በጋምቤላ ክልል የምትገኛው ፓጋግ የገጠር ቀበሌ፤ የዛሬን አያድርገውና የኮንትሮባንድ ንግድ የሚጧጧፍባት፤ ዶላር ከፓውንድ የሚመነዘርባት፤ የኤሌክትሮኒክስ እቃ የሚቸበቸብባት የድንበር ከተማ ነበረች፡፡
ዛሬ ግን የመከራና የስደት መናሃሪያ ሆናለች፡፡ የደቡብ ሱዳናዊያን ስደተኞችም ወደ ኢትዮጵያ ከሚገቡባቸው አምስት የድንበር አካባቢዎች አንዷ የፓጋግ መንደር ናት፡፡ በደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር እና በምክትላቸው ዶ/ር ሪክ ማቻር መካከል የተፈጠረ የስልጣን ሽኩቻ ውሎ ሳያድር በጐሳ ወደ ተቧደነ ግጭትና ጦርነት ከተቀየረ ወዲህ ስደት በርክቷል፡፡
በሱዳን ልዩ ወታደሮች፣ በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስና ልዩ ጥበቃ ‹‹አካባቢው ሰላም ነው›› ሊባል ቢችልም፤ በቅርብ ርቀት ከፍተኛ የተኩስ ድምፅ እንደሚሰማ ድንበር ጠባቂዎቹ ይገልፃሉ፡፡
እዚያ የደቡብ ሱዳን ስደተኞችን መዝግቦ እርዳታ መስጠት ቀላል ስራ አይደለም፡፡ የጋምቤላ ክልል ነዋሪ የሆኑት የኑዌር ብሔረሰብ አባላት በብዛት እየተቀላቀሉ መሆናቸውን የሚናገሩ የእርዳታ ሰራተኞች፤ የሱዳንና የኢትዮጵያ ዜጎችን ለመለየት እንደተቸገሩ ይገልፃሉ፡፡  
ወደ ኩሌ መጠለያ ጣቢያው ስንደርስ ስንዴ፣ አተር፣ ፋፋ፣ የአትክልት ዘይት፣ ስኳር፣ ማሽላ ለቤተሰብ ሲከፋፈል ነበር፡፡ ከየካቲት 22 እስከ ግንቦት 7 ቀን 2006ዓ.ም ድረስ ብቻ ከ51ሺህ በላይ የደቡብ ሱዳን ስደተኞችን የተቀበለው “ኩሌ አንድ” የስደተኛ የመጠለያ ጣቢያ፤ ተጨማሪ ስደተኞች ማስተናገድ ስለማይችል “ኩሌ ሁለት” በሚል ሌላ መጠለያ ተከፍቷል፡፡   
ግንቦት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. የተከፈተው “ኩሌ ሁለት” የስደተኞች መጠለያ፤ በየቀኑ ሁለት ሺ ስደተኞችን እያስተናገደ እስካሁን ሃያ ሺህ መቀበሉን አስተባባሪ ሃላፊ ላባ ለሚሳ ጠቁመዋል፡፡
ስደተኞች ለምዝገባ ከሚገቡበት የመጠለያ ጣቢያው ደጃፍ ላይ አንዲት ሴት አዛውንት በሃዘንና በትካዜ ተቀምጠዋል - በዚያ ፀሐይ በዚያ ሃሩር፡፡ ወደው አይደለም፡፡ የጠፋ ልጃቸው ይመጣ እንደሆነ ተስፋ በማድረግ እዚያው ገላጣ ቦታ በፀሐይ ሲጠበሱ ይውላሉ። ልጃቸው ከመጣ ያያቸው ይሆናል፡፡ እሳቸው ግን ማየት አይችሉም፡፡ ይሄን ያወቅሁት በኋላ-ነው ከራሳቸው አንደበት፡፡ ሴትየዋን አነጋገርኳቸው፡፡
ስምዎ ማን ይባላል?
ናኛክ ጀውዋጅ
በዚህ ጸሀይ… ለምን ወደ መጠለያው አይገቡም?
ጉዳይ አለኝ…
ከመጡ ስንት ጊዜ ሆነዎት፣ ቤተሰብ አለዎት?
አለኝ፡፡ አሁን ግን ብቻዬን ነኝ፡፡
ትተዋቸው መጡ?
በአካባቢያችን ጦርነቱ የተነሳው ባልታሰበ ሰዓትና ጊዜ ነው፡፡ ከቤቴ በራፍ ላይ ቆሜ ልጆቼን ብጣራ እንኳን የሚሰማኝ አጣሁ፡፡ መሮጥ አልቻልኩም፡፡ እጄን ያዙኝ፣ ምሩኝ እያልኩ ወዲህ አዘገምኩ፡፡ አንዳንድ ጥሩ ሰዎች ስለነበሩ ረዱኝ፡፡
እጄን ያዙኝ የሚሉት ለምንድን ነው? መራመድ አይችሉም?
መንገዱ ጉድጓድ ይሁን ድንጋይ፣ ወንዝ ይሁን ባህር ማየት አልችልም፡፡ አይነ ስውር ነኝ፡፡ (እንባቸው ይወርዳል)፡፡ ከመጣሁ አራት ቀኔ ነው፡፡ እዚህ ያደረሱኝ ሰዎች ናቸው፡፡ ከመጣሁ ሰዓት ጀምሮ ግን ከጠዋት እስከ ማታ ከዚህ ከመጠለያ ጣቢያው በራፍ አልነሳም፡፡ በአጠገቤ ኮቴ ከሰማሁ የጠፋብኝ የአስራ አምስት ዓመቱ ልጄ ሮጦ መጥቶ የሚያቅፈኝ ይመስለኛል፡፡ እናም ኮቴ ስሰማ ጆሮዬን ሰጥቼ በደንብ እሰማለሁ፡፡ እናንተ ሰላምታ ስትሰጡኝ፤ “ልጅሽ መጣ” ብላችሁ የምትነግሩኝ መስሎኝ ነበር፡፡ ከጦርነቱ ተርፎና አምልጦ ከመጣ… በህይወት ካለ..(ዝም አሉ)
እንደው አየነው የሚል ሰውም አላገኙም?
ብዙ ከብቶች አሉን፡፡ እነሱን እየጠበቀ እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡ የስምንተኛ ክፍል ተማሪ ነበር። እርሻችንንም ልጄ ነበር የሚቆጣጠረው፡፡ እንግዲህ ከአካባቢው ራቅ ብሎ ስለነበር ምናልባት ተኩሱ ደርሶበት ይሆን ብዬ እሰጋለሁ፡፡ ትናንት ከእኔ አካባቢ የመጡ ሰዎች አናግረውኝ ነበር፡፡ በቀያችን አንድም የቀረ ሰው የለም ብለውኛል፡፡  እንግዲህ መንገድ ላይም ከሆነ ወይንም በዚሁ ሰፊ ካምፕ በአንዱ ስፍራ ካለ፣ በዚህ መንገድ ሲያልፍ ሊያየኝ ይችላል በሚል ነው በዚህ ፀሃይ ቁጭ ብዬ የምጠብቀው፡፡ የልጄን ስም ለመንግስት ብትሰጡልኝልና ልጄን ቢያገኙልኝ…፡፡
የእኔ ልጅ ብቻ አይደለም የጠፋው፡፡ ብዙ ሰው ከልጆቹ ጋር ተጠፋፍቷል፡፡ አንድ ጎረቤቴ ዛሬ እዬዬ ሲል ነበር፡፡ “ሶስት ወንድ ልጆቼን በመጠለያው ዞሬ ዞሬ አጣኋቸው፣ ለወታደርነት ወስደውብኛልም” ሲል ነበር። እንግዲህ እኔስ በምን አውቃለሁ..ጦርነት ከሌለበት ሀገር ልጄ በኖረ፡፡ ምን አውቃለሁ… ምን እየበላ እንደሆነ…(መሬቱን ይዳስሳሉ፣ ደረታቸውን በሀዘን ደጋግመው ይመታሉ) ዓይነ ስውር ባልሆን እዚህም እዚያም እሄድ ነበር፡፡
በመጠለያ ጣቢያው ያገኘኋቸው ሌላ አዛውንት፣ ከመጠለያ ጣቢያው ለአንድ ወር የሚሰጣቸውን ራሽን ለመቀበል ወረፋ እየጠበቁ ነበር፡፡
ስምዎትን ማን ልበል?
ታችዋክ እባላለሁ፡፡ ከማታያ ነው የመጣሁ፡፡ መንገድ  ስንጓዝ አራት ቀን ፈጅቶብናል፡፡ በአምስተኛው ቀን ነው እዚህ የደረስነው፡፡ በረሃ ስለሆነ በእባብ መነደፍ ሁሉ ነበር፡፡ አልፎ አልፎም የሀገራችን ዘራፊዎች ስላሉ፣ ገንዘባችንን ፈትሸው ይወስዱብናል፡፡
ብቻዎትን ነው ወደዚህ አካባቢ የመጡት?
ልጆቼ ጠፍተውብኛል፡፡ ማን እንደወሰዳቸው አላውቅም፡፡ በመንደራችን ብዙ ሰው በሀዘንና በጭንቀት ተወጥሮ ነው ያለው፡፡ አካባቢያችን በጦርነቱ ተጎድቷል፡፡ ብዙ ሰው ሞቶብናል፡፡  በወባ የሞተውም ብዙ ነው፡፡ እንግዲህ ድርድሩ ጥሩ ከመጣና ሰላም ከሰፈነልን ወደ ሃገሬ መመለስ ነው የሚናፍቀኝ፡፡ የሀገራችን ሰዎች በጦርነቱ እየረገፉ እያለቁ እኮ ነው፡፡  
በምን ነበር የሚተዳደሩት?
በእርሻ ነበር የምተዳደረው፡፡ ሶስት የእርሻ ቦታና 34 ከብቶች ነበሩኝ፡፡ ነድቼ አላመጣቸው ነገር አልቻልኩም፡፡ ተዘርፈው ሊሆን ይችላል፡፡ ሁለት ሚስቶቼ እና የተወሰኑ ልጆቼ አብረውኝ መጥተዋል፡፡
ሸሽታችሁ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታችሁ በፊት በሀገራችሁ የተነሳው ግጭት ምን ይመስል ነበር?
ጦርነት ምን ቀለም አለው? እኛ የምናሳዝን ህዝቦች ነን፡፡ መሪዎቻችን በአለም እና በአፍሪካ መሪዎች አማካኝነት ካልተዳኙ ህዝባችን ገና ያልቃል፡፡ ህፃናት ሴቶች እየሞቱ ነው፡፡ ወንዶችም ይገደላሉ፡፡ እኛ ሀብታሞች ነን፡፡ ሀገራችን ሰላም ሆኖ ተመልሰን መኖር ነው የምንፈልገው፡፡


     በሥልጣኔ በተራመዱት አገራት፣ ትልቁ የፖለቲካ መከራከሪያ ምን መሰላችሁ? “የመንግስት በጀት” ነው። ታስታውሱ እንደሆነ፤ ከአመት በፊት በርካታ የአሜሪካ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በበጀት ክርክር ሳቢያ ለሳምንታት ያህል ተዘግተው ቆይተዋል፡፡
የተፎካካሪ ፓርቲዎች የበጀት ክርክር መቼም ቢሆን አያባራም፡፡ የእንግሊዝ ፓርላማ አብዛኛውን ጊዜ የሚሟሟቀው በበጀት ሙግት ነው፡፡ የጣሊያን፣ የፈረንሳይ፣ የግሪክ፣ የስፔን መንግስታት ሲንገዳገዱና ከስልጣን ሲወርዱ የምናየው፤ የአውሮፓ መንግስታት በኢኮኖሚ ቀውስ ሲወዛገቡና ጐዳናዎች በተቃውሞ ሰልፍ ሲጥለቀለቁ የምንመለከተው በሌላ ምክንያት አይደለም፤ በበጀት ጉዳይ እንጂ፡፡ በእርግጥም የፓርቲዎችና የፖለቲከኞች የአስተሳሰብ ልዩነት፣ በተጨባጭና በግላጭ አፍጥጦና አግጥጦ የሚወጣው፣ የበጀት መጠንና አመዳደብ ላይ ነው።
ወደ ነፃ ገበያ ሥርዓት የሚያዘነብሉ ፓርቲዎች፣ ለምሳሌ በአሜሪካ ሪፐብሊካን ፓርቲ፤ የእንግሊዝ ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ በተቻለ መጠን የመንግስት በጀት በየጊዜው እያበጠ እንዳይሄድ ይከራከራሉ። በአብዛኛው፣ ለፍርድ ቤቶች፣ ለህግ አስከባሪና ለመከላከያ ሃይል የሚመደበው በጀት ግን እንዲቀንስ አይፈልጉም፡፡ በተቃራኒው ለነፃ ገበያ ሥርዓት ያን ያህልም ፍቅር የሌላቸውና  ገናና መንግስት እንዲኖር የሚፈልጉ ፓርቲዎች ደግሞ፤ መንግስት ሁሉም ነገር ውስጥ እንዲገባ እየገፋፉ፣ ለዚህኛውም ለዚያኛውም በጀት እንዲጨመር ይወተውታሉ። በአጭሩ፤ የፓርቲዎች የፖለቲካ አቋም በተግባር የሚገለጠው የበጀት አመዳደብ ላይ ስለሆነ አጥብቀው ይከራከራሉ።
እንደ “አለመታደል” ሆኖ፣ በኛ አገር በበጀት ጉዳይ የሚከራከርና የሚሟገት ፓርቲም ሆነ ፖለቲከኛ ብዙ አይታይም። መንግስት ለ2007 ዓ.ም ያዘጋጀው የበጀት ዝርዝር ለፓርላማ ከቀረበ ሁለት ሳምንት አለፈው። ገንዘቡም ቀላል አይደለም። ከ178 ቢሊዮን ብር በላይ ነው። ከዜጎች ጠቅላላ አመታዊ ገቢ (ምርት) ውስጥ ሩብ ያህሉ ማለት ነው። ግን፣ ስለ በጀቱ መጠንና አመዳደብ እስካሁን ለምልክት ያህል እንኳ ውይይትና ክርክር አልሰማንም።
አንደኛ፤ የበጀቱ መጠን፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ፣ የዜጎችን ኪስና ኑሮን ይነካል። መንግስት፤ በየአመቱ የብዙ ቢሊዮን ብር በጀት የሚመድበው ታክስ በመሰብሰብና የብር ኖት በማሳተም ነው፡፡ ታክስ የሚሰበሰበው ከዜጎች ኪስ ነው። በ2000 ዓ.ም እና በ2003 ዓ.ም እንደተደረገው መንግስት የብር ኖት በገፍ አትማለሁ የሚል ከሆነም፤ በዋጋ ንረትና በኑሮ ውድነት የዜጐች ህይወት ይጐሳቆላል፡፡ ሁለተኛ፤ የበጀቱ መጠን ብቻ ሳይሆን የበጀቱ አመዳደብም የዜጐችን ኑሮ ይነካል። ለምሳሌ… ላለፉት 7 አመታት... “በዚህ ዓመት ግንባታቸው ይጠናቀቃል” እየተባለ፣ በየአመቱ ከቢሊዮን ብር በላይ ሲመደብላቸው የነበሩ የተንዳሆ፣ የከሰም፣ ከዚያም የርብ ግድቦች... በመጪው አመትም ከቢሊዮን ብር በላይ ይመደብላቸዋል። ገንዘቡ የት እየገባ ይሆን ግንባታዎቹ ለአመታት የተጓተቱት?
ሃብት በማባከን ዋና ተጠቃሽ ሆነው ለተገኙት ዩኒቨርስቲዎች የሚመደበው በጀትስ? በትምህርት ሚኒስቴር ስር ለሚተዳደሩት ዩኒቨርስቲዎችና ተቋማት፣ ዘንድሮ 25 ቢሊዮን ብር እንደሚመደብላቸው ስንሰማ፣ ይሄ ሁሉ ብር የት ይገባ ይሆን ብለን በደንብ ማሰብ አያስፈልገንም? ይህንን እንደ ዋነኛ ሥራ የሚቆጥሩ ፖለቲከኞች የሚፈጠሩት መቼ ይሆን? ምሁራንስ?

“የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ”
(የእንግሊዞች አባባል)

ከዕለታት አንድ ቀን አንደ ቀንድ - አውጣ (Snail) ወደ አንድ ቡና ቤት ከመሸ በኋላ ይሄዳል፡፡ ከዚያም በሩን ያንኳኳል፡፡
ባለቡና ቤቱ፤ በሩን ዘጋግቶ እየጨራረሰ ነው፡፡
“ማነው?” ይላል የቡና ቤት ባለቤት፡፡
“እኔ ነኝ!” ይላል ቀንድ አውጣ፡፡
“ትንሽ መጠጣት ፈልጌ ነበር”
“መሸኮ! ከዚህ ወዲያ አላስተናግድም!”
“እረ በእግዚሃር አስተናግደኝ! ምንም ሄጄ እምዝናናበት ቦታ የለኝም፡፡ የት እንደምሄድም አላውቅም! እባክህ ተባበረኝ!”
“አያ ቀንዳውጣ! እየዘጋሁ ነው ስልህ ምንድን ነው ችግርህ? ትመለሳለህ ተመለስ አለበለዚያ ዋጋህን ታገኛለህ! ተግባባን?”
“ባለቡና ቤት፤ እኔ አንድ ነገር ሳልቀምስ ወደ መኝታዬ መሄድ አልችልም! ይገባሃል?”
“ቆይ እንግዲህ እንዲገባህ ምን ማድረግ እንደምችል አሳይሃለሁ!” እያለ የዘጋውን በር ይከፍትና ይወጣል፡፡
ቀንድ - አውጣው በሁኔታው ተደስቶና የበለጠውን ዕውነት አስረዳዋለሁ ብሎ ፍንድቅድቅ ብሏል፡፡
ሰውዬው ግን ንግግሩን ሁሉ አቋርጦ በንዴት ተወጥሮ ወደውጪ መጣና፤
“አንተ ማነኝ ብለህ ነው ይሄ ሁሉ ጉራ? ይሄ ሁሉ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት?” ሲል ጠየቀው፡፡
ቀንዳውጣውም፤
“ጌታዬ፤ ውሃ ጠምቶኝ ነው ያስቸገርኩህ፡፡ እባክህ…” ብሎ ሳይጨርስ፣ ባለሆቴሉ ባለ በሌለ ኀይሉ በቲራ ጠረገው፡፡ ቀንድ አውጣው ሩቅ ከመሽቀንጠሩ የተነሳ፤ የት ሄዶ እንደወደቀ እንኳን ያየው የለም!!
ከአንድ ዓመት በኋላ ቀንድ አውጣው ወደዚያው ሆቴል መጣ፡፡ ዛሬም ሰዓቱ በጣም ረፍዷል፡፡ ያ ባለ ሆቴል በሩ ሲንኳኳ፤
“ማነው?” አለ፡፡
“እኔ ነኝ!”
“ማ?”
“እኔ ቀንድ አውጣ!”
“አንተ ዛሬም ልትለክፈኝ መጣህ?”
“አይ፤ ዛሬስ አንድ ጥያቄ ብቻ ኖሮኝ ነው የመጣሁት”
ባለሆቴሉ ወጣና፤
“ምንድን ነው የፈለከው?”
ቀንዳውጣውም፤
“አንዲት ጥያቄ ብቻ ናት ያለችኝ፡፡”
“እሺ ተናገር?”
“ባለፈው ዓመት አሽቀንጥረህ ከጣልከኝ ቦታ እዚህ ለመድረስ ተጉዤ ተጉዤ፤ ይሄው ዛሬ ደረስኩኝ፡፡ ለመሆኑ ለምን ነበር እንደዛ በቲራ የመታኸኝ?!”
*    *    *
በየትኛውም ሰዓት ያረፈደ ሰው፤ ቅጣቱ እንደተጠበቀ መሆኑን አንርሳ፡፡ ማንም በመሸ ሰዓት ረግጦ ሊያሽቀነጥረን እንደሚችልም እንገንዘብ፡፡
ማዝገማችን፣ መንቀርፈፋችንና መዘግየታችን በራሱ መልክና ጊዜ ወደኛው ፊቱን አዙሮ እንደቀንድ አውጣው ሊያስመታን መቻሉ አይቀሬ ነው፡፡ ለምን ሆነ? ብለን በዓመቱ መጠየቅ ቢያንስ መሳቂያ ከመሆን አያሳልፈንም፡፡ ሌሎች ውቴላቸውን ዘግተው ሳይቆልፉ በፊት ነቅቶ መምጣት ብልህነት ነው፡፡
የሀገራችን ስሞች አስገራሚ ናቸው፡፡ በወትሮ ማዕረጉ የሹም/የንብረት ባለቤት የምንለው፤ ስሙ የኃደራ ስም ይባላል፡፡ ባላገር፣ ወታደር፣ ባላባት፣ ስደተኛ፤ ባለቤት እንዲሉ፡፡ የሀገር ባለኃደራነት መሆኑ ነው፡፡
የማኅደር ስም የሚባል አለ ደግሞ፡፡ አደራችንን አንዘንጋ የሚል የማደሪያ ስም ነው፤ ቃሉ፡፡ በየጊዜው ቃል ስንገባም “ዕውን እፈጽመዋለሁ? እንበል፡፡ የመሬት፣ የቦታ ርስት ወዘተ ንብረት ባለቤትነት ዶሴ እንደማለት ነው፡፡ የሚገርመው የማህደርም፤ የባለኃደራም ሌብነት ነበር፡፡ የዱሮ ዘመን ባለቤትነት ከዛሬ ሊለይ ይችላል፡፡ እንደ እውነቱ ግን ሁሉም ከላይ እየታዘዘ ከመፈፀሙ አኳያ፤ የቋንቋ ነገር ካልሆነ በቀር  ሁሉም ስሙ “ሙስና” ነው፡፡
የተቀብዖ ስም እንዲል መጽሐፍ ሹመት ብቻውን ፍሬ አያፈራም! የተቀባንበት፣ የተሾምንበት፣ ኃላፊነት የተቀበልንበት ስም ያው የተቀብዖ ስም ነው፡፡ ታዲያ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋልን”፣ “ከሰው መርጦ ለሹመት፣ ከእንጨት መርጦ ለሹመት”ን እንደበቀቀን እያቀነቀንን፤ እስከመቼ እንጓዛለን? ምንም ዓይነት ኮርስ ልውሰድ፣ ዋናው ቁም ነገር፣ “ሹመቱ ለአገር እንዳገለግል፣ ኃላፊነቴን እንድወጣ ነው” እንላለን? ወይስ በሹምነቱ ዘመን ያልበላ፣ እየበላ ያለና ወደፊትም የማይበላ ማን ሹም አለ? ከበይው የሚይቋደስ፣ ባለ አላባ፣ ባለ ኮሚሽንስ ማን አለ?
ሐዲድ ተሠራ ስንል ሲመነቀል፣ አገር ያደነቀው ምሁር አፈራን ስንል፤ “አያሌው ሞኙ ሰው አማኙ” ሲለን፣ ውጪ አገር ወኪል አድርገን ስንልክ “አፍንጫችሁን ላሱ” ሲለን፤ ምን ዓይነት ተዓማኒነት ልናስተናገድ ነው?
“እያንዳንዱ አሣ አጥንት እንዳለሁ ሁሉ፤ እያንዳንዱ ሰው ስህተት አለው” ይላሉ አዋቂዎች፡፡ ሆኖም ይህን ብሂል መሠረት አድርገን ስንሳሳት፣ አውቀን ስንሳሳትና ለሁሉም ዋናው ሰበብ ማግኘት ነው ስንባል መክረማችን፤ አሳሳቢ ነው፡፡
“አንድ ‹ባሪያ› በምድር ላይ እየተጓዘ እስካለ ድረስ ያንተ ነፃ መሆን (ተዓምር) ፍፁም አልሆነም!” ይላሉ የፍልስፍና ሊቃውንት፡፡
ዕውነት ነው፡፡ የአስተሳሰብ ባርነት፣ የአመለካከት ባርነት፣ የጠባብነት ባርነት፣ የመላላት ባርነት፣ እኔን ከተከተልክ - ነፃ ነህ የመባል ባርነት፤ ዲሞክራሲን እንደፈለጉ በሚተረጉሙና በሚተገብሩ የፖለቲካ ባላባቶች መጠርነፍ ባርነት…ወዘተ ውስጥ መኮድኮድ እርግማን ነው፡፡ ስለሆነም እንዴት? ለምን? ብሎ መጠየቅ ታላቅ እርምጃ ነው!
“የመጨረሻው ከባድ የብረት በርም የሚከፈተው በትንሽ ቁልፍ ነው” (ቻርለስ ዲከንስ)
ቻርለስ ዲከንስ ትንሽ ነን ብለን ተስፋ አንቁረጥ፡፡ ችሎታና ዕውቀቱን ከያዝን የመጨረሻውን ከተምበሪ ልንከፍተው እንችላለን ሲል ነው፡፡ አንዱ የእኛ ፖለቲከኞች ችግር እራስን አሳንሶ ማየት የሚሆነው ለዚህ ነው!!
የሚከተለው አገርኛ ግጥም በልኩ ያስገነዝበናል፡፡
“ዓመት ነው?”
ዕድሜ ነው?
ስሜት ነው?
ተስፋ ነው መጪው ቀን?
ወይስ ኩራት እራት፣ ከውስጡ የቀረ፣ ትርጉም ይኖር ይሆን?”
ተስፈኝነት፣ አዎንታዊነት፣ ትዕግሥትና ጽናት ከሌሉ ለአገራችን ትግል አስተዋጽኦ አይዋጣልንም፡፡
ማርቲን ሉተር ኪንግ፤
“ዓለም ነገ ልታልቅ ነው ቢሉኝም፣ ዛሬ ዛፍ መትከሌን አልተውም” ያለን ለዚህ ነው፡፡
በአንፃሩ ትላንትም፣ አሁንም፣ ያለውን ሁኔታ እደግፋለሁ፤ አንደኛ የልማት አርበኛ ነኝ፤ አንደኛ “ኮብል ስቶኒስት ነኝ!”፤ አንደኛ አገራዊ ምሁርና የሚዲያ ተቆርቋሪ፤ የፖለቲከኛ ተንታኝ ነኝ የሚል ቢበዛ፤ ቆም ብሎ “ዕውን ነውን?” ማለት ያባት ነው! “የሚስቅልህ ሰው ስለበዛ፣ ትክክል ነኝ ብለህ አታስብ!” የሚለው የእንግሊዞች አባባል፤ ፍሬ - ጉዳይ አለው የሚባለው ለዚህ ነው፡፡


Published in ርዕሰ አንቀፅ

በኪሎ 35 ብር የነበረው በርበሬ 55 ብር እየተሸጠ ነው
በ115 ብር እንዲሸጥ የተተመነው ባለ 5 ሊትሩ ዘይት 150 ብር ገብቷል

በመዲናዋ የተለያዩ አካባቢዎች የስኳር፣ የዘይትና የዳቦ እጥረት ተከስቷል
የፍላጎትና አቅርቦት አለመመጣጠን የፈጠረው ነው ተብሏል

     ሰሞኑን በአንዳንድ መሰረታዊ ሸቀጣ ሸቀጦች ላይ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ እየታየ ሲሆን ነጋዴዎችና  የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች የአቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም ውጤት ነው ብለዋል፡፡
በተለይ የበርበሬ፣ የስንዴ ዱቄትና የምስር ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ ያሳየ ሲሆን የስኳር፣ ዘይትና ዳቦ እጥረትም መከሰቱን ሪፖርተሮቻችን በአዲስ አበባ የተለያዩ የገበያ ስፍራዎች ተዘዋውረው ባደረጉት ቅኝት አረጋግጠዋል፡፡ ሸማቾች የዋጋ ጭማሪው እንዳማረራቸው ሲገልፁ፣ ነጋዴዎች፤ የሸቀጦች አቅርቦት ከፍላጎት ጋር  አልተጣጣመም ብለዋል፡፡
ከሳምንት በፊት በኪሎ 35 ብር ይሸጥ የነበረው ዛላ በርበሬ፣ እስከ 20 ብር ጭማሪ አሳይቶ ኪሎው በ55 ብር እየተሸጠ ሲሆን በንግድ ሚኒስቴር የመሸጫ ዋጋ ተመን ከወጣላቸው ሸቀጦች አንዱ የሆነው የስንዴ ዱቄት ከ12 ብር ወደ 14 ብር ከፍ ብሏል፡፡ የምስር ዋጋም በኪሎ 21 ብር የነበረው 25 ብር እየተሸጠ መሆኑን ከተለያዩ የገበያ ስፍራዎች የተሰበሰቡ የዋጋ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
በሌላ በኩል ስኳር፣ ዘይትና ዳቦ የመሳሰሉትን እንደልብ ማግኘት እንደተሳናቸው ነዋሪዎች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ በሳሪስ አካባቢ በአንድ ዳቦ ቤት ዳቦ ለመግዛት ተሰልፈው ያገኘናቸው አቶ ወንድይፍራው ደምሴ፤ ለቤተሰቦቻቸው በየእለቱ ዳቦ እንደሚገዙ ገልፀው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደታክሲ ትራንስፖርት ሁሉ ዳቦ ለመግዛትም ሰልፍ መያዝ የግድ ሆኗል ይላሉ፡፡ ከዚህም የባሰው ግን ለረጅም ደቂቃዎች ከተሰለፉ በኋላም ዳቦ አልቋል እየተባሉ በተደጋጋሚ ባዶ እጃቸውን ወደ ቤታቸው መግባታቸው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በሳሪስ አብዛኞቹ የችርቻሮ ሱቆች ስኳር የጠፋ ሲሆን ያላቸውም ቢሆኑ ከበፊት ዋጋው  እስከ 4.50 ብር እየጨመሩ እንደሚሸጡ ሸማቾች ተናግረዋል፡፡ መሰረታዊ ሸቀጦችን በማቅረብ የህብረተሰቡን ፍላጎት ያሟላሉ በተባሉ የሸማቾች የህብረት ስራ ማህበራት ሱቆችም የአቅርቦት እጥረት እንዳለ የጠቆሙት ሸማቾች፤ ዘይት ባለ 5 ሊትሩ 115 ብር እንዲሸጥ የዋጋ ተመን ቢወጣለትም አሁን እስከ 150 ብር እየተሸጠ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በጥቂት ቀናት ውስጥ የበርበሬ ዋጋ የ20 ብር ጭማሪ ለምን እንዳሳየ የጠየቅናቸው የበርበሬ አከፋፋይ  አቶ ምሳሌ ወ/አምላክ፣ የበርበሬ ምርት በአብዛኛው የሃገራችን አካባቢዎች በስፋት የሚሰበሰበው ከመስከረም እስከ ህዳር ወር ባለው ጊዜ እንደሆነ ጠቅሰው ወደ ክረምት መግቢያ ላይ ምርት በስፋት ስለማይገኝ ዋጋው እንደሚጨምር አስረድተዋል፡፡ በአሁን ወቅት ከባሌ አካባቢ የሚመጣ በርበሬ ለገበያ እንደሚቀርብ የጠቆሙት ነጋዴው፤ አምራቾች ዋጋው ላይ ጭማሪ በማድረግ ለአከፋፋዮች እየሸጡ እንደሆነ ጠቅሰው የአቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣም መኖሩን አብራርተዋል፡፡
ክረምት ላይ የበርበሬ ብቻ ሳይሆን የብዙ መሰረታዊ ፍጆታዎች ዋጋ እንደሚጨምርም ነጋዴው ይናገራሉ፡፡ ምርቱ በሚገኝባቸው የገጠር አካባቢዎች መንገዱ ጭቃ ስለሚሆን ነጋዴው ወደ አምራቾች ሄዶ ምርቱን ለማምጣት አይሞክርም ያሉት አቶ ምሳሌ፤ ወቅቱ የእርሻ በመሆኑም ገበሬው ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ለመግዛት ሲል የምርቱን ዋጋ ያዝ እንደሚያደርገው ተናግረዋል፡፡
“የአብዛኛው ሸማች ገቢ ባላደገበት ሁኔታ የሸቀጦች ዋጋ በየጊዜው መጨመሩ ጤናማ አይደለም” ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡን በአለማቀፍ ድርጅት ውስጥ የኢኮኖሚ አማካሪ የሆኑት ባለሙያ፤ ወቅት እየጠበቀ በሸቀጦች ላይ የሚስተዋለው የዋጋ ጭማሪ አቅርቦትን ከፍላጎት ጋር በማጣጣም ረገድ እያደገ ነው የሚባለው ኢኮኖሚ ክፍተት እንዳለበት ያመለክታል ብለዋል፡፡ መንግስት ገበያውን ለመቆጣጠር መሞከሩም የችግሩ መንስኤ ነው የሚሉት ባለሙያው፤ ገበያው በምርት አቅርቦቱ መጠን እንዲመራ መንግስት መፍቀድ አለበት ሲሉ አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡
የምጣኔ ሃብት ባለሙያው ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ በበኩላቸው፤ የሸቀጦች ዋጋ መጨመርና መቀነስ የአቅርቦቱና ፍላጎቱ መጠን የሚወስነው መሆኑን ጠቅሰው፣ መንግስት ገበያ መር ኢኮኖሚ ነው የምከተለው እያለ በሌላ በኩል ዋጋ ትመና ውስጥ መግባቱ ችግር እንደሚያስከትል ይናገራሉ፡፡ መንግስት ዋጋ ከመተመን አልፎ የራሱን ጅምላ ሽያጭ እያቋቋመ መሆኑን ያስታወሱት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ አሰራሩ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ይጠቅማል ተብሎ ቢታሰብም ውጤታማ ይሆናል ለማለት አያስደፍርም ብለዋል፡፡
“በየጊዜው የጤፍ ዋጋ ቀንሷል ቢባልም ሰው መግዛት ስለተወ እንጂ በእርግጥ በሚፈለገው መጠን ዋጋው ስለቀነሰ አይደለም” የሚሉት ባለሙያው፤ የብር የመግዛት አቅሙ እየተዳከመ ከመምጣቱ ጋር ተደማምሮ ከውጭ የሚገቡ ነዳጅ፣ የምግብ ዘይት፣ ስንዴ፣ ስኳርና የመሳሰሉት ዋጋቸው በከፍተኛ ደረጃ ሊጨምር ይችላል ብለዋል፡፡
የሸቀጦችን ዋጋ በተመለከተ ማዕከላዊ ስታቲስቲክስ የሚያወጣቸው መረጃዎች ምን ያህል ትክክለኛ ናቸው የሚለው አጠያያቂ ነው የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ 90 ሚሊዮን ህዝብ ባለበት ሰፊ ሀገር አቅርቦትንና ፍላጎትን ማጣጣም ከባድ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በአዲስ አበባ ያለው የኑሮ ሁኔታ ከሌላው ለየት ይላል ያሉት አስተያየት ሰጪው፤ከተማዋ  የዲፕሎማቲክስ መዲና መሆኗ፣ የውጭ ኢንቨስተሮችና አቅም ያላቸው ሰዎች በመዲናይቱ መበራከትና ቀደም ሲል በከተማዋ ዙሪያ የነበረው ገበሬ አሁን ወደ ቀን ሰራተኝነት ተቀይሮ ሸማች መሆኑ ተፅዕኖ አሳርፏል በማለት  ያስረዳሉ፡፡ እስከ 2 ሚሊዮን የሚደርስ ገበሬ ከተማዋን ተቀላቅሎ ሸማች ሆኗል የሚል ግምት እንዳለም  ባለሙያው ተናግረዋል፡፡
መንግስት በትላልቅ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች ላይ ብቻ በማተኮር መሰረታዊ ፍላጎቶችን ችላ ማለቱ ጥቂቶች ብቻ በስግብግብነት ተጠቃሚ እንዲሆኑ በር ከፍቷል የሚሉት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ የተለያዩ የጅምላ ሽያጮች በጥቂት ሰዎች ቁጥጥር ስር መዋሉን በምሳሌነት ይጠቅሳሉ፡፡
እንዲህ ያለ የዋጋ ንረት ሲፈጠር መንግስት የተለያዩ የማረጋጊያ ስልቶችን መጠቀም እንዳለበት የጠቆሙት ምሁሩ፤ አንዳንድ መሰረታዊ ሸቀጦች በሃገር ውስጥ ሊመረቱ የሚችሉበትን ሁኔታ መፍጠር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ መንግስት አቅሙ ላላቸው ባለሃብቶች ከ500 እስከ 800 ሄክታር መሬት በመስጠት እንዲያለሙ ድጋፍ ማድረግና የምርት አቅርቦቱን መጨመር አለበት ሲሉም ይመክራሉ፡፡
የዓለም ምግብ ፕሮግራም ወደ 6.5 ሚሊዮን ሰዎች የምግብ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል የሚል ሪፖርት ማውጣቱን የጠቀሱት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ “ሃገሪቱ የ70 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ባለቤት ሆና ለግብርና አገልግሎት የዋለው 14 በመቶው ብቻ ነው፣ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የውሃ ማማ ብትባልም ዛሬም ከምግብ እርዳታ ፈላጊነት መላቀቅ አልቻለችም” ይላሉ፡፡  
መንግስት መሬት አልሚዎች ከባንክ ብድር የሚያገኙበትን ሁኔታ እያመቻቸና ተገቢውን ድጋፍ እያደረገ የምርት መጠኑን በማሳደግ፣ አቅርቦቱን ከፍላጎቱ ጋር ማመጣጠን አለፍ ሲልም ለውጭ ገበያ በማቅረብ ገቢ ማስገኘት አለበት ሲሉ የመፍትሄ ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡ መንግስት እስካሁን ትኩረት የሰጠው ለመሰረተ ልማት ዝርጋታ መሆኑን በመግለፅም “የሃገሪቱን ሃብት ተጠቅሞ የዜጎቹን የምግብ ዋስትና ወደ ማረጋገጥ ፊቱን ማዞር አለበት” ብለዋል ምሁሩ፡፡
የተባበሩት መንግስታት ተወካይ ሆነው በዚምባቡዌ ሲሰሩ፣ሮበርት ሙጋቤ ከእርሻ መሬታቸው ያፈናቀሏቸውን ነጭ ገበሬዎች አግኝተው ኢትዮጵያ መጥተው እንዲያለሙ በግል ጠይቀው እንደነበር ያስታወሱት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት ፍቃደኛ ባለመሆኑ ገበሬዎቹ አማራጫቸውን ሞዛምቢክ አድርገው በዘጠኝ ወር ውስጥ የሃገሪቱን ምርት በ3 እጥፍ መጨመራቸውን በመጥቀስ፣መንግስትም እንደነዚህ አይነት ባለሙያዎችን መጋበዝ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
የገበያ ዋጋን ለማረጋጋት የአጭርና የረጅም ጊዜ የመፍትሄ እቅድ ያስፈልጋል የሚሉት ምሁሩ፤ በተለይ አምራቾችንና ነጋዴዎችን መቆጣጠር የሚችሉ ጠንካራ የሸማቾች ማህበራትን ማደራጀት እንደሚያስፈልግ ይመክራሉ፡፡
በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የንግድ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አማከለ ይማም “የስንዴ አቅርቦትን በተመለከተ ከዚህ ቀደም በቂ ማብራሪያ ሰጥተናል፣ ደግመን አንሰጥም፤ የዱቄት ዋጋ ጨምሯል የሚባለውም ምናልባት ንግድ ሚኒስቴር ከዘረጋው የገበያ ትስስር ውጪ የሆኑ ነጋዴዎች የሚሸጡበት ዋጋን ተመርኩዞ ሊሆን ይችላል እንጂ በንግድ ትስስሩ ስር ባሉ የንግድ ተቋማት የዱቄት ዋጋ ጭማሪ አልተደረገም” ሲሉ አስተባብለዋል፡፡

Published in ዜና

ኢትዮጵያ ከ108 የዓለም ሃገራት በድህነት ከአፍሪካዊቷ ሃገር ኒጀር ቀጥላ ሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ  የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ጥናት ያመለከተ ሲሆን የኢኮኖሚ  ባለሙያዎች ሃገሪቷ ድሃ መሆኗ የሚስተባበል አይደለም ብለዋል፡፡
ሰሞኑን  ዩኒቨርሲቲው ይፋ ባደረገው የጥናት ውጤት፤ በኢትዮጵያ ከሚኖሩ ዜጎች 76 ሚሊዮን ያህሉ ድሆች ሲሆኑ በድሆች ብዛትም ከህንድ፣ ከቻይና፣ ከባንግላዴሽና ፓኪስታን ቀጥሎ ኢትዮጵያ  በ5ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ብሏል፡፡
የድህነት መጠኑን በመቶኛ ስሌት ያስቀመጠው ጥናቱ፤ ኢትዮጵያ ከአጠቃላይ ህዝቧ 87.3 በመቶው ድሃ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 58.1 በመቶው ለኑሮው አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ያልተሟሉለት ምስኪን ተመፅዋች ዜጋ ነው ብሏል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የአገራትን የድህነት ደረጃ የለካው የትምህርት፣ የጤናና የኑሮ ሁኔታዎችን መሰረት ያደረጉ አስር መስፈርቶችን  በመጠቀም ሲሆን፣ በአገሪቱ በገጠር ከሚኖረው ህዝብ 96.3 በመቶው፣ ከከተማ ነዋሪው ደግሞ 46.4 በመቶው  በድህነት አረንቋ ውስጥ እንደሚኖር በሪፖርቱ  ተመልክቷል፡፡
የድህነቱ መጠን በክልል ደረጃ ሲታይ፣ የሶማሌ ክልል 93 በመቶ ድሃ ህዝብ በመያዝ ቀዳሚ ሲሆን፤ ኦሮምያ በ91.2 በመቶ ሁለተኛ፣ አፋር በ90.9 በመቶ ሶስተኛ፣ አማራ በ90.1 በመቶ አራተኛ፣ ትግራይ በ85.4 በመቶ አምስተኛ ደረጃን ይዘው እንደሚገኙ ጥናቱ  ጠቁሟል፡፡ 20 በመቶ ድሃ ህዝብ ይኖርባታል ያላትን አዲስ አበባ ከአገሪቱ አነስተኛ ቁጥር ያለው ድሃ በመያዝ ቀዳሚ ያደረጋት ይሄው  ጥናት፣ ድሬደዋን በ54.9 በመቶ፣ ሐረርን በ57.9 በመቶ ሁለተኛና ሶስተኛ አድርጎ አስቀምጧቸዋል፡፡
 በሌላ በኩል የአፍሪካ ልማት ባንክ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መረጃ፣ ኢትዮጵያ ባለፉት አስር  አመታት በአማካይ ከአስር በመቶ በላይ እድገት ማስመዝገቧን ሲመሰክር፣ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ቻንታል ሄበርት በበኩላቸው፤ አገሪቱ የከፋ ድህነትን በመቀነስ ረገድ ስኬታማ መሆኗን ሰሞኑን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ መናገራቸው ተዘግቧል፡፡
የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲን የጥናት ሪፖርት በተመለከተ አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው የቀድሞው የኢዴፓ ፕሬዚዳንትና የኢኮኖሚ ባለሙያው  አቶ ሙሼ ሰሙ በሰጡት ምላሽ፤“ረሃቡንና ጥማቱን እንዲሁም የኑሮ ውድነቱን በተጨባጭ እየኖርኩት ስለሆነ አውቀዋለሁ” በማለት የኢትዮጵያን  ድህነት  ለማመን የኦክስፎርድና የአይኤምኤፍ ሪፖርት አያስፈልገኝም ብለዋል፡፡
“የድህነት መለኪያው  መስፈርት ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን ዓለም የተመዘነበት  ነው፤ በእርግጥም ውጤቱ  ኢትዮጵያን በትክክል ይገልፃታል” ያሉት አቶ ሙሼ ፤ዜጎች ራሳቸው ድህነቱን እየኖሩት ስለሆነ የማንንም ምስክርነትና ማስተባበያ አይፈልጉም ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ እንደተለመደው ሪፖርቱን ያወጡት የአገራችንን እድገትና ብልፅግና ማየት የማይፈልጉ ጠላቶቻችን ናቸው በማለት ራሱን ማታለል እንደሌለበት የገለፁት አቶ ሙሼ፤ መንግስት አገሪቱን ከድህነት ለማውጣት የተለየ መላ መዘየድ  እንዳለበት የኦክስፎርድ ጥናት  አመላካች ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለውጥ ለማምጣት እያደረገች ያለውን እንቅስቃሴ ማንም አይክደውም ያሉት የኢኮኖሚ ባለሙያው፤“ሪፖርቱ የእኛን ፍላጎት ካላንፀባረቀ አንቀበልም የሚለው የተለመደ የኢህአዴግ ምላሽ   አያዋጣም፣ እንደውም ራሱን ለመፈተሽ የሪፖርቱን መውጣት እንደ መልካም አጋጣሚ ሊቆጥረው ይገባል” ሲሉ መክረዋል፡፡
በዜጐች መካከል ሰፊ የሃብት ልዩነት መኖሩን የጠቆሙት የኢኮኖሚ ባለሙያው ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ በበኩላቸው፤ “በኢትዮጵያ ድህነት አሁንም አለ” የሚባለው ትክክል ነው ብለዋል፡፡ “ትላልቆቹ የኢኮኖሚና የፋይናንስ ተቋማት- እነ ንግድ መርከብ፣ ቴሌኮም የመሳሰሉት በመንግስት ስር በመሆናቸው የሚያገኙት ገቢ መልሶ ለመሰረተ ልማት ነው የሚውለው፡፡ ለእያንዳንዱ ዜጋ የሚደርስበት መንገድ  የለም፡፡ የኢኮኖሚ እድገቱን በGDP (አጠቃላይ የምርት እድገት) ስንመለከተው፣ የድሃውን ህዝብ ትክክለኛ ህይወት እያሳየንም፡፡” በማለት ምሁሩ  አስረድተዋል፡፡
ፕሮፌሰር አማር ካስያን የሚባሉ ምሁር፣ የሰብአዊ  እድገት መለኪያ (human development indicators) ማውጣት አለብን በማለት ትምህርት፣ ጤናና  ረጅም እድሜ መኖር የሚሉ ሶስት መለኪያዎችን  እንደፈጠሩ የጠቆሙት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ ረጅም እድሜ የሚለው መለኪያ በምግብ ራስን መቻል ስለሚያካትት  እንደተባለውም ኢትዮጵያ ወደ ኋላ ቀርታለች ብለዋል፡፡
የሚሊኒየም የልማት ግቦች ተብለው የተነደፉትን በእርግጠኝነት እንደርስባቸዋለን፤ እንደውም እኔ ነበርኩ ስመራው የነበረው ያሉት ምሁሩ፤ “በእቅዱ እንደተቀመጠው ሁሉም ህፃናት ትምህርት ቤት የመግባት እድል አላቸው፣ ነገር ግን 1ኛ ደረጃን የመጨረስ እድላቸው የመነመነ ነው፡፡” በማለት በሚሊኒየም የልማት ግቡ የተቀመጠውን አሳክተናል ማለት የሰውን ልጅ ልማት አሳክተናል ማለት እንዳልሆነ ጠቁመዋል፡፡
በጤና ዘርፍም በርካታ የጤና ተቋማት  ተገንብተዋል፣ጥያቄው ግን በቂ ሃኪሞችና  የህክምና መሳሪያዎች ተሟልቶላቸዋል ወይ የሚለው ነው ያሉት ምሁሩ፤ እንዲያም ሆኖ በጤና መስክ መንግስት የሰራው ስራ የሚመሰገን ነው ሲሉ አድንቀዋል፡፡
በቅርቡ ወደ አድዋ ሄደው ያዩትና በሌሎች ክልሎች በስራ አጋጣሚ የተመለከቱት የድህነት ሁኔታ የሚዘገንን እንደሆነ ዶ/ሩ አልሸሸጉም፡፡ በመንግስት ሚዲያዎች “ህብረተሰቡን በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ተጠቃሚ አድርገናል” የሚሉ ዘገባዎችን በተደጋጋሚ መስማታቸውን የጠቀሱት ምሁሩ፤ ጥያቄው እነዚህ ፕሮጀክቶች የምን ያህል ሰው ህይወት ቀይረዋል  የሚለው ነው ብለዋል፡፡
“ቻይና ባለፉት አምስት አመታት 5 ሚሊዮን ህዝብ ከድህነት  አውጥታለች፤ ሆኖም  ዛሬም ከአፍሪካ ህዝብ ብዛት የሚልቅ ድሆች አሏት፤ በነደፈቻቸው ስትራቴጂዎች ግን በፍጥነት ዜጐቿን ከድህነት እያወጣች ነው” ሲሉም ዋናው ጉዳይ ህዝቡን ከድህነት አረንቋ ማውጣት  እንደሆነ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡
በእድገት ጉዳይ ላይ በአገር ደረጃ ግልጽ የሆነ ህዝባዊ ውይይት አለመኖሩን የተቹት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ መንግስት ኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ ያወጣው ሪፖርት ሃሰት ነው የሚል ከሆነ፣ ያንን  በተግባር ማረጋገጥ መቻል አለበት ብለዋል፡፡
የኦክስፎርድን ሪፖርት እኔም አንብቤዋለሁ፤ ነገር ግን ሪፖርቱን እንዴት እንደሰሩት አናውቅም ያሉት በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሀጂ ኢብሳ፤ “እኛ እንደመንግስት ማንም እብድ ከመሬት ተነስቶ አጠናሁ ብሎ የሚያወጣውን አንቀበልም” ብለዋል፡፡ “የመረጃው አላማ ምንጩና መነሻው ምንድን ነው? የሚለውን አናውቅም፤ ከኛ ጋርም ግንኙነት የለውም”፡፡ በማለት መልሰዋል- ሃላፊው፡፡ “እኛ በሃገር ደረጃ ድህነት ምን ያህል ቀንሷል የሚለውን የምንለካው አለም በተቀበላቸውና በተስማማባቸው መለኪያዎች ተጠቅመን ነው” የሚሉት ኃላፊው፤ “ከድሮው በተለየ ከአለማቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ጋር የኢትዮጵያ መንግስት ተቀራራቢ የሆነ የእድገት ሪፖርት እያወጣ መሆኑ የኦክስፎርድን ጥናት ተቀባይነት ያሳጣዋል” ብለዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው ከኒጀርና ከኢትዮጵያ በመቀጠል “የአለማችን ቀዳሚ ድሆች” ብሎ ያሰለፋቸው ስምንት አገራት አፍሪካ ውስጥ ሲሆኑ እነሱም  ማሊ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ብሩንዲ፣ ሶማሊያ፣ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ላይቤሪያ፣ ጊኒና ሴራሊዮን ናቸው፡፡

Published in ዜና

ነዋሪዎች በውሃ እጦት እየተሰቃየን ነው ሲሉ አማረሩ

በጋምቤላ ከተማ ለሃያ ዓመት እንዲያገለግል ታስቦ በውሃ ሃብት ሚኒስቴር በ46 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የጋምቤላ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት በመበላሸቱ፣ ነዋሪዎች በውሃ እጦት እየተሰቃየን ነው ሲሉ ምሬታቸውን ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡
አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የከተማዋ ሆቴል ባለቤት እንደተናገሩት፤ አገልግሎት ከጀመረ የሰባት ዓመት ዕድሜ ብቻ ያስቆጠረው  የጋምቤላ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት አገልግሎት እየሰጠ ባለመሆኑ   ለሁለት ሳምንትና ከዚያም በላይ ለሆነ ጊዜ ከተማዋ የውሃ እጥረት ያጋጥማታል፡፡
የውሃ ችግሩ  በማየሉ የተነሳም የጋምቤላ ከተማን ለሁለት ከፍሎ ከሚያልፈው የባሮ ወንዝ ውሃ እየቀዱ ለመጠጣት መገደዳቸውን የጠቆሙት ነዋሪዎቹ፤ ልጆቻቸው በውሃ ወለድ በሽታ እየተጠቁ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በ1996 ዓ.ም. ለ20 ዓመት እንዲያገለግል ታስቦ  የተገነባው የጋምቤላ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ሁለት መሰረታዊ ችግሮች እንዳሉበት ያመለከቱት ምንጮች፤ የውሃ መሳቢያ ፓምፑ የዲዛይን ችግር ስላለበት በደለል እንደሚሞላና የተገጠሙት ፓምፖችም ደረጃቸውን የጠበቁ እንዳልሆኑ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
በመጠጥ ውሃ እጦት ክፉኛ እንደተቸገሩ የተናገሩት የከተማዋ ነዋሪዎች፤ጉዳዩ የሚመለከተው አካል ለችግራቸው አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጣቸው ተማፅነዋል፡፡  የጋምቤላ ክልል የውሃና ኢነርጂ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ዶራር ኮሞን በስልክ አግኝተን ስለጉዳዩ ልንጠይቃቸው ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ “ስብሰባ ላይ ነኝ” በማለታቸው ሳይሳካልን ቀርቷል፡፡
የጋምቤላ ክልል የውሃና ኢነርጂ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ዶራር ኮሞን በበኩላቸው፤ የውሃ እጥረቱ መከሰቱን አምነው አንዳንድ አካባቢዎች አልፎ አልፎ ቢሆንም ውሃ እንዲያገኙ ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ለውሃው መቋረጥ ምክንያት የሆነውን ችግር ለመቅረፍም በ2ሚ. ብር ፓምፕ መገዛቱን የጠቆሙት ሃላፊው፤ እስከ 2007 ምርጫ ብልሽቱ ተስተካክሎ ነዋሪው የተሟላ የንፁህ መጠጥ ውሃ አገልግሎት ያገኛል ብለዋል፡፡

Published in ዜና

ጋዜጠኛ መሰለ መንግሥቱና አቶ ሐጐስ ኃይሉ ፈቃድ ተሰጣቸው

         የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ዘንድሮ ለ6 የግል ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ፈቃድ ለመስጠት አቅዶ በቂ የሬዲዮ ሞገዶችን ቢያቀርብም፣ ፍላጎትና ብቃት ያለው ድርጅት ያለመቅረቡን አስታወቀ፡፡
የባለሥልጣኑ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ፤ ለአባይ 102.9 እና ለብሥራት 101.1 የግል ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ፈቃድ በሰጡበት ጊዜ እንደገለጹት፣ ለአዲስ አበባ፣ ለባህርዳርና ለሀዋሳ ከተሞችና አካባቢው 6 የግል ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ፈቃድ ለመስጠት ሁለት ጊዜ በማስታወቂያ ቢጋብዙም ፍላጎትና ብቃት ያለው ተወዳዳሪ ድርጅት እንዳልቀረበ ገልፀዋል፡፡
በመጀመሪያው ዙር ለአዲስ አበባና አካባቢዋ አንድ፣ ለባህርዳር ከተማና አካባቢዋ አንድ የግል ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ፈቃድ ለመስጠት በማስታወቂያ ቢያወዳድሩም፣ ለአዲስ አበባ ሦስት ተወዳዳሪዎች ሲቀርቡ የባህርዳሩን የጠየቀ የለም፡፡ ለአዲስ አበባ ከተወዳደሩት መካከል መስፈርቱን አሟልቶ የተገኘው አባይ ኤፍኤም 102.9 ሬዲዮ ጣቢያ ሲፈቀድለት ሁለቱ ተወዳዳሪዎች ተሰርዘዋል፡፡
ባለሥልጣኑ በሁለተኛው ዙር ለአዲስ አበባ ሦስት፣ ለሀዋሳ አንድ የግል ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ሞገድ አዘጋጅቶ ቢያወዳድርም፣ ለአዲስ አበባው አንድ ጣቢያና ለሀዋሳው ምንም ተወዳዳሪ አልቀረበም፡፡ ለአዲስ አበባ ከተወዳደሩት ውስጥ አንዱ ያቀረበው ፕሮፖዛል መስፈርቱን ስላላሟላ ሲሰረዝ፣ በመጀመሪያው ዙር ተወዳድሮ ውድቅ የተደረገበት “ኦያያ መልቲ ሚዲያ” (ብሥራት) ስህተቱን አርሞ በመቅረቡ ተመርጦ 101.1 ሜጋ ሄርዝ እንደተሰጠው አስረድተዋል፡፡
ፈቃድ የተሰጣቸው ኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያዎች ሥራ ሲጀምሩ በብሔራዊ መግባባት፣ በዲሞክራሲ ግንባታና መልካም አስተዳደር እንዲሁም ለልማት ስራዎች ትኩረት እንዲሰጡ፣ ወቅታዊ፣ ትክክለኛና ሚዛናዊ መረጃ እንዲያቀርቡ አቶ ልዑል አሳስበዋል፡፡
የአባይ 102.9 ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ባለቤት አቶ ሐጎስ ኃይሉ ባደረጉት ንግግርም ሬዲዮ ጣቢያቸው፣ ውጭ አገርና አገር ውስጥ ያሉ ባለሀብቶች በአክሲዮን ያቋቋሙት መሆኑን ጠቅሰው፣ ልዩ ድጋፍ በሚሹ የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ አተኩሮ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡
የኦያያ መልቲ ሚዲያ (ብሥራት) 101.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ባለቤት ጋዜጠኛ መሰለ መንግሥቱ፣ 101.1 ሬዲዮ በአውሮፓና አሜሪካ ተወዳጅ ጣቢያ መሆኑን ጠቅሶ፣ እዚህም ተወዳጅ እንዲሆን ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግ ተናግሯል፡፡
ባለፉት አምስት ዓመታት በ4 ሰዓት ፕሮግራም እግር ኳስን ብቻ ሲያስተላልፍ መቆየቱን ጠቅሶ፣ አሁን በ18 ሰዓት ስርጭቱ ሁሉንም ስፖርቶችና የተለያዩ የመዝናኛ ፕሮግራሞች እንደሚያቀርብበት ገልጿል፡፡ እግር ኳስን በሬዲዮ ተመልከቱ ፕሮግራም ላይ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የመጀመሪያና የሁለተኛ ዲግሪ መመረቂያ ጽሑፍ መስራታቸው፣ ፕሮግራሙ ምን ያህል ተወዳጅ እንደሆነ ያመለክታል ያለው መሰለ መንግሥቱ፤ የመዝናኛ ፕሮግራሙንም እዚህ አገር ከተለመደው ውጪ በተወዳጅ አቀራረብ በቀጣዩ ሐምሌ ወር እንደሚጀምር አስታውቋል፡፡

Published in ዜና

መድረኩ ከውይይቱ በኋላ አቋም ለመያዝ አቅዷል

     አዲሱ “የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች መድረክ” በወቅቱ የሚዲያ ባለሙያዎች ፈተና፣ በፕሬስ ህጉና በፀረ - ሽብር አዋጁ ላይ የሚያጠነጥን የውይይት መድረክ ማዘጋጀቱንና ነገ ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ ቀበና አካባቢ በሚገኘው አዲስ ቪው ሆቴል እንደሚካሄድ የመድረኩ ፀሃፊ አቶ ነብዩ ኃይሉ ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ “በአሁኑ ሰዓት በጋዜጠኝነታቸው ታስረው ዋጋ እየከፈሉ ያሉ ባለሙያዎች አሉ፣ እስርና እንግልቱም ቀጥሏል” ያሉት አቶ ነብዩ፤ጋዜጠኛው በሚጋፈጣቸው ፈታኝ ሁኔታዎች ዙሪያ ውይይት ከተደረገ በኋላ መድረኩ አቋም በመያዝ መግለጫ እንደሚያወጣ አስታውቀዋል፡፡
የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማልና አቶ ጌታቸው ረዳ በውይይቱ ላይ እንዲሳተፉ መጋበዛቸውን የገለፁት የመድረኩ ፀሀፊ፣ እስካሁን ግን ኃላፊዎቹ በስብሰባው ላይ መገኘት አለመገኘታቸውን አላሳወቁም ብለዋል፡፡
“የፕሬስ ነፃነት፣ የጋዜጠኞች ደህንነትና ልማት” በሚል መሪ ቃል በሚካሄደው በዚህ የውይይት መድረክ ላይ የህግ ባለሙያው አቶ ተማም አባቡልጉና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ዲፓርትመንት ዲን ዶ/ር አብዲሳ ዘርአይም እንደሚገኙና የመወያያ ሀሳብ እንደሚያቀርቡ አቶ ነብዩ ገልፀዋል፡፡ “በአሁኑ ሰዓት ጋዜጠኞች ሀሳባቸውን በመግለፃቸው መንግስት የፀረ-ሽብር አዋጁን መሳሪያ በማድረግ ለእስር እየዳረጋቸው ነው” ያሉት አቶ ነብዩ፤ በዚህም የተነሳ ጋዜጠኞች በሥራቸው ደህንነት እንደማይሰማቸው ጠቁመው፣ “አፈናው ወደፊት እንዴት መቆም አለበት?” በሚለው ጉዳይ ላይ ውይይት ከተካሄደ በኋላ  መድረኩ አቋም ይይዛል ብለዋል፡፡

Published in ዜና

“በመጪው ምርጫ ከ80 በመቶ በላይ ድምፅ ለማሸነፍ እየተጋን ነው”

ኢዴፓ በመጪው ዓመት ለሚካሄደው አገራዊ ምርጫ ዝግጅት ለማድረግ በቀጣዩ ሐምሌ ወር  በአምስት ከተሞች ህዝባዊ ስብሰባ እንደሚጠራ አስታወቀ፡፡ ከምርጫ 97 በፊት ወደነበርንበት አቋማችን  ተመልሰናል ያሉት የፓርቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ በቀጣዩ ምርጫ ከሰማንያ በመቶ በላይ ድምፅ በማግኘት ፓርላማ ለመግባት ከወዲሁ ዝግጅት መጀመራቸውን ጠቁመዋል፡፡
አዲሱ የስራ አስፈፃሚ ከተመረጠ ወዲህ ከህዝብ ጋር የመገናኛ መድረክ አለመፈጠሩን የገለፁት ፕሬዚዳንቱ፤ ለዚህም ምክንያቱ የፋይናንስ እጥረት እንደነበር ጠቁመው አሁን ግን ችግሩ ተቀርፎ በአምስት ከተሞች ህዝባዊ ስብሰባዎችን ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡
የፓርቲውን ጽ/ቤቶች በየክልሉ ለማደራጀትና ለመክፈት በስፋት እየሰሩ እንደሆነ የገለፁት ዶ/ር ጫኔ፤ በአፋር ክልል አምስት ዞኖች እንዲሁም በቤንሻንጉል ጉሙዝ ስምንት ዞኖችና ወረዳዎች ውስጥ ደጋፊዎችና አባላትን እንደመለመሉ አስታውቀዋል፡፡
ፓርቲው ከምርጫ 97 በፊት ወደነበረበት አቋሙ መመለሱን በመግለፅም በመጪው ዓመት በሚካሄደው ምርጫ ከ80 በመቶ በላይ ድምጽ በማሸነፍ፣ ፓርላማ ለመግባት ከወዲሁ በትጋት እየሰሩ እንደሆነ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡  
ፓርቲው በመጪው ሐምሌ 12 በአዲስ አበባ መብራት ሃይል የመሰብሰቢያ አዳራሽ የመጀመሪያውን ህዝባዊ ስብሰባ የሚያካሂድ ሲሆን በመቀጠልም በመቀሌ፣ ባህር ዳር፣ ሃዋሳና ናዝሬት ተመሳሳይ ህዝባዊ ስብሰባዎችን እንደሚያደርግ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

      የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ በየቦታው በአባላቶቼ ላይ የሚደርሰው ግድያና እስራት ተባብሶ ቀጥሏል፤ ይህንንም አወግዛለሁ ሲል ለአዲስ አድማስ ገለፀ፡፡ በምስራቅ ጎጃም ዞን እነማይ ወረዳ ደንጎሊማ ቀበሌ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ምሽት ላይ የፓርቲው የቀበሌ ተጠሪ የነበሩት አርሶ አደር ሞሳ አዳነ በታጣቂ ካድሬዎች ተደብድበው ህይወታቸው ማለፉን መኢአድ ገልጿል፡፡
በወረዳው የፓርቲው ምክትል ሰብሳቢና የዞኑ ወጣቶች ጉዳይ ተጠሪ መቶ አለቃ ደምመላሽ ጌትነት ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፣ ሟቹ አርሶ አደር ከዚህ ቀደም በመኢአድ አባልነታቸው የተነሳ ከእድርና ከቤተክርስቲያን እንዲገለሉ በመደረጋቸው፣ መገለሉ እንዲነሳላቸው ለወረዳው መስተዳደር አቤቱታ አቅርበው ነበር፡፡
የመኢአድ የቀበሌ ተጠሪው ባለፈው ቅዳሜ የወረዳው ታጣቂ ካድሬዎች በሆኑት አቶ አዲሱ ጫኔና አቶ ብርሀኑ ታመነ ተደብድበው ጭንቅላታቸው ላይ በደረሰባቸው ከፍተኛ ጉዳት በደብረ ማርቆስ ሆስፒታል ሲታከሙ ቆይተው ለህልፈት እንደተዳረጉ የጠቆሙት መቶ አለቃ ደምመላሽ፤ አንደኛው ካድሬ ወዲያውኑ ሲያዝ ሌላኛው ከስርዓተ ቀብሩ በኋላ በቁጥጥር ስር መዋሉን ተናግረዋል፡፡
በዚያው በእነማይ ወረዳ ነዋሪና የመኢአድ አባል የሆኑት አቶ ይበልጣል ወንድሜነህ፤ ቤትህ ውስጥ መሳሪያ ደብቀሃል በሚል ቤታቸው ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ ከተፈተሸ በኋላ ወደ እስር ቤት ትሄዳለህ ተብለው መወሰዳቸውንና እስካሁንም የገቡበት እንደማይታወቅ ፓርቲው አስታውቋል፡፡
“በተመሳሳይ ሁኔታ በደቡብ ጎንደር፣ ጭልጋ ወረዳ የመኢአድ ሰብሳቢ የሆኑት ሻምበል ንጉሴ ደርሶ፤ በእስርና በእንግልት ላይ ይገኛሉ” ያሉት የመኢአድ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ተስፋሁን አለምነህ፤ በየክልሉና በየወረዳው የሚገኙ አባሎቻችም ላይ የሚደርሰው ግድያ፣ እስርና እንግልት በአስቸኳይ እንዲቆም እንጠይቃለን ብለዋል፡፡
ከአንድ ወር በፊት የአቃቂ አካባቢ ነዋሪና የአዲስ አበባ የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ የነበሩት አቶ ጥጋቡ ደበላ፤ ባልታወቀ ምክንያት ቤታቸው ውስጥ ተገድለው መገኘታቸውን የተናገሩት አቶ ተስፋሁን፤ አስክሬናቸው የተገኘው ከሞቱ ከሁለት ቀን በኋላ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
በደቡብ ጎንደር ይፋግ ቀበሌ ውስጥ የማዳበሪያ ብር ክፈል አትክፈል የሚል ውዝግብን ተከትሎ አቶ ሞላ ወረታ በተባሉ የመኢአድ አባል ላይ በተፈፀመባቸው ድብደባ፣ ግንቦት 9 ቀን 2006 ዓ.ም ህይወታቸው ማለፉንና በአላማጣ ከተማ የሚገኙ የመኢአድ አባል መምህር ኢያሱ ሁሴን በእስር ላይ እንደሚገኙም የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል፡፡ “በተለያዩ አካባቢዎች በፓርቲው አባላት ላይ አፈናና ግድያ እየተፈጸመ፣ የፓርቲው እንቅስቃሴም እየተገደበ ነው” ያሉት ኃላፊው፤ መንግስት በፓርቲው ላይ ወከባ እየፈጠሩ ያሉትን ካድሬዎች ከእኩይ ተግባራቸው እንዲታቀቡ ያስጠንቅቅልን ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ዙሪያ የእነማይ ወረዳን ፖሊስ ምላሽ ለማግኘት ሙከራ ያደረግን ቢሆንም የወረዳው ፖሊስ አዛዥ የኢንስፔክተር መስፍንም ሆነ የወረዳው ወንጀል መከላከል ክፍል ኃላፊ ስልኮች ዝግ በመሆናቸው ምላሻቸውን ለማካተት ያደረግነው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡

Published in ዜና
Page 8 of 18