Administrator

Administrator

አገሪቱ ከግጭትና ቀውስ አዙሪት አልወጣችም ብሏል
· መንግስት የዜጎችን ደህንነት ማስጠበቅ አልቻለም ይላል
· ጠንካራ ተፎካካሪዎች እንዳይፈጠሩ እንቅፋት በዝቷል


ነፃነትና እኩልነት ፓርቲ፤ የተመሰረተበትን የአምስተኛ አመት በዓል በተለያዩ ኹነቶች ሲያከብር መሰንበቱን ገልጿል፡፡ ክብረ በዓሉን ምክንያት በማድረግም የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ግንቦት 10 ቀን 2016 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ፤ የፓርቲውን የአምስት አመት አጠቃላይ ጉዞ፣ ስኬቶቹን፣ ተግዳሮቶቹንና ውስንነቶቹን በመገምገም ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችን ለይቷል ተብሏል፡፡

ነእፓ- የዛሬ 5 ዓመት?!
“ከዛሬ አምስት አመት በፊት ነፃነትና እኩልነት ፓርቲ ሲመሰረት፣ ግዙፍ ራእይና ተልእኮ ሰንቀን፣ በርካታ ዓላማዎችንና ግቦችን ከፊታችን አስቀምጠን፣ በከፍተኛ የሀገር ፍቅርና በጋለ የስራ ስሜት ነበር፣” ይላል-ፓርቲው በመግለጫው፡፡ ወደ ኋላ አምስት ዓመት መለስ ብሎም ዕቅዶቹን፣ ራዕዩን፣ ግቦቹን፣-- ያስታውሳል - ፓርቲው፡፡
“ነእፓ ከዛሬ አምስት አመት በፊት ሲመሰረት መላ የሀገራችን ህዝቦች ውድ ዋጋ የከፈሉለት እንዲሁም በታላቅ ተስፋና ጉጉት የተቀበሉት “የፖለቲካ ሪፎርም” ዳር እንዲደርስ የበኩላችንን ለማበርከት ቃል ገብተን ነበር፣
“የዛሬ አምስት አመት ነእፓን ህያው ስናደርግ ሀገራችንን ወደተሻለ ማህበረ-ኢኮኖሚ የእድገት ደረጃ ለማስፈንጠር፣ ጠንካራ ዴሞክራሲ፣ የፖለቲካ መረጋጋትና ሰላም የሰፈነባት፣ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የተከበሩበት፣ ነፃነት፣ እኩልነትና ፍትህ የተረጋገጡባት ሀገር ለመመስረት ተስፋ ሰንቀን ነበር፣
“የነፃነትና የእኩልነት መንገዳችንን አሀዱ ብለን ስንጀምር የተራራቁትን አቀራርበን፣ የተጣሉት አስታርቀን፣ የተለያዩትን አንድ አድርገን፣ በሀገራችን ሰላምና መረጋጋት፣ ወንድማማችነትና እህትማማችነት እንዲሰፍን አልመን ነበር፣
“የነእፓን ጉዞ አንድ ብለን ስንጀምር ድህነትና ኋላ ቀርነት፣ ድርቅና ርሀብ፣ የእርስ በእርስ ጦርነት መገለጫዋ የሆነችውን ሀገራችንን ከተዘፈቀችበት አዙሪት ለማላቀቅና፣ የወገናችንን የተሰበረ ልብ ልንጠግን ቃል ገብተን ነበር፣
“ነእፓ የሀገራችንን የፖለቲካ ምህዳር ሲቀላቀል ሚዛናዊነት፣ ምክንያታዊነት፣ አብሮ ማሸነፍ፣ ከሴራና ከጥሎ ማለፍ ፖለቲካ መራቅ የትግላችን አልፋና ኦሜጋ እንዲሆኑ፣ ግልጽ ዓላማዎችና ስልቶች ነድፈን ነበር፡፡
“በጉዟችን መነሻ ላይ የቀን ጉርስ፣ የአመት ልብስ እንደ ሰማይ የራቃቸውን የድሀ ድሀ ዜጎቻችንን ቢያንስ ምግብ፣ ልብስ፣ መጠለያ፣ ትምህርትና ጤና የመሰሉ ለአንድ ሰብአዊ ፍጡር የሚገቡ መሰረታዊ ፍላጎቶችን ለሁሉም ዜጎቻችን እንዲሟሉ የበኩላችንን ለማበርከት በከፍተኛ ቁጭትና ህዝብን የማገልገል ፍላጎት ነበር፡፡” የሚለው ፓርቲው፤ ሁሉም ነገር በምኞት የቀረበት ይመስላል፡፡
አመርቂና ተስፋ ሰጪ ውጤቶች
ነእፓ በመግለጫው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት አስቸጋሪ በሆኑ ውስጣዊና ውጫዊ ተግዳሮቶችና የፖለቲካ ምህዳር ውስጥም ሆኖ በርካታ ተግባራትን ማከናወን እንደቻለ፣ አመርቂና ተስፋ ሰጪ ውጤቶችንም ማስመዝገቡን ጠቁሟል። ፓርቲው፤ ፈጸምኳቸው ከሚላቸው ስራዎቹና ስኬቶቹ ጥቂቶቹን ለአብነት ይጠቅሳል፡፡
“ከጅምሩ “ፓርቲ እጩ መንግስት ነው” የሚል ጠንካራ እምነት አንግበን፣ መንግስት ለመሆን ከሚያስፈልጉን ጉዳዮች መካከል በርካታ የፖሊሲ ሰነዶችን አዘጋጅተናል፡፡ ባለፉት አምስት አመታት ወሳኝ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጥናት ላይ የተመሰረቱ አማራጭ ሀሳቦችን አመንጭተናል፡፡ ለሀገርና ለህዝብ አይጠቅሙም ያልናቸውን የመንግስት ፖሊሲዎችና አሰራሮች እንዲወገዱ ሞግተናል፣
“ባለፉት አምስት ዓመታት የነእፖ የትግል ስልቶች ማለትም ሚዛናዊነት፣ ምክንያታዊነትና አብሮ ማሸነፍ በሀገራችን ፖለቲካ ውስጥ እንዲሰርጹ ጥረት አድርገናል፡፡ በእኒህ ዓመታት ሚዛናዊነትንና ምክንያታዊነትን መርህ አድርገን ባሰናዳናቸው ፖሊሲዎችና ፕሮግራሞች፣ ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ ባወጣናቸው የአቋም መግለጫዎች፣ ባዘጋጀናቸው ሁነቶችና የውይይት መድረኮች የተካረረው የሀገራችን ፖለቲካ እንዲለዝብ፣ ዋልታ ረገጥ የፖለቲካ ባህላችን ወደ መሀል እንዲመጣ አዎንታዊ ሚና ተጫውተናል፡፡
“የብሄራዊ መግባባት አጀንዳ ከቃል አልፎ ወደ ተግባር እንዲሸጋገር በጉልህ የሚታይ እንቅስቃሴ አድርገናል፡፡ እጅግ ግዙፍ የሆነው የአገራዊ ምክክር አጀንዳ በመንግስት ተወስዶ መተግበር ከጀመረበት ወቅት ጀምሮ፣ ሂደቱ እንዳይበላሽ፣ እንዳይጠለፍና የመንግስትና የገዢው ፓርቲ የፖለቲካ አጀንዳ ማስፈጸሚያ እንዳይሆን ታሪካዊ ኃላፊነታችንን ለመወጣት ጥረት አድርገናል፣ “የሰሜኑ የሀገራችን የእርስ በርስ ጦርነት በሰላማዊ መንገድ ይፈታ ዘንድ የጦርነትን አስከፊነትና የሰላምና ጥቅም አጉልተን ስለ ሰላም ሰብከናል፡፡ የጦርነት ጥሩ፣ የሰላም መጥፎ የለውም ብለን ከሰላም ጎን ቆመናል፡፡ ጦርነት ይቁም ማለት ዋጋ በሚያስከፍልበት፣ ስለ ሰላም መናገር ነውር በሆነበት በዚያ አስጨናቂ ወቅት ሰላምን ሰብከናል፣
 “ገዢው ፓርቲና መንግስት ስህተት ሰርተዋል ብለን ስናምን ድምጻችንን ከፍ አድርገን ተቃውመናል፡፡ ጠንካራና በመርህ የሚመራ ተቃዋሚ ለመሆን ለሀገርና ለህዝብ የገባነውን ቃል ተግባራዊ ለማድረግ ታትረናል፡፡ የተፎካካሪ ፓርቲ ኃላፊነታችንን ከጭፍን ተቃዋሚነትና “ስህተት ፈላጊነት” እንዲሁም መርህ አልባ የገዥ ፓርቲ ደጋፊነት ነጻ ሆነን ለሀገርና ለህዝብ ጥቅም የቆመ እውነተኛና ጠንካራ ተፎካካሪ ለመሆን አቅማችን የፈቀደውን ሁሉ አድርገናል፣
“የህግ የበላይነት እንዲረጋገጥ፣ ፓርቲና መንግስት እንዲለያዩ አጥብቀን ሞግተናል፣ የሀገራችን እድገት ነቀርሳ የሆነው ሙስና እና ብልሹ አሰራሮች እንዲቆሙ፣ የመንግስት ሹማምንት በስልጣናቸው ሲባልጉ ሽንጣችንን ገትረን ሞግተናል፡፡ በሀገር ሰላምና በዜጎች ደህንነት ላይ በደረሱ ጥቃቶች የህዝብ ድምጽ ሆነን ድምጻችንን አሰምተናል፣
 “መንግስት ጠንካራ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እንዲፈጠሩ ምቹ የህግ ማእቀፍና በቂ ድጋፍ ሊደረግ ይገባል፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን ለረዥም ዘመናት በገነገነው ኢ-ዴሞክራሲያዊ ስርአት፣ ዛሬም ጠንካራ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እንዳይፈጠሩ እንቅፋቶችን እየፈጠረ ይገኛል፡፡ በሀገራችን ማየት የምንፈልገው ጠንካራ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ይወለድ ዘንድ በተፎካካሪ ፓርቲዎች ላይ የሚደረጉ ልዩ ልዩ ጫናዎች እንዲቆሙና  ምቹ ምህዳር ለመፍጠር የፌደራልም ሆነ የክልል መንግስታት የበኩላቸውን እንዲያደርጉ አጥብቀን እናሳስባለን፣
“የልማት የመጨረሻ ግብ የዜጎችን ህይወት ምቹና ደስተኛ ማድረግ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የፌዴራልም ሆነ የክልል መንግስታት በልማት ስም የሚያካሂዷቸው ፕሮጀክቶች የዜጎችን ህይወትና ደህንነት ታሳቢ ያደረጉ፣ በቂ ጥናት የተደረገባቸው፣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቂ ውይይትና መግባባት የተደረሰባቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡ ይሁን እንጂ ባለፉት አመታት መንግስት በልማት ስም የሚያካሂዳቸው ፕሮጀክቶች፣ ዜጎችን ለከፍተኛ እንግልትና ስቃይ ሲዳርጉ ተስተውሏል፡፡ በመሆኑም መንግስት የሚፈጽማቸውን ፕሮጀክቶች በግልጽነትና ኃላፊነት ስሜት እንዲያካሂድ፣ በዜጎች ላይ ሊደርስ የሚችል ማበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት ለማስወገድ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ እናሳስባለን፣
ሀገራችን ካለችበት የግጭትና የጦርነተ አዙሪት ትላቀቅ ዘንድ ብሄራዊ መግባባት ብቸኛውና ምትክ የሌለው መፍትሄ እንደሆነ መላው የሀገራችን ህዝቦችና የፖለቲካ ኃይሎች ያምናሉ፡፡ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ ሀገራዊ መግባባት እውን ይሆን ዘንድ ከፓርቲው ምስረታ ጀምሮ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ብዙዎች በጉጉት የሚጠብቁትን ሀገራዊ ምክክር ተግባራዊ ለማድረግ መንግስት የአገራዊ ኮሚሽን ማቋቋሙና ይኸው ኮሚሽን ላለፉት ሁለት ዓመታት ዝግጅት በማድረግ ላይ መሆኑን በተደጋጋሚ ሲገልጽ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ በአንጻሩ የሀገራዊ ምክክር ሂደት ከጽንሱ ጀምሮ የግልጽነትና የአሳታፊነት ችግር አለበት በሚል በርካታ የፖለቲካ ኃይሎች ከሂደቱ ራሳቸውን አግልለዋል፡፡ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ ሀገራዊ ምክክር መሰረቱና የመጨረሻ ግቡ በቁልፍ የፖለቲካ ተዋናዩች መካከል መተማመንን መፍጠር ነው ብሎ የሚያምን ሲሆን፣ መተማመን የሌለበት ሀገራዊ ምክክር ውጤቱ ጊዜና ገንዘብ ከማባከን ያለፈ እንደማይሆን ይገነዘባል፡፡ በመሆኑም የሀገራዊ ምክክር ይሳካ ዘንድ መንግስትና የምክር ኮሚሽኑ ሂደቱን ግልጽ፣ አሳታፊና ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ እንዲመሩት እያሳሰብን፣ በተመሳሳይ የፖለቲካ ኃይሎችና ሌሎች የሚመለከታቸው አካት ሀገራችን ካለችበት ውስብስብ ችግር ትወጣ ዘንድ ብቸኛው አማራጭ “ምክክር” መሆኑን በመረዳት፣ ለሂደቱ መሳካት የቡኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪያችንን እናቀርባለን፣
“ከዛሬ ስድስት አመት በፊት የተጀመረው የፖለቲካ ሪፎርም፣ ኢትዮጵያውያን ተስፋ ያደረጓቸውና ለረዥም ጊዜ ሲመኟቸው የኖሩ ነጻነት፣ እኩልነት፣ ማበራዊ ፍትህ፣ ሰብአዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች መከበር፣ ፍትሀዊ የልማት ተጠቃሚነትና ሌሎች ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ተገቢ መልስ ያገኙ ዘንድ ገዢው ፓርቲና መንግስት ታሪካዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጥሪ እናቀርባለን፣
በአሁኑ ወቅት በሀገራችን ከሚስተዋሉ ችግሮች መካከል አንዱ በአጎራባች ክልሎች መካከል የሚፈጠሩ የወሰንና የማንነት ግጭቶች ይገኙበታል፡፡ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ለሁለት አመት የተካሄው ጦርነት በፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት እልባት ቢያገንም፣ በአማራና በትግራይ ክልሎች አዋሳኝ ቦታዎች አሁንም ውጥረት እንደነገሰባቸው ናቸው፡፡
 በአፋርና በሱማሌ ክልሎች አጎራባች ወረዳዎች በሚፈጠር ግጭት የበርካታ ወገኖቻችን ደም እየፈሰሰ ይገኛል፡፡ በተመሳሳይ በሌሎች ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች በወሰንና በማንነት ጉዳዮች በሚፈጠር ጉዳት ከፍተኛ ሰብአዊና ቁሳዊ ጉዳት እየደረሰ ይገኛል፡፡ የወሰንና የማንነት ጉዮችን ለመፍታት ከአመታት በፊት ተቋቁሞ የነበረውና ሰፊ ተስፋ ተጥሎበት የነበረው “የአስተዳደር ወሰንና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን” የሚጨበጥ ስራ ሳይሰራ በመፍረሱ ችግፎቹ ዛሬም ቀጥለዋል፡፡ በመሆኑም የፌዴራል መንግስትና የክልል መስተዳድር አካላት፣ በወሰን ምክንያት በክልሎች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶችና በዚህ ምክንያት የሚፈሰውን የዜጎች ደምና የሚወድመውን የሀገር ሀብት ለመታደግ አስፈላጊውን እንዲያደርጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን፣
 “ሀገራችን ለገባችበት ሁለንተናዊ ቀውስ ዋነኛ ምክንያት የሆነው የእርስ በእርስ ጦርነት በአፋጣኝ ይቆም ዘንድ መንግስትም ሆነ ነፍጥ አንግበው የሚታገሉ ኃይሎች ለሰላም ቅድሚ እንዲሰጡ እያሳሰብን፣ ሀገራችን ካለችበት የቀውስ አዙሪት በአጭር ጊዜ ተላቃ ሰላም፣ ነጻነት፣ እኩልነት፣ ፍትህ የሰፈነባት፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት የተረጋገጠባት ሀገር ትሆን ዘንድ መላው የሃገራችን ህዝቦችና ሌሎች የሚመለከታቸውን አካላት የበኩላቸውን እንዲወጡ በድጋሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡”
እንግዲህ የ5 ዓመት ለጋ ዕድሜ ብቻ ያለው ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት ሃገሪቱ የወጣችውን የወረደችውን፣ ህዝቧ የገጠመውን ያሳለፈውን -- መከራና ውጣ ውረድ፤ ግጭትና ጦርነት፤ ሞትና ሰቆቃ፣ ድህነትና እጦት ከሞላ ጎደል በመግለጫው አካቶታል፡፡ ራሱ ፓርቲው ያበረከተው አስተዋጽኦና አሉታዊ ተጽዕኖ ምን እንደሆነ ለማወቅ ግን መጠነኛ ጥናትና ፍተሻ ይፈልጋል፡፡ ወደፊት እንመለስበት ይሆናል፡፡



በተባበሩት መንግስታት፣ የሕጻናት አድን ድርጅት (ዩኒሴፍ)፤ በኢትዮጵያ 8.8 ሚሊዮን ሕጻናት ከትምሕርት ገበታ ውጭ ሆናቸውን አስታውቋል። ድርጅቱ ባለፈው ሰኞ ባወጣው የሩብ ዓመት ሪፖርት እንዳመለከተው፣ ከትምሕርት ገበታ ውጭ የሆኑ ሕጻናት ቁጥር በእጅጉ ጨምሯል።
በዩኒሴፍ የሩብ ዓመት ሪፖርት መሰረት፤ወደ 3 ሚሊዮን ለሚጠጉ ሕጻናት የትምህርት ድጋፍ ለማድረግ ጥረት ቢደረግም፣ ካለፈው ዓመት አጋማሽ አንስቶ ከትምህርት ውጭ የሆኑ ሕጻናት ቁጥር በከፍተኛ መጠን መደጉ ተመልክቷል፡፡
ባለፈው መጋቢት ወር ፣ 156 ሺ ያህል ሕጻናት ብቻ የድንገተኛ የትምህርት ድጋፍ እንዳገኙ የሚያትተው ሪፖርቱ፤ ለ ግሩመንስኤ ናቸው ያላቸውን ክስተቶች ዘርዝሯል። በስድስት ክልሎች የበልግ ወቅት ዝናብን ተከትሎ፣ በኢትዮጵያ 8.8 ሚ. ህጻናት ከትምህርት ገበታ ውጭ መሆናቸው ተገለጸ የተከሰቱ የጎርፍና በሰባት ክልሎች ያጋጠሙ የድርቅ አደጋዎች ለችግሩ መንስዔ እንደሆኑ
ተጠቁሟል፡፡ በፈረንጆቹ 2024 ዓ.ም የመጀመሪያ ሦስት ወራት ውስጥ የትምህርት መሰረተ ልማቶች ውድመት የ4 . 5 በመቶ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የተዘጉ ት/ ቤቶች ብዛት በ18 በመቶ ማደጉን ሪፖርቱ ይጠቁማል፡፡በዚህ ሩብ ዓመት 21 ግብረ ሰናይ ድርጅቶች በቀውስ ለተጠቁ አካባቢዎች ድንገተኛ የትምህርት ድጋፍ ቢያደርጉም፣ ተጨማሪ
የድጋፍ ዓይነቶችና የሰብዓዊ ዕርዳታ እቅርቦት ከሌለ፣ አስከፊ ሁኔታ እየተፈጠረ ችግሩን ሊያሰፋው እንደሚችል ዩኒሴፍ ስጋቱን ገልጿል።
በኢትዮጵያ 10 ሚሊዮን ያህል ሕጻናት የትምህ ርት ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸውየዩኒሴፍ መረጃ ያሳያል።

በቀጣዮቹ 10 ቀናት ከባድ ዝናብ እንደሚጠበቅ ተጠቁሟል


ከመጪው ሰኔ  ወር እስከ መስከረም በሚዘልቀው የክረምት ወቅት መጠኑ ከፍ ያለ ዝናብ ስለሚኖርና አደገኛ ሁኔታ ሊፈጠር ስለሚችል ጥንቃቄ እንዲደረግ የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) አሳስቧል።  የኢትዮጵያ ሜትሮሎጂ ኢንስቲትዩት በበኩሉ፤ በቀጣዮቹ 10 ቀናት ከባድ ዝናብ እንደሚጠበቅ አስታውቋል፡፡
በአየር ንብረት ለውጥ ቀውስ በተደጋጋሚ በሚመታው የምስራቅ አፍሪካ ቀጠና፣ በመጪዎቹ ወራት ከመደበኛው መጠን ከፍ ያለ ዝናብ ሊጥል እንደሚችል የገለጸው የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ)፤ ማዕከላዊና ሰሜን ኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ፣ ኤርትራ፣ አብዛኛው ኡጋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ በሱዳንና በኬንያ ጠረፎች ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚጠበቅ በሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ በአንጻሩ ምዕራብ ኢትዮጵያና ሰሜን ምስራቅ ደቡብ ሱዳን ከመደበኛው ከፍ ያለ ደረቅ የአየር ንብረትን የሚያስተናግድ መሆኑን ገልጿል። ክረምቱ ኢትዮጵያና ኤርትራን በመሳሰሉ ሀገራት ቀደም ብሎ መታየት ሲጀምር፣ በጅቡቲ እንዲሁም በሱዳንና በደቡብ ሱዳን ዘግየት ብሎ እንደሚጀምር ኢጋድ በሪፖርቱ ላይ ጠቅሷል።
የኢትዮጵያ ሜትሮሎጂ ኢንስቲትዩት በበኩሉ ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው መረጃ፤  በቀጣዮቹ አሥር ቀናት ሰፊ ቦታዎችን ያካተተና የተጠናከረ ዝናብ እንደሚኖር አመላክቷል። በዚህም በአጠቃላይ በሚቀጥሉት ቀናት ከኦሮሚያ ክልል ምስራቅና ምዕራብ ወለጋ፣ ቄለም ወለጋ፣ ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ፣ ቡኖ በደሌ፣ ጅማ፣ ኢሉባቦር፣ ቦረና እና ምስራቅ ቦረና፤ ጉጂ እና ምዕራብ ጉጂ፣ ባሌ ከመደበኛው ከፍለ ያለ ዝናብ እንደሚጠበቅ አስታውቋል።  በተመሳሳይ  በአማራ ክልል ሰሜን፣ ማዕከላዊ፣ ደቡብና ምዕራብ ጎንደር፣ ምስራቅና ምዕራብ ጎጃም እንዲሁም አዊ ዞኖችን ጨምሮ በሌሎች አካባቢዎች ላይ ከፍ ያለ የዝናብ ስርጭት እንደሚኖር በሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡

አንዳንድ እውነተኛ ታሪክ እንደተረት ይነገራል። የሚከተለውን ዓይነት ነው።
ናፖሊዮን ከስፓኒሽ ጦርነት ሲመለስ (1809) በጣም ተበሳጭቶና እየተቅበጠበጠ ነበር ይባላል። የቅርብ ሰዎቹና አፍ- ጠባቂዎቹ፣ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩና የፖሊስ አዛዡ ሲያሴሩበት እንደነበር ሹክ ይሉታል። ገና ወደ መዲናይቱ እንደገባ ወደ ቤተ-መንግሥቱ በማምራት፣  የሚኒስትሮቹንና የበላይ ባለሥልጣናቱን ስብሰባ ጠራ። ገና እየገቡ ሳሉ ከተሰብሳቢዎቹ ኋላ ኋላ እየተከተለ ወዲህ ወዲያ እንደ ግሥላ መንቆራጠጡን ቀጠለ። ከዚያም ሴረኞች እሱን በመቃወም እንደሚያደቡ፣ አሻጥረኞች የገበያ ዋጋ እንደሚሸቅቡ፣ ህግ አርቃቂዎች ፖሊሲውን እንደሚያዘገዩና፣ የገዛ ሚኒስትሮቹ እሱን ዝቅ አድርገው መመልከት እንደጀመሩ ያልተያያዘ ዓረፍተ ነገር በሚመስል ማጉተምተም ተናገረ።
የውጪ ጉዳዩ ሚኒስትሩ ታስራንድ ጠረጴዛው ላይ ዘመም ብሎ ተቀምጧል። አይሞቀው አይበርደው ዓይነት።
ናፖሊዮን ወደ ታስራንድ እያየ፡- “ሚኒስትሮች ራሳቸውን ለጥርጣሬ ዕድል ከሰጡት፤ ክህደት ጀምረዋል ማለት ነው” አለ።
“ክህደት” የሚለውን ቃል ሲጠራ አፍጦ ወደ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ እያየ ነው። ይደነግጣል ወይም ይፈራል ብሎ ጠብቋል። ሚኒስትሩ ግን ፈገግ ብቻ ነው ያለው። ፀጥና ስልችት ያለ መልክ ነው የሚታይበት። ይሄ ናፖሊዮንን ቅጥል አደረገው።
በመጨረሻ ናፖሊዮን ፈነዳ። ወደ ታስራንድ ቀርቦ  ፊቱ ላይ አፍጦ፤
“አንተ ፈሪ ነህ። ምንም ዕምነት የሌለህ። ለአንተ ምንም የተባረከ ነገር የለም። የገዛ አባትህን ከመሸጥ የማትመለስና አሳልፈህ የምትሰጥ ነህ። በሀብትና በንብረት አንቆጠቆጥኩህ፤ ግን መልሰህ እኔን ከመጉዳት በስተቀር ምንም የምትሰራው ነገር የለህም። የበላህበትን ወጪት ሰባሪ ነህ።”
ሌሎቹ ሹማምንት ዐይናቸውንም፣ ጆሯቸውንም ማመን አቃታቸው። ድፍን አውሮፓን ያንቀጠቀጠው ዕውቁ ጄኔራል እንዲህ ሆኖ አይተውት አያውቁም።
ናፖሊዮን ቀጠለ፣
“አንተን እንደ መስታወት አንክትክት ማድረግ ነው። ያንን ለማድረግ ደግሞ እኔ ፍፁም ሥልጣን አለኝ። ግን ላንተ በጣም ጥላቻው ስላለኝ ልጨነቅብህ አልፈልግም። ለምን ገና  ዱሮ እንድትለቅ እንዳላደረግሁ አይገባኝም። ግን ግዴለም ጊዜ አለኝ!” አለ። ትንፋሹን ጨርሶ ንግግሩ ቁርጥ ቁርጥ እያለ፣ ፊቱ ቲማቲም  መስሎ፣ ዓይኑ ካፎቴ ወጥቶ እየተጉረጠረጠ፤ “አንተ ትቢያ ነህ። የሀገር ውስጥ ትል።… ሚስትህስ ብትሆን? ሳን ካርሎስ ውሽማዋ መሆኑን መች ነግረኸኝ ታውቃለህ?” አለ።
ታሴራንድም፡
“እንደሚመስለኝ ጌታዬ፣ ይሄ መረጃ በክቡርነትዎም  ሆነ በእኔ ክብር ላይም ለውጥ ያመጣል ብዬ ስላላመንኩኝ ነው” አለ እርግት እንዳለና፣ ካለበት ንቅንቅም ሳይል።
ናፖሊዮን ጥቂት ተሳድቦ ወጥቶ ሄደ።
ታሴራንድ ተነስቶ እንደተለመደው ቅስስ ባለ አረማመዱ ክፍሎቹን እያቋረጠ፤ ከእንግዲህ ዐይኑን አናየውም በሚል የመሸማቀቅ  ቆፈን ውስጥ ወዳሉት ሚኒስትሮች ዘወር ብሎ፡-
“ጎበዝ፤ እንዲህ ያለ ታላቅ ሰው፤ እንዲህ ያለ ከንቱ ፀባይ ይዞ ሲገኝ አያሳዝንም?!” አለ። ናፖሊዮን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩን አላሰረውም። ከሥልጣኑ ግን አነሳው። ውሎ አድሮም አባረረው። ህዝቡ ግን ታላቅ ንጉስ የነበረ መሪውን፣ ከርሞ፣ ከርሞ ትንሽ-ትልቁ ነገር ሲያበሳጨው ለመጀመሪያ ጊዜ አስተዋለ።
ይህን ሁሉ ረጋ ብሎ የታዘበው የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ታሴራንድ፣ ቆይቶ አንድ ታሪካዊ ንግግር ተናገረ፡-
“ይሄ የፍፃሜው መጀመሪያ ነው” አለ።
***
በማንኛውም ደረጃ ያለ መሪ ትዕግሥት ከሌለው፣ ለበታቾቹ  ንቀት  ካደረበትና ራሱን መቆጣጠር ካቃተው፤ ክብሩንና ቦታውን የሚጠብቅ በሳል ቀላል ሰው በቀላሉ ያሸንፈዋል።
“የፍፃሜው መጀመሪያ” መሆኑን ይነግረዋል። ውጥረት በበዛና ችግሮች በተወሳሰቡ ሰዓት ስሜታዊነት ፖለቲካዊና ማህበራዊ ሂደት ውስጥ አያሌ ችግሮች ተደቅነው ጉዳዩ የሚመለከታቸው መሪዎች እያስጨነቋቸው መሆኑ ይታያል። ስሜታዊነት የሚያጠቃቸው  መሪዎች ረጋ-ባሉ መሪዎች መተካት ይኖርባቸዋል።
የጋሉትን ለማብረድ፣ የበረዱትን አሰልጥኖና ገርቶ እንዲተኩ ማድረግ ብልህነትና በሳልነት ነው። ነጋ ጠባ እየተካረሩና እየተወሻሹ የትም አይደረስም። በአንፃሩ ዐይን ያወጣ ሸፍጥና የፊት ለፊት አሻጥርን ምን ግዴ ብሎ  እጅን አጣጥፎ መቀመጥም አያዋጣም። “ብትርህን የምታውሰው መልሰህ  መውሰድ ለምትችለው ሰው ብቻ ነው” የሚባለውን የሶማሌ ተረት በቅጡ ማጤን ይጠበቅብናል። በክንድ ርቀት ሆኖ መታየት ያለባቸውንና ተጨባብጦ መተማመን የሚገባቸውን ጉዳዮች በንቁ ዐይን ማየት ያስፈልጋል። በየትኛውም የፖለቲካ መስክ ትግልን ለዕድል መተው የማያዋጣበት ጊዜ አለ። “ጎረቤቶችህ በጀርባህ ላይ ጥጃ ሲያሸክሙህ እሺ ብትል፤ ላሚቱንም ጨምረው ይጭኑብሃል” ይሏልና ቆራጥነትን ከብልህነት፤ አስተውሎትን ከስሜታዊነትና ከቁጡነት፤ በአጭር ጊዜ በራሱ ሂደት የሚሟሽሸውን፤ ከረዥምና በታቀደ፣ ያለመታከት ጉዞ፤ ለፍሬ የሚበቃውን መለየት፣ አስፈላጊ ሲሆን፤ አዋህዶ የመራመድን ዝግጅት ማሟላትም ተገቢ የሚሆንበትን ወቅት ማወቅ ግድ ነው።
የፖለቲካ ሂደት እንደየወቅቱ ተለዋዋጭ ቢሆንም በተለይ የሀገራችን ፖለቲካ እንደ ኳስ ጨዋታ፣ ኳስ ባለችበት አካባቢ ብቻ በማተኮር የምንጓዝበት አይደለም። እንደዚያ ካደረግን ኪሳራ ይበዛል። የጨዋታው ቦታ አራምባ ሲመስለን ቆቦ፣ የካ ሲመስለን መካ የሚሆንበት ጊዜ ብዙ ስለሆነ መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ሁለት ጎል ብቻ ያለው አይደለምና።
ነጋ ጠባ የሚባባስ ሁኔታ፣ ነጋ ጠባ የማንማርበት የፖለቲካ ጨዋታ፣ ነጋ ጠባ ውሃ ቅዳ ውሃ መልስ የምንልበት መዳከር ለሀገርና ለህዝብ አይበጅም። አጥብቀን የምንይዘውን እንወቅ። ስለጋራ አገር እናስብ። እኔ ባቀናሁበት አገር ማንም አይኖርበትም የሚል ራስ-ወዳድነት የማይገዛ እንደሆነ ሁሉ፣ ሌላ ያቀናው  ላይ መኖር አልፈልግም ማለትም የአፍራሽ እልህ ነው። በዚህ ሁሉ የፖለቲካ ሂደት ማህል ከዛሬ ነገ የተሻለ ውጤትና የተሻለ እርምጃ፣ የተሻለም ተስፋ ሲጠብቅ፣ ከቅራኔ ክረትና ከመበቃቀል ህልም እንዲሁም ከአለመተማመን አረንቋ፣ የማንወጣ ከሆነ፡ “ደረቁ ከበደኝ እያልኩ እርጥብ ያሸክመኛል” ይለናልና፤ ለዘለቄታው ህዝብን ላለማጣት ቆም ብሎ ማስተዋል ይሻላል።

 “ሜላድ የብራና ማዕድ” የተሰኘ የጥንታዊ ብራናዎችና ተያያዥ ቁሳቁሶች አውደ ርዕይ በመጪው ሰኔ ወር ይከፈታል፡፡ “ኑ ድንቅ ነገር እዩ” በሚል መሪ ቃል የተሰናዳው በአይነቱ ልዩ ነው የተባለው የብራና አውደ ርዕይ ሰኔ 8 እና 9 ቀን 2016 ዓ.ም በቦሌ ደብረሳሌም መድሃኔአለም ካቴድራል እንደሚካሄድ “ሜላድ ጥንታዊ የብራና ፅሁፍ መፃፊያ የስዕል መሳያና ማሰልጠኛ ማእከል ሰሞኑን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል፡፡
አውደርዕዩ ብፁአን አባቶች፣ ጳጳሳት፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ ምዕመናንና የመንግስት የስራ ሀላፊዎች በሚገኙበት እንደሚከፈት የተነገረ ሲሆን መግቢያ በነፃ ነው፡፡ በጋዜጣዊ መግጫው ላይ ብፁእ አቡነ መቃሪዮስ  የሱማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶስ አባልን ጨምሮ በርካታ መምህራንና አባቶች የተገኙ ሲሆን ሜላድ ጥንታዊ የብራና መፅሀፍት ዝግጅት ማዕከል በደብረ ሊባኖስ የሃይማኖት የቅርስ የታሪክና የስርዓተ ቤተ-ክርስቲያን ተቆርቋሪ በሆኑት በቆሞስ አባ ኪዳነማሪያም አበበና የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው አማካኝነት መቋቋሙ ተነግሯል፡፡ “ሜላድ” ማለት አለደ፣ አከማቸ፣ ሰበሰበ ከሚለው የግዕዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ስሙ የማዕከሉን ተግባርና ርዕይ በአግባቡ የሚገልፅ ነው ተብሏል፡፡ ማዕከሉ የብራና ቆዳዎች ዝግጅትን ጨምሮ የብራና ፅሁፍና እርማት፤ ድጉሰት የቅዱሳን ስዕላት አሳሳልና የሀረግ አሰራር ሙያዎችን በአንድ ማዕከል ስር በማደራጀት ታሪክን ለትውልድ ለማስተላለፍ እየተጋ የሚገኝ ተቋም መሆኑም ተገልጷል፡፡

አዲስ አበባ “ሕፃናትን ለማሳደግ ተመራጭ አፍሪካዊት ከተማ” ለማድረግ የተከናወኑ ሥራዎች ፍሬ አፍርተዋል፤ ከተማችን አፍሪካዊ እህቶቿንና ወንድሞቿን ተቀብላ ልምድ የምታጋራ ሆናለች። በዓለም አደባባይም በተምሳሌት እየተነሣች ነው ብለዋል የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አበቤ።
ለዚህም ነው፣ ከሰሞኑ በርካታ ከንቲባዎችና የሚኒስቴር ኀላፊዎች ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ወደ አዲስ አበባ ያቀኑት  - ከደቡብ አፍሪካና ከሴራሊዮን፣ ከኬንያና ታንዛንያ ከመሳሰሉ ሀገራት።
ከንቲባ አዳነች በሀገራዊ ዜማዎችና ጭፈራዎች ታጅበው እንግዶቹን ከተቀበሉ በኋላ፣ ዐጠር ያለ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ሕፃናትን ለማሳደግ ተመራጭ የአፍሪካ ከተማ የሚል ራዕይ ይዘን ነው ሥራ የጀመርነው። የአፍሪካ ጎብኚዎች ይህን ሲሰሙ፣ “ይሄማ የኛም ምኞት ነው። ይሄንማ እኛም እናውቃለን” የሚል ስሜት ቢፈጠርባቸው አይገርምም። የልጆች አስተዳደግን ለማሻሻል መጣር እንደሚያስፈልግና መጪውን ዘመን የሚቀይር ኢንቨስትመንት  እንደሆነ እናውቃለን ብለዋል የሉሳካ ከንቲባ።
ራዕይን በጥቂት ቃላት እቅጩን መግለጽ መልካም ቢሆንም፣ ምኞትን ወደ ዝርዝር ዕቅድ መመንዘርና ሠርቶ ማሳየት ግን… ብዙ ጊዜ አይሳካም።
ከንቲባ አዳነች ዋና ዋና ዕቅዶችንም ባጭር ባጭሩ አንድ ሁለት ብለው ለመጥቀስ ሞክረዋል። ለነገሩማ የጉብኝቱ ዋና ቁም ነገር፣ “ገለጻ የማቅረብ” ጉዳይ አይደለም። የጎብኚዎቹም ፍላጎት ንግግር ሰምተው ለመረዳት ሳይሆን በየቦታው በአካል ተገኝተው በዐይናቸው ለማየት እንደሆነ መገመት አይከብድም። ለዚህም ይሆናል ከንቲባ አዳነች ገለጻውን ዐጠር አድርገው ያቀረቡት።
የሆነ ሆኖ አዲስ አበባ ለሕጻናት ዕድገት እንዲሁም ለወላጆች አመቺ እንድትሆን በሁሉም መስክ መከናወን ከሚገባቸው ሥራዎች መካከል ዋና ዋናዎቹን ጠቅሰዋል።
በሦስት ዓመት ውስጥ 1000 የሕፃናት ማቆያ ቦታዎችን ማዘጋጀት
ሕጻናት በአቅራቢያቸው የመጫወቻ ቦታ እንዲኖራቸው፣ ንጽህናቸው የተጠበቀና አስፈላጊ ቁሳቁስ የተሟላላቸው 12 ሺ የመጫወቻ ስፍራዎችን ማዘጋጀት
ከ1000 በላይ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ለሕጻናት አመቺና ማራኪ በሆነ መንገድ በአዲስ መልክ ማሰናዳት
97 የጤና ተቋማትም ሕጻናትን ተቀብለው የተሟላ አገልግሎት እንዲሰጡ፣ ለልጆች መስተንግዶ ተስማሚና ማራኪ ቦታ እንዲያዘጋጁ፣ የመጫወቻ ቁሳቁሶች እንዲኖሯቸው ማድረግ
ቤት ለቤት ለወላጆችና ለአሳዳጊዎች የምክር አገልግሎት የሚሰጡ 5000 ሙያተኞችን አሰልጥኖ ማሰማራት
በሦስት ዓመት ውስጥ ይከናወናሉ የተባሉ ዕቅዶችን ከንቲባዋ አንድ ሁለት ብለው ሲጠቅሱ፣ በአድማጮች ዘንድ በርካታ ጥያቄዎችና የጥርጣሬ ስሜቶች እንደሚፈጠሩ ልትገምቱ ትችላላችሁ። አልተሳሳታችሁም።
ከታንዛንያ የመጡት የትምህርት፣ የቴክኒክና ሙያ ሚኒስትር ለይላ መሀመድ ሙሳ እንዲህ ይላሉ። በመጀመሪያው ዕለት ከንቲባዋ ራዕያቸውንና ዕቅዳቸውን ሲገልጹላቸው ለማመን ተቸግረዋል። “ይሄ ሁሉ እንዴት ተግባራዊ ሊሆን ይችላል?” የሚል ጥርጣሬ ነበር የተፈጠረብኝ ብለዋል - ለይላ።
ከተማዋን ዞረው ካዩ በኋላ ደግሞ የታዘቡትን ይነግሩናል።
ከንቲባዋንና መንግሥትን ላሞግሳቸው እወዳለሁ በማለት ለይላ አስተያየታቸውን ሲሰጡ፣ የሕጻናት አስተዳደግን ለማሻሻል ከንቲባዋ ያከናወኑት ሥራ የሚጨበጥ የሚዳሰስ ሥራ ነው ብለዋል።
“ከንቲባዋ የራዕይና የዕቅድ ብቻ ሳይሆን የተግባርም ሰው ናቸው። ራዕይ ከመያዝ ወይም ዕቅድ ከማውጣት ባሻገር ሥራውንም በአካል እየሄዱ ይከታተላሉ። በሄዱበት ሁሉ ሕጻናት ከንቲባዋን በደስታ ሲቀበሉና እየሮጡ ሲያቅፉ አይቻለሁ። ከንቲባዋ ለሥራው ምን ያህል ቅርብ እንደሆኑ ታዝቤያሁ” ብለዋል ለይላ።
ከንቲባ አዳነች ከሦስት ዓመት እቅድ ውስጥ በአንድ ዓመት ተኩል ውስጥ ምን ያህል እንደተሳካ ሲገልጹ፣ የከተማችን የሕጻናት ማቆያ ማዕከላት 597 ደርሰዋል። ጥቂት ነው የሚቀረን። አንድ ሺህ እናደርጋቸዋለን ብለዋል።
በወላጆች ጤንነትና በሕጻናት አስተዳደግ ዙሪያ ቤት ለቤት የምክር አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች እስካሁን ከ2000 በላይ ሰልጥነው ሥራ እንደጀመሩ ከንቲባዋ ገልጸዋል። ሰሞኑን ደግሞ 3000 ሙያተኞች ስልጠናቸውን አጠናቅቀው ተመርቀዋል።
ለወላጆችና ለአሳዳጊዎች የምክር አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች ሲመረቁም በአካል ተገኝተው እንዳዩ የተናገሩት የናይሮቢ የጤና ም/ሚኒስትር ሱዛን ሌንጌዋ፣ “ቤት ለቤት የምክር አገልግሎት የማድረስ አገልግሎት ለኛ አዲስ ነገር ነው፤ አዲስ ልምድ አግኝተንበታል” ብለዋል።
አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በአዲስ መልክ እንዲሻሻሉ፣ የጤና ተቋማትም ለሕጻናት አገልግሎት አመቺና ማራኪ እንዲሆኑ በርካታ ሥራዎች እንደተከናወኑ ማየታቸውንም ተናግረዋል።
የተቀናጀ አሠራራቸው የሚደነቅ ነው። የትምህርት፣ የጤና፣ የትራንስፖርትና ሌሎች ዘርፎች ሁሉ፣ በከተማው አስተዳደር ትኩረታቸውን በመሰብሰብ ተግባራቸውን በማናበብ  በመሥራት ውጤት አግኝተዋል ብለዋል - ሱዛን።


ቻርለት ኬሪች (ናይሮቢ፤ የፋይናስና ኢኮኖሚ ቢሮ ኀላፊ)
ዐይን ገላጭ ልምድ ነው ያገኘነው። ከተሞችንን ለሕጻናት አመቺ ለማድረግ፣ የግድ ሰፋፊ ቦታዎች ያስፈልጋሉ ማለት እንዳልሆነ አይቻለሁ።
የከንቲባዋ ራዕይ አዲስ እይታን የሚፈጥር ነው። በተወሰኑ ቦታዎች ትልልቅ የሕጻናት መጫወቻዎችን ከመገንባት ይልቅ በየአካባቢያቸው በቅርባቸው በሺ የሚቆጠሩ የመጫወቻ ስፍራዎችን ለማዘጋጀት ነው እየሠሩ ያሉት።
የሕጻንነት ዕድሜ ለአካላዊና ለአእምሯዊ ዕድገት ከፍተኛ ድርሻ አለው። ሦስት ዓመት እስኪሞላቸው ድረስ በየሰፈራቸው በየአቅራቢያቸው ከቤት ውጭ ምቹ የመጫወቻ ቦታ እንዲያገኙ ማድረግ በጣም ትልቅ ሥራ ነው። ትምህርት ቤት ሲገቡ ዕውቀት የመጨበጥ ዐቅማቸው ጥሩ ይሆናል። ዕድሜ ልክ የሚያገለግል ኢንቨስትመንት ነው ማለት ይቻላል።
እነዚህ ሕጻናት ሲያድጉ፣ በትክክል የተገነባ አዲስ ትውልድ ይኖራችኋል ብዬ እጠብቃለሁ።
ዪቮኔ ኢኪሳውዬር - የፍሪታውን ከንቲባ፡
የመዋዕለ ሕጻናት ትምህርት ቤቶችን አይተናል። ለትናንሽ ሕጻናት የተዘጋጁ የመጫወቻ ቦታዎችንም ጎብኝተናል። አንዲት እናት አግኝቼ እንደነገረችን፣ ቦታው አቧራማ ነበር። ሕጻናትን ለጤና ጠንቅ የሚያጋልጥ ነበር። አሁን ግን ንጹሕ ነው። በልምላሜ አረንጓዴ ለብሶ ደስ ይላል። የመጫወቻ ቁሳቁሶችም ተዘጋጅተውለታል። በዚህም የአካባቢው ሰው ደስተኛ ነው።
ከተሞችን ለሕጻናት አመቺና ተስማሚ ማድረግ እንደሚያስፈልግ እንገነዘባለን። የፕሮጀክት ሰነድ ማዘጋጀትም ጥሩ እንደሆነ እናውቃለን። ትልቁ ቁም ነገር ግን በተግባር መሥራት ነው። እኔን ያስደሰተኝና ያስደነቀኝ፣ ሐሳቦችና ሰነዶች በተግባር መሬት ላይ ተሠርተው ማየቴ ነው።
ቺላንዶ ናካሊማ ቺታንጋላ - የሉሳካ ከንቲባ፡
ለልጆች ዕድገት የምንሠራቸው ነገሮች መጪውን ዘመን የሚቀይሩ ኢንቨስትመንቶች እንደሆኑ ይታወቃል። እዚህ አዲስ አበባ በተግባር እየተሠራ ነው። እኛንም ለሥራ አነሣሥቶናል።
ለወላጆችና ለአሳዳጊዎች የምክር አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች ሥልጠናቸውን አጠናቅቀው ሲመረቁ አይተናል። ያልተለመደ ነገር ነው። ገርሞኛል። የከተማው አስተዳደር ለሕጻናት አስተዳደግ በሁሉም መስክ ብዙ ኢንቨስት እያደረገ እንደሆነ ተረድቻለሁ። የአፍሪካ የከተማ ከንቲባ እንደመሆኔ፣ ጥሩ የልምድ አጋጣሚ ሆኖልኛል። አፍሪካ በፍጥነት የምታድግ አህጉር ናት። በሕፃናት ላይ ኢንቨስት ማድረግ አለብን።
ሱዛን ሌንጌዋ - የናይሮቢ የጤና ም/ሚኒስትር፡
ሁሉንም ዘርፍ ያካተተ የመንግሥት አሠራር ይደነቃል። በትምህርት፣ በጤና፣ በትራንስፖርትና በሌሎችም ዘርፍ ሁሉ ትኩረታቸውን በመሰብሰብ ተግባራቸውን በማናበብ እንዲሠሩ የከተማው አስተዳደር  የተቀናጀ አሠራር አለው።
አዲስ አበባን ለልጆች አስተዳደግ ምቹ ለማድረግ ሁሉንም መስክ አቀናጅቶ መሥራት እንደሚያስፈል ብቻ ሳይሆን እንደሚቻልም ነው ያየሁት። ትምህርት ቤቶችን፣ የመጫወቻ ቦታዎችን፣ የሕጻናት ማቆያ ስፍራዎችን አይተናል። ለወላጆች የምክር አገልግሎት የሚሰጠሩ ከ3ሺ በላይ ባለሙያዎች ሰልጥነው ሲመረቁም በአካል ተገኝቼ ተመልክቻለሁ። ለኛ አዲስ ነገር ነው። አዲስ ልምድ እናገኝበታለን።
ለይላ መሀመድ ሙሳ (የትምህርት፣ የቴክኒክና ሙያ ሚኒስትር)፡
ከንቲባዋንና መንግሥትን ላሞግሳቸው እወዳለሁ። የሕጻናት አስተዳደግን ለማሻሻል ያከናወኑት ሥራ፣ የሚጨበጥ የሚዳሰስ ሥራ ነው። የሕጻናት ደህንነትን ለማረጋገጥ፣ በአግባቡ ትምህርት እንዲያገኙ፣ የጤና አገልግሎት እንዲሟላላቸው ለማድረግ ብዙ እንደተሠራ አይቻለሁ።
ዛሬ እጃችው ውስጥ ባለ አነስተኛ ዐቅም ተጠቅመን ውጤት ለማምጣት አስተማማኝ አመራርና የተቀናጀ አሠራር አስፈላጊ እንደሆነ በተግባር ተመልክተናል።
በመጀመሪያው ዕለት ከንቲባዋ ራዕያቸውንና ዕቅዳቸውን ሲያስረዱን፣ ይሄ ሁሉ እንዴት ተግባራዊ ሊሆን ይችላል የሚል ጥያቄና ጥርጣሬ ነበር የተፈጠረብኝ። ከንቲባዋ የራዕይና የዕቅድ ብቻ ሳይሆን የተግባርም ሰው ናቸው። ሥራውንም በአካል እየሄዱ ይከታተላሉ። በሄዱበት ሁሉ ሕጻናት ከንቲባዋን በደስታ ሲቀበሉና እየሮጡ ሲያቅፉ አይቻለሁ። ከንቲባዋ ለሥራው ምን ያህል ቅርብ እንደሆኑ ታዝቤያለሁ።


የኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ዋና አሰልጣኝ በትረማርያም ገዛሐኝ በኮላሮዶ አሜሪካ በሚካሄደው “ ስፓርታን ካፕ ሻምፒዮንሺፕ” ላይ ኢትዮጵያና ምስራቅ አፍሪካን በመወከል ይሳተፋል። ዛሬ በኮሎራዶ በሚጀመረው ሻምፒዮን ሺፕ ላይ በ7 የተለያዩ ዘርፎች የውድድር መደቦች የቴኳንዶ ክለቦች፤ ማሰልጠኛዎችና አካዳሚዎች ተሳታፊ እንደሚሆኑ ታውቋል።
የኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ዋና አሰልጣኝ (ሳቦም) በትረማርያም ገዛኸኝ ከኮሎራዶ ለስፖርት አድማስ በሰጠው አስተያየት በስፓርታን ካፕ ሻምፕዮናው ላይ
የኢትዮጵያን እና የቀድሞ አሰልጣኙን ኪሮስን ስም  ከፍ ለማድረግ መዘጋጀቱን አስታውቋል። ሳቦም በትረማርያም በአንድ ቀን ውስጥ በአራት የተለያዩ የውድድር መደቦች ተደራራቢ ተሳትፎዎችን ያደርጋል። በቴኳንዶ የፓተርን ትርዒት፤ የነጥብ ፍልሚያ ፤ ለቀበቶ የሚደረግ ስፓርታ ፋይት እና ወደ ኦሎምፒክ ሊያሳልፍ የሚችል የስፓሪንግ ውድድር ላይ ነው። በስፓርታን ካፑ ላይ የተለያዩ አገራትን የሚወክሉ የቴኳንዶ ክለቦችና ስፖርተኞች ተሳታፊ ሲሆኑ በእያንዳንዱ የውድድር መደብ ከ18-20 ተወዳዳሪዎች ይገኙበታል።ሳቦም በትረማርያም በሚሳተፍባቸው 4 የውድድር መደቦች 3 እና 4 ተጋጣሚዎችን ጥሎ ማለፍ እንዳለበት ገልፆ፤ ዋንኛ እቅዱ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ለከፍተኛ የቀበቶ ሽልማት ለመብቃት ነው።
ከኮሎራዶው ሻምፓዮንሺፕ በኋላ በአርጀንቲና በሚካሄደው የኢንተርናሽናል ቴኳንዶ የዓለም ሻምፒዮና እንዲሁም በክሮሺያ በሚዘጋጀው ግዙፉ የኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ዓለም ዋንጫ ላይ መሳተፍ መብቃት መሆኑን ለስፖርት አድማስ ተናግሯል።
ሳቦም በትረማርያም ከኮሎራዶ ስፖርታን ካፕ በፊት በኢንተርናሽናል ቴኳንዶ  99 ሜዳሊያዎችን በአገር ውስጥ፤ በአህጉር አቀፍና በዓለምአቀፍ ውድድሮች የሰበሰበ  ነው።  የቴኳንዶ ስፖርተኛ፤ አሰልጣኝና ባለሙያው  በቴኳንዶ ስፖርት ከ21 ዓመታት በላይ የቆየ ሲሆን 5ኛ ዳን( 5ኛ ዲግሪ ጥቁር ቀበቶ) ታጥቋል።
 ከ2 ወር በፊት በአሜሪካ በተካሄደውና  14 አገራት በተሳተፉበት “ኮምባት ቴኳንዶ “ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያና አፍሪካን በመወከል ሲወዳደር አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አስመዝግቦ ነበር ወደ አገሩ የተመለሰው። በኮሎራዶው ስፓርታን ካፕ ለመሳተፍ የበቃውም በዚህ ውጤቱ ነው።
ሳቦም በትረማርያም ገዛኸኝ በኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት በአገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ውድድሮች 99   ሜዳሊያዎችን በመሠብሰብ ከፍተኛ ውጤት አስመዝግቧል። በኢንተርናሽናል ቴኳንዶ 5 የተለያዩ የውድድር ዘርፎች በፍልሚያ፤ ልዮ ትርኢትና ቴክኒኮች ለ5 ተከታታይ ዓመታት የአፍሪካ ሻምፒዮን   ሲሆን በአገር አቀፍ ውድድሮችም ለ13 ዓመታት አከታትሎ በማሸነፍ ስኬታማ ሆኗል ።
በትረማርያም “ሪል ዋርየር” በሚል ስያሜ የቴኳንዶ ማሰልጠኛ  በመመስረት ያለፉትን 9 ዓመታት  እየሰራ  ቆይቷል። አዲስ አበባ ውስጥ በሚገኙ ሁለት ቅርንጫፎችም በሁሉም የዕድሜ ደረጃዎች ከ150 በላይ ሰልጣኞችን እያስተማረበት ነው።


ከቦታ ቦታ እየተዘዋወሩ ለሰዎች ምክር በመስጠት የታወቁ አንድ ብልህና ጨዋታ አዋቂ ሽማግሌ ነበሩ፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አንድ ጅል ዛፍ ጫፍ ላይ ሆኖ፤
“አባቴ እባክዎ ምክር ፈልጌያለሁ ይርዱኝ?” ሲል ይጠይቃል፡፡
“በጄ፤ ምን ልምከርህ?”
“ይቺን ቅርንጫፍ ልጥላት እዚች ጋ ልመታት ነው”
“መክረህ ጨርሰሃል ልጄ እንደውሳኔህ ቀጥል”
ይመታዋል፡፡ ቅርንጫፉ ይወድቃል፡፡
ሌላ ቅርንጫፍ ይጠቁምና፤ “ይሄኛውንም ቅርንጫፍ ለመጣል እዚህ ጋ ልሰነትር ነው” ይላል፡፡
“መክረህ ጨርሰሃል ልጄ እንደበጀህ ቀጥል” ይሉታል፡፡
ያለውን ቦታ ሲመታው ቅርንጫፉ ተገንጥሎ ይወድቃል፡፡
እንዲህ እንዲህ እያለ ቅርንጫፎቹን ሁሉ በመጥረቢያ ገነጣጥሎ ይጨርሳል፡፡ ከዚያም፤
“አባቴ፤ ቀጥዬ የቱን ልምታ?” ይልና ይጠይቃል፡፡
“እንግዲህ የቀረህ አንተኑ ይዞ የሚወድቀውን መምታት ነው”
“መውደቁን ግን ይወድቃል?”
“አሳምሮ ይወድቃል”
“እንግዲያውስ አልምረውም!”  ብሎ የተቀመጠበትን ግንድ ከበላዩ ይመታዋል፡፡ ተገንድሶ ሲወድቅ ራሱኑ ጭንቅላቱን መትቶ ይፈነክተዋል፡፡
“አባቴ፤ ግንዱ ሙሉውን አልወድቅ አለኝ ምን ይበጀኛል?”
“መፈንከቱ አልበቃህ ብሎ ነው?  ምልክት መስጠቱ እኮ ነው፤ አልገባህም?”
“ዛሬ እሱን ሳልጥል ከእዚህ ንቅንቅ አልልም!”
“እንግዲህ በጄ አላልከኝም ክፉኛ- አክርረሃል፡፡ አናቱን ብለህ እምቢ ካለህ የቀረህ ግርጌው አደል?”
ሞኙ ከእግሩ ስር ያለውን ግንድ መከትከት ይጀምራል፡፡
“ልጄ፤ እኔ ወደምሄድበት ልሂድ ስመለስ መጨረሻህን አያለሁ”
“ምነው አባቴ እስከዳር አብረውኝ ላይቆዩ ነው? እስካሁን አብረን ቆይተን?”
“ያንተ አንሶ ለኔ እንዳይተርፍ ብዬ ነዋ! ግዴለህም ከሶስታችን አንዳችን ለወሬ ነጋሪ እንኳ እንቆይ፡፡ ኋላ መጨረሻህን ባይ ነው የሚሻለኝ!” ብለው ሄዱ፡፡
ሽማግሌው ሲመለሱ ግንዱም ሰውዬውም ወድቀው አገኟቸው፡፡ ሰውዬው እግሩ ተሰብሮ ወገቡ ተቀጥቅጦ ሲያቃስት ደረሱ፡፡
“ይሄውልዎት አባቴ ተሰበርኩ ግን ግንዱን ጥዬዋለሁ”
“እሱም አፍ ቢኖረው እንዳንተው ጣልኩት ነበር የሚለው፡፡ አይ የናንተ ነገር ተያይዞ መውደቅ እንጂ ተደጋግፎ መቆም አልሆነላችሁም” አሉት፡፡

***
መክሮ የጨረሰ የሌላ ምክር አይሰማም፡፡ ወይም አያስፈልገኝም ይላል፡፡ እራሱን ጭምር ይዞ የሚወድቀውን ግንድ በመጣል የሚረካ ብዙ ግብዝ አይተናል እያየንም ነው፡፡ ይህ ሂደት በፖለቲካ ፓርቲ፣ በመንግስታዊ መዋቅሮች፣ በየቢሮው ወዘተ የአዘቦት ጉዳይ ሆኗል፡፡ ጉዟችን ሁሉ ደክሞ ደክሞ እንደገና ከዜሮ የመጀመር የሆነው አንድም በዚህ ሳቢያ ነው፡፡ “ቀጥዬ የቱን ልምታ?” ማለት እንጂ “ቀጥዬ የቱን ላድነው” የሚል ሰው አልተዋጣልንም፡፡ በዚህም ቁልቁል ማደግን ባህል አድርገነዋል፡፡ ሌላው ፈሊጣችን ደግሞ ብንቆስልም ብንደማም ካደረስነው ጥፋትና ከደረሰብን ጉዳትም ለመማር አለመቻላችን ነው፡፡ “ተሳስቼ ይሆን?” ከማለት ይልቅ፣ “ካለመስዋዕትነት ድል የለም” ማለትን እናዘወትራለን፡፡
አንድያችን ተንኮታኩተን ካልወደቅን “ያለምኩትን ብለቅ አይማረኝ” እያልን ሙጭጭ ማለት ነው፡፡ የእርግማን ክፉ ከትንሽም ከትልቅም ስህተት ፈጽሞ አለመማር ነው፡፡
ራስን በአዲስ መላ፣ በአዲስ መርህ፣ በአዲስ ፕሮግራም ከመውለድ ይልቅ ከትላንቱ ክታቤ ጋር ልሙት ማለትን ለደጉም ለክፉውም የምንምልበት ቃለ-መሀላ አድርገነዋል፡፡
የእኛ ነገር “ተፍቆ ጥርስ አይሆን፣ ተመክሮ ልብ አይሆን” ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡
የትላንት ቂም፣ የትላንት ያደረ - ሂሳብ፣ አገር ላያለማ  ነገር፣ ከእነ ግንዳችን ካልወደቅን ያሰኘናል፡፡ የቡድንና የቡድን አባቶች  ብሎ ተቧድኖ “ከቦምብ ከመትረየስ” ከማለት ይልቅ፣ ቢያንስ “ከሰማይ በራሪ-ከምድር ተሽከርካሪ” ማለት መሻሉን ካላየን እድሜ -አለማችንን ጠብ-ጠማሽ ሆነን እንደመቅረት ነው፡፡ ከበረታን በዱሮ በሬ ማረስ ይቻላል ብሎ ቢነሱ እንኳ የዱሮ እልህ፣ የዱሮ ጉልበት፣ የዱሮ መሬትና የዱሮ የእህል ዘር እንደ ልብ ስለማይገኝ አርቆ ማሰብ  ተገቢ ነው፡፡ በአንፃሩ አዲስ በሬ በአቅልና በተገቢው ማሳ ላይ ይውላል ብሎ ማሰብም አዲስ ባዩ ቁጥር ጉሮ - ወሽባዬ ማለት ይሆናል፡፡ የወረት ውሻ ስሟ ወለተ - ጊዮርጊስ ነው እንዲሉ፡፡
በኢትዮጵያ የፖለቲካ አደባባይ ላይ የሚታዩ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ማህበራትና ቡድኖች “ሁሉን ጥዬ እኔ ልታይበት፣” “እኔ ልዩ የክት ልብስ አለኝ” ከሚለው እምነት ይልቅ የተግባር ቅደም -ተከተላቸውን መልክ በማስያዝ፣ የፖለቲካው ስር የሰደደ ችግር በጋራስ ሆነን ሊፈታ ይችላልን? ብለው፣ አስቀድሞ የተረጋጋ ማረፊያ ህዝቡ ውስጥ፣ ቀጥሎ በየፖለቲካ መዋቅሩ ላይ፤ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ የአየር ጠባይ አንፃር ሲታይ፣ ምንም ነገር ቀላል ነው ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፡፡ ጊዜ አለኝ ብሎ መዘግየትም ሞኝነት ነው፡፡ ከትላንት የምንበደረው ጊዜ እንኳ ቢገኝ መውሰድ ነው የሚባልበት ዓይነት ትግል ጠይቋል ወቅቱ፡፡ ከቶውንም ሁሉም የፖለቲካ ነገር በራስ የሚሰራ፣ የገዛ አፈርን  እያሸተቱ ከህዝቡ ጋር ተሆኖ የሚሰራ እንጂ የማናቸውም ቴክኖሎጂ የሩቅ - መቆጣጠሪያ (Remote control) የሚከናወነው አይደለም፡፡ እንደ ዱሮው “በጠባቧ ቢሮአችን  ተቀምጠን የሰፊውን ህዝብ  የልብ ትርታ እናዳምጣለን /እንቆጣጠራለን!” የሚባልበት ወቅት አይደለም፡፡ የየቢሮውን ቀይ - ጥብጣብ ማሸነፍን  ይጠይቃል፡፡ የህዝቡን ልብ  በመንፈስም በዐይነ-ሥጋም ማሸነፍን የግድ ይላል፡፡
ይህን ሁሉ ካደረጉ በኋላ እንግዲህ “መቀመጫ ያገኘ እግሩን መዘርጊያ አያጣም” ለመባባል ይቻላል!!



     በአገራዊ ምክክሩ የሚሳተፈው የሙስሊሙ ቁጥር አናሳ መሆኑን የገለፀው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት  የተሳታፊዎች ልየታ  በድጋሚ እንዲካሄድ ጥሪ አቅርቧል። በሙስሊሙ በኩል የቀረቡ አጀንዳዎች በምክክሩ ውስጥ እንዲካተቱም ጠይቋል።
“የሙስሊሞች ተሳትፎ በሕዝባችን ቁጥር ልክ መሆን አለበት” ያለው ም/ቤቱ”፤ የተሳታፊዎችና የአወያዮች ቁጥር በኮሚሽኑ የአካታችነት መርህ አማካይነት አንዲታይ አመልክቷል።
ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለአገራዊ ምክክር ኮሚሽን የበላይ ጠባቂ፣ ለፕሮፌሰር መስፍን አርአያ በፃፈው ደብዳቤ፤  የሕዝበ ሙስሊሙን የምክክር እጀንዳዎች ለጉባኤው ለማሰማትና ለማብራራት የሚችሉ ተገቢ ቁጥር ያላቸው ሙስሊም ተወካዮች እንዲካተቱ የሚጠይቅ ሃሳብ ከህዝቡ መምጣቱን ገልጿል። በዚህም ምክንያት “ስብጥሩ በፍትሐዊነት እንደገና ይቃኝ” ሲል ጠይቋል።


ኮሚሽኑ ከትግራይ ክልል ውጪና ግጭት ባለባቸው የአማራና ኦሮሚያ ክልሎች አንዳንድ አካባቢዎችን ሳያካትት፣ በ10 ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ለምክክሩ የሚሳተፉ አካላትን ልየታ ቢያካሂድም፣ “የሙስሊሙ ቁጥር አነስተኛ ነው” ብሏል - ጠቅላይ ምክር ቤቱ፡፡
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ተወካዮች ከአገራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ሦስት ሃላፊዎች ጋር  ውይይት ማድረጋቸውም ተነግሯል። “በባለሞያ በተሰጠ መግለጫ ላይም  በተሳታፊና በአወያይ ደረጃ የሙስሊሞችን ተሳትፎ እንዲነገረን ብንጠይቅም፣ ከምክክር ኮሚሽኑ ምላሽ አልተሰጠንም” ሲል ጠቅላይ ምክር ቤቱ አስታውቋል፡፡
አገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ውሳኔውን በድጋሚ እንዲያጤነው የጠየቀው ጠቅላይ ምክር ቤቱ ለኮሚሽኑ የቀረቡ የመስሊሙ አጃንዳዎች እንዲካተቱና ህዝበ ሙስሊሙም በቁጥሩ ልክ ተሳታፊ እንዲሆን ጥሪ አቀርቧል።
በኢትዮጵያ በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ለመፍጠር እንደሚያስችል የታመነበት የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን በአዋጅ ተቋቁሞ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡

Page 2 of 708