተንጠለጠሉባቸው ተራራዎች ራሳቸው ግዙፎች ናቸው፡፡ በከበረው ሃሳብህ ምክንያት አክብሬሃለሁ፡፡ ሸጋ ልብ ወገን ወዳድ፣የነጻነት ጥማት ከግጥሞችህ ውስጥ ይፈልቃልና ብራቮ ብያለሁ!!
“የቃየን ፉከራ”ሌላው ለዳሰሳዬ የመረጥኩት ግጥም ነው፡፡
ለቃየን ውላጆች ጀግና መኾን ማለት
መሸለል፣መፎከር፣“ዘራፍ-ዘራፍ” ፉጨት፡፡
መንገዱን የሳተ ዐይኑን ያልገለጠ ደቦል ገደሉና፤
ተው ጋሜ ሽለላ፣ፉከራ ቀረርቶ
“ትመታ እንደኹ ምታ…”
እንደ ማስመሰል ሳግ በውሸት ተሰርቶ
እንጀራው ሲጋገር ባሰት እርሾ ቦክቶ፡፡
ይህ ነው ዝማሬያቸው
የከንቱነት ክብር የቃላት ኳኳታ
የሰውነት ሽሽት የወናነት ሆታ፡፡
የአንበሳ ደቦል ገድሎ አደባባይ ላይ መፎከር እንዴት ነውር እንደሆነ በተለይ ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ሩቅ አይመስለኝም፡፡ የአድዋ ድል ጀግኖች ዛሬ ጀግና አይደላችሁም ብንባል ወይም እኛ ራሳችንን ጀግና ነን? ብለን ብንጠራጠርም ቢያንስ ትርጉሙ የሚገባን ይመስለኛል፡፡ የጀግንነት መጀመሪያው እውነት መናገርና ለእውነት ዋጋ መክፈል ነው፡፡
በአደባባይ እውነት መናገር የቻለ ሰው ጀግንነት ይጎድለዋል ማለት አይቻልም፡፡ ብዙዎቻችን ሆዳችንን ስንከተል፣ነጻነታቸውን የሚጠይቁ ጥቂት ሰዎች አሉን፡፡ብዙ ችግሮቻችንም የወናነት ናቸው፡፡…ጋንዲን እየጠቀስን፣ግን እንደ ሂትለር እንኖራለን፤እንደ ሊንከን እያወራን እንደ ሞሶሎኒ ጦር እንስላለን፡፡
“ቤልማ”
ማዶ ማዶ ማየት ቁጥር 3 እነሆ፡-
ማደጎ እንደሰጡት እንደ አሳዳጊ አልባ፣
ዝናም እንደሻተ
ሰኔ እንደራቀበት እንደ ዱር አበባ፣
ምኞት ነው ቀለቤ
እንባ ነው ማዕዴ
ትካዜ ነው ምግቤ፡፡
አይመስለኝም ነበር፤ሰው ብቻ እሚመንን
ለካ ሃገር ሲከፋው፤ትካዜ ሲወርሰው
ይሸሻል ከጀማው፤ይደበቃል ከሰው፡፡
ሰኔ የራቀበት አበባ ከኛ አይብስም- እኛ ነጻነት ተርበናል፡፡ ነጻነት ምን እንደ ሆነ ከሶስት መቶ አመታት በፊት ጀፈርሰን የጻፋቸው ደብዳቤዎች ይነግሩናል፡፡ እኛ ግን ዛሬም በነጻነት መናገር የሰማይን ያህል እየራቀን ነው፡፡ በገዛ ሃገራችን አንገታችንን መድፋት ግድ ሆኖብናል፡፡ ቀደም ሲል እንዳየነው ዓይነት የግጥም ስሜት ቢኖረውም ይኸኛው የሚለየው ሃገር መሸፈቱ፣ሃገር መደበቁ ነው፡፡ ወይም ሃገር ገዳም መግባቱ!! ይህ ደግሞ የልብ መመነን ሊሆን ይችላል፡፡ ማን ያውቃል!!
“ፈጣሪን ምስረታ”
ሸንጎ ተመካክረው ጉባኤ ዘርግተው
ያሳመኑኝ ሰዎች እግዜር ሞቷል ብለው፡፡
“የዓለም መሠረት፣የሰው ልጅን መሪ
አልፋና ዖሜጋ አድራጊ ፈጣሪ፤
የነገ ፍጻሜ፣የትናንት ጀማሪ
እኛ ነን ስላሴ መሰረቱን ሰሪ፡፡”
ሲሉ ወንጌል ጻፉ፡፡
ድንጋዩን ዳቦ ብለው ስለሚነግሩን ዋሾዎች ታሳያለች - ግጥሟ፡፡
የግርማ ግጥሞች ባብዛኛው ሃገራዊ ብሶቶች ናቸው፡፡ እውነትም ይህንን ማየቱ ነው - አንዱ አድናቆቴ፡፡ ሃገር የመውደድ አባዜ አለበት፡፡ ከጥቂት ትሩፋን አንዱ ነው - ገጣሚው!
ስለፍቅር ደግሞ እንዴት ጻፈ? ብለን እንጠይቅ፡፡ መቼም ፍቅር በትግልም በጦርነትም ውስጥ የሚወለድ ምትሃት ነውና አይቀርም፡፡ ”ምሽትና ፍቅር” በሚለው ግጥሙ እንዲህ ብሏል፡-
ተያየን በምሽት፣በአዲሳባ ሌሊት
በሐምሌ ደመና፣በድቅድቁ ጽልመት፡፡
ብርሃን ንፉግ ነው፣ኮከብ ይደብቃል
ምሽቱ ግን ቸር ነው፣ጨረቃን ያመጣል፡፡ (“ያመጣል”የሚለውን “ያደምቃል”ቢለው ምቱ ጠንከር ባለ!!”
ደግ አይበረክትም፣ደመናውም ቀንቶ
ጋረደው ሰማዩን፣እንደጥጥ ባዘቶ፡፡
በንጋቱ ጮራ፣የሄድሺው አንቺዬ
ምሽት ተማምኜ፣በእሱ ተስፋ ጥዬ፤
በሬ መች ተዘጋ፣ትመጫለሽ ብዬ፡፡
ከዕፀ በለስ ዕጣው ድርሻ ለቆረሰ
የመገንገን ውርስ ቀድሞ ለቀመሰ፤
ምን ባልንጀራ አለ? ከምሽቱ ሌላ
ለሄዋን መንታ ልብ የሚፈልግ መላ?
እንደጋኔን ጠሪ፣ምሽት ተጓድኜ
በውድቅት ሌሊት፣ወንዝ መሐል ኾኜ፡፡
አነበንባለኹ በማላውቀው ዜማ
የሰወረሽ ጋኔን ጩኸቴን ቢሰማ፡፡
ይህንን መዘርዘር፣መተንተን አያስፈልግም፡፡ በየልባችሁ ትርታ አዋድዱት፡፡ ግጥሞቹ የዜማና የምት ችግርም የለባቸውም፡፡ ስርዓተ ነጥቦችንም በሚገባ ተጠቅሟል፡፡አንዳንድ ግጥሞቹን ባንድ ሙሉነት ውስጥ መንቶና፣ሶስቶን በመገጣጠም አበጅቷቸዋል፤ተያያዥ አድርጎ በንዑስ ክፍሎች መከፋፈሉም አንባቢ ሳይሰለች እንዲያጣጥም ያደርገዋል፡፡ብቻ ግርማ ሞገስ ያለው ሆኗል፡፡
ይልቅስ አሳዛኝና አናዳጅ ጉድለቶቹ አጨራረስ ላይ የሚታዩ ናቸው፡፡ መዝጊያ ላይ ብዙ ግጥሞች ተበላሽተዋል፡፡ እግራቸው እንደተቀቀለ ፓስታ ተጥመልምለዋል፡፡ እውነት ለመናገር በአርትዖት የሚስተካከሉ ጥቂት የማይባሉ ግጥሞች አሉ፡፡…ግን በቸልታ ወይም ባለማጣጣም የተበላሹ ግጥሞች ብዙ ናቸው፡፡ሲያናድዱ!! ለምሳሌ- ላፈቀረ መንፈስ…ጀግንዬ…ውዳሴ ገበሬ…ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ ይሁን እንጂ “የጠፋችውን ከተማ ሃሰሳ” ጠንካራ አጥንት ያላቸው ጭብጦች የያዘ፣አድማስ የሚተረክክ፣ልብን የሚቆፍር እውነት ያረገዘ፣የግጥም ለዛውን ሳይተው ቁም ነገር የሚተርክ ውበታም የግጥም መድበል ነው!!...ገጣሚውን በድጋሚ ብራቮ ብያለሁ!!

Saturday, 23 February 2013 11:55

የግጥም ጥግ


መጣች
መጣች
እቴ መጣች
መጣች
ውዴ መጣች
መቼ ሄዳ ቀረች
መቼ ከእጄ ወጣች
አምቼ ሳልጨርስ
ተመልሳ መጣች!
ሄደች ብዬ ሳማት
ውል እያፈረሰች
እንባ ሆና መጣች
አይኔ ስር ፈሰሰች
ስትሄድ እያየኋት
ከአይኖቼ እየራቀች
የእንባ ጅረት ሆና
አይኔ ስር ፈለቀች!
ወለላ
የእኔ ወለላ
ሄደች ስል
ሆነች የሌላ
መጥታለች
ዙራ በመላ
ዘለላ
የእኔ ዘለላ
የራቀች መስላ
አይኔ ስር
መጣች በመላ
ሰርታብኝ
የእንባ ዘለላ
እኔው ልፈር እንጂ
አንቺ ምን በወጣሽ
ሄደች ብዬ ሳማሽ
ዞረሽ በአይኔ መጣሽ
ሄዳለች እያልኩኝ
በሩቅ ስናፍቅሽ
ዞረሽ በአይኔ መጣሽ
ከቶም ሳልጠብቅሽ
የእንባ ኩሬ ሆነሽ
ቀድቼ እማልዘልቅሽ
ሌት ተቀን ብጨልፍ
ዘለለት ብጠልቅሽ
አይንሽም ጥርስሽም
ሳቅሽም ለዛሽም
እቴ ሁለመናሽ
እያየሁ ሲርቀኝ
ምን ይውጠኝ ብዬ
ሲጠበኝ ሲንቀኝ
የገባሽልኝን
ቃልሽን አክብረሽ
እንባ ሆነሽ መጣሽ
በአይኔ ቦይ አሳብረሽ
ትታኝ ሄደች ብዬ
ከአጠገቤ ርቃ
አምቼ ሳልጨርስ
ክሴን ሳላበቃ
ስትሄድ እያየኋት
ከጐኔ እየራቀች
እምባ ሆና መጥታ
አይኔ ስር ፈለቀች
ጥላኝ ሄደች ስላት
ውድዬ ጨክና
በደም ስሬ በኩል
መጣች ቁስል ሆና
እኔም እንዳይከፋኝ
ሌላም እንዳይከፋኝ
ስውር ቁስል ሆነች
በጣቴ እማላካት
በሩቅ ስፈልጋት
ሳያት አሻግሬ
ፀፀት ሆና መጥታ
ገባች በደም ስሬ
ይሄውና ጥርስሽ
ሁሌ እሚናፍቀኝ
ይሄውና ሳቅሽ
ያየሁት ሲርቀኝ
ይሄው ሁለመናሽ
ቀርቶ እሚያስጨንቀኝ
ከደም ስሬ ገብቶ
እየተናነቀኝ
መጣች ተመልሳ
ትታኝ ሄደች ስላት
የጐን ውጋት ሆና
ዋግምት የማይነቅላት
የኔ ቃል አክባሪ
የኔ መልከመልካም
መጣች ተመልሳ
ሆናኝ ልብ ድካም!

 

“----አቶ ዮፍታሄ ንጉሴን የማውቃቸው ከቀኝ ጌትነታቸው በኋላ መምህር ከነበሩበት ዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት እድገት ቅዱስ ጊዮርጊስ ትምህርት ቤት ይባል ወደነበረው ዲሬክተር ሆነው በመጡበት ጊዜ፣ ከሰሩአቸው ትያትሮች አንዱ ላይ የሕፃን አክተር ሆኜ ስተውን ነው፡፡ “ሶረቲዮ”፣ “የኛማ ሙሽራ”፣ “ቦረናና ባሌ በጣልያን ወረራ ጊዜ” በሚሉትና በሌሎችም በአክተርነት ሰርቻለሁ፡፡
ከጣሊያን ወረራ በኋላ ጃንሆይ ሲመለሱ አቶ ዮፍታሄም ተመልሰው የድሮ ተማሪዎችን በመሰብሰብ “አፋጀሽኝ” የተባለውን ትያትር በቤተመንግሥት ለማሳየት ሐምሌ 16 ቀን 1933 ዓ.ም ትያትሩ እንዲታይ ተማሪዎች ሲሰበሰቡ እኔም ካለሁበት ተሰብስቤ “አፋጀሽኝ”ን (ሴት ገፀ ባህርይ) ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡
ከዚያ ጊዜ በኋላ አልተለየሁአቸውም፡፡ በኋላም ሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚደንት በነበሩበት ጊዜ እኔም በዚያው የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት የመዝገብና የፐርሶኔል ሹም በነበርኩበት ጊዜ አለቃዬ ስለነበሩ ህይወታቸው እስካለፈበት ጊዜ ድረስ አልተለያየንም፡፡ የእሳቸውን ታሪክ በመጠኑም ቢሆን እንድገልፅ በመታደሌ እድሌን አመሰግናለሁ፡፡“ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ምን አይነት ፀባይ ነበራቸው፤ ታጋሽ ናቸው፣ ቁጡ…? ትእግስተኛ፣ አዋቂ፣ ሁሉንም በእርጋታ የሚመሩ ነበሩ፡፡ ጠባያቸው ይሄ ነው፡፡ አሁን ስለጠባያቸው ሳይሆን የምናገረው ስለ ስራቸው ነው፡፡ “አፋጀሽኝ”ን ከሰራሁ በኋላ “ዓለም አታላይ” የሚለውን የመድረክ ትያትራቸውን ራሴ ዓለም አታላይ ሆኜ ሰርቻለሁ፡፡ ከኔ ጋር የሰራው ይድነቃቸው ተሰማ ያራዳ ኮረዳ ሆኖ ሰርቷል፡፡
ዮሐንስ ወዳዘጋጀው ታሪካቸው ልምጣ፡፡ እኔ አቶ ዮፍታሔ ከሞቱ በኋላ በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት “አፋጀሽኝ” ትያትር ለማዘጋጃ ቤት አክተሮች እንዳስጠናና እንዳሳይ ታዘዝኩ፡፡
እነ ተስፋዬ ሳህሉን፣ እነ… ሁሉን ላስታውስ አልችልም፡፡ እነሱ እነሱን ሰብስበው ይኼን ትያትር አስጠንቼ አሳይቻለሁ፡፡ እንግዲህ ትያትሩን አስጠንቼ ባሳየሁበት ጊዜ በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት አሁን ለመጀመርያ ጊዜ አደባባይ የወጣ ታሪካቸውን እኔ ለጉባኤው ገልጬ ነበር፡፡ ያ የገለጥኩት ታሪክ በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ ተፃፈ፤ በጊዜው፡፡ ትያትሩ ተደነቀ፡፡ እንደገና እነሱም እየደጋገሙ አሳይተውታል፡፡
(የ95 ዓመቱ አዛውንት አቶ በለጠ ግርማ በባለቅኔው ዮሐንስ አድማሱ የተዘጋጀውና በወንድማቸው በዶ/ር ዮናስ አድማሱ የአርትኦት ሥራው የተሰራለት “የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ አጭር የህይወቱና የፅሁፉ ታሪክ” መፅሐፍ ሰሞኑን በተመረቀበት ወቅት ከተናገሩት የተወሰደ)

 

ቴዲ ሊ ጽፎ ያዘጋጀውና ሊ ፔፕ ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበው “ከመጠን በላይ” የፍቅር ፊልም ነገ ከሰዓት በኋላ በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የክልል ከተሞች ይመረቃል፡፡ የ102 ደቂቃ ያለውን ይሄን ፊልም ለመሥራት ዘጠኝ (?) መፍጀቱን ያመለከተው ሊፔፕ ፊልም ፕሮዳክሽን፣ ፊልሙ በስድስት ዓለምአቀፍ ቋንቋዎች ተተርጉሞ ለመታየት መዘጋጀቱንና የተቀረፀበት ካሜራም SD Mark II canon መሆኑን ገልጿል፡፡ አጽመ ታሪኩን ባልተለመደ ውሳኔ ላይ ባደረገው የፍቅር ፊልም ላይ አማኑዔል ይልማ፣ ሄለን በድሉ፣ ሸዊት ከበደ፣ ኤልያስ ወሰንየለህ፣ ጋዜጠኛ መሳይ ወንድሜነህ፣ ቴዎድሮስ ጋሻው በዛና ሌሎችም በትወና፣ አማኑኤል ይልማና ሃይሉ አመርጋ (ጃኖ ባንድ) የማጀቢያ ሙዚቃ በመስራት፣ ቴዎድሮስ ወርቁ ፊልሙን ኤዲት በማድረግ ተሳትፈዋል፡፡

Saturday, 23 February 2013 11:45

ዝንቅ

“አስራ ሁለት ሆነን አንድ ሴት ወደን
እሷ ትስቃለች እኛ ተጨንቀን”
(የአዝማሪ ግጥም፤ ከእማማ ውዴ የሰማሁት)
ተለውጫለሁ፡፡
እዚህ ግቢ በቆየሁባቸው ሦስት ከሩብ አመታት ሞዴል የሆነ ህይወት ስመራ ቆይቻለሁ፡፡ ምንም ምስጢር የለውም፡፡ እዚህ ለምን እንደመጣሁ አውቃለሁ፡፡ ለትምህርት ነው፡፡ ክፍል እየገባሁ ትምህርቴን በስነ ሥርዓት እከታተላለሁ፡፡ የማይዛነፍ የጥናት ፕሮግራም አለኝ፣ በዚያ መሰረት አጠናለሁ፡፡ በትርፍ ጊዜዬ ስለስዕል፣ አነባለሁ፡፡ (አባቴ ምርጥ ሠዓሊ ነው) አልፎ አልፎ የራሴን ስኬቾች እሰራለሁ፡፡ ፊሊፕስ ዲጂታል ሬዲዮ አለኝ፤ ሬዲዮ አዳምጣለሁ፡፡ ቁርአን እና መፅሐፍ ቅዱስ አነባለሁ፡፡ መፅሐፍ ቅዱስ በቀን አምስት ምዕራፍ እያነበቡ በሦስት መቶ ስልሳ አምስት ቀናት፣ ማለት በአንድ አመት ያልቃል፡፡ በቀን አምስት ምዕራፍ አነባለሁ፡፡ ኮሌጅ ከገባሁ አሁን አራተኛ ዙር እያነበብኩ ነው፡፡ ዘንድሮ የሩብ አመት፣ ማለት አራት መቶ ሃምሳ ምዕራፎች አንብቤአለሁ፡፡ ከጐበዝ ልጆች ጋር ቼዝ እጫወታለሁ፡፡
ንፅሕናዬን እጠብቃለሁ፡፡
አሁን ግን ተለውጫለሁ፡፡
ቅብጥብጥ፣ እረፍት የለሽ፣ ጭንቀታም ሆኛለሁ፡፡ አባቴ ይህን ቢሰማ ምን እንደሚል አላህ ነው የሚያውቀው፡፡
***
የመጀመሪያ ዓመት ተማሪ ሆኜ ከገባሁ ጀምሮ ሁሌ እንደገረመኝ ነው፤ የተማሪው ወሬ፡፡ ሁሌም ስለሴቶች ነው፡፡ የኮሌጅ ወንዶች ስለሴቶች የሚያወሩትን ያህል የትኛውም የተፃፈ መፅሐፍ፣ የትኛውም የሴቶች ስብስብ፣ የትኛውም የህብረተሰብ ክፍል… ግማሹን እንኳን አይለውም፡፡
እኔ አይደለም ስለሴቶች ስለምንም ነገር አላወራም፡፡ ስለዚህ “…ድንጋይ ነው፣ ግዑዝ ነው፣ ዱዳ ነው፣ በድን ነው…” ይሉኛል፡፡ እንዳልሆንኩ ግን ያውቃሉ፡፡ እነርሱ የሚያደርጉትን ስለማላደርግ፣ አብሬአቸው ስለሴት ስለማላወራ “እርሱ ምንም አያውቅም” ይላሉ፡፡ እንደማውቅ ግን ያውቃሉ፡፡
አንድ ቀን ተሸነፍኩላቸው፡፡ ሁሉም ተሰብስቦ የየራሱን የሴት ምርጫ ሲናገር ድንገት ተመስጬ አዳምጥ ነበር፡፡ አንዳች ነገር ነው ጆሮዬን የያዘው፡፡
እኔ-አጠር ብላ ወፈር ያለች፤ ስትሄድ ፈጠን ፈጠን የምትል…
እኔ-ጥርሶቿ ነጫጭ የሆኑ፣ ጉንጮቿ የሚሰረጐድ…
እኔ-በጣም ቀይ የሆነች፣ ዳሌዋ ደልደል ያለ…
እኔ-ቀይ መልበስ የምታበዛ ሴት፣ በራሷ የምትተማመን…
እንዲህ እንዲያ ሲሉ ቆይተው ድንገት ከመሃላቸው አንዱ “አንተስ?” አለኝ፡፡
የምለውን ለመስማት ፊታቸው ላይ ታላቅ ጉጉት ይነበባል፡፡ አንዳች ነገር ፈንቅሎኝ መናገር ጀመርኩ፡፡
“…ቀጭን ሴት፣ እጅግ በጣም ቀጭን የሆነች፣ አጥነት እና ቆዳ ብቻ፣ እና ረዥም፣ አፍንጫዋ ሰልካካ፣ ጥርሶቿ ነጫጭ ሆነው ድዷን የተነቀሰች፣ አንገቷ ረዥም፣ ትከሻዋ ክብ፣ ከንፈሮቿ ስስ በጣም፤ ፀጉሯ ጥቁር፣ ብዛት ያለው እና ረዥም መሆን አለበት፤ ጣቶቿ ረዣዥም፤ ዓይኖቿ ጥቁር፣ ደግሞም መሃከለኛ፤ ድምጿ ረጋ ያለ፤ እና ቁጡ የሆነች፤ ጠይም፡፡”
ድምፄ ዝግ ብሎ ሃይል አለው፡፡ የወትሮው ቅዝቃዜ ተለይቶታል፡፡ ንግግሬም በአካላዊ ገለፃ የታገዘ ነበር፡፡ ልጆቹ አውርቼ ማብቃቴን ያወቁት ጨርሼ ረዘም ላለ አፍታ ከቆየሁ በኋላ ነበር፡፡ መጨረሴን እንዳወቁ ሁሉም በአንድ ላይ ሳቁ - ከጣራ በላይ፣ ከት ብለው፣ ከትከት ብለው ሳቁ፡፡ …ንግግሬ ውስጥ የትኛው ስህተት እንደነበረ፣ የትኛው እንደሚያስቅ አልገባህ አለኝ፡፡
“እብዶች” ብዬ ጥያቸው ወጣሁ፡፡
“የምትወዳት ልጅ እንጥሏ ምን አይነት ቢሆን ደስ ይልሃል?! ምላሷስ?!” ሲለኝ ሰማሁት አንዱ፡፡
ከዚያ በኋላ ሁሉንም ዘጋኋቸው፡፡ ማለቂያ በሌለው ዝምታዬ ዘለቅሁበት፡፡ ዝምታዬ ዋሻዬ ነው፤ መደበቂያዬ፤ የአባቴ ውርስ፤ በቁሙ እያለ ያወረሰኝ፡፡
ከዚያ በኋላ “ጓደኞቼ” ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ይሳለቁብኛል፡፡
ሲበዛ ሃሳባዊ ነህ…
ለካንስ እብድ ኖረሃልና…
ነገርህ ሁሉ የጤነኛ አይደለም…
አጉል ልዩ ፍጡር ልሁን ትላለህ…
ለምን የኮሌጁን ሳይካትሪስት አታናግረውም
አንተ የኛ ሰቃይ የሆንከው እኛ ሰንፈን እንጂ አንተ ብሩህ ሆነህ እንዳልሆነ አሁን ገባኝ ወዘተ ወዘተ ይሉኛል፡፡
አሁን ይኸ ሁሉ እኔ ከተናገርኩት ጋር ምን ያገናኘዋል?!
***
…ሁለቴ ይሁን ሦስቴ እዚህ ግቢ ከሴት ተማሪዎች የፍቅር ደብዳቤዎች ደርሰውኛል፡፡ ከእነማን እንደሆነ ግን አላውቅም፡፡ ብቻ እዚህ ግቢ ውስጥ እኔ የምፈልጋት አይነት ሴት እንደሌለች አውቃለሁ፡፡ ስለዚህ ሦስቱንም ወረቀቶች በቅጡ እንኳን ሳላነባቸው ነው የቀደድኳቸው፡፡ ከ”ጓደኞቼ” ለአንዱ ደርሶት ቢሆን ኖሮ ሺህ መቶ ሚሊዮን ፎቶ ኮፒ አባዝቶ ይበትነው ነበር፡፡ መጠየቄን ከእኔ በቀር ማንም አያውቅም፡፡
…ይህ ሁሉ ሊሆን እንደሚችል አባቴ ነግሮኝ ነበር፡፡

ምን እማይነግረኝ ነገር አለ እሱ?! በእኔ እና በእርሱ መሃል ያለው ግልፅነትና ቅንጅት በሦስቱ ሥላሤዎች መሃል መኖሩንም እንጃ፡፡ ውስጡን ገልብጦ ነው የሚነግረኝ፡፡ የእኔንም ህልሜን እንኳን እንድደብቀው አይፈልግም፡፡ ስለ ክህደት ይቆጥረዋል፡፡ ከሚያወራልኝ ታሪኮች መሀል ስለ እናቴ የሚነግረኝ ከምንም በላይ ይመስጠኛል፡፡ “እናትህ ነብር ነበረች” ብሎ ይጀምራል፡፡ “..ነፍሷን ይማርና” አይልም፤ አሁንም በህይወት እንዳለች ነው የሚቆጥረው መሰል፡፡ በነገራችን ላይ እኔን ስትወልድ ነው የሞተችው፤ በሃያ አመቷ፤ …አባቴ ያኔ ሃያ ሦስት ነበር፡፡ ከሞተች አንስቶ እስካሁን ድረስ ብቻውን ነው የሚኖረው፡፡ አንድ ቤት ውስጥ የምንኖረው አባቴ፣ እኔ፣ አንዲት ነጭ ድመት ነን፡፡ ተመላላሽ ሠራተኛ አለችን፡፡
“…ቀጭን ነበረች ሲበዛ፤ አጥንትና ቆዳ ብቻ፡፡ …ጥርሶቿ ነጫጭ ሆነው ድዷ በሚያምር ንቅሳት የተዋበ ነበር፡፡ አፍንጫዋ እንዲህ ነው” (አመልካች ጣቱን አፍንጫው ጥግ ላይ ሰክቶ)… ይህን ታሪክ ስንቴ እንደነገረኝ አላውቅም፡፡ ግን ቢያንስ በቀን አንዴ ሳይነግረኝ አይውልም፡፡ በጣም ይወዳት ነበር፡፡ ብዙ አያወራም፤ ካወራም ስለ እርሷ ነው፡፡…
“…ሁለተኛ ደረጃ ስንማር ነበር ያፈቀርኳት፡፡ …ከስንት ጭንቀት በኋላ ደብዳቤ ፃፍኩላት፡፡ ደብዳቤውን በሰጠኋት ማግስት እሳት ለብሳ እሳት ጐርሳ መጥታ በጥፊ አናጋችኝ፡፡ (ቀኝ ጉንጩን እያሻሸ) አንድ ሳምንት ግቢው ውስጥ መጠቋቆሚያ ሆንኩኝ፡፡ ያን ሰሞን ራሴን ብሰቅል ወይ የሆነ አሲድ ብጠጣ ደስታውን አልችልም ነበር፡፡ …በኋላ እየሳቀች መጥታ ይቅርታ ጠየቀችኝ፡፡ …ቀጭን ነበረች፤ አጥንት እና ቆዳ ብቻ፤ ፀጉሯ ጥቁር፤ ከንፈሮቿ ስስ፤ አንገቷ ረዥም፤ ትከሻዋ ክብ፡፡”
ሲያወራልኝ ሁሌ ተመስጦ ስለሆነ፤ የማዳምጠው ሁሌ ተመስጨ ነው፤ በከፍተኛ ጉጉት ተይዤ፡፡ ዝምተኛ ቢሆንም ሲናገር ወሬውን ጥሩ ያስኬደዋል፡፡ ዝምታ ከጊዜ በኋላ የተጣባው እንደሆነ ያስታውቃል፡፡ …አባቴ ሠዓሊ ነው፡፡ ታዲያ የቀጭን የረዥም፣ የሰልካካ ሴት ምስል ነው ስቱዲዮውን የሞላው፤ ሳሎናችንንም ጭምር፤ መኝታ ቤቶች ሳይቀሩ፡፡ በተለያየ ሁኔታ ተስለው፡፡ …ገንዘብ ሲፈልግ ብቻ ነው ሌሎች አይነት ሥዕሎችን የሚሰራው፡፡
የሰሞኑን ጭንቀቴን ለአባቴ ደውዬ ልነግረው ብዬ ፈራሁ፡፡ ጤንነቴን እንዲጠራጠር፣ በእኔ ያለውን እምነት እንዲያጣ አልፈለግሁም፡፡ ሆኖ የማያውቅ ነገር ነው የሆነው፡፡ እኔም ራሴ ነገሩን ደጋግሜ ሳስበው እየቄልሁ ያለሁ ይመስለኛል፡፡ ስለፊልም ታሪክም የማስብ ይመስለኛል፡፡ የማክሲም ጐርኪይ ልብ-ወለድም ትውስ ይለኛል፤ ሃያ ስድስት ዳቦ ጋጋሪዎች በአንድነት አንዲት ሴት ያፈቀሩበት ታሪክ፡፡ የእኔ ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ እኔ ብቻዬን ሆኜ ነው ብዙ ሴቶች ያፈቀርኩት፡፡ በራሴ ህይወት ውስጥ እየተከሰተ ያለ ነገር መሆኑን መቀበል ፍፁም አልቻልኩም፡፡ ለወሬ የማይመች ነገር ነው፤ መያዣ መጨበጫ የሌለው፡፡
ፍቅር ይዞኛል፡፡
በጉዳዩ ላይ ብዙ አስቤበታለሁ፡፡ ቡና እየጠጣሁ፤ የእግር ጉዞ እያደረኩ፤ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቼ አስቤበታለሁ፡፡ በአሰብኩት ቁጥር ግን ሁሉም ነገር ይበልጥ እየከበደ ይመጣል፤ እየተጫነኝ፡፡
ሌላው ይቅር ክፍል መግባት አቁሜያለሁ፤ አላጠናም፤ ውሎዬ ከተማ ነው፡፡ ከኮሌጅ ጠዋት የወጣሁ ማታ የግቢው ሰዓት እላፊ ሲደርስ እመለሳለሁ፡፡ ዝምታዬ በርትቷል፡፡ …ቅዠቴም ለጉድ ሆኗል፡፡
የቀረኝ አንድ አማራጭ ነው፡፡ ለአባቴ መደወል፡፡
“ሄሎው… አባቴ”
“አቤት ማሙሽ…”
ሁሌም ለእርሱ ማሙሽ ነኝ፡፡ አሁን ሃያ አንድ ዓመት ሆኖኛል፡፡
“ምነው ደህና አይደለህም እንዴ!? ድምፅህ… ልክ አይደለም፡፡”
“አባቴ ሁሌ አንድ ነገር እነግርሃለሁ እልና፤ ከዚያ በቃ..” ዝም አልኩ፡፡
“…ማሙሽ እኔ ይህን መስማት አልችልም፡፡ የእኔ ልጅ ነው ለአባቱ መናገር ስላለበት ጉዳይ የሚጨነቀው?!”
“እንዴት መሰለህ አባቴ፤ ትንሽ ግራ የሚያጋባ ሆኖብኝ ነው እንዴት እንደምነግርህ የጨነቀኝ፡፡”
“ማሙሽ! በእርግጥ ከልጄ ጋር ነው እያወራሁ ያለሁት?! አነተ ነህ ችግርህን ለእኔ ለመንገር የምትጨነቀው ወይ?!”
“አባቴ አትቆጣ፡፡ ቆይ ልንገርህ በቃ፡፡ ይሄውልህ፣ ምን መሰለህ፣ እ-እንትን፤ አለ አይደል… ፍቅር…” ከት ብሎ ሳቀ፤ የደስታ ሳቅ፤ የአባቴ ሳቁ በጣም ነው ደስ የሚለው፡፡ የሳቁ ዜማ እና ግጥም ደራሲ ራሱ ነው፡፡
“ፍቅር ያዘህ? ታዲያ ይህ ምን የሚያስደንቅ ነገር አለው? ሁሌ እነግርህ አልነበር ሊከሰት እንደሚችል? ቆይ ኮሌጅ ውስጥ ከምትማር ልጅ ጋር ወይስ…?”
“ይህን ከመመለሴ በፊት ስለ እናቴ የምትነግረኝን ታስታውሳለህ? ስለ ቅጥነት፣ ስለ…”
“አዎ፤ እናትህ ቀጭን ነበረች፤ አጥንት እና ቆዳ ብቻ፤ ፀጉሯ ጥቁር፤ ረዥም እና ጫካ ነበር፤ ጥርሶቿ ነጫጭ ነበሩ፤ ድዷ…” የዘወትር ትርክቱን ከጨረሰ በኋላ ጠየቀኝ፡-
“እና እሷን የምትመስል ሴት ነው ያፈቀርኩት በለኛ!”
እሷን የምትመስል ሴት ሳትሆን ሴቶች!”
“ምን?!...” የድምፁ ቃና ተለወጠ፡፡ “…አልገባኝም ማሙሽ”
“አባቴ፣ ደብዳቤ ልፅፍልህ ብሞክር አልቻልኩም፡፡ በስልክ እንዳልነግርህ የሚሆን አይደለም፡፡ እና ምን እንደሚሻል አላውቅም”
“እባክህ ማሙሽ አስጨነከኝኮ”
“ይቅርታ አባቴ”
ሳላስበው እንባዬ መጣ፤ ድምፄ የለቅሶ ቃና ያዘ፡፡
“ቆይ ቆይ ዛሬ ምንድነው?” አለኝ አባቴ፡፡
“ሀሙስ”
“ወደ መቀሌ ሁሌ ነው መሰለኝ በረራ ያለው፡፡ በቃ ቅዳሜ ወይ እሁድ እደርሳለሁ እሺ?”
ደነገጥኩ፡፡
ምንም ከማለቴ በፊት የተለመደውን “ማሙሽ እወድሃለሁ” ብሎ ስልኩን ዘጋው፡፡ መነጋገሪያውን አንከርፍፌ ብዙ ቆየሁ፡፡ ባለ ሱቁ የመንጠቅ ያህል ሲቀበለኝ ነው የባነንኩት፡፡ ሂሳቡን ከፍዬ ወጣሁ፡፡ ቀስ ብዬ እያዘገምኩ ወደዚያ የፅህፈት መሳሪያ መደብር አቀናሁ፡፡ በመቀሌ ትልቁ የፅህፈት መሳሪያ መደብር ነው፡፡ ሁለት እህትማማቾች ናቸው ደንበኛን የሚያስተናግዱት፤ ዮርዳኖስ እና ሙሉ ብርሃን፡፡ የሃያ አንድ እና የሃያ አመት ወጣት ሴቶች፡፡ አንዷ እቃ ታቀብላለች፤ ሌላኛዋ ሂሳብ ትቀበላለች፡፡ …በሆነ አጋጣሚ ድንገት እንዲያው ድንገት ወረቀት አልቆብኝ ልገዛ ገባሁ፡፡ በፊት ቢሆን ከሌላ መደብር ነበር የምገዛው፡፡

…ጭር ብሎ ነበር ቤቱ፡፡ …የሁለቱም ሴቶች አለባበስ ሆን ተብሎ አይን ለመያዝ የተደረገ ይመስላል፡፡ መጀመሪያ አንዲቷን አየሁዋት፡፡ ቀይ ናት፡፡ ፀጉሯን ለቃዋለች፤ ፍሪዝ ነው፤ ጥቁር፣ ብዛት ያለው፣ ረዥም ፀጉር፡፡ አይኖቿ ጥቋቁር ናቸው፤ መሀከለኛ፡፡ ጥርሷ ፍንጭት፣ ሰውነቷ ደልደል ያለ ነው፡፡ ቁመቷ አጭር፡፡ ትከሻዋ ክብ ነው፡፡ …ወደ ሌላይቱ ዞርኩ፡፡ ፈገግ ብላለች፤ የጥርሶቿ ንጣት ያስደነግጣል፡፡ ችምችም ያሉ ናቸው፡፡ ድዷን ተነቅሳዋለች፡፡ በጣም ያምራል፡፡ ቅጥነቷ ለጉድ ነው፡፡ አጥንት እና ቆዳ ብቻ ነች፤ ረዥም ናት፤ አፍንጫዋ ደግሞ ሰልካካ፤ አንገቷም ሰልካካ ነው፡፡ ከንፈሮቿ ስሶች ናቸው፡፡

እንደ እህቷ ከንፈሮች አይወፍሩም፡፡ …አይኖቿ ትንንሾች ናቸው፤ ገጿ ደግሞ ጠይም፡፡ ፀጉሯን ሰብስባ መሃል አናቷ ላይ አሲዛዋለች፣ አጭር ነው፡፡ በስተመጨረሻ ጐን ለጐን እንደቆሙ አንድ ላይ አየሁዋቸው፡፡ ይሄኔ ሰውነቴ መራድ ጀመረ፡፡ ትንፋሼ ፈጣን እና ቁርጥ፣ ቁርጥ የሚል ሆነ፡፡ ብብቴን፣ ውስጥ እጄን፤ አፍንጫዬን አላበኝ፡፡ ዘላለምን ለሚያህል ጊዜ ቆሜ ቀረሁ፡፡ ወይም እንደዚያ መስሎኛል፡፡
ደልደል ያለችው (ዮርዳኖስ) ተናገረች፡-
“ምን ነበር ወንድሜ?”
ሌላ መአት፡፡ የድምጿ እርጋታ ከድንዛዜዬ ከማንቃት ፈንታ ባለሁበት ውዥንብር እንድቀጥል አደረገኝ፡፡ ከስንት ትግል በኋላ ያሰብኩትን ዘንግቼ ብዕር ገብይቼ ወጣሁ፡፡ ያን ሌት አይኔ ፈጦ አደረ፡፡ ምን እንዲያ ሊያደርገኝ እንደቻለ አልገባህ አለኝ፡፡ ልጆቹ በሁኔታዬ አለቅጥ ነበር ግራ የተጋቡት፡፡ እኔም በእራሴ እንደዚያው፡፡… አስር አስር ጊዜ ሲተያዩ ነበር፡፡
ምን እንዲያ እንዳደረገኝ ለማወቅ እዚያ ቤት ተመላለስኩ፡፡ በቀን ከሁለት ጊዜ በላይ እሄድ ነበር፡፡ እርሳስ፣ እስኪርብቶ፣ የብዕር ቀለም፣ ባይንደር፣ አጀንዳ፣ ሀይላይተር… መደብር ውስጥ ያሉትን እቃዎች በየተራ ገዛሁ፡፡ ከልጆቹ ጋር ተላመድን፡፡ ውሎ እያደር ችግሬ ገባኝ፡፡ ድንገት መደብሩ ውስጥ አንዲቷን ልጅ ብቻ ያየሁ እንደሆነ የሆነ ጉድለት ይሰማኛል፡፡

ያኔ ቶሎ እወጣለሁ፡፡ ያሉት ሁለቱም ካልሆኑ አንዳንዴ እንደውም ከበር እመለሳለሁ፡፡ ሁለቱ አንድ ላይ የሆኑ እንደሆኑ ግን ነፍሴ በሀሴት ትዘላለች፡፡ …በተቃራኒው ደግሞ እህትማማቾቹ እኔን ሊያገኙኝ የሚፈልጉት ለየብቻ ነው፡፡ አንድ ላይ ሳገኛቸው አንዷ አንዷን ከአጠገቧ ለማራቅ የማትዘይደው የለም፡፡ ሊታረቅ የማይችል ውዥንብር ተፈጠረ፡፡ ዮርዳኖስ እና ሙሉ ብርሃን እስከ መኳረፍ ደረሱ፡፡ …የእኔም ጭንቀት እየበረታ መጣ፡፡
…ለእኔ አንድ ላይ ሲሆኑ ነው ያን ምስል በጥምረት የማገኘው፡፡ የሁለቱ ገፅ ድምር ነው አንድ መስል የሚሰጠኝ፡፡ የአንዲቷ ፀጉር ሲደመር፣ የሌላዋ አፍንጫ ጥንቅር… የውብ ሴት ምስል ይታየኛል ያኔ፡፡
ውስጤ ያለችውን ሴት ሁለት ሴቶች ላይ ተበታትና አገኘኋት፤ ዮርዳኖስ እና ሙሉ ብርሃን ላይ፡፡ እና ሁለቱንም እኩል አፈቀርኳቸው፤ በአንድ ላይ፡፡ በቃሉ ተራ ትርጉም ሁለት ሆኑ እንጂ እኔ ያፈቀርኩት አንዲት ሴት ነው፡፡
…አባቴ ስቱድዮ ውስጥ ከተለመደው የቀጭኗ ሴት (ለምን እንደሆነ እንጃ እናቴ ማለት ከበደኝ) ምስል የተለዩ ሁለት ስዕሎች አሉ፤ ጐን ለጐን የተቀመጡ፡፡ አባቴ “በሁለቱ ስዕሎች ውስጥ ያለውን ምስጢር ካገኘህ ሽልማት አለህ” ብሎ ነበር፡፡ ለቀናት ያህል አፍጥጬባቸው ብውልም ምስጢሩን ልፈታው አልቻልኩም ነበር፡፡ አባቴ እንዲነግረኝ ብለምነውም ፍቃደኛ አልነበረም፡፡ “እራስህ ፈልገህ ማግኘት አለብህ፡፡” ነበር መልሱ፡፡ መልስ መስጫው ጊዜ አልፎ እንዳይሆን እንጂ አሁን መልሱን አግኝቼዋለሁ፡፡
አሁን ሁሉ ነገር ግልጽ ሆነልኝ፡፡ ውስጤ እንዳትረሳ ሆና በህያው ብሩሽ የተሳለችው ሴት፣ እንዳትገረሰስ ሆና የፀናችውን ሴት መቀሌ ሰማይ ስር ሁለት ሴቶች ላይ አገኘኋት፡፡
…አንድ ነገር እፈራ ነበር፡፡ ልክ እሷን የምትመስል ሴት ካላገኘሁ ጓደኛ ሊኖረኝ እንደማይችል ጠንቅቄ አውቅ ነበር፡፡ ፍራቻም ነበረኝ፤ እንደማላገኝ፤ አሁን ግን…
መደብሩ ጋ ስደርስ አመነታሁ፡፡ ልመለስ ግን እንደማልችል አውቃለሁ፡፡ ገባሁ፡፡ ሁለቱም በሰፊ ፈገግታ ተቀበሉኝ፡፡ አንዳች ምሉዑነት ተሰማኝ፤ እርካታ፤ እድለኝነት፡፡
…በሁለቱ እህትማማቾች መሐል ያለው ቅራኔ ትዝ ሲለኝ ግን ቅዝቃዜ ወረረኝ፡፡ እነርሱን ካወቅሁ ወዲህ የተለያየ ስሜት በየደቂቃው ይፈራረቅብኛል፡፡ ሐዘን ከደስታ፣ እርጋታ ከእረፍት ማጣት ጋር፡፡ …የዮርዳኖስ እና የሙሉብርሃን ቅራኔ ከእለት እለት እየበረታ መጥቷል፡፡ አሁንም እንዲህ የጐሪጥ እየተያዩ አብሬአቸው ልቆይ አልቻልኩም፡፡ ነዶኝ ትቻቸው ወጣሁ፡፡
የወትሮው ጭንቀቴ ባሰብኝ፡፡ እግሮቼ እስኪዝሉ በመቀሌ አውራ ጐዳናዎች ላይ ተንከራተትኩ፡፡ ሀውዜን አደባባይን ለማይቆጠር ጊዜ ዞርኩት፡፡ ጐዳና አሉላ፣ ጐዳና ሠላም፣ ጐዳና አግአዚ፣ ጐዳና ሙሴ ላይ ለማይቆጠር ጊዜ ተመላለስኩ፡፡ ሲመሽ እና ስዝል ጊዜ ኮንትራት ታክሲ ይዤ ወደ ኮሌጅ አመራሁ፡፡
…የመኝታ ክፍል ተጋሪዎቼም ሆኑ ሌሎች ተማሪዎች እንደድሮው አይደሉም፡፡ ወይም እንደዚያ መስሎኛል፡፡ በሀዘኔታ ነው የሚያዩኝ፡፡ የበፊቱ ንቀት የለም፡፡
…ብዙዎቹ ችግሬን ሊካፈሉ ቀርበው ሲጠይቁኝ በጩኸት አስደንግጬአቸዋለሁ፡፡ እንዲያም ሆኖ ይንከባከቡኛል፡፡ አልጋዬ ተነጥፎ ነው የሚጠብቀኝ፡፡ ሎከር ስከፍትም ታጥበው የተቀመጡ ልብሶችን ነው የማገኘው፡፡ ግን ይህም ያናድደኛል፡፡ የሌሎች እርዳታ ስር መውደቄ ያበግነኛል፡፡
(…ግን፣ ግን ይህን ሁሉ እንዴት ሊሆን ቻለ) አፍጠው የሚያዩኝን ጓደኞቼን እንዴት ዋላችሁ እንኳን ሳልል ጫማዬን ብቻ አውልቄ ተጠቅልዬ ተኛሁ፡፡
…አባቴ ቅዳሜ አምስት ሰዓት ተኩል መቀሌ ገባ፡፡ እስክንገናኝ ብዙ እንደተጨነቀ ያስታውቅበታል፡፡ ከአዲስ አበባ የሚነሳበትን ሰዓት አስታውቆኝ ስለነበር አየር ማረፊያ ድረስ ሄጄ ነው የተቀበልኩት፡፡ ተጠመጠመብኝ፡፡ ተጠመጠምኩበት፡፡ አይኑ እንባ አዘለ፡፡ ተጐሳቁዬ ነበር፡፡ በጣም ከስቻለሁ፡፡ አይኖቼ ሠርጉደዋል፡፡ ፀጉሬ ተንጨባሯል፡፡ አለቀሰ፡፡ አላለቀስኩም፡፡

ከንፈሬን በላሁት፡፡ ሁሉን ነገር ለመስማት አለመጠን ጓጉቶ ነበር፡፡ ከአየር ማረፊያው ወደ መቀሌ ከተማ እየሄድን ጀመርኩለት፤ አክሱም ሆቴል ነበር አልጋ የያዝኩለት፤ እዚያ ጨረስኩለት፡፡ እንደጠበኩት ብዙ አልተገረመም፤ መጐሳቆሌ ከፈጠረበት ሀዘን በስተቀር ምንም እንግዳ ስሜት አላየሁበትም፡፡ ሁለት ሴት በአንድ ላይ እኩል ማፍቀሬ የፈጠረበት ግልጽ ስሜት ግልጽ አልነበረም፡፡ ልጆቹን ለማየት ግን በጣም ጓጉቷል፡፡ ሰኞ እለት አስተዋወቅሁት፡፡ ሁለቱንም አንድ ላይ ሲያያቸው ከእኔ የባሰ የስሜት ማዕበል ነበር የመታው፡፡ አባቴ እንዲያ ሲሆን ሳይ የመጀመሪያ ጊዜዬ ነው፡፡ ጉንጬን በእጁ እየዳበሰ ለረዥም ጊዜ ፈዞ ቀረ፡፡
ሰዓሊ ስለሆነ በሁለቱ ገጽ ላይ ያለውን ቅኔ ለማግኘት እና ለመረዳት ጊዜ አልወሰደበትም፡፡ የመባነን ያህል ነቅቶ የኋላ ኋላ ተዋወቃቸው፡፡ ዮርዳኖስ እና ሙሉ ብርሃን በአባት እና ልጅ አኳኋን ቅጥ አምባር ማጣት አለቅጥ ነው ግራ የተጋቡት፡፡
በእኔ ላይ የሆነው በአባቴ ተደገመ፡፡
አባቴ፤ መቀሌ ወር ያህል ቆየ፤ ያለምንም ፋይዳ፡፡ ሁሌም እምናወራው ወሬ አንድ አይነት ነው፤ ልጆቹ የሚወደዱ እንደሆነ፡፡ አንድም ቀን በመፍትሔው ላይ ተነጋግረን አናውቅም፡፡ ለዚህ፣ ለዚህ የእሱ መምጣት እንዳስፈለገ አልገባኝም፡፡ ….ያም ሆኖ ግን ባህሪዬ ተስተካክሏል፡፡
የምወደው አባቴ አጠገቤ ስላለ ይሆናል፡፡ ማጥናት ጀምሬአለሁ፡፡ ሰውነቴም መጠገን ይዟል፡፡ ከዮርዳኖስ እና ከሙሉ ብርሃን ጋር ያለን ግንኙነት ግን ምንም መሻሻል ሳያሳይ እንደነበር ቀጥሏል፡፡ …አባቴ የመጣው የዕረፍት ጊዜውን ለማሳለፍ እንደሆነ እየመሰለኝ መጥቷል፡፡
አባቴ፣ መቀሌ ባለበት ቀናትም የሥዕል ሥራውን አላቋረጠም፡፡

ከሸራ፣ ከቀለም ሽታ፣ ከብሩሽ፣ እና ከቅርፆች…ተነጥሎ ሊኖር አይችልም፡፡ ግን ምን እየሳለ እንደሆነ አሳይቶኝ አያውቅም፡፡ እኔም አልጠየቅሁም፡፡ ሲጨርስ መጀመያ የሚያሳየው ለእኔ እንደሆነ ግን ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ በፊት ቢሆን ግን ሲጀምር፣ መሀል ላይም፣ ሲጨርስም ያሳየኝ ነበር፡፡ እንዲያውም አንዳንዴ ሀሳብ ብልጭ ሲልለት በችኮላ የወረቀት ላይ ንድፎቹን ያሳየኝ ነበር፡፡ የሆነስ ሆነና የመቀሌ ሰማይ ስር ሆኖ ምን እየሳለ ይሆን ይኼ ምርጥ ሰዓሊ እያልኩ አስባለሁ፡፡
ፈተና እየተቃረበ ስለሆነ አባቴም በስዕል ስራው ስለተጠመደ፣ በቀን በቀን መገናኘቱን ትተነዋል፡፡ ቢበዛ ከሁለት ቀን አንዴ ብንገናኝ ነው፡፡ ዛሬ ካገኘሁት አራተኛ ቀኔ ነው፡፡ ጥናቴን ስጨርስ ወደ ከተማ፣ አባቴ ወዳለበት ሄድኩ፡፡ አካሄዴ የመፍትሔውን ነገር እንዲያስብበት ለመንገር እና ቸልተኝነቱ ከምን እንደመነጨ ለመጠየቅ…ብቻ በብሶቶች ተሞልቼ ነው አባቴ ወደ አረፈበት ሆቴል ያመራሁት፡፡ ያዳፈንኩት የመሰለኝ ፍቅር ቦግ ብሎ እየተቀጣጠለ ነው፡፡
አክሱም ሆቴል ስገባ አባቴ ጉርሻ ያስለመደው አስተናጋጅ፣ በሰፊ አፉ ትልቅ ሳቅ እየሳቀ ወደ እኔ መጣ፡፡ እንደወትሮው ሆኖ እጅ ነሳኝ፡፡ እጆቹን ወደ ኋላ አጣምሮ፤ ስብር አለ ወደፊት፡፡ ቀና ሳይል እጆቹን ብቻ አላቆ ቢጫ ፖስታ አቀበለኝ፡፡ አባቴ ነው እንዲህ አይነት ቀለም ያለው ፖስታ የሚጠቀመው፡፡
ደነገጥኩ፡፡
“ምንድነው? አባቴስ?!”
“ዛሬ ወደ አዲስ አበባ በረሩ”
“ምነው? ምን ተፈጠረ? ማለቴ ሳይነግረኝ? ሳንገናኝ?”
“አይ በደህና ነው፡፡ እስኪ የተውልህን መልእክት አንብበው”
ስልት በሌለው ሁኔታ ፖስታውን ቀደድኩት፤ እጄ እየተንቀጠቀጠ ነው፡፡
“…ማሙሽ ዮርዳኖስ የእኔ ባለቤት የአንተ…ሆና አብራኝ ወደ አዲስ አበባ በራለች፡፡ ሙሉ ብርሃን ደግሞ ትምህርትህን እንደጨረስክ አብራህ ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት በሙሉ ፈቃደኝነት እየጠበቀችህ ነው፡፡ እንግዲህ ሁለቱንም የኛ፣ ሁለታችንም የእነሱ ሆንን ማለት አይደል? ከዚህ ውጭ መፍትሔውን ሙሉ ሊያደርግ የሚችል ምንም አማራጭ የለም፡፡ ማሙሽ በዚህ ሁኔታ ወደ አዲስ አበባ የተመለስኩት ነገሩን መጀመሪያ ስትሰማ ሐሳቤ ስህተት ቢመስልህ ገጽህ ላይ ሊታይ የሚችለውን ስሜት ልቋቋም እንደማልችል ስላመንኩ ነው፡፡ በደንብ አስብበት እስኪ፡፡ እኔ ብዙ አስቤበታለሁ፡፡ በነገራችን ላይ የሠርጋችሁን ቀን የአንተ ምርቃት ቀን ብታደርጉት በጣም ደስ እንደሚላት ሙሉ ብርሃን ነግራኛለች፡፡ መልካም ጊዜ፡፡ ማማሽዬ እወድሃለሁ፡፡
አባትህ”
አቃሰትኩ፡፡
አስተናጋጁ ሁለት እጆቹን ወደኋላ አጣምሮ አጠገቤ አለ፤ አሁንም፡፡
“ክፍላቸው ውስጥ ዕቃ ትተውልህ ሄደዋል መሰል ቁልፍ ሰጥተውኛል፤ ይኸው” ብሎ ቁልፍ አስጨበጠኝ፡፡
በደመ ነፍስ ወደ ስድስት ቁጥር አመራሁ፡፡ ገና በር ከመክፈቴ ዓይን ከሚስቡ ሰው አከል የሁለት ሴቶች ምስል ጋር ተፋጠጥኩ፡፡ የዮርዳኖስ እና የሙሉ ብርሃን ምስል…
ተንደረደርኩ፡፡ በአንድ እግር ስንዘራ የዮርዳኖስን ምስል ሸነተርኩት፡፡ ሁለት፣ አራት…በጥርሴ፣ በእግሬ፣ በእጄ…እፎይ!
ወደ ሙሉ ብርሃን ምስል ስዞር በሩ ሳይንኳኳ ተከፈተ፡
ሙሉ ብርሃን፡፡
ሙሉ ብርሃን በአካለ ሥጋ ከፊቴ ቆማለች፤ ምስሏ ከኋላዬ አለ፡፡
አየኋት፡፡
አየችኝ፡፡
አየኋት፡፡
አየችኝ፡፡
…ቀስ በቀስ ስሜቴ ሲረጋጋ ይታወቀኛል፡፡ እጆቿን ዘርግታ ተንደረደረች፡፡ አቅፋ አልጋ ላይ ጣለችኝ፡፡
ከወደቅንበት የተነሳነው ሁለታችንም ድንግልናችንን አልጋው ላይ ጥለን ነው፡፡
1992 ዓ.ም፤ መቀሌ