ታዳጊዎች ለማጨስ እንዳይበረታቱ ከፍተኛ ቀረጥ ሊጣል ነው
በፓኬት እንጂ በነጠላ መሸጥ ሊከለከል ነው

    የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ሰሞኑን በቢሾፍቱ ከተማ ለመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ባዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም ላይ በአገሪቱ የሲጋራ አጫሹ ቁጥር እየጨመረ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን በሲጋራ ምርት ላይ ከፍተኛ ቀረጥ እንደሚመጣል ተጠቆመ፡፡
በ2003 ዓ.ም የተደረገውን የሥነ ህዝብና ጤና ጥናት (DHS) ዋቢ በማድረግ በቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፎች እንደተመለከተው፤ የአጫሾች ቁጥር ወደ ስድስት ሚሊዮን ገደማ ይሆናል፡፡ ከአጫሾቹ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዙት ወንዶች ቢሆኑም የሴት አጫሾች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡ የአገሪቱ አጠቃላይ አመታዊ የሲጋራ ፍላጐትም ወደ 5 ቢሊዮን ፍሬ ደርሷል ተብሏል፡፡
ከአገሪቱ አጠቃላይ የሲጋራ ፍላጐት 53 በመቶ ያህሉ የሚሸፈነው በብሔራዊ ትምባሆ ሞኖፖል ሲሆን 4.6 በመቶ ከውጪ በማስገባት፣ 38 በመቶ ደግሞ በኮንትሮባንድ (ህገወጥ) ንግድ ነው፡፡ ትምባሆ፤ ሱስ አስያዥ የሆነውን ኒኮቲን የተባለ ንጥረ ነገር ጨምሮ ከአራት ሺህ በላይ ኬሚካሎችን በውስጡ ይይዛል፡፡ ከእነዚህ ውስጥም 250 ያህሉ እጅግ አደገኛ ኬሚካሎች ሲሆኑ 50 የሚደርሱት ደግሞ ካንሰር አምጪ ኬሚካሎች መሆናቸውን የአለም ጤና ድርጅት ተወካዩ አቶ ዋሲሁን መላኩ ተናግረዋል፡፡
አዕምሮአችን የተስተካከለ ጤና እንዳይኖረው ከሚያደርጉ ጉዳዮች አንዱ ሱሰኝነት ነው ያሉት ዶክተር ሙሴ ገብረሚካኤል፤ በትምባሆ ውስጥ የሚገኘውና ኒኮቲን የተባለው ንጥረ ነገር አንጐላችን ውስጥ የተለያዩ ለውጦችን በመፍጠር አንጐላችንን የኒኮቲን ጥገኛ ያደርገዋል ብለዋል፡፡ ትንባሆ ውስጥ የሚገኘው ሱስ አስያዥ ኒኮቲን መጠኑ እየጨመረ በመጣ ቁጥር  ለአዕምሮ ህመም እንዲሁም ለሞት የመጋለጥ እድል እንደሚጨምር ገልፀዋል፡፡
መከላከል እየተቻለ ለሞት መንስኤ ከሚሆኑ የአለማችን የጤና ጠንቆች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው ትምባሆ፤ ለከፍተኛ የደም ግፊት፣ ለልብ ህመም፣ ለተለያዩ ካንሰር ህመሞች፣ ለአይን ሞራ ግርዶሽ፣ ለጥርስ መበስበስ፣ ለጨጓራ ቁስለት፣ ለአንጐል በሽታ፣ ለጋንግሪንና ለስንፈተ ወሲብ እንደሚያጋልጥም የአለም ጤና ድርጅት መረጃ ያመለክታል፡፡
በ2013 የተደረገና በአለም ጤና ድርጅት ይፋ የሆነ የጥናት ውጤት እንደሚጠቁመውም፤ በአለማችን በትምባሆ ሣቢያ በሚከሰቱ የጤና ችግሮች ህይወታቸውን የሚያጡ ሰዎች ቁጥር በኤድስ፣ በትራፊክ አደጋ፣ በአደንዛዥ እፅ፣ በግድያ ወንጀልና ራስን በማጥፋት ከሚሞቱት ሰዎች አጠቃላይ ድምር ይበልጣል፡፡ በአሁኑ ወቅት በዓለማችን 1.3 ቢሊዮን የትምባሆ ተጠቃሚዎች የሚገኙ ሲሆን በየዓመቱም 5 ሚሊዮን የሚሆኑት በትምባሆ ምክንያት ህይወታቸውን ያጣሉ፡፡ የሟቾቹ ቁጥር ካደጉት አገራት ይልቅ ገና በማደግ ላይ ባሉት አገራት ይጨምራል፡፡
በአገራችን ትምባሆ በተለያዩ መንገዶች በጥቅም ላይ የሚውል ሲሆን ማጨስ፣ ማኘክ፣ መታጠንና ማሽተት ዋንኞቹ የትምባሆ ተጠቃሚዎች የሚያዘወትሯቸው መንገዶች ናቸው፡፡ በተለይ ከከተማ ወጣ ባሉ አካባቢዎች በማኘክና በማሽተት የትምባሆ ተጠቃሚ መሆን የተለመደ ነው፡፡
በከተሞች አካባቢ በፋብሪካ የሚዘጋጁ የትምባሆ ምርቶች የሚዘወተሩ ሲሆን በብሔራዊ ትምባሆ ሞኖፖል የሚመረቱት ግስላ፣ ኒያላ፣ ኢሌኒና ዲላይት የተባሉት የሲጋራ አይነቶች ገበያውን በከፍተኛ ደረጃ ተቆጣጥረውታል፡፡  
ማልቦሮ፣ ዊንስተን፣ ሮዝማን፣ ኤል ኤንድ ኤም እና ኬንት የተባሉት የሲጋራ አይነቶች ደግሞ በህጋዊ መንገድና በኮንትሮባንድ ከውጪ አገር እየገቡ ለአገራችን ገበያ የሚቀርቡ የሲጋራ አይነቶች ናቸው፡፡
የትምባሆ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ የሥራ ዕድል በመፍጠርና የታክስ ገቢ በማስገኘት ለአገሪቱ የሚሰጠው ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ ከፍተኛ ቢሆንም የሚያስከትለው ችግርና የሚፈጥረው ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ከፍተኛ በመሆኑ፣ ቁጥጥርና ክትትል በማድረግ፣ በትምባሆ ሣቢያ የሚሞቱ ዜጐችን መታደግ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆኖ በመገኘቱ፣ ህግ አውጥቶ፣ አሠራሩን መቆጣጠር እንዳስፈለገ በኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን አማካሪ አቶ መንግስተአብ ወልደአረጋይ ተናግረዋል፡፡ በተለይም ማጨስ በሚጀመርበት የወጣትነት ዕድሜ ውስጥ የሚገኙ ዜጐች ሲጋራ በቀላሉ ለማግኘት እንዳይችሉ በትምባሆ ላይ የሚጣለውን ታክስ ከፍ በማድረግ፣ የሲጋራ መሸጫ ዋጋን ለመጨመር የሚያስችል ስትራቴጂ ተነድፎና ረቂቅ ህግ ወጥቶ በገንዘብና ኢኮኖሚ ሚኒስትር ጥናት እየተደረገበት እንደሆነ አማካሪው ጠቁመዋል፡፡ ህጉ በቅርቡ ፀድቆ ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልፀዋል፡፡
ባለፈው ዓመት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፀደቀውን የትምባሆ ቁጥጥር አዋጅ ለማስፈፀም ሥልጣንና ኃላፊነት የተሰጠው የኢትዮጵያ የምግብ፣ መድኀኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን፤ ህዳር 22 ቀን 2007 ዓ.ም የትምባሆ ቁጥጥር መመሪያ በማውጣት አፅድቋል፡፡ በቅርቡም ተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚጀመር ሲሆን በትምባሆ ምርቶች ሽያጭ፣ ዝውውርና አጠቃቀም ላይ ቁጥጥርና ክትትል እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡
በአዲሱ አዋጅና መመሪያ መሰረትም፣ ማንኛውም የኤሌክትሮኒክስ ኒኮቲን መስጫ መሳሪያ ማምረት ወደ ሀገር ውስጥ ማምጣት፣ ማከፋፈል፣ መሸጥ ወይም በማንኛውም መንገድ ገበያ ውስጥ ማስገባት የተከለከለ ነው፡፡
የትምባሆ ምርቱ ለጤና አደገኛ መሆኑን የሚገልፅ የማስጠንቀቂያ ፅሁፍ የሲጋራ ባኮውን 30 በመቶው ያላነሰ ቦታ በሚሸፍን መልኩ መገለፅ ይኖርበታል፡፡ የትምባሆ ምርትን በችርቻሮ የመሸጥ ፍቃድ የተሰጣቸው ሰዎች ምርቱን ለአይን በሚታይ መልኩ መደርደርና ገዥን መሳብ አይችሉም፡፡ የትምባሆ ምርት የሚሸጠው ባልተከፈተ ፓኬት ወይም ማሸጊያ ሲሆን ሲጋራን በነጠላ መሸጥ የተከለከለ መሆኑን አዲሱ አዋጅና መመሪያ ያዛል፡፡
ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊዎች በትምባሆ ምርት ግዥም ሆነ ሽያጭ ላይ ተሳታፊ መሆን እንደማይችሉ የደነገገው አዲሱ መመሪያ፤ የትምባሆ ምርት በችርቻሮ በሚሸጥበት ወቅት ሻጩ የገዥውን ዕድሜ ከተጠራጠረ ህጋዊ ፓስፖርት፣ የመንጃ ፈቃድ ወይም የነዋሪነት መታወቂያ ካርድ አይቶ ማረጋገጥ አለበት ይላል፡፡ አዲሱ መመሪያ ሲጋራ ማጨስ የማይፈቅድባቸውን ቦታዎች በዝርዝር የገለጸ ሲሆን፤ ሆቴሎች፣ የመጠጥ ቤቶች፣ የምሽት ክለቦች፣ መዝናኛ ክበቦች፣ ካፌዎች፣ ምግብ ቤቶች፣ የመንግስትና የግል መስሪያ ቤቶች፣ ሊፍቶች፣ መታጠቢያ ቤቶች፣ ፋብሪካዎችና የንግድ መደብሮች፣ ሲኒማ፣ ቲያትርና ቪዲዮ ቤቶች፣ ሙዚቃ ማሣያ አዳራሾች፣ የህዝብ መሰብሰቢያ ቦታዎች፣ የህዝብ ትራንስፖርቶች፣ እንዲሁም ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ልጆች በሚገኙባቸው ሥፍራዎች ሁሉ ማጨስ የተከለከለ ነው፡፡
አዲሱ ህግና መመሪያ በቅርቡ ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆን ደንብና መመሪያውን በማይተገብሩ አካላት ላይም ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ ተገልጿል፡፡ ከሶስት ወራት በኋላ በሚወጡ ፊልሞች ላይ ሲጋራ እንዳይጨስና የሚጨስባቸው አጋጣሚዎች ካሉም በፊልሙ ላይ የሲጋራን ጎጂነት የሚገልፁ ፅሁፎች በስክሪኑ ላይ እንዲጻፉ የሚያስገድድ አሰራርም እንደሚጀመር ተገልጿል፡፡

Published in ዋናው ጤና

     ሂሳብ፣ የዛሬው የመጨረሻው ጭውውታችን ነው፣ ማርጀትና መሞትን የሚመለከት፡፡ ጥናቱን የሚያቀርብልን ጓድ አስተዳደር ነው፡፡ መድረኩ ይኸውልህ!
ኬሚስትሪ፣ ጓድ ሰብሳቢ፣ ይህ አርእስት ስጋት ላይ ጥሎኛል፣ ማለቴ ጡረተኛ ስለሞት ማውራት አለበት እንዴ? እንደኔ ከዚህ አርእስት መራቅ ይሻላል!
ምህንድስና፣ አቤት ፍርሃት! አይዞህ ጭውውቱን እስክንጨርስ አትሞትም፣ ለማናቸውም ብትሞትም አንዴ ነው፣ ደግመህ ትሞትም፡፡ ስለዚህ ፍርሃትህን ወደ ጎን አድርገው፡፡
አስተዳደር፣ ጓዶች፣ አርእስቱን እንተወው ለማለት ትንሽ የዘገየ ይመስለኛል፡፡ እኔም እኮ የማይናቅ ጊዜ መሰናዶው ላይ አጥፍቻለሁ፡፡
ሂሳብ፣ መልካም፣ በል ጥናትህን አቅርብልን፡፡
አስተዳደር፣ በመጀመሪያ ሦስታችሁንም ለማመስገን እፈልጋለሁ፣ የሚነበቡ ፅሁፎች ባትሰጡኝ ኖሮ በፍፁም ልወጣው ባልቻልኩ ነበር፡፡
በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፣ ስለ ፕሮቶን፣ ኤሌክትሮን ባላወራሁም ነበር፡፡ እስቲ ከመሰረቱ ልጀምር፡፡ ሳይንስ ሲያስተምረን ሁሉ ነገር፣ ማለትም ከድንጋይ እስከ ሰው ያለው ሁሉ የተገነባው ከአቶሞች እንደሆነ ነው፡፡
አቶሞች በተራቸው ከፕሮቶኖችና ኤሌክትሮኖች የተነቡ ሲሆን፣ ፕሮቶኖች ከኳርክ ዝርያዎች ተቀነባብረው የተሰሩ ናቸው፣ ኤሌክትሮን ግን እራሷን የቻለች ናት፡፡ ጓዶች፣ ከወር በፊት “ኳርክ” ምንድነው ብትሉኝ ኖሮ፣ እንቁራሪት የሚያሰማው ድምፅ    ነዋ! እል ነበር፡፡ እንደምታዩት እኔም መጠነኛ ትምህርት ቀስሜያለሁ!
የሚነሳው ጥያቄ የአቶሞች ዕድሜ ስንት ነው? ያረጃሉ ወይ? የሚል ነው፡፡ የፊዚክስ ባለሙያዎች ሲያስረዱ፣ የፕሮቶን እድሜ 1031 ዓመታት (ማለትም 10 ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን) ሲሆን ኤሌክትሮን ግን ጨርሶ የማትለወጥ ናት፡፡
ታዲያ ይኸ እንዲህ ከሆነ በአቶሞች የተገነቡት ሀዋሳ፣ ብሎም ተክሎችና እንስሳት እንዴትና ለምን ማርጀት ቻሉ? አንዳንዶች ሲያስረዱ፣ ህዋስ ከአቶም የበለጠ ውስብስብ፣ እንቁራሪት (የህዋሳት ስብስብ) ከአንድ ህዋስ የበለጠ ውስብስብ ናቸው፡፡ እነኚህ ምሁራን እንደሚሉት ውስብስብነት (ኮምፕሌክሲቲ) ወደ ህይወት ያመራል፣ አይቀሬ ነው፡፡ ህይወት ወደ ሞት! ይህ አባባል ወደ ፍልስፍናው የሚያደላ ስለሚመስል ባንገፋበት ይሻላል፡፡
ባለአንድ ህዋስ ባክቲሪያም እኮ ታረጃለች፣ ማለትም ውስብስብነት በይፋ የማይታይበት፣ ለምን? እርጅናን የሚቆጣጠሩ ጂኖች አሉ? አንዳንድ ሰዎች እስከ 130 ዓመት እንደሚኖሩ የታወቀ ነው፣ ባካባቢያቸው ምክንያት ይሆን? ብዙ ጊዜ እነኚህ ሰዎች ዳገትማ ስፍራ፣ ንፁህ አየርና ውሃ በሚገኝበት የሚኖሩ ናቸው፡፡ ለምግባቸውም ከስጋ ይልቅስ ተክሎችን ያዘወትራሉ ይባላል፡፡ ተክሎችን ስንመለከት፣ በአሁኑ ወቅት በሰሜን አሜሪካ፣ ካሊፎርኒያ ግዛት ውስጥ “ሴኮያ” የተባለ ዛፍ እስከ 3,800 ዓመት እንዲኖር በተደረገ ምርምር በ C-14 እና ከግንዱ ቀለበቶች ቁጥር ተረጋግጧል፡፡
የዚህ ዓይነት ዛፍ፣ ትልቅና ረጅም ዕድሜ ያለው የግንዱ ግማሽ - ወገብ ስፋት (ሬዲየስ) 4,85 ሜትር፣ ዙሪያ ርቀት (ሰርከምፈረንስ) 30 ሜትር፣ የቅርፊት ውፍረት 61 ሴንቲሜትር መሆኑ ታውቋል፡፡ እርግጥ፣ ሴኮያ በንግዱ መወፈርና በቅርፊቱ ደንዳና መሆን ምስጥ፣ ዝናብ፣ በረዶ ሊያጠቁት የቻሉ አይመስልም፡፡ ሌላው የዛፉ ከፍታ ቦታ በማደግ ከእንስሳት መራቁ ነው፡፡ ከሴኮያ ህዋሳት የምንማረው ይኖራል?
[“ከዚህም ከዚያም” (የ4 ጡረተኞች ጭውውት) ከተሰኘው የፕሮፌሰር ግርማ ሙልኢሳ መፅሃፍ የተቀነጨበ]

Published in ዋናው ጤና

አውሮፓ ህብረት ምርጫውን የማይታዘበው በገንዘብ ችግር ነው
ተቃዋሚዎች ባይነግሩንም  ከጠ/ሚኒስትሩ ጋር ተወያይተው ነበር
እነ “ኤፈርት” ከአውራው ፓርቲ  ጋር የሚያገናኛቸው ነገር የለም ተባለ

    ባለፈው ማክሰኞ በቀድሞው ኢቴቪ (በአዲሱ EBC) በምርጫ ዙሪያ የቀረበው ዘገባ አስደምሞኛል (ሌላ ምርጫ የለኝማ!) ለነገሩ ዘገባ ከማለት ይልቅ ያፈጠጠ የምርጫ ቅስቀሳ ቢባል ይቀላል (መተቸቴ እኮ አይደለም?!) ቢያንስ ግን በEBC ጋዜጠኛ ባይሰራ ይመረጥ ነበር (ልማታዊ ጋዜጠኛ መሆኑ አልጠፋኝም!)
እኔ የምለው ግን… EBC በቢቢሲ ሞዴል ይዋቀራል የተባለው ቀረ እንዴ? (ኧረ እንኳንም ቀረ!)፡፡ ለምን አትሉም? ለልማታዊ መንግስት አይመችማ! (ኒዮሊበራሎች እጅ ጠምዛዞች “arm twister” ናቸው!)
እናላችሁ… የEBC ጋዜጠኛ ስላለፉት ነፃ፣ ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ምርጫዎች በቃሉ የፃፈውን ስክሪፕት ትንሽ ካነበነበ በኋላ “በግንቦቱ ምርጫ ዙሪያ ያሰባሰብኩትን የነዋሪዎች አስተያየት ተከታተሉኝ” አለ፡፡ (አስተያየት ሰጪዎቹ “አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች”ን አስታወሱኝ!) አይገርማችሁም… እነዚህ “ነዋሪዎች” ሁሌም ምርጫ ሲደርስ ከተፍ ይላሉ፡፡ እናም “ይሆነኛል… ይበጀኛል… የምለውን …”፣ “ልማቱን ያስቀጥልልኛል ያልኩትን …”፣ “ልማታዊ መንግስት የምለውን --” ወዘተ-- እንመርጣለን እያሉ አስተያየት ሰጡ፡፡ አንዳንዶቹም “ህዝቡ በምርጫው እንዲሳተፍ በመቀስቀስ የዜግነት ግዴታዬን እወጣለሁ” አሉ፡፡ (ግዴታና ውዴታ ተምታታብን እኮ!) እኔ የምላችሁ … EBC የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ላይ እንደሆንን አልሰማም እንዴ? (የነፃ ገበያ አቀንቃኞች ሃሳብ አልተስተናገደም ብዬ እኮ ነው!)
በነገራችን ላይ--ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፤ “የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ከሌለ፣ ዕጣ ፈንታችን የሶማሊያ ዓይነት ነው” ሲሉ አስጠንቅቀዋል፡፡ (የEBC ጋዜጠኞችን ይመለከታል!) ለማንኛውም ግን  የምርጫ ቅስቀሳው ተጀምሯል፡፡ የጀመረው ግን ኢህአዴግ አይደለም፤ EBC ነው፡፡ (“ያለ ዕዳው ዘማች” አሉ!)
ሰሞኑን ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ለአገር ውስጥና ለውጭ ጋዜጠኞች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ምን እንደታዘብኩ ልንገራችሁ? ከስልጣናቸው ጋር በደንብ መለማመዳቸውን፡፡ (ፈጣን ተማሪ ናቸው ማለት ነው!) ቢሆኑማ ነው--- ሰሞኑን “የዓለማችን ምሁር መሪዎች” በሚል ከእነ ኦባማ ተርታ መሰለፍ የቻሉት፡፡ (ለአገር ገፅ ግንባታ ማለፊያ ግብዓት አገኘን!)
እናላችሁ … የማይለመድ የለም-- ሥልጣኑን በደንብ ተለማምደውታል፡፡ ለዚህ እኮ ነው በሰሞኑ መግለጫ  ከሌላው ጊዜ በተለየ ተረጋግተው… በልበሙሉነት… ቁጣና ፍረጃ ሳያበዙ… ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች መልስ ሲሰጡ ያየነው፡፡ (አሁን ተረብ ብቻ ነው የቀራቸው!)  በተለይ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በተመለከተ የተናገሩት ያልተጠበቀ ነው (ተቃዋሚዎች ራሳቸው መገረማቸው አይቀርም!) ጋዜጣዊ መግለጫቸውን የቋጩት፤ “ለጋራ አገራችን በጋራ እንወያይ የሚል ጥሪ ማቅረብ እፈልጋለሁ” በሚል መልዕክት ነው፡፡  (“ባንዳፍ” ብለናቸዋል!)
ብዙዎች ግን አንድ ጥያቄ አላቸው፡፡ “ይሄ አቋም የግላቸው ነው የፓርቲያቸው? ወይስ የመንግስታቸው?” የሚል፡፡ ለእኔ ግን ለውጥ የለውም፡፡ ዋናው ከአንጀታቸው መሆኑ ነው፡፡ ከባለፈው ምርጫ የዞረው የፈረደበት “የሥነምግባር ደንብ” ግን አሁንም አልቀረም፡፡ (ፊርማ ከሌለ፤ ውይይት የለም!) እኔ ተቃዋሚዎችን ብሆን ግን --- የአበሽነት እልሄን ዋጥ አድርጌ፣ የተባለውን ግጥም አድርጌ እፈርም ነበር (“ኩራት እራት አይሆንም” አለ አበሻ!)በሰሞኑ ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ጠ/ሚኒስትሩ ከአዳዲስ መረጃዎች ጋር አስተዋውቀውናል፡፡ ከአንዳንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ጋር በግል የመወያየት ዕድል እንደገጠማቸው አስታውሰው፤ አመራሮቹ የሥነምግባር ኮዱን ፈርመው የፓርቲዎች የጋራ ም/ቤትን እንዲቀላቀሉ አሳምነው ከላኳቸው በኋላ ሌሎቹ አልተስማሙም ብለው እንደቀሩ ተናግረዋል፡፡ (ተቃዋሚዎች ውይይቱን ምስጢር ማድረጋቸው ግን ያስተዛዝባል!) ስንቱን ነገር ሲነግሩን ከርመው …  እንዴት ይሄን ይደብቁናል?! ለነገሩ አይፈረድባቸውም፡፡  (ከ”ኢህአዴግ ጋር ተሞዳሞዱ” የሚል ውግዘት ፈርተው ይሆናል!)
ጠ/ሚኒስትሩ ሌላም የነገሩን መረጃ አለ፡፡ አንዳንድ ተቃዋሚዎች ለውይይት ሲጋበዙ “እነ እገሌ ካሉ (እነ እገሌ እኮ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ናቸው!) አንሳተፍም” እንደሚሉ ጠቁመው፤ ከዚህ አቋማቸው ወጥተው በጋራ ለመወያየት መዘጋጀት እንዳለባቸው መክረዋቸዋል (ተቃዋሚዎች የባህርይ ለውጥ ያስፈልጋቸዋል!) እኔ የምለው … ኢህአዴግ ለየብቻችን ካላነጋገረን የሚሉት በልማት መወጠሩን ዘንግተውት ነው ወይስ ልማቱን ለማደናቀፍ? (መቼም ልማቱን ትቶ ሲወያይ አይከርምም!)
እንዲያም ሆኖ… የደቡብ ሱዳን ፓርቲዎችን ለማደራደር እሳቸውና ፓርቲያቸው ካሳዩት ጥረትና ትዕግስት  አንጻር ለአገራቸው ፓርቲዎች ገና ብዙ ጥረትና ትዕግስት ይቀራቸዋል፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ፤ አሁንም በደቡብ ሱዳን ጉዳይ ተስፋ እንደማይቆርጡም ተናግረዋል፡፡ እርግጠኛ ነኝ ---- በአገራቸው ተቃዋሚዎችም ተስፋ አይቆርጡም፡፡
ከጠ/ሚኒስትሩ የሰማነው ሌላ አዲስ መረጃ ምን መሰላችሁ? … የኢህአዴግ ናቸው ሲባሉ የነበሩት የንግድ ድርጅቶች - ኢንዶውመንትስ- (እነ ኤፈርትን ለማለት ነው!) ከኢህአዴግ ጋር ምንም ግንኙነት እንደሌላቸው ነግረውናል፡፡ ይሄ ትንሽ ግራ ያጋባል፡፡ የኢህአዴግ ካልሆኑ የማን ናቸው? (የተቃዋሚዎች እንዳይሆኑና  እንዳይገርመኝ!) ከመጪው የግንቦት አገራዊ ምርጫ ጋር የተያያዙ አንዳንድ ውዥንብሮችንም ጠ/ሚኒስትሩ አጥርተዋል፡፡ የአውሮፓ ህብረት በምርጫው በታዛቢነት የማይሳተፈው መንግስት ሳይጋብዘው ቀርቶ ሳይሆን በራሱ የገንዘብ ችግር እንደሆነ ነግረውናል፡፡ አንዳንድ ወገኖች ግን ለአውሮፓ ህብረት ግብዣው የቀረበለት ባለቀ ሰዓት ነው ይላሉ፡፡ (“እንዳያማህ ጥራው---” ሆኗል ለማለት እኮ ነው!) የሆኖ ሆኖ ግን  ጠ/ሚኒስትሩ እንዳሉት፤ “ምርጫው በእጃችን ነው፡፡” ሰናይ ሰንበት!

እኔ የምላችሁ ግን … ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ ስንት ዓመቱ ነው? ይሄንን ቀላል ጥያቄ የምጠይቃችሁ ወድጄ እንዳይመስላችሁ፡፡ ግራ ቢገባኝ ነው፡፡ ሌላም ጥያቄ አለኝ - ያለፈው ሥርዓት ከተገረሰሰ ምን ያህል ጊዜ ሆነው? (ውዥንብሩ መጥራት አለበት!) አንዳንዴ ያለፈው ሥርዓት “አስማተኛ” ይመስለኛል፡፡ ለምን መሰላችሁ? አንዳንድ ሰዎች አሁንም ከ24 ዓመት በኋላ እንኳን ስለሱ ማውራት አልተዉም፡፡ ለሁሉ ነገር ያለፈውን ሥርዓት ካልጠሩ አይሆንላቸውም - በተለይ የኢህአዴግ ካድሬዎች፡፡ (ፍሬሾቹን ማለቴ ነው!)
 ሰሞኑን EBC ባቀረበው የዜና ዘገባ ላይ “…የሴቶች ጥቃት ያለፈው ሥርዓት ችግር ስለሆነ እንታገለዋለን…” (really?!) የሚል ነገር የሰማሁ መሰለኝ፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል … ራሱ ኢህአዴግም እንኳን  የሴቶች ጥቃት “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ነው አይልም፡፡ እንዲያ ካለማ--- ያለፈው ሥርዓት አልተገረሰሰም ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ እንዳልኩት “አስተማኛ” ነው፡፡ (መቃብር እየፈነቀለ የሚወጣ!)
ይሄውላችሁ --- በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዓይነትም በመጠንም እየጨመሩ ለመምጣታቸው ከፖሊስ ፕሮግራም የበለጠ ማስረጃ የለም፡፡ (የሴቶች መብት ተሟጋቾችም ምስክር ናቸው!) አስገድዶ መድፈር፣ አሲድ መድፋት፣ ከባድ ድብደባና የአካል ማጉደል እንዲሁም አሰቃቂ ግድያዎች…በእጅጉ በርክተዋል፡፡ (ሰብዓዊ ልማት ተዘንግቷል!)
እናም--- የሰሞኑ የEBC ዘገባ blame shifting (“የእምዬን ወደ አብዬ”) እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡ ሃቁን እንነጋገር ከተባለ --- የሴቶች ጥቃት  “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ሳይሆን የእኛው የራሳችን ችግር ነው፡፡ (የኋላ ቀርነት፣ የትምህርት አለመስፋፋት፣ የግንዛቤ ማነስ፣ የአመለካከት ችግር ወዘተ…) ነገርዬው እምብዛም ከስርዓት ጋር የሚያያዝ አልመሰለኝም (ፖለቲካ እኮ አይደለም!) የግድ የሥርዓት ችግር ነው ከተባለም ባለቤቱ የአሁኑ ሥርዓት ነው፡፡ እናሳ? … እናማ በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ወዳለፈው ሥርዓት ለማሻገር ከመታተር ይልቅ እውነታውን ተቀብሎ ለመፍትሄ መትጋት ይሻላል፡፡ (ያለፈው ሥርዓት ከበቂ በላይ የራሱ ኃጢያቶች እንዳሉት አንዘንጋ!!)
ይሄውላችሁ ----- እንኳንስ በቅርብ ዓመታት እየተባባሰ የመጣው “የሴቶች ጥቃት” ይቅርና በእርግጥም ካለፈው ሥርዓት የተወረሱ ናቸው የሚባሉት (እነ ድህነት፣ ሙስና፣ የስልጣን ጥመኝነት፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት፣ የነፃነት አፈና፣ የፍትህ መጓደል ወዘተ…) ቢሆኑም እንኳ --- 20 ዓመት ስላለፋቸው  ውርስነታቸው አብቅቷል፡፡ (ከአባት የተወረሰ ንብረትም እኮ ለዘላለም በውርስነት አይጠራም!) ከምሬ እኮ ነው… ከአሁን በኋላ ችግሮችን ባለፈው ሥርዓት ማሳበብ ራስን ለትዝብት ማጋለጥ ነው፡፡
በመጨረሻ አንድ ሃሳብ ላቅርብ፡ ከፆታዊ ጥቃቶች አንዱ የሆነው አስገድዶ መድፈር፣ ለምን በፀረ ሽብር ህጉ ውስጥ አይካተትም? ይሄ እኮ… ሥርዓቱን ወይም ህገመንግስቱን በኃይል ለመናድ ከመሞከር ፈፅሞ አይተናነስም፡፡ ሴቶች ላይ ጥቃት መፈጸም - ቤተሰብን --- ህዝብን --- መንግስትን ---- አገርን --- ማሸበር ነው!!

“...በሴቶች ላይ የሚፈጸመው የአስገድዶ መድፈር ጥቃት በአብዛኛው ቅርብ በሆኑ     ወይንም በሚታወቁና እምነት በተጣለባቸው ወንዶች አማካኝነት ነው፡፡  ይህም     በስነተዋልዶ ጤና በኩል በከፍተኛ ሁኔታ የጤናን ችግር ከሚያስከትሉና የሴቶችን የሰብአዊ መብት ከሚገፉ ድርጊቶች የተመደበ ነው፡፡” - WHO
ከላይ ያነበባችሁት እውነታ በመላው አለም ከግምት ውስጥ የገባና ሀገራት ችግሩን ለመቅረፍ ያላሰለሰ ጥረት ሲያደርጉ የሚስተዋልበት ነው፡፡ የአለም የጤና ድርጅት መረጃውን በማከልም የሚከተሉትን ነጥቦች ለንባብ ብሎአል፡፡
በቅርብ በአለም ላይ የተገኘው መረጃ እንደሚገልጸው፡-
በአለም አቀፍ ደረጃ 35% የሚሆኑ ሴቶች በሕይወት ዘመናቸው በሚያውቁትም ይሁን በማያውቁት ሰው የወሲብ ጥቃት ተፈጽሞባቸዋል፡፡
ከእነዚህም ውስጥ በአማካኝ 30% የሚሆኑት ሴቶች በቅርባቸው ካለ ወይንም አብሮአቸው በሚኖር ሰው ድርጊቱ እንደተፈጸመባቸው መስክረዋል፡፡
በአለም 38% የሚሆኑ ሴቶች ሕይወት የጠፋውም በሚያውቁዋቸው ወይንም በኑሮ ተጋሪዎቻቸው መሆኑን የአለም የጤና ድርጅት ይመሰክራል፡፡
በሴቶች ላይ የሚደርስ ጥቃት በአካል፣ በአእምሮ፣ በወሲብ የሚፈጸም ሲሆን ይህም ለስነተዋልዶ ጤና ወይንም ሌላ ተያያዥ ለሆኑ የጤና እክሎች (ኤችአይቪ) ሊያጋልጥ ይችላል፡፡
በሴቶች ላይ የወሲብ ጥቃቱን የሚፈጽሙት ወንዶች ምናልባትም ዝቅተኛ ትምህርት ያላቸው ወይንም በቤተሰቦቻቸው ዘንድ ለሕጻናት በቂ ትኩረት ወይንም እንክብካቤ ሲደረግ ማየት ያልቻሉ ወይንም በቤተሰብ ዘንድ ጥቃት ሲፈጸም፣ ጎጂ የሆኑ አልኮሆል የመውሰድ ልምድ፣ የስርአተ ጾታ ክፍፍል ሲደረግ መመልከት፣  የሴቶች እኩልነት ዝቅ ማለትን እያዩ ያደጉ ሊሆኑ እንደሚችሉ ዘገባው ያስረዳል፡፡
ባለፈው ሳምንት እትም የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በመቀሌ ከተማ ሐይደር ሆስፒታል ያቋቋመውን ተገደው የተደፈሩ ሴቶች የሚታከሙበትን ሞዴል ክሊኒክ በንባብ ማስጎብኘታችን ይታወሳል፡፡ በዚያም ያገኘናቸውን ባለጉዳዮች ማብራሪያ አቅርበን ለዚህ እትም ቀጣይ እንደሚኖረው ገልጸናል፡፡ በመግቢያው ላይ “...መምህርማ አባት ወይንም እናት...” የሚለውን ርእስ የተጠቀምነውም ምክንያት ስላለው ነው፡፡ ለዚህ እትም ማብራሪያ ያገኘነው በሞዴል ክሊኒኩ ከምትሰራው ከሲ/ር አበባ ከበደ ነው፡፡
በመቀሌ የተከሰተ አንድ ታሪክ እናስነብባችሁ፡-
ሰውየው በመቀሌ ከተማ በሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት አስተማሪ ነው፡፡ ከሚያስተምራቸው ተማሪዎች መካከል የተወሰኑትን ጥናት አስጠናችሁዋለሁ በማለት በየቀኑ በተራ በተራ ከእርሱ ጋር እንዲቆዩ ያደርጋል፡፡ የመምህሩ አላማም ሕጻናቱን ማስተማር ሳይሆን አስገድዶ መድፈር ነበር፡፡ ድርጊቱን ከፈጸመ በሁዋላም ልጆቹ ለማንም ይህንን ታሪክ እንዳይ ናገሩ ...ከተናገሩም ጉዳት እንደሚያደርስባቸው እያስጠነቀቀ ነበር የሚለቃቸው፡፡ በስተመጨረሻውም ከእርሱ ጋር ለመቆየት ተረኛ የነበረች በእድሜዋ ወደ አስራ ሁለት አመት የሚሆናትን ሕጻን በፊንጢጣዋ ጭምር ስለደፈራት ሁኔታው ከቁጥጥር ውጭ ይሆናል፡፡ ሕጻኑዋ እንደተለመደውም በማስጠንቀቂያ ቢለቃትም ...እርስዋ ልትደብቀው የማትችለው በመሆኑ ሰውየው ይጋለጣል፡፡  የህጻኑዋ ቤተሰቦች ልጅቱን ወደሐኪምቤት በማድረስ ወደህግ ቦታም ሄደው ጉዳዩን በመከታተል ላይ ናቸው፡፡
“...እዚህ ላይ አንድ የሚያሳዝን ክስተት ተፈጽሞአል፡፡ ሰውየው ሕጻኑዋን ከጥቅም     ውጭ     አድርጎ በመድፈሩ ምክንያት የልጅቱ ገላ እንዳይሆን ሆኖአል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ     ...መምህሩ ኤችአይቪ ቫይረስ በደሙ ውስጥ የሚገኝ በመሆኑ ህጻኑዋንም በቫይረሱ እንድትያዝ አድርጎአታል፡፡ መምህሩ ዛሬ በህግ የተያዘ ቢሆንም የህጻኑዋ የወደፊት የህይወት እጣ ፈንታ ግን ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡ እጅግ ...ያሳዝናል፡፡ መምህርማ በእናትና አባት የሚመሰል አይደለምን? ይህንን ድርጊት ይፈጽማል ብሎ መገመት እጅግ ያስቸግራል፡፡ እንደዚህ ያለው መምህር የሌሎች     መልካም ስነምግባር ያላቸውን መምህራን በጎ ተግባር የሚያጠፋ ስለሆነ ተገቢው እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል፡፡”ሲስተር አበባ እንደገለጸችው ...ይህች ልጅ ጉዳትዋ ስለከፋ ወደህግና ሕክምና ቀረበች እንጂ ይህ መምህር ጥቃት ያደረሰባቸው ሌሎች ህጸናትም አሉ፡፡ ማንኛውም ቤተሰብ ልጆቹን ግልጽ ውይይት ማስተማር እንዳለበትንና ልጆች ከማንኛውም ሰው የሚሰጣቸውን ማስጠንቀቂያ ወደጎን በመተው እውነቱን ለወላጆቻቸው መንገር እንዳለባቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡
ሲስተር ሳራ በአይደር ሆስፒታል ያነጋገርናት ባለሙያ ናት፡፡ እሱዋም እንደምትመሰክረው ወላጆችም ይሁኑ ትምህርትቤቶች እንደዚህ ያለውን አስጸያፊ ተግባር ህጻናቱ አስቀድሞውኑ እንዲያውቁ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
“...በተለይም ወላጆች በግልጽ ልጆቻቸውን ተገዶ በመደፈር ሁኔታ ላይ የሚያስተምሩ     አይመስለኝም፡፡ እንዲሁ በደፈናው ሴት ልጆቻቸውን ለምን በሰአቱ ከትምህርት ቤት     አትመጪም ወይንም ለምን ከወንድ ጋር ትሄጃለሽ የመሳሰሉትን ተግባራዊ የማይደረጉትን ቁጣዎች ሊሰነዝሩ ይችላሉ፡፡ ይህ ግን ትክክለኛው የማስተማሪያ መንገድ     አይደለም፡፡
ልጆቹ ከትምህርት ቤት መውጫ መግቢያ ሰአታቸውን መጠበቅ የሚገባቸው ለምን ድነው? ምን ችግር እንዳይገጥማቸው ነው?
ሕጻናቱ ከወንድ ጋር አትሂጂ የሚለውን ቁጣ በደፈናው ሊቀበሉት የማይችሉትን መሰንዘር ትክክለኛው መንገድም ስላልሆነ... ከሱ ይልቅ ወንዶችም ሆኑ ሴቶች በተሳሳተ መንገድ በልጆ ላይ ምን ጉዳት ሊያስከትሉ እንደሚችሉ እና ይህ ግን የሁሉም ወንዶች እና ሴቶች ተግባር እንዳ ልሆነም ማስረዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተለይም ተገዶ መደፈር ምን ማለት እንደሆነና በልጆቹ ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት እና የመብታቸውን ሁኔታ በትክክል እንዲያውቁ ማድረግ ከወላጆች፣ ከትምህርት ቤቶች እንዲሁም ከመላው ሕብረተሰብ የሚጠበቅ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡”
ሴቶች የወሲብ ጥቃት ወይንም ትንኮሳ ደርሶባቸዋል ሲባል የግድ የወሲብ ግንኙነት ተደርጎአል ማለት ብቻ አይደለም፡፡ ነገር ግን ወሲብ ለመፈጸም ሙከራ ማድረግ፣ በእጅ ወይንም በአይን በመሳሰሉት ሁሉ የተለያዩ ትንኮሳዎችን ማድረግ፣ በንግግር በመሳሰሉት ሁሉ ሴቶችን መተንኮስ፣ መብትን መጋፋት መሆኑን ከግምት የማያስገቡ አሰራሮች ሴት ልጆችን እየጎዱ መሆኑን ሲ/ር አበባ ገልጻለች፡፡
“...ታካሚዋ የመጣችው መስከረም ወር ላይ ነው፡፡ እድሜዋ አስራ ሁለት አመት     ይሆናል፡፡ ልጅቱዋ በአሳዳጊዋ አራት ጊዜ የወሲብ ጥቃት ተፈጽሞባታል፡፡ ያች ልጅ     ወደሐኪም ቤት መጥታ ሕክምና ከተደረገላት በሁዋላ የተሰጣት ምስክርነት ክብረ ንጽህናዋ እንዳልተነካ እና የመደፈር ምልክት እንዳልታየባት ነው፡፡ ይህንን ይዛ ወደህግ     ቦታ ስትሄድ ግን ልጅትዋ የምትናገረውን ምስክርነት ከምንም ሳይቆጠር ክብረ ንጽህናዋ ስላልተወሰደ ለክስ መሰረት የሚሆን ነገር የለም ከሚል ፋይሉም ተዘግቶአል... ሰውየውም     በነጻተለቅቆአል፡፡”
ልጅትዋ በአሳዳጊዋ አራት ጊዜ የወሲብ ጥቃት ከተፈጸመባት እንዴት ክብረንጽህናዋ አልተወሰደም የሚል ጥያቄ በአንባቢዎች ዘንድ የሚጭር ነው፡፡ ሲ/ር አበባ እንደገለጸችው፡-
“...የድንግልና ቀለበቱ በተፈጥሮ የተለያየ አፈጣጠር አለው፡፡ አይነቱ አራት አይነት     ሲሆን ከዚያ ውስጥ አንደኛው ቅርጽ በራሱ ጊዜ የመለጠጥ ባህርይ ያለው ነው፡፡ ይሄ     አይነቱ ሲሆን ከግንኙነት በሁዋላ ተመልሶ ወደቦታው የሚገጥም ነው፡፡  እንደዚህ አይነት ተፈጥሮ ከሆነ የመድማት ወይንም የመቁሰል ምልክት ስለማያሳይ ክብረንጽህና አልተነካም ሊባል ይችላል፡፡  ነገር ግን ልጅትዋ በሰውየው ተደጋጋሚ የወሲብ ጥቃት እንደደረሰባት ከገለጸች እና ሌሎች መረጃዎች ከተሰባሰቡ ሐኪም     የክብረንጽህና መወሰድ ምልክት በገላዋ ላይ አይታይም በማለቱ ብቻ መረጃው በሐኪም     ካልተረጋገጠ ክስ ለመመስረት አያበቃም በሚል ጥፋተኛውን መልቀቅ በልጅትዋ     ሞራልና የወደፊት ሕይወት ላይ ጠባሳ እንደሚጥል መገመት አያዳግትም፡፡”  
የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር በመቀሌ ሐይደር ሆስፒታል ባቋቋመው ሞዴል ክሊኒክ የሚመጡ ታካሚዎች ከሌሎች ታካሚዎች ጋር በመደባለቅ ወረፋ ሳይጠብቁ በቀላልና በፍጥነት አስፈላጊው ምርመራና ሕክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ከተጠቃሚዎች ለመረዳት ተችሎአል፡፡ ተገዶ መደፈር የደረሰባቸው ሴቶች እርግዝና መኖር ያለመኖሩ፣ ከኤችአይቪ ቫይረስ ነጻ መሆን ያለመሆናቸው እና የመሳሰሉትን ሕክምናዎች በነጻ ከማግኘታቸውም በላይ ጉዳያቸው በህግ እንዲታይላቸው አስፈላጊው ሕክምናና መረጃ ካለምንም ክፍያ ይሰጣቸዋል፡፡ በመሆኑም በቅርብ ጊዜ  ስራውን የጀመረው ክሊኒክ በሶስት ወር ጊዜ ውስጥ ከ75/ያላነሱ ባለጉዳዮችን ማስተናገዱን ሲ/ር አበባ ገልጻለች፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

     በአዲስ አበባ ከተማ ለመጀመርያ ጊዜ ኢንተርናሽናል የግማሽ ማራቶን ውድድር የካቲት 1 ቀን ላይ እንደሚካሄድ ታወቀ፡፡ ውድድሩን ሄማ ሬስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ያዘጋጃል፡፡ ትናንት በራዲሰንብሉ ሆቴል በተሰጠው መግለጫ ሄማ ሬስ የኢትዮጵያን አትሌቲክስ ስፖርት በልማቱ ዘርፍ ለማሳደግ እና የውድድር አድማሱን ለማስፋፋት እንደተቋቋመ ተገልጿል፡፡ የሄማ ሬስ ዋና ስራ አስኪያጅ ዋና ሱፕር ኢንቴንዳንት ሁሴን ሼቦ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ከፍተኛ ልምድ ያለው አሰልጣኝ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ዋና ሱፕር ኢንቴንዳንት ሁሴን ሼቦ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ሲናገር‹‹ በርካታ ወጣት አትሌቶች ልምምድ ይሰራሉ፡፡ ግን ውድድር የማግኘት እድላቸው ጠቧል፡፡ ስለዚህም መፍትሄ የሚሆን ውድድር አዘጋጅተናል›› ብሏል፡፡  
አዳዲስና ጠንካራ አገርን የሚወክሉ አትሌቶች ለማፍራት ያግዛል በተባለው የግማሽ ማራቶን ውድድሩ ላይ ከ2000 በላይ ብቁ አትሌቶች እንደሚሳተፉ ሲጠበቅ፤ ከኡጋንዳ፤ ከኬንያ፤ ከሞሮኮ፤ ከቻይና እና ከአውሮፓ የተለያዩ አገራት አትሌቶች እንደሚመጡም ተነግሯል፡፡ ከዋናው ውድድር በተያያዘ በሚካሄደው የ10 ኪሎሜትር ህዝብ አሳታፊ የጎዳና ላይ ሩጫ የተዘጋጀሀ ሲሆን 10ሺ ስፖርተኞች ይሳተፉበታል፡፡ የኢትዮጵያ ታላላቅ አትሌቶች ጥሩነሽ ዲባባ፤ ስለሺ ስህን፤ የኔው አላምረው፤ ኢማና መርጋ፤ ሰንበሬ ተፈሪ ለውድድሩ ስኬታማነት በክብር አምባሳደርነት ድጋፍ ሰጥተዋል፡፡
 ሄማ ሬስ ደረጃውን የጠበቀ የአትሌቶች ማሰልጠኛ ማእከል ለመገንባት እንዲሁም በክልሎች እና በከተማ መስተዳድሮች የተለያዩ የትራክ እና የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድሮችን የማዘጋጀት ዓለማዎች መሰነቁም በጋዜጣዊ መግለጫው ተጠቁሟል፡፡

በኤሮቢክስ አሰልጣኝነት ከ10 ዓመታት በላይ የሰራው አቤኔዘር ይብዛ በእግር ኳስ አሰልጣኝነት ሙያው የሚያስፈልገውን ትምህርት የቀሰመ ቢሆንም የመስራት እድል አላገኘም፡፡ ከ3 ዓመት በፊት ትሬፓታ የተባለውን የእግር ኳስ አሰለጣጠን ፍልስፍና መቅረፅ ችሏል፡፡ ግን የሙከራ እድል ማግኘት አልቻለም፡፡ የስፖርት ባለሙያው አቤኔዘር ይብዛ ባለፈው ሳምንት ከስፖርት አድማስ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ በተጨዋችነት ስላሳለፈው ጊዜ፤ ከዚያም በኢትዮጵያ እግር ኳስ  ያስተዋላቸውን ሁኔታዎች፤ በስፖርቱ ዙርያ ያሉትን መሰረታዊ ችግሮችን ከዓለም አኳያ በንፅፅር በማየት ማብራርያ ሰጥቷል፡፡ የቃለምልልሱ ሁለተኛ ክፍል ከዚህ በታች እንደቀረበው ነው፡፡

ትሬፓታ እንዴት ተፈጠረ?
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ስልጠና ችግር ላይ መሆኑን ሁሌም እየተነጋገርን ግን ምንም አለመሰራቱ ያሳስበኛል የሚለው አቤነዘር፤ መፍትሄ መፈለጉን ስላመነበት የግሉን ጥረት አድርጓል፡፡ ኢትዮጵያ  በእግር ኳሷ አንድ የተለየ እና ከዓለም ጋር ተፎካካሪ የሚያደርግ የስልጠና ስርዓት ያስፈልጋታል ብሎ መፍትሄ ለማፈላለግ ሲመራመር ቆይቷል፡፡ ምሳሌ አድርጎ የተነሳው ደግሞ በባርሴሎናው አካዳሚ ላሜሲያ ያስተዋለውን የስልጠና መዋቅርን ነው፡፡ የቀድሞው የሆላንድ ምርጥ ተጨዋች እና አሰልጣኝ ዮሃን ክሮይፍ፤ ቶታል ፉትቦልን እንዴት ይዞት ስፔን እንደገባ አጥንቷል፡፡ ይህንኑ ሲያስረዳም  የሆላንድ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የነበሩት ሩኒስ ሚሸልስ በአያክስ ክለብ የሚሰሩበትን ስልጠና ወደ ስፔን በማሻገር ዮሃን ክሮይፍ እንዴት ስኬታማ እንደሆነ በማብራራት  ነበር፡፡ ክሮይፍ በዚህ የጨዋታ ታክቲክ በሱ ዘመን የሚፈለግበት ደረጃ ባይደርስም ይሁንና በላሜሲያ አካዳሚ ከስር መሰረቱ እንዲሰራበት አደረገ፡፡ በአንድ ወቅት አድጎ ከፍተኛ ለውጥ በማምጣት በዓለም አቀፍ ደረጃ ገንኖ ይወጣል በሚል እምነት ነበር፡፡ ይሄው የስልጠና ስርዓት በቅብብሎሽ አካዳሚው ውስጥ ሲሰራበት ቆይቶ ከቫን ሀል ወደ ፍራንክ ሪያካርድ በመጨረሻ በባርሴሎና ፔፔ ጋርድዮላ የአሰልጣኝነት ዘመን ክለብ ተግባራዊ ሆኖ ውጤቱን ለማየት ተችሏል፡፡ በዚህ አይነት መንገድ የሚሰራበት የአሰለጣጠን ስርዓት ለኢትዮጵያ እግር ኳስ በጣም ያስፈልገዋል ብሎ ያመነው አቤኔዘር ተመሳሳይ የአሰለጣጠን ለውጥ  በኢትዮጵያ ውስጥ ለመተግበር ለረጅም ጊዜ እራሱን በማዘጋጀት እና ምርምሩን በማሳደግ ቆይቷል፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስ ከላይ በዝርዝር የሰፈሩት የስልጠና መሰረታዊ ግብዓቶች ላይ ሰፊ ተግባራት አለመከናወናቸው በመገንዘብ ይጀመራል፡፡ በስልጠና ፍልስፍና እና የአጨዋወት ታክቲክ ባለመኖሩ በስፖርቱ እድገት እና ለውጥ ለማሳየት አልተቻለም፡፡ አሁን ያሉን ቡድኖች በክለብ እና በብሄራዊ ቡድን ደረጃ በኢንተርናሽናል ውድድር የማለፍ እድል የምናገኘው በጥሎ ማለፍ ነው፡፡  በራሳችን መንገድ ሰርተን ስለማናውቅ ሁሌም ተከታይ ነን፡፡ ስለዚህም የራሳችን መንገድ ያስፈልገናል በማለት አቤኔዜር ይብዛ ትሬፓታን ለመፍጠር እንደተነሳሳ ያስረዳል፡፡  የተሻለ ውጤት ሊመጣ የሚችለው ከላይ የተዘረዘሩት መሰረታዊ ብቃቶች በክህሎት ዳብረው ሲሄዱ ብቻ ነው በማለትም በልበሙሉነት ይናገራል፡፡ የጨዋታ ፍልስፍናውን በቅርቡ ውጤቱን ለማየት እንዲቻል ተብሎ የተጠነሰሰ ነው፡፡ አቤኔዘር ትሬፓታ የጨዋታ ፍልስፍናን የፈጠርኩት ከቲኪታካ የባርሴሎና  አጨዋወት ተነስቼ ነው ይላል፡፡ በመጀመርያ የተጨዋቾቻችን ኪሎ ክብደት አነስተኛነት ከሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ጋር ሲነፃፀር እንዳነስን በማየት በራሳችን ፍልስፍና ጨዋታ ተሻሽለን የምንገኝበት ስልት ነው፡፡ በትንፋሽ ብልጫ ስላለን በምንሸፍነው ኪሎ ሜትር ከሌላው ዓለም ብልጫ ለመውሰድ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ተጨዋቾች በተፈጥሯቸው አጫጭር ኳስ መጫወት ይወዳሉ፡፡ ተሰጥኦም አላቸው፡፡ ትሬፓታ ይህን ኳስ ይዞ የመጫወት ክህሎትን ዓላማ እንዲኖረው ውጤት እንዲያስገኝ የምናዳብርበት ይሆናል፡፡ በሂደት ማሸነፍ የምንችልበት ነው፡፡
እኔ የፈጠርኩት የጨዋታ ፍልስፍና በይበልጥ ተፎካካሪ እንደሚያደርገን እና ዓለምን እንድንቋቋም እንደሚያስችለን በይበልጥ ማሳየት ፍላጎቱ አለኝ፡፡  ይህን የጨዋታ ፍልስፍናዬን ትሬፓታ ብየዋለሁ፡፡ ትሬፓታ የሚለውን ስያሜ የፈጠርኩት ከጣሊያንና እንግሊዘኛ ቃላቶች ውህደት ነው፡፡ በአማርኛ ቋንቋ ለጨዋታው ፍልስፍና ሙሉ ስያሜ ስላጣሁ ነው ብሏል፡፡ ትሬፓታ በዓለም የስልጠና ፍልስፍና ውስጥ አንድ ስልት ሆኖ የሚገባበት አቅም እንዳለው የሚያምነው አቤኔዜር፤   በጣሊያንኛ ትሬ ማለት ሶስት ሲሆን ፓ ማለት ማቀበል ታ ደግሞ ታክቲክ ነው፡፡ በአጠቃላይ የሶስትዮሽ የጨዋታ ፍልስፍና ማለት ነው፡፡ በሌላ አቅጣጫ ትርጓሜ ሊኖረውም ይችላል፡፡ ታ ለሶስት ማዕዘን፤ ፒ ለፒራሚድ እንዲሁም ቲ ለታክቲክ አድርገን ሶስት ማዕዘናዊ ፒራሚዳዊ ታክቲክ እንደማለት ነው፡፡ ዓለም በብዛት የሚያውቀው 4321 የጨዋታ ታክቲክ ይህን አሻሽሎ የመጣ ነው፡፡ በጣም ተጠጋግተን ተጋጣሚን አድክመን ለመጫወት የሚያስችለን ነው፡፡ ምናልባትም 33 ለ11 ብልጫ ኖሮን ልንጫወትበት የምንችለው ታክቲክ ይሆናል፡፡ ሁል ጊዜ በትሬፓታ 3ለ1 ሆነን ነው ተቃራኒ ቡድንን የምንገጥመው፡፡ በየትኛውም አቅጣጫ የሚንቀሳቀስን የተቃራኒ ቡድን ተጨዋች ለሶስት መካከላከል፤ አንድ ተጨዋች ብዙ በመንቀሳቀስ ይሰራል፡፡ እድሜያቸው ከ13 ጀምሮ የሆኑ ታዳጊዎች ላይ የስልጠና መዋቅሩን ተግባራዊ አድርጎ በመስራት በ17 አመታቸው ለክለብ እና ለብሄራዊ ቡድን የሚበቁ ምርጥ ተጨዋቾችን አሰልጥኖ ማውጣት ይቻላል፡፡ የእድሜ ማጭበርበር ለዚህ አሰራር የሚያዋጣ አይደለም፡፡ በትክክለኛ እድሜ ከሌላው አለም በተለይ ከሰሜን እና ምእራብ አፍሪካ ቡድኖች ጋር ተፎካካሪ ሆኖ ለመቅረብ የሚያግዝ ስልጠና ያስፈልጋል፡፡በትሬፓታ አንድ ተጨዋች ለሙሉ ብቃት የሚበቃው በኢትዮጵያ ደረጃ  ከአስራ ሶስት አመት ተነስቶ በአስራ ሰባት አመቱ ነው፡፡ ሂደቱ እንዳይነጥፍ ከስር ከስር በመተካት ይሰራበታል፡፡ በሃያ ዓመቱ ለብሄራዊ ቡድን ብቻ ሳይሆን በፕሮፌሽናል ደረጃ ብቁ የሆኑና ለብዙ አመት ቢያንስም እስከ ሰላሳ ዓመታቸው በብቃት የሚጫወቱትን በቀላሉ በትሬፓታ ማፍራት እንደሚቻልም በልበ ሙሉነት ይናገራል፡፡
ከገነነ  ተጠጋግቶ መጫወት አንፃር  ሲታይ
የትሬፓታ ስልጠና በእርግጥ ከዚህ በፊት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ከተሞከሩ የስልጠና ዘዴዎች እና የጨዋታ ፍልስፍናዎች በብዙ መልኩ ልዩነት አለው፡፡ ከዚህ ቀደም የገነነ መኩርያን ተረዳድቶ ወይንም ተጠጋግቶ መጫወት የተባለውን ፍልስፍና በንፅፅር መገምገሙን አቤኔዘር ያስረዳል፡፡ ገነነ ፈጥሮታል በተባለው የጨዋታ ፍልስፍና ተጨዋቾች ምን ድረስ ተጠጋግተው እንደሚጫወቱ ምክንያታቸው እና ውጤቱ የተብራራ አይመስለኝም የሚለው አቤኔዜር፤ በገነነ የጨዋታ ፍልስፍና ተጋጣሚን ከራስ ሜዳ ጠራርጎ ማውጣት ቢባልም በትሬፓታ ጨዋታ ደግሞ ተጋጣሚን እየቀነሰ ሜዳን አጥቅቶ መጫወት የሚል ዘዴ መኖሩን በማስረዳት ነው፡፡ በትሬፓታ ሜዳን ማጥቃት ምንድነው፤ የባላጋራ ቡድን ተጨዋች በእኔ ቡድን ሜዳ ውስጥ ቢቀር እሱን መጠበቅ የለብኝም፤ ሜዳውን አጠቃላው ተጨዋች እቀንሳለሁ ሜዳን አጠባለሁ፡፡ ወደ ግብ ክልል እደርሳለሁ ጎል ፈጥሬ አገባለሁ፡፡ ድንገት ኳሱ ቢነጠቅ በመልሶ ማጥቃት ቡድኑን አደጋ ላይ የሚጥል አጨዋወት አይሆንም ተብሎ ቢጠየቅም ትሬፓታ ለዚህም መልስ አለው፡፡ አይገባም፡፡ ምክንያቱም በትሬፓታ ሁል ጊዜ ስንጫወት 3ለ1 ሆኖ ክፍተት በሌለበት ሁኔታ መጫወት ኳስ ወደ አደገኛ ክልል እንዳትገባ ስለሚያደርግ ነው፡፡ በገነነ ፍልስፍና 21 ሰው በተቃራኒ ቡድን ሜዳ መሰብሰቡን ያመጣል፡፡ በመጀመርያ በዚህ ጨዋታ ቦታ ለመፍጠር እና ለማግኘት ይቸግራል፡፡ ምክንያቱም 22 ሰው በግማሽ ሜዳ ሲገኝ ምን ያህል ሜዳው  እነደሚጠብ ማሰብ ነው፡፡ ሁለተኛ በጠበበ የጨዋታ ሜዳ ላይ ኳስ የአካል ንክኪ ስላለው ኢትዮጵያን ተጨዋቾች ደግሞ በአካል ብቃት ስለምንደክም ኳስን በቀላሉ በመቀማት አደጋ መፍጠሩ አይቀርም፡፡ ለምን ጥንካሬ በብዛት አንሰራም ይላል ኳስ ጨዋታ ምንግዜም የሚያደክም ነገር አለው ይህን ሰርቶ ማዳበር ይጠይቃል፡፡ የገነነ ፍልስፍና መፅሃፉ ላይ እንዳየሁት ምንም አይነት ፎርሜሽን የሚያነሳው ነገር የለም፡፡ ያለን ነገር ተብሎ የተፈጠረ ቋንቋ ቢኖርም በገነነ የጨዋታ ፍልስፍና ስላለው ነገር ምንም በግልፅ የተቀመጠ ማብራርያ የለም፡፡ በትሬፓታ የጨዋታ ፍልስፍና ብዙ ልዩ ነገሮች አሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን ተጨዋቾች ትንፋሽ አላቸው ባላጋራዎች ፈጣን ጡንቻ አላቸው፡፡ በሳንባችን ፈጣን ጡንቻዎን ማሸነፍ እንችላለን የሚል መሰረታዊ ስራ በትሬፓታ አጨዋወት መተግበሩ ውጤት ያመጣል፡፡
የሙከራ እድል ለምን አጣ?
ትሬፓታ የፈጠርኩት ከሶስት ዓመት በፊት ነው የሚለው አሰልጣኝ አቤኔዘር የጨዋታ ፍልስፍናውን በክለብ ደረጃ በተለይ በሲ ቡድኖች ለመተግበር ተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም ከድካም በስተቀር ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ወደ አዲስ አበባ ትልልቅ ክለቦች በመሄድ የተሻለ ነገር አለኝ በማለት ሊያሳምን ሞክሮ ምንም ምላሽ ማግኘት አልቻለም፡፡ በታዳጊዎች ላይ ልስራና ስፖርቱን እናሳድግ ብዬ  ብዙ ደክሜያለሁ፡፡ አንዳንዶች ሃሳቤ በመስማት ጥሩ ነው ብለው ቢደግፉም ትንሽ ጊዜ ስጠን ይሉና ተግባራዊ ለማድረግ ግን ይሳናቸዋል፡፡ ወደ ክለቦች ለመቅረብ ብዬ ሌላ ሙከራም አድርጌ ነበር፡፡ በአካል ብቃት አሰልጣኝነት ተቀጥሬ በመግባት የጨዋታ ፍልስፍናዬን ለማስፋፋት ያደረግኩት ሙከራ ነው፡፡ ይሁንና በዚህ መንገድም መሞከርያ እድሉን አላገኘሁም፡፡ በእርግጥ ክለቦች በትሬፓታ የጨዋታ ፍልስፍና ታዳጊዎቻቸውን ለማሰራት ብዙ በጀት ስለሚጠይቃቸው  ፈቃደኛ ያልሆኑ ይመስለኛል፡፡ በየክለቦቹ በቂ የልምምድ ሜዳ፤ የስልጠና መሳርያዎች እና ቁሳቁሶች እንዲሁም የላብ መተኪያ እና የምግብ አቅርቦቶች አለመሟላታቸው እንቅፋቶች ይሆናሉ፡፡ በቂ የህክምና አገልግሎትም ይጠይቃል፡፡ ለትሬፓታ የጨዋታ ፍልስፍና በቂ የስልጠና መዋቅር ለመዘርጋት ደግሞ የተዘረዘሩት ነገሮች በጣም ያስፈልጋሉ፡፡ በጨዋታው ፍልስፍና ለመስራት ከባለሙያዎች ጋር ለመምከር ባደረግኩት ሙከራም በቅርብ ከማውቃቸው ሰዎች እንኳን ድጋፍ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ ገና የፍልስፍናውን ስያሜ ስናገር የሳቁብኝ ብዙዎች ናቸው፡፡ ማንም ለመቀበል ቸግሮታል፡፡ ወደ መንግስት እና የግል አካዳሚዎች ሃሳቡን ለማቅረብ የተወሰኑ ጥረቶች አድርጌም ነበር፡፡ በዚያ ግን ለስልጠና ሙያ ዲግሪ እና ከዚያም በላይ የትምህርት ደረጃ በመጠየቁ እንዳማይሳካልኝ ተረድቺያለሁ፡፡ በሌላ በኩል በኢትዮጵያ እግር ኳስ የአሰልጣኞች ቅጥር ያለው አሰራር እንቅፋት የሆነብኝ ይመስለኛል፡፡ ለአዲስ አሰልጣኝ እና የጨዋታ ፍልስፍና በቂ የስራ እድል የለም፡፡ ለነባር አሰልጣኞች ብቻ ነው እድል ያለው የሚጠየቀው ልምድ ብዙ ነው አዲስ ሃሳብ ያለው የመቀጠር እድል የለውም፡፡ ቢያንስ ለዋናው ቡድን ልምድ ያለው አሰልጣኝ እንደመስፈርት ቢቀመጥ መልካም ነው ለቢ እና ለሲ ቡድኖች በተለምዶ የስራ ልምድ መጠየቁ ለአዳዲስ የስልጠና ባለሙያዎች እና ፍልስፍናቸው የመቀጠር እድል መንፈጉ እኔንም ተፈታትኖኛል፡፡፡
በአጠቃላይ በትሬፓታ የጨዋታ ፍልስፍናዬ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ትንሽ ጣሳ ውሃ ይዜ መጥቻለሁ፤ ይህን የጣሳ ውሃ በተቃጠለው የኢትዮጵያ ህዝብ አንጀት እረጨዋለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ጠቃሚነቱን አስቦ የሚሰራበት ባለባልዲ ይመጣል ብዬ ተስፋ አድርጊያለሁ፡፡ ባለባልዲው ባለበርሜሉን ይፈጥራል፤ ባለበርሜሉ ደግሞ በቧንቧ ያመጣው ይሆናል፡፡ ከዚያም በኢትዮጵያ እግር ኳስ የጨዋታ ፍልስፍናው በእድሜዬ ተግባራዊ ባይሆን አሁን ተጀምሮ ሂደቱን ጠብቆ ከሄደ ለሌሎች የእድገት እንቅስቃሴዎች መነሳሻ የሚሆን አቅም ይፈጥራል ብዬ አምናለሁ፡፡
የጨዋታ ፍልስፍናዬን ለመተግበር በጉጉት እጠባበቃለሁ፡፡ ወደ ሚዲያ የመጣሁትም ይህን ትኩረት ለመፍጠር ነው፡፡ ለህዝብ  ያስተዋውቀኛል በሚል ነው፡፡ እያደገ የሚሄድበት መንገድ ይሄው ነው፡፡

Saturday, 20 December 2014 13:19

የፀሃፍት ጥግ

(ስለ ምርጫ)
* ከአዲስ ምርጫ የምንማረው ነገር ቢኖር ከቀድሞው ምርጫ ምንም አለመማራችንን ነው፡፡
ጌራልድ ባርዛን
* ምርጫ የምናካሂድበት ብቸኛው ምክንያት ከህዝብ የተሰበሰበው አስተያየት ትክክል መሆኑን ለማወቅ እንደሆነ ተሰምቷችሁ ያውቃል?
ሮበርት ኦርቤን
* በኦሎምፒክ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ብር ያሸልማል፡፡ በፖለቲካ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ግን ያስረሳል፡፡
ሪቻርድ ኒክሰን
* በፖለቲካው ዓለም ሴቶች ደብዳቤ ይተይባሉ፤ ቴምብር ይለጥፋሉ፤ በራሪ ወረቀት ያሰራጫሉ፡፡ ከዚያም ከምርጫው ይወጣሉ፡፡ ወንዶች ይመረጣሉ፡፡
ክላሬ ቡዝ ሉሴ
* እጩ ተመራጭ ከመንገድ ማዶ ሆናችሁ ከለያችሁ የምርጫ ወቅት ሪቅ አይደለም ማለት ነው፡፡
ኪን ሁባርድ -
* የምርጫ ድምፅ መመዘን እንጂ መቆጠር የለበትም፡፡
ጆን ክሪስቶፍ ፍሬድሪክ ቮን ሺለር
* የነፃ ምርጫ ችግሩ ማን እንደሚያሸንፍ ቀድሞ አለመታወቁ ነው፡፡
ሊኦኒድ ብሬዥኔቭ
* የምርጫው ውጤት የሚወሰነው ድምፅ በሚሰጡ ሰዎች ሳይሆን ድምፁን በሚቆጥሩ ሰዎች ነው፡፡
ጆሴፍ ስታሊን
* እንግሊዞች ነፃ ነን ብለው ያስባሉ፡፡ ነፃ የሚሆኑት ግን በፓርላማ አባላት ምርጫ ወቅት ብቻ ነው፡፡
ዣን ዣኪዩስ ሩሶ
* ሰዎች ከአደን በኋላ፣ በጦርነት ወቅት ወይም ከምርጫ በፊት የሚዋሹትን ያህል መቼም አይዋሹም፡፡
ኦቶ ቫን ቢስማርክ

Published in ጥበብ

    የሰው ልጅ አለኝታውና ማዕረጉ፣ ሞገሱና ኩራቱ ታሪኩ ነው፡፡ ታሪክ ደግሞ ታሪክነቱን ሊያገኝ የሚችለው የሰው ልጅ ራሱ ከትውልድ ወደ ትውልድ ጠብቆ በሚያስተላልፋቸው ወጐቹ፣ ቋንቋዎቹ፣ አፍአዊ ኪነቃሎቹ፣ ፊደልና ሥነ ጽሑፎቹ አማካኝነተ መኾኑ አያከራክርም፡፡ ታሪኩን በራሱ ፊደል መዝግቦ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚያስተላልፍ አገር ደግሞ በእጅጉ የታደለ ነው፡፡ በዓለም ላይ ከሚገኙ አያሌ አገራት መካከል የራሳቸውን ፊደል ቀርጸው የሚጠቀሙት ግን በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ከእነዚህም አንዷ በራስ ፊደል ተጠቃሚ ኢትዮጵያ መኾኗ ለሕዝቦቿ ታላቅ ኩራት ነው፡፡ ለዚህ ታሪካዊ ዕድል ያበቋት የጥንት አባቶቻችን ተጋድሎ በዚህ ትውልድ ያለነውንና ቀጣዩንም ጭምር በእጅጉ ያኮራል፡፡ ይህ ታሪካዊ ኩራት ዘለቄታዊነቱን ሊያገኝ የሚችለው ግን ይህ ትውልድ የተረከበውን ታሪካዊ ቅርስ በሚገባ ጠብቆ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ሲችል ብቻ መኾኑን ለአፍታም ቢሆን መዘንጋት የለበትም፡፡
እስከአሁንም ድረስ ኢትዮጵያ ወጐቿን፣ ቋንቋዎቿን፣ ባሕሎቿን ኪነ ቃሎቿንና የመሳሰሉትን በራሷ ፊደል ቀርፃ (ታሪኳን መዝግባ) ከትውልድ ትውልድ አሸጋግራለች፡፡
 ወደፊትም ታሸጋግራለች የሚለው ግን ጥያቄ ውስጥ እየገባ ነው፡፡ ምክንያቱንም በፊደሎቿ ላይ የተደጋገሙ ዘመቻዎች መካሔዳቸውና እየተካሄዱም በመገኘታቸው በሚል ዐጭር መልስ ከመዝጋት ይልቅ በመጠኑም ቢሆን መዘርዘሩ ተገቢ ይመስለኛል፡፡
የአገሪቱ የቋንቋ ምሁራን ለሁለት ጐራ ተከፍለው ፊደሎቻችን በዝተዋልና ይቀነሱ በሚሉና ፊደሎቹ ህፀፅ የለባቸውም በሚሉ ሐሳቦች መፋጨት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፤ ማለትም ዘመናትን አስቆጥረዋል፡፡
ይህ የፊደሎች ይቀነሱ ጉዳይ ከረጅም ዓመታት ጀምሮ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ በተለያዩ ግለሰቦችና ቡድኖች በቃል ሲወሳና በጽሑፍም ሲዘገብ መቆየቱ ይታወቃል፡፡ እንደምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ፊደሎች ይቀነሱ ብለው ከተነሡት ጥቂቶቹን እንመልከት፡፡
አቶ በእምነት ገብረ አምላክ፤ “የአንድ ቋንቋ ዕድገት ወይም አማርኛ እንደተስፋፋ ፲፱፻፵፯ ዓ.ም” መጽሐፋቸው “አማርኛን ማሻሻል ያስፈልጋል” ከሚለው ንዑስ ርዕስ ሥር ያሠፈሩት እንዲህ ይነበባል፡-
“…የአማርኛ ፊደሎች ብዛት ከመጠን ያለፈ ብዙ ስለሆነ መቀነስ አለበት፡፡…ብዙው ዓለም በ፳፮ የላቲን ፊደሎች የሚጠቀም ሲሆን አማርኛ ግን በ፻፪፴፯ ፊደሎች ይጻፋል…” በማለት የፊደሎቹ መብዛት ያስከተሏቸውን ችግሮች “ለጽሕፈት ያሳስታሉ፣ የእጅ ጽሕፈት መኪና እንዳይሠራ እንቅፋት ሆነዋል፣ ከመብዛታቸው የተነሣ ለጥናት ያስቸግራሉ፡፡ በእዚህም ምክንያት የፊደል በረከቱ ሳይደርሳቸው የሚቀሩ ብዙዎች ናቸው፡፡”
 በማለት ፊደሎቹ እንዲቀነሱ አስተያየታቸውን ዘርዝረዋል፡፡ ከበእምነት በፊትም ሆነ ከእሳቸው በኋላ በፊደላት ይቀነሱ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ ግለሰቦችና ቡድኖች ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ እነዚህም የመሰላቸውን መንገድ በመከተል የፈረዱባቸውን ሆሄያት እያስወገዱ መዝገበ ቃላትን ያህል ትልቅ ሥራ ለሕዝብ እያሠራጩ ይገኛሉ፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ይባስ ብለው የፊደል ገበታው ሙሉ በሙሉ እንዲለወጡ የራሳቸውን ጥናት እስከማቅረብ ደርሰዋል፡፡ አማርኛ ቋንቋ የሚጠቀምባቸውን ፊደላት እርግፍ አድርገን ትተን በላቲን ፊደሎች ሙሉ በሙሉ እንጠቀም ያሉም አሉ፡፡ እስቲ በግንባር ቀደምትነት ተጠቃሽ ሊሆኑ ይችላሉ ያልኳቸውን ሁለቱን ብቻ በምሳሌነት ለመጥቀስ ልሞክር፡፡
የመጀመሪያው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር በየካቲት ፲፱፻፺፫ ዓ.ም አዘጋጅቶ ያቀረበው “የአማርኛ መዝገበ ቃላት” የሚለው ነው፡፡ የመዝገበ ቃላቱ አዘገጃጀት በአዲስ የፊደል ገበታ መሠረት የቀረበ ሲሆን የፊደሎቹ ብዛት ሃያ ስምንት ናቸው፡፡ ይህም ከነባሩ የፊደል ገበታ አምስቱ ፊደላት ማለትም (ሐ፣ ሠ፣ ኅ፣ ዐ፣ ፀ) የተባሉትን ከጨዋታ ውጪ አድርጎ መሆኑ ነው፡፡
የቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከሉ ሆሄያቱን በመቀነስ ብቻ አልቆመም፡፡ “አንድ ፊደል መወከል ያለበት አንድን ድምፅ ነው፡፡” በሚል የሥነ ልሳን መርኅ ሰበብ የፊደል ማሻሻያ በማድረግ “ሀ” በራብዕ ድምፅ “ሃ” እየተባለ መጠራቱ ቀርቶ በግእዙ ድምፅ “ኸ” እየተባለ እንዲጠራ፤ ለምሳሌ - በቀድሞው አባባል (አጻጻፍ) “ይኸው” ተብሎ በሚጻፈው ምትክ “ይሀው” ተብሎ እንዲጻፍና “ሀ” በ “ኸ” ድምፅ እየተተካ እንዲነበብ፡፡
በተመሳሳይም ሁኔታ “አ” በራብዕ “ኣ” እየተባለ መጠራቱ ቀርቶ በ “ኧ” ድምፅ እንዲጠራና የ “ኧ”ን ቦታ እየተካ እንዲነበብ፤ (ለምሳሌ፡-“ኧረ!” በሚለው ምትክ “አረ!” ተብሎ እንዲጻፍና “አ” በ “ኧ” ድምጽ እንዲጠራ ወይም እንዲነበብ) ተደርጓል፡፡…” በማለት በመዝገበ ቃላቱ መግቢያ ላይ ዐውጇል፡፡ በዚህም መሠረት ፡- ፀሐይ ለማለት ፀሐይ መባሉም ቀረና “ፀኸይ” ሆነ፡፡ ሀገር ለማለት ኸገር፤ ሀብት ለማለት ኸብት፣ እያልን ልንጽፍ ወይም ልንናገር ነው፡፡ ታድያ ይኸ ለፊደሎቻችን ዕድገት ነው ወይስ ውድቀት?
ሁለተኛው በምሳሌነት የምጠቅሰው ከዛሬ አራት ዓመት በፊት ማለትም በ2001 ዓ.ም “ብቸኛው አፍሪካዊ ፊደል (The Sole African Alphabet)” በሚል ርዕስ ዶ/ር ፍቅሬ ዮሴፍ “ተሻሽሎ የቀረበ አዲስ የኢትዮጵያ ሥርዓተ - ፊደል ገበታና የንባብ መለማመጃ” መጽሐፍ አዘጋጅተው ያሠራጩት ነው፡፡ በዶ/ር ፍቅሬ ዮሴፍ የጥናት ውጤት መሠረት፤ ነባሩ የፊደል ገበታ በቁጥር መብዛት ብቻ ሳይሆን በቅርጽም ጭምር ሙሉ ለሙሉ ተለውጠው እናገኛለን፡፡ ከግእዝ (የመጀመሪያ) ፊደላት በስተቀር ማለት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊው ፊደል እንዲሻሻል ባቀረቡት አዲስ የፊደል ገበታ መሠረት በመጽሐፋቸው ገጽ 68 ያሠፈሩትን ተመልከቱት፡-
“የኢትዮጵያ ስርአተ ፊደሉ ገበታ” “የኢትዮጵያውያኑ ህብረ ብሔራዊ ሩሕየ” ይላል፡፡ መቼም ቃላቱ የተለመዱ በመሆናቸው እንደምንም ተመራምራችሁ በግምትም ቢሆን አንብባችሁት ከሆነ ትደነቃላችሁ፡፡ ጐበዝ በዚህ ዓይነትማ እስከ አሁን ተምሬአለሁ ያለው ሁሉ እንደገና ፊደል ቆጠራ መግባቱ እኮ ነው፡፡ ታድያ! እንዲህ ዓይነቱ በፊደል ላይ የሚካሄደው ዘመቻ ለዕድገት ነው? ወይስ ለውድቀት? ያሰኛል፡፡
የሚገርመው ይህንን ያህል ጥናት አድርገው የደከሙበትን የፊደል ገበታ ማሻሻል ሥራ እሳቸው ራሳቸው አልተጠቀሙበትም፡፡ በመጽሐፋቸው የተላለፈው መልእክት የተተየበባቸው ፊደላት በሙሉ ማለት ይቻላል፣ በነባሩ የፊደል ገበታ መሠረት ነው፡፡ መቀነስ አለባቸው ያሏቸውን ፊደሎች ሳይቀር እንደ አገባባቸው ተጠቅመውባቸዋል፡፡ ከመጽሐፉ ሽፋን ጀምሮ ብንመለከት ስርኣተ - ፊደል ብለው አላበላሹትም፤ በአግባቡ “ሥርዓተ - ፊደል” በማለት ጽፈውታል፡፡ ወደ ውስጥ ገፆቹም ዘልቀን ስናይ ሦስቱ “ሀ” ዎች (ሀ፣ ሐ፣ ኅ) ፣ ሁለቱ “ሰ”ዎች (ሰ፣ሠ)፣ ሁለቱ “አ”ዎች (አ፣ ዐ) እና ሁለቱ “ፀ”ዎች (ፀ፣ጸ) እንደየአገባባቸው ጥቅም ላይ ውለው እናገኛቸዋለን፡፡ ይህን በማድረጋቸው አደንቃቸዋለሁ፡፡
የ “ብቸኛው አፍሪካዊ ፊደል (The Sole African Alphabet) መጽሐፍ አቅራቢ በኢትዮጵያ ፊደል ላይ ጥልቅ ግንዛቤ እንዳላቸውና ከፍተኛ ጥናት እንዳካሄሔዱም መጽሐፋቸው ይመሠክርላቸዋል፡፡ እንዲያውም በመጽሐፋቸው ገጽ 9 ላይ የውጪ አገር ዜጐች የሆኑ ወዳጆችና የሥራ ጓደኞች እንደነበሯቸውና የኢትዮጵያን ፊደል ሊያስተምሯቸው ሲሞክሩ የፊደሉን ብዛት በማየት ብቻ እየተሳለቁባቸውና ተስፋ በመቁረጥም የማይሞከር መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ታድያ! በቁጭት ተነሣሥተው “Oh la! la! L’ alphabet ethiopien C’ est trop complique” (ኦ!ላ!ላ የኢትዮጵያ ፊደል በጣም ውስብስብ ነው) ያሏቸውን የፈረንሳይ አምባሳደር አባባል ለማክሸፍ ደረጉትን ጥረት እንዲህ ሲሉ ገልጸውታል፡-
“…እኔም ቀድሞውኑ ከፍተኛ ቁጭት ስለበነበረብኝ ከመቅጽበት ዶ/ር ሞሪስ የሚባለውን የፈረንሣይ ዜጋ ጓደኛዬን “ተወራረዳቸውና በ15 ቀናት ውስጥ አሰልጥኜህ አማርኛ እንድታነብ አደርግሃለሁ፣” በማለት በገባሁለት ቃል መሰረት ጓደኛዬ አማርኛን በ15 ቀናት ውስጥ አቀላጥፎ ማንበብ እንደቻለ አስታውሳለሁ፡፡
የአዲስ አበባ ከተማን በተሽከርካሪ በምናቆራርጥበት  ወቅት “ኮካ ኮላ - ሜታ ቢራ - ፊሊፕስ፣ …” የሚሉትን ማስታወቂያዎቸ ጓደኛዬ እያነበበ ችሎታውን ሲያረጋግጥልኝ በማየቴ ምንኛ እረካ ነበር፡፡ …” ብለው አስፍረዋል፡፡ ይህም አባባላቸው “አስተማሪው ካለ የፊደላችን ቁጥር መብዛት ለጥናት አያስቸግርም፡፡” የሚል ዓይነት መልእክት የሚያስተላልፍ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ይህም ብቻ አይደለም፣ በዚሁ ከላይ በተገለጸው መጽሐፋቸው እስከ ገጽ 10 ድረስ የኢትዮጵያ ፊደል ከ3000 ዓመታት የማያንስ ዕድሜ ያለውና በዓለም ላይ በቀደምትነት ከተፈለሰፉት ፊደላት መሐከል መሆኑን በመጥቀስ ያሞካሹታል፡፡ ታድያ! ይህን ያህል ያደነቁትንና ከኢትዮጵያም አልፈው አፍሪካዊ ፊደል ብለው ክብር የሰጡትን ፊደል በማሻሻል ስም እንዴት እንዳልነበረ ለማድረግ ቻሉ? ያሰኛል፡፡ በበኩሌ ከመጽሐፉ እንደተረዳሁት ከመንፈሳዊና ፖለቲካዊ አመላከት በመነጨ ሁኔታ በመነሳት ነባሩ ፊደል እንዲለወጥ ፈልገዋል፡፡ ምክንያቱም፤
1ኛ/ በቄስ ት/ቤቶች ፊደልን ለማስተማር በፊደል ገበታው ላይ ከተቀመጡ 8 ሰሌዳዎች መካከል በተለይ የመደበኛው ሆሄያትና የመልእክተ ዮሐንስ ሰሌዳዎች ስሜታቸውን እንደነኩት ነው፡፡ ይህንንም በመጽሐፋቸው ገፅ 24 ላይ “… በተረፈ የቀሩት 2 ሰሌዳዎች ገበታውን ከማጣበብ በስተቀር ለኢትዮጵያዊነት መገለጫ ምንም ዓይነት አስተዋጽኦ የላቸውም…” በማለት መግለጻቸው
2ኛ/ ፊደሉ ሙሉ ለሙሉ መለወጥ እንዳለበት ምክንያታቸውን ሲያቀርቡ “… በአሁኑ ወቅት የአማርኛ ቋንቋ ከግእዝኛ እየራቀና ከፍተኛ ዕድገትም እያሳየ በመሔዱ፣ እንዲሁም ደግሞ በአገራችን በርካታ የብሔር ብሄረሰቦች ቋንቋዎች የሚገኙ በመኾኑ፣ ፊደሉ አሁን በሚገኝበት ደረጃ አዲስ የተከሰቱትን ሁኔታዎች አሟልቶ፣ የወቅቱን አማርኛና ብሔረሰቦችን ቋንቋዎች አጥጋቢ በሆነ መልክ ለመጻፍ የሚያስችል ሆኖ አይታይም፡፡ …” (ገጽ 19) ብለው የገለጹትን በማንበቤ ነው፡፡
 ዶ/ር ፍቅሬ ለፊደሉ ካላቸው ከበሬታ የተነሳ ከኢትዮጵያ አሳልፈው ለአፍሪካ እንዲሂበን ያልተመኙትን ያህል በማሻሻል ሰበብ ጭራሽ ሁሉም እንዲለወጡ ያደረጉት ሙከራ ትክክል አይደለም፡፡
 የኢትዮጵያ ፊደል ያልነው ግዕዝ ወይም ተረካቢው አማርኛ ለአንድ ብሔረሰብ መገልገያ እንዲሆን የተፈለሰፈ አይደለም፡፡ ምናልባትም የግዕዝ ነው፡፡  ያም የራሱ የኾነ ምክንያት ስለነበረው ዛሬ ላይ ሆነን የምናነሳው ሊሆን የሚችል አይመስለኝም፡፡ ስለሆነም ዶ/ር ፍቅሬ ያተኮሩበት አማርኛ ቋንቋ ዕድገት የፊደል ገበታውን ሙሉ በሙሉ ቀርቶ አንዷን ቅንጣት ሆሄም የሚያስቀይር አይደለም፡፡ በጥቅሉ ሲታይ ሁሉም “የፊደል መሻሻል ወይም መለወጥ” ጥያቄ ሐሳብ አቅራቢዎች አማርኛ በሚለው ላይ ለምን ትኩረት እንዳደረጉ ከሚሰነዝሯቸው ምክንያቶች መረዳት ይቻላል፡፡
ለመኾኑ! አማርኛ የራሱ የሆነ ብቸኛ የፊደል ገበታ አለውን? “የይሻሻል ወይም የይለወጥ” ሐሳብ መቅረብ የሚገባውም ይህ ጥያቄ መልስ ሲያገኝ ብቻ ይመስለኛል፡፡ እናም በሚቀጥለው ሳምንት ይህን የተመለከተ ፅሁፌን ለማቅረብ እሞክራለሁ፡፡   

Published in ጥበብ

በቢኒያም ሃብታሙ የተፃፉ ወጐችን ያካተተው “የሰራተኛዋ ሜሞ እና ሌሎችም” የተሰኘ መፅሀፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ውሏል፡፡ መፅሀፉ ናሆምና ገበያነሽ የተባሉ ወንደላጤና የቤት ሰራተኛ የተፃፃፉትን አዝናኝ መልእክቶችና ማስታወሻዎች የያዘ ነው፡፡ በ144 ገፆች የተሰናዳው መፅሀፉ፤ ለአገር ውስጥ በ46 ብር፣ ለውጭ በ10 ዶላር ለሽያጭ ቀርቧል፡፡ፀሐፊው በቅርቡ “ነብስ ወለድ ወጎች” በሚል ኢ-ልብወለድና መንፈስ አነቃቂ መጣጥፎችን ለንባብ እንደሚያበቃ ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

Page 4 of 13