Administrator

Administrator

      በምስራቅ ሐረርጌ ዞን “ጫት አምራች” የተባሉ አካባቢዎች ላይ ከፍተኛ ቀረጥ በመወሰኑ ሳቢያ፣ ጫት አምራች ገበሬዎችና ነጋዴዎች ለስደት መዳረጋቸው ተሰምቷል፡፡ በጫት ምርት ላይ የተጣለው ከፍተኛ ቀረጥ በጫት ንግድ ቤተሰቦቻቸውን የሚያስተዳድሩ ዜጎች የዕለት ጉርሳቸውን እንኳን ለማግኘት ተፈታትኗቸዋል ነው የተባለው፡፡


ከሁለት ዓመታት ወዲህ ተወስኗል የተባለው ከፍተኛ የጫት ቀረጥ ባስከተለው ጫና፣ ገበሬዎች ለነጋዴዎች ጫት የሚያስረክቡበትን ዋጋ እንዲያረክሱ እንዳስገደዳቸው የዞኑ ነዋሪዎች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። በአንድ ኪሎ ግራም ጫት ከፍ ያለ ቀረጥ መጣሉን የጠቆሙት ነዋሪዎቹ፤ ይህም ከፍተኛ ቀረጥ ጫናውን አምራች ገበሬዎች ላይ ማሳረፉን አስረድተዋል።
“ቀረጡ የተወሰነው ከሁለት ዓመታት ወዲህ ነው” የሚሉት ነዋሪዎች፣ ይህም በሕጋዊ መንገድ  ወደ ሶማሊያ (ሞቃዲሾ)፣ ሶማሊላንድና ፑንትላንድ የሚላከውን የጫት መጠን በእጅጉ እንደቀነሰው ይገልጻሉ።
አቶ አብዲሳ የተባሉ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን በጫት ንግድ ላይ የተሰማሩ ነጋዴ እንደ ገለፁት፣ ቀደም ሲል ለጫት የሚከፈለው ቀረጥ በአንድ ኪሎግራም 5 ዶላር ነበር።
ከሁለት ዓመት ወዲህ ግን ወደ ሶማሊያ የሚላከው ጫት ላይ በአንድ ኪሎግራም 10 ዶላር (570 ብር ገደማ) ቀረጥ መጣሉ፣ በነጋዴው ላይ ጫና በመፍጠሩ ጫትን ከገበሬዎች በርካሽ ዋጋ እንዲረከብ ማድረጉን  ይገልጻሉ። ቀረጡን ላለመክፈል ሲሉም በርካታ ነጋዴዎች ሕገ ወጥ አካሄድ መምረጣቸውንም ጠቁመዋል።


የንግድ እና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ያደረገው ጥናት ለዚህ ከፍተኛ የቀረጥ ጭማሪ አስተዋጽዖ ማድረጉን የሚናገሩት ነጋዴው፤ በተለይ ጥናቱን ባደረገው ቡድን ውስጥ የተካተቱት ባለሙያዎች “ስለጫት አመራረትና የሽያጭ ሂደት ጥልቅ ዕውቀት የሌላቸው መሆናቸው”  ለችግሩ ያስረዳሉ፡፡
“ቀደም ሲል ጫት ወደ ሶማሊያ ተወስዶ፣ በዶላርም፤ በሶማሊያ ሽልንግም፤ በብርም ይሸጥ ነበር። ነጋዴው ሁሉ ከዚያ ሽያጭ የተገኘውን ብር ሰብስቦ፣  ወደ ባንክ ያስገባል። ይሁንና የውጭ ምንዛሬ ዋጋ መጨመሩን ተከትሎ ነጋዴው ሕገ ወጥ ንግድን መረጠ” ብለዋል - አቶ አብዲሳ ለአዲስ አድማስ።
በሌላ በኩል፣ መንግስት ከምስራቅ ኦሮሚያ ዞኖች ወደ ሶማሊያ ክልል በቀን የሚገባው የጫት መጠን ወደ 17 ሺህ እንዲወርድ ወስኖ የነበረ ቢሆንም፣ በቅርቡ የጫት ኮታው ወደ 127 ሺህ ኪሎግራም እንዲመለስ መደረጉን አቶ አብዲሳ ያወሳሉ። ግን ውሳኔው የጫት ዋጋን ከመርከስ አላዳነውም ይላሉ።


ይህም ሕገ ወጥ ንግድ መንግስት በተለያዩ አካባቢዎች ያቋቋማቸውን ኬላዎች ጥሶ በማለፍ የሚከወን እንደሆነ ነጋዴው ያብራራሉ። ንግዱን ለማቀላጠፍ ሲባል፣ ለአንድ ‘አይሱዙ’ የጭነት መኪና እስከ 300 ሺህ ብር ድረስ በየኬላው ለሚገኙ የጸጥታ አካላት ጉቦ እየተሰጠ እንደሚታለፍ ነጋዴው ጠቅሰዋል።
የጫት ቀረጡ ምዕራብ እና ምስራቅ ሐረርጌ ላይ ተጽዕኖውን ቢያሳርፍም፣ በተለይ ምስራቅ ሐረርጌ ላይ ያደረሰው ጉዳት የከፋ መሆኑን አቶ አብዲሳ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል። “የጫት ምርቱን ወደ ሶማሊያ በብዛት የሚልከውና፣ ሌሎች አማራጭ ምርቶችን የማያመርተው የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ስለሆነ፣ ጉዳቱ የከፋ ሆኖበታል።” ብለዋል።
በጋራ ሙለታ፣ ኦቦራ፣ ፈዲስ እና ጃርሶ አካባቢዎች የሚኖሩ ጫት አምራች ገበሬዎች የዕለት ጉርሳቸውን ለመሸፈን እያዳገታቸው መምጣቱ የጠቀሱት የዞኑ ነዋሪዎች፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ገበሬዎች ከቀዬአቸው ተፈናቅለው ወደ ሐረር፣ ድሬደዋ፣ አዲስ አበባና ጅግጅጋ መሰደዳቸውንም ተናግረዋል።


እነዚሁ ጫት አምራች ገበሬዎች ከዚህ በፊት ለጫት ምርት ስራ የሚጠቀሙባቸውን የውሃ ፓምፕና ጄኔሬተሮች፣ እንዲሁም የመኖሪያ ቤታቸውን የብረት በር ከመሸጥ አንስቶ እስከ ማገዶ እንጨት ለቀማ ድረስ የጉልበት ስራዎችን በመስራት የዕለት ጉርሳቸውን ለመሸፈን እየጣሩ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ አክለው ገልፀዋል።
የምስራቅ ሐረርጌ ዞን አስተዳደርም ሆነ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት አልሰጡም የሚሉት ነዋሪዎቹ፣ ችግሩ አስቸኳይ መፍትሔ ካልተበጀለት፣ ችግሩ እየሰፋና እየከፋ እንደሚመጣ ነው ያስጠነቀቁት።
በጉዳዩ ዙሪያ ማብራሪያ ለመጠየቅ ወደ ምስራቅ ሐረርጌ አስተዳዳሪ ወይዘሮ ሚስኪ መሐመድ ዘንድ በተደጋጋሚ ስልክ ብንደውልም፣ ሙከራችን ሳይሳካ ቀርቷል፡፡



በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ስልጤ ዞን፣ ስልጢ ወረዳ የበልግ ዝናብ ባስከተለው ጎርፍ ከ130 በላይ አባወራዎች ከመኖሪያ ቤታቸው መፈናቀላቸው ተነግሯል። ለበልግና ለመኸር የተዘጋጀ የእርሻ መሬት በጎርፍ እንደተያዘም ተገልጿል።
የዞኑ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ሃላፊ ወይዘሮ ወሲላ አሰፋ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ ከመደበኛው መጠን በላይ እየጣለ በሚገኘው የበልግ ዝናብ ሳቢያ ጎፍለላ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑ 132 አባወራዎች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለዋል።
150 ቤቶች እና 235 ሄክታር የእርሻ መሬት በጎርፍ እንደተያዙም የጠቆሙት ሃላፊዋ፤ አደጋው በሰዎች ሕይወትና ንብረት ላይ የከፋ ጉዳት እንዳያደርስ ጥረት መደረጉን አመልክተዋል።
“በአሁኑ ሰዓት ከመኖሪያ ቤታቸው የተፈናቀሉ አባወራዎች በጊዜያዊ መጠለያ እንዲጠለሉ አድርገናል” ያሉት ሃላፊዋ፣ ከፌደራልና ክልል ተቋማት ጋር በመቀናጀት ለእነዚሁ ተፈናቃዮች የምግብ ዕርዳታ እየተሰጠ መሆኑን ገልፀዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ሃላባ ዞን በደረሰው የጎርፍ አደጋ የአምስት ሰዎች ሕይወት ማለፉን የዞኑ አስተዳደር ማስታወቁ የሚታወስ ነው። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ)፣ አንድ ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ መሆናቸውን በቅርቡ ባወጣው ሪፖርት አመልክቷል።



የአገራችንን የግማሽ ምእተ አመት የፖለቲካ የኢኮኖሚና የማህበራዊ  እንቅስቃሴ የሚያስቃኘው  የኮሎኔል መርሻ ወዳጆ አዲስ መጽሐፍ፣ የፊታችን እሁድ ግንቦት 11 ቀን 2016 ዓ.ም  ከቀኑ 8 ሰአት ጀምሮ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጽሐፍት ኤጀንሲ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ የመጽሐፉም ርእስ  ”በሦስቱ መንግስታት ያጋጠሙኝ እድሎችና ተግዳሮቶች”  የሚል ነው፡፡

ደራሲው፣ ከፖሊስ መኮንንነት አንስቶ እስከ ሚኒስትርነት ባለው የሥራ ህይወታቸው  ኃላፊነታቸውን በብቃት ለመወጣት የቻሉ መሆናቸው ተጠቁሟል፡፡

የኢትዮጵያ ፖሊስ ኮሌጅ (አባዲና)  ዋና አዛዥ በመሆን ያገለገሉት ኮሎኔል መርሻ፤ ከቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዩኒቨርሲቲ  የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በፖለቲካል  ሳይንስና  በኢኮኖሚክስ ያገኙ ሲሆን፤ በአሜሪካና በህንድም  የሁለተኛ ዲግሪ  ትምህርታቸውን  ተከታትለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፖሊስ ሰራዊት የላቀ ደረጃ ላይ እንዲደርስ ካደረጉት ከብርጋዴር ጄነራል ጽጌ ዲቡ ጋር በቅርበት የመሥራት እድል ያገኙት  ኮሎኔል መርሻ ወዳጆ፤ ከጄነራሉ ጋር በመሆንም ሰራዊቱን የማቋቋም ሚና ተጫውተዋል፡፡

ኮሎኔል መርሻ፣ የማእከላዊ ፕላን ኢንስፔክሽን መምሪያ ኃላፊ ሆነው የሰሩ  ሲሆን፤ በ1977 ዓ.ም  የአገር ውስጥ ንግድ ሚኒስትር በመሆንም አገልግለዋል፡፡

በ423 ገጾች የተቀነበበው  መጽሐፋቸው 3 ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ ከልጅነት እስከ ዕውቀት ያሳለፉትን ህይወት  ዳስሰውበታል፡፡ ይህንን የሥራና የህይወት ታሪካቸው የተካተተበት መጽሐፍን አዘጋጅቶ ለማሳተም 3 ዓመት ያህል እንደወሰደባቸውም ኮሎኔሉ ተናግረዋል፡፡

”በሦስቱ መንግስታት ያጋጠሙኝ እድሎችና ተግዳሮቶች” የተሰኘው የኮሎኔል መርሻ ወዳጆ መጽሐፍ በ750 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

የፊታችን እሁድ የሚካሄደውን  የመጽሐፍ ምረቃ መርሐ-ግብር የሚያዘጋጀውና የሚያስተባብረው  ተወዳጅ ሚድያ እና ኮሚኒኬሽን መሆኑ ታውቋል፡፡

ከዚህ ቀደም ለህዝብ ባቀረበቻቸውና ከፍተኛ ተወዳጅነት ባገኘችባቸው ”ላሊበላ“ ፣ ”ገዳም“ ፣ ”በላልበልሃ“ በተሰኙ ነጠላ ዜማዎቿ  የምትታወቀው ድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ”ማያዬ“ የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበሟን የፊታችን አርብ ትለቃለች፡፡

ሰርቶ ለማጠናቀቅ ዘጠኝ ዓመት እንደፈጀ የተነገረለት አዲሱ የሙዚቃ አልበም 12 ያህል ዜማዎች የተካተቱበት ሲሆን፤ አንጋፋው ናሆም ሪከርድስ ፕሮዱዩስ አድርጎታል፡፡

በዚህ የሙዚቃ አልበም ውስጥ ኤልያስ መልካን ጨምሮ አንጋፋና ወጣት የሙዚቃ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

አዲሱን የሙዚቃ አልበም  አስመልክቶ ዛሬ ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም ረፋዱ ላይ ድምጻዊቷና የሙዚቃ ባለሙያዎች በማርዮት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተነገረው፤ አበጋዝ ክብረወርቅ፣ ኤልያስ መልካ፣ ሚካኤል ሃይሉ፣ ታምሩ አማረ፣ አዲስ ፍቃዱና ብሩክ ተቀባ በቅንብር፤ ወንድወሰን ይሁብ፣ ናትናኤል ግርማቸው፣ ሀብታሙ ቦጋለ፣ ጥላሁን ሰማው፣ በግጥም ሲሳተፉ፤ ኤልያስ መልካ፣ አንተነህ ወራሽ፣ እሱባለው ይታየው፣ ብስራት ሱራፌል፣ ዘርአ ብሩክ ሰማው በዜማ ተሳትፈዋል፡፡ በሚክሲንግና ማስተሪንግ ሰለሞን ኃይለማርያም የተሳተፈ ሲሆን፤ በፕሮዱዩሰርነት ወንድወሰን ይሁብ እንደተሳተፈበት ታውቋል፡፡

”ማያዬ“ የተሰኘው የድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል አዲስ የሙዚቃ አልበም የፊታችን አርብ ግንቦት 9 ቀን 2016 ዓ.ም በናሆም ሪኮርድስ የዩቲዩብ ቻናል እንዲሁም በዓለማቀፍ የሙዚቃ መተግበሪያዎች ይለቀቃል ተብሏል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በባሌ አጋርፋ የተወለደችው ድምጻዊቷ፤ የሁለት ሴት ልጆች እናት ስትሆን፣ ላለፉት 10 ዓመታት በትወናና በድምጻዊነት የኪነጥበብ ዘርፍ ስታገለግል መቆየቷ ተጠቁሟል፡፡

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቲያትር ጥበባት ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘችው ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ከዚሁ የትምህርት ክፍል በቲያትር ፎር ዴቨሎፕመንት የሁለተኛ ድግሪ እጩ ተመራቂ ናት፡፡

Saturday, 11 May 2024 00:00

የተሻለ ይገባታል

    ለአንዲት ሀገር ሁለንተናዊና የተሟላ እድገት አስተማማኝነት፣ የስርአተ ጾታ እኩልነትን ማስፈንና በተለይም የህብረተሰብና የሀገር ተፈጥሮአዊ የህልውና መሰረት የሆኑትን ሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት በማያወላዳ መልኩ ማረጋገጥ ለጥያቄ የማይቀርብ ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡
በከተማችን ባለፉት ተከታታይ የለውጥ አመታት ለትውልድ የሚተላለፉ ትላልቅና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ በመጨረስና ለህዝብ የገባውን ቃል በተግባር በማሳየት አንጸባራቂ ውጤቶችን ያስመዘገበው መንግስትም፤ የሴቶችን ጾታዊ ጥቃት ለመከላከልና ሁለንተናዊ ተሳትፎዋቸውንና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የህግ ማዕቀፎችን ከማዘጋጀት ባለፈ አስተማማኝነቱ ሊረጋገጥ የሚችለው የተጋላጭነታቸውን ምንጭ በማድረቅና አስፈላጊውን ስራዎች በመስራት ላይ መሆኑን በተግባር ለማሳየት ቆርጦ በመነሳት፣ በከተማችን አዲስ አበባ ደቡባዊ አቅጣጫ፣ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለከተማ በሀገራችን በአይነቱ የመጀመሪያው ፈርቀዳጅ የሆነ የሴቶች የተሀድሶና የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከል በከፍተኛ ጥራት ገንብቶ በማጠናቀቅ ሌላኛውን ታሪካዊ አሻራ አኑሯል፡፡


ይህ ማእከል በአንድ ዙር በሺዎች የሚቆጠሩ የጾታዊ ጥቃት ሰለባ የሆኑ እና ለማህበራዊ ቀውስ የተጋለጡ ሴቶችን ያለአንዳች ቅድመ ሁኔታ ተቀብሎ ምግብ፤ መኝታና አልባሳትን ጨምሮ ሌሎች ሁሉን አቀፍ መሰረታዊ ፍላጎቶችን አቅርቦ ከሶስት እስከ ስድስት ወራት የሚቆይ ሞያዊና ስነ-ልቦናዊ ድጋፍና ስልጠናዎችን በመስጠት ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ማእከሉ በውስጡ ከሚሰጣቸው አገልግሎቶች መካከል የስነ-ውበት ፤የሞግዚትነት ወይም የህጻናት ክብካቤ ፤የመስተንግዶ፤የአሌክትሪክና የሸክላ የእንጨት ስራዎች፤እንዲሁም የጋርመንት ስልጠና እና ሌሎች ዘርፈብዙ አገልግሎቶችን አካቷል፡፡ የግንባታ ጥራቱም እልፍ ሴቶችን ከአስከፊው የወሲብ ንግድ ወይም ከጨለማ ህይወት አርነት በማውጣት የአዲስ ብሩህ ተስፋ ህይወት ብርሃን እንደሚያጎናጽፍ ብሎም ለከተማችን ብቻ ሳይሆን ለክልል መስተዳድር እህት ከተሞችም አንድ ምእራፍ ወደፊት የሚያሻግር ተግባራዊ ትምህርት እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡


ይህ ማዕከል በክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ሀሳብ አመንጪነት የብዙሀን ሴቶች መኖሪያ በሆነችው መዲናችን በተገቢው መንገድ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን መጥቀም ያልቻሉ
ከዚህም ባለፈ ለዘርፈ ብዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የተጋለጡ መሆናቸውን በማስተዋል፣ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የረጅም ጊዜ ጥናት እንዲደረግበት አቅጣጫ በማስቀመጥና ለዘርፉ ምሁራኖች የተለያዩ ገንቢ ሀሳቦችን በማቅረብ ግንባታው ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ በመከታተል አላማውን ለማሳካት በሚያስችል መልከአ ምድራዊ አቀማመጥና ምቹ የአየር ንብረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ይህ ፕሮጀክት በተለይም ክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ የህብረተሰቡን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ሀሳቡን ከማመንጨት አንስቶ እስከ ማገባደጃው ባለው ሂደት በልዩ አይን ክትትል በማድረግ በ11 ወራት እንዲጠናቀቅ ያላሰለሰ ድጋፍና ክትትል በማድረግ፣ ችግር ፈቺ ሀሳብ የማፍለቅና ፕሮጀክቶችን የማስፈጸም አቅማቸውን በተግባር ያሳዩበት ነው፡፡ማእከሉ በውስጡ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ የየራሳቸው ኪነ-ህንጻዊ ውበት እንዲሁም የስፋትና የከፍታ ደረጃ ያላቸው ህንጻዎችን የያዘ፤ ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳዎችን፤ግዙፍ ኤልኢዲ ስክሪን የተገጠመለት የመዝናኛ አምፊ ቴአትር፤ የአትክልት እርሻ ማሳን ብሎም ከፍተኛ መጠን ያለው ንጹህ ውሃ የሚያቀርብ የራሱ የከርሰ ምድር ውሃ ጉድጓድ ከነ ግዙፍ ታንከሩ የያዘ ነው፡፡


ይህ ማዕከል የስርአተ ጾታ እኩልነትን ከማረጋገጥ እንዲሁም ለወደፊት አጠናክረን የምንከተለውን የፖለቲካ አቅጣጫ ከማመላከት አኳያ በመዲናችንም ሆነ በሀገራችን የመጀመሪያው ቢሆንም ተጨባጭ ውጤትና ስር ነቀል ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ለውጦችን እንደሚያመጣ ጅማሬው ያመላክታል፡፡ በመሆኑም ከዚህ ተቋም የሚገኘው ተሞክሮ ተቀምሮና ሰፍቶ በአጭር ጊዜ ውስጥ በእህት ክልል መስተዳድር ከተሞችና በአጎራባች ሀገራት
ትምህርት የሚወሰድበት ተምሳሌት ፕሮጀክት እንደሚሆን አያጠራጥርም፡

ፕሉታርክ እንደጻፈው የሚከተለው አፈ-ታሪክ አለ።
ከክርስቶስ ልደት በፊት በ454 ዓመት፣ ኮሪዮሳኑስ የሚባል የሮማ ወታደራዊ መሪ ነበር። በጥንታዊ ሮም ታላቅ ወታደራዊ ጀግና ነው የተባለ ነበር። በርካታ ጦርነቶችን አሸንፏል። በዚህም አገሪቱን ከብዙ ጥፋት አድኗታል ተብሎለታል። ብዙውን ህይወቱን በጦር ሜዳ ስላሳለፈ በአካል የሚያውቁት ጥቂት ሮማውያን ብቻ ናቸው። በዚህ ምክንያት ከሞላ ጎደል ወደ አፈ-ታሪክነት ተለውጧል። አፈ-ታሪክ ታሪኩ እነሆ።


በ454 (ከክ.ል.በፊት) ወታደራዊ መሪ ኮሪዩሳኑስ የጦር ሜዳ ዝናዬንና ስሜን ተጠቅሜ ፖለቲካው ውስጥ ልግባ ሲል አሰበ። ከፍተኛ የምክር ቤት እንደራሴ ለመሆን ለሚያበቃው ቦታም የምርጫ ተወዳዳሪ ሆኖ ቀረበ። የምርጫ ተወዳዳሪዎች ወደተወለዱበት ቦታ ሄደው፣ ለጎሳቸው ሰው ንግግር ማድረጋቸው የዚያን ጊዜ ባህላዊ ህግ ነበርና፤ ኮሪዮላኑስም ወደ ህዝቡ ቀርቦ 17 ዓመት ሙሉ ለሮም ሲታገል በጦር ሜዳ በጥይት የተመታባቸውን ከደርዘን በላይ የሆኑትን የሰውነቱን ጠባሳዎች እየገለጠ አሳየ። ከዲስኩሩ ይልቅ ህዝቡን እንባ በእንባ ያደረገው የሰውነቱን ጠባሳዎች ማየት ነበር። ኮሪዮላኑስ በምርጫው እንደሚያሸንፍ እርግጠኛ መሰለ።
የምርጫው ቀን ሲደርስ ኮሪዮላኑስ በድፍን የምክር ቤት አባላትና በከተማው መኳንንት ታጅቦ ወደ ምርጫው ጣቢያ ገባ። ተራው ህዝብ ይሄ ሁሉ ጉራና እመረጣለሁ የሚል ልበ-ሙሉነት ከየት መጣ አለ በሆዱ።


ኮሪዮላኑስ አብረውት የሄዱትን አብዛኛዎቹን ወገኖቹን የሚጥም ንግግር አደረገ። ሆኖም፤ ዲስኩሩ ዕብሪትና ድፍረት የተሞላበት ከመሆኑም በላይ፤ በምርጫው ያለጥርጥር እንደሚያሸንፍ፣ የጦር ሜዳ ድሎቹን እንደሚኮራባቸው የሚያሳይ ሲሆን፤ ለሱ የገዢ መደብ ወገኖች ብቻ የሚገቡ ቀልዶችን በመጨመር እየፎከረ፤ ተቃዋሚዎቹንም በንቀት በማንገዋጠጥና በቁጣ  እየወነጀለ፤ ቢመረጥ ለሮም የበለጠ ሀብት እንደሚያስገኝ ደሰኮረ። በዚህ ንግግሩ ህዝቡ የአፈ-ታሪክ ጀግናችን ይለው የነበረው ታላቁ መሪ ተራ ጉረኛ መሆኑን ታዘበ። የሁለተኛው የጉራ ንግግሩ ይዘት በአገሩ ናኘና ህዝቡ ይሄንንማ አለመምረጥ ነው ተባባለ። እንዳለውም ህዝቡ ኮሪዮላኑስን ሳይመርጠው ቀረ።
ኮሪዮላኑስ በመሸነፉ ተናዶ ወደ ጦር ሜዳው ተመለሰ። ይሁን እንጂ ያልመረጠውን ህዝብ እንደሚበቀለውና ልክ- እንደሚያገባው በምሬት ዛተ። ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በትልቅ መርከብ ወደ ሮም የሚገባውን እህል ለተራበው ህዝብ በነፃ ለማደል የምክር ቤቱ አባላት አስበው በጉዳዩ ለመምከር ተሰባሰቡ። በመካከል ግን ድንገት ኮሪዮላኑስ ብቅ አለና መድረኩን ቀማቸው። ይህን እህል ማከፋፈል በአጠቃላይ ለከተማይቱ ጎጂ ነው ሲል ተከራከረ። ጥቂቶቹን አሳመነ። በዚያም አላበቃ። የዲሞክራሲን ፅንሰ-ሀሳብ ጭምር ኮነነው። የህዝብ ተወካዮቹንና አዲሶቹን ተመራጮች በማስወገድ የከተማዋን አገዛዝ ለቀድሞዎቹ ገዢዎች (ስፓትራሺያን) መስጠት ይኖርብናል ሲል ክፉኛ ተሟገተ።


የኮሪዮላኑስን የመጨረሻውን ንግግር ህዝቡ ሲሰማ ቁጣው ወሰኑን ጣሰ። የህዝቡ ተወካዮች ደግሞ ኮሪዮላኑስ ህዝቡ ፊት ይቅረብ አሉ። ኮሪዮላኑስ ግን አሻፈረኝ፣ ህዝብ ፊት አልወጣም አለ። ከተማይቱ በሁሉም አቅጣጫ በህዝብ አመጽ ተቀጣጠለ። ይሄኔ ምክር ቤቱ የህዝቡን እንቅስቃሴ በመፍራት እህሉ ይከፋፈላል በሚለው ላይ ወሰነ። ሸንጎው በዚህ ህዝቡን ያረጋጋና እፎይ ያለ መሰለው። ህዝቡ ግን ኮሪዮላኑስ ያነጋግረን! ይቅርታ ይጠይቀን! ማለቱን ቀጠለ። ከፀፀተውና ጠባዩን አሳምሮ ሀሳቡን የሚያነሳ ከሆነም ወደ ጦር ሜዳ እንዲሄድ እንደሚፈቅዱለት ተናገሩ።
በመጨረሻ ኮሪዮላኑስ ህዝቡ ፊት ቀረበና ንግግር አደረገ። በዝግታና ለስለስ ባለ ቃና ጀመረና ቀስ እያለ ወደ ይፋ ዘለፋ ተሸጋገረ። ቃናው ሁሉ የዕቡይ ሆነ። የህዝብን ክብር የናቀ ዲስኩር ሆነ። ሰውን ማዋረድ ጀመረ። እሱ የበለጠ በተሳደበ ቁጥር ደግሞ የህዝቡ ቁጣ የበለጠ ገነፈለ። በመጨረሻ በጩኸት አፉን አዘጉት።
ሸንጎው ኮሪዮላኑስን በማውገዝ የሞት ፍርድ ፈረደበት። ዳኞቹንም እንደተለመደው ከታሪፒያ ቋጥኝ ቁልቁል እንዲወረውርና የሞት ቅጣት እንዲፈፀምበት አዘዛቸው። ህዝቡንም ውሳኔውን ደገፈ። ሆኖም ፓትሪሺያንኖቹ ጣልቃ ገብተው በመደራደር የሞት ቅጣቱ ወደ “ዕድሜ ልክ ከሥራ መገለል” እንዲሻሻል ተደረገ። የሮማ ታላቅ የጦር መሪ፤ ሁለተኛ ሮማ ከተማ ድርሽ እንደማይል ተረዳው፣ ህዝብም መንገድ ላይ ወጥቶ በይፋ ጨፈረ። እንደዚህ ያለ ጭፈራና በዓል ከዚህ ቀደም በሮማ ታይቶ አይታወቅም። የሮማ ህዝቦች ወራሪ ጠላት ሲያሸንፉ እንኳን እንደዚህ ዓይነት ፌሽታ አድርገው አያውቁም።

***


ከ2000 ዓመታት በፊት የሆነን ነገር መለስ ብሎ ያስተዋለ አያሌ ትምህርት ያገኛል።
ስንቶቻችን ራሳችንን ደገምን? ስንቶቻችን ራሳችንን በአፈ-ታሪኩ ውስጥ እናያለን? ሁኔታዎችን ስናጤን ታሪክ ብቻ ሳይሆን አፈ-ታሪክም ራሱን ይደግማል ያሰኘናል። ራስንም ወደፊት ነው እየሄድኩ ያለሁት ወደኋላ? ብሎ መጠየቁ አይቀርም። ከትላንት እስከዛሬ ተጠይቀው በግማሽ-ጎፈሬ ግማሽ-ልጩ መልክ ተመልሰው ወይም ከናካቴው ሳይመለሱ ቀርተው፣ እስከዛሬ የሚያጨቃጭቁን አያሌ ጥያቄዎች ነፍስ-እየዘሩ፣ በአካል እየተፋጠጡን (“ዴጃ ቩ” (deja vu) እንደሚባለው) “የት ነበር ያየናቸው?” የሚያሰኝ ድግግም ስዕሎች ነበሩ ዛሬም አሉ። የድንበር ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። ሀሳብ የመግለፅ፣ የመሰብሰብ፣ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ጥያቄ… ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። የሰብአዊ መብት ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። የብሔር ብሔረሰብ ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ፤ ወዘተ የሚገርመው ግን ታሪክ-ሰሪዎቹና የፖለቲካ መሪ ተናዋዮቹም ችግር ከሞላ ጎደል መደገማቸው ነው። መፈክሮችና መዝሙሮች ሳይቀሩ ሲደገሙ ማየት አስገራሚ ነው።
ለጉድ የጎለተው ሁሉንም ይታዘባል።
ገጣሚው እንዳለው፤
“ሲጨልም ስንነቃ፣ ሲነጋ ስንተኛ
እንቅልፍ እንኳ ካቅሙ መች ሞላልን ለእኛ።
ዘመን ተዘባርቆ ዓመት ተዟዟረ
ህልምም ወደ ኋላ፣ ማየት ተጀመረ”
ገዢው ፓርቲ በሙሉ አቅም የሚመራበት ሁኔታ ሲጠፋና፤ አዳዲሶች ፓርቲዎች በተደራጀ ሁኔታ የመምራት ሁኔታ ላይ ካልሆኑ፣ ሀገር ወደፊት መራመድ አቅቷት ወደኋላ እንዳትመለስ፣ ሀገር-ወዳዶች ሁሉ የሁኔታውን አሳሳቢነት መገንዘብ አለባቸው። ምን አይነት እገዛ ያስፈልጋል? ምን አይነት አቅም መፍጠር ይገባል? ብሎ ማሰብ ወሳኝነት ይኖረዋል። መድረክ ላይ ባሉ ፓርቲዎች ላይ አቃቂር ከመሰንዘር ባሻገር የእኛ አስተዋፅኦ ምን ይሁን ማለት ደግ ነው። የወቅቱ ጥሪ ይሄው ነው።
ሶስት ታዋቂ ሰዎች ስለታሪክ እንዲህ ይሉናል።
ታሪክ ራሱን ይደግማል። የታሪክ ጸሐፊ ግን አንዱን ይደግማል። (ፊሊፕ ጉዳላ- እንግሊዛዊ ፀሐፊ)
ታሪክ ራሱን አይደግምም። የታሪክ ጸሐፊ ግን አንዱን ይደግማል። (የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር)
ታሪክ ራሱን ይደግማል። ከታሪክ ስህተቶችም አንዱ ይሄ ነው (ክላርንስ ዳሮው የፈረንሳይ ጠበቃ)
ታሪክ መልኩን እየለዋወጠ ራሱን ይደግማል። በየጊዜው ግን የሚያስከፍለን ዋጋ እየጨመረ ነው የመጣው።
(ቶማስ ቤይሌ አሜሪካዊ የታሪክ ባለሙያ)
እንግዲህ የሚሰማንን መውሰድ የእኛ ፋንታ ነው።
በ1966 ዓ.ም የነበረውን ህዝባዊ እንቅስቃሴ፣ በ1983 የነበረውን የሽግግር ሁኔታና ዛሬ በሪፎርም ማግስት ያለንበትን ወቅት በሚገባ ስናጤን፣ ወደኋላ እንድናይ የሚያመላክቱ የበዙ ሁኔታዎች ስዕል እናገኛለን። ይሄ ደግሞ አሳሳቢ ነው። “ከነገር ሁሉ ምን ትጠላለህ?” ቢለው “ወደ ትላንትና መመለስ” አለ፤ የሚባለው የዚሁ ማገናዘቢያ ነው።

በትግራይ ክልል፣ ምስራቃዊ ዞን፣ ሃውዜን ከተማ የሚገኝ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ ቅርስ መዘረፉ ተሰምቷል። ቅርሱ በከተማዋ በሚገኘው እንዳ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ይገኝ እንደነበረ ተገልጿል።
ይኸው ቅርስ ከወርቅና በከፊል ከብር የተሰራ መስቀል መሆኑን አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የቤተ ክርስቲያኑ አገልጋይ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል።
ከ125 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረው ይህ መስቀል፣ በ1891 ዓ.ም. ራስ መኮንን ሃውዜንና አካባቢውን በሚያስተዳድሩበት ወቅት ለቤተ ክርስቲያኗ ያበረከቱት እንደነበር እኚሁ አገልጋይ ጨምረው አብራርተዋል። የቅርሱ መዘረፍ የታወቀው በቅርቡ ቢሆንም፣ ቅርሱ ከንብረት ክፍል እንዲወጣ የተደረገው ግን ሐምሌ 19 ቀን 2015 ዓ.ም. እንደሆነ አገልጋዩ ይናገራሉ።
ንብረቱ ከተቀመጠበት ክፍል የወጣው በቤተ ክርስቲያኗ ሰበካ ጉባዔ ዋና ጸሐፊው መልዓከ ብርሃናት አሸናፊ ወረስ ፈቃድ ሲሆን፣ የወጣበት ምክንያት ቅርሱን ለጎብኚዎች “ለማሳየት” በሚል እንደነበር እኚሁ አገልጋይ ተናግረዋል።


ይሁንና ለተወሰኑ ወራት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ሳቢያ ለሞቱ ሰዎች የፍትሐት ጸሎት በብዛት ሲደረግ በመቆየቱ፣ የቅርሱን ሁኔታ ለማረጋገጥና የት እንዳለ ለማወቅ አጋጣሚው እንዳልነበር ጠቅሰዋል።
በመጨረሻም፣ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም ቀን የመስቀሉ አለመኖር ሊታወቅ መቻሉን አገልጋዩ ያወሳሉ። ይህንንም ተከትሎ፣ የቤተ ክርስቲያኑን ቄሰ ገበዝ ጨምሮ ሌሎች የቤተ ክርስቲያኗ አገልጋዮች ቅርሱን ለማፈላለግ ቢሞክሩም ሙከራቸው አለመሳካቱን ነው የሚያመለክቱት።
የቤተ ክርስቲያኗ አገልጋዮች ለፖሊስና ለትግራይ ክልል ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ ጥቆማ ማቅረባቸውን እኚሁ አገልጋይ ገልጸው፣ ነገር ግን ተገቢው ትኩረት እንዳልተሰጠው አስረድተዋል።
የዚህ መስቀል ሙሉ መረጃ በትግራይ ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ ተሰንዶ የተቀመጠ መሆኑን አዲስ አድማስ ከተመለከተው የቅርሱ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።


አርበኛ ወይዘሪት ሆይ ከበደች ስዩምን የሚዘክር መርሃ ግብር በነገው ዕለት ቅዳሜ ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም በወመዘክር አዳራሽ ታላላቆች በታደሙበት ይከናወናል፡፡ በተጨማሪም የአርበኛዋን አንጸባራቂ ገድል የሚያሳይ  አጭር ድራማም ለታዳሚው ይቀርባል፡፡


በታሪካችን ሂደት ሴቶች  ያላቸውን አስተዋፅኦ የሚዘክር ልዩ የፓናል ውይይት ከኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች ጋር ታጅቦ እንደሚቀርብም አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡

በመርሃ ግብሩ ላይ ዶ/ር ዘካሪያስ አምደብርሀን፣ ሴቶችን ከኢትዮጵያ ታሪክ አንጻር የሚያስቃኝ ጥናታዊ ጽሁፍ የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ወይዘሮ ዮዲት አምሀ አበራ ደግሞ  የሴቶችን የስነልቦና ጥንካሬና እንዴት ይበረታታሉ? በሚለው ላይ አተኩረው ጥናታዊ መረጃ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡

 የህግ ባለሙያዋ ወይዘሮ ማሪያ ሙኒር ደግሞ  ሴቶች ከወንድሞቻቸው ጎን በመቆም  እንዴት የለውጥ ሀዋርያ ይሆናሉ? በሚለው ላይ ሀሳብ ያጋራሉ፡፡ የጅማ ዩኒቨርሲቲ የአንደኛ አመት ተማሪ  ኤልዳና ዮሀንስ በበኩሉ፤ አዲሱ ትውልድ ምን ይጠበቅበታል? በሚለው ላይ ጠንካራ ሀሳብ  እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል፡፡

በነገው ዕለት የሚታወሱትና የሚዘከሩት አርበኛ ወይዘሪት ሆይ  ከበደች ስዩም፤ የዛሬ 83 አመት በተደረገው የኢትዮጵያና የጣሊያን ጦርነት ላይ  ከፍተኛ የድል መንፈስ የነበራቸውና በጦር ሜዳው ላይም በጀግንነታቸው የተወደሱ ነበሩ፡፡

  ባለፉት 50 ዓመታት ከ8ሚ. በላይ ዜጎችን መድረስ ችሏል

  በአሁኑ ወቅት 700ሺ ዜጎች የፕሮጀክቱ  ተጠቃሚዎች ናቸው

  ትልቅ የሀገር ሃብት ነውና መከበርና መጠበቅ አለበት ተብሏል



ላለፉት አምስት አሰርት ዓመታት የቤተሰባቸውን እንክብካቤ ያጡና የቤተሰባቸውን እንክብካቤ ለማጣት በአደጋ ላይ ያሉ ህፃናትን የቤተሰብ እንክብካቤና ጥበቃ አግኝተው እንዲያድጉ ለሁለንተናዊ ዕድገታቸው የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ በማሟላት እንክብካቤ በመስጠት የሚታወቀው ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፤ የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት በዓል  በይፋ ማከበር ጀመረ።

ድርጅቱ በእነዚህ አመታት፤ በአማራጭ የቤተሰብ ክብካቤ፣ በቤተሰብና ማህበረሰብ አቅም ግንባታ፣ በአስቸኳይ ጊዜ ሰብአዊ ድጋፍ እንዲሁም በትምህርት በጤናና በወጣቶች ማብቂያ ፕሮግራሞች ከ8ሚ. በላይ ዜጎችን መድረስ እንደቻለ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡  

ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ የተመሰረተበትን የ50ኛ ዓመት ክብረ-በዓል  አስመልክቶ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በድርጅቱ ዋና መ/ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።

የኤስ ኦ ኤስ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ዳይሬክተር አቶ ሳህለማርያም አበበ ክብረ-በዓሉን አስመልክተው ሲናገሩ፤ ”ለ50 ዓመታት በቁርጠኝነት ፣በፍቅርና በብዙ ለውጦች የታጀበውን ክብረ በዓል ለማክበር በመብቃታችን ታላቅ ኩራት ይሰማናል።” ብለዋል፡፡

“ድርጅቱ ዛሬ የደረሰበት የስኬት ምዕራፍ የሰራተኞቻችን፣ የለጋሾቻችን፣ አጋሮቻችንና የምናገለግላቸው ማህበረሰቦች የጋራ ጥረትና የማያቋርጥ ድጋፍን የሚያንፀባርቅ ነው። በራስ መተማመንና በጥንካሬ የገጠሟቸውን ተግዳሮቶች ሁሉ አልፈው የትናንት ህፃናት የዛሬዎቹን ብርቱ ወጣቶች ማሳያ ነው።” ሲሉም አክለዋል፡፡


ያለፉት ዓመታት የልማት ስራዎቹንና ስኬቶቹን ለመዘከር ዓመቱን ሙሉ የሚከወኑ የተለያዩ የድርጊት መርሃ ግብሮችን ማዘጋጀቱን የገለፀው ኤስ ኦ ኤስ፤ ክብረ በዓሉ የድርጅቱን  ስኬቶችን ለማንፀባረቅ፣ ያበረከተውን  አስተዋፅኦ በጉልህ ለማሳየት፣ ድርጅቱን ያገለገሉትን ሰራተኞችና ደጋፊዎቹን ዕውቅና ለመስጠት እንዲሁም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙትን ህፃናት ለማገልገል ያለውን ቁርጠኝነት ለማሳየት ዕድል እንደሚሰጠውም አመልክቷል።

በ1966 ዓ.ም በአገራችን ለተከሰተው ድርቅ ከመንግስት ለቀረበለት ጥሪ ምላሽ ለመስጠት ወደ ኢትዮጵያ የገባው ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፣ የመጀመሪያ ሥራውን በመቀሌ የጀመረ ሲሆን፤ ዛሬ አገልግሎቱን አስፋፍቶ በ 9 ክልሎች ውስጥ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፣ “ህፃናት በፍቅር በሰላምና በሙሉ ዋስትና ሲያድጉ ማየት” የሚል ራዕይ ያነገበ መሆኑን የሚናገሩት ዳይሬክተሩ፤ምንም እንኳን ዋና  የትኩረት አቅጣጫዎቹ ህፃናት ቢሆኑም ቅሉ በአሁኑ ወቅት በማህበረሰብ ልማት ላይ በስፋት ተሰማርቶ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

በአንድ የኢመርጀንሲ ፕሮጀክት ወደ ስራ የገባው ድርጅቱ፤ ዛሬ 41 ፕሮጀክቶች ላይ እየሰራ እንደሚገኝና  ከእነዚህ ውስጥ 7ቱ ብቻ የህፃናት ፕሮጀክቶች እንደሆነ ይገልፃል። የኤስ ኦ ኤስ ዳይሬክተር እንዳስረዱት፤ የቀሩት የማህበረሰብ ልማት ፕሮጀክቶች ናቸው።



 ድርጅቱ በህፃናትና ቤተሰብ ላይ አተኩሮ ከሚያከናውናቸው ጉልህ ስራዎች ጎን ለጎንም፣ የወጣቶች ልማትና የስራ ፈጠራ፣ የአደጋ ጊዜ እርዳታ፣ የትምህርትና ጤና ስራዎችም ላይ በስፋት እንደሚሳተፍ ለማወቅ ተችሏል።

የኤስ ኦ ኤስ አመራሮች የ50ኛ ዓመት ክብረ በዓላቸውን አስመልክተው በዛሬው ዕለት ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ከሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር እንዲሁም ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ተወክለው የተገኙ ሃላፊዎች ስለ ድርጅቱ በጎ ሥራዎች  ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።

በአገሪቱ ህጋዊ ፍቃድ ተሰጥቷቸው ከሚንቀሳቀሱ 5ሺ የሚደርሱ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች መካከል ኤስ ኦ ኤስ ተጠቃሽ ነው ያሉት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን  ም/ዳይሬክተር ፤ድርጅቱ በስራውም በምግባሩም የተከበረና የተደነቀ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያው ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች  በግዙፍነቱ በአለማቀፍ ደረጃ የሚጠቀስ ነው ያሉት ም/ ዳይሬክተሩ፤ ትልቅ የአገር ሃብትና ተቋም በመሆኑ መከበርና መጠበቅ አለበት ብለዋል።

 ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ ከ1949 ጀምሮ የቤተሰብ እንክብካቤ ላጡ ህፃናት በፍቅር የተሞላ ቤተሰብ ሲሰጥ የቆየው የዓለማቀፉ የኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች ፌዴሬሽን አካል ነው።  ኤስ ኦ ኤስ በመላው ዓለም በ132 አገራት የሚንቀሳቀስ ሲሆን በዓለማቀፍ ደረጃ የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመት  እያከበረ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ነዋሪነታቸውን በአሜሪካ ያደረጉት  አቶ ጥበበ እሸቱ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ከ2.5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ የቁሳቁስ ድጋፍና ለ7ሺ500 አረጋውያን ሙሉ ወጪውን በመሸፈን የምሣ  ማብላት መርሃ ግብር አከናውነዋል፡፡  

አቶ ጥበበ ትላንት ሚያዝያ 29 ቀን 2016 ዓ.ም በመቄዶንያ ማዕከል በመገኘት አረጋውያኑን ምሣ ያበሉ ሲሆን፤ በርካታ ብርድልብሶችንና ጫማዎችንም ለማዕከሉ አበርክተዋል፡፡

ድጋፉን በማድረጋቸው  ደስተኛ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ጥበበ እሸቱ፤ ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ለመቄዶንያ የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ለማድረግም ቃል ገብተዋል።

ከዚህ ቀደም ደቡብ ወሎ ጋሸና አካባቢ በጦርነቱ ምክንያት ለተፈናቀሉ ሰዎች 150 ቤቶችን ሰርተው ያስረከቡት በጎ አድራጊው አቶ ጥበበ፤በቅርቡም በትግራይና በአማራ ክልል ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ድጋፍ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን ተናግረዋል፡፡

መቄዶንያ የበጎ አድራጎት ማህበር ምንም ጧሪና ደጋፊ የሌላቸውን በተለይም ደግሞ እራሳቸውን ችለው መንቀሳቀስ፣ መመገብና መፀዳዳት የማይችሉ የአልጋ ቁራኛ የሆኑና የሰው ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው አረጋውያንንና አዕምሮ ሕሙማንን ከወደቁበት ጎዳና ላይ በማንሳት ከ7,500 በላይ የሚሆኑ ተረጂዎችን በአዲስ አበባ፣ ደሴ፣ ድሬዳዋ፤ ሻሸመኔ፣ አድዋ፤ ባህርዳር፣ ሐረር፤ ጋምቤላ እና ጎሬ፣ መቱ፣ ጂማ፤ ሰንዳፋ በኬ፣ ሐዋሳ፣ አሶሳ፣ ጎንደር፣ ደብረማርቆስ፣ አምቦ፣ ኮረም፣ ሰመራ፣ ሰቆጣ፣ አምደወርቅ፣ ላሊበላ፣ አዲስ ዘመን፤ አምቦ እና አርባምንጭን ጨምሮ በአጠቃላይ በ25 ከተሞች ውስጥ በመደገፍ ላይ  ይገኛል።

በቀጣይም በወሊሶ፣ ሱልልታ፣ ሰበታ፣ ደብረ ብርሃን፤ ሆሳዕና፣ ዲላ፣ ጂግጂጋ  እና በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞች ላይ የበጎ አድራጎት ተግባሩን ለማከናወን  ከወዲሁ እንቅስቃሴ መጀመሩን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Page 3 of 708