የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት?

ይህን ጽሑፍ ያዘጋጀሁት ስለ አንጋፋው ደራሲ አቤ ጉበኛ አንዳንድ ሃሳቦችን ለመሰንዘር ነው። ጽሑፉ ከምርምርም በሉት ከጥናት ሥራ ጋር የሚመደብ አይደለም፡፡ ወፍ በረር ወይም ወፍ ዘለል ምልከታ አይባልም፡፡ በአጭሩ እኔ ስለአቤ የተሰማኝን የገለጽሁበት መላምታዊ ስሜት ነው፡፡
አቤን እኔ በሚገባ ወይም በቅርበት አላውቀውም፡፡ የአቸፈር ሰው መሆኑን፣ ዳንግላ መማሩን የተረዳሁት በቅርቡ ነው፡፡ የእኛ ዘመን ምሁራን “የየት አገር ሰው ነህ?” ተባብለው በይፋ አይጠያየቁም ነበር፡፡ በትምህርት ቤት ዘመኔ “ሰይፈ-ነበልባል” የተባለውን ድርሰቱን ያነበብሁ ይመስለኛል፡፡ በእኔ የጉርምስና ዘመን፣ በእኔ አካባቢ ስሙ እንደ ሌሎች ደራሲዎች ጎልቶ ሲነገር አልሰማሁም፡፡ ወይም የግንኙነት አድማሴ ጠባብ ነው ወይም በጆሮዬ ተኝቼበታለሁ፡፡ አሁን ይህን እያልሁ ያለሁት በዚያ በእኔ ዘመን ላይ ቆሜ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ አዎ! እንደ ከበደ ሚካኤል፣ እንደ መንግስቱ ለማ፣ እንደ ፀጋዬ ገ/መድህን፣ ሌላው ቢቀር እንደ መንግስቱ ገዳሙ እንኳ በስሙ አይዘመርለትም ነበር፡፡ የፈጠራ ስራው የወረደ ስለሆነ? ፈፅሞ አይመስለኝም፡፡ ሥራዎቹማ! እሳት ጫሪ፣ አነጋጋሪ፣ የአብዮት ማዕበል ጠሪ ነበሩ፡፡ ፀባዩ ከሰው ስለማይገጥም? ይህ በከፊል እውነት ሊሆን ይችላል፡፡ አቤ እከክልኝ-ልከክልህን የማያውቅ በራሱ የሚተማመን የቀለም ሰው ነበር፡፡ ይህን ሁሉ የሆነ ደራሲ ለምን ደመ መራራ ሆነ? መልሱን እኔም አልሰጣችሁም፤ እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡
በእነዚያ ዘመናት በአቤ ስም ላይ የተጫኑትን ቋጥኞች ከሥር መሰረታቸው ፈልፍሎ ለማወቅ በእርግጥም ጥልቅ ጥናትና ምርምር ይጠይቃል፡፡ እኔ ግን መላምቴን ጎን-ለጎን ባስሔድ ጆሮውን የሚነፍገኝ እንደማይኖር ተስፋ አለኝ፡፡
1. አቤና የአጼው ዘመን
በዚያን ዘመን የነበሩ ደራሲያን፣ አብዛኛዎቹ በቀኝ እጃቸው ብዕር፣ በግራ እጃቸው ሥልጣን የጨበጡ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የዘመኑ ሹም የሰራው ብቻ ሳይሆን በሩቁ በማንኪያ የነካው ወጥ ሁሉ ይጣፍጥለታል፡፡ ለምን ቢሉ? ወጡ እንዳይጎረና ዙሪያ ከበው የሚያማስሉለት ብዙ ሌቄዎች ከጎኑ ስላሉ … የዚያ ሁሉ ወጥ አማሳይ እጅ ያረፈበት ወጥ ደግሞ በየትኛውም መመዘኛ ሲታይ ላይጣፍጥ አይችልም፡፡
አቤ በዚያን ዘመን የግሽ-አባይ ጎርፍ ከገጠር አምጥቶ ከቀለጠው ከተማ የዶለው ብቸኛ ፍጡር ይመስለኛል፡፡ በቀኝ እጁም የያዘው ብዕር ብቻ ነው፡፡ ብዕሩም በቅኔ ቤት እንጂ በገነተልዑል ግቢ ውስጥ ገብቶ ያልተሟሸ ነው፡፡ ቃላቱም ቱባ-አገራዊ ሽካራ እንጅ ቤተመንግሥታዊ ለስላሳ አይደለም፤ አስተሳሰቡም ደረቅ-ገጠራዊ እንጅ ከተማዊ-ጮሌ አይመስለኝም፡፡ ገፀ-ባህርያቱም አብዛኛዎቹ ከውጭ አገር የኮረጃቸው ሳይሆን ከአካባቢው በተጨባጭ የፈጠራቸው ናቸው። በፖለቲከኞች ቋንቋ ለመናገር፣ አቤ ለዘመኑ ቢሮክራሲ አጎብዳጅ አልነበረም። (አስር ጊዜ አይመስለኝም… ይመስለኛል… የምለው ያለምክንያት አይደለም፡፡ አንድም ከላይ እንደገለጽሁት ጽሑፉ ጥናታዊ አለመሆኑን ለማረጋገጥ ነው፡፡ ሁለትም ለዚህ መረጃ የሚሆን ማጣቀሻ የፈረንጅ ስም ለመጥራት ስላልፈለግሁ ነው፡፡ ሶስትም አገራዊ ሊቃውንትን በመረጃነት እንዳላቀርብ የቀሰምሁት ዘመናዊ የፈረንጅ ትምህርት የሚስበኝ ወደ ነጭ ምሁራን እንጂ ወደ እራሴ ሊቃውንት አለመሆኑን ለማስገንዘብ ጭምር ነው፡፡)
ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ልመለስ፡፡ እና! የአቤ ስም በዘመነ አፄ ለምን ገንኖ አልወጣም? ልብ በሉ፤ አቤ በዚያን ዘመን ግራ እጁ ባዶ ቢሆንም ቀኝ እጁ የሚንቦገቦግ የብዕር ሰይፍ ጨብጧል፡፡ ይህ ሰይፈ-ነበልባል የዘውዱን ህዝባዊ የብዕር ሰው ስም በስርአቱ እንዲታፈን መደረጉ ተገቢም ባይሆን የሚጠበቅ ነው፡፡ ያኔ ሥዩመ እግዚአብሔርን መዳፈር ራሱን ፈጣሪን መድፈር ሆኖ ይቆጠራል፡፡ ይህንን የስዩማንን ድፍረት ቅኔ የቆረጠባት ቤተክርስቲያንም ብትሆን በደግ የምትቀበለው አይመስለኝም፡፡ ቀብታ ያነገሰችውን ንጉሥ ከጉያዋ የወጣ ደብተራ፣ በግራ እጁ ስልጣን ያልጨበጠ ብዕረኛ፣ የቁም-ስቅሉን ሲያበላው ቁጭ ብላ አትመለከተውም፡፡ ያኔ! አቤን አውግዢው፤ ወይም የይቅርታ ደብዳቤ አስጽፊው ብትባል አቤን እንዲጽፍ ሳታስገድደው የምትቀር አይመስለኝም፡፡
ንጉሡና በእሳቸው አካባቢ ያሉት መኳንንትና መሳፍንት አቤን የሚመለከቱት እንደ ኮሚኒዝም በጎሪጥ ነው፡፡ በዘመነ አብዮት ቆምጬ፤ “ኢምፔሪያሊዝምን በጎሪጥ ሶሻሊዝምን እንደ በላይ ዘለቀ አያቸዋለሁ” ብሏል አሉ፡፡ ይህ በዘመኑ ቢሮክራሲ የጎሪጥ የሚታይ ሰው፣ ግራ እጁ ባዶ የሆነ፣ ብዕሩ አርፎ የማይተኛ ተንኳሽ፣ በዐይነ-ቁራኛ የሚታይ ሞገደኛ ብዕረኛ፣ እንኳንስ ስም አሞጋሽ፣ አፍ-አካፋች ጓደኛም አይኖረውም፡፡ እንኳንስ በቀኛቸው ብዕር፣ በግራቸው ሥልጣን የጨበጡት ደራሲያን፣ የእነሱ ቅርበት ያላቸውም ንዑስ ደራሲያንም ቢሆኑ አቤን የሚቀርቡ አይመስለኝም፡፡ ከእሱ ጋር መታየት ከእሱ ጋር መፈረጅ ነው፡፡ ከእሱ ጋር መፈረጅ ደግሞ ከእሱ ጋር ግዞት መውረድ ያስከትላል፡፡ በመሆኑም በዘመኑ አቤን የከበቡት ስም አጥፊዎቹ እንጅ ስም አልሚዎቹ አይደሉም ባይ ነኝ፡፡ በቀረው ተመራማሪው ይሙላበት፡፡  
2. አቤና የተማሪው እንቅስቃሴ
እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ በአገራችን ብቻ ሳይሆን በመላው ተራማጅ ዓለም ህዝቦች ዘንድ አንቱ የተባለ ማህበር ነበር፡፡ ማህበሩ ጥልቅ ተራማጅ ብቻ ሳይሆን የሶሻሊስት ርዕዮት አለም ተከታይ ጭምር ነበር፡፡ እንቅስቃሴውም በአገር ውስጥ የነበረው ተሰሚነት ቀላል አልነበረም፡፡ የዘውዱን ስርዓት ቦርቡሮ የጣለው ይህ እንቅስቃሴ እንደሆነ ይታመናል፡፡ ምንም እንኳ ዋርዳ ወይም ማማት ወፎች ፈልገው ያገኙትን የሾላ ፍሬ (አብዮት መሆኑ ነው) አንድ ጉራሽ ሳይቀምሱት ዛፉ ላይ ወጥተው ሲንጫጩ፣ የቤተ መንግሥት ጫካ ተንተርሶ፣ እረኛ መስሎ የበግ ለምድ ለብሶ፣ ያደፈጠ ዝንጀሮ የሾላውን ፍሬ ቢቀማቸውም፣ የተማሪው እንቅስቃሴ ለዚያን ጊዜው ለውጥ ያበረከተው አስተዋጽኦ እጅግ ከፍተኛ ነበር፡፡
ይህ እንቅስቃሴ በላይን ንጉሡ አንቀው ከቀበሩት ጉድጓድ አውጥቶ የታጋይ ካባ ያለበሰ ማህበር ነው። ደጃዝማች ታከለን ፈርጣጭ ንጉሥ አጋች ብሎ ያሟካሸ ነው፡፡ ከዘመኑም ደራሲያን መካከል መርጦ የተቡ ብዕርተኞች ብሎ የካበና የሾመ ነው፡፡ ለ“አልወለድም” ደራሲ፣ በግራ እጁ ባዶ ሆኖ ሥርዓቱን ቀድሞ ለተፋለመ ህዝባዊ የብዕር ሰው፣ ማህበሩ ለምን ያኔ! የጎላ ዕውቅና አልሰጠውም? በግሌ ይህ ተራማጁ የተማሪዎች እንቅስቃሴ በመጽሔቶቹ ላይ ስለ አቤ የፃፈውን ነገር አላነበብሁም፡፡
አቤ በሩሲያ ሥነ-ጽሑፍ ውስጥ ሥራው በተራማጅነት ተፈርጆ ሰፊ መድረክ ሲሰጠው፣ ተራማጁ የተማሪው ማህበር ለምን ስለአቤ ምንም ሳይል አለፈ? አቤ የተማሪው ማህበር የቆመለተን ዓለማ ሙሉ-በሙሉ ያሟላ ብዕረኛ ነው፡፡ የዘውድን ሥርዓት በብዕሩ በጽናት ተፋልሟል፡፡ ለዚህም ድፍረቱ ተግዞ ታስሯል፡፡ ከዘመኑ ብዕረኞች መካከል እንደ አቤ የዘውድ ስርዓትን በብዕሩ በግልጽ የሞገተ ደራሲ እንኳን ያኔ፣ አሁንም ያለ አይመስለኝም፡፡ ታዲያ፣ ጉዳዩ ይህ ሆኖ ሳለ፣ በዓላማ የተሳሰረውን ህዝባዊ ደራሲ፣ ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ለምን ስሙን ሊያገነው አልቻለም? እውን “አልወለድም”ን ባያነብ ነው? ሠይፈ ነበልባልን አንብቦ ባይገባው ነው? ቢያንስ “አንድ ለእናቱ” ብቻውን የአቤን ስም ማግነን ይሳነዋል? የዳኛቸው ወርቁን ብቸኛ ልብወለድ “አደፍርስ”ን በየጥናት ክበባት ያስነበበን የተማሪ ማህበር፣ ለምን ከአቤ ስራዎች አንዱን እንድንወያይበት አላደረገም? የአቤስ የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት? መልሱን ባውቀውም አልነግራችሁም፡፡ እናንተም እንድትነግሩኝ አልፈልግም፡፡ ለምን ብትሉ መላምት እንጅ ጥናትና ምርምር አይደለምና፡፡
3. አቤና ደርግ
“ሶሽያሊስት ነኝ” ያለው የደርግ መንግሥት ሶሽያሊስት አመለካከት ላላቸው የጥበብ ሰዎች ወዳጅ አልነበረም፡፡ ማርክስ ለማለት ማርቆስ የሚሉትን የደርግ አባላት ያስተካከሏቸው ደብተራቸውን ወርውረው፣ ትምህርታቸውን ጥለው ለዘመናት የታገሉለት አብዮት በእርግጥ የፈነዳ መስሏቸው አገር ቤት የገቡት፣ የተማሪውን ማህበር ሲያንቀሳቅሱ የኖሩት እውነተኛ ተራማጆ ናቸው፡፡ እነዚህም ወጣት ተራማጆች በወጉ ሳይደራጁ አገር ቤት ገብተው ደርግ እርስ-በእርስ ያጨፋጨፋቸውና የተረፉትን እራሱ አርዶ አስፋልት ላይ ያሰጣቸው ናቸው፡፡ በአጭሩ ኮትኩተው-አሰልጥነው፣ መግበው ያሳደጉት ውሻ የበላቸው የዋህ ታጋዮች ናቸው፡፡
ወደ አቤ ስመጣ፣ ደርግ በአብዮት ስም የተረከባት አገር እነአቤ ቀደም ብለው በህዝባዊ ብዕራቸው ያደነቋት፣ የዘመሩላት፣ የተጋዙላት ኢትዮጵያ ናት፡፡ እጅግ በርካታ ህዝቦች አንድ-አንድ ጡብ እየጨመሩ በገነቡት ቤት ላይ ደርግ የመጨረሻዋን ጡብ እንኳ ሳያሰቀምጥ የቤቱ ባለቤት እኔ ነኝ አለ፡፡ በእርግጥም ደርግ ምንም አይነት ጡብ በዚህ የቤት ሥራ ላይ አላኖረም፡፡ በአንፃሩ ግን ደርግ በዘውድ ሥርዐት ታማኝነቱ፣ በአጣና ደብዳቢነቱ፣ በግድያ ፈፃሚነቱ፣ ሕንፃ ገንቢ የሆኑ ተማሪዎችን፣ ምሁራንን በአጠቃላይ ምስኪን ገበሬዎችን አሳዶ ይገድል፣ ህዝባዊ የፈጠራ ሰዎችን ያስር፣ ከግዞት እንዳይወጡ በር ዘግቶ ይጠብቅ የነበረ ዋርድያ ነው፡፡ ይህ ዋርድያ የአገሪቱን ስልጣን ከተረከበበት ቀን ጀምሮ በአፉ ሶሻሊዝም እየሰበከ፣ በተግባር ሶሽያሊስት አመለካከት የነበራቸውን የጥበብ ሰዎች ከኢምፔሪያሊዝም ጋር ደምሮ የጎሪጥ ያያቸው ጀመር፡፡ እንደ አቤ ባይበረታባቸውም መንግስቱ ለማና ሌሎችም የደርግ ጥላቻ ዒላማ ነበሩ፡፡
የአቤ ድርሰቶች ለደርግ የተዋጡለት አይመስልም። ለስልጣን ወይም ለገንዘብ የማይንበረከከው አቤ፤ ከጊዜ በኋላ ብዕሩን ወደ ደርግ እንደሚያዞርበት ገብቶታል፡፡ ደርግ የጀመረውን ትውልድ የማጥፋት ዘመቻውን አቤ ዐይቶ እንዳላየ፣ ሰምቶ እንዳልሰማ ሆኖ በፀጋ የሚቀበለው አይሆንም። በዚህም መሰረት አቤን ከአካባቢው አርቆታል፡፡ የ“አልዋለድም” ደራሲ ጭራሮ-እንጨት ሆኖ ያቀጣጠለውን የአብዮት እሳት ቀርቦ እንዳይሞቅ አግዶታል፡፡ ምንም ዐይነት አስተዋጽኦ እንዳላደረገ ሆን ብሎ ወደ ጎን ገፍቶታል። ዛሬም እንደ ትላንቱ አቤ ከሁሉም የተገለለ ብቸኛ ደራሲ ሆኗል፡፡ ዛሬም እንደ ትላንቱ በጃንዳርም ሰላዮች የሚጠበቅ የብዕር ሰው ተብሏል፡፡ ከአቤ ጋር ቆሞ መታየት ሳይቀር ቀይ ሽብርን የሚጋብዝ አስፈሪ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የእሱን ብዕር ምርኳዝ አድርገው ሥልጣን ላይ የወጡ ደርጎች ለምን የአቤ ስም እንዲቀበር ፈለጉ? በእርግጥም አቤ በወቅቱ የደርግ ስጋት ነበረ? አዎ! ነበረ፡፡ ምንአልባት በወቅቱ የፈለቁት ሕቡዕ ድርጅቶች መልምለውት ይሆን? ጨርሶ አልተጠጉትም፡፡ አቤ ከእነሱ ሁሉ ባላይ አርቆ የሚያስብ ታጋይ ብዕረኛ ነበር፡፡ አሁን አጠገቤ ቢሆን ኖሮ “ማንም ተልካሻ በተጠራበት ስም ታጋይ፣ ተራማጅ፣ አትበለኝ” ብሎ ይገስፀኝ ነበር፡፡ አቤ ያኔ! ወደ አንዱ ጎራ ጠባ ቢልማ ኑሮውና ቀብሩም የውሻ ባልሆነ ነበር፡፡
የተፋለመለትን ህዝብ አምኖ ለህዝብ መብትና ፍትህ እየጮኸ፣ የተጋዘለት ህዝብ ግን ሳይደርስለት ደሙ-ደመ ከልብ ሆኖ ቀረ፡፡
እና! በፈጣሪ ተሰይሞም ሆነ ጠበንጃ አንግቦ ሥልጣን ላይ የወጣ ሹም ሁሉ ለምን አቤን ጠላው? ለምን አሳደደው? ለምን ሊቀበር የማይችለውን ስሙን ለመቅበር ሞከረ? መልሱን እኔም አልነግራችሁም … እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡ ጥያቄ?

Published in ጥበብ
  • የኃይል መቆራረጥና የጥሬ ዕቃ አቅርቦት ዋና ፈተና ሆኗል
  • ድሬደዋ ጨርቃጨርቅ በሶስት ዓመት ውስጥ ለ402 ቀናት መብራት አላገኘም
  • ድሬደዋ የምግብ ኮምፕሌክስ በመብራት መቋረጥ በቀን 200 ሺ ብር እያጣ ነው


    ባለፈው ሳምንት የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ከተለያዩ ሚዲያዎች ለተውጣጡ ጋዜጠኞች የጉብኝት ፕሮግራም አዘጋጅቶ ነበር። ጉብኝቱ ከሞጆ ቆዳ ፋብሪካ ጀምሮ አዳማ የሚገኘውን ኤልሲ አዲስ ኢንዱስትሪያል ዲቨሎፕመንት ፒኤልሲ የተባለ የቱርክ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካን ጨምሮ በቀጥታ በድሬደዋ የሚገኙ የጨርቃጨርቅ፣ የሲሚንቶ፣ የምግብና መሰል ፋብሪካዎችን አስቃኝቷል። በዚህ ጉብኝት በተለይ የመብራት መቋረጥና ከእነአካቴውም መጥፋት በኢንዱስትሪው ዘርፍ የተጋረጠ አብይ ፈተናና አደጋ መሆኑን ታዝበናል፡፡
ሞጆ ቆዳ ፋብሪካ
ሞጆ ቆዳ ፋብሪካ በመንግስት የተቋቋመ ቢሆንም አሁን ግን ወደ ግል ይዞታነት ተቀይሮ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡ በ30 ሚሊዮን ብር ካፒታል የሚንቀሳቀሰው የቆዳ ፋብሪካው፤ 85 በመቶ ምርቱን ለውጭ ገበያ የሚልክ ሲሆን 15 በመቶውን አገር ውስጥ ለሚገኙ እንደ አንበሳ እና ካንጋሮ ያሉ ጫማ አምራች ድርጅቶች እንደሚያቀርብ የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሬድዋን በዳዳ ተናግረዋል፡፡ በዚህ ዓመት ከዘርፉ 11 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት መታቀዱም ተገልጿል፡፡ በፊት ጥሬ ቆዳ ብቻ ሲልክ የቆየው ፋብሪካው፤ በአሁኑ ወቅት የተዘጋጁና ያለቀላቸው የበግ፣ የፍየልና የበሬ ቆዳዎች ወደ ጣሊያን፣ ቻይናና ሌሎች አገሮች በመላክ ላይ መሆኑን የገለፁት አቶ ሬድዋን፤በቀጣይ የአዞ ቆዳን አዘጋጅቶ ለመላክ መታቀዱንም አብራርተዋል፡፡
ፋብሪካውን በጎበኘንበት ወቅት የተመለከትነው የፋብሪካው ፅዳት ምቾት አይሰጥም፡፡ በፋብሪካው ሽታ ምክንያት ጉብኝቱን አቋርጠው የወጡ፣ ያስመለሳቸውና መረበሽ የታየባቸው ጋዜጠኞች ነበሩ፡፡ አብዛኞቹ ሰራተኞች ይህን ተቋቁመው እየሰሩ ቢሆንም ለአደጋ መከላከያ ተብሎ የተዘጋጀ ልብስ የላቸውም፣ አብዛኞቹ ከወገብ በታች የላውንደሪ ላስቲክ አሸርጠው ነው የሚሠሩት። በአጠቃላይ “safety first” ለሚለው መርህ ፋብሪካው ትኩረት የሰጠው አይመስልም፡፡ ምንም እንኳ የቆዳው መሽተት ተፈጥሮአዊ እና የሚጠበቅ ቢሆንም ጤንነትን በሚያቃውስ ደረጃ መሆኑ ግን ሊታሰብበት ይገባል፡፡ የፋብሪካው ወለል በአብዛኛው እርጥብ ሲሆን በጥንቃቄ ካልተራመዱ አንሸራቶ በአፍጢም የሚደፋ አይነት ነው፡፡
ለዚህም ነው አስጎብኛችን አቶ ሬድዋን “እንዳያንሸራትታችሁ ተጠንቀቁ” እያሉ በተደጋጋሚ ሲያስጠነቅቁን የነበረው፡፡ ፋብሪካው የሰራተኞቹን የጤና ሁኔታ በምን መልኩ ይጠብቃል በሚል ላነሳነው ጥያቄም ሲመልሱ “ክሊኒክ አላቸው፤ ሲያማቸው ይታከማሉ” በማለት በአጭሩ አልፈውታል፡፡ ይሁን እንጂ በተረፈ ምርት አወጋገድ ከ90 በመቶ በላይ ፋብሪካው የተዋጣለት እንደሆነ አቶ ሬድዋን በተደጋጋሚ ገልፀውልናል፡፡
ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ እንዳይሰራ የግብዓት፣ የገንዘብና የሎጂስቲክስ ችግሮች እንቅፋት እንደሆኑበት የሚናገሩት ስራ አስኪያጁ፤ እነዚህ ችግሮች በተፈለገው ፍጥነትና መጠን ቆዳን አዘጋጅቶ ለመላክ አላስቻሉንም ይላሉ፡፡ የጥሬ ቆዳ አቅርቦት እጥረት እንዲሁም  የኬሚካልና መለዋወጫ እቃዎችን ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ስለሚጠይቅ፣ የሚሰራበትን ብር ይይዘዋል ያሉት  አቶ ሬድዋን፤እነዚህን ፈተናዎች ለመፍታት ብድር፣ ሎጂስቲክስና መሰል ጉዳዮች በመንግስት ትኩረት እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡
ኤልሲ አዲስ ኢንዱስትሪያል ልማት ፒኤልሲ
ይህ የቱርክ የጨርቃጨርቅ ፋብሪካ እ.ኤ.አ በ2003 አዳማ ላይ በ150ሺ ስኩየር ሜትር ቦታ ላይ የተቋቋመ ነው፡፡ በ160 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት ስራ የጀመረው ፋብሪካው፤የበጀቱን ግማሽ ብቻ እየተጠቀመ እንደሆነ ተጠቁሟል። የጥጥ አቅርቦትና የጥራት ማነስ ችግር ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ እንዳይሰራ እንዳደረገው ተገልጿል። ይህን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ከመንግስት ጋር በመመካከር፣ ከአዲስ አበባ በአንድ ሺህ ኪ.ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው የኦሞ ወንዝ አካባቢ 400 ሺህ ሄክታር መሬት ወስዶ ጥጥ በማምረት ላይ ሲሆን ከሁለት ወር በኋላ ፋብሪካው የራሱ ጥጥ ይኖረዋል። ከሁለት ዓመት በኋላ ሙሉ በሙሉ በራሱ ጥጥ ማምረት የሚጀምር ሲሆን ከአምስት ዓመት በኋላ የሚፈለገው መጠን ያህል የራሱ ጥጥ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡ በዚህ ዓመትም 10 ሚሊዮን  ዶላር ገቢ እንደሚያስገኝ ይጠበቃል፡፡ ሁለተኛው ክፍል የፋብሪካው ማስፋፊያ ሲጠናቀቅ የሰራተኞቹ ቁጥር ወደ ስድስት ሺህ እንደሚያድግ ተብራርቷል፡፡
ፋብሪካው በግዙፍና በዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የተደራጀ ሲሆን ሰራተኞች በእጃቸው የሚነኩት የተወሰነ ነገር ብቻ ነው፡፡ ያን የሚያህል ፋብሪካ እነዛ ሁሉ ማሽኖች ተሰናስለው ያለእንከን ሲሰሩ ማየት ግርምት ይፈጥራል፡፡ በዚያ ላይ የማሽኖቹ ድምፅም ጆሮን የሚረብሽ አይደለም፡፡ ተረፈ- ምርቱ የጥጥ ፍሬ ሲሆን ለዘይት ምርት ግብአትነት የሚጠቀሙ ድርጅቶች እንደሚወስዱት ተገልጿል፡፡
የተማረ ሰው ኃይል፣ የጥሬ ዕቃ አቅርቦትና የኃይል መቆራረጥ በስራው ላይ ችግር እየፈጠረ እንደሆነ የተናገሩት የፋብሪካው ኃላፊዎች፤ በተለይ የተማረ የሰው ኃይል እጥረት ብሎም ከሰለጠኑ በኋላ ፍልሰቱ ፈታኝ እንደሆነበት አልደበቀም፡፡ በፋብሪካው 85 በመቶ ያህሉ ሴት ሰራተኞች ሲሆኑ ይህም ለሴቶች ብዙ የስራ ዕድል በሌለባት ኢትዮጵያ ትልቅ አጋጣሚ እንደሆነ የፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ ገልፀዋል፡፡ የሰራተኞቹ ደሞዝም ከሌሎች ፋብሪካ ሰራተኞች የተሻለ እንደሆነ የገለፁ ሲሆን ተዘዋውረን ያነጋገርናቸው ሰራተኞችም በስራውም ሆነ በክፍያው ደስተኞች እንደሆኑ ነግረውናል፡፡
የፋብሪካው ፕሬዚዳንት በቴክስታይል ዘርፍ የረጅም ጊዜ ልምድ ያላቸው በመሆኑ በወቅቱ የቱርክ አምባሳደር የነበሩት የአሁኑ የአገሪቱ  ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ፣ ከፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ጋር በመነጋገር ሊከፈት እንደቻለ በጉብኝታችን ወቅት ተገልፆልናል፡፡ 1100 ሰራተኞች ያሉት ኤልሲ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ፤ 95 በመቶ ያህል ሠራተኞቹ ኢትዮጵያዊያን ናቸው፡፡ ወደፊት ሰራተኞችን በማሰልጠን መቶ በመቶ በኢትዮጵያዊያን ሰራተኞች እንደሚመራም ተገልጿል፡፡ ግቢው ፋብሪካ ሳይሆን የተዋበ የሀብታሞች ሰፈር ነው የሚመስለው። የሠራተኞች ክበቡ ከአንድ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ ሬስቶራንት ጋር ይፎካከራል፡፡ ግቢው በአበባና በተለያዩ ዛፎች ያጌጠ ነው፡፡
ናሽናል ሲሚንቶ (ድሬደዋ)
በአገራችን የመጀመሪያው ሲሚንቶ ፋብሪካ ነው ናሽናል ሲሚንቶ፡፡ በ1936 ዓ.ም የተገነባው ሲሚንቶ ፋብሪካው፤ በቅርቡ ትልቅ ግዙፍ ማስፋፊያ ተገንብቶለት የድሮው ፋብሪካ በጡረታ ላይ ነው። በአሁኑ ሰዓት ምንም እየሰራ ባይሆንም ወደፊት ላይም (ኖራ) ሊመረትበት እንደታቀደ ተገልጾልናል፡፡   
በአዲሱ ግዙፍ የማስፋፊያ ፋብሪካ ለሲሚንቶ ግብአት የሚሆኑ የማይኒንግ ስራዎች ይከናወናሉ፡፡ በፊት በቀን 500 ቶን ያመርት የነበረ ሲሆን አሁን በቀን ሶስት ሺህ ቶን የማምረት አቅም አለው፡፡ የታክስ እፎይታን ጨምሮ ትልቅ ድጋፍ እንደሚያደርግ ኃላፊዎቹ ገልፀዋል፡፡ ፋብሪካው በምስራቅ የሀገሪቱ ክፍል ያለውን የሲሚንቶ ፍላጎት ከማርካቱም በላይ በሀገሪቱ የደቡብ ምስራቅ ማለትም ሀዋሳና አካባቢዋ እንዲሁም  ወደ ጎረቤት አገራት የመላክ እቅድም አለው፡፡ ፋብሪካው ሙሉ አቅሙን መጠቀም ሲችል  በቀን 40ሺህ ቶን ማምረት እንደሚችልና በሰው ኃይልና በቴክኒክ ችግሮች በሙሉ አቅሙ እየሰራ እንዳልሆነ ተጠቁሟል፡፡
በዋናነት ሲሚንቶ የሚጠቀመው መንግስት በመሆኑ የገበያ እጥረት እንደማያሰጋቸው የፋብሪካው ኃላፊዎች ይናገራሉ፡፡ የባቡር ሀዲድ፣ የጋራ መኖሪያ ቤቶች፣ ሆቴሎች፣ የአውሮፕላን ማረፊያና መሰል መሰረተ ልማቶች ስለሚገነቡ የሲሚንቶ ፍላጎት ይጨምራል የሚል እምነት እንዳላቸው የፋብሪካው ኃላፊዎች ይገልፃሉ፡፡ በተለይም በምስራቁ የአገሪቱ ክፍል የሲሚንቶ ፍላጎት አሁን ካለው ፍላጎት እንደሚጨምር የሚያመለክት ጥናት እንዳለ ኃላፊዎች ገልፀው፣ አሁን ያለው ከገበያ ጋር የተያያዘ ችግር ጊዜያዊ መሆኑንም በጉብኝታችን ወቅት ተገልጿል፡፡ አልፎ አልፎ የኃይል መቆራረጥ ቢኖርም ፋብሪካው ተለዋጭ የኃይል አቅርቦትን ይጠቀማል፡፡ 1ሺህ ሰራተኞች ያሉት ናሽናል ሲሚንቶ፤ 2.1 ቢሊዮን ብር ካፒታል አለው፡፡ እጅግ ግዙፍና ዘመናዊ በመሆኑ ግቢውን ጎብኝቶ ለማጠናቀቅ ብዙ ሰዓት ፈጅቶብናል፡፡
የድሬደዋ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ
ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረችበት ዘመን በ1931 ዓ.ም የተቋቋመው የድሬደዋ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ፤ የ76 ዓመት የእድሜ ባለፀጋ ቢሆንም በተጋረጡበት ዘርፈ ብዙ ችግሮች የተነሳ በአሳዛኝ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡ ለ45 ዓመታት በውጭና በአገር ውስጥ የጨርቃጨርቅ ሙያ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ አቶ ፈቃደ ገ/ህይወት ፋብሪካው ስላለበት ሁኔታ ሲናገሩ እንባ ይተናነቃቸዋል፡፡ ድሬደዋ ጨርቃጨርቅ ለሌሎች ጨርቃጨርቅ ፋብሪካዎች እናትም አባትም ነው። የሚሉት አቶ ፈቃደ፤ በኃይል አጥረትና ሌሎች ችግሮች ፋብሪካው ለአደጋ መጋለጡን ይናገራሉ፡፡
በተለያየ ወቅት ጣሊያኖች. እንግሊዞች፣ ጀርመኖችና ጃፓኖች አገሮች አስተዳድረውታል፤ ከዚያ በኋላም በደርግ ዘመን በመንግስት ስር ይንቀሳቀስ የነበረ ሲሆን የሚሊተሪ የደንብ ልብሶችን ማምረት ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበር አቶ ፈቃደ ገልፀዋል፡፡ ከደርግ ውድቀት በኋላ በኢህአዴግ የመንግስት ይዞታዎችን ወደ ግል ማዞር በመጀመሩ እ.ኤ.አ በ2007 ወደ ግል ይዞታነት ተዛውሮ መስራት ጀመረ፡፡ ባለሀብቶቹ ሲረከቡት እጅግ በደካማ ይዞታ ላይ እንደነበር ሥራ አስኪያጁ ይናገራሉ፡፡ የፋብሪካው ማሽኖች የ50 እና 60 ዓመት እድሜ ያላቸው በመሆኑ፣ እንዲሁም ጥሬ ዕቃ አቅርቦት (ጥጥ) እጥረትና በኃይል መቆራረጥ ሳቢያ በፋብሪካው ላይ የህልውና አደጋ እያንዣበበት ነው ይላሉ፡፡ በሶስት ዓመታት ውስጥ ለ402 ቀናት መብራት አለማግኘቱን በመጥቀስ የተለያዩ ችግሮች ተደማምረው ምርታማነቱ እየቀነሰ የመጣው ፋብሪካው፤ የገንዘብ ብድሩን መክፈል እነዳቃተውና የወለዱም መጠን እየጨመረ መምጣቱን ስራ አስኪያጁ ይገልጻሉ፡፡ ይህንን የኃይል መቆራረጥ ችግር ፋብሪካው ለኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በማልከት ጉዳዩ ለጠ/ሚኒስትሩ ቀርቦ የብድር መክፈያ ጊዜው ለሁለት ዓመት ተራዝሞለታል፡፡ ፋብሪካውን ከውድቀት ለመታደግ ከ4 ጊዜ በላይ የብድር ማግኛ ፕሮፖዛሎችን ለልማት ባንክ ማቅረባቸውን ያስታወሱት ስራ አስኪያጁ፤ አንዳቸውም ምላሽ እንዳላገኙ ይናገራሉ፡፡ ፕሮፖዛሉ በዋናነት ትኩረት ያደረገው ያረጁ ማሽኖችን በአዲስ መተካት፣ ከአራት መቶ በላይ ተጨማሪ የሰው ኃይል መቅጠርና ድርጅቱን ምርታማ ማድረግ ላይ ነው ያሉት ስራ አስኪያጅ፤ ብድሩ ተገኝቶ ፕሮፖዛሉ ተግባራዊ ቢደረግ ኖሮ ፋብሪካው በየዓመቱ 29 ሚሊዮን ዶላር ምንዛሪ እንደሚያስገባ ተተንብዮ ነበር ብለዋል፡፡
ከልማት ባንክ የተጠየቀው ብድር ባይሳካም ሌላ ጥረት መደረጉን ሥራ አስኪያጁ ይናገራሉ፡፡
ህንድ ቦምቤይ ከሚገኝ አንድ ባለሀብት ጋር በጥምረት ለመስራት ስምምነት ላይ ተደርሶ ባለሀብቱ ማሽኖች ይዞ ለመምጣት ፍላጎት ማሳየቱን ጠቁመው ለዚህ ፕሮጀክት 30 ሚሊዮን ዶላር እና 1,200 ተጨማሪ ሰራተኞች እንደሚያስፈልጉም ገልፀዋል፡፡ እቅዱ ተሳክቶ ፋብሪካው ስራ ከጀመረም 80 በመቶ ምርት ለውጭ ገበያ እንደሚልክ ተጠቁሟል፡፡ ይህን ሁሉ ፈተና በጉያው ይዞ የሚንገታገተው ፋብሪካው፤ ባለፈው ዓመት ምርትን ኤክስፖርት በማድረግ ውጤታማ ከሆኑ 10 ፋብሪካዎች ሰባተኛ በመውጣት ተሸልሟል፡፡ ዘንድሮም 2 ሚሊዮን ዶላር ምንዛሪ ይጠበቅበታል፤ ይሁን እንጂ “በዚህ ሁሉ አጣብቂኝ ውስጥ ሆኖ ሁለት ሚሊዮን ዶላር ምንዛሪ ማስገኘት ህልም ነው፤ ያልዘራነውን አናጭድም” ሲሉ ስራ አስኪያጅ ሀዘናቸውን ገልፀዋል፡፡
ፋብሪካውን ከውድቀት ለመታደግ በተለያዩ ጊዜያት ለመንግስት አካላት አቤት ማለታቸውን ጠቁመው፤ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትም ፋብሪካውን እንደጎበኙ ገልፀዋል፡፡ በተወካዮች ም/ቤት የኢንዱስትሪ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ የፕራይቬታይዜሽን የመንግስት የልማት ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ኤጀንሲ ኃላፊዎች እና ሌሎችም ጉብኝት አድርገው ችግሩን ቢረዱም እስካሁን የተገኘ መፍትሄ የለም ብለዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ የኢንዱስትሪውን ዘርፍ የስድስት ወራት እንቅስቃሴ አስመልክተው ለጋዜጠኞች ማብራሪያ የሰጡት የኢንዱስሪ ሚኒስትር አቶ አህመድ አብተው፤ ፋብሪካው ወደ ግል ሲዛወር የአገር ውስጥ ባለሀብቶች የመንግስት ንብረት ሲገዙ የሚደረገው ማበረታቻ ሁሉ እንደተሟላለት ገልፀው፤ ፋብሪካው 35 በመቶ ቀድሞ ከፍሎ 65 በመቶውን በአምስት አመት ውስጥ መክፈል ሲገባው ሳይከፍል በመቅረቱ፣ እንዲሁም ለጥጥ መግዣ ከልማት ባንክ የተበደረውን ገንዘብ ባለመክፈሉ ሌላ ብድር የማይፈቅድለት መሆኑን ገልፀው በማገገሚያ ግዜ ውስጥ ገብቶ በሌሎች አማራጮች የሚቀጥልበት ሁኔታ እየተፈለገ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ፋብሪካው 1,500 ሰራተኞች ይዞ በአጣብቂኝ ውስጥ የሚገኝ ሲሆን ሰራተኞቹም “ተስፋ ቆርጠናል፤ ጥረታችን ጡረታችንን ለማስከበር ነው” ብለዋል፡፡
ድሬደዋ የምግብ ኮምፕሌክስ
ድሬደዋ የምግብ ፋብሪካ በ1988 ዓ.ም በ55 ሚሊዮን ብር ካፒታል በ300 ሰራተኞች ሰራ እንደጀመረ የፋብሪካው ስራ አስኪያጅ አቶ ካህሉ ንጉስ ይገልፃሉ፡፡ ፋብሪካው በ1996 ዓ.ም በ1997፣በ1998 ዓ.ም በአጠቃላይ በ70.2 ሚሊዮን ብር የተለያዩ ማስፋፊያዎችን አድርጓል፡፡ እ.ኤ.አ የካቲት 11 ቀን 2011 ወደ ግል ይዞታነት የተዛወረው ፋብሪካው፤ በአገር አቀፍ ደረጃ ተወዳጅ የሆነውን እና 80 በመቶ አዲስ አበባ የሚሸጠውን ቬራ ፓስታን በማምረት ይታወቃል፡፡ ወደ ግል ይዞታነት ከተዛወረ በኋላ ፋብሪካው ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ችግሮቹን መለየትና የሰራተኞቹን ጥያቄ መመለስ ቅድሚያ እንደተሰጠው የጠቆሙት ዋና ስራ አስኪያጁ፤ 175% የደሞዝ ጭማሪና የመዋቅር ለውጥ መደረጉን አብራርተዋል፡፡
ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት በቀን ሁለት ሺህ ኩንታል ዱቄት፣ 600 ኩንታል ፓስታ፣ እንዲሁም 90 ኩንታል ዳቦ ያመርታል፡፡ በፊት ሙሉ በሙሉ የአውስትራሊያ ስንዴን በግብአትነት ይጠቀም የነበረው ፋብሪካው፤ በአሁኑ ወቅት በ2004 ዓ.ም ባሌ ውስጥ 6 የተደራጁ ማህበራት የሚያመርቱትን የአገር ውስጥ ስንዴ በግብአትነት ይጠቀማል፡፡ በቅርቡም በ6.6 ሚሊዮን ብር አጠቃላይ የፋብሪካው የጥገና ስራ መከናወኑ ተገልጿል፡፡ ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት ለሀረር፣ ለድሬደዋና ለሀረማያ ዩኒቨርሲቲዎች በቋሚነት ዳቦ ያቀርባል፡፡ 165 ሚሊዮን ብር ካፒታል ያለው ድሬደዋ የምግብ ኮምፕሌክስ፤ በ2012 ኢንግላንድ ከሚገኝ ድርጅት በጥራት፣ በቅንጅታዊ አሰራር፣ በምርት አቅርቦት፣ ሰው ኃይልን በአግባቡ በመጠቀም እና ወጪን በመቀነስ፣ ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡
ሆኖም የሃይል መቆራረጥ ለፋብካው ፈተና እንደሆነበት ተገልጿል፡፡ በቀን ሁለትና ሶስት ጊዜ የሚቆራረጠው መብራት ለስራቸው እንቅፋት ሆኖብናል ያሉት አቶ ካህሱ፤ “ወዴት ሄደን አቤት እንደምንል ግራ ገብቶናል” ይላሉ፡፡ የሃይል መቆራረጡ ከመልካም አስተዳደር ችግር ጋር የተገናኘ ነው የሚሉት ሥራ አስኪያጁ፤ ለከተማ አስተዳደሩ ፀረ ሙስና ቢሮ አመልክተው ጉዳዩን እየተከታተለው እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ እስከዚያው ግን በመብራት መቆራረጥ በቀን 200ሺህ ብር ኪሳራ እየደረሰባቸው እንደሆነ ገልፀዋል፡፡ የድሬደዋ ከተማ ከንቲባ አቶ አሳድ ዚያድ በበኩላቸው፤ የፋብሪካው የኃይል መቆራረጥ ከመልካም አስተዳደር ችግር የመጣ መሆኑን አምነው ክትትል እየተደረገበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የጥሬ ዕቃ አቅርቦት የድሬደዋ የምግብ ፋብሪካ ሌላው ፈተና ነው፡፡ በህገ-ወጥ መንገድ ከውጭ የሚገቡ ፓስታና መሰል ምርቶች በፋብሪካው ላይ የተጋረጡ ችግሮች እንደሆኑ ተነግሯል፡፡ እነዚህ ችግሮች ከተስተካከሉና የኃይል መቋረጥ መፍትሄ ካገኘ ዘንድሮ አምስት ሺህ ኩንታል ፓስታ፣ አምስት ሺህ ኩንታል መካሮኒና 10 ሺህ ብስኩቶችን ወደ ውጭ ኤክስፖርት ለማድረግ ታቅዷል፡፡ “ይሁን እንጂ ፋብሪካው ጥራት ያለውና ከኬሚካል የፀዳ ግብአት እየተጠቀመ፣ ለሚያመርተው ምርት ታክስ እየከፈለ ሌሎች ህገ-ወጥ ነጋዴዎች ግን በህገ-ወጥ መንገድ ታክስ ሳይከፍሉ ፓስታና መካሮኒዎችን ከእኛ እኩልና ከእኛ በላይ በሆነ ዋጋ ይሸጣሉ” ያሉት አቶ ካህሱ፤ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ህገ-ወጦችን እንዲያስቆም፤ ፌደራል መንግስት ኃይል አቅርቦት ላይ አሻጥር የሚሰሩ አካላትን ትኩረት ሰጥቶ እንዲከታተል ጥሪ አቅርበዋል፡፡   
የፋብሪካው ሰራተኞች በቂ የደሞዝ ጭማሪና እድገት እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ የ175% የደሞዝ ጭማሪ መደረጉን የገለፁት ሥራ አስኪያጁ፤ ለአብዛኞቹ ብዙ ልምድ ያላቸው ሠራተኞች የትምህርት ደረጃቸው ባይፈቅድም እንዳደላደሉ ገልፀው፤ መዋቅሩ በትምህርት ደረጃ ይሰራ ቢባል 60 በመቶው ሰራተኛ ተንሳፋፊ ይሆን እንደነበር ተናግረዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ መታየት ያለበት ካለ በቀጣይ የሚታይ ይሆናል ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ አህመድ አብተው ፋብሪካዎች ላይ ችግር እየፈጠረ ስላለው የሀይል መቆራረጥ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ ብዙ ፋብሪካዎች ያሉት አዲስ አበባ በመሆኑ መብራት ሀይል ቅድሚያ ሰጥቶ የትራንስሚሽንና የዲስትሪቢውሽን መስመሮችን በማደስ፣ በማጠናከርና መስመሮችን በመለየት ስራ ላይ እየተጋ መሆኑን ገልፀው፤ በክልሎችም ተመሳሳይ ስራ ለመስራት መታቀዱን ተናግረዋል፡፡
የመኢሶ ዳዋሌ የባቡር ሀዲድ ዝርጋታ
ድሬዳዋ ከተማን ወደ ቀኝ ትቶ በመልካ ጀብዱ ወደ ጅቡቲ የሚያመራው የመኢሶ ደዋሌ የባቡር ሀዲድ ዝርጋታ ስራም በፍጥነት እየተከናወነ እንደሆነ ተመልክተናል፡፡ 346 ኪ.ሜ የሚሸፍነው  ፕሮጀክቱ፤ ከአጠቃላይ ስራው 35 በመቶው መጠናቀቁን የመኢሶ ደዋሌ የባቡር መንገድ ፕሮጀክት ማናጀር ኢ/ር መኮንን ጌታቸው በጉብኝቱ ወቅት ተናግረዋል፡፡ 1.4 ቢሊዮን ዶላር የተበጀለት ይህ ፕሮጀክት፤ ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ቀጥሎ ትልቁ ፕሮጀክት እንደሆነ ኢ/ር መኮንን ተናግረዋል፡፡ ስራው ከመጠናቀቁ በፊት 37 ኪ.ሜትር ለሙከራ እንደሚከፈት የገለፁት ኢ/ሩ፤ ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ ባቡር በሚያልፍባቸው ቦታዎች ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ መነቃቃት ይፈጠራል ብለዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ጅቡቲ 676 ኪ.ሜትር ርዝመት ያለው የባቡር መስመር እየተዘረጋ ሲሆን አጠቃላይ 3 ቢሊዮን ዶላር እንደተመደበም ተገልጿል፡፡ 676 ኪ.ሜትሩ የባቡር መንገድ በተለየዩ የባቡር መንገድ ስራ ላይ በተሰማሩ ድርጅቶች እየተሰራም እንደሆነ ታውቋል፡፡

    ብዙዎቹ የግጥም መጽሐፍት ሸንበቆ ናቸው፡፡ ሲታዩ ሸንኮራ ይምሰሉ እንጂ ሲከፈቱ ኦና መሆናቸውን ደጋግመን ተወያይተናል፡፡ በዚህ ባሳለፍነው ወር እንኳ ቢያንስ ሶስት ጊዜ ያህል በሬድዮ “ምን ይሻላል?” በሚል አውርተናል፡፡ ማውራቱ አይከፋም!... የምንናገረው እውነት ከሆነ፤ እውነት አርነት ያመጣል፤ ቃልም ህይወትን ያመጣል፡፡ እንደ ክርስቶስ ቃል፣ ቃላችን መንፈስና ህይወት ባይሆንም እውነት ካለበት ግን፣ በዚያ ቀንበር ሊሰበር ይችላል፡፡
ይህ የቃል ብዛት ደግሞ ነገ በክበቡ ሰፈር የሚነድድ ችቦ፣ ለውጥ የሚያመጣ ብርሃን ይፈጥራል፡፡ ማጠቃለያ ባንሰጥበት እንኳ የኛ ዘመን ችግር ሳያምጡ መውለድ ይመስለኛል፡፡ ይህ ደግሞ ዓለም አቀፋዊ መልክ ነው። ያ ባይሆን ኖሮ እስከዛሬ ድረስ የሚፃፉት የግጥም ማስተማሪያ መጽሐፍት በዋቢነት የሚያነሱዋቸው ፅሑፎች የሼክስፒር ሶኔቶች፣ የእነድራይደን፣ የእነዲክሰን፣ የእነሚልተን ወዘተ ብቻ ባልሆኑ ነበር፡፡
ድሮ ለጥበብ ማማጥ፣ ለእንጀራ ከማማጥ ይጠና ነበርና አንድ ሰው ክበቡን በጉሹ ለገበያ አያወጣም፤ ድፍድፉ እስኪፈላ ይጠብቃል፡፡ ምክንያቱም ወደ ራሱ ብቻ ሳይሆን ወደ ህዝቡ ያያል፡፡ ግና ይህ ሁሉ ቢሆንም እኛ በራሳችን ጊዜ የቻልነውን ያህል ለለውጡ ብንተጋ፣ ነውጡ የሚፈጥረው ውበት፣ የሚያፈልቀው ምንጭ አለ፡፡ የምንመዝዘው ባለሁለት ስለት ሰይፍ ራሳችንንም ሌሎችንም እየገረዘ፣ ውበት በድንኳናችን ቬሎ ታጠልቃለች፣ በነፍሳችን ትሞሸራለች ብዬ አምናለሁ፡፡
ለዚህም ይመስለኛል በዚህ ሁሉ ፍራሽና ገለባ መሃል፣ ወፈር ወፈር ያሉ ፍሬዎች ተጠብሰው የሚሸቱ እሸቶች፣ በመዓዛቸው የሚያማልሉ ውበቶች ብቅ የሚሉት፡፡
ከሁለት ወር በፊት የወጣው የሲሳይ ታደሰ “ለፍቅራችሁ” የተሰኘ የግጥም መጽሐፍ ጥሩ ተስፋ እሚያጭር ነው፡፡ ጠበቅ ያሉ ሀሳቦች አራት ማዕዘን አተያዮች ይንፀባረቁበታል፡፡ ግጥም አራት አቅጣጫ ሲያይ ሸጋ ነው፤ እንደምሁራኑ እምነት፡፡ ለዚህ ደግም የነርሱ እምነት ብቻ አይጠበቅም፤ ብቻችንን ማመን እንችላለን፡፡ ግጥም አንዱ ትልቁ ነገር፤ እንደሽንኩርት ገላ እየላጡ አዳዲስ መልክ በማሳየት ተዓምር ማሰኘት ነው፡፡ ሲሳይ እንደዚያ ነው፡፡ ሥራው ላይ እንደሞቀኝ እንዳልፅፍበት ከኑሮ ጋር ያለው ነፃ ትግል ፋታ አይሰጥም፡፡ ሥራና እንጀራ ውበትን ከአፍ ይነጥቁ የለ!... “አፈር ይበላ!” እንዳንል ትርጉሙ ሞት ነው፤ ሞት ደግሞ ማንን ጠቀመ?... ሲሳይ እንዲህ ይላል? “ህዝብ አዳም ሰካራም” በሚል ግጥሙ፡-  
እንኳን ተጨልጦ፣
እንኳን ተገልብጦ፣
ጠብታው የሚያሰክር የሚያዞር ጢንቢራ፣
እግዜር ጠመኩ ይበል ኑሮ ይሉት ቢራ፡፡
እንዲያውም ቢራ አድርጎ አለሰለሰው እንጂ ደረቅ ጠጅ ሳይሆን ይቀራል? ወይም ካቲካላ? … ሲሳይ እግዜር ጠመቀው ይበል እንጂ የጠመቁልንማ ራሳችን የፈጠርናቸው ጋኖች ናቸው፡፡ ጋኑ ውስጥ ግን ብቅልና ጌሾ ማን ከተተ? የሚለውን ጥያቄ እንደየ ዐውዶቻችን እንመልሳቸው፡፡ ብቻ ሲሳይ ጥሩ ብሏል፡፡ ኑሮው አስክሮናል፡፡
በመጽሐፍ ቅዱስ አይን ውስጥ ግንድ እያገላበጡ ስለሌሎች ስንጥር ማውራትን የሚመለከተውን ሀሳብ ሲሳይ “ወንፊትና ሳቁ!” ብሎ እንዲህ አስቀምጦታል፡-
ከእለታት አንድ ቀን ከዘመናት በፊት፣
የመርፌን ተፈጥሮ - አስተዋለው ወንፊት፡፡
እናም አይቶ - አይቶ --
ቆይቶ -- ቆይቶ
ብዙ ተመልክቶ ---
በመርፌው ጭራ ጫፍ - የተሰነጠቀ፣
ክር ማስገቢያ አይቶ - ስለተደነቀ፣
“ቀዳዳ አለብህ”
አለና ወንፊቱ - በመርፌ ላይ ሳቀ፡፡
እግዜር ያሳያችሁ! ወንፊት ያን ሺህ ቀዳዳ ይዞ፣ በመርፌ አንድ ቀዳዳ ሲስቅ ማሳየት ጥሩ ዕይታ ነው፡፡ እኛ መች አየነው!... ገጣሚ ግን እንዲህ ማየት አለበት። ይህ ደግሞ ከሰዎች አፍ እየተለቀመ የመጨረሻዎቹ ሁለት ስንኞች ላይ እንደሚረጭ ስኳር አይደለም፡፡ ሀሳቡ ከላይ እስከታች የተያያዘና ሙሉ ነው፡፡
ይሁንና መጨረሻው ላይ “ቀዳዳ አለብህ” የሚለውን ዝርዝር ሲያይ እርቃን ማሳየት አይጠበቅበትም ነበር። ክር ማስገቢያ ማለት ቀዳዳ ነዋ!... “የልብ አይን” የሚለው የሲሳይ ሌላው ግጥም ስለፍቅር አጥር ወይም ቅጥር አፍራሽነት ያሳያል፡፡
… መች እንደሆን እንጃ
ብቻ ከዛሬው ቀን - ከዚህ ዕለት በፊት፣
ፊትሽ ተቀምጬ - ተቀምጠሸ ከኔ ፊት፣
በእንጭጭ ምልከታ - እያየሁሽ ባይኔ፣
“ጨረቃ መሳይ ነሽ” - ብዬሽ ከሆነ ያኔ፣
ባክሽ ይቅር በይኝ - ዋሽቼሽ ነው እኔ!
ምናልባትም ትናንትና …
እይታዬ - ተጥበርብሮ፣
አብጄና አቅሌ ዞሮ ..
ይሆን እንጂ ለደቂቃ፣
ኧረ አንቺሽ ምንሽም - አይመስልም ጨረቃ
እናም እርሺው ባክሽ - አምልጦኝ ነው በቃ!
አሁንማ ገብቶኝ - በቅጥ ሳስተውለው፣
ለካስ ጨረቃ ናት - አንችን የምትመስለው፡፡
ፍቅር ልክ እያጣ ሲሄድ፣ ማማው እየናጠጠ ወደላይ ከፍ ሲል፣ እንዲህ ነው፡፡ ደግሞ እውነቱን ነው፤ የርሱ ውብ ሸጋ፣ የርሱ የዓለም ብርቅ እንዴት ሆና ነው በተውሶ ቀለም ከተዋበች ጨረቃ ጋር የምትመሳሰል? እግዜር እጁን ታጥቦ የሠራት ውብ! ያኔ ተሣሥቶ፣ ወይም የነዋይ ደደበን “ጨረቃ” የሚል ዘፈን ሠምቶ ነው? … ስለዚህ ይቅርታ! ብሏል፡፡ ደስ ይላል!
“ሥጋት” የሚል ርዕስ የተሰጣት አጭሯ የሲሳይ ታደሰ ግጥም እንዲህ ትላለች፡-
ንጋት ኋላ ሸሽቷል …
ከፊት ደግሞ መሽቷል፡፡
እስቲ ምርኩዝ ላብጅ - ልቤ ጠረጠረ፣
የ’ርጅና ነው ተራው - ማደግሞ ቀረ፡፡
ይህ ግጥም አንዳች ምስጢራዊ ነገር ያለው ይመሥላል፡፡ ተምሳሌታዊም ነው፡፡ ሕይወት ጉዞ ነው። ሲወለዱ ይነጋል፤ ሲሞቱ ይመሻል፡፡ ሲወለዱ በደረት የተሳቡትን ያህል፣ ሲያረጁ እንደ ደጋን መጉበጥ አለ። ያኔ ደግሞ ምርኩዝ ያስፈልጋል፡፡ እርጅናው ግን የቱ ነው? … የልብ ወይስ የአካል? በሞቀ ደም የተወጠረው ጉንጭ፣ በቅዝቃዜ በረዶ ሲሸበሸብ ይሆን? ወይስ አንኳር ሕልም እንደ ደመና ሊበተን?
የገጣሚው አንዱ ጥሩ ጐን ለሕይወት ያለው ትኩረት ነው፡፡ ሕይወት ውስጥ ብዙ ልቃቂቶች ቢጠቀለሉም፣ በየቀለማቸው እየፈተለና ከግራ-ቀኝ እየወረወረ፣ ሊሸርባቸው ሞክሯል፡፡ “ክፉ ፍርሃት” በሚለው ግጥሙ ቅኝታችንን እንቋጭ፡፡  
ጨለማ እኮ …
በድቅድቁ ምሽቱ ላይ …
ጥቁር ሌሊት መቀለሙ፣
ፅልመቱ ውስጥ ተስፋ አርግዞ
ሊነጋ ነው መጨለሙ፡፡
ብርሃን ግን …
ካድማሱ ጥግ ብቅ ብሎ
ፀሃይን ክንፉን ሚዘረጋው፣
የመከነ ተስፋ ይዞ
ሊጨልም ነው የሚነጋው፡፡

Published in ጥበብ

     ዳንኤል፣ ጤነኛ፣ ለቅርጫት ኳስ ጨዋታ ተስማሚ ቁመና ያለው፣ በ30ዎቹ የዕድሜ አጋማሽ የሚገኝ ጎልማሳ ነው፡፡ አንድ ቀን ከሰዓት በኋላ ጓደኞቹ፣ በተሟሟቀ የቅርጫት ኳስ ጨዋታ መኻል በቁልምጫ ዳኒ፣ ”ትከሻህ ላይ ያለው ጥቁር ነገር ምንድነው?” በማለት የጠየቁትን ዳንኤል በፍፁም አይዘነጋውም፡፡
ከጥቂት ሳምንታት በኋላ ያ ጥቁር ነገር ምን እንደሆነ ለማወቅ ሲመረመር፣ ሜላኖማ (melanoma) የተባለ ኃይለኛ የቆዳ ካንሰር በሽታ መሆኑ ተነገረው፡፡ ሐኪሞቹ ሞህ (Mohs’) በተባለ ማይክሮግራፊክ ቀዶ ህክምና በካንሰር የተጠቁትን ኅብረ-ህዋሳት (ሴሎች) አስወገዱለት። ነገር ግን ሁለት ወር ያህል እንደቆየ ካንሰሩ በአካሉ ተሰራጭቶ፣ ብብቱ ስር ያበጠ የነጭ ደም ሴሎች ቋጠሮ (እባጭ) አስተዋለ፡፡ ሐኪሞቹ ለበሽታው ኬሞቴራፒ (chemotherapy) የተባለ የካንሰር መድኃኒትና ሌሎች ኬሚካሎች ቢሰጡም፣ በሽታውን ግን መግታት አልቻሉም፡፡
እንዲያውም ሐኪሞቹ ለሚሰጡት ህክምና “አሻፈረኝ አልበገርም” ያለው በሽታ ይብስ ተስፋፍቶ ወደ ሳንባው ተዛመተ፡፡ በዚህ ጊዜ ሐኪሞቹ የዳንኤልን የበሽታ መከላከያ አቅም በማነቃቃትና ከፍ በማድረግ የካንሰርን ዕጢ እንዲወጋ ኢንተርፌሮን አልፋ (Interferon-alpha) የተባለ ህክምና ጀመሩለት፡፡ ነገር ግን ዳንኤል ህክምናው በጣም ስለከበደውና ስላመመው ከመጀመሪያ ቀን በኋላ ሌላ ህክምና መቀበል አቃተውና ቆመ፡፡
“ዳንኤልን ለመጀመሪያ ጊዜ ያገኘሁት የካንሰር ህክምናውን ከጀመረ ከአንድ ዓመት በኋላ ነው። በዚያን ጊዜ የቆዳው ካንሰር ከሳንባው አልፎ ጉበቱንም ጀምሮት ስለነበር፤ በሽታው በፍጥነት እየተባባሰበትና ጤንነቱ እያሽቆለቆለ ነበር፡፡ የምግብ ፍላጎቱ በጣም ትንሽ ስለነበር ምግብ አይበላም። በዚህ የተነሳ ክብደቱ 16 ኪሎ ያህል ቀንሶ ነበር፡፡ ክብደቱን መሸከም ስላቃተው የሚንቀሳቀሰው እንኳ ከዘራ እተደገፈ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ቅርጫት ኳስ መጫወት ቀርቶ ሥራ እንኳ መሥራት አይችልም” በማለት የዳንኤልን አስገራሚ የፈውስ ታሪክ በፌብሩዋሪ 2014 ዲስከቨሪ መፅሄት ላይ ያቀረቡት በቫይቪሚያ ደሴት የኑትሮን ቴራፒ ተቋም የጨረር ህክምና ባለሙያ ሚ/ር ጀምስ ዌልሽ ናቸው፡፡
“አሁን ካንሰሩ ወደ አጥንቱ በመዛመቱ፣ በቀኝ ታፋው ላይ ከፍተኛ ስቃይ ያለው ህመም እየተሰማው ነው፡፡
በዚህ ጊዜ ዳንኤል በህይወት የሚኖረው ጥቂት ወራቶች ብቻ ቢሆን ነው ብዬ ስላሰብኩ፣ ስቃዩን ለማስታገስ ያህል በተለይ በታፋው ላይ ብቻ ያነጣጠረ በጣም የአጭር ጊዜ የጨረር ህክምና (ራዲየሽን ትራፒ) ሰጠሁት፡፡ እንደቀዶ ህክምና ሁሉ የጨረር ህክምናም የውስጥ አካል ህክምና ብቻ ነው፡፡ ኬሞቴራፒና ሌሎች በጥንቃቄ የሚሰጡ የመድኃኒትና ኬሚካሎች ህክምናዎች ግን በሽታው በተከሰተበት ስፍራ ብቻ ሳይሆን በአካባቢውም ተፅዕኖ መፍጠር ይችላሉ፡፡ የጨረር ህክምና እንደዚያ አይደለም፡፡ ተፅዕኖ የሚፈጥረው፤ ጨረሩ ባረፈበት የተለየ ስፍራ ላይ ብቻ ነው፡፡
“ዳንኤልን ህመሙ ካልተሻለው እንደገና ለመታየት ከሳምንት በኋላ እንዲመጣ ወይም በስልክ ብቻ እንደማናግረው ቀጠሮ ሰጥቼ ሸኘሁት፡፡ ዳንኤል በቀጠሮው መሰረት ሲመጣ የታፋው ስቃይ በጣም ተሽሎት ነበር፡፡ የጨረር ህክምናው ሰራ ማለት ነው። ይሁን እንጂ መራመድ ካልቻለ በዚያው ይቀራል እንጂ ወደዚህ ክሊኒክ አይመጣም በሚል እሳቤ፣ ከሶስት ወር በኋላ እንዲመጣ ቀጠርኩት፡፡
“የታፋው ስቃይና ህመም በመጥፋቱ በጣም ብደሰትና ብገረምም በተለያየ ሞገድ የካንሰር ሴሎቹን ለመግደል የተደረገለት የራዲዮ ቴራፒ ህክምና ህመሙን ቢያስታግስለት እንጂ በሽታውን ከስሩ መንግሎ እንደማያጠፋና ምንም ለውጥ እንደማያመጣ ሳስበው ድካሙ ሁሉ ከንቱ ሆኖ ተሰማኝ፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል፤ ዳንኤልን ዳግመኛ አየዋለሁ ብዬ አልጠበኩም ነበር፡፡   
“ነገር ግን፣ ከሶስት ወር በኋላ ዳንኤል መጥቶ ሳየው በጣም ተገረምኩ፤ በጣም ተደሰትኩ፡፡ የታፋ ህመሙ በፍፁም በመጥፋቱ የሚወስዳቸውን የህመም ማስታገሻ መድኃኒቶች አቁሟል፡፡ ፊቱ ላይ የበሽተኝነትና የመገርጣት ሳይሆን የጤንነት ስሜት ይነበብ ነበር፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ በጣም የገረጣውና የኮሰመነው የበሽተኛ ሰውነቱ አገግሞ አራት ተኩል ያህል ኪሎ ጨምሯል፡፡ በአጠቃላይ ከጥቂት ወራት በፊት ከነበረበት ሁኔታ በጣም ተሽሎታል፡፡
“የዚያኑ ‘ለታ፣ ሲቲ ስካን እንዲነሳ ፕሮግራም ያዝኩለት፡፡ ነገር ግን ምንም አይነት አዲስ በሽታ ቢገኝበት ምንም ማድረግ እንደማይቻልና አዲስ ህክምና እንደማይደረግለት አስጠነቀቅሁት፡፡ እንደዚያም ብለው ዳንኤል ግን ሲቲ ስካኑን መነሳት ፈለገ፡፡ ወደ ራዲዮሎጂ ክፍል ወሰድኩትና ፊልሙን ከተነሳ በኋላ አብረን እንድናየውና እንድንነጋገርበት ወደ እኔ ክፍል ጠራሁት፡፡
“ይኼኔ ነው እንግዲህ ነገሮች ድንገት የበለጠ አስደሳች መሆን የጀመሩት፡፡ ከአንድ ሰዓት በኋላ ዳንኤል የተነሳውን ለማየት ወደ ራዲዮሎጂው ክፍል ሄድኩ፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ በሳንባውም ሆነ በጉበቱ ላይ ካንሰር እንደነበረ የሚሳይ አንዳችም ምልክት አጣሁበት፡፡ አጥንቶቹ ኖርማል ናቸው፤ ብብቱ ስርም ምንም ያበጠ ነገር (ዕጢ) አይታይም። ይህ ፊልም በፍፁም የዳንኤል ሊሆን አይችልም፤ ምልክት ሲደረግባቸው ተደበላልቀው ይሆናል፤ ስለዚህ የተሳሳተ ነው የሚል ስሜት ተሰማኝ። ነገር ግን በጣም አቅርቤ ስመለከተው፣ በአንድ ወቅት ካንሰሩ በነበረበት ስፍራ፣ የጨረር ህክምና (ራዲዬሽን) ሲደረግለት የተፈጠረ በጣም ትንሽ “የራዲዮግራፊክ ጭረት” አየሁ፡፡ ነገር ግን አንዳችም የካንሰር ዕጢ በቦታው አልነበረም፡፡ ታፋ ላይ የተደረገ የጨረር ህክምና በጣም ሩቅ በሆኑት ሳንባ፣ ጉበትና ብብት ላይ ተፅዕኖ ስለማይፈጥር፣ የስካኑን ፊልም ወደ ቢሮዬ አምጥቼ ለዳንኤል አሳየሁ፤ ሌላ ህክምና አድርጎ እንደሆነም ጠየቅሁት፡፡ እሱም የህመም ማስታገሻ መድኃኒቶቹን ከማቆሙ በስተቀር አንዳችም ህክምና እንዳላደረገ ነገረኝ፡፡
“ዳንኤል በጥቂት ወራት ውስጥ እንዲመለስ ቀጥሬው በትልቅ ፈገግታ ወደቤቱ ተመለሰ፡፡ በዚያች ቀን በምድር ላይ እጅግ ደስተኛ ሰው እንደሆንኩ አስቤ ነበር፡፡ ነገር ግን ተሳስቼያለሁ፡፡ እኔ በህይወት ያለሁ ሁለተኛው ደስተኛ ሰው ነበርኩ፡፡ በቀጠሮው መሰረት ዳንኤል ከሶስት ወር በኋላ ሲመለስ፣ አዲስ ሰው መስሎ ነበር የመጣው፡፡ ከበፊቱ ሁለት ኪሎ ተኩል ያህል ክብደት ጨምሮ ጡንቻዎቹ ስለፈረጠሙ ወደ ስራ ከመመለሱም በላይ ከረዥም ጊዜ ቆይታ በኋላ ቅርጫት ኳስ ትንሽ ትንሽ መጫወት ጀምሮ ነበር፡፡ ለሁለት ዓመት ተከታታይ ምርመራ ካደረገና የሲቲ ስካኑ ውጤትም ንፁህ መሆኑ ከተረጋገጠ በኋላ የሚሰራው ሥራና የሚመራው ህይወት ስላለው፣ ሌላ ቀጠሮ ሳልሰጠው ቀረሁ። ይሆናል ተብሎ የተፈራውን ግምት ሁሉ አሸንፎ እነሆ ዳንኤል ከያዘው የካንሰር ህመም ተፈውሷል። ይህ የሆነው የዛሬ 12 ዓመት ገደማ ነበር፡፡ ዳንኤል በምን ሁኔታ ተፈወሰ? ማለታችሁ አይቀርም። የጨረር ህክምና ባለሙያውም ሆኑ ሌሎች ሐኪሞችና ተመራማሪዎች እንዴት እንደተፈወሰ በፍፁም አያውቁም፡፡ ጀምስ ዌልሽ የፈውሱን ምስጢር ባያውቁም፣ “እውነቴን ነው የምላችሁ፤ የዳንኤልን ተአምራዊ ፈውስ አምኜ ተቀብያለሁ። ነገር ግን የፈጠረብኝ ግራ መጋባት አሁንም ድረስ እንደቀጠለ ነው” ብለዋል፡፡ ምክንያቱም የዳንኤል ፈውስ የመጀመሪያ ገጠመኝ ከመሆኑም በላይ እጅግ አስገራሚ ክስተት ነው፡፡ ከአካባቢው ርቆ የሚገኝ የካንሰር በሽታን ማዳን፣ አልፎ አልፎ የሚያጋጥምና ለማብራራት የሚያዳግት ለማብራራት የሚያዳግት ግልፅ ያልሆነ (abscopal phenomenon) ክስተት ነው ብለዋል-ዌልሽ፡፡
“ዕድሜ ልክ ለሚያሰቃዩ ሰዎች የዚህ ዓይነት ህክምና ለመስጠት ውጤቱን አንዴ ማየት በቂ ሊሆን ይችላል፡፡ የእኔም ሙከራ፣ በትክክል ዳንኤል ላይ የተፈጠረውን ዓይነት ፈውስ መፍጠር ስለሆነ፤ በሌሎች በሽተኞችም ላይ ቢሞከር ምናልባት ሊሰራ ይችል ይሆናል፡፡
አብስኮፓል የሚለው ከላቲንና ከግሪክ ቃላት የተገኘ ነው፡፡ ትርጉሙም “ከእይታ፣ ከግብ ወይም ከዓላማ የራቀ” ማለት ሲሆን፣ እ.ኤ.አ በ1953፣ በአንድ የውስጥ አካል ላይ የተደረገ የጨረር ህክምና ከዚያ ርቆ በሚገኝ የአካል ክፍል ላይ ተፅዕኖ መፍጠሩን ተገንዝበው ቃሉን ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሙት አር ኤች ሞል (R.H mole) የተባሉት ሐኪም ናቸው፡፡
ይህ ፈውስ አብዛኛውን ጊዜ ከራዲዮቴራፒ ጋር የተሳሰረ ቢሆንም በሌሎች cryotherapy፣ hyperthermia በተባሉ የውስጥ አካል ካንሰር ህክምናዎች ላይ እንደሚሰራ ተስተውሏል፡፡ ህክምናው እንዴት እንደሚያድን ግን በፍፁም የሚታወቅ ነገር የለም፡፡       

Published in ዋናው ጤና

ማነው ሲምካርድ? ማነው ቀፎው? (ሁለቱም ከሌሉ አንደውልም!)

    አንዳንድ የአፍሪካ አምባገነን የስልጣን ሱሰኞች ትዝ ሲሉኝ ማንን እያስታወስኩ እንደምፅናና ታውቃላችሁ? የአውራውን ፓርቲ ሹማምንት! ቧልት እንዳይመስላችሁ---ከልቤ ነው፡፡ እርግጥ ነው ፓርቲው ኢትዮጵያን መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገራት ከማሰለፉ በፊት ከስልጣን የመልቀቅ ሃሳብ እንደሌለው በግልፅ አስታውቋል፡፡ ነገርዬው እውነት ይሁንም ሃሰት ፓርቲው እንጂ አባላቱ ስልጣን ላይ የመክረም ሃሳብ እንደሌላቸው በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ በተለይ ደግሞ የቀድሞዎቹ አንጋፋ ታጋዮች፡፡ ፓርቲው ስልጣን ላይ እስካለ ድረስ መሪዎቹ ማንም ቢሆኑ አንድ ናቸው ልትሉኝ ትችላላችሁ (“ድስት ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም”እንደማለት) እውነት ብላችኋል፡፡ እኔ ደግሞ ከቅኝ ግዛት ነጻነት ማግስት ጀምሮ ዚምባቡዌን እንደ ግል ንብረታቸው እየተቆጣጠሩ በቅርቡ 80 ምናምነኛ ዓመት የልደት በዓላቸውን ያከበሩትን ሮበርት ሙጋቤን ለንፅፅር አመጣላችኋለሁ፡፡ በነገራችሁ ላይ ሙጋቤ ልደታቸውን ሲያከብሩ   ስልጣን የመልቀቅ ሃሳብ እንዳላቸው ተጠይቀው “ፓርቲዬን ለማን ትቼ!” ሲሉ ከስልጣን የሚገላግላቸው ሞት ብቻ እንደሆነ በተዘዋዋሪ ተናግረዋል፡፡
ከጥቂት ዓመታት በፊትም አንድ የውጭ ጋዜጠኛ “ሚስተር ፕሬዚዳንት የዚምቧቡዌን ህዝብ መቼ ነው የሚሰናበቱት?” ሲል ይጠይቃቸዋል (መቼ ነው ከስልጣን የሚለቁት ለማለት ፈልጎ ነው) አጅሬው ሙጋቤ ምን ቢሉ ጥሩ ነው? “ህዝቡ ወዴት ሊሄድ ነው?” ብለው አረፉት፡፡ ህዝቡ እስካለ ድረስ መሰነባበት የለም ማለታቸው እኮ ነው፡፡ አንዴ የድሮ ቅኝ ገዢአቸውን የእንግሊዙን ጠ/ሚኒስትር ቶኒ ብሌይርን ለማብሸቅ ብለው ምን እንዳሉ ታውቃላችሁ? “ሚስተር ብሌር፤ ዚምባቡዌ ኢዝ ማይን!” ብለዋል አሉ፡፡ (“አትልፋ! ዚምባቡዌ የእኔ ብቻ ናት” ማለታቸው ነው)  እስቲ አስቡት--- የኢህአዴግን የመተካካት ስትራቴጂ ሙጋቤ ቢሰሙ እንዴት እንደሚቀልዱ! “ማን አባቱ ነው ማንን የሚተካው!” ብለው ቱግ ነበር የሚሉት።  እሳቸው ብቻ ግን አይደሉም በአፍሪካ ስልጣንን የሙጥኝ ብለው በአምባገንነት ሕዝባቸውን የሚገዙት፡፡ የጥንቱ የኢህአዴግ ወዳጅ የአሁኑ ቀንደኛ ጠላት የኤርትራው መሪ ኢሳያስ አፈወርቂ እንኳንስ እንደኛ አገር 70 ምናምን ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዲቋቋሙ ሊፈቅዱ ቀርቶ፣ስለተቃዋሚ ፓርቲ ሲወራ ቢሰሙ እንኳ ኤሌክትሪክ ነው የሚጨብጡት፡፡ (ተቃዋሚ በእኔ መቃብር ላይ እንጂ እስትንፋሴ እያለች አይሞከርም ባይ ናቸው!) የኡጋንዳው ሙሴቪኒስ ቢሆኑ? እንዴት ነው ይሄን ሁሉ ዓመት ተቃዋሚን እያሸነፉ በስልጣን የዘለቁት? አያችሁ ---- በአገሬ ባለስልጣናት የምፅናናው ወድጄ አይደለም፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ በቀጣዩ ምርጫ በጠቅላይ ሚኒስትርነት የመቀጠል ፍላጎት እንዳላቸው ሲጠየቁ ምን አሉ? “ይሄ የሚወሰነው በፓርቲዬ እንጂ በእኔ ፍላጎት አይደለም፤ ኢህአዴግ ታች ወርደህ የቀበሌ ሊቀመንበር ሁን ካለኝ እሆናለሁ፤ በጠ/ሚኒስትርነት የበለጠ አስተዋፅኦ ታበረክታለህ ካለኝም---” ብለዋል፡፡ ሙጋቤ ተመሳሳይ ጥያቄ ቢቀርብላቸው ምን እንደሚሉ አልታያችሁም፡፡ “እኔ ካልቀጠልኩ ታዲያ ሕዝቤን ማን ይመራዋል!? ይሉ ነበር፡፡ ለዚህ እኮ ነው በኢህአዴግ የምፅናናው፡፡ እንዲያም ሆኖ በአንድ ወቅት አቦይ ስብሃት “ከአፍሪካ ፓርቲዎች ኢህአዴግን የሚስተካከለው የለም” ባሉት ነገር አልስማማም፡፡ (በግምት ነዋ የተናገሩት!)
እርግጥ ነው ኢህአዴግም ቢሆን የስልጣን ኮርቻው ላይ ከተፈናጠጠ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡ ግን ቢያንስ አንድ መሪ (ጠ/ሚኒስትር) እስከ 80 ምናምን ዓመቱ በድዱ አይገዛንም፡፡ (የፓርቲው ባህል አይፈቅድማ!) ስለዚህ በዚህ እፅናናለሁ፡፡ ለምሳሌ ከ20 ዓመት በላይ ኢህአዴግንና ጦቢያን የመሩት ጠ/ሚኒስትር መለስ ድንገት በሞት ሲለዩ የስልጣን ፉክቻ አላየንም (ቢያንስ በአደባባይ!) እነሙጋቤ አገር ቢሆን ኖሮ ምን እንደሚፈጠር አስቡት፡፡ እናም ኢህአዴግ የጠ/ሚኒስትሩን ህልፈት ተከትሎ በትጥቅ ትግሉ ያልነበሩትን አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በፓርቲው ሊቀመንበርነትና በጠ/ሚኒስትርነት መምረጡ የጦቢያን ልጆች ማስገረሙ አልቀረም፡፡ ዛሬም ድረስ እኮ ጠ/ሚኒስትሩ እየመሩ መሆናቸውን የምንጠራጠር ቀላል አይደለንም፡፡
ለዚህ እኮ ነው ብዙዎች በግልም በቡድንም፣ በአማርኛም በእንግሊዝኛም ደጋግመው “ጦቢያን በትክክል እየመራት ያለው  ማነው?” ወይም “Who is in Charge?” እያሉ የሚጠይቁት፡፡ እዚህች ጥያቄ ውስጥ ግን ብዙ የተጠቀጠቁ ጥርጣሬዎችና መላምቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ አንድ የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኝ የሆነ ወዳጄ ያለኝን ላጋራችሁ፡፡ (ኒዮሊበራሊዝም የሚለውን ቃል “አክራሪ ነፍጠኛ” በሚል ወደ አገር-በቀል ፍቺ ለውጬዋለሁ!) እናላችሁ … ይሄ ወዳጄ፤ አሁንም ድረስ የአገሪቱ ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ናቸው ብሎ አያምንም፤ እሳቸው ለስሙ ወንበሩ ላይ ተቀመጡ እንጂ ከጀርባ ሆነው መሪነቱን የሚዘውሩት አንጋፋ የኢህአዴግ ታጋዮች ናቸው ባይ ነው፡፡ (ህወሓቶች ማለቱ መሰለኝ!)
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል----እኔ በበኩሌ “የጠ/ሚኒስትርነቱን ቦታ በትክክል ማነው የያዘው?” የሚለው ብዙም አያስጨንቀኝም፡፡ የደቡብ ህዝቦች ግንባር ይሁን ህወሓት ወይም ኦህዴድ አሊያም ብአዴን  ለእኔ ለውጥ የለውም (ያው ኢህአዴግ ነዋ!) ለእኔ ቁምነገሩ ምን መሰላችሁ? “እንዴት ነው የሚገዛኝ?” የሚለው ነው። “ራዕዩ የማን ነው” በሚለውም አልጨነቅም፡፡ “ራዕዩ ምንድነው?” በሚለው እንጂ፡፡
በአሁኑ ሰዓት ጦቢያን የሚመራት ማነው “Who is in Charge?” የሚለው ጥያቄ ያሳሰባቸው ቧልተኞች  የፈጠሩትን ቀልድ ላልሰማችሁ ላሰማችሁ፡፡ (ኮፒራይቱ የሰፊው ህዝብ እንደሆነ ይታወቅልኝ!)
 አንዱ ኤፍኤም ሬዲዮ ይደውላል - ዘፈን ለመምረጥ።
ደዋይ - ዘፈን ለመምረጥ ነበረ፤ የእገሌን …
ኤፍ ኤም- ማን እንበል? ከየት ነው?
ደዋይ-    የገዢው መደብ አባል ነኝ---- ከደቡብ!
ኤፍ ኤም- (ደንገጥ ብሎ) ከደቡብ … እሺ ዘፈኑ ይቀጥላል …
(የኤፍኤሙ ጋዜጠኛ ከድብልቅልቅ ስሜት ሳይወጣ ሌላ ዘፈን መራጭ ይደውላል)
ኤፍ ኤም- ሄሎ … ማን እንበል? ከየት ነው?
ደዋይ -    ዘፈን ለመምረጥ ነበር
ኤፍኤም- ራስህን አስተዋውቀን?
ደዋይ -    የገዢው መደብ አባል ነኝ - ከትግራይ!
ኤፍኤም - እንዴትነው ነገሩ? አሁን ከደቡብ ደውሎ የገዢው መደብ አባል ነኝ ብሎኛል እኮ?    
ደዋይ- ዝም ብሎ ነው ባክህ … እነሱ ቀፎ፤ እኛ ሲም ካርድ ነን!
እውነቱ ግን ምን መሰላችሁ? ቀፎውም ሲምካርዱም ያስፈልገናል፡፡ አንዱ ያለሌላው ጥቅም አይሰጥም፡፡   ሲም ካርድ ብቻውን አይደውልም ፤ ቀፎ ብቻውንም እንደዚያው፡፡
ስለዚህ ቀፎውም ሲምካርዱም እኩል ያስፈልጉናል እያልኩ ነው፡፡ በእርግጥ በቴሌ አሰራር ነገሩ የተለየ ሆኗል፡፡ ቀፎም ሲም ካርድም አንድ ላይ ሆነው መደወል አልተቻለም - ኔትዎርክ በሚሉት ችግር!! ገዢዎቻችንን ከኔትዎርክ መቆራረጥ ይሰውርልን! በተረፈ ያንዱ ቀፎ መሆንና የሌላው ሲም ካርድነት ጣጣ የለውም፡፡ ሁለቱም እኩል ያስፈልጉናል!!

  • በችላ ባይነታችን የአድዋ ድል ተረት እንዳይሆን ያሰጋል
  • የእቴጌ ጣይቱ የጦርነት ገድል አለመነገሩ ብዙዎችን አሳዝኗል
  • ለአዲሱ ትውልድ ስለ አድዋ ድል ምን ታሪክ ልናስተላልፍለት ይሆን?

ገሠሦ፣ ምንድብዳብ፣ (በትግርኛ የተቆራረጠ ማለት ነው) ኪዳነ ምህረት ገሠሦ፣ ማርያም ሸዊት፣ ራዕዮ፣ እንዳባገሪማ ገዳም፣ ሶሎዳ፣ … ምንድናቸው ቢባል፣ ስንቶቻችን በትክክል እንመልስ ይሆን? እርግጠኛ ነኝ ከታሪክ ምሁራን በስተቀር፣ ብል ያለማጋነን ብዙዎቻችን አናውቀውም፤ ግን ደግሞ አይፈረድብንም፡፡ ምክንያቱም ስለእነዚህ ስሞች የሚገልጽ አንዳች ምልክት በአካባቢያቸው አልተደረም፡፡ ታሪካቸው በሚዲያ ሲነገርም አይሰማም፡፡ ነገር ግን  አጥንት ተከስክሶና ደም ፈስሶ ከኢትዮጵያዊ ማንነታችን ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ታሪካዊ ትስስር አላቸው፡፡
ከላይ እንደፈተና የዘረዘርኩላችሁ ስሞች የሚገኙት በትግራይ ክልል በአድዋ ከተማ ዙርያ ሲሆኑ ሁሉም የተራራ ስሞች ናቸው፡፡ ተራ ተራሮች ግን አይደሉም-ይለያሉ፡፡ የነፃነትና የድል ተራሮች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያዊነት መገለጫ፣ የኩራት ተራሮች ሊባሉ ይችላሉ፡፡  
የአውሮፓ አገራት፣ ከኢትዮጵያና ከላይቤሪያ በስተቀር በርካታ የአፍሪካ አገራትን ወርረው ቅኝ ተገዥ እንዳደረጉት ሁሉ፣ የጣሊያ ወራሪ ፋሺስት ጦርም፣ አልተሳካለትም እንጂ ኢትዮጵያን ወርሮ ለማስገበር ሞክሮ ነበር፡፡ ጀግኖቹ አያት ቅድመአያቶቻችን፤ ወንድ ሴት፣ ወጣት ሽማግሌ ሳይሉ “እምቢኝ ለአገሬ! በሕይወት እያለሁ አገሬን ጠላት አይገዛትም! ..” ብለው፣ ረሃብና ችግር ሳይበግራቸው በዱር በገደሉ ለአምስት ዓመት መሽገው ጠላትን ተፋልመዋል፡፡
የማታ ማታም መጋቢት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ዘመናዊ የጦር መሳሪያ፣ መድፍና መትረዬስ እስከ አፍንጫው የታጠቀውን የጣሊያን ወራሪ ጦር ተጋፍጠው (ያውም በጥቂት ኋላ ቀር ጠመንጃዎች፣ በጦር፣ በጋሻና ጐራዴ) በጀግንነት በመፋለም አጥንታቸውን ከስክሰውና ደማቸውን አፍስስው ነፃ ሀገር፣ ነፃ ኢትዮጵያን ያስረከቡን በእነዚህ ተራሮች ላይ ተዋግተው ነው፡፡
የአድዋ ሰንሰላታማ ተራሮች፣ አገራቸውን የወረረውን የኢጣሊያ ጦር ለመውጋት ከየክልሉ ተጠራርተው መጥተው ጦርነቱ በድል ሲያበቃ፣ እዚያው በቆሙበት የቀሩ ይመስላል፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል! ለወገን ጦር መሸሸጊያና መከታ፣ ለጠላት ጦር አበሳና ፈተና የሆኑት እኒያ የተፈጥሮ ተራሮች እውቅና ተሰጥቷቸው መከበር፣ መዘከርና መወደስ ቢገባቸውም፣ ዞር ብሎ ያያቸው እንኳ የለም፡፡ “የጣሊያን ወራሪ ጦር የተሸፈነበት ስፍራ” የሚል ጠቋሚ ምልክት እንኳ ስለሌለ የዛሬውና መጪው ትውልድ በቃል ከሚተላለፍለት “የአድዋ ጦርነት ድል” የሚል “ታሪክ” በስተቀር ትክክለኛ ስፍራው የት እንደሆነ ለማወቅ ያዳግተዋል፡፡ በዚህ አያያዛችን  ከቀጠለማ የ “አድዋ ድል” ተረት እንዳይሆን ያሰጋል።
እጅግ የሚያሳዝነው ነገር፣ የተፈጥሮ ጀግኖቹ መዘንጋት ብቻ አይደለም፡፡ ከመላ አገሪቱ የተውጣጡ እጅግ በርካታ የነፃነት አርበኞች ውድና ክቡር ሕይወታቸውን ቢሰጡም፣ ነገሬ ብሎ ያስታወሳቸው የለም፡፡ ለምሳሌ ከአድዋ ጦርነት እጅግ አሰቃቂና ከሁለቱም ወገን ብዙ ሺዎች ያለቁበት የምንድብዳብ ውጊያ ዋና ተዋናይ የነበሩት ወጣቱ ጄነራል ፊታውራሪ ገበየሁ ምንም የሠሩት ገድል እንዳልተነገረላቸው የእንዳአምባ ትራቭል ኤጀንሲ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አሳየ ታረቀኝ ተናግረዋል፡፡ “ደረታቸውን ሰጥተው የጠላትን ጦር መግቢያ መውጪያ በማሳጣት  ሲተገትጉ፣ በጥይት ተመትተው ሞቱና እዚያው ምንድብዳብ ተቀበሩ፡፡ በመቃብራቸው ላይ ምልክት ስላልተደረገ በትክክል የት እንደተቀበሩ እንኳ አይታወቅም፤ በተቃራኒው ግን ጣሊያኖች ጀኔራል ዳቦርሜዳ ሞቶ በተቀበረበት ሥፍራ በድንጋይ ላይ ስሙን ጽፈው ስለተው፣ አሁን ድረስ ታሪኩ ይታወሳል” ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ጦር አሰላለፍ በአራት አቅጣጫ እንደነበር አቶ አሳየ ይናገራል፡፡ ሶሎዳ ተራራ ስር፣ ከሸዋ የመጡ 400 የኦሮሞ ፈረሰኞች መሽገው ነበር፡፡ 2ኛው ከአድዋ መውጫ፣ 3ኛው የራስ አሉላና የራስ መኮንን ጦር፣ እምባ መላክ ወይም ውጊያው በተካሄደበት ኪዳነምህረት ገሠሦ፣ በእቴጌ ጣይቱ የሚመራው 4ኛ ጦር፣ ከኪዳነምህረት ገሠሦ ጀርባና ጐን መሽጐ ነበር፡፡ የኢጣሊያም ጦር በአራት አቅጣጫ ነው የመጣው፡፡ በአራት አቅጣጫ የመጣው ባሻ አውአሎምና ሌሎች የስለላ (እንተለጀንስ) ሰዎች አሳስተው በነገሯቸው መሠረት እንደሆነ ይነገራል፡፡
ባሻ አውአሎም ሐረጐት ካልተነገረላቸው የአድዋ ጀግኖች አንዱ ናቸው፡፡ ባሻ አውአሎም በኤርትራና በትግራይ የሚመላለሱ ነጋዴ ነበሩ፡፡ ቀደም ሲል ራስ አሉላ ኢጣሊያኖችን እየሰለሉ እንዲግሯቸው፣ የኢትዮጵያን ጦር ምስጢር ደግሞ አሳስተው እንዲጠቁሟቸው ከባሻ አውአሎም ጋር ተስማምተው ነበር፡፡ በዚያው መሠረት፣ ባሻ የኢትዮጵያ ጦር ከኪዳነምህረት ገሠሦ ጀርባ ባለ ተራራ ላይ መመሸጉን ለጣሊያኖቹ ይነግራሉ፡፡ ስለዚህ ጀኔራል አርሞንዲ ጦሩን እየመራ ኪዳነምህረት ገሠሦ ተራራ ላይ ይመሽጋል፡፡ በዚህ ጊዜ እነ ራስ አሉላ በጀርባው ቆርጠው ገብተው መድፍ ሲተኩሱ ከአድዋ 10 ኪ.ሜ ወደ ኋላ መሆኑን አርሞንዲ አያውቅም ነበር፡፡ ስለዚህ፣ ለተቀረው ጦር “ገብቻለሁ” ሲል በተመሳሳይ ሰዓት ከሦስቱም አቅጣጫ ተኩስ ተከፈተበት፡፡ ጄነራል አርሞንዲ የሞተበት ውጊያ በሶስት አቅጣጫ የሚከፈል ነው፡- ኪዳነምህረት ገሠሦ፣ ምንድብብና ማርያም ሸዊት ነው፡፡ (የቦታ ስምና አቅጣጫ ስገልጽ ከተሳሳትኩ ለመታረም ዝግጁ ነኝ፡፡) ጄነራል ዳቦርሜዳ የሞተው ማርያም ሸዊቶ በተባለው ተራራ ላይ ነው፡፡ ጄነራል ባራቶሪ ደግሞ የተገደለው ራዕዮ ተራራ ላይ ነው፡፡ ጄነራል አልባርቶኒ ያመለጠው ደግሞ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ገብቶ ተደብቆ ነው። የኢትዮጵያ ወታደሮች ከቤተክርስቲያኑ አውጥተው ያልገደሉት፣ ለቤተክርስቲያን ክብር ብለው እንደነበር ይነገራል፡፡ ጄነራል ኤሌናም በጦርነቱ ተገድሏል፡፡
ይህን በአንድ ጊዜ ሦስት የወራሪው ጄኔራሎች የተገደሉበትን፣ አንዱ ጀነራል የተማረከበትን ጦርነት ነው እኛ ኢትዮጵያውያን ችላ ብለን የዘነጋነው፡፡ የአድዋ ድል የኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን የጥቁር ሕዝቦችም ጭምር ነው፡፡ እስከ አፍንጫው ድረስ ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀና የማይሸነፍ የሚመስለው የአውሮፓ ቅኝ ገዥ በጦርና በጐራዴ የተሸነፈበትና የተዋረደበት በመሆኑ ክብር ተሰጥቶት ለቀጣዩ ትውልድ ታሪኩ በቅጡ መሸጋገር ነበረበት፡፡ ግን ምን ያደርጋል በእጅ ያለ ወርቅ ሆነ እንጂ!
ዘንድሮ በአድዋ ከተማ የተከበረው የድል በዓል እጅግ ደማቅ ነበር፡፡ ያደመቁት ደግሞ ከአዲስ አበባ ከእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ተነስተው 1000 ኪ.ሜ 43 ቀናት በእግራቸው ተጉዘው አድዋ ከተማ የደረሱት አምስት ተጓዦች ናቸው፡፡
ተጓዦቹ ብርሃኔ ንጉሤ፣ መሐመድ ካሣ፣ ኤርምያስ ዓለሙ፣ ሙሉጌታ መገርሳና (ደብሊው) ዓለምዘውድ ካሳሁን በአድዋ ጦርነት ወቅት የኢትዮጵያ ሠራዊት የተጓዘባቸውን መንገዶች ተከትለውና ታሪካዊ ስፍራዎችን ጎብኝተው፣ ባለፈው እሁድ በ118ኛ የአድዋ ድል በዓል መታሰቢያ ዕለት በሶሎዳ ተራራ አናት ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ አውለብልበው በዓሉ ወደሚከበርበት የተራራው ግርጌ ሲወርዱ “ሰልፍ ሜዳ” ተሰልፎ ይጠባበቅ የነበረው የአድዋ ከተማና አካባቢው ህዝብ፣ አባት አርበኞች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና ተማሪዎች በከፍተኛ እልልታና ጭብጨባ ተቀብለዋቸዋል፡፡ ተራራው አናት ላይ ወጥተው የተቀበሏቸውም ብዙዎች ናቸው፡፡
የዚህ ጉዞ ዓላማ ምንድነው? ሐሳቡስ እንዴት መጣ? … አንገታችንን ቀና አድርገን፣ ደረታችንን ነፍተንና አፋችንን ሞልተን እንድንናገር ምክንያት ለሆነን ለአድዋ ድል ክብርና ዋጋ የሚሰጡ ሰዎች አሉ። አባቶቻችን ባዶ እግራቸውን ተጉዘው እንዴት ነው ይህን ክብር ያጎናፀፉን? ድካማቸው ምን ይመስላል? እንዴትስ ይገለፃል? .. የሚሉ ጉጉ የአዲስ ትውልድ አባላትም አይጠፉም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሀሳብ ካላቸው ሰዎች መካከል አንዱ ሙሉጌታ መገርሳ (ደብሊው) ነው፡፡ ወደ አድዋ ደርሶ መልስ ጉዞ በእግሩ በማድረግ የአባቶቻችንን ድካምና እንግልት በተግባር ለማየት ወስኖ ነበር፡፡
ሙሉጌታ የፊልም ባለሙያ በመሆኑ የብርሃኔ ንጉሤ አጭር ፊልም ቀረፃ እንዳለ ይነገረዋል፡፡ “አሁን አልችልም፤ አድዋ እሄዳለሁ” ይላቸዋል፡፡ ይህንን ሐሳብ የሰሙት ጉዞውን አብረውት ለማድረግ ይስማሙና አምስት ሆነው፣ ቀን ቆርጠው፣ የአድዋ ድል በዓል በሚከበርበት ዕለት ከስፍራው ለመድረስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ይኼው ነው መነሻው፡፡
ተጓዦቹ በጉዞአቸው ወቅት የኢትዮጵያ ጦር ከተጓዘበት መንገድ ወጣ እያሉ ታሪካዊ ቦታዎችን አይተዋል፣ አስደሳችና አሳዛኝ ነገሮች እንዳጋጠማቸውም ይናገራሉ፡፡ ተጓዦቹ በጣም ካዘኑባቸው ነገሮች አንዱ ለአድዋ ጦርነትና ድል መነሻ የሆነው የውጫሌ ውል የተፈረመበት “ይስማ ንጉሥ” የተባለ ስፍራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ይስማ ንጉስ” የተባለው ስፍራ ባይኖር ኖሮ የአድዋ ጦርነት አይደረግም ነበር፤ ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን አፍሪካውያንና የዓለም ጥቁር ህዝቦች የሚኮሩበት የአድዋ ድልም አይኖርም ነበር፡፡ በድሉ ቦታ ምንም መታሰቢያ እንደሌለው ሁሉ በይስማ ንጉስም እቴጌ ከተቀመጡበት ድንጋይ በስተቀር ምንም ነገር ባለመሰራቱ በጣም አዝነናል” ብሏል ጋዜጠኛና የፊልም ባለሙያው ብርሃኔ ንጉሤ፡፡ ለመሆኑ ይስማ ንጉሥን ስንቶቻችን እናውቃለን? የቱሪስት መስህብስ የሚሆነው መች ይሆን?
ሌላው ተጓዦቹ ያዘኑበት ነገር በአድዋ ጦርነት ትልቅ ሚና ተጫውተው ብዙም ያልተወራላቸው ጀግኖች መኖራቸው ነው፡፡ ከእነዚህ ጀግኖች አንዷ እቴጌ ጣይቱ ብጡል ናቸው፡፡ እቴጌ የውጫሌን ውል ሲቃወሙ፣ “እኔ ሴት ነኝ፤ ጦርነት አልወድም፡፡ ግን እንደዚህ ዓይነት ውል ከምቀበል ሞትን (ጦርነትን) እመርጣለሁ” በማለት አፄ ምኒልክን ለጦርነት አነሳስተው በጦርነቱ ቦታ ስለፈጸሟቸው በርካታ ገድሎች ያለመነገሩ አሳዝኗቸዋል፡፡ ሴቶች በጦርነቱ ላይ የነበራቸው ሚና በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ ቀኑን ሙሉ ዕቃ ተሸክመው ይጓዛሉ፤ የወንዶቹ ጉዞ ሲያበቃ የሴቶቹ አያበቃም፤ እራት ማዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል። ይህ ብቻም አይደለም፤ ግማሾቹ ሚስቶች ናቸው፡፡ ሌሊት ተነስተው ቁርስ ማዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስለዚህ እቴጌ ጣይቱን ማክበርና ማድነቅ በዚያ ጦርነት ላይ ከፍተኛ ሚና የተጫወቱትን ሴቶች ሁሉ ማክበርና ማድነቅ ስለሚሆን እቴጌይቱን የሚዘክር ነገር መሰራት አለበት ብለዋል፡፡
ብዙም ያልተነገረላቸው ሌላው የአድዋ ጀግና ባሻ አውአሎም ሐረጎት ናቸው፡፡ የእሳቸው ሚና ባይኖር ኖሮ የአድዋ ጦርነት ምን ዓይነት መልክ ይኖረው እንደነበር መገመት አይቻልም፡፡ እሳቸውም እንደ እቴጌ ሁሉ ምንም አልተነገረላቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ጦርነቱን በድል እንዲያጠናቅቅ ስለተጫወቱት ሚና ወጣቱ ትውልድ ማወቅ አለበት፡፡ ባሻ አውአሎም ትልቅ ታሪክ እያላቸው የተረሱ ጀግና ስለሆኑ ስለእሳቸው በሚገባ መሠራት እንዳለበት መታዘባቸውን ተጓዦቹ ተናግረዋል፡፡
የአድዋ ድል ተገቢውን ክብር እንዳላገኘም ይናገራሉ፡፡ በተለይ ሙሉጌታ መገርሳ አድዋ ድል በፍፁም ተገቢውን ክብር እንዳላገኘ ሲናገር “ብራዚል ከእግር ኳስ ሌላ በሳንባ ዳንስ (ካርኒቫል) ፌስቲቫል ትታወቃለች፤ የዓለም ህዝቦችም ሳንባ ዳንስን ለማየት ወደዚያ ይሄዳሉ፡፡ ስፔይን ደግሞ በቲማቲም የመደባደብ ባህል፣ ከኮርማ ጋር የመሯሯጥ ዓመታዊ ካርኒቫል ስላላት የዓለም ታዋቂ ሚዲያዎች ሽፋን ይሰጡታል፡፡ እዚህ ግን ለዓለም ጥቁር ህዝቦች ትልቅ ኩራት የሆነው የነፃነት መካ መዲና፣ ክብርና የሚገባውን ዋጋ ስላልሰጠነው ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ሽፋን አልሰጡትም፡፡
ይህ የነፃነት በዓል ክብርና ትኩረት አግኝቶ ቢሆን ኖሮ ከሳንባ ዳንስና ከቲማቲም መደባደብ የበለጠ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ሽፋን ያገኝ ነበር፡፡ የአድዋ ሰንሰለታማ ተራሮችም የማይደፈር የሚመስለው የቅኝ ገዥ ኃይል አከርካሪው የተሰበረበት ዓውደ ውጊያ በመሆናቸው፤ ኢትዮጵያውያንና አፍሪካውያን ብቻ ሳይሆኑ፣ የዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች ሁሉ እንደ መካመዲና ሊሳለሙትና ሊያዩት ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን “ባለቤቱ ያቃለለውን አሞሌ …” እንደሚባለው ሆነና የሚገባውን ክብርና ትኩረት አጣ” ብሏል፡፡
የአድዋ ጉዞ ይቀጥላል ወይስ በዚሁ ያበቃል? በቀጣይስ የአድዋ ድል ተገቢውን ክብርና ትኩረት እንዲያገኝ ምን ይደረጋል?... የሚሉ ጥያቄዎች ቀርበውላቸው የአድዋ ተጓዦች መልስ ሰጥተዋል፡፡   
ተጓዥና የጉዞሰው አስተባባሪ በመሆን ሲሰራ የነበረው ያሬድ ሹመቴ ከአሁን በኋላ የአድዋ ጉዞ በየዓመቱ የሚቀጥል መሆኑን ተናግሯል፡፡ ቀጣዩ ጉዞ የሚቀራረቡ ጓደኛማቾች ሚያደርጉት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያውያን፣ አፍሪካውያን፣ ጥቁርና ነጭ የዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች፣የቻሉት የአድዋ ጀግኖች ባለፉት መንገድ በመጓዝ፣ ያልቻሉት ደግሞ በተለያዩ መጓጓዣዎች አድዋ ደርሰው ውጊያው በተካሄደባቸው ተራሮች ተገኝተው ድሉን እንደሚያከብሩት ያሬድ ተናግሯል፡፡
ጉዞውን ለማስቀጠል፣ አቅም ጊዜና ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እኛ ከዚህ ስንመለስ ወደየግል ስራችን እንመለሳለን፡፡ ስለዚህ ፕሮጀክት ተቀርፆ ጉዞውን የሚያስተባብርና ተግባራዊ የሚያደርግ አንድ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡
ኮሚቴው ሙሉ ጊዜያቸውን እዚያ ላይ አድርገው የሚሰሩ ሰራተኞች ቀጥሮ ያሰራል። ዓለም አቀፍ እውቀትና የሚዲያ ሽፋን እንዲያገኝ ለማድረግ ከፍተኛ የገንዘብ አቅም ይጠይቃል፡፡ ዘንድሮም ከተለያዩ ሚዲያዎች የተውጣጡ ጋዜጠኞች በስፍራው ተገኝተው እንዲዘግቡ የተደረገው አንድ ባለሀብት ስፖንሰር በማድረጋቸው ነው፡፡ ባለሀብቱ አቶ ዳዊት ገ/እግዚአብሔር ይባላሉ፡፡ ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ፣ ዓለም አቀፍ እውቅናና የሚዲያ ሽፋን ለማግኘት ከፍተኛ ድካም ብዙ ካፒታልና ጥረት የሚጠይቅ ነው፡፡ ፕሮጀክቱን ለመጀመር አቶ ዳዊት ለጊዜው አንድ ሚሊዮን ብር ለመስጠት ቃል በመግባታቸው ለአገራቸው ሉዓላዊነት መከበር ሲሉ ደማቸውን ባፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ህይወታቸውን መስዋዕት ባደረጉ የአድዋ ጀግኖች በመላው ዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች ስም እናመሰግናቸዋለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ክቡር ዓላማ መላው ህዝብና ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች ድጋፍ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን ብሏል አስተባባሪው ያሬድ ሹመቴ፡፡
አድዋ ላንድ ማርክ የተባለ ድርጅት ደግሞ 10 በ15 በሆነ ሰሌዳ ላይ በአማርኛና በእንግሊዝኛ “አድዋ” የሚለውን ቃል በሰሎዳ ተራራ ላይ ጽፎ ለመስቀል ቦታ መረከቡን አስታውቋል፡፡
ከመንግሥትም ሆነ ከአገር ወዳድ ዜጐች ብዙ ይጠበቃል፡፡ ምንስ ቢሆን ህይወታቸውን ሰውተው ነፃ አገር ያስረከቡን ጀግኖች ታሪክ መዘከርና ለአዲሱ ትውልድ ሃቁን ማስተላለፍ ያቅተናል እንዴ? ጐበዝ! ያልተዘመረላቸውን የአድዋ አርበኞችን እንዘምርላቸው!! አውደ ውጊያዎቹንም ስፍራ እንወቃቸው!!  

Published in ህብረተሰብ

   የአርሲ ጉዞዬ አስደናቂ ማስታወሻ

“በል እንዳትቀር እፈልግሃለሁ አልኩት፡፡ ትንሽ ቆይቶ ምልክት አደረገልኝ፤ ሞባይሌ ላይ። ደወልኩለት፡፡ ‘አንድ ልነግርህ ፈልጌ የረሳሁት ነገር አለ’ አለ፡፡ ያ ታጣቂ ገበሬኮ ራሱ መጥቶ - ያኔ ያልኳችሁ ስህተት ነው፤ የመጀመሪያው ቦታ ነው ትክክል ብሎ ነገረኝ- አለ … Can you imagine?” (አይገርምህም? እንደማለት) አለ ዶ/ር በመደመም፡፡
“That’s how the muse works! ውቃቢ ሲፈቅድ እንዲህ ነው አየህ!” እንቅልፍ የነሳው ነገር ነበረ ማለት ነው ታጣቂውን፡፡ “አዎ በስህተት ነው - እኔ ምን ሆኜ እንደሆን አላውቅም፤ መጀመሪያ በትክክል ነበርኮ የተናገርኩት’ አለ፤ አለኝ፡፡” “ታጣቂውም Re-affirm አረገ (ዳግመኛ አረጋገጠ) … ይሄ ምን ማለት ነው … ከ38 ዓመት በኋላ … በየጭንቅላቱ ውስጥ የሚሄድ ነገር አለ …”
“Guilt ም (የጥፋተኝነት ስሜት) አለ፤ ጭንቀትም አለ … ምንም ዓይነት ነገር ሊኖር ይችላል … አንድ ወዳጄ ከርቸሌ የነበረ ወዳጄ (ዘመዴም ነው) የአራት ኪሎ አካባቢ ሰው ነው-በዱሮው መንፈስ … አስከሬን እየሸኘን ሳለ ቅዳሜ ለት ቴክስት ልኬለት ነበር- ‘በጥምቀተ-ባህርም ታቦት ሲሸኝ እንዲህ በህዝብ አይጥለቀለቅም’ ብዬ፡፡ እሱ ምን ብሎ መለሰ … “Take photos of the guilt-ridden offsprings of the killers” …
(በወንጀለኝነት ስሜት የሚናወጡትን ገዳዮች ልጅ-ልጆች ፎቶ አንሣ-እንደማለት ነው)
እንግዲህ ሁሉም በየፊናው አዕምሮው ውስጥ የቀረ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ የእኛ ሰዎች እንዲህ ማሰባቸው አይገርምም! በኋላም ከዚህ ዘመዴ ጋር ስናወራ … “የላኩልህን ሚሴጅ ለሙሉጌታ አነበብክለት ወይ?” ብሎኝ ነበር፡፡ “እንዴት ብዬ ዶ/ር ሙሉጌታኮ በወፈ-ሰማይ ህዝብ ተከቦ ነበር” ብዬዋለሁ፡፡ ዞሮ ዞሮ ያው መልዕክቱን አሁን አድርሻለሁ” አልኩት፡፡ ተሳሳቅን፡፡ …
ወደ ሳጉሬ ስንገባ ፈረሰኞቹ በዛ ግርማ-ሞገስ ባለው አጀብ ሲቀበሉን the grandiosity of the moment (የዚያች ቅፅበት ድምቀት-ከግዝፈት) መግለፅ ከምችለው በላይ ነበረ! ለዚህ ነው ቴክስት የላኩለት፡፡ ቀረርቶ፣ ሽለላ፣ ለቅሶ … ድብልቅልቅ ወኔና ዕንባ፤ ከ38 ዓመት በኋላ! በጣም ስሜቴን አጥለቅልቆት ነበር! ማመን አልቻልኩም - ሙሉ ከተማ ሲንቀሳቀስ ማየት … ሲጐርፍ ሲሳብ ሲሰበሰብ፤ በአንድ አይነት የኮቴ-ቅኝት ሲፈስ መመስከር …
“አዎ ተቀነባብሮልናል፡፡ እኛ ከፍቅረማርያም ጋር ያሰብነው አባቴ ከሚካኤል ወደ ሥላሴ ይሂዱና በሰላም ይረፉ ብለን ነው፡፡ ነገሩ እንዴት ነበር መሰለህ? ክፍሌ ዘመድ ወዳጁን ሁሉ፣ በታህሣሥ 26 መሆኑ ነው፤ ሰበሰበና “እንዲህ ተገኝቷል ምን እናድርግ?” አለ፡፡ መቼ ነው ያሰባችሁት?” ሲሉት፤ የካቲት ውስጥ (ጊዜ እንዳንፈጅ ነው ብሏቸዋል)። “የት እንዲቀበር ነው የምትፈልጉት?” ሲሉት እዚያው ሥላሴ ግቢ ውስጥ አላቸው፡፡ “ይሄኮ የእናንተ፣ የአባታችሁ ቀብር ጉዳይ ብቻኮ አይደለም፡፡ የእኛንም ሰዎች ነው የምንቀብረው …”
እኛ እንግዲህ ስላሴ የክፍሌ እናት የተቀበሩበት ለመቅበር ነበር ያሰብነው … ‘በጭራሽ እኛኮ ሙስሊሞች ነን አብዛኛዎቻችን፡፡ … እዛ ቀብራችሁ እንዴት ብሎ ሌላው ዘመድ አዝማድ ይይ? አይሆንም-ፊት ለፊት፤ ሁሉም ሊያይ የሚገባበት ቦታ ነው መቀበር ያለባቸው! የእናንተ ሰው ብቻ ሳይሆን፤ ሌሎችንም ጭምር ያን ጊዜ ያለቁትን ለማስታወስ ነው የምንፈልገው - ብለው አሻፈረኝ አሉ -የአገር ሽማግሌዎቹ! … እኔም ፍቅረ ማሪያምም ሌሎችም ተሟገትናቸው - አይሆንም አሉ! ሁሉም ተቀበለ … ካሰብኩት በላይ ሆነ፡፡ ሁሉም በኋላ ሲያዩ … ቶላ በዳዳ በል፣ መኰንን አካ በል … ትላልቅ ያገር ሰዎች፤ በኋላ ሲያዩት ተደሰቱ ነው እምልህ፡፡ አይሆንም ብለው የነበሩት ሰዎች - በጣም ጥሩ ሆነ አሉ … ዘሪሁን የመቃብር ቤቱን ሥራ ጀምር ተባለ፣ … ሐውልት መሥራትና መጽሔት ማዘጋጀት አዲሳባ ያለው ኮሚቴ ሥራ ነው … ሌላው የአገሬው ኮሚቴ መስተንግዶ ይሥራ ተብሏል፡፡ በዚህ ተከፋፈልን … እኛ ገንዘብ እንደምንም ማከፋፈል ጀመርን-እዚህ ደረስን…
“ብዙ ብር አወጣችሁ?’
“አዎ ሀውልቱ ከ60 እስከ 70ሺ ሳይወስድ አልቀረም፡፡ መጽሔቱ እንደዛው ወጪ አለበት…”
“አንዱ የነካኝ ነገር አብዛኛዎቹ የቀብሩ ታዳሚዎች ሙስሊሞች ናቸው … ይሄንን ማመን አልቻልኩም፡፡ ግራ ቀኙ ሙስሊም ነው … የፕሮግራሙ መሪው የተናገረውን ታሪክ በትክክል ተረድቼው ከሆነ ፊታውራሪ ሱማሌያ ሄደው ነው ቁራን ቀርተው የመጡት ነው ያለው መሰለኝ…”
“አይ፤ እዚሁ ነው፡፡ የሱማሌ፤ ቁራን የሚያውቅ ሰው … ሱማሊኛም ይችላሉ አባቴ -የሚችሉት በዚያ ሱማሌ የተነሳ ነው፡፡ እዚሁ ነበር … እሱን አግኝተውት ቁራን ቀሩ፡፡ የአማርኛ ትምህርት በኋላ ላይ ተማሩ … እንደዚህ እንደዚህ ነው የሆነው
“መጀመሪያ ምን ነበሩ? ክርስቲያን ሆነው ነው ቁራን የቀሩት ማለት ነው?” ብዬ ጠየኩት፡፡   
“መጀመሪያማ በእኛ አካባቢ እስልምና አለ፡፡ እስልምናም ክርስትናም ባንድ አካባቢ ባንድ ዘመን ነው የገባው፡፡ የመጣው፡፡ ሳጉሬ፡፡ አያቴ ሁለቱም ሲመጡ አይተዋል! ያኔ ምናልባት በራስ ዳርጌ ጊዜ ነው - በሚኒሊክ ጊዜ መሆኑ ነው … ኦገቶ አያቴ በሚኒሊክ ጊዜ ነበሩ - ባላባት ናቸው ያን ጊዜ … እስልምናም ክርስትናም ሲመጣ - ከዛ በፊት ያው አዋማ ነው የሚባሉት - ያው በኦሮሞ አይነት አኗኗር ውስጥ የነበሩ ዕምነቶች ያልነካቸው ነበሩ …ኋላ ግን ኦገቶ እስላም ሆኑ፡፡ እስላምን ተቀበሉ። አብዛኛዎቹን የሚስቶቻቸውን ልጆች እስላም አደረጉ፡፡ የአባቴን እናት ልጆች (የሴት አያቴን) እነሱን ደሞ ክርስቲያን አረጓቸው፡፡ አንድ ቱሱራ የሚባል አለ፡፡ ክርስቲያን አልሆንም ብሎ እስላም ሆነ! ሌሎቹ አራቱ ማለት - ተክሌ፣ አበበ፣ በቀለ እና አሹ እምትባል ሴት ክርስቲያን ሆኑ! እንግዲህ፤ በኋላ ለባላባትነት አባቴን መርጠዋል ማለት ነው፡፡ ክርስትና ከተነሳህ ያው ከሥርዓቱ ጋር ቀረብ ትላለህ፡፡ ከሲስተሙ ጋር፡፡ እናቴንም ያገቡት ለዛ ነው፡፡ እናቴ እንግዲህ የማህል ሠፋሪ ልጅ ናት! ባሻ ገድሌ የእናቴ አባት የአንኮበር ሰው ናቸው፡፡ ከራስ ዳርጌ ጋር ሄደው ማህል የሰፈሩ ሰው ናቸው፡፡ አያቴ፤ የእናቴ እናት፣ ጠራ መንዝ ናቸው፡፡
“ስለዚህ አንኮበርና ጠራ ናቸዋ እናትህ?”
“አዎን፡፡ ሚስት ስጡን ቢሏቸው (በዚያን ጊዜ አጠራር) ‘ለጋላ አንሰጥም!” ብለው ነበር፡፡ በኋላ ፎከሩ፡፡ በቀለ ክርስቲያን የመሆን እድል አገኙ …. እስላም ሆነው ነበረ ማለት ነው አባቴ፡፡ … ካሜላ ነው ስማቸው … ሚካኤል ማለት መሰለኝ፡ ከካሜላ በፊት ጨዊቻ ነው እሚባሉት አባቴ፡፡ ጨዊቻ የኦሮሞ ስም ነው! ሌላ የእስላም የቁርዓን ስም ነው … ካሜላ … በኋላ የክርስትና አባታቸውን አውቅ ነበረ … ደጃች ወንድይራድ … እንደዛ ገደማ ናቸው፡፡ ከትልልቆቹ አንዱ፡፡ … ቁራንም ቀርተው፣ ክርስትናን ተነስተው፣ ባላባትነቱንም ተቀብለው ነበር ማለት ነው … አባታቸው ካረፉ በኋላ ባላባትነቱን ተረከቡ፡፡ ብዙ ልጆች ነበሩ ታላላቆችም ነበሩ፡፡ ሦስት ታላላቆች። ብዙ ጊዜ ልምዱ እንደዛ ነው - የመጀመሪያው ልጅ-የበኩር ልጅ ነው የሚወርሰው-ባላባትነቱን፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ግን እንደዚያ አልነበረም-ለአባቴ ነበር የተናዘዙላቸው!” አለኝ፡፡
እኔም በመገረም፤ “ከመስጊድና ከቤተክርስቲያን ጋር የነበራቸው ቀረቤታ በጣም ፍላጐት አሳድሮብኛል፡፡ አስገራሚ ዕውነት ነው” “Fundamental to the Ethiopian society የኢትዮጵያ ህ/ሰብ የመሠረት ደንጊያ ነው ብዬ አሰብኩ፡፡ እስካሁን ወሎ ብቻ ነበር ሲጠቀስ የኖረው - አሁን ሳጉሬ መጣ-አርሲ - a very profound aspect of religion- በአንድ አገር ውስጥ መስጊድንም እራሱ አሠርቶ፣ ቤተክርስቲያንንም (በዕውነተኛ ልቡና ሠርቶ) መጓዝ ድንቅ ነገር ነው። ትምህርት ነው፡፡ ከባድ ነው ከ38 ዓመት በኋላ ያገኘነው ማጠየቂያ (Justification)፡፡ ይኸው ሥላሴ ኮረብታ ላይ ታይቷል፡፡ በመሠረቱ የእስላም ሴት ለቅሶ ስትመጣም አላቅም… ግን መዓት መጡ … አለቀሱ … ለቀስተኞቹ በብዛት ሙስሊሞች ናቸው …በብዛት ያለቅሳሉ … በጣም ይገርማል … እንዲህ ያለ ማረጋገጫ አይገኝም - እኔ ከዚህ አኳያ (angle) ነው ያየሁት፡፡
ሌላው የእኔ የግሌ እይታ፤ በእኛ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ዘመን የአርሲ ዕድገት በህብረት ዘማቾችን ደርግ ያላቸውን አስታውሳለሁ … በትክክል ባልጠቅሰውም … “ቅምጥል ንዑስ ከበርቴዎች፣ እጃቸውን የእንጀራ ጠርዝ የሚቀደው … “ጥቁር ወተት ነጭ ኑግ አምጣ እያሉ ገበሬውን ሱሪ ባንገት ሲያስወልቁት ከርመዋል…” በሚል ዓይነት ነበር ዘማቾቹን የሚከስ የሚወቅሳቸው፡፡
“…አንተ በሦስት ማዕዘን የማይታረቅ ቅራኔ ውስጥ ገብተህ ነበረ ማለት ነበርኮ! ፀረ-ፊውዳል የተማሪ እንቅስቃሴ ባንድ በኩል፤ እሳቸው ደግሞ ፀረ-ደርግ ሆነው ይታገሉ፣ ይዋጉ ነበር፡፡ ደርግ ደግሞ በእኛ በዘማቾች ላይ ጥቁር ወተት ነጭ ኑግ እያለ ነው፡፡ በጣም ማራኪ ታሪካዊ ሦስት ማዕዘን ነው የሚታየኝ፤ በጣም ስቦኛል! … Deep inside (ውስጠ-ነገሩን ለመረመረ)   የማህበረሰባችንን አካሄድ የሚያሳይ ስዕልም ያለው ይመስለኛል… ብዙ ነገር በውስጡ የሚያልፍ የህይወት፣ የሞትና የተረፈ-ህይወት ነገር አለው” ትልቅ ፅሁፍ ይወጣዋል ከታሰበበት፡፡ የእስላም-ክርስቲያን ዕምነት ውሁድ (harmony) በኢትዮጵያ ሁሌም የነበረ፣ ያለና እሚኖር ነው፤ የሚለውን ዕሳቤ ፍንትው አድርጐ ያሳየናል፡፡ የአንድነት አገራዊ መገለጫኮ ይሄው ነው … ማሳያ ነው፡፡ አንተስ ይሰማሃል?” አልኩት፤ የኮረኮረኝን ያህል ተናግሬ፡፡  
“እኔማ አውቀዋለሁ፡፡ ድሮውኑ እስላም ክርስቲያን እኮ አንድ ላይ ነው የሚኖረው፡፡ ቆይ ልንገርህ፡፡ ኦገቶ እስላም ሆነ፡፡ እስላም ነው፡፡ አርሲ ኦሮሞ ከብት አርቢ ነው፡፡ አራሽ አይደለም ከአመጣጡ፡፡ ይሄንን እዚህ ባላባት ሆነው ከኃ/ሥላሴ ጋር … ኃ/ሥላሴ ኦገቶን በደምብ ያውቋቸዋል አሉ፡፡ ሲመጡ ከዚህ የሸዋ ኦሮሞዎችን ኑ ባካችሁ ያገሬን ሰው፣ ያገሬን ገበሬ፤ ግብርና አስተምሩልኝ ብለው የአጐቴን የመኰንንን የሰናይትን አያት፤ ሌሎችም ሰዎች እዚህ አምጥተው እንዲሠፍሩ አርገዋል፡፡ ቤት ሰጥተዋል፡፡ ከዛ ምን ሆነ አንድ ጊዜ አንድ ክርስቲያን ሰው ሞተ አሉ፡፡ የመቃብር ቦታ፣ ቤተክርስቲያን፣ የለም፡፡ የት ነው ያለው ወደ ኢቴያ። ቦሩ ጃዌ እሚባል ቦታ … በቃሬዛ፣ በጠፍር አልጋ ተሸክመው ወስደው እዛ ቀበሩ፡፡ በኋላ ኃ/ሥላሴ ጋ ሄደው፤”በል ፅላት ስጠኝ” ብለው መድኃኔ ዓለምን ቆረቆሩ!”  
“እኒሁ ኦገቶ?!” ገርሞኝ ጠየኩት፡፡
“አዎ ኦገቶ፡፡ ጋለማ ሥር ያለች ከተማ እሁድ ገበያ ትባላለች፡፡ እዛ ቆረቆሩ፡፡ ሠንሠለታማው ጋራ ሥር ያለችው እሁድ ገበያ ውስጥ ያለ ቤተክርስቲያን ኖረ ማለት ነው፡፡ አሁንም አሉ፤ የዚያ ቤተክርስቲያን፤ ቀዳሽ ቄሶች፣ ልጅ ልጆች፡፡ እዚያው ሠፈሩን መሬቱን ይዘው ይኖራሉ፡፡ ከዛ ደባል እግዚሃር-አብ አለ፡፡ በጥምቀት ጊዜ ይኬድበታል፡፡ መድኃኔዓለም ከከተማው ወጣ ያለ ነው፡፡ ወደላይ 4ኪ.ሜ ገደማ። እና አንድ አጐቴ ከሌሎች ጋር ሆነው እዚህ ከተማ ውስጥ እግዚሄርአብን ከመድህኔዓለም ደባልነት አውጥተው አሁን እሁድ ገበያ ውስጥ እንዲኖሩ አርገውታል፡፡ እና ኦገቶ ናቸው ቤተክርስቲያን ያሠሩት፡፡ የዚያን ክርስቲያን ሰውዬ መሞትና ኢቴያ ቦሩ ጃዌ ድረስ ሄዶ (50 ኪ.ሜ) መቀበር፤ ካዩ ወዲያ ነው እንግዲህ! ይሄ ዕውነተኛ ታሪክ ነው! እና ለእኔ ዓይነት ሰው እስላም - ክርስቲያን ልዩነት ዓይነት Sense (ስሜት) ምንም የለም፡፡ ምንም ማስተናገጃም የለኝም፡፡”
“ከዚህ ሁሉ ዓመት በኋላ የዛሬው ሥነ ስርዓት የፈጠረብህ ስሜት ምንድነው? እንዴት ታየዋለህ? በአጭሩ”
“እኔ አሁን እንደማየው ካሁን ወዲያ፤ የተበጣጠቀው ታሪክ መልሶ መገጣጠም የተጀመረ ይመስለኛል … ምናልባት ካሁን ወዲያ የተሻለ ህይወት ለመኖር እንችል ይመስለኛል እንጂ ካሁን በፊት ያጋጠመኝ የነበረው ስሜት … እንደጠላትነት ነበረ … ደርግ ወድቆ ይሄኛው መንግሥት ሲመጣ ምን ነበረ መሰለህ … በቀለን የገደለ ሰው እናውቃለን ለምንድነው ከሰን የማናሳስረው? ገዳዮቹን ፖሊሶች እናውቃለንኮ ለምንድነው የማናሳስረው ሲባል ነበር … ያ አይነት ስሜት ነበር፡፡ ይሄ ቂም ነው፡፡ ቂም ነው፡፡ አልተዋጠልኝም ነበረ፡፡ የመገፋፋት ሁኔታ ነበረ ልልህ ነው፡፡ እና ታላቅ ወንድሜም እሱን ሰምቶ እንዲህ ይባላል ብሎኝ ነበር፡፡ ቃታ-የሳበ ሁሉ አስተሳሰብ አያስፈልግም እና ተውኩ፡፡ ተው አልኩት፡፡ እዛ ውስጥ አንገባም ተባባልን፡፡ እና ሌላም አጐቴ ነበረ፡፡ በቂም እሚያስብ፡፡ ያጋጥመኝ ነበር … ያኔ ታስታውስ እንደሆን (የዛሬ 26 ዓመት ግድም) ሰላምና መረጋጋት የሚባል ነበረ …”
“እንዴ በደንብ ነው የማስታውሰው!”
“አሰላ ውስጥ ሰላምና መረጋጋት ውስጥ ሲያገለግል የነበረ አጐቴ ሲነግረኝ፤ አለቃው አንድ የቡድን መሪ አድራጊ-ፈጣሪ የነበረና የእኛ አባትን ታሪክ ይሄንን ያወራ የነበረ አለ፡፡ ‘ገዳዮቹ ማናቸው?’ ብሎ ይጠይቃል፤ አለ፡፡ ለምን ገዳዮቹን ሰብስበን እዚህ አንጨርሳቸውም? ከዛ በኋላ ቂማችሁን ተወጥታችኋል ማለት ነው፤ ለምን እንደዚህ አናረግም?’ አለኝ አለ፡፡ እስቲ ቆይ ዕድል ስጠኝ ብዬ በኋላ ተውኩት፤ አለ፡፡ እና እንደዛ እንደዛም ሆኖ ነበር! በዛ ውሰጥ ነው ያለፍነው! ያ ፈሊጥ ነበረ! ጊዜ ወዳንተ ሲያዘነብል ቂም መወጣት ወይም አንተን ወደዘመመበት ለማዝመም የተደረገ ሙከራ ነበረ። ጊዜው ያመቻል፡፡ አጋጥሞኛል፡፡ እሱ 2ኛ ነው፡፡ ሌላም እንደዚሁ ዘመዳችን የሆነ በጊዜው አድሃሪ ምናምን ብሎ ተሳድቧል ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ ባለፈው ቅዳሜ መጣና አየሁት፡፡ ገበሬ ማህበር ደምበኛ አብዮታዊ ባሻሪ የነበረ ነው፡፡ በኋላ ተገናኘን!! እሱኮ እደዚህ ያረገ ነው አሉኝ፡፡ አሁን ሌላ ሆነ! እሁድ ልሄድ አስቤያለሁ - ገጠር!
“ምን ልታደርግ?”
እንዲሁ ዘመዶቼን ልጠይቅ፡፡ ይቺ አሁን የነብር ቆዳ ለብሳ የፎከረችዋን ሴትዮ አላየሁዋትም ነበር፡፡ ሁሌ በሄድኩ ቁጥር እሷን አገኛለሁ …  ደሞ ያጐቴ ሚስት ልጅ አለች እሷንም ሄጄ ላያት፣ ልሰማት እፈልጋለሁ … አብረንም ብንሄድ መልካም ነው እና አሁን በረጋ መንፈስ ምንም ችግር የሌለው፤ ነገር መሥራት ይቻላል…አየህ፤ “ለካ እንዲህ ማድረግ ይቻላል?!” ነውኮ ያልነው! ይሄን ያህል አልጠበቅነውም”
“አገርን ማነቃነቅኮ ነው፡፡ እኔም በጭራሽ ለማመን አልቻልኩም”
“ዕውነት ነው አንድ አፅም ታሪክ እየሰራ ነው! ሰው እንደጉድ ፈሰሰ፡፡
በቪዲዮ በስፋት መቀረፅ ነበረበት! እንደታሪክ፣ እንደ እስላም-ክርስቲያን አንድነት፤ የብዙ ነገር ማሳያ ነው፡፡ በቲቪ መታየት ነበረበት-ለትውልድ ማስተማሪያ! አመለጠን - ብዙ ይዘጋጅ ብለን ነበረ … ታሪክና ሃይማኖት እንዴት የተሣሠሩ እንደሆኑና የመንግሥታት መለዋወጥ የማታ ማታ ንክች እንደማያደርጋቸው ያሳያል!!”
“That’s excellent! አመሰግናለሁ ዶ/ር ሙሉጌታ!”

Published in ህብረተሰብ

              በየአመቱ የአለማችንን ቢሊዬነሮች እየመረጠ ይፋ የሚያደርገው ፎርብስ መጽሄት፣ ዘንድሮም ለ28ኛ ጊዜ የ2014 ቢሊየነሮችን ዝርዝር ሰሞኑን  ይፋ አድርጓል፡፡ የማይክሮሶፍት ኩባንያ መስራቹ ቢል ጌትስ፣ በ76 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት የአመቱ የአለማችን ቁጥር አንድ  ባለጸጋ ሆኗል፡፡ ላለፉት አራት አመታት በሜክሲኳዊው የቴሌኮሙኒኬሽን ኩባንያ ባለቤት በካርሎስ ስሊምን ቀዳሚነቱን ተነጥቆ የቆየው ቢል ጌትስ፣ ዘንድሮ ቀንቶታል፡፡ ካርሎስ ስሊምን ከኋላው በማስከተል መሪነቱን መልሶ ወስዷል፡፡
ፎርብስ ባለፉት 20 አመታት ይፋ ካደረጋቸው የአለማችን ባለጸጎች ዝርዝር ውስጥ፣ በአስራ አምስቱ የአንደኛነትን ስፍራ የተጎናጸፈ ነባር ባለጸጋ ነው - ቢል ጌትስ፡፡ በ72 ቢሊዮን ዶላር የአለማችንን ሁለተኛ ባለሃብትነት ደረጃ የያዘውን ካርሎስ ስሊምን ተከትሎ በፎርብስ ዝርዝር ሶስተኛ ተደርጎ የተቀመጠው፣ ስፔናዊው ባለጸጋ አማንቺዬ ኦርቴጋ ነው - በ64 ቢሊዬን ዶላር ሃብት፡፡  አሜሪካዊው ቢሊዬነር ዋረን በፌ በ58 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር፣ የኦራክል ኩባንያ ባለቤት ላሪ ኤሊሰን በ48 ቢሊዮን ዶላር የአራተኛና የአምስተኛነቱን ደረጃ ይዘዋል፡፡ በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት 1ሺህ 645 የአለማችን ቢሊየነሮች፣ በድምሩ 6 ነጥብ 4 ትሪሊዮን ዶላር የተጣራ ሃብት እንዳላቸው የዘገበው ፎርብስ፣ ይሄን ያህል ቁጥር ያላቸው ቢሊየነሮች ሲመዘገቡ የዘንድሮው  የመጀመሪያው ነው ብሏል፡፡
በፎርብስ የቢሊየነሮች ዝርዝር ታሪክ፣ 2014 በሴት ቢሊየነሮች ቁጥር ክብረ ወሰን የተመዘገበበት ነው፡፡ በዘንድሮው የፎርብስ ዝርዝር ከተካተቱት የአለማችን ቀንደኛ ቢሊየነሮች፣ 10 በመቶ ያህሉ ወይም አንድ መቶ ሰባ ሁለቱ ሴቶች ናቸው፡፡ በአመቱ ዝርዝሩን ለመጀመሪያ ጊዜ የተቀላቀሉ ሴቶች ቁጥርም ክብረወሰን ተመዝግቦበታል፡፡ 42 አዳዲስ ሴት ቢሊዬነሮች በዝርዝሩ ውስጥ ሊካተቱ ችለዋል፡፡
ከ2014 የፎርብስ ሴት ቢሊዬነሮች ቀዳሚነት የያዘችውና የዎልማርት ኩባንያ ወራሽ የሆነችው ባለ 36 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላሯ ክርስቲ ዋልተን፣ በአጠቃላዩ ዝርዝር ውስጥ ደግሞ የዘጠነኛ ደረጃን አግኝታለች፡፡ የታዋቂው ኮስሜቲክስ አምራች ኩባንያ የሎሪየል ባለቤት ፈረንሳዊቷ ሊላኒ ቤተንኮርት፣ ከሴት ቢሊየነሮች ሁለተኛነትን፣ ከአጠቃላይ ቢሊየነሮች አስራ አንደኛነትን ይዛለች - በ 34 ነጥብ 5 ቢሊዬን ዶላር፡፡ በዝርዝሩ ውስጥ ብዙ ሴት ቢሊዬነሮችን በማስመዝገብ ቀዳሚነቱን የያዘችው አሜሪካ ናት - በ58 ሴት ቢሊየነሮች፡፡ ጀርመን 16 ሴት ቢሊዬነሮችን ስታስመዘግብ፣ ብራዚልም 14 ሴት ቢሊዬነሮችን አስመርጣለች፡፡
በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ በቴክኖሎጂ በተለይ ደግሞ በኢንተርኔት መስክ የተሰማሩ ባለጸጎች በጥሩ ሁኔታ ተወክለዋል ብሏል ፎርብስ፡፡ የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙከርበርግ፣ የአምናውን ጥሪቱን ከእጥፍ በላይ በማሳደግ 28 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር አድርሶ ስለተገኘ፣ ዘንድሮ 21ኛ ደረጃ ተሰጥቶታል፡፡ ዝርዝሩ እንደሚያሳየው፣ የጎግል መስራቾቹ ላሪ ፔጅ እና ሰርጂ ብሪን፣ በ32 ነጥብ 3 እና በ31 ነጥብ 8 ቢሊዮን ዶላር 17ኛ እና 19ኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ 32 ቢሊዮን ዶላር ያካበተው የአማዞን ዶት ኮም ባለቤት ጄፍ ቤዞስ በበኩሉ፣ በጎግሎቹ ባለጸጎች ጣልቃ ገብቶ 18ኛው የአለማችን ቢሊየነር ተብሏል፡፡ የአለማችንን ቢሊየነሮች ዝርዝር ለመጀመሪያ ጊዜ ከተቀላቀሉት አዳዲስ ባለጸጎች መካከል በቴክኖሎጂ መስክ የተሰማሩም ይገኙበታል፡፡ በዘርፉ ስመጥር የሆነውን ድሮፕቦክስ የተባለ ኩባንያ የሚመራው ድሪው ሆስተን ከእነዚህ አዲስ ገቢ የቴክኖሎጂ ሞጃዎች አንዱ ነው፡፡ የሄውሌት ፓካርድ ኩባንያ ባለቤት ሜግ ዊትማንም፣ በቴክኖሎጂ ዘርፍ በቢሊዬነሮች ዝርዝር ውስጥ ከሰፈሩት ሁለት ሴቶች አንዷናት፡፡
ከሁለት ወራት በፊት የመንግስት ስራቸውን ያቆሙት የቀድሞው የኒውዮርክ ሲቲ ከንቲባ ማይክል ብሉምበርግ፣ በ33 ቢሊዮን ዶላር የ16ኛነቱን ደረጃ መያዙን የሰሙ አንዳንድ ጠርጣራዎች፣ “ይሄ ሰው በተሰጠው ስልጣን ከአጉል ነገር ጋር ሳይነካካ አይቀርም” ብለው ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ፎርብስ ግን፣ “የለም እንዲያ አይደለም!... ሚስተር በሉምበርግ አብዛኛውን ሃብቱን ያካበተው፣ በሌላ ሳይሆን በግሉ ባቋቋመው የሚዲያ ኩባንያ ነው” ብሏል፡፡
‘የአመቱ ከሳሪ’ እና ‘የአመቱ አትራፊ’
ያለፈው አመት የማትረፍ ብቻ ሳይሆን የመክሰር ጭምር ነበር ይላል ፎርብስ፡፡ በሃብት ላይ ሃብት ያፈሩ ብዙዎች ቢኖሩም፣ አይከስሩት ኪሳራ ያስተናገዱም አልታጡም፡፡ ከእነዚህ ከሳሪዎች መካከል ቅድሚያውን የያዘው ደግሞ፣ ብራዚላዊው ባለጸጋ ኤኪ ባቲስታ ነው፡፡ ለታዋቂውና ለትርፋማው የባቲስታ የነዳጅና የተፈጥሮ ሃብቶች አምራች ኩባንያ፣ አመቱ መልካም አልነበረም፡፡ ኩባንያው የወሰደውን ከፍተኛ ብድር መመለስ ተስኖት፣ በቂ ምርት አውጥቶ ለገበያ ማቅረብ አቅቶት ሲንገዳገድ ነው አመቱ ያለቀው፡፡ አመቱ ተጠናቆ ሂሳቡ ተደማምሮ ተቀናንሶ ሲሰላ ታዲያ፣ አስደንጋጭ ውጤት ነበር የተገኘው፡፡  አምና የ10 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላር ባለቤት የነበረው ብራዚላዊው ባለጸጋ ባቲስታ፣ ዘንድሮ በእጁ ላይ የተገኘው 300 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ነው፡፡ ፎርብስም ይሄን ቀን የጣለው ሰው፣ “ይህን ገንዘብ ይዘህ በዚህ ዝርዝር ውስጥ ምን ታደርጋለህ!” ብሎ ከሰልፉ አስወጥቶታል፡፡
አመቱ ለባቲስታ እንጂ ለዙከርበርግ የኪሳራ አይደለም፡፡ የፌስቡክ መስራቹ ማርክ ዙከርበርግ፣ በአመቱ የሃብት ጭማሪ ካስመዘገቡ ገበያ የሞቀላቸው ባለጸጎች መካከል ቀዳሚው ነው ተብሏል፡፡ በ2013 በእጁ ላይ የነበረውን 13 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ከእጥፍ በላይ አሳድጎ፣ በ2014 የሃብቱን መጠን 28 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር አድርሶታል፡፡ ዙከርበርግ በአመቱ ከፍተኛ ገንዘብ ያፈራው የአለማችን ቀዳሚ ባለጸጋ ተብሏል - በፎርብስ፡፡
የሞጃዎች አገር
በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ቀንደኛ ባለሃብቶች ዝርዝር ውስጥ፣ በርካታ ዜጎቿን ያሰለፈችው ቀዳሚት አገር፣ ታላቂቷ አሜሪካ ናት፡፡ በ492 የሞላላቸው ቢሊዬነሮቿ ዝርዝሩን ያጥለቀለቀችውን አሜሪካን ተከትላ፣ ቻይና 152 ቢሊየነሮቿን ስታሰልፍ፣ ሩሲያ በበኩሏ 111 ቢሊየነሮቿን በዝርዝሩ ውስጥ አስገብታለች፡፡  አልጀሪያ፣ ሉቲኒያ፣ ታንዛኒያ እና ኡጋንዳ በዘንድሮው የፎርብስ መጽሄት ዝርዝር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ስማቸውን ያስጠቀሷቸውን  አንዳንድ ቢሊየነሮችን አፍርተዋል፡፡ እነ አሜሪካ ብዙ ቢሊዬነሮችን ባፈሩበት ባለፈው አመት፣ እነ ቱርክ ብዙ ቢሊዬነሮቻቸውን አጥተዋል፡፡ የዋጋ ግሽበት ክፉኛ እየደቆሳት ያለችው ቱርክ፣ አምና ከነበሯት ቢሊዬነሮች አስራ ዘጠኙን ተነጥቃለች፡፡ የመገበያያ ገንዘቧ የመግዛት አቅም ከአሜሪካ ዶላር ጋር ሲነጻጸር ባለፈው አመት 20 በመቶ የወረደባት ኢንዶኔዢያም ብትሆን፣ ስምንት ቢሊየነሮቿን አጥታለች፡፡
ቁማር እና ዶላር
በምድረ አሜሪካ በቁማር ስሙ ለሚጠራው ሼልደን አዴልሰን፣ አመቱ ገዳም ነበር፡፡ ከሰባት አመታት በፊት በዚሁ ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት አስር የአለማችን ቀዳሚ ቢሊየነሮች አንዱ የነበረው አዴልሰን፣ ሃብቱ አሽቆልቁሎበት ደረጃውን ለሌሎች ተረኞች አስረክቦ ነበር የባጀው፡፡  ዘንድሮ ግን የቁማር በለስ ቀንቶት፣ ተጨማሪ 11 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር አፍሶ ተገኝቷል፡፡ እናም ከ2007 ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ፣ ከአስሩ ቀንደኞች ተርታ ተመልሶ ተቀላቅሏል - በስምንተኛነት፡፡  እንግሊዛዊቷ የድረገጽ ቁማር አጫዋች ዴኒስ ኮቴስም፣ እንዲህ እንደ አዴልሰን በቁማር ቀን ከወጣላቸው የአመቱ ባለጸጎች አንዷ ናት፡፡ በአባቷ ሱቆች ውስጥ በካሸርነት ተቀጥራ እየሰራች፣ ጎን ለጎን ትምህርቷን ትከታተል የነበረችው ኮቴስ፣ በኋላ ላይ ቁማር እንደሚያዋጣት በማሰብ ከወንድሟ ጋር ባቋቋመችው ቤት 365 የተሰኘ አቋማሪ ኩባንያ 1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላር አፍሳ በፎርብስ ዝርዝር ውስጥ ሰተት ብላ ገብታለች፡፡ ካዚኖ ተብሎ በሚጠራው ቁማር ጨዋታ ቢሊዮን ዶላሮችን ካፈሱ መሰል የቁማር ሃብታሞች ሌላው፣ ባለ 22 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላሩ ሉዊ ቺ ው ይባላል፡፡
‘ራስ ሰራሾች’ እና ‘ወራሾች’
በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት 1ሺህ 645 የተለያዩ አለም አገራት ቢሊየነሮች ውስጥ፣ ሁለት ሶስተኛ ያህሉን ወይም 1ሺህ 80ዎቹን፣ ‘ራስ ሰራሽ ቢሊየነሮች’ (self-made billionaires) ይላቸዋል ፎርብስ መጽሄት፡፡ ከምንም ተነስተው ጥረው ግረው በመስራት፣ በየተሰማሩበት የሙያ መስክ ስኬት ያስመዘገቡ ባለጠጎች ለማለት ነው፡፡
207 ያህሉ ከእናት ከአባታቸው ወይም ከዘመድ ወዳጅ ጓደኛቸው አልያም ከሌላ አካል ዳጎስ ያለ ሃብት የወረሱ ባለጸጎች ናቸው፡፡ የተቀሩት 352 ቢሊየነሮች ደግሞ፣ ምንም እንኳን የተወሰነውን ሀብት ያገኙት በውርስ ቢሆንም፣ እግራቸውን አጣጥፈው የወረሱትን የሚበሉ ተጧሪዎች አይደሉም ተብሏል፡፡ ፎርብስ እንደሚለው፣ እነዚህኞቹ ባለጸጎች በውርስ ያገኙትን ሃብት መነሻ በማድረግ ጠንክረው የሰሩና የበለጠ ሃብት እያፈሩ ለትልቅ ደረጃ የበቁ ብልሆች ናቸው፡፡
አዲስ ገቢዎች እና ተሰናባቾች
በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ቢሊየነሮች ዝርዝር ውስጥ፣ 268 አዲስ ገቢ ቢሊየነሮች ተካተዋል። በርካታ አዳዲስ ቢሊየነሮች በተፈጠሩበትና ክብረወሰን በተመዘገበበት በዘንድሮው አመት፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በዝርዝሩ ከተካተቱ አዲስ ገቢዎች መካከል፣ 50ው ከአሜሪካ፣ 37ቱ ደግሞ ከቻይና ናቸው፡፡ ስማቸው ለመጀመሪያ ጊዜ በፎርብስ ዝርዝር ውስጥ ከተካተተላቸው አዳዲስ ቢሊየነሮች መካከል የምትጠቀሰው፣ ከቢሊየነሮች ሁሉ በዕድሜ ለጋ የሆነችው ፔሬና ኬ ናት፡፡ የሆንግ ኮንግ ዜግነት ያላት ይህቺ የ24 አመት ወጣት፣ በ1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር በ1ሺህ 284ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠች የልጅ ሃብታም ናት፡፡ 1ሺህ 540ኛ ደረጃ የያዘችው የፌስቡክ አጋር መስራች ሸሪል ሳንበርግ እንዲሁም ከሰሞኑ ከፌስቡክ ጋር የ19 ቢሊዮን ዶላር ሽያጭ የተዋዋሉት የዋትዛፕ መስራቾች ጃን ኩም እና ብሬን አክተንም ለዝርዝሩ አዲሶች ናቸው፡፡
ከዚህ በፊት በዝርዝሩ ውስጥ ተካተው የነበሩና ዘንድሮ ግን የተሰናበቱ ጊዜ የጣላቸው ባለጸጎችም አልታጡም፡፡ 47 የእስያ ፓሲፊክ፣ 20 የመካከለኛው ምስራቅና የአፍሪካ አገራት ቢሊየነሮች በዚህ አመት ከፎርብስ ዝርዝር ተሰርዘዋል፡፡ አምና ቢሊየነር ተብለው በፎርብስ ከሰፈሩበት መዝገብ፣ ዘንድሮ ስማቸው የተፋቀባቸው የከሰሩ ባለጸጎች በድምሩ አንድ መቶ ናቸው፡፡ ከእነሱ በተጨማሪ ሌሎች 16 ቢሊየነሮችም ከዚህ አለም በሞት በመለየታቸው ከዝርዝሩ ተሰርዘዋል፡፡ ከከሰሩት በታች ከሞቱት በላይ አንድ ሰው አለ - ከሁሉም በላይ አይከስሩ ኪሳራ የገጠመው ኖርዌጂያኑ ኦላቭ ቶን፡፡ ፎርብስ አሰላሁት እንዳለው፣ አምና 5 ነጥብ 75 ቢሊዮን ዶላር የነበረው ይሄ ባለጸጋ፣ ዘንድሮ ቤሳቢስቲን የሌለው ነጭ ደሃ ሆኗል፡፡
ጥቁር ቢሊየነሮች
በዚህ አመት የፎርብስ ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት 1,645 ቢሊየነሮች፣ ጥቁሮች ዘጠኝ ብቻ ናቸው። ከአህጉሪቱ ብዙ ቢሊየነሮችን በማስመዝገብ ቀዳሚነቱን የያዘችው ናይጀሪያ መሆኗን የፎርብስ ዘገባ ያሳያል፡፡ በናይጀሪያ የመጀመሪያዋ ሴት ቢሊየነር ሆነችው ፎሎሩንሽኮ አላኪጃ በ2ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ዝርዝሩን የተቀላቀለች ሲሆን፣ የአገሯ ልጅ አሊኮ ዳንጎቴም አምና ከነበረበት 20 ያህል ደረጃ በማሻሻል 23ኛ ላይ ተቀምጧል - በ25 ቢሊዮን ዶላር፡፡ ላለፉት አመታት በአፍሪካ አህጉር አንደኛው ቢሊየነር ሆኖ የዘለቀው ዳንጎቴ፣ ዘንድሮም ክብሩን የሚነጥቀው አፍሪካዊ ባለሃብት አልተገኘም፡፡  ናይጀሪያዊቷ ፎሎሩንሽኮ አላኪጃ፣ የአንጎላዋ ኢሳቤል ዶሳንቶስ እና ኦፕራ ዊንፍሬይ በዝርዝሩ ውስጥ የተካተቱ ሶስቱ ብቸኛ ጥቁር ቢሊየነሮች ናቸው፡፡  የኛው ሼክ መሃመድ ሁሴን አል አሙዲ በ15 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር 61ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ
  • በችላ ባይነታችን የአድዋ ድል ተረት እንዳይሆን ያሰጋል
  • የእቴጌ ጣይቱ የጦርነት ገድል አለመነገሩ ብዙዎችን አሳዝኗል
  • ለአዲሱ ትውልድ ስለ አድዋ ድል ምን ታሪክ ልናስተላልፍለት ይሆን?

ገሠሦ፣ ምንድብዳብ፣ (በትግርኛ የተቆራረጠ ማለት ነው) ኪዳነ ምህረት ገሠሦ፣ ማርያም ሸዊት፣ ራዕዮ፣ እንዳባገሪማ ገዳም፣ ሶሎዳ፣ … ምንድናቸው ቢባል፣ ስንቶቻችን በትክክል እንመልስ ይሆን? እርግጠኛ ነኝ ከታሪክ ምሁራን በስተቀር፣ ብል ያለማጋነን ብዙዎቻችን አናውቀውም፤ ግን ደግሞ አይፈረድብንም፡፡ ምክንያቱም ስለእነዚህ ስሞች የሚገልጽ አንዳች ምልክት በአካባቢያቸው አልተደረም፡፡ ታሪካቸው በሚዲያ ሲነገርም አይሰማም፡፡ ነገር ግን  አጥንት ተከስክሶና ደም ፈስሶ ከኢትዮጵያዊ ማንነታችን ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ታሪካዊ ትስስር አላቸው፡፡
ከላይ እንደፈተና የዘረዘርኩላችሁ ስሞች የሚገኙት በትግራይ ክልል በአድዋ ከተማ ዙርያ ሲሆኑ ሁሉም የተራራ ስሞች ናቸው፡፡ ተራ ተራሮች ግን አይደሉም-ይለያሉ፡፡ የነፃነትና የድል ተራሮች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያዊነት መገለጫ፣ የኩራት ተራሮች ሊባሉ ይችላሉ፡፡  
የአውሮፓ አገራት፣ ከኢትዮጵያና ከላይቤሪያ በስተቀር በርካታ የአፍሪካ አገራትን ወርረው ቅኝ ተገዥ እንዳደረጉት ሁሉ፣ የጣሊያ ወራሪ ፋሺስት ጦርም፣ አልተሳካለትም እንጂ ኢትዮጵያን ወርሮ ለማስገበር ሞክሮ ነበር፡፡ ጀግኖቹ አያት ቅድመአያቶቻችን፤ ወንድ ሴት፣ ወጣት ሽማግሌ ሳይሉ “እምቢኝ ለአገሬ! በሕይወት እያለሁ አገሬን ጠላት አይገዛትም! ..” ብለው፣ ረሃብና ችግር ሳይበግራቸው በዱር በገደሉ ለአምስት ዓመት መሽገው ጠላትን ተፋልመዋል፡፡
የማታ ማታም መጋቢት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ዘመናዊ የጦር መሳሪያ፣ መድፍና መትረዬስ እስከ አፍንጫው የታጠቀውን የጣሊያን ወራሪ ጦር ተጋፍጠው (ያውም በጥቂት ኋላ ቀር ጠመንጃዎች፣ በጦር፣ በጋሻና ጐራዴ) በጀግንነት በመፋለም አጥንታቸውን ከስክሰውና ደማቸውን አፍስስው ነፃ ሀገር፣ ነፃ ኢትዮጵያን ያስረከቡን በእነዚህ ተራሮች ላይ ተዋግተው ነው፡፡
የአድዋ ሰንሰላታማ ተራሮች፣ አገራቸውን የወረረውን የኢጣሊያ ጦር ለመውጋት ከየክልሉ ተጠራርተው መጥተው ጦርነቱ በድል ሲያበቃ፣ እዚያው በቆሙበት የቀሩ ይመስላል፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል! ለወገን ጦር መሸሸጊያና መከታ፣ ለጠላት ጦር አበሳና ፈተና የሆኑት እኒያ የተፈጥሮ ተራሮች እውቅና ተሰጥቷቸው መከበር፣ መዘከርና መወደስ ቢገባቸውም፣ ዞር ብሎ ያያቸው እንኳ የለም፡፡ “የጣሊያን ወራሪ ጦር የተሸፈነበት ስፍራ” የሚል ጠቋሚ ምልክት እንኳ ስለሌለ የዛሬውና መጪው ትውልድ በቃል ከሚተላለፍለት “የአድዋ ጦርነት ድል” የሚል “ታሪክ” በስተቀር ትክክለኛ ስፍራው የት እንደሆነ ለማወቅ ያዳግተዋል፡፡ በዚህ አያያዛችን  ከቀጠለማ የ “አድዋ ድል” ተረት እንዳይሆን ያሰጋል።
እጅግ የሚያሳዝነው ነገር፣ የተፈጥሮ ጀግኖቹ መዘንጋት ብቻ አይደለም፡፡ ከመላ አገሪቱ የተውጣጡ እጅግ በርካታ የነፃነት አርበኞች ውድና ክቡር ሕይወታቸውን ቢሰጡም፣ ነገሬ ብሎ ያስታወሳቸው የለም፡፡ ለምሳሌ ከአድዋ ጦርነት እጅግ አሰቃቂና ከሁለቱም ወገን ብዙ ሺዎች ያለቁበት የምንድብዳብ ውጊያ ዋና ተዋናይ የነበሩት ወጣቱ ጄነራል ፊታውራሪ ገበየሁ ምንም የሠሩት ገድል እንዳልተነገረላቸው የእንዳአምባ ትራቭል ኤጀንሲ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ አቶ አሳየ ታረቀኝ ተናግረዋል፡፡ “ደረታቸውን ሰጥተው የጠላትን ጦር መግቢያ መውጪያ በማሳጣት  ሲተገትጉ፣ በጥይት ተመትተው ሞቱና እዚያው ምንድብዳብ ተቀበሩ፡፡ በመቃብራቸው ላይ ምልክት ስላልተደረገ በትክክል የት እንደተቀበሩ እንኳ አይታወቅም፤ በተቃራኒው ግን ጣሊያኖች ጀኔራል ዳቦርሜዳ ሞቶ በተቀበረበት ሥፍራ በድንጋይ ላይ ስሙን ጽፈው ስለተው፣ አሁን ድረስ ታሪኩ ይታወሳል” ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ጦር አሰላለፍ በአራት አቅጣጫ እንደነበር አቶ አሳየ ይናገራል፡፡ ሶሎዳ ተራራ ስር፣ ከሸዋ የመጡ 400 የኦሮሞ ፈረሰኞች መሽገው ነበር፡፡ 2ኛው ከአድዋ መውጫ፣ 3ኛው የራስ አሉላና የራስ መኮንን ጦር፣ እምባ መላክ ወይም ውጊያው በተካሄደበት ኪዳነምህረት ገሠሦ፣ በእቴጌ ጣይቱ የሚመራው 4ኛ ጦር፣ ከኪዳነምህረት ገሠሦ ጀርባና ጐን መሽጐ ነበር፡፡ የኢጣሊያም ጦር በአራት አቅጣጫ ነው የመጣው፡፡ በአራት አቅጣጫ የመጣው ባሻ አውአሎምና ሌሎች የስለላ (እንተለጀንስ) ሰዎች አሳስተው በነገሯቸው መሠረት እንደሆነ ይነገራል፡፡
ባሻ አውአሎም ሐረጐት ካልተነገረላቸው የአድዋ ጀግኖች አንዱ ናቸው፡፡ ባሻ አውአሎም በኤርትራና በትግራይ የሚመላለሱ ነጋዴ ነበሩ፡፡ ቀደም ሲል ራስ አሉላ ኢጣሊያኖችን እየሰለሉ እንዲግሯቸው፣ የኢትዮጵያን ጦር ምስጢር ደግሞ አሳስተው እንዲጠቁሟቸው ከባሻ አውአሎም ጋር ተስማምተው ነበር፡፡ በዚያው መሠረት፣ ባሻ የኢትዮጵያ ጦር ከኪዳነምህረት ገሠሦ ጀርባ ባለ ተራራ ላይ መመሸጉን ለጣሊያኖቹ ይነግራሉ፡፡ ስለዚህ ጀኔራል አርሞንዲ ጦሩን እየመራ ኪዳነምህረት ገሠሦ ተራራ ላይ ይመሽጋል፡፡ በዚህ ጊዜ እነ ራስ አሉላ በጀርባው ቆርጠው ገብተው መድፍ ሲተኩሱ ከአድዋ 10 ኪ.ሜ ወደ ኋላ መሆኑን አርሞንዲ አያውቅም ነበር፡፡ ስለዚህ፣ ለተቀረው ጦር “ገብቻለሁ” ሲል በተመሳሳይ ሰዓት ከሦስቱም አቅጣጫ ተኩስ ተከፈተበት፡፡ ጄነራል አርሞንዲ የሞተበት ውጊያ በሶስት አቅጣጫ የሚከፈል ነው፡- ኪዳነምህረት ገሠሦ፣ ምንድብብና ማርያም ሸዊት ነው፡፡ (የቦታ ስምና አቅጣጫ ስገልጽ ከተሳሳትኩ ለመታረም ዝግጁ ነኝ፡፡) ጄነራል ዳቦርሜዳ የሞተው ማርያም ሸዊቶ በተባለው ተራራ ላይ ነው፡፡ ጄነራል ባራቶሪ ደግሞ የተገደለው ራዕዮ ተራራ ላይ ነው፡፡ ጄነራል አልባርቶኒ ያመለጠው ደግሞ ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ገብቶ ተደብቆ ነው። የኢትዮጵያ ወታደሮች ከቤተክርስቲያኑ አውጥተው ያልገደሉት፣ ለቤተክርስቲያን ክብር ብለው እንደነበር ይነገራል፡፡ ጄነራል ኤሌናም በጦርነቱ ተገድሏል፡፡
ይህን በአንድ ጊዜ ሦስት የወራሪው ጄኔራሎች የተገደሉበትን፣ አንዱ ጀነራል የተማረከበትን ጦርነት ነው እኛ ኢትዮጵያውያን ችላ ብለን የዘነጋነው፡፡ የአድዋ ድል የኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን የጥቁር ሕዝቦችም ጭምር ነው፡፡ እስከ አፍንጫው ድረስ ዘመናዊ መሳሪያ የታጠቀና የማይሸነፍ የሚመስለው የአውሮፓ ቅኝ ገዥ በጦርና በጐራዴ የተሸነፈበትና የተዋረደበት በመሆኑ ክብር ተሰጥቶት ለቀጣዩ ትውልድ ታሪኩ በቅጡ መሸጋገር ነበረበት፡፡ ግን ምን ያደርጋል በእጅ ያለ ወርቅ ሆነ እንጂ!
ዘንድሮ በአድዋ ከተማ የተከበረው የድል በዓል እጅግ ደማቅ ነበር፡፡ ያደመቁት ደግሞ ከአዲስ አበባ ከእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ተነስተው 1000 ኪ.ሜ 43 ቀናት በእግራቸው ተጉዘው አድዋ ከተማ የደረሱት አምስት ተጓዦች ናቸው፡፡
ተጓዦቹ ብርሃኔ ንጉሤ፣ መሐመድ ካሣ፣ ኤርምያስ ዓለሙ፣ ሙሉጌታ መገርሳና (ደብሊው) ዓለምዘውድ ካሳሁን በአድዋ ጦርነት ወቅት የኢትዮጵያ ሠራዊት የተጓዘባቸውን መንገዶች ተከትለውና ታሪካዊ ስፍራዎችን ጎብኝተው፣ ባለፈው እሁድ በ118ኛ የአድዋ ድል በዓል መታሰቢያ ዕለት በሶሎዳ ተራራ አናት ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ አውለብልበው በዓሉ ወደሚከበርበት የተራራው ግርጌ ሲወርዱ “ሰልፍ ሜዳ” ተሰልፎ ይጠባበቅ የነበረው የአድዋ ከተማና አካባቢው ህዝብ፣ አባት አርበኞች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላትና ተማሪዎች በከፍተኛ እልልታና ጭብጨባ ተቀብለዋቸዋል፡፡ ተራራው አናት ላይ ወጥተው የተቀበሏቸውም ብዙዎች ናቸው፡፡
የዚህ ጉዞ ዓላማ ምንድነው? ሐሳቡስ እንዴት መጣ? … አንገታችንን ቀና አድርገን፣ ደረታችንን ነፍተንና አፋችንን ሞልተን እንድንናገር ምክንያት ለሆነን ለአድዋ ድል ክብርና ዋጋ የሚሰጡ ሰዎች አሉ። አባቶቻችን ባዶ እግራቸውን ተጉዘው እንዴት ነው ይህን ክብር ያጎናፀፉን? ድካማቸው ምን ይመስላል? እንዴትስ ይገለፃል? .. የሚሉ ጉጉ የአዲስ ትውልድ አባላትም አይጠፉም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሀሳብ ካላቸው ሰዎች መካከል አንዱ ሙሉጌታ መገርሳ (ደብሊው) ነው፡፡ ወደ አድዋ ደርሶ መልስ ጉዞ በእግሩ በማድረግ የአባቶቻችንን ድካምና እንግልት በተግባር ለማየት ወስኖ ነበር፡፡
ሙሉጌታ የፊልም ባለሙያ በመሆኑ የብርሃኔ ንጉሤ አጭር ፊልም ቀረፃ እንዳለ ይነገረዋል፡፡ “አሁን አልችልም፤ አድዋ እሄዳለሁ” ይላቸዋል፡፡ ይህንን ሐሳብ የሰሙት ጉዞውን አብረውት ለማድረግ ይስማሙና አምስት ሆነው፣ ቀን ቆርጠው፣ የአድዋ ድል በዓል በሚከበርበት ዕለት ከስፍራው ለመድረስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ይኼው ነው መነሻው፡፡
ተጓዦቹ በጉዞአቸው ወቅት የኢትዮጵያ ጦር ከተጓዘበት መንገድ ወጣ እያሉ ታሪካዊ ቦታዎችን አይተዋል፣ አስደሳችና አሳዛኝ ነገሮች እንዳጋጠማቸውም ይናገራሉ፡፡ ተጓዦቹ በጣም ካዘኑባቸው ነገሮች አንዱ ለአድዋ ጦርነትና ድል መነሻ የሆነው የውጫሌ ውል የተፈረመበት “ይስማ ንጉሥ” የተባለ ስፍራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ “ይስማ ንጉስ” የተባለው ስፍራ ባይኖር ኖሮ የአድዋ ጦርነት አይደረግም ነበር፤ ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን አፍሪካውያንና የዓለም ጥቁር ህዝቦች የሚኮሩበት የአድዋ ድልም አይኖርም ነበር፡፡ በድሉ ቦታ ምንም መታሰቢያ እንደሌለው ሁሉ በይስማ ንጉስም እቴጌ ከተቀመጡበት ድንጋይ በስተቀር ምንም ነገር ባለመሰራቱ በጣም አዝነናል” ብሏል ጋዜጠኛና የፊልም ባለሙያው ብርሃኔ ንጉሤ፡፡ ለመሆኑ ይስማ ንጉሥን ስንቶቻችን እናውቃለን? የቱሪስት መስህብስ የሚሆነው መች ይሆን?
ሌላው ተጓዦቹ ያዘኑበት ነገር በአድዋ ጦርነት ትልቅ ሚና ተጫውተው ብዙም ያልተወራላቸው ጀግኖች መኖራቸው ነው፡፡ ከእነዚህ ጀግኖች አንዷ እቴጌ ጣይቱ ብጡል ናቸው፡፡ እቴጌ የውጫሌን ውል ሲቃወሙ፣ “እኔ ሴት ነኝ፤ ጦርነት አልወድም፡፡ ግን እንደዚህ ዓይነት ውል ከምቀበል ሞትን (ጦርነትን) እመርጣለሁ” በማለት አፄ ምኒልክን ለጦርነት አነሳስተው በጦርነቱ ቦታ ስለፈጸሟቸው በርካታ ገድሎች ያለመነገሩ አሳዝኗቸዋል፡፡ ሴቶች በጦርነቱ ላይ የነበራቸው ሚና በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ ቀኑን ሙሉ ዕቃ ተሸክመው ይጓዛሉ፤ የወንዶቹ ጉዞ ሲያበቃ የሴቶቹ አያበቃም፤ እራት ማዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል። ይህ ብቻም አይደለም፤ ግማሾቹ ሚስቶች ናቸው፡፡ ሌሊት ተነስተው ቁርስ ማዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስለዚህ እቴጌ ጣይቱን ማክበርና ማድነቅ በዚያ ጦርነት ላይ ከፍተኛ ሚና የተጫወቱትን ሴቶች ሁሉ ማክበርና ማድነቅ ስለሚሆን እቴጌይቱን የሚዘክር ነገር መሰራት አለበት ብለዋል፡፡
ብዙም ያልተነገረላቸው ሌላው የአድዋ ጀግና ባሻ አውአሎም ሐረጎት ናቸው፡፡ የእሳቸው ሚና ባይኖር ኖሮ የአድዋ ጦርነት ምን ዓይነት መልክ ይኖረው እንደነበር መገመት አይቻልም፡፡ እሳቸውም እንደ እቴጌ ሁሉ ምንም አልተነገረላቸውም፡፡ የኢትዮጵያ ጦርነቱን በድል እንዲያጠናቅቅ ስለተጫወቱት ሚና ወጣቱ ትውልድ ማወቅ አለበት፡፡ ባሻ አውአሎም ትልቅ ታሪክ እያላቸው የተረሱ ጀግና ስለሆኑ ስለእሳቸው በሚገባ መሠራት እንዳለበት መታዘባቸውን ተጓዦቹ ተናግረዋል፡፡
የአድዋ ድል ተገቢውን ክብር እንዳላገኘም ይናገራሉ፡፡ በተለይ ሙሉጌታ መገርሳ አድዋ ድል በፍፁም ተገቢውን ክብር እንዳላገኘ ሲናገር “ብራዚል ከእግር ኳስ ሌላ በሳንባ ዳንስ (ካርኒቫል) ፌስቲቫል ትታወቃለች፤ የዓለም ህዝቦችም ሳንባ ዳንስን ለማየት ወደዚያ ይሄዳሉ፡፡ ስፔይን ደግሞ በቲማቲም የመደባደብ ባህል፣ ከኮርማ ጋር የመሯሯጥ ዓመታዊ ካርኒቫል ስላላት የዓለም ታዋቂ ሚዲያዎች ሽፋን ይሰጡታል፡፡ እዚህ ግን ለዓለም ጥቁር ህዝቦች ትልቅ ኩራት የሆነው የነፃነት መካ መዲና፣ ክብርና የሚገባውን ዋጋ ስላልሰጠነው ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ሽፋን አልሰጡትም፡፡
ይህ የነፃነት በዓል ክብርና ትኩረት አግኝቶ ቢሆን ኖሮ ከሳንባ ዳንስና ከቲማቲም መደባደብ የበለጠ ዓለም አቀፍ የሚዲያ ሽፋን ያገኝ ነበር፡፡ የአድዋ ሰንሰለታማ ተራሮችም የማይደፈር የሚመስለው የቅኝ ገዥ ኃይል አከርካሪው የተሰበረበት ዓውደ ውጊያ በመሆናቸው፤ ኢትዮጵያውያንና አፍሪካውያን ብቻ ሳይሆኑ፣ የዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች ሁሉ እንደ መካመዲና ሊሳለሙትና ሊያዩት ይገባ ነበር፡፡ ነገር ግን “ባለቤቱ ያቃለለውን አሞሌ …” እንደሚባለው ሆነና የሚገባውን ክብርና ትኩረት አጣ” ብሏል፡፡
የአድዋ ጉዞ ይቀጥላል ወይስ በዚሁ ያበቃል? በቀጣይስ የአድዋ ድል ተገቢውን ክብርና ትኩረት እንዲያገኝ ምን ይደረጋል?... የሚሉ ጥያቄዎች ቀርበውላቸው የአድዋ ተጓዦች መልስ ሰጥተዋል፡፡   
ተጓዥና የጉዞሰው አስተባባሪ በመሆን ሲሰራ የነበረው ያሬድ ሹመቴ ከአሁን በኋላ የአድዋ ጉዞ በየዓመቱ የሚቀጥል መሆኑን ተናግሯል፡፡ ቀጣዩ ጉዞ የሚቀራረቡ ጓደኛማቾች ሚያደርጉት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያውያን፣ አፍሪካውያን፣ ጥቁርና ነጭ የዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች፣የቻሉት የአድዋ ጀግኖች ባለፉት መንገድ በመጓዝ፣ ያልቻሉት ደግሞ በተለያዩ መጓጓዣዎች አድዋ ደርሰው ውጊያው በተካሄደባቸው ተራሮች ተገኝተው ድሉን እንደሚያከብሩት ያሬድ ተናግሯል፡፡
ጉዞውን ለማስቀጠል፣ አቅም ጊዜና ገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እኛ ከዚህ ስንመለስ ወደየግል ስራችን እንመለሳለን፡፡ ስለዚህ ፕሮጀክት ተቀርፆ ጉዞውን የሚያስተባብርና ተግባራዊ የሚያደርግ አንድ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡
ኮሚቴው ሙሉ ጊዜያቸውን እዚያ ላይ አድርገው የሚሰሩ ሰራተኞች ቀጥሮ ያሰራል። ዓለም አቀፍ እውቀትና የሚዲያ ሽፋን እንዲያገኝ ለማድረግ ከፍተኛ የገንዘብ አቅም ይጠይቃል፡፡ ዘንድሮም ከተለያዩ ሚዲያዎች የተውጣጡ ጋዜጠኞች በስፍራው ተገኝተው እንዲዘግቡ የተደረገው አንድ ባለሀብት ስፖንሰር በማድረጋቸው ነው፡፡ ባለሀብቱ አቶ ዳዊት ገ/እግዚአብሔር ይባላሉ፡፡ ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ፣ ዓለም አቀፍ እውቅናና የሚዲያ ሽፋን ለማግኘት ከፍተኛ ድካም ብዙ ካፒታልና ጥረት የሚጠይቅ ነው፡፡ ፕሮጀክቱን ለመጀመር አቶ ዳዊት ለጊዜው አንድ ሚሊዮን ብር ለመስጠት ቃል በመግባታቸው ለአገራቸው ሉዓላዊነት መከበር ሲሉ ደማቸውን ባፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ህይወታቸውን መስዋዕት ባደረጉ የአድዋ ጀግኖች በመላው ዓለም ነፃነት ወዳድ ህዝቦች ስም እናመሰግናቸዋለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ክቡር ዓላማ መላው ህዝብና ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች ድጋፍ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን ብሏል አስተባባሪው ያሬድ ሹመቴ፡፡
አድዋ ላንድ ማርክ የተባለ ድርጅት ደግሞ 10 በ15 በሆነ ሰሌዳ ላይ በአማርኛና በእንግሊዝኛ “አድዋ” የሚለውን ቃል በሰሎዳ ተራራ ላይ ጽፎ ለመስቀል ቦታ መረከቡን አስታውቋል፡፡
ከመንግሥትም ሆነ ከአገር ወዳድ ዜጐች ብዙ ይጠበቃል፡፡ ምንስ ቢሆን ህይወታቸውን ሰውተው ነፃ አገር ያስረከቡን ጀግኖች ታሪክ መዘከርና ለአዲሱ ትውልድ ሃቁን ማስተላለፍ ያቅተናል እንዴ? ጐበዝ! ያልተዘመረላቸውን የአድዋ አርበኞችን እንዘምርላቸው!! አውደ ውጊያዎቹንም ስፍራ እንወቃቸው!!  

Published in ህብረተሰብ

     ቅድመ ሶቅራጥስ ከነበሩ የግሪክ ፈላስፎች መካከል ታለስ የተባለው ፈላስፋ “የህይወት ምንጭ ዋናው አሃድ ውሃ ነው” ይላል፡፡ በእርግጥም ውሃ የህይወት መሰረት ነው፡፡ ህይወት ስንል ግን ሥጋዊ አካላዊውን ህይወትና መንፈሳዊውን ህይወት ማለታችን ነው፡፡ ሰው የምንለው ፍጡር የሥጋና የመንፈስ ውህድ ነው እና ሥጋዊ ማንነቱን ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ ህልውነቱን ጭምር ወስደን ለዚህ ጽሑፍ እንዲስማማን እናድርግ፡፡ የፍልስፍና፣ የሃይማኖት እና የተረት አስረጂዎችን በመጠቀም፡፡
ግዮን በጥንታዊያን ስልጡኖች፣ በታላቁ መፅሃፍና በአገር ቤት አፈ ታሪኮች ታላቁ መንፈሳዊ እሴት የሚሰጠው ወንዛችን ነው፡፡ ግዮን ከአፈጣጠሩ አፀደ ነፍስ የሆነችው ገነትን ከሚያጠጡት አራቱ ወንዞች አንዱ ነው/ ኤፌሶን፣ ጤግሮስ፣ ኤፍራጥስ እና ግዮንን አስታውሱ፡፡ ለሥጋዊ ህይወት አስፈላጊ ከሆኑት ውሃዎችም በላይ የነፍስና መንፈስ ማረፊያ የሆነቸውን ገነትን የሚያለመልም ነው። ለወንዝ ወንዝማ ሚሲሲፒም፣ ቮልጋም፣ ፊያም ወንዝ ናቸው፤ ግና ነፍስና ገነትን ማጠጣት ከቶ አይቻላቸውም፡፡ ምክንያቱም ግዮን አይደሉማ! ግዮን እኮ ከዕጸ ህይወት ሥር የሚመነጭ ወንዝ ነው/ባህሪ ሐሳብን ይመልከቱ፡፡ ዕጸ ህይወት ደግሞ ዘለዓለማዊ ህይወትን የምታስገኝ ፍሬ የምታፈራ ዛፍ ናት፡፡
ኢትዮጵያ በራሷም ሆነ በሌሎች አገሮች አፈታሪክ፣ መለኮትና የደቂቅ መለኮት መኖሪያ መሆንዋ የተመሰከረ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን የአማልክት ልጆች መሆናቸውን፣ ኢትዮጵያም የአማልክት መኖሪያ ምድር መሆንዋን ብዙዎች ጥንታዊያን ማህበረሰቦች አጥብቀው ይስማማሉ። ሌሎችም ባይመሰክሩ እንኳ አይክዱም/የግሪክና የግብጽ ጥንታዊ ጽሁፎችን ይመልከቱ/፡፡ የአማልክት መኖሪያ ስንል ምን ማለታችም እንደሆነ ለማሳየት እንዲረዳን የግሪኩን ፈላስፋ አፍላጦንን በአስረጅነት እንጠቀም፡፡ The Republic በሚለው ድርሳኑ ውስጥ ነገረ ህላዌን (ዲበ አካል/metaphysics) ሲያብራራ፣ ሁለት ዓለማት መኖራቸውን ማለትም የመሆን ዓለም  (ዓለመ ህላዌ/world of being) እና ዓለመ አምሳያ (world of becoming) ብሎ ከፍሎ ይገልጻቸዋል፡፡
ሀ) ዓለመ ህላዌ (የመሆን ዓለም/world of being) እውቀት፣ እውነት፣ ፍትህ፣ ውበት፣ መልካምነት ወዘተ አማናዊ፣ ደገኛ፣ አልፋ ኦሜጋ፣ ቀዋሚ ባህሪያት ያሉዋቸው ነገሮች የሚኖሩባት ሲሆን በዓለመ ህላዌ መመሳሰል፣ ቅዠት፣ ጥላ፣ ብዥታ፣ ወዘተ የሚባል ነገር የለም፤ ሁሉም ነገር የምር ነው። የምር በቃ፤ በራሱ እርግጥ የሆነ ነው፡፡ እውነትና እውቀት መኖሪያቸው በዚህ ነው፡፡ የማይለዋወጥ፣ ዘመን የማይሽረው፣ ጊዜና አውድ የማይቃወመው እውነት መገኛው በዓለመ ህላዌ ነው፡፡ በዚህ መሰረት በጸና እውነት ላይ የሚመሰረት እውቀትም እርግጠኛነቱ የታመነ ዘለዓለማዊ፣ ምክንያታዊ፣ ጽኑ እና በሁሉም አመክንዮ ተቀባይነት ያለው ነው፡፡ ይህ የጠቢባን ልቦና ምጥቀት እና የጥበባቸው ረቂቅነት የሚመረምረው እውነት ነው፤ ለሚተጉት ለሚሹት አስመሳይነት ቦታ የላቸውም፤ ቅዠትና ብዥታም የህይወት ጎዳናቸውን አያስተጓጉለውም፡፡
ትክክለኞቹን ዋነኞቹን የእውቀት፣ እውነት፣ ፍትህ፣ ውበት፣ መልካምነት ወዘተ ምንጮቹን ያውቃል፤ የዓለመ ህላዌ ሰው፡፡ በምክንያት በምርምር፣ በአልቦ መድሎ እና በአልቦ ስሜት ብቻ ይመረምራል አለመ ህላዌ፡፡ ዛሬ ምን እየተካሄደ እንዳለና ነገ ምን ሊመጣ እንደሚችል በእርግጠኝነት፣ በጽኑ እምነት፣ በጠራ እውነት ላይ ተመስርተው ይታወቃሉ፤ ምክንያቱም በዓለመ ህላዌ ያሉት ነገሮች ሁሉ ዘለዓለማዊያን ናቸው፡፡ ይህ ዓለም (ዓለመ ህላዌ በሌላ ታላቅ ፈላስፋ በቅዱስ አውግስጦስ/St. Augustine ደግሞ ሃገረ ኢየሩሳሌም/the city of Jerusalem ይባላል፡፡)
ለ) ዓለመ አምሳያ/ World of Becoming/ ይህ ደግሞ የዓለመ ህላዌ የእውቀት፣ እውነት፣ ፍትህ፣ ውበት፣ መልካምነት ወዘተ ቅጅዎች፣ ጥላ፣ ግልባጭ፣ አምሳያዎች መኖሪያ እንደ ማለት ነው፡፡ የአምሳያ ዓለም እርግጠኝነት አያውቅም፣ እራስን የመሆን ነገር የለውም፣ ዘለዓለማዊነት አልሰረጸውም፣ አመክንዮ አይዛመደውም፣ እውቀት አይዋሃደውም፣ ከእውቀት እጅግ የራቀ ነው፡፡ ንፋስ፣ ወዠቦ፣ ሞገድ የሚያነዋውጠው ዓለም ነው ዓለመ አምሳያ፡፡ መርጋት፣ መቆም፣ ሚዛናዊነት ባህሪያቱ አይደለም፡፡ ሁሉም ነገር ተለዋዋጭ ነው፤ የአፍታ ህላዌ የሚያባክነው ቀልበ ቢስ፣ ከጥላው የተጣላ ዓለም ነው፤ ዓለመ ህላዌ፡፡ መታመንን፣ ማስረገጥን፣ ቋሚነትን፣ ህልውነትን ማሳየት የማይቻለው ዐውዳዊና አስመሳይ ዓለም ነው፤ እውቀትና እውነትን ዓለመ አምሳያ ውስጥ ፈልጎ ማግኘት አይቻልም፤ ምክንያቱም ሁሉም ነገር በድለላና በሽንገላ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ነው፡፡ ፈላስፋው ቅዱስ አውግስጦስ ሃገረ አቴና/ the city of Athens/ ይለዋል፤ አለመ አምሳያን፡፡ የአለመ አምሳያ እውነት አማናዊ አይደለም፤ ጥላ ነው፤ ብርሃናዊ አይደለም ብዥታ ነው፤ ዘለዓለማዊ አይደለም ጊዜያዊ ነው፤ መልስ የሚሰጥ አይደለም የሚሸነግል ነው፡፡ በጥበብ በምርምር፣ በአመክንዮ ሳይሆን በስንፍና በቧልት፣ በሰበብ ላይ የተመሰረተና የሚመራ፣ በጠቅላላው ስሜት እና ወኔ የሚያደላበት ዓለም ነው፤ ዓለመ አምሳያ፡፡ ለዕለት፣ ለስሜት፣ ለገለፍተኝነትና ለደምፍላት መገዛት ዋና መገለጫ ባህሪው ነው፤ ዓለመ አምሳያ፡፡
ጉዳዩን የበለጠ ግልጽ ለማድረግ አፍላጦን የሁለቱን ዓለማት ልዩነት ለማስገንዘብ የተጠቀመበትን ታሪክ እዚህ ጋር ብንጠቅሰው መልካም ይሆናል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ በአንድ ዋሻ ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ነበሩ፤ ወደ ኋላና ወደ ጎን ማየት እንዳይችሉ በሰንሰለት ታስረዋል፤ ማየት የሚችሉት ፊት ለፊት ብቻ ነው፡፡ ከፊት ለፊታቸው ባለው ዋሻው ግድግዳ ላይ የሚታየው የጥላ ቅርጻ ቅርጾች ናቸው፡፡ ከሰዎቹ ጀርባ ባለው የዋሻው ቀዳዳ በሚገባ ጥቂት ብርሃን አማካኝነት የሚፈጠሩ የጥላ ቅርጻ ቅርጾች፣ ከፊት ለፊታቸው ባለው የዋሻው ግድግዳ ላይ ለሰዎቹ ይታያቸዋል፡፡ በዋሻው ውስጥ ያሉ ሰዎች የሚያውቁት እውነት እና እውቀት ቢኖር ይሄው ለዘመናት በዋሻው ግድግዳ ላይ ሲፈራረቅ የሚያዩት ጥላ ነው፡፡ ዋሻው ውስጥ ብዙ አመት ያሳለፉት እና ጥላዎችን የሚመራመሩት የጥላዎችን ዑደታዊ እንቅስቃሴ፤ ንግስናቸው፣ ጭፈራቸው ነው (ጎጃሞች ሰተት ብለው ቆመው የሚንቀጠቀጡት እስክስታ ከዓባይ ፏፏቴ የተቀዳ መሆኑን ልብ ይሏል) በአጠቃላይ ግዮን ለኢትዮጵያዊያን ማንነት እና ባህል ሆኗቸዋል፡፡ ተረቶች እና ምሳሌዎችንም ሳንረሳ (ዓባይ አረጀ አሉ ሽበት ቀላቀለ፤ አንድ ሰው ብቻውን ይሻገር ጀመረ)፡፡ ሌላው ይቅርና የዓባይ አካባቢ ሽፍታና የሌላው አካባቢ ሽፍታ ያላቸው ግርማ መደንግጽ እጅግ የተለያየ ነው፡፡
ግዮን ለኢትዮጵያዊያን አድባር፤ የስልጣኔ ምንጭ፤ የልማት ልዑክ ነው፡፡ ግዮን የእህል ውሃ መወሰኛ፤ የኮከብ መቁጠሪያ፤ መንገድ መሪ፤ ዘመን ቀያሪ ቀመራቸው ነው፡፡ የጥም መቁረጫ፣ የሃሳብ መወጠኛ፣ የአልገዛም ባይነት፣ የጀግንነት የታላቅነት ግርማ ነው፤ ለኢትዮጵያዊያን፡፡ የኢትዮጵያዊ ልቡ እንደ ግብረ ጉንዳን ታታሪ፣ እንደ አንበሳ ደፋሪና እንደ ጠቢብ ተመራማሪ ነው፡፡ ጉልበቱን ከክህሎቱ አጣምሮ ለዘላለም ምስክርነት የተከላቸው ውቅርና ትክል ድንጋዮች የታታሪነቱ ምስክር ናቸው (አክሱም፣ ላሊበላ፣ ጢያ ወዘተን ያስታውሱ)፡፡ ጦሩን ሰብቆ ጋሻውን ነጥቆ አፈር ከድሜ ያበላቸው ጠላቶቹ ለኢትዮጵያዊ ደፋር ልቦና ምስክር ናቸው (ግብጾችና ጣልያንን ልብ ይሏል)፡፡ ፍትህ አዋቂነቱን፣ ተመራማሪነቱን፣ የጽድቅ ፍቅሩን ለማስረገጥ ደግሞ ወደየ ቤተ አምልኳችን ብቅ ማለት ነው፡፡ ዋቂ ፈታ፣ መስጅድ፣ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ሲመሰክሩለት የኖሩት የጠቢባን ልቦና የሚያፈልቀውን እውቀት ነው፡፡
ግዮን እና ኢትዮጵያ ታዲያ በዓለመ ህላዌ ያሉ ምጡቃን ረቂቃን እንጅ፤ በግዘፈ አካል በሚኖርበት ዓለመ አምሳያ ውስጥ ብቻ ያሉ አይደሉም፡፡ ግዮናዊያን ቋንቋቸው ግዕዝ ነው። ረቂቅነታቸውን መግለጫ፣ ህልውነታቸውን ማወጃ፣ ሰማያዊነታቸውን መመስከሪያ መሳሪያቸው ግዕዝ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊና ግዮን መግባቢያቸው፣ ነገዳቸው፣ ብሔራቸው ግዕዝ ነው፤ ምክንያቱም ግዕዝ እንደ ኢትዮጵያና ግዮን ሁሉ ጥንታዊ ነውና፡፡ ኢትዮጵያዊና ግዮን ነፍስና ስጋቸው የሚጣመረው በግዕዝ ነው፡፡ ኢትዮጵዊ እና ግዮን በሁለቱም ዓለማት ህልው የሚሆኑት በግዕዝ ነው፡፡ ኢትዮጵያን እና ግዮንን በዓለመ አምሳያና በዓለመ ህላዌ ለመረዳት የግዕዝ መሰላልን መጠቀም ግድ ይላል፤ በግዕዝ መሰላል ከዋሻው (ጎጥ፣ ቀበሌ፣ ጎሳ፣ ቅራቅንቦ) ሰንሰለቱን በጣጥሶ ሽቅብ ወደ ጸሐይ (ወደ ሰውነት፣ ወደ ንጽህና) ማረግ ይጠይቃል፡፡ ኢትዮጵያዊ፤ ታታሪ ደፋሪና ተመራማሪ ልቦናውን በተዋህዶ አንግቦ አንገቱን ቀና ማድረግ ይገባዋል፡፡ ግዮንን በሰቂለ ህሊና፣ በቁመተ አካል ነው መመርመር ያለብን። ስንቀመጥ ነው ሁሉም ነገር ትልቅ መስሎ የሚታየን፡፡ ስንቆም ስንመረምረው እንበልጣለን እንጅ አናንስም፡፡ የተቀመጣችሁ ተነሱ! ወደ ፀሐይ ተመልከቱ!!

Published in ህብረተሰብ
Page 12 of 17