Administrator

Administrator

የስነተዋልዶ ጤና ምንነት በአለም አቀፍ ደረጃ ተመሳሳይ ቢሆንም ምክንያቶቹ ግን በታዳጊ አገሮች በአብዛኛው የተለዩ ናቸው፡፡ በታዳጊ አገሮች የሚገኙ እናቶች በ 5/ማይል እርቀት የጤና ጣቢያ ካገኙ ደስተኞች ናቸው፡፡ በታዳጊ አገሮች የሚገኙ እናቶች ጤና ጣብያው ምንግዜም በስራ ላይ ሆኖ ከቆያቸውና ለታካሚዎች በቂ ምላሽ የሚሰጡ ሙያተኞች እንዲሁም የተሟላ አቅርቦት በጤና ተቋሙ ካለ ደስተኞች ናቸው፡፡ ብዙውን ጊዜ ከላይ የተጠቀሱት ሁነቶች ተሟልተው የሚገኙ ባለመሆኑ የስነተዋልዶ ጤና አገልግሎት የተጉዋደለ ይሆናል፡፡ በታዳጊ አገሮች የተለያዩ መሰረተ ልማቶች...ለምሳሌ...እንደ መንገድ የጤና ተቋም በቅርበት አለመኖር የትራንስፖርት ችግር የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ጉዳዮች የመሳሰሉት ካልተሙዋሉ እናቶች ወደ ጤና ተቋም በጊዜው ሄደው እርዳታ እንዳያገኙ ያደርጋቸ ዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የስነተዋልዶ ጤና በሴትና በወንድ በባልና ሚስት መካከል ባለው መቀራረብና ለውይይት መገባበዝም ሁኔታው እንደማሻሻል ሙያተኞች ይመሰክራሉ፡፡ ቀጣዩን የተሳታፊ መልእክት ታነቡ ዘንድ እንጋብዛለን፡፡

.....እህ የምትኖረው በደብረማርቆስ ከተማ ሲሆን በህመም ምክንያት ባልተቤቷ ወደ እኔ ማለትም ወደአዲስ አበባ ይዞአት መጣ፡፡ ሁኔታዋን ከተመለከትኩ በሁዋላ ለባልተቤቷ ጥያቄዬን ሰነዘርኩ፡፡ ጥ: ባልተቤትህ ምንዋን ነወ ያመማት? መ: እኔ እንጃ... ጥ: እንዴት እኔ እንጃ? ሚስትህ ምንዋን እንደሚያማት አታውቅም እንዴ? መ: አረ እኔ አላውቅም... ጥ: አልጠየቅሀትም? መ: እኔም አልጠየቅሁዋት...ብጠይቃትም አትነግረኝ... በባልተቤቷ አመላለስ በጣም ተበሳጨሁና...ፊን ወደእህ መለስኩ፡፡ ጥያቄየን ገና ሳልጀምር ...ና ተነስ አብዬ...አለችኝ እና ወደጉዋሮ ተያይዘን ሄድን፡፡ ጥ: ፈልገሽኝ ነው አልኩዋት... መ: እናስ...እንዴ...እሱ ፊት ምን ልትጠይቀኝ ነው ብዬ እኮ ነው? ጥ: እንዴ እኔ ምን እጠይቅሻለሁ...የመጣሽው ታምመሽም አይደል እንዴ? ምንሽን ነው የታመምሽው ነው የምልሽ? መ: አ...አ...ይ...ሕመሙንም ቢሆን ለሚስትህ ነግሬያት የለ...እሱዋ ትንገርህ...ዪ...እኔስ ምኑንም አላውቀውም... አለችኝ፡፡ እህን ከባለቤቴ ባገኘሁት መረጃ መሰረት ወደማህጸን ሐኪም ወሰድኩዋት፡፡

እዚህ ላይ ለመናገር የምፈልገው በተለይም በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች በግልጽነት መነጋገር ስለማይችሉ ሕመማቸው ስር ከሰደደ በሁዋላ ወደሕክምና ይሄዳሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ካለውጤት ብዙዎች ይጎዳሉ፡፡ ተሳታፊ የስነተዋልዶ ጤና በታዳጊ አገሮች የሚለው ርእስ ሊያሳይ የፈለገው በመንግስት ወይንም ሌሎች በሚመለከታቸው አካላት ሊሟሉ የሚገባቸውን ነገሮች ሳይሆን ከዚያ ውጪ ህብረተሰቡ በልማድ የሚፈጽማቸውን ነገሮች ነው፡፡ ለዚህ ማብራሪያ የሚሰጡን ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህርና የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ እንደ ዶ/ር ዳዊት ማብራሪያ በታዳጊ አገሮች የሚገለጹ ችግሮች በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ የተለያዩ ሲሆኑ ከነዚህም መካከል ትምህርት ማጣትና ድህነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ አንዲት ሴት ትምህርትን የተቋደሰች ከሆነች በብዙ መልኩ በጤናዋ ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉ ነገሮችን አስቀድማ መከላከል ትችላለች፡፡

ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል፣ ጥንቃቄ የጎደለው ጽንስ ማቋረጥን ማስወገድ፣ ተላላፊ ኤችአይቪ የሆኑትን ሕመሞች ለመከላል የሚያስችሉ ነገሮችን አስቀድሞ ለማወቅ፣ በኢኮኖሚው ረገድ ጥገኝነትን ለማስወገድ እንዲረዳ አቅም የፈቀደውን ስራ መስራት፣ የግል ንጽህናን መጠበቅ ...ወዘተ ከላይ የተጠቀሱትንና ሌሎችንም ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ከስነተዋልዶ ጤና አኩዋያም ሆነ ለማንኛውም የአኑዋዋር ዘዴ ለማስተካከል እንዲቻል ትምህርት ወሳኝነት አለው፡፡ ድህነት ከስነተዋልዶ ጤና አጠባበቅ አንጻር ጎጂ የሚሆንባቸው መንገዶች የሚኖሩ ሲሆን በተለይም አስቀድሞውኑ ሕመሙ እንዳይከሰት ለማድረግ እና ከተከሰተም በሁዋላ በፍጥነት ወደሕክምና ተቋም ለመሄድ እንቅፋት የሚሆንበት አጋጣሚ ይስተዋላል፡፡ በኢ ኮኖሚው በዝቅተኛ ደረጃ የሚኖሩ ሰዎች እራቅ ወዳለ አካባቢ ለመሄድ ለትራንስፖርት የሚከፍሉት ስለማይኖራቸው የሚከሰተውን ችግር መቀበልን ይመርጣሉ፡፡

ይህ ደግሞ በቀጣዩ የህይወት አቅጣጫቸው ላይ አንድ እክል እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ እንደ ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ የስነተዋልዶ ጤናን ከአገር ወደህብረተሰብ እንዲሁም ወደቤተሰብ ዘልቆ ገብቶ ሲታይ ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ነገሮች ጫና የሚያሳድ ሩበት ሁኔታ ይታያል፡፡ የስነተዋልዶ ጤና ጉዳይ የሴቶች ብቻ ሳይሆን የወንዶችም ጉዳይ ነው፡፡ በእርግጥ በአብዛኛው ሲጎዱ የሚታዩት ሴቶች ቢሆኑም ወንዶቹም የሚያጋጥማ ቸው ችግር እንደሚኖር እሙን ሲሆን በተለይም በሴቶች ላይ የሚደርሰውን ጉዳት ለመፍታት የወንዶች ተሳታፊን በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ በሚፈጠሩ የጤና እክሎች ላይ በግልጽ መወያየት የአንድ ባልና ሚስት ተግባር መሆን አለበት፡፡ ሴቶችና ወንዶች ለሚያስፈልጉዋቸው ማናቸውም የኑሮ ሁኔታዎች በእኩል መወሰን መቻል አለባቸው፡፡ ሴቶች ከባሎቻቸው ጋር በተለይም ከስነተዋልዶ ጤና ጋር በተያያዘ መወሰን የሚገባቸው እና በቀጥታ ከሕይወታቸው ጋር ተያያዥ የሆኑ ነገሮች ያሉ ሲሆን ከነዚህም መካከል የሚወለዱ ልጆችን ቁጥር እና በምን ያህል የጊዜ ልዩነት መውለድ እንዳለባቸው አስቀድሞ መወሰን ይገኝበታል፡፡

አንዲት ሴት ልጅ የምትወል ድበትን ጊዜና ሊኖራት የሚገባውን የልጅ ቁጥር በወንዱ የገቢ አቅም ላይ ተመርኩዛ ብቻ ሳይሆን ከእራስዋም ጤና አንጻር ልትመለከተው ይገባታል፡፡ ይኼውም በላይ በላይና ብዙ ልጅ በመውለድ እየዋለ እያደረ የሚከሰተውን የስነተዋልዶ ጤና ችግር አስቀድማ ልትከላከል ትችላለች፡፡ የቤት ውስጥ ጥቃት ሌላው ለስነተዋልዶ ጤና ችግር የሚዳርግ ድርጊት ነው፡፡ የተለያዩ ጥናቶች እንደሚያስረዱት 50 ኀ ሴቶች የቤት ውስጥ ጥቃት ሰለባ ናቸው፡፡ የቤት ውስጥ ጥቃት ሲባል አካላዊ፣ መንፈሳዊ ፣ኢኮኖሚያው ተብሎ ሊከፈል የሚችል ሲሆን አካላዊ ጥቃት ከሚባሉት ውስጥ አስገድዶ መድፈር አንዱ ነው፡፡ ይህ አጋጣሚ በሴቶች ላይ የስነአእምሮ እና የአካል ችግር ያስከትላል፡፡ በዚህ መንገድ የተጎዱ ሴቶች ባጠቃላይ እራሳቸውን ማግለልና ዝቅ ማድረግ ይታይባቸዋል፡፡ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች የሚባሉት እንደ ጠለፋ ግርዛት እና በቤት ውስጥ ልጅን ማዋለድ የመሳሰሉት ሌሎች የስነ ተዋልዶ ጤናን የሚፈታተኑ ድርጊቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ድርጊቶች በቤት ውስጥ ሚፈጸሙ ሲሆኑ በቤት ውስጥ ያለው አስተሳሰብ ሲቀየር ግን ችግሩም ሊቃለል እንደሚችል ይታመናል፡፡ ውፍረት ሴቶችን ለስነተዋልዶ ጤና ችግር ከሚያጋልጡ መካከል ናቸው፡፡ አመጋገብን ከመጠን በታችም ሆነ ከመጠን በላይ ማድረግ ጎጂ መሆኑ የተመሰከረለት ነው፡፡ ስለዚህ አካልን በተገቢው መንገድ እንቅስቃሴ በማድረግ መጠበቅ ጠቃሚ ነው፡፡

የግል ጽዳትን መጠበቅ የስነተዋልዶ ጤናን ከመጠበቅ አኩዋያ በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ የመራቢያ አካልን እና አካባቢውን በተገቢው መንገድ አለማጽዳትም ሆነ ከተገቢው በላይ ማጽዳት ጎጂ መሆኑን አስቀድሞ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ በመራቢያ አካል አካባቢ በተፈጥሮ የሚገኙ ባክሪያዎች ኢንፌክሽንን የሚከላከሉ ስለሆነ በኬሚካሎችና በመሳ ሰሉት በመጠቀም አለአግባብ ማስወገድ ለችግር ያጋልጣል፡፡ ዶ/ር ዳዊት በስተመጨረሻ እንደሚሉት የስነተዋልዶ ጤናን ሁኔታ ሰፋ አድርጎ ለመመልከት ቢሞከር በአገራችን ብዙ የተሸሻሉ ነገሮች አሉ፡፡ የእርግዝና ክትትል ማድረግ፣ በጤና ተቋም እና በህክምና ሙያተኛ እርዳታ መውለድ ፣ ከወለዱም በሁዋላ ክትትል ማድረግ፣ የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ተጠቃሚ መሆን...ወዘተ ... ከላይ በተጠቀሱትና የጤና ኤክስንሽን ሰራተኞች በየአካባቢው መኖር እንዲሁም የጤና ጣቢያዎች መገንባት በመሳሰሉት ምክንያቶች መሻሻሎች የሚታዩ ቢሆንም ነገር ግን ገና ብዙ መሰራት ያለበቸው ነገሮች እንዳሉ ሁኔታዎች ያሳያሉ ብለዋል ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ፡፡

ባለፈው ረቡዕ በደሴቲቷ አገር በኢንዲያን ኦሽን ትልቅ ዓለም አቀፍ ኤግዚቢሽን ተዘጋጅቶ ነበር - ውድ ውድ የከበሩ ድንጋዮችና የአልማዝ ጌጣጌጦች የቀረቡበት፡፡ ለዚህም ከቻይና፣ ከሆንግኮንግ፣ ከታይላንድ፣ ከህንድ እና ከአውሮፓ የመጡ ገዢዎች በኤግዚቢሽኑ ላይ ተገኝተው ነበር፡፡ በዚህ ግርግር መሃል ነው ፖሊስ አንዱን የቻይና ቱሪስት በስርቆት ጠርጥሮት በቁጥጥር ሥር ያዋለው፡፡ ቱሪስቱ 171 ሺ ብር ገደማ የሚያወጣ አልማዝ (diamond) ውጠሃል በሚል ነበር የተጠረጠረው፡፡ “ዓላማው መስረቅ ነበር” ሲል ለሮይተርስ የተናገረው የስሪላንካ ፖሊስ ቃል አቀባይ አጂት ሮሃና፤ በኤክስሬ መመርመርያው በጉሮሮው ውስጥ የነበረውን አልማዝ ማየት እንደቻለ ገልጿል፡፡ የ32 ዓመቱ ቻይናዊ ቾው ቼንግ አልማዙን በኤግዚቢሽኑ ላይ እየተመለከተ ሳለ እንደዋጠው ታምኗል፡፡

ኤግዚቢሽኑ የተካሄደበት አዳራሽ ባለቤት ክሪስቶፈር ዊጅኩን በበኩሉ፤ ቻይናዊው ቱሪስት ኦሪጂናሌውን አልማዝ በሲንቴቲክ አልማዝ ለመለወጥ እንደሞከረ ለሮይተርስ ተናግሯል፡፡ “እኔ እንዳስተዋልኩት ገባውና ከመቅጽበት አልማዙን ዋጠው” ብሏል ዊጅኩን ለሮይተርስ፡፡ የኢንዲያን ኦሽን ደሴት በአልማዞችና በጌጣጌጥ ኢንዱስትሪዋ የታወቀች ስትሆን በ2011 እ.ኤ.አ የኤክስፖርት ገቢዋ 532 ሚ .ዶላር እንደነበር ሮይተርስ ጠቁሟል፡፡ ይሄ የፈረደበት ቻይናዊ እንግዲህ የዋጠውን አልማዝ እስኪተፋ ድረስ መከራውን መብላቱ አይቀርም፡፡ የሌብነት መዘዝ ይሄው አይደለ!!

ከ1ሺ ኪ.ግ በላይ ይመዝናል በርገሩን ለመስራት 4 ሰዓት ፈጅቷል በአሜሪካ የሚኒሶታ ግዛት ውስጥ የሚገኝ አንድ ካዚኖ ቤት (ቁማር ማጫወቻ) እጅግ በጣም ትልቁንና ከፍተኛ ክብደት ያለውን ቺዝበርገር በመስራት በጊነስ የድንቃድንቅ መዝገብ ውስጥ ስሙን አሰፈረ፡፡ ከቤከን የተሰራው ቺዝበርገር 10 ጫማ ስፋት ሲኖረው ከ1ሺ ኪ.ግ በላይ ክብደት እንዳለው ታውቋል፡፡ (ከ10 ኩንታል በላይ ማለት ነው) “ዛሬ ያየሁት አስደናቂ የቡድን ሥራ ያስገኘውን የዓለም ክብረወሰን የሰበረ በርገር ሲሆን ጣዕሙም በጣም አሪፍ ነው” ሲሉ የጊነስ ሪከርድስ ተወካይ ፊሊፕ ሮበርትሰን ለአሶሼትድ ፕሬስ ተናግረዋል፡፡ በርገሩ በአጠቃላይ ዳቦውንና ማሰማመሪያዎቹን ጨምሮ 2ሺ 14 ፓውንድ ክብደት እንዳለው የዘገበው ዱሉዝ ኒውስ ትሪቡን፣ ቀድሞ የተመዘገበው የበርገር ክብደት 881 ፓውንድ እንደ ነበር ጠቅሷል፡፡

በብላክ ቢር ካዚኖ ሪዞርት የሚሰሩ ሼፎች ግዙፉን ቺዝበርገር ለማሰናዳት አራት ሰዓታት እንደፈጀባቸው ታውቋል፡፡ በርገሩ ከ33 ኪ.ግ ቤከን፣ 23 ኪ.ግ ሰላጣ፣ 23 ኪ.ግ በስላች የተቆረጠ ሽንኩርት፣ 13 ኪ.ግ ኩከምበር እና 13 ኪ.ግ ቺዝ የተሰራ ሲሆን የበርገሩን ዳቦ ለመጋገር ብቻ ሰባት ሰዓት እንደወሰደ ታውቋል፡፡ አሶሼትድ ፕሬስ በስፍራው ተገኝቶ እንደተመለከተው፤ በርገሩን ለማንሳት ክሬን አስፈልጐአቸው ነበር፡፡ በርገሩ የተሰራውም በውጭ ምድጃ (outdoor oven) እንደሆነ ታውቋል፡፡

ቻይናዊው ሁ ሴንግ አንዲት የሚወዳት ፍቅረኛ አለችው፡ እናም ፍቅሩን ለመግለፅ ብቻ ሳይሆን Surprise ሊያደርጋት (ሊያስደምማት) ያስብና ትንሽ ይቆዝማል - ሃሳብ እያወጣ እያወረደ፡ ብዙዎቹ የመጡለትን ሃሳቦች አናንቆ ጣላቸው - ፍቅረኛውን ለማስደመም ብቃት እንደሌላቸው በመቁጠር፡፡ በአዕምሮው የሃሳብ ጅምናስቲክ ሲሰራ ቆይቶ ግን አንዲት ሃሳብ አንጀቱ ላይ ጠብ አለችለት፡፡ ሃሳቡን ለመተግበርም ሲበዛ ተጣደፈ፡፡ ፍቅረኛውን ሊያስደምምበት በወጠነው ሃሳብ እሱ ራሱ ቀድሞ ተደመመና ቁጭ አለ፡፡ ከድማሜው ሲወጣ ሃሳቡን ወደ ተግባር ለውጦ የማሰቡን በረከት ሊቋደስ ቋመጠ፡፡ በቻይና የቾንኪዊንግ ግዛት ነዋሪ የሆነው ሴንግ፤ ፍቅረኛውን በምን ሰርፕራይዝ እንደሚያደርጋት ለማንም አልተናገረም፡፡ ምስጢር ነው - እሱና እሱ ብቻ የሚያውቁት፡፡ ፍቅረኛውም የምታውቀው ሰርፕራይዝ ከተደረገች በኋላ ይሆናል፡፡ ሁሴንግ በቀጥታ የሄደው እንደ ዲኤች ኤል ያለ ፈጣን መልዕክት አድራሽ ተቋም ጋ ነበር፡፡ እዚያም እንደደረሰ ስለሚያደርሱት እቃ ወይም መልዕክት ምንነት ሳይናገር በካርቶን የታሸገ ስጦታ እፍቅረኛው ቢሮ እንዲወስዱለት ብቻ ተነጋገረና ተስማማ፡፡ የአገልግሎት ክፍያውንም ሳያቅማማ ፈፀመ፡፡

ለፍቅረኛው ሊልክላት ያሰበው ስጦታ አበባ አልነበረም፡፡ ጫማ፣ ወርቅ፣ አልማዝ ወይም ወድ አልባሳትም አይደለም፡፡ ለፍቅረኛው ለመላክ ያሰበው ራሱን ነው፡፡ በዚህ ነው የሚወዳትን ፍቅረኛውን ማዝናናትና ማስደመም ያማረው፡፡ እናም መልዕክቱን የሚያደርሱት የድርጅቱ ሠራተኞች ወደ ቤቱ ከመምጣታቸው አስቀድሞ ራሱን እንደ ስጦታ እቃ በካርቶን ውስጥ አሳሽጐ ጠበቃቸው፡፡ መልዕክት አድራሾቹ “አገር አማን” ብለው በተለመደ ፈጣን የአገልግሎት አሰጣጣቸው፣ በአደራ የተሰጣቸውን እቃ ወደተባሉበት ሥፍራ ለማድረስ ከነፉ - በዘመናዊ ፈጣን አውቶሞቢላቸው፡፡ ሆኖም መሃል ላይ የቴክኒክ ችግር ገጠማቸው፡፡ የአድራሻ ስህተት ተፈጠረ፡፡ ይሄ ስህተት ደግሞ ከሁሉም በላይ ራሱን በካርቶን ውስጥ ላሳሸገው ምስኪኑ ሴንግ ከባድ ፈተና ነበር - የህይወት መስዋዕትነት እስከማስከፈል የሚደርስ፡፡ ሴንግ በካርቶኑ ውስጥ ታሽጐ የሚቆየው ቢበዛ ለ30 ደቂቃ ያህል መስሎት ነበር፡፡

በተፈጠረው የአድራሻ ስህተት ግን ጊዜው ወደ 3 ሰዓታት ተራዘመበት፡፡ ጉድ ፈላ - ሴንግ! ካርቶኑ ውስጥ በአየር እጦት ተሰቃየ፡፡ የማታ ማታ ግን እሽጉ ካርቶን እፍቅረኛው ቢሮ መድረሱ አልቀረም፡፡ ፍቅረኛው ካርቶኑን ለመክፈት ስትጣደፍ፣ የሥራ ባልደረባዋ ደግሞ ሰርፕራይዙን ቀርፃ ለታሪክ ለማስቀመጥ ካሜራዋን ደግና እየተጠባበቀች ነበር፡፡ ካርቶኑ ሲከፈት ግን ሰርፕራይዝ የሚያደርግ ሳይሆን በድንጋጤ ክው የሚያደርግ ነገር ገጠማቸው፡፡ ሁ ሴንግ ካርቶኑ ውስጥ ሩሁን ስቷል፡፡ በአየር እጥረት ታፍኖ፡፡ በስጦታ ሰርፕራይዝ ለመደረግ ቋምጣ የነበረችው ፍቅረኛው፤ ህይወቱን ለማትረፍ ተጣድፋ የድንገተኛ ህክምና ባለሙያዎችን አስጠራች፡፡ የህክምና እርዳታ ካገኘ በኋላ ሴንግ ነፍሱ ተመለሰችለት፡፡

“ጉዞው ያንን ያህል ረዥም ጊዜ ይወስዳል ብዬ አላሰብኩም ነበር” ያለው የዋሁ አፍቃሪ፤ “በእሽጉ ካርቶን ውስጥ ሆኜ አየር የማገኝበት ቀዳዳ ለማበጀት ሞክሬ ነበር፤ ሆኖም ካርቶኑ በጣም ወፍራም ስለሆነ አልቻልኩም፤ ጩኸት እንዳላሰማ የነገሩን ድንገቴነት (Surprise) ማበላሸት አልፈለግሁም” ብሏል፡፡ የመልዕክት አድራሹ ድርጅት ቃል አቀባይ በበኩሉ፤ “ገና ከመጀመርያው ምን እንዳሰበ ቢነግረን ኖሮ እሽጉን አንወስድለትም ነበር፤ እንስሳትን እንኳን ለማጓጓዝ ስንቀበል አየር ማግኘት እንዲችሉ በተለየ መያዣ ውስጥ ነው የምናደርጋቸው” ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል - ለኦሬንጅ ኒውስ፡፡ አይገርምም! ፍቅረኛውን ለማስደመም ሲል ህይወቱን ሊያጣ ለጥቂት እኮ ነው የተረፈው፡፡ ካልጠገቡ አይዘሉ፤ ካልዘለሉ አይሰበሩ የሚለው ሀገራዊ አባባል ለቻይናዊው ሁ ሴንግ አይሰራ ይሆን?!

በእባብ የተነደፈ የኔፓል ተወላጅ እባቡን መልሶ በመንከስ ብድሩን እንደመለስ ሰሞኑን ተዘግቧል፡፡ ሮይተርስ የኔፓል ዕለታዊ ጋዜጣ አናፑርና ፖስትን ጠቅሶ እንደዘገበው፤ ሞሃመድ ሳልሞ ሚያ የተባለውን ግለሰብ ኮብራ እባብ የነደፈው በሩዝ ማሳ ውስጥ ነበር፡፡ ሞሃመድ ግን ዝም አላለም፡፡ የገባበት ገብቶ በመያዝ ነክሶ ገድሎታል - እባቡን፡፡ “በዱላ ልገድለው እችል ነበር፤ ነገር ግን በጥርሴ ነክሼ ገደልኩት፤ ምክንያቱም ተናድጄ ነበር” ብሏል ከአገሪቱ መዲና ከካትማንዱ ደቡብ ምስራቅ 200ኪ.ሜ ላይ በምትገኘው መንደር የሚኖረው የ55 ዓመቱ ሞሃመድ፡፡ በኔፓል “ጐማን” እየተባለ የሚጠራው ይሄ የእባብ ዝርያ “ኮመን ኮብራ” በሚል ስያሜም ይታወቃል ብሏል አናፑርና ፖስት፡፡ በእባቡ የተነደፈው ሞሃመድ ሳልሞ ሚያ፤ በመንደሩ የጤና ጣቢያ ህክምና እየተደረገለት ሲሆን ለህይወቱ እንደማያሰጋው ተገልጿል፡፡

እባቡ በኔፓል በመጥፋት ላይ ካሉ የማያጠቡ እንስሳት ዝርያ ዝርዝር ውስጥ የተካተተ ባለመሆኑ እባቡን ነክሶ የገደለው ግለሰብ ከክስ እንደዳነ የአካባቢው ፖሊስ ባለስልጣን አስታውቋል፡፡ እንዲያ ባይሆን ኖሮማ እባቡን ነክሶ በመግደሉ ፍ/ቤት ይቆማት ነበር ተብሏል፡፡ ይታያችሁ … ሞሃመድ እባቡን ነክሶ የገደለው ለአደን አይደለም - ስለነደፈው እንጂ፡፡ ቢሆንም በመጥፋት ላይ ያሉ እንስሳትን መግደል በኔፖል ያስጠይቃል ብሏል - ሮይተርስ፡፡

በሰማይ ላይ የሚበሩ ክንፍ ያላቸው አውቶሞቢሎች እውን የማድረግ ህልም ከዛሬ 82 ዓመት ገደማ ጀምሮ የተወጠነ የቴክኖሎጂ ትልም ሲሆን እስካሁን ግን እንደ ሳይንሳዊ ፊክሽን (ልቦለድ) ሲቆጠር የቆየ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ግን በሳይንሳዊ ልቦለድነት የሚጠቅሳቸው ማንም አይኖርም፡፡ ለምን ቢባል? በቅርቡ ለገበያ ሊቀርቡ እንደሆነ እየተነገረ ነዋ! የሚበረው መኪና የመጀመርያ በረራውን ያጠናቀቀ ሲሆን በመጪው አመት Transition በሚል ስያሜ ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡ አውቶሞቢሉ ሁለት መቀመጫዎች፣ አራት ጐማዎችና የሚታጠፉ ክንፎች እንዳሉት ታውቋል፡፡ የክንፎቹ መታጠፍ አውቶሞቢሉ እንደ መኪናም በመሬት ላይ መሽከርከር እንዲችል ያደርገዋል፡፡ ባለፈው አመት Transition በ1ሺ 400 ጫማ ከፍታ ለ8 ደቂቃዎች እንደበረረ የሚታወቅ ሲሆን የንግድ ጀቶች በ35ሺ ጫማ ከፍታ ነው የሚበሩት፡፡

ገና ካሁኑ Transition የተባለውን በምድር ተሽከርካሪ በሰማይ በራሪ መኪና ለመግዛት 100 ሰዎች 10ሺ ዶላር በቅድሚያ ከፍለዋል፡፡ የአውቶሞቢሉ አምራች ኩባንያ Terrafugia inc. በመጪው ሳምንት አዲሱን በራሪ መኪና በኒውዮርክ ለህዝብ እይታ የሚያቀርብ ሲሆን ከዕይታው በኋላ የገዢው ቁጥር እንደሚጨምር ተገምቷል፡፡ ሆኖም ግን Transition በየመንገዱ ላይ እንደልብ የሚታይ አውቶሞቢልም አይደለም፡፡ ለምን ቢሉ? 279ሺ ዶላር ያወጣል ተብሎ ይገመታል - ባለ ክንፋሙ አውቶሞቢል! ይሄን አውቶሞቢል በምድር ላይ እያሽከረከራችሁ ሳለ በትራፊክ ብትጨናነቁ ምንም ማድረግ አትችሉም፡፡

ምክንያቱም ከመሬት ወደ አየር ለመነሳት ማኮብኮብያ ሜዳ ያስፈልገዋል፡፡ የሚበር መኪና በአሜሪካውያን ምናብ ውስጥ ልዩ ቦታ ነበረው፡፡ ከ1930ዎቹ ዓመታት ጀምሮ የፈጠራ ባለሙያዎች ይሄን አውቶሞቢል ለመስራት ሲታትሩ ቆይተዋል፡፡ የአየር መንገድ ኢንዱስትሪ ተንታኝ የሆነው አሜሪካዊው ሮበርት ማን እንደሚለው፤ የሚበሩ አውቶሞቢሎችን እውን ከማድረግ አንፃር እንደ Terrafugia ኩባንያ እጅግ የቀረበ ማንም የለም፡፡ ኩባንያው ለአውቶሞቢሎቹ ልዩ ጐማዎችንና ለተለመዱት መኪኖች ጥቅም ላይ ከሚውሉ መስተዋቶች ቀለል ያሉትን ለመጠቀም ለመንግሥት ጥያቄ አቅርቦ ተፈቅዶለታል፡፡ የአየር መንገድ ኢንዱስትሪ ተንታኙ ሮበርት ማን እንደተናገሩት፤ ከዛሬ አምስት አመት በፊት በፌደራል አቪዬሽን አድሚኒስትሬሽን ውሳኔ ኩባንያው የተለየ ቀላል የስፖርት ኤርክራፍት ስታንዳርድ በመፍጠር እገዛ ተደርጐለታል፡፡ ስታንዳርዱ የኤሮፕላኑን መጠንና ፍጥነት እንዲሁም የፓይለቶች የፈቃድ መስፈርቶችን የሚወስን ነው፡፡ ኩባንያው እንደሚለው፤ የመኪናው ባለቤት የሚሰጠውን ፈተና ማለፍ ያለበት ሲሆን Transition የተባለውን አውቶሞቢል ለማብረር የ20 ሰዓታት በረራ ማጠናቀቅ የግድ ይላል፡፡

አውቶሞቢሉ በመሬት ላይ በሰዓት 70 ማይል የሚፈተለክ ሲሆን በአየር ላይ 115 ማይል ይበራል፡፡ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በአጠቃላይ የአቪዬሽን ገበያው እያሽቆለቆለ መምጣቱን የሚናገሩት ተንታኙ፤ ለዚህም ምክንያቱ ከፍተኛ የነዳጅ ወጪና በአምራቾቹ ላይ የሚያርፈው የወጪ እዳ ነው ይላሉ፡፡ ሌላው ችግር የበረራ ትምህርት የሚወስዱ ሰዎች ጥቂት መሆናቸው ነው፡፡ “ይሄ ለማምረትም ሆነ ለገበያ ለማቅረብ እርካሽ የሚባል ኤርክራፍት አይደለም” የሚሉት ሮበርት ማን፤ “አዲሱ በራሪ መኪና አንዳንድ ለየት ያሉ ነገሮች አሉት፤ እናም ጥቂት ሽያጮች ያገኛል፡፡ ነገር ግን ጥያቄው ምርቱ ትርፋማ ሊሆን ይችላልን? የሚለው ነው፡፡ ተንታኙ ባለሙያ እንደሚሉት ለዚህ ባለክንፍ አውቶሞቢል የበጠ የገበያ ስፍራ የሚሆነው የአሜሪካ ምዕራባዊ ክፍል ነው፡፡ ለምን ቢሉ? በዚያ አካባቢ ሰዎች ረዥም ርቀት ከማሽከርከር ይልቅ መብረርን የሚመርጡ በመሆናቸው ነው፡፡

Terrafugia በበራሪ መኪናዎች ላይ መስራት ከጀመረ ስድስት ዓመት ገደማ ይሆነዋል - ከ2006 ዓ.ም አንስቶ ማለት ነው፡፡ ባለፈው ዓመት በጋ ላይ ኩባንያው ምርቱን በ2011 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) ለማቅረብ የገባውን ቃል ለማዘግየት ተገዶ ነበር - በዲዛይን ተግዳሮቶች እና የመለዋወጫ እቃዎች አቅርቦት ችግር ጋር በተያያዘ ማለት ነው፡፡ በራሪው ተሽከርካሪ በኒውዮርክ ለእይታ ሲቀርብ የደንበኞችንና የኢንቨስተሮችን ዓይን እንደሚስብለት ኩባንያው ተስፋ አድርጓል፡፡ “ራሳችንን ለአውቶሞቲቩ ዓለም እንደ አዋጭ ኩባንያ እያስተዋወቅን ነው” ብለዋል - የኩባንያው ቃል አቀባይ፡፡

ኮሎኔል አወል አብዱራሂም በኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት ላይ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ለማበርከት ባመነጩት ሃሳብ የደደቢት ስፖርት ክለብን በ1989 ዓ.ም መስርተዋል፡፡ ታዳጊ ህፃናትን በማሰልጠን ከ16 ዓመት በፊት የተጀመረው ክለቡ ገና በወጣትነት እድሜው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ጉልህ አስተዋፅኦ ማበርከቱ እንደሚያኮራቸው ኮ/ል አወል አብዱራሂም ይናገራሉ፡፡ በሚቀጥሉት አምስት አመታት ውስጥ የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒየንስ ሊግ ዋንጫን አሸንፎ በዓለም ክለቦች ዋንጫ ላይ አፍሪካን ለመወከል እንዲበቃም ምኞት አላቸው፡፡ ደደቢት በኢትዮጵያ ክለቦች ከፍተኛ ውድድር የሆነውን ፕሪሚዬር ሊግ መሳተፍ ከጀመረ ዘንድሮ ገና በአራተኛው የውድድር ዘመኑ ላይ ቢሆንም፤ በሊጉ የሻምፒዮናነት ፉክክር ከሚጠቀሱት 3 ክለቦች አንዱ ሆኗል፡፡ ለወቅቱ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 9 ተጨዋቾች በማስመረጥም ግንባር ቀደሙ ነው፡፡

የደደቢት የስፖርት ክለብ ስለሚገኝበት ወቅታዊ ሁኔታ፤ በወደፊት አቅጣጫዎቹ እና ተያያዥ ጉዳዮች ዙርያ ከክለቡ መስራችና ፕሬዝዳንት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም ጋር ስፖርት አድማስ ቃለምምልስ አድርጓል፡፡ - የደደቢት ስፖርት ክለብ የተመሰረተበትን 16ኛ ዓመት ከሳምንት በፊት አክብሯል፡፡ ክለቡ በዚህ ጊዜ ያለፈባቸውን ጉልህ ሂደቶች እና ዛሬ የደረሰበትን ደረጃ እንዴት ይመለከቱታል? የደደቢት የስፖርት ክለብ በወቅታዊ የእግር ኳስ እንቅስቃሴው ጥሩ ደረጃ ላይ ነው፡፡ በተለያዩ የስልጠና ፕሮጀክቶች እና ውድድሮች የሚሳተፉ የክለቡ ቡድኖች የሚያበረታታ ውጤት እያሳዩ ናቸው፡፡ የቡድኖቹን ጥንካሬ እና ውጤታማነት በብዙ መልክ መግለፅ ይቻላል፡፡ በፕሪሚዬር ሊግ ተወዳዳሪ የሆነው ዋናው ቡድን የውድድር ዘመኑ ሲጋመስ በደረጃ ሰንጠረዥ አናት ላይ ሆኖ ነው፡፡ ይህ ውጤት ድንገተኛ ክስተት አይደለም፡፡ ክለቡ በፕሪሚዬር ሊግ በተሰለፈባቸው ባለፉት ሶስት የውድድር ዘመናት ለሻምፒዮናነት ከሚፎካከሩ ሶስት ክለቦች አንዱ ነበር፡፡ ዘንድሮም ይህን ብቃት መቀጠሉ የሚያኮራ ነው፡፡ ክለባችን በአደረጃጀቱ በተለይ በተጨዋቾች ስብስቡ አስፈላጊው ጥራት እንዲኖር ያተኩራል፡፡

እንግዲህ ከ16 አመት በፊት ክለቡ ሲመሰረት የተነሳንበት መሰረታዊ አካሄድ ከ10 አመት በታች የሆኑ ህፃናትን አሰባስቦ በማሰልጠን ነበር፡፡ በታዳጊ እና ወጣት ተጨዋቾች ማሰልጠኛ ፕሮጀክቶች ላይ በትኩረት በመስራት ጥራት ያላቸውን ተጨዋቾች ማፍራት አቅደን ነበር የተነሳነው፡፡ አንድ ክለብን በብቁ የተጨዋቾች ስብስብ እና ጥራት ባለው አደረጃጀት ለማቆም ከስር ተነስቶ በረጅም ጊዜ እቅድ መስራቱ አስፈላጊ ነው፡፡ ከ16 አመት በፊት ክለቡን የጀመርንበት የ U-10 ቡድን በሚያገኘው ስልጠና በአገሪቱ ምርጥ ደረጃ ላይ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ስልጠናችንን ወደ U-15 በማሳደግ ቀጠልን፡፡ በ1992 ዓ.ም የደደቢት እግር ኳስ ክለብ በታዳጊ እና ወጣት ቡድኖቹ በአገር አቀፍ ውድድሮች ጥሩ ተፎካካሪ ሊሆን ከመቻሉም በላይ በስብስቡ ጥራት እንደሞዴል ሊታይ የበቃ ነበር፡፡ የደደቢት U-17 ቡድን በነበረው የስብስብ ጥራት እና የተሟላ የብቃት ደረጃ ለአዲስ አበባ ሞዴል ሆኖ ከመታየቱም በላይ የከተማ መስተዳደሩን ፈቃድ አግኝቶ በአገር አቀፍ ውድድር ተሳታፊ ሊሆን የበቃ ብቸኛው የግል ፕሮጀክት ነበር፡፡ እንግዲህ ከክለቡ ምስረታ በኋላ ለሰባት ዓመታት በታዳጊ እና ወጣት ቡድኖች ሰፊ ስራ በማከናወን ቆይተናል፡፡ ከዚያ በኋላ በተመሰረተው ዋና ቡድን 2000 ዓ.ም ላይ ወደ ብሄራዊ ሊግ ውድድር ገባን፡፡ ክለቡን ከመሰረትን ከ12 ዓመት በኋላ ደግሞ ፕሪሚዬር ሊጉን ለመቀላቀል በቅተናል፡፡ ክለቡ የሚያንቀሳቅሳቸው የታዳጊ እና ወጣት ተጨዋቾች ማሰልጠኛ ፕሮጀክቶች ስኬታማ ናቸው?

ደደቢት ብቁ እና ምርጥ ተጨዋቾችን ከተለያዩ ክለቦች በከፍተኛ ገንዘብ አሰባስቦ የተጠናከረ ክለብ የሚባልም ነገር አለ? የተጨዋቾች ግዢ በአንድ ክለብ አወቃቀር የሚያስፈልግ አሰራር እንደሆነ እናውቃለን፡፡ በተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ማንም ክለብ የሚሳተፈው በቡድኑ የተጨዋቾች ስብስብ ያሉ ክፈተቶችን ለመሙላት እና ልምዱን ለማጠናከር ነው፡፡ የደደቢት ስፖርት ክለብ የተጨዋቾች ግዢን እንደ ዋና ፖሊሲው ተንቀሳቅሶ የሚሰራበት አይደለም፡፡ የእግር ኳስ ክለባችንን ለመገንባት የምንከተለው ፖሊሲ ከምስረታችን ጀምሮ በሰራንባቸው የታዳጊ እና ወጣት ተጨዋቾች ማሰልጠኛ ፕሮጀክቶች የማያቋርጥ እድገት ላይ የተመሰረተ መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በደደቢት የስፖርት ክለብ 150 ስፖርተኞችን ይዘናል፡፡ በU-15 ደረጃ በአርባ ምንጭ እና በመቀሌ በሚገኙ ሁለት የፕሮጀክት ማእከሎች 55 ስፖርተኞች በመያዝ እየሰራን ነው፡፡ ለዋናው ቡድን መጋቢ እንደሚሆን የታመነበት እና በU- 17 ደረጃ የምናንቀሳቅሰው ፕሮጀክት 25 ስፖርተኞችን በማቀፍ እየሰራ የሚገኘው በአዲስ አበባ ነው፡፡

ባለፈው አመት በስራ አጋጣሚ ወደ ጋና ሄጄ ባገኘሁት ሃሳብ ደግሞ የተስፋ ቡድንም መስርተናል፡፡ በU-19 ደረጃ የምናሰለጥንበት ይህ የተስፋ ቡድን ለዋናው የቡድን መዋቅር መሰረት መሆኑን በማመን ያስጀመርነው ነው፡፡ ይህን የተስፋ ቡድን በU- 17 ደረጃ ከምንሰራበት የቢ ቡድን ጋር በማቀናጀት የምናንቀሳቅሰው ነው፡፡ በቢ ቡድን ያሉ ተጨዋቾችን በቀጥታ ወደ ዋናው ቡድን በማሳደግ መስራት ውጤታማ አያደርግም፡፡ ስለዚህም በU-19 የምንሰራበትን የተስፋ ቡድኑን ወደ ዋናው ቡድን ለምናሳድጋቸው ተጨዋቾች እንደመሸጋገርያ የምንጠቅምበት ይሆናል፡፡ በዚህ የተስፋ ቡድን ፕሮጀክት በየዓመቱ ያለማቋረጥ ዋናውን ቡድን የምንገነባበትን ሂደት በጥሩ መሰረት ይዘነዋል፡፡

ለክለቡ መጠናከር የሚያግዙ ወጣት ተጨዋቾች ከማፍራት ባሻገር በአገሪቱ ከፍተኛ የሊግ ውድድር ተሳታፊ በሆኑ ክለቦች ለመጫወት የሚበቁ ተጨዋቾችን በዝውውር ገበያው በማቅረብ ገቢ ለማግኘት ተስፋ ያደረግንበት እንቅስቃሴም ነው፡፡ አርባ ምንጭ ላይ በምንሰራው የU- 17 ፕሮጀክት ደግሞ ከሁለት ዓመት በኋላ ለፕሪሚዬር ሊግ የሚመጥኑ ተጨዋቾችን እንደምናወጣበት በእርግጠኝነት እናገራለሁ፡፡ በአጠቃላይ ከእነዚህ የታዳጊ እና ወጣት ተጨዋቾች ፕሮጀክቶች ወደ ሌሎች ክለቦች ያዘዋወርናቸውን ስፖርተኞች ባይኖሩም ዋና ቡድናችንን በእነዚህ ፕሮጀክቶች መገንባቱ በገሃድ የሚታይ ጥቅም ነው፡፡ ዘንድሮ በፕሪሚዬር ሊግ በሚወዳደረው ዋናው ቡድናችን ላለፉት አራት አመታት በማሰልጠን ያፈራናቸውን 7 ተጨዋቾች አስገብተናል፡፡ ደደቢት የስፖርት ክለብ በአደረጃጀቱ የሚያስፈልጉትን መሰረተ ልማቶች አሟልቷል ?ወይንስ ችግሮች አሉ? እንግዲህ ለዋናው ቡድን የስፖርት ክለቡ የተጨዋቾች ካምፕ አለው፡፡ የትጥቅ አቅርቦቱም የተሟላ ነው፡፡ በመሰረተ ልማት ደረጃ ለደደቢት ክለብ ትልቁ ችግር የራሱን የልምምድ ሜዳ አዘጋጅቶ በተማከለ ሁኔታ አለመንቀሳቀሱ ነው፡፡ ደደቢት የራሱ ሜዳ የለውም ማለት ያሳዝናል፡፡ በፋይናንስ ያለው አቅም ደካማ መሆን ያለበትን የሜዳ ችግር ለመቅረፍ ዋና እንቅፋት ሆኖበታል፡፡ በእርግጥ ክለቡ ከአዲስ አበባ መስተዳደር የልምምድ ሜዳውን የሚያቋቁምበት መሬት አግኝቷል፡፡ የከተማዋ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ እና የመስተዳደሩ አመራሮች የሰጡን ትብብር ከፍተኛ ምስጋና የሚገባው ነው፡፡ በደደቢት የእግር ኳስ ክለብ ስር እዚህ አዲስ አበባ ላይ የሚሰሩ አራት ቡድኖች አሉ፡፡ በአርባምንጭ ያለው ፕሮጀክታችን የሜዳ ችግር የለበትም፡፡

የአርባ ምንጭ መስተዳድር የክለባችን ፕሮጀክት በመደገፍ በከተማዋ የሚገኝ ስታድዬም ቅድሚያ ተሰጥቶን ለፕሮጀክታችን እንደሜዳ እንድንገለገልበት በመፍቀዱ በዚያ ችግር የለብንም፡፡ በመቀሌ ፕሮጀክትም ከክልሉ መስተዳድር ተመሳሳይ ድጋፍ እያገኘን ነው፡፡ እዚህ አዲስ አበባ ተቀማጭ የሆኑት አራት ቡድኖች ግን መደበኛውን የስልጠና እና የልምምድ ፕሮግራም በአራት የተለያዩ ቦታዎች ተዘበራርቀው እየተገለገሉ ናቸው፡፡ እነዚህ አራት ቡድኖች ለሚሰሩባቸው ሜዳዎች ኪራይ በምንከፍለው ገንዘብም ብዙ ወጭ እያወጣን ነው፡፡ አሁን ዋናው ቡድን የሚሰራውየመድን ክለብን ሜዳ ተከራይቶ ነው ፡፡ በአንድ ልምምድ እስከ 700 ብር እየከፈለ ነው፡፡ የተስፋ ቡድናችን ደግሞ በፌደራል ፖሊስ ሜዳ ይገለገላል፡፡ የሴቶች ቡድኑ በህንፃ ኮሌጅ ሜዳ እየሰራ ነው፡፡ ሌላው የፕሮጀክት ቡድን ደግሞ የሚጠቀመው የቀበሌ ሜዳ ነው፡፡ በእነዚህ አራት የተለያዩ ሜዳዎች አራቱ ቡድኖች ተዘበራርቀው መስራታቸው በሜዳ ክራይና በትራንስፖርት ወጪ የስፖርት ክለቡ እየተቸገረ ነው፡፡ ከገንዘብ ወጪውም ሌላ ብዙ እድገትን የሚያስተጓጉሉ ችግሮች እየገጠሙን ነው፡፡ ዋናው ቡድን ከሚሰራበት የመድን ሜዳ በቀር በሌሎቹ ሜዳዎች የተመቹ አይደሉም፡፡ በፈለግነው ሰዓት እና ፕሮግራም ሜዳዎቹን ስለማንጠቀምም ተሰቃይተናል፡፡ የማይመቹት ሜዳዎች በየቡድኑ የተያዙ ተጨዋቾችን ለጉዳት መዳረጋቸው የሚያስቆጭ ነው፡፡ እናም በደደቢት ክለብ ላይ በመሰረተ ልማት ረገድ አሳሳቢው ችግር የራሳችን ሜዳ ሊኖረን አለመቻሉ ነው፡፡ ይሄን ችግር በቀጣይ ዓመት ለመፍታት ፍላጎት አለን፡፡ የአዲስ አአባ መስተዳደር መሬት በሊዝ ሰጥቶናል፡፡ መሬቱን በሊዝ መግዛት ቢኖርብንም 7.5 ሚሊዮን ብር መክፈል ባለመቻላችን እስካሁን አልተረከብነውም፡፡ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ከፍለን ካልተረከብነው ሊወሰድብን ይችላል፡፡

የየፕሮጀክቶቹን እንቅስቃሴ ውጤታማ ለማድረግ፤ በየደረጃው የሚወዳደሩ የክለቡን ቡድኖች ማንቀሳቀሻ በጀት ለመመደብ እንዲሁም ክለቡን በመሰረተ ልማት ለማጠናከር በቂ የፋይናንስ አቅም ያስፈልጋል፡፡ የደደቢት ስፖርት ክለብ የሚተዳደርበት አቅም ምን ደረጃ ላይ ነው? የደደቢት ስፖርት ክለብ በቂ የፋይናንስ አቅም የለውም፡፡ በየፕሮጀክቱ የምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ውጤታማነት፤ በዋናው ቡድን የፕሪሚዬር ሊግ ጠንካራ ተፎካካሪነት ፤ እንዲሁም በአፍሪካ ደረጃ ባሳየነው አቅም እና ለብሄራዊ ቡድን ከፍተኛ ብዛት ያለውን የተጨዋቾች አስትዋፅኦን በመመልከት ክለቡ በከፍተኛ ፍጥነት እድገት ላይ እንደሚገኝ ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ይሁንና እነዚህ አበረታች እንቅስቃሴዎችን በዘላቂነት ለመቀጠል የሚያስፈልገው አስተማማኝ ፋይናንስ ግን የተጠናከረ አይደለም፡፡ ከፈጣኑ የክለባችን እድገት ተያይዞም የፋይናንስ ፍላጐቱ እየጨመረ ይሄዳል፡፡ የደደቢት ስፖርት ክለብ ከ16 አመታት በፊት ከተመሰረተ አንስቶ ዛሬም ድረስ የራሱ ገቢ የለውም፡፡ የክለቡ የፋይናንስ አቅም በአጋርነት አብረውን በሚሰሩት ግለሰቦች እና አጋር ድርጅቶች ድጋፍ የተወሰነ ነው፡፡ ክለቡ ሲመሰረት ከተወሠኑ ደጋፊዎች የምናገኘው ድጋፍ በሺዎች የተወሰነ ነበር፡፡ በየውድድር ዘመኑ ግን ክለቡ እያደገ ከመምጣቱ፤ በአህጉራዊ ውድድሮች ተሳታፊ ከመሆኑ እና በተለያዩ ፕሮጀክቶች በስፋት በመንቀሳቀስ ላይ መገኘቱ ከደጋፊዎቻችን በሚሊዮን የሚገመት መዋእለንዋይ የምንፈልግበት ደረጃ ላይ አድርሶናል፡፡

ባለፉት አራት የውድድር ዘመናት አጋር ድርጅቶች በየጊዜው በሚያደርጉልን መዋጮ በጀታችንን በመሸፈን ስንሰራ ቆይተናል፡፡ በ1999 ዓ.ም ክለቡ 10ኛ ዓመቱን ሲያከብር አንዳንድ ድርጅቶች እና ኩባንያዎች በገንዘብ መዋጮ ለክለቡ ድጋፍ መስጠት ጀምረዋል፡፡ የመጀመርያውን ድጋፍ ያገኘነው ለኢትዮጵያ ስፖርት ማደግ ከፍተኛ ፍላጎት ካላቸው ክቡር ሼህ መሃመድ አላሙዲ ነው፡፡ ከእርሳቸው ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ እስከ 18 ሚሊዮን ብር አግኝተናል፡፡ ከዚያ በኋላ ከመከላከያ ድርጅቶች ጋር የምንሰራበትን ሁኔታ በመፍጠር ስንቀሳቀስ ቆይተናል፡፡ ዛሬ እነዚህ የመከላከያ ድርጅቶች የክለቡ ግንባር ቀደም አጋሮች ናቸው፡፡ በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ድርጅቶቹ የክለቡ የፋይናንስ ደጀን ነበሩ ለማለት ይቻላል፡፡ ከመከላከያ ድርጅቶቹ ሲሰጥ የቆየው የበጀት ድጋፍ በስፖንሰርሺፕ ስምምነት አይደለም፡፡ ለክለቡ ባላቸው ተቆርቋሪነት የክለቡ ራዕይ ዘላቂነት እንዲኖረውና ለአገር የሚሆነውን አስተዋፅኦ በማመናቸው የበጀት ድጋፍ እያደረጉልን ይገኛል፡፡ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝና የመከላከያ ብረታ ብረት ኢንጅነሪኒግ ኮርፖሬሽን ዋናዎቹ የክለቡ አጋሮች ናቸው፡፡ እንግዲህ ክለቡ ለዘንድሮ የውድድር ዘመን የያዘው በጀት 16 ሚሊዮን ብር ነው፡፡ ከዚህ በጀት 80 በመቶው የተሸፈነው በእነዚህ ድርጅቶች ነው፡፡

አሁን የክለቡ አመራሮች የክለቡን የፋይናንስ አቅም ለማጠናከር በሚያስችል አቅጣጫ ለመስራት ወስነናል፡፡ ክለቡ በፋይናንስ አቅም ተዳክሞ ከሚገኝበት የዕድገት አቅጣጫ እንዳይሰናከል አጋሮቻችን የዚህ እቅድ ዋነኛ ሃይል ናቸው፡፡ በዚህ መሰረት በቀጣይ የውድድር ዘመን የደደቢት ስፖርት ክለብን በባለቤትነት የሚያስተዳድር ራሱን የቻለ ኩባንያ ለማቋቋም ወስነናል፡፡ ይህ አቅጣጫ የክለቡን የፋይናንስ አቅም በማጠናከር ለህልውናው ወሳኝ ምእራፍ መሆኑን አምነንበታል፡፡ የመከላከያ ድርጅቶች ከደደቢት ጋር በአጋርነት መስራታቸው ከመከላከያ ክለብ የጥቅም መጋጨትን የሚፈጥር ሁኔታ አይደለም ወይ ? የመከላከያ ክለብ ባለቤትነት የሚኒስትር መስሪያ ቤቱ እና ሠራዊቱ ነው፡፡ ባለኝ መረጃ መሠረት ክለቡ ከሠራዊቱ በሚገኝ መዋጮ እና በሚኒስትር መስሪያ ቤቱ በሚለቀቅ በጀት የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ እኔው ራሴ በመከላከያ ሚኒስትር ሰራተኛነት እስከ ባለፈው ዓመት በቆየሁባቸው ዓመታት ለመከላከያ ክለብ በየወሩ ከደሞዜ መዋጮ ሳደርግ ቆይቻለሁ፡፡ በአጠቃላይ የደደቢት እና የመከላከያ ክለቦች ከፋይናንስ ድጋፎች ጋር በተያያዘ የገቡት የጥቅም ግጭት ሆነ ቅራኔ ያለ አይመስለኝም፡፡ የመከላከያ ሚኒስትር እና ሰራዊቱ ለደደቢት ክለብ የሚከፍሉት መዋጮ የለም፡፡

የደደቢት ስፖርት ክለብ አጋሮች የሆኑት የመከላከያ ድርጅቶች እንጂ የመከላከያ ሚኒስትር እና ሰራዊቱ አይደለም፡፡ በእርግጥ ደደቢት በስታድዬም በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ክለቡን ለመደገፍ የሚመጡ የሠራዊቱ አባላት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ይህ ግን እንደማንኛውም የስፖርት ማህበረሰብ ቡድኑን በማድነቃቸው ብቻ የሚያደርጉት እንጅ የክለቡ ባለድርሻ ሆነው አይደለም፡፡ ክለቡ የገቢ ምንጮቹን ለማስፋት የሚያደርጋቸው ጥረቶች በምን ደረጃ ላይ ናቸው? በአገራችን እግር ኳስ ላይ የተጋረጠ አንዱ ትልቅ ችግር የስፖርት ስፖንሰርሺፕ አሠራር አለመስፋፋቱ ነው፡፡ የማልያ ስፖንሰር ሺፕ እንኳን አግኝቶ የክለብን የገቢ አቅም መጨመር ብዙ የተጠናከረ አይደለም፡፡ ደደቢት በማልያ ስፖንሰርሺፕ በፈርቀዳጅነት ሊታይ የሚገባ ጥረት አድርጓል፡፡ ለሁለት አመት በሚቆይ የውል ስምምነት የደደቢት የማልያ ስፖንሰር የሆነው የሳምሰንግ ኩባንያ ነው፡፡ ስምምነቱ ከጅምሩ ለክለቡ 1 ሚሊዮን 400ሺ ብር ያስገኘ ነው፡፡ በማልያ የስፖንሰርሺፕ ድጋፍ የሳምሰንግ ኩባንያ የሚከፍለን ገንዘብ በ300ሺ እንዲጨምር አቤቱታ አቅርበን ነበር፡፡

በጎ ምላሽ አግኝቶ ከማሊያ ስፖንሰር ሺፕ የምናገኘው ገቢ 1 ሚሊዮን 700ሺ ብር ደርሷል፡፡ የማልያ ስፖንሰርሺፕ ድጋፉን ያገኘነው በኢትዮጵያ የሳምሰንግ ኩባንያ ወኪል ሆኖ በሚሰራው የጋራድ ኩባንያ በኩል ነው፡፡ የስፖንሰርሺፕ ውሉን በፈርቀዳጅነት ስንጀምረው በቂ ጥቅም አግኝተንበት አይደለም፡፡ ከኩባንያው ጋር በዘላቂነት የምንሰራበትን መግባባት ለመፍጠር ብለን የፈፀምነው እንደሆነ መታወቅ አለበት፡፡ በርግጥ በመደበኛው አሠራር የማልያ ስፖንሰሩ ትጥቆቹን በሙሉ ለክለቡ ማቅረብ ነበረበት፡፡ እኛ ጅምር የስፖንሰርሺፕ ድጋፉ ቀጣይነት እንዲኖረው ለማበረታታት ብለን ሙሉውን ትጥቅ በመግዛት በመጠቀም ላይ ነን፡፡ ከሚቀጥለው የውድድር ዘመን ጀምሮ ይህን የማልያ ስፖንሰርሺፕ በአዲስ የውል ስምምነት ለማሻሻል እንፈልጋለን፡፡ የሳምሰንግ ኩባንያ ኃላፊዎችም ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀውልናል፡፡ በተለያዩ መንገዶች ሌሎች አጋር ድርጅቶችን በስፖንሰርሺፕ ድጋፍ በዙሪያችን እንዲሰባሰቡ ብንፈልግም በኢትዮጵያ ስፖርት በጋራ ተጠቃቅሞ የመስራት አካሄድ ባለመጠናከሩ አልተሳካልንም፡፡

በርካታ ኩባንያዎችና ድርጅቶች የስፖንሰርሺፕ ስምምነት ለጋራ ጥቅም ይሆናል የሚል እምነት የላቸውም፡፡ የስፖንሰርሺፕ ድጋፍን ከልመና ጋር የምናያይዝበት ደካማ አስተሳሰብ አለ፡፡ የገቢ ምንጮችን የሚያጠናክሩ የስፖንሰር ሺፕ ድጋፎችን ለማግኘት የአገሪቱ እግር ኳስ ደረጃ አለማደግ እንደ ዋና ምክንያት ሆኖ ይጠቀሳል፡፡ ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሮች በየውድድር ጠንካራ ተሳትፎና ውጤት እያገኙ መምጣታቸው የብሔራዊ ቡድኖች በትልልቅ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ ውድድሮች በዘላቂ ሁኔታ መሳተፋቸው የስፖንሰሮችን ፍላጎት ሊፈጥር እንደሚችል ግን ተስፋ እያደረግን ነው፡፡ መጭው ጊዜ በስፖንሰርሺፕ ድጋፎች የክለቦችን የገቢ ምንጭን ለማስፋት ተስፋ አስቆራጭ አይደለም፡፡ ደደቢት በፌደሬሽኑ በኩል በሚያጋጥሙ ምቹ ያልሆኑ አሰራሮችን በተደጋጋሚ በመጋፈጥ፤ በመቃወም እና ጠንካራ አቋሞቹን በማንፀባረቅ ይታወቃል፡፡ በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር ፕሮፌሽናል የሊግ ኮሚቴ አለመመስረቱን በተመለከተ ምን አስተያየት ይኖርዎታል? ደደደቢት ብሄራዊ ሊግ መወዳደር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ከፌደሬሽኑ ምቹ ያልሆኑ አሰራሮች ጋር ፊት ለፊት ሲጋጠም ቆይቷል፡፡ ክለቡ የማያምንበትን አሰራር በመተቸት እና አቋሙን በመግለፅ የሚታገል ነው፡፡

በማንኛውም ሁኔታ ለምናቀርባቸው ጥያቄዎች ምላሽ ባናገኝም ለመመርያ ተገዢ በመሆን አቋማችንን ከመግለፅ ወደኋላ አንልም፡፡ የሊግ ኮሚቴ ፌደሬሽኑን ባቀፈ ኮሚቴ የሚሰራበትን ሁኔታ በጣም የምንቃወመው ነው፡፡ የአንድ አገር ሊግ ውድድር በፕሮፌሽናል መካሄድ ካለበት የኮሚቴ አሰራር አይሆንም ፡፡ የፕሪሚዬር ሊግ ውድድርን ተሳታፊ ክለቦች በባለቤትነት ይዘውት እንደኩባንያ መተዳደር አለበት፡፡ በዚህ አይነት አሰራር አለመወዳደራችን ብዙ ነገር እያሳጣን ነው፡፡ በመጀመርያ ደረጃ የሊግ ውድድሩ ለክለቦች በቂ የገቢ አቅም እየፈጠረ አይደለም፡፡ የክለቦች የሜዳ ገቢ እጅግ አነስተኛ ነው፡፡ በዚያ ላይ ፌደሬሽኑ ተገቢ ያልሆነ ድርሻ ይወስዳል፡፡ ከሜዳ ገቢ የፌደሬሽኑ ድርሻ 32 በመቶ መሆኑይህ በፍፁም ትክክል አይደለም፡፡ በዚህ አይነት ዓመቱን በሙሉ ከሜዳ የምንስበስበው ገቢ የአንድ ተጨዋች ደሞዝ እንኳን የሚሸፍን አይደለም፡፡ ፕሮፌሽናል የሊግ አመራርን በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር መከተል ጊዜ ሊሰጠው አይገባም፡፡ የሊጉ ውድድር አብይ ስፖንሰር በማግኘት ከፍተኛ ገቢ ማምጣት አለበት፡፡ ለተወዳዳሪ ክለቦች በቂ የገቢ ድርሻ የማያስገኝ ውድድር ምንም አይነት እድገት ሊኖረው አይችልም፡፡ በአጠቃላይ ክለቦች የተለያዩ የገቢ ምንጮች ሊፈጥሩ የሚችሉበትን አሰራር ዘርግቶ መስራት ያስፈልጋል፡፡ ከ4 ዓመት በፊት በክለቦች ብቻ የሚመራ ፕሮፌሽናል የሊግ ኮሚቴ ለማቋቋም ክለቦች አቋም ነበራቸው ፡፡ ይህ አቋም እስከዛሬ ለምን ተግባራዊ ማድረግ እንዳልተቻለ አይገባኝም፡፡

አርቲስት ፍቃዱ አያሌው ባጋጠመው የነርቭ ህመም ወደ ታይላንድ ባንኮክ ሄዶ ህይወቱን የሚታደግ ህክምና እንዲያገኝ በህክምና ባለሙያዎች ተወሰነ፡፡ የሰዓሊው ጓደኖችና ወዳጅ ዘመዶች በውጭ አገር በሚያደርገው ህክምና ጥሪ ለማሰባሰብ እያስተባበሩ ናቸው፡፡ ሰዓሊ ፍቃዱ የነርቭ ህመሙ ለመታከም አዲስ አበባ ለሚገኘው የሚዮንግ ሰንግ ሆስፒታል ቆይታ ቢኖረውም ሙሉ ለሙሉ ሊፈወስ አልቻለም፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የስነጥበብ ትምህርት ቤት በማዕረግ የተመረቀው አርቲስት ፍቃዱ አያሌው በዳንዲቦሩ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመምህርነት አገልግሏል፡፡ለሰዓሊው የውጭ ሀገር ህክምና ድጋፍ ለሚያደርጉ ሁለት የሞባይል ስልክ ቁጥሮች 0911742168 እና 0919193132 መጠቀም የሚቻል ሲሆን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአካውንት ቁጥር 1000031068 437 መላክ እንደሚቻል አስተባባሪዎቹ ገልፀዋል፡፡

የኢትዮጵያ የዜማ አባት የሚባለው ቅዱስ ያሬድ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች እየተዘከረ ሲሆን አዲስ አበባ የሚገኘው የደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ ቤተክርስትያን፤ የዜማ አባቱ የተወለደበትን 1500ኛ የልደት በዓል ነገ ከረፋዱ አራት ሰዓት እንደሚያከብር አስታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን አዲሱ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እንደሚገኙ በሚጠበቅበት በዓል፤ “በቅዱስ ያሬድ ታሪክ እና ሥራዎች” ላይ ውይይት ይካሄዳል ተብሏል፡፡

ፒያሳ አካባቢ የሚገኘው ኤልቤት ሆቴል ከዚሁ ልደት ጋር በተያያዘ የቅዱስ ያሬድ ዜማዎች በተባበሩት መንግስታት የባሕል ቅርስ ሆነው መመዝገባቸውን አስመልክቶ ዝግጅት እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡ ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት በሚቀርበው ዝግጅት፤የቅዱስ ያሬድ ቤተክርስትያን ዘማሪዎች ያሬዳዊ ዜማ እንደሚያቀርቡ ተገልጿል፡፡

በሻሸመኔ ከተማ ጥበብ አፍቃሪዎች የተቋቋመው ከ “አድማስ ፊት” የኪነጥበብ ማህበር 42ኛ ዝግጅቱን ነገ ከሰዓት በኋላ በከተማዋ ሁለገብ አዳራሽ እንደሚያቀርብ ገለፀ፡፡ በዚህ ጥበባዊ ዝግጅት ላይ አርቲስት ታምሩ ብርሃኑ እና ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ልምዳቸውን ለታዳሚዎች እንደሚያካፍሉ ማህበሩ አስታውቋል፡፡