Monday, 09 March 2015 11:30

የአዲስ አድማስ ትውስታዎች

Written by 
Rate this item
(14 votes)

     በአብዛኛው ፓርቲዎች ለብቻቸው አየር ላይ የተንጠለጠሉ ናቸው፡፡ ከዜጎች ተጨባጭ ችግር ተነስተው መፍትሄ ለመፈለግ የመጡ አይደሉም፡፡ መሰረት የሌለው አመለካከታቸውን ዜጎች ላይ የሚጭኑ ናቸው፡፡ ለመመረጥ ብቻ ብሎ የፖለቲካ አስተሳሰብን ከህዝብ ቃርሞ መሄድ ትክክል አይደለም፡፡ እኔ ብመረጥ፤ በምን አገባኝ ስሜት መያዛችን፣ ምን ዋጋ አለው በሚል ተስፋ ቆራጭነት ቁጭ ማለታችን እንዲያበቃ የበኩሌን ድርሻ ለመወጣት እፈልጋለሁ፡፡”
(ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሣ፤ ለፓርላማ የግል ዕጩ ተወዳዳሪ በነበሩ ወቅት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ከሰጡት ቃለ - ምልልስ የተወሰደ፤
የካቲት 11 ቀን 1992 ዓ.ም)

“አዲስ አበባ መስተዳድር ካለ ቅድመ ዝግጅትና ካለ ውይይት ድንገት በነዋሪው ላይ የሚጭናቸው ህጎችና ሌሎች መሰናክሎች የንግድ እንቅስቃሴውን አዳክመዋል፡፡ መስተዳደሩ በሩን ለውይይት ዘግቶ ለእርምት እድል ነፍጓል፡፡
መስተዳደሩ ራሱን ከነዋሪው አርቋል፡፡ ለማገልገል ሳይሆን በነዋሪው ለመገልገል የፈለገ ይመስላል፡፡”
የቀድሞ የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት (አቶ ክቡር ገና፤ ምክር ቤቱ ባዘጋጀው “ምረጥ አዲስ አበባ” ዘመቻ ላይ  ከተናገሩት የተወሰደ፡፡
አዲስ አድማስ የካቲት 4 ቀን 1992 ዓ.ም)

“ከረጅም አመታት በኋላ ከሚወደኝ የሀገሬ ህዝብ ጋር ለመቀላቀል በመቻሌ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡ ከዚህ የሙዚቃ ትርኢት የሚገኘው ገቢም በድርቅ ለተጎዱ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ የሚውል ይሆናል፡፡
ልዩ ፍቅር ከሚያሳየኝ የኢትዮጵያ ህዝብ ጎን ሆኜ በድርቅ ለተጎዱት ወገኖቼ መርጃ እንዲሆን ማናቸውንም የኪነ ጥበብ ሀብቴን ብሰጥ ለእኔ መታደል ነው፡፡ ዋስትናችንና ኃይላችን የኢትዮጵያ ህዝብ ፍቅር መሆኑን ከልብ አምናለሁ፡፡”
(አስቴር አወቀ፤ ጥር 27 ቀን 1992 ዓ.ም በአገሯ የመጀመሪያ ኮንሰርቷን ስታቀርብ
ለአዲስ አድማስ ከላከችው መልዕክት የተወሰደ)

“አሁን በስራ ላይ ያሉትን ህጎች የሚመለከቱ መሰረታዊ ጉዳዮች ውስጥ ሳንገባ የህጉ አፈፃፀም ሂደት እንዲቀላጠፍ በማድረጉ ስራ ላይ ብዙ መሻሻል የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ነገሮች ግን አክስዮን ገበያውን ከማቋቋም ሊገቱን አይችሉም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከዚህ ቀደም በንጉሰ ነገስቱ ዘመን የአክስዮን ገበያ ነበር፡፡ አሁን ያለው የንግድ ህግም ያኔ የነበረው ነው፡፡ በመሆኑም የአክሲዮን ገበያው ሂደት ሙሉ በሙሉ ህጋዊ ነው፡፡ ህጋዊ እስከሆነ ድረስ በመንግስት በኩል ይኖራል ብለን የምንጠብቀው ጣልቃ ገብነት የለም፡፡ መንግስት በአንዳንድ መልኩ የገበያውን ሂደት የሚያቀላጥፉ ሁኔታዎችን ቢያመቻች ደስ ይለናል፡፡ ይህንንም ያደርጋል ብለን እንጠብቃለን፡፡ ከዚህ ውጪ ከመንግስት ጋር የሚያጋጨን ነገር የሚኖር አይመስለኝም፡፡”
(አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፤  የአዲስ አድማስ ጋዜጣ የመጀመሪያ እትም ላይ ስለ አክስዮን ገበያ ታህሳስ 29 ቀን 1992 ዓ.ም ከተናገሩት የተወሰደ)

Read 5191 times