Administrator

Administrator

አንዳንድ ጨዋታ የዕውነት ያህል አሳማኝ ነው፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በተባበሩት መንግሥታት ጉባዔ ላይ ከፍተኛ ጭቅጭቅ ይነሳል፡፡ በኃይል ጭቅጭቁን ያካረሩት አራት አገሮች ናቸው፡-
1ኛ/ እንግሊዝ
2ኛ/ ፈረንሣይ
3ኛ/ እሥራኤል
4ኛ/ ሩማኒያ
እንዲያ በኃይል ያጨቃጨቃቸው አጀንዳ፤ “አዳምና ሔዋን የየት አገር ሰዎች ናቸው?” የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
በመጀመሪያ ሙግቷን ያቀረበችው እንግሊዝ ናት፡፡ እንዲህ ነው ያለችው፤ በተወካይዋ አማካኝነት፤
“አዳምና ሔዋን ያለጥርጥር እንግሊዞች ናቸው፡፡ ለምን ቢባል፤ እንግሊዛዊ ሰው ብቻ ነው አንዲት ሴት ትፈጠር ዘንድ በጨዋነት የገዛ ጎድኑን አሳልፎ የሚሰጥ”  
ይሄኔ የፈረንሳዩ ተወካይ ከመቀመጫው ተፈናጥሮ ተነሳና፤
“በጭራሽ እንደዛ አይሆንም! እስቲ የአዳምን ቁመናና ቁንጅና ተመልከቱ፡፡ ራቁቱን ሆኖ እንኳን እንዴት እንደሚያምር ልብ - በሉ፡፡ ይሄ ሊኖረው የሚችለው ፈረንሳዊ ብቻ ነው” አለ፡፡
ቀጥሎ የቀረበው ተሟጋች እሥራኤላዊው ተወካይ ነበር፡፡ እንዲህ አለ፡-
“በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በትክክል እንደተቀመጠው፤ፍጥረት የተፈጠረው በቅድስቲቱ ምድር ነው፡፡ ስለዚህም አዳምና ሔዋን የተመረጡት ህዝቦች ናቸው! ስለሆነም አይሁዳውያን ናቸው!”
ይሄኔ የሩማኒያው ተወካይ ጭንቅላቱን እየነቀነቀ ብድግ አለና፤
“የለም! በእኛ በሩማንያን ዕምነት አዳምና ሔዋን ሊሆኑ የሚችሉት ሩሲያዊ ነው!”
“እንዴት? አስረዳና?” ብለው ሁሉም ጮሁበት፡፡
የሩማንያው ተወካይም፤
“ምክንያቴን ላቅርብላችሁ፡፡ በዓለም ላይ ሩሲያዊ ብቻ ነው በደንብ ሳይበላና በደምብ ሳይለብስ ገነት ውስጥ ነው ያለሁት የሚል!” ሲል ገለፀ፡፡
ተጨበጨበለት!!
*   *   *
አገርን ከሌላ አገር ማስበለጥ፣ የራስን ፓርቲ ከሌላው ፓርቲ የበላይ ነው ለማለት መሞከርና እኔ እሻል እኔ እሻል መባባል፣ ጥንትም ነበረ፣ አሁንም ያለ እና ወደፊትም የሚኖር ነው፡፡ ያም ሆኖ ያላንዳች ምክናዊነት፣ አንዱ ሌላውን መብለጥ አይችልም፡፡ አመክንዮ ይፈልጋል፡፡
በሀገር ደረጃ ሲታይ ከፖለቲካ ጥንካሬ እስከ ኢኮኖሚ ጥንካሬ፣ ከዚያም የወታደራዊ አቅም፣ እንዲሁም ማህበራዊ መሰረትን ይጠይቃል፡፡ እነዚህን ለማሟላት ብርቱ ድካም፣ የረዥም ጊዜ ባለታሪክ መሆንንም ይጠይቃል፡፡
በሀገራችን ያየናቸው ለውጦች ከወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት፣ እስከ ተማሪ እንቅስቃሴ፣ ውለው አድረውም የተደራጁ ወታደራዊ ኃይሎች አመራር ሥር የወደቁ ነበሩ፡፡ በዚሁ ዙሪያ የተደራጁ ፓርቲዎችና ድርጅቶች ተወልደዋል፡፡ ወደ ትጥቅ ትግልም ያደጉ ታይተዋል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ግን እርስ በርስ ከመቆራቆስና ከመጠላለፍ፣ አልፎ ተርፎም ከመጨራረስ በስተቀር ሁነኛ የፖለቲካ መድረክ ፈጥረው፣ ሁነኛ ክርክርና ሀቀኛ ሙግት ተሟግተው፣ እዚህ ስምምነት ላይ ደረሱ የሚባልላቸውና የሚያኮሩ አልተገኙም፡፡ መንግሥትና ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣አይጥና ድመት ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ነበሩ፡፡ ክፍተቱ ሰፊ ነው፡፡ እስከ ዛሬ ስናይ የኖርነው፤ የቂም በቀል፣ የደባና የሤራ፣ ከእኔ በላይ ላሣር እና የደም መፈላለግ ፍጥጫ በመሆኑ የሰላማዊ ትግል ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ፣በሰለጠነ መልክ ተነጋግሮ ዳር መድረስ ያልተሞከረ ነው፡፡ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤ “የኢትዮጵያ ፖለቲከኛ ሁሉ በየኪሱ ትናንሽ ዘውድ ይዞ ነው የሚዞረው!”
ከተማሪ እንቅስቃሴ ጊዜ ጀምሮ እንደመሪ መፈክር ሲያገለግል የኖረው፤   
‹‹unity is power››
‹‹አንድነት ኃይል ነው›› የሚል ነበር፡፡
“United, we stand
 Separated, we fall!›› የሚልም ነበር፡፡ (‹‹ከተባበርን እንቆማለን፤ከተነጣጠልን እንወድቃለን!›› እንደ ማለት ነው፡፡) በአጭሩና በተለመደው የአማርኛ አባባል፤‹‹ድር ቢያብር አንበሳ ያሥር›› ማለት ነው፡፡ ይሄ ዛሬም ይሠራል፤በአግባቡ የሚጠቀምበት ከተገኘ፡፡ ጥበብ ይጠይቃል፡፡ በሆይ ሆይታና በግርግር፤ በችኮላ የሚፈጠር አካሄድ መጨረሻው አያምርም፡፡ የፖለቲካ ድርድር የአንድ ወገን ብልጠት አይደለም፡፡ የሀገር ጉዳይ ነውና ሁሉም ወገን በልባዊነት ሽንጡን ጠበቅ ሊያደርግበት የሚገባ ነገር ነው፡፡ በተንኮል ሽረባም የሚሆን ነገር አይደለም፡፡ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
‹‹ነገር በሆድ ማመቅ
ለትውልድ መርዝ መጥመቅ›› የሚለን ለዚህ ነው!
ከሁሉም በላይ መቻቻል የሚፈተንበት፣ሆደ-ሰፊውና አስተዋዩ የሚለይበት ነው። የፖለቲካ ብልህነት ጠርቶ የሚወጣበት ነው፡፡ ዲሞክራሲ የተሸናፊዎች መብት መሆኑን በእርግጥ የምናጣራበት ሂደትም ነው፡፡ ገዢው ዘራፍ ሳይል፣ተገዢው በቂምና በቅሬታ ሳይወጣ ማየት እንሻለን፡፡ ሰላማዊ ትግል የሰላም አገር መለያ ነውና፣ከትንቅንቁ ባሻገር ግልፅ ውይይት እንጠብቃለን፡፡ ስለታሰሩ የተቃዋሚ አባላት ምን ሀሳብ እንደሚነሳ ለመስማት እንጓጓለን፡፡ ስለምርጫ ህግጋት ለውጥ ምን እንደሚወሳ ለማዳመጥ እንተጋለን፡፡ በመጨረሻ ግን አንደበተ ርቱዕነት ብቻውን የአሸናፊነት መገለጫ እንዳልሆነ እናውቃለን፡፡ ቀናነት፣ ቁጡነትን ማስወገድ፣ የቤት ሥራን በሚገባ ሰርቶ መምጣት፣ ወቅታዊ (timely) የሆነውን ጉዳይ፤ ጊዜ ከማይሽረው (timeless) ጉዳይ ለይቶ ማየት ወሳኝነት አላቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን፤
‹‹በርበሬ አይሆንም ዕጣን
ንግግር አይሆንም ሥልጣን››
የሚለውን አባባል አለመዘንጋት ነው! ይሄን ልብ እንዲሉም አደራ ጭምር እናስታውሳለን፡፡

ከአፍሪካ እና የመካከለኛው ምስራቅ አየር መንገዶች አንደኛ ደረጃን ይዟል

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ሰዓትን በማክበር ከአለማችን አየር መንገዶች 11ኛ፣ ከአፍሪካና ከመካከለኛው ምስራቅ አገራት አየር መንገዶች ደግሞ የ1ኛ ደረጃን መያዙን አለማቀፉ የአቪየሽን የመረጃ ተቋም “ፍላይትስታትስ” ሰሞኑን ባወጣው ወርሃዊ አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017 የመጀመሪያ ወር ካደረጋቸው 8 ሺህ ያህል በረራዎች 81 በመቶ ያህሉን ያጠናቀቀው፣ በረራዎቹን ለማጠናቀቅ ካስቀመጠው ጊዜ በ15 ደቂቃዎች ውስጥ መሆኑንም ተቋሙ በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
አየር መንገዱ በበረራ ሰዓት አክባሪነት በአለማቀፍ ደረጃ ባስመዘገበው ከፍተኛ ውጤት ጥልቅ ደስታ ተሰምቶናል፤ ስኬቱ የአየር መንገዳችን የ12 ሺህ ትጉህ ሰራተኞች ጥረት ውጤት በመሆኑ ‹እንኳን ደስ አላችሁ› ለማለት እወዳለሁ ብለዋል፤ ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ተወልደ ገብረ መድህን፡፡
“ሰዓቱን የጠበቀ በረራ ማከናወን የክቡራን ደምበኞቻችንን ፍላጎት በአግባቡ ለማሟላት ወሳኝ መሆኑን በአግባቡ እንረዳለን፤ ሁላችንም ሰዓቱን የጠበቀ በረራ እንዲኖር ለማስቻል ተግተን እየሰራን ነው” ሲሉም አክለዋል፡፡

    የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማኅበር 25ኛ ዓመት የብር ኢዮበልዩ በዓሉን ያከበረ ሲሆን ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የቦርድ ሊቀመንበሩ አሳታውቀዋል፡፡
ማኅበሩ 25ኛ የብር ኢዮበልዩ በዓሉንና ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤውን ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል ባከበረበት ወቅት የቦርድ ሊቀመንበሩ ኢ/ር አበራ በቀለ፣ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው የአባሎቻቸው የመፈፀም አቅም እየጎለበተ የኮንትራት አስተዳደር፣ የሳይት ማኔጅመንትና የኩባንያ አደረጃጀት እየተሻሻለ መሆኑን ተናግረዋል።
ማኅበሩ ሲመሠረት የአባላት ቁጥር 30 እንደነበር የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ በአሁኑ ወቅት የአባላት ቁጥር ከ1600 በላይ መድረሱን፣ ከአዲስ አበባ ውጭ በክልል ከተሞች በባህርዳር፣ በመቀሌና በሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መክፈቱ የስኬታማነቱ መገለጫ ናቸው ብለዋል፡፡
አገሪቷ ባለፉት 25 ዓመታት ያከናወነቻቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች፣ የቤቶች ግንባታ፣ የመንገዶች፣ ድልድዮች፣ የኃይል ማመንጫ ግድቦች…. ፕሮጀክቶችና የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች አቅም አይመጣጠንም ያሉት ኢ/ር አበራ፤ ከመንግሥት ጋር በጣምራ በመሆን ኮንትራክተሮች ራሳቸውን የሚያደራጁበት የአቅም ግንባታ ሥራ ይጠብቀናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የፕሮጀክቶችን መጓተትና መዘግየት በተመለከተ ውጫዊና ውስጣዊ ምክንያቶች እንዳሉ ጠቅሰው፣ ውጫዊ የምንለው፣ ሥራው ለኮንትራክተሮች ሲሰጥ ፅድት ብሎ ተሰርቶ፣ ፕላኑ ፣ በጀቱ፣… ካልተሰጠ፣ ፕላኑ የሚቀየር፣ በጀቱ የሚቀነስ ከሆነ፣ ከሥራው ጋር ተያያዥነት ያላቸው ነገሮች ሥራ ካልተጠናቀቀ፣ ማለትም ሥራው ከመጀመሩ በፊት የተጠናቀቀ ዶክመንት ካልቀረበ  ፕሮጀክቱ ይጓተታል፡፡ ውስጣዊ ምክንያቶች የሚባሉት ደግሞ የኮንትራክተሩ የአቅም ማነስ ችግር ነው፤ በተለይ የፋይናንስ፡፡ “የኮንትራክተሩ ገንዘብ ያለው ሚክሰር፣ ገልባጭ፣ ዶዘር፣ የመሳሰሉት ላይ ስለሆነ ሥራ ማስኬጃ ያጥረዋል፤ ገንዘብ እስኪያገኝ ድረስ ሥራው ይዘገያል፣ ይጓተታል በማለት አስረድተዋል፡፡

በአውሮፓ ትልቁ የሆቴል ዘርፍ ኩባንያ የሆነው የፈረንሳዩ አኮር ሆቴልስ ግሩፕ በአዲስ አበባ ሶስት ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችን ለመክፈት የሚያስችለውን የግንባታና የማኔጅመንት ስምምነት ከኢትዮጵያውያን ባለሃብቶች ጋር መፈጸሙን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው ባለፈው ረቡዕ ያወጣውን መግለጫ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገነቡት ሶስቱ ሆቴሎች እስከ መጪዎቹ አራት አመታት ጊዜ ውስጥ ግንባታቸው ተጠናቅቆ ስራ ይጀምራሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ሆቴሎቹ በድምሩ 527 ያህል የመኝታ ክፍሎች ይኖሯቸዋል፡፡
ኩባንያው በአዲስ አበባ ከተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን አቅራቢያ የሚከፍተውና 162 መኝታ ክፍሎች የሚኖሩት የመጀመሪያው ሆቴል በሶስት አመታት ውስጥ ተጠናቅቆ ስራ እንደሚጀምር የሚጠበቅ ሲሆን፣ በዚሁ አካባቢ የሚገነባውና 135 የመኝታ ክፍሎች የሚኖሩት ሁለተኛው ሆቴልም በሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተነግሯል፡፡
ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አቅራቢያ የሚገነባውና እ.ኤ.አ በ2021 ግንባታው ተጠናቅቆ ስራ ይጀምራል ተብሎ የሚጠበቀው ሶስተኛው ሆቴል ደግሞ፣ 230 መኝታ ክፍሎች እና 22 ወለሎች እንደሚኖሩት ተገልጧል። አኮር ሄቴልስ ኩባንያ በአፍሪካ የሆቴል ኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማራ 40 አመታት ያህል እንደሆነው ያስታወሰው ሮይተርስ፤ በ21 የአፍሪካ አገራት በከፈታቸው 94 ሆቴሎች፤ ከ10 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል መፍጠሩንም አክሎ ገልጧል፡፡

      የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማኅበር 25ኛ ዓመት የብር ኢዮበልዩ በዓሉን ያከበረ ሲሆን ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የቦርድ ሊቀመንበሩ አሳታውቀዋል፡፡
ማኅበሩ 25ኛ የብር ኢዮበልዩ በዓሉንና ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤውን ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል ባከበረበት ወቅት የቦርድ ሊቀመንበሩ ኢ/ር አበራ በቀለ፣ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው የአባሎቻቸው የመፈፀም አቅም እየጎለበተ የኮንትራት አስተዳደር፣ የሳይት ማኔጅመንትና የኩባንያ አደረጃጀት እየተሻሻለ መሆኑን ተናግረዋል።
ማኅበሩ ሲመሠረት የአባላት ቁጥር 30 እንደነበር የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ በአሁኑ ወቅት የአባላት ቁጥር ከ1600 በላይ መድረሱን፣ ከአዲስ አበባ ውጭ በክልል ከተሞች በባህርዳር፣ በመቀሌና በሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መክፈቱ የስኬታማነቱ መገለጫ ናቸው ብለዋል፡፡
አገሪቷ ባለፉት 25 ዓመታት ያከናወነቻቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች፣ የቤቶች ግንባታ፣ የመንገዶች፣ ድልድዮች፣ የኃይል ማመንጫ ግድቦች…. ፕሮጀክቶችና የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች አቅም አይመጣጠንም ያሉት ኢ/ር አበራ፤ ከመንግሥት ጋር በጣምራ በመሆን ኮንትራክተሮች ራሳቸውን የሚያደራጁበት የአቅም ግንባታ ሥራ ይጠብቀናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የፕሮጀክቶችን መጓተትና መዘግየት በተመለከተ ውጫዊና ውስጣዊ ምክንያቶች እንዳሉ ጠቅሰው፣ ውጫዊ የምንለው፣ ሥራው ለኮንትራክተሮች ሲሰጥ ፅድት ብሎ ተሰርቶ፣ ፕላኑ ፣ በጀቱ፣… ካልተሰጠ፣ ፕላኑ የሚቀየር፣ በጀቱ የሚቀነስ ከሆነ፣ ከሥራው ጋር ተያያዥነት ያላቸው ነገሮች ሥራ ካልተጠናቀቀ፣ ማለትም ሥራው ከመጀመሩ በፊት የተጠናቀቀ ዶክመንት ካልቀረበ  ፕሮጀክቱ ይጓተታል፡፡ ውስጣዊ ምክንያቶች የሚባሉት ደግሞ የኮንትራክተሩ የአቅም ማነስ ችግር ነው፤ በተለይ የፋይናንስ፡፡ “የኮንትራክተሩ ገንዘብ ያለው ሚክሰር፣ ገልባጭ፣ ዶዘር፣ የመሳሰሉት ላይ ስለሆነ ሥራ ማስኬጃ ያጥረዋል፤ ገንዘብ እስኪያገኝ ድረስ ሥራው ይዘገያል፣ ይጓተታል በማለት አስረድተዋል፡፡

የደቡብ ኮርያ የጦር ሃይል አባላት የሆኑ ወታደሮች በኮርያ ዘመቻ ወቅት የተሳተፉና በጽናት በመታገል ታላቅ ውለታ የሰሩ ኢትዮጵያውያን ዘማቾችን ለመርዳት የሚውል የገንዘብ ድጋፍ እያሰባሰቡ እንደሚገኙ ተዘግቧል፡፡
የደቡብ ኮርያ ጦር በኦፊሻል የፌስቡክ ገጹ ላይ ያወጣውን መረጃ ጠቅሶ ኮፖጆላ የተባለው ድረገጽ ትናንት እንደዘገበው፣ የአገሪቱ 27ኛ ክፍለ ጦር አባላት የሆኑ ወታደሮች በአበል መልክ ከሚሰጣቸው ገንዘብ የተወሰነውን በማሰባሰብ በአለማቀፉ የእርዳታ ድርጅት በኩል ለኢትዮጵያውያን የኮርያ ዘማቾች ለመላክ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡
እ.ኤ.አ በ1951 በተጀመረው የሁለቱ ኮርያዎች ጦርነት፣ ከ6 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ዘማቾች ደቡብ ኮርያን በመደገፍ ለአምስት አመታት ያህል በጽናት መታገላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ 122 ያህሉ ሲሞቱ 536 የሚሆኑት ደግሞ የመቁስል አደጋ እንደደረሰባቸው ገልጧል፡፡
ደቡብ ኮርያውያኑ ወታደሮች የሚያሰባስቡት ገንዘብ፣ በህይወት ለሚገኙ 350 ያህል ኢትዮጵያውያን ዘማቾች እንደሚደርስ የጠቆመው ዘገባው፣ ወታደሮቹ የኢትዮጵያውያን ዘማቾችን ፎቶግራፎች ይዘው በኩራት ስሜት ውለታቸውን እየዘከሩ የሚያሳየው ፎቶግራፍ፣ በጦሩ የፌስቡክ ድረገጽ ላይ መለቀቁንም አክሎ ገልጧል።

ለኦሮሚያ 2 ቢ ብር ተመድቧል - ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
 
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፤ በኦሮሚያ ስድስት ወረዳዎች የምግብ ዋስትናቸው ያልተረጋገጠ ከ1 ሚ. በላይ ሰዎችን ለመደገፍ የ2 ቢ. ብር
ፕሮጀክት ይፋ አደረገ፡፡ ባለፈው ሳምንት በአዳማ ከተማ አዩ ኢንተርናሽናል ሆቴል ይፋ ባደረገው በዚህ ፕሮጀክት ላይ፤ የክልሉ ኃላፊዎች፣ የወረዳ ተወካዮች፣ የወርልድ ቪዥን ካንትሪ ዳይሬክተሮችና ፕሮጀክት ማናጀሮች ተገኝተዋል፡፡ አምስት አመት የሚዘልቀው ይሄው ፕሮጀክት የሚተገበርበት ገንዘብ የተገኘው ዩስኤይድ ለዚሁ ተግባር ከመደበው 175 ሚሊዮን ዶላር ላይ እንደሆነ በዕለቱ ተነግሯል። ወርልድ ቪዥን ላለፉት 40 ዓመታት በኦሮሚያ ክልል 24 ወረዳዎችና አምስት ዞኖች የምግብ ዋስትና ድጋፍና ሌሎች የተቀናጁ የልማት ስራዎችን በመስራት ከ6 ሚ. በላይ ህፃናትንና በጣም ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ሲያገለግል መቆየቱም በዕለቱ ተገልጿል፡፡ ወርልድ ቪቪን ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም ባጠናቀቀው የአምስት አመት የልማትና የምግብ ድጋፍ ፕሮግራም ከ1.5 ሚ. በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረጉን የገለፁት የኦሮሚያ ክልል የደህንነት፣ የግብርናና የተፈጥሮ ሀብት ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድነት ደገፋ አሁንም ወርልድ ቪዥን በ6 ወረዳዎች የምግብ የጤናና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ላይ ለመስራትና ወገኖችን ለመደገፍ ያቀረበውን ትልቅ ሀብት በአግባቡ መጠቀም አለብን ሲሉ ተናግረዋል፡፡የወርልድ ቪዥን የልማትና የምግብ ድጋፍ ፕሮግራም (DFAP) ፕሮጀክት ዳይሬክተር አቶ ጉቱቴሶ እንደገለፁት፤ የዘንድሮው ፕሮጀክት በዋናነት የሚያተኩረው የምግብ ዋስትናቸው ባልተረጋገጠ የኦሮሚያ የአማራና የደቡብ ክልል አካቢዎች ሲሆን ይህን ፕሮጀክት ለማሳካት የ3.8 ቢ. ብር በጀት ማግኘታቸውን ጠቅሰው፣ የአማራው ከሁለት ሳምንት በፊት ይፋ መሆኑንና የደቡቡ በቅርቡ በሀዋሳ እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡ የምግብ ዋስትናቸው ላልተረጋገጠ የሦስቱ ክልል አካባቢ ማህበረሰቦች ከምግብ ድጋፍ በተጨማሪ የተቀናጁ በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ ያሉት አቶ ጉቱ ከነዚህም መካከል በግብርና፣በጤና፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በአኗኗር ዘይቤ በገጠር ስራ ፈጠራና በመሰል ስራዎች ላይ በማተኮር ድርቁን ተከትሎ የመጣውን የምግብ እጥረት እንዲቋቋሙ ይደረጋል ተብሏል፡፡

Saturday, 11 February 2017 14:08

የሙዚቃ ጥግ

 - ለውጥ ሁሌም ይከሰታል፡፡ የጃዝ ሙዚቃ አንዱ ድንቅ ነገር ያ ነው፡፡
   ማይናርድ ፈርጉሰን
- ጃዝ ወደ አሜሪካ የመጣው የዛሬ 300 ዓመት ከባርነት ጋር ነው፡፡
  ፖል ዋይትማን
- የጃዝ መንፈስ የግልፅነት መንፈስ ነው፡፡
  ሔርቢ ሃንኮክ
- ጃዝ ግሩም የመማሪያ መሳሪያ ይመስለኛል፡፡
  ጆን ኦቶ
- በቀን ሦስት ሰዓት ገደማ ጃዝ አዳምጣለሁ፡፡
  ሉዊስ አርምስትሮንግን እወደዋለሁ፡፡
ፊሊፕ ሌቪን
- ጃዝ በተፈጥሮው የብዙ የተለያዩ ዓይነት
ሙዚቃዎች ጥርቅም ነው፡፡
  ዴቪድ ሳንቦርን
- ስለ ጃዝ ማውራት ሁልጊዜም አስደሳች ነው።
  ክሊንት ኢስትውድ
- የጃዝ ሙዚቃ በጣም በርካታ አስደናቂ ዝነኞችን ፈጥሯል፡፡
  ዊንቶን ማርሳሊስ
- ጃዝ ከሌሎች የሙዚቃ ዘውጎች ተውሷልም፤ ለሌሎች የሙዚቃ ዘውጎች አውሷልም፡፡
  ሔርቢ ሃንኮክ
- ጃዝ ልክ እንደ ወይን ጠጅ ነው፡፡ በአዲስነቱ ለባለሙያዎች ብቻ ነው የሚሆነው፤ ሲቆይ ግን ሁሉም ይፈልገዋል፡፡
  ስቲቪ ላሲ
- የጃዝ ሙዚቃ የስሜቶች ቋንቋ ነው፡፡
  ቻርልስ ሚንጉስ
- ጃዝ የማሽን ዘመን የሐገረሰብ ሙዚቃ ነው፡፡
  ፖል ዋይትማን
- ጃዝ የዕለት ተዕለት ህይወትን አቧራ ያጥባል።
  አርት ብሌኪ
- ጃዝ የአሜሪካ ክላሲካል ሙዚቃ ነው፡፡
  ቢሊ ቴይለር

  ሃሊ ቤሪ - የኦስካር አሸናፊ

       ሃሊ ቤሪ በ21 ዓመት ዕድሜዋ የፊልም ተዋናይ ለመሆን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኒውዮርክ ስትጓዝ ገንዘብ አልቆባት ክፉኛ ተችግራ ነበር፡፡ ፒፕል መፅሔት እንደዘገበው፤እናቷ ተጨማሪ ገንዘብ ለልጇ መላክ ተገቢ አይደለም ብላ ወሰነች፡፡ ራሷን እንዳትችል ማሳነፍ ነው በሚል እሳቤ፡፡
    በዚህ ወቅት ነው ሃሊ ቤሪ፣ከቤት አልባ ምስኪኖች ጋር በመጠለያ ውስጥ የኖረችው፡፡ ከሪደር ዳይጀስት ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ቤሪ ስትናገር፡- “በዚያ ሁኔታ ውስጥ ማለፌ፣ራሴን እንዴት መምራት እንዳለብኝና በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ እንዴት መኖር እንደምችል አስተምሮኛል - በመጠለያ ውስጥ ወይም ከእጅ ወደ አፍ በሆነ ገቢም ቢሆን፡፡ ምንጊዜም የራሴን መውጫ መፍጠር እንደምችል የማውቅ ሰው ሆኛለሁ” ብላለች፡፡ የሆሊውዷ ዝነኛ
ተዋናይት ሀሊ ቤሪ፣ የኦስካር አሸናፊ ናት፡፡

---------------------------------

                           ጄምስ ካሜሮን - የፊልም ዳይሬክተር

      ጄምስ ካሜሮን “The Terminator” የተሰኘውን የፊልም ስክሪፕት ሲፅፍ፣በቂ ገቢ አልነበረውም፡፡ ከእጅ ወደ አፍ የሚባል ነበር፡፡ እንደ IGN ዘገባ፤ለተወሰኑ ጊዚያትም በመኪና ውስጥ ለማደር (መኖር) ተገዷል -
ለቤት ኪራይ የሚከፍለው ገንዘብ ስላልነበረው፡፡
    በወቅቱ ካሜሮንን በእጅጉ ያሳስበው የነበረው ጉዳይ ግን ገንዘብ አልነበረም፡፡ “The Terminator” የተሰኘውን ስክሪፕቱን ዲያሬክት ማድረግ ብቻ ነበር የሚፈልገው - በዘርፉ በቂ ልምድ ባይኖረውም፡፡ የፊልም ጽሁፉን ለፕሮዱዩሰሮች ሲያቀርብ፣ብዙዎቹ ስክሪፕቱን ቢወዱለትም፣እሱ በዳይሬክተርነት መስራቱን ግን አይፈልጉም ነበር፡፡
   ካሜሮን ግን በሀሳቡ ፀና፡፡ በመጨረሻም ከፕሮዱዩሰር ጋሌ አኔ ሁርድ ጋር አጋርነት ፈጠረ፡፡ ፕሮዱዩሰሩ የፊልም
ፅሁፉን መብት ከገዛው በኋላ በዳይሬክተርነት መደበው፡ ፡ ካሜሮን ህልሙን እውን አደረገ፡፡ “The Terminator”
በመላው ዓለም ታይቶ፣77 ሚ. ዶላር ገቢ አስገኝቷል፡፡

----------------------------------

                                ጄነፈር ሎፔዝ - ድምፃዊትና ተዋናይት

      ጄኔፈር ሎፔዝ የ18 ዓመት ኮረዳ ሳለች ዳንሰኛ የመሆን ከፍተኛ ጉጉትና ፍላጎት ነበራት፡፡ እንደ ማንኛውም ለልጁ የወደፊት እጣፈንታ የሚጨነቅ እናት፣ሎፔዝ ኮሌጅ ብትገባላት ትወድ ነበር- እናቷ፡፡ ሆኖም ሎፔዝ አሻፈረኝ አለች፡፡ በዚህ ሰበብ በእናትና በልጅ መካከል አለመግባባት ተፈጠረና ከቤት ወጣች፡፡ ከቤት ከወጣች ጀምሮም በዳንስ
ስቱዲዮዋ ሶፋ ላይ ማደር ጀመረች ሲል ዘግቧል - ደብሊው መጋዚን፡፡
    “ቤት አልባ ነበርኩ፤ነገር ግን ይሄንን ነው የምሰራው ብዬ ለእናቴ ነግሬያታለሁ” ብላለች፤ ሎፔዝ ለደብሊው መጋዚን፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላ በአውሮፓ የዳንስ ስራ አገኘች፡፡ ከዚያ በኋላ ሁሉም ነገር ተለወጠ፡፡ የ46 ዓመቷ ዝነኛ አቀንቃኝ፣ ተዋናይት፣ፕሮዱዩሰርና ዲዛይነር ጄኔፈር ሎፔዝ ባለፈው ዓመት 28.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን ፎርብስ ዘግቧል። ያኔ እንኳንስ እናቷ ራሷ ሎፔዝም፣ የዚህን ያህል ተወዳጅ፣ሚሊዬነር፣ስኬታማ ---እሆናለሁ ብላ መች አሰበች!?

----------------------------------

                              ቻርሊ ቻፕሊንና ወንድሙ

     ቻርሊ ቻፕሊንና ወንድሙ ከኑሮ ጋር ፊት ለፊት የተጋፈጡት ገና በለጋ የልጅነት ዕድሜያቸው ነበር፡፡ የአባታቸውን ድንገት ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ተከትሎ፣ እናታቸው የአዕምሮ ህክምና ሆስፒታል ውስጥ ገባች፡፡ ይኼን ጊዜ ታዳጊው ቻፕሊንና ወንድሙ ራሳቸውን ማስተዳደር ነበረባቸው - Charliechapline.com እንደዘገበው፡፡
    ሁለቱም ወላጆቻቸው በትርኢት ሙያ ውስጥ ስለነበሩ፣ ቻፕሊንና ወንድሙ የእነሱን ዱካ ለመከተል ወሰኑ፡፡ መንገዱ አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡ የማታ ማታ ግን ቻርሊ ቻፕሊን ስኬት ተቀዳጀ፡፡ ዛ ሬም ድ ረስ ከ ድምፅ
አ ልባው የ ፊልም ዘመን ታላላቅ ተዋናዮች አንዱ በመሆን ይጠቀሳል - ኮሜዲያኑ ቻፕሊን፡፡

 የደራሲ፣ አርታኢና ሀያሲ ዓለማየሁ ገላጋይ ልብ ወለድ ‹‹በፍቅር ስም›› የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡ 30 ጀምሮ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ኢ/ር ጌታሁን ሄራሞ፣ ቴዎድሮስ አጥላውና አሸናፊ መለሰ በመፅሐፉ ላይ ዳሠሳ የሚያቀርቡ ሲሆን በሀይሉ ገ/እግዚአብሔር - ወግ፤ ገጣሚ ኤፍሬም ስዩም - ግጥም እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ‹‹ተረት ፊልሞች›› አስታውቋል። መድረኩን የሚመራው ጋዜጠኛ ደረጀ ሀይሌ ነው
ተብሏል፡፡ ‹‹በዕለቱም በመፅሃፉ ሁለንተና ላይ ውይይት ይካሄዳል፡፡ እርስዎ መፅሃፉን ካላነበቡ እንብበው፣ ካነበቡ ተዘጋጅተው፣ እንዲያም ሲል እኔ ያነበብኩት የደራሲውን ቀደምት ልቦለዶች ነው ካሉ የመወያያ መድረኩ እርስዎንም ያሳትፋልና እንዳይቀሩብን›› ብሏል-ደራሲው በጥሪ ካርዱ ላይ ባሰፈረው ማስታወሻ፡፡