Administrator

Administrator

በጋዜጠኛና ደራሲ አሰግድ ሀምዛ ተፅፎ የታተመው “በህይወት መስኮት” የተሰኘ መፅሃፍ ዛሬ በሀዋሳ ከተማ ይመረቃል፡፡ መፅሃፉ፤ ወጎችና የፍቅር ደብዳቤዎችን ያካተተ ሲሆን ደራሲው በመምህርነት ባገለገለበት ሙርሲ ብሔረሰብ ውስጥ የታዘበውንና የኖረውን እውነታ በሚጥም ቋንቋና ውበት ፅፎታል፡፡
141 ገፆች ያሉት መፅሀፉ ዛሬ ሲመረቅ፣ የዘርፉ ምሁራን አስተያየት የሚሰጡ ሲሆን በስነ ስርዓቱ ላይ የጥበብ አፍቃሪዎችና ቤተሰቦች እንደሚታደሙ ታውቋል፡፡ መፅሃፉ አገር ውስጥ በ40 ብር፣ በውጭ አገር በ8 ዶላር እንደሚሸጥ ተገልጿል፡፡

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ሰውየው አእምሮ ሀኪም ዘንድ ይሄድና…“ዶክተር፣ መጥፎ ተግባራት እየፈጸምኩ ህሊናዬ እየረበሸኝ ነው…” ይለዋል፡፡
ዶክተሩም… “እና መጥፎ ድርጊት ከመፈጸም የሚከላከል ህክምና እንዳደርግልህ ነው የምትፈልገው?” ይለዋል፡፡ ሰውየውም… “አይደለም…”  ይላል፡፡
ዶክተሩም… “ታዲያ ምን ፈልገህ መጣህ?” ይለዋል፡፡
ሰውየው ምን ቢል ጥሩ ነው…“ህሊናዬን ከሥሩ ነቅለህ አውጣልኝ!”
‘አልሰሜን ግባ በለው’ አሉ…እኛ ዘንድ ቢመጣ ህሊና እያለም እንዴት ‘ህሊናቢስ’ መሆን እንደሚቻል ‘በስምንተኛ ዲግሪ’ ደረጃ እናሰለጥነው ነበር፡፡ የምር ግን የህሊና ነገር እኮ እኛ አገር የሆነች ተረስታ ከአሮጌ አንሶላ ጋር የተጠቀለለች ነው የምትመስለው፡፡  
እናላችሁ…“ትንሽ ህሊና እንኳን የለህም!” ብሎ አማረኛ ቀረ፡፡ ህሊና የሰው ስም ብቻ የሚመስለን እየበዛን ነዋ! (“ህሊና ቢኖረኝ እዚህ አገር ታገኙኝ ነበር ወይ…” ያልከን ወዳጃችን በእግርህ አስነካኸው እንዴ!)
እኔ የምለው…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ነገርየው እንዴት ነው…‘ጉልቤ’ ነገሮች በዙብና! ልክ ነዋ…ጉልቤነት ማለት እኮ የግድ ‘አገጭ ማጣመም’፣ ጥርስን ‘በመሀረብ ማስቋጠር’ ምናምን ማለት ብቻ አይደለም፡፡ የዘንድሮ ‘ጉልቤነት’… አለ አይደል…መአት መልክ አለው፡፡
እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ይቺን ስሙኝማ…የሆነ ሚኒባስ ታክሲ ላይ ያየነው ‘ጥቅስ’ ነው…‘ጥቅሱ’ ምን ይል መሰላችሁ… (ምንም ደስ ባይልም መነገር አለበት፣) “አፍህን ከምትከፍት ሱቅ ክፈት” ይላል፡፡
እናላችሁ…እንዲህ አይነት በህዝብ መገልገያ ላይ ከእግር ጥፍር እስከ ራስ ጸጉር ‘ሙልጭ የምንደረግበት ዘመን ላይ ደርሰንላችኋል፡፡ የምር ግን… እንደዚህ አይነት ነገር መጀመሪያ ስናይ ፈገግ እንደ ማለት ይቃጣናል፡፡ ግን… እኛም ተሰዳቢዎች መሆናችን ሲገባን…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ምን መሰላችሁ…‘የቤትሽን ዓመል እዛው’  ‘አትንጣጪ’ ምናምን ሲባል ዝም ተብሎ ተከረመና አሁን ደግሞ “አፍህን አትክፈት…” ወደ መባል ደርሰናል፡፡
የምር እኮ…ነገርየው በዚሁ ከቀጠለ …ቀስ ብሎ…በአንድ ወቅት እዚች ዋና ከተማችን ጎራ ያለ የገጠሩ ሰውዬ… “አዲስ አበባ ገዳይ ጠፋ እንጂ ሟች ብዙ ነበር!”  ያለበት አይነት ስድብ ነገ ተነገ ወዲያ የማይለጠፍበት ምክንያት የለም፡፡ እነማ…እንደዚህ አይነት ነገር ሲበዛብን፣
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
የምር አስቸጋሪ ጊዜ ነው፡ የደንብ ልብስ የለበሱ በከተማው ጎዳናዎች በበዙበት ጊዜ፣ ማስቲካና መፋቂያ ሻጮች ሲሯሯጡ በምናይበት ጊዜ… አንዳንድ አካባቢ ተረጋግቶ መገበያየት እንኳን እያስቸገረ ነው፡፡ እኔ የምለው… እግረ መንገዴን…የገበያተኛ መዋከብ ‘የደንብ ጥሰት’ ለመሆን ያንሳል እንዴ!
በቀደም መርካቶ ዕቃ ቢጤ ለማየት ወጣ ብለን… “አይ መርካቶ!”  ብለን ተመለስን እላችኋለሁ፡፡ የምር እኮ… የምንጣፍ ሱቆች በበዙበት አካባቢ መራመድ እስኪያቅታችሁ ድረስ ትከበባላችሁ፡፡  ‘የደላላው’ ብዛት! የሆነ ሱቅ ውስጥ ለመግባት ስታስቡ ወጣት ደላሎች እየተከተሉ… “መጋዘኑ እዛ’ጋ ነው፣ ቅናሽ አለው…” “እዛ ሱቅ ያለው አሪፍ ነው…” ምናምን እየተባለ እስኪሰለቻችሁ ድረስ የሚቀባበሏችሁ ወጣቶች ብዛታቸው… አለ አይደል… ያበሳጫል ብቻ ሳይሆን ‘ያስፈራል’ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡
እንግዲህ ይህ ሁሉ ሲሆን በአካባቢው የደንብ ልብስ የለበሱ ሰዎች ውር፣ ውር ይታያሉ— የሚያስጥል የለም እንጂ፡፡ እናላችሁ… ገበያተኛ ሲጉላላ፣ ደንብ አስከባሪውም ዝም፣ ነጋዴውም ዝም፣ ሁሉም ዝም ሲሆን… አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንላለን፡፡  
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እዚህ አገር መድረክ ላይም ‘ሙልጭ’ ተደርጎ መሰደብ እየተለመደ ነው፡፡ መጀመሪያ ሰብሳቢው…“መሀላችን የተሰገሰጉ የራሳቸው ዓላማ ያላቸው…” ምናምን እያለ ‘ሆረር’ ምናምን ነገር ይለቅባችኋል፡፡
‘አስተያየት ሰጪው’ ተነስቶ… “በተባለው ላይ የምጨምረው የለኝም…” ይልና  “ዕድገታችንን ለመግታት የሚፍጨረጨሩ አንዳንድ የስብሰባው ተካፋዮች ላይ እርምጃ ለምን እንደማይወሰድ…” በቁጭት ይጠይቃል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን እከሌ፣ እከሌ ተብሎ እስካልተጠቀሰ ድረስ አንዳንድ “…የስብሰባው ተካፋዮች…” የሚለው ሁላችንንም ስለሚመለከት…አለ አይደል…
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” እንድንል ያደርገናል፡፡
አሀ… ማን በበላው ማን ‘ራዳር’ ውስጥ ይገባል! ልጄ ዘንድሮ ‘…ሁሉም እንደ የሥራው…” ምናምን የሚል አባባል፣ ‘ጥቅስ’…ነገር አይሠራም፡፡ ልጄ…ዘንድሮ ሰው ‘ባልሠራው’ የሚበላበት፣ ‘ባልሠራውም’ የሚበላውን የሚያጣበት ዘመን ነው፡፡
ይቺን ስሙኝማ…የመንገድ ግንባታ ሥራ ላይ ነው አሉ፡፡ እናላችሁ…አንዱ ሠራተኛ አካፋ አልነበረውም፡፡ ታዲያ…አለቃውን፣ “አካፋ የለኝም…” ይለዋል፡፡ አለቅየውም…“ታዲያ ምን ያነጫንጭሀል! አካፋ ከሌለህ ሥራ አትሠራ!” ይለዋል፡፡ ሰውየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው… “ታዲያ እንደ ሌሎቹ ሠራተኞች ምን ተደግፌ ልቁም?” ብሎ አረፈላችሁ፡፡
እናማ…በየቢሮው፣ በየሥራ ቦታው ‘አካፋ ተደግፈን’ የምንቆም መአት ነን፡፡
ይቺን አሪፍ ነገር ስሙኝማ…ሰውየው ለጓደኛው ሲደውል ከጀርባ ድምጽ ይሰማል፡፡ “የምን ጫጫታ ነው የምሰማው?” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም… “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ይለዋል፡፡ ሰውየውም ግራ ይገባዋል፡፡ “የእህቴን ልደት ዓመታዊ በዓል ብሎ ነገር ምንድነው? ወይ ልደት ታከብራለህ፣ ወይ ዓመታዊ በዓል ታከብራለህ፡፡ ሁለቱ የሚገናኙ አይደሉም…” ይለዋል፡፡
ጓደኛየው ምን ብሎ ቢመልስ ጥሩ ነው…“አይ ሞኞ…የእህቴን አሥራ ስምንተኛ ዓመት ልደት አሥራ አምስተኛ ዓመታዊ በዓል እያከበርን ነው…” ብሎት አረፈ፡፡ አሪፍ አይደል!
የዕድሜ ነገር ከተነሳ… ይቺን ስሙኝማ…“በቀደም ሀያ ዘጠነኛ ዓመቴን ሳከብር ለምንድነው ስጦታ ያልሰጠኸኝ?”  ብትለው እሱዬው… “ረሳሽው እንዴ! የዛሬ አምስት ዓመት ሀያ ዘጠነኛ ልደትሽን ስታከብሪ ሽቶ አልሰጠሁሽም?” ብሏት አረፈ፡፡
እናላችሁ…ጉልቤነት መልኩን እየለዋወጠ መከራችንን እያበላን ነው፡፡ ቤት አከራይ በቀን ሁለት ባሊ ውሀ ብቻ እየፈቀደ፣ መብራት በሦስት ሰዓት ላይ እያጠፋ፣ “ከአንድ ሰዓት በኋላ ማምሸት ክልክል ነው…” አይነት ክፉ ሚስት እንኳን የማታስበው ‘ህግ እያረቀቀ’ ይቆይና አንድ ቀን ማታ በር ይንኳኳል፡፡ እናንተም ስትከፍቱ አከራያችሁ ተኮሳትረው ቆመዋል፡፡ እናንተም…“ደህና አመሹ፣ ምነው ደህና!” ስትሉ ምን ትባሉ መሰላችሁ…“ኪራዩ ላይ ከሰኞ ጀምሮ አንድ ሺህ ብር ጨምረናል፡፡
 ካልተስማማችሁ በሁለት ቀን ውስጥ ቤቱን ልቀቁልን፡፡” የምር ያበሳጫል፡፡ ስሙኝማ…የብስጭት ነገር ከተነሳ … “እንትናዬው ምን ያህል ብታበሳጨው ነው ሴቶችን እንደዚህ ጠምዶ የያዛት!” የሚያሰኝ ንግግር ገጥሟችሁ አያውቅም!
ሰውየው ጓደኛውን… “ሬድዮ ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጠረው በገነት ውስጥ ነው ሲሉ ሰማኋቸው፡፡
ምን ማለታቸው ነው?”  ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ጓደኝዬውም ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“እሱን የነገሩህ ሰዎች ፈጣሪ አዳምን ፈጠረ፡፡ ከዚያም ከጎኑ የጎድን አጥንት አወጣና የመጀመሪያውን ድምጽ ማጉያ ፈጠረ ማለታቸው ነው፣”  ብሎት አረፈ፡፡‘ጉልቤነትን’… አለ አይደል… ሲሆን ያስወግድልን፣ ካልሆነም የምንሸከምበትን ትከሻ ያደንድንልን፡፡
“የበጎቹ ጠባቂ ሆይ፣ ‘ወየት’ ነህ!” የምንልበትን ጊዜ ያሳጥርልን፡፡  
ደህና ሰንብቱልኝማ!

   ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት የውሃ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ደርሶ ኖሮ ከውሃው ወጥታ ወደ ባህሩ ዳርቻ ትሄዳለች፡፡ይቺ ኤሊ ቀስ እያለች በረጅሙ የአሸዋ መንገዷ ስታዘግም ሁለት ጓደኛሞች ያዩዋታል፡፡
አንደኛው ፤ “ይቺ ዔሊ ወዴት ነው የምትሄደው?” ይላል፡፡
ሁለተኛው፤ “የመውለጃ ጊዜዋ ደርሶ ይሆናል”
አንደኛው፤ “የመውለጃዋ ጊዜ ቢደርስ ወደ አሸዋው ምን ያስኬዳታል? መኖሪያዋ ውሃ ውስጥ ነው፡፡ እዚያው ወልዳ ተገላግላ እርፍ አትልም እንዴ?”
ሁለተኛው፤ “ለምን ውሃ ውስጥ እንደማትገላገል አላውቅም፤ የማውቀውና ሰዎች ሲሉ የሰማሁት ግን፤ ኤሊ የመውለጃዋ ጊዜ ሲደርስ ወደ ባሕሩ ቅርብ ዳርቻ አይደለም የምትጓዘው፡፡ ከውሃው እጅግ እርቃ ወደማይታይ አቅጣጫ ነው የምትሄደው”
“ልጆችዋን እሩቅ ቦታ ሄዳ የምትገላገል ከሆነ፤ በኋላ እንዴት አድርገው ልጆችዋ ከሷ ጋር ይገናኛሉ? እናታቸው በባሕሩ ውስጥ መሆኗንስ እንዴት ያውቃሉ?”
ይህ ጥያቄ በጣም ውስብስብና በቀላሉ የሚፈታ ስላልሆነላቸው በአቅራቢያው ወደሚገኝ አንድ ጠቢብ ዘንድ ሄደው ሊጠይቁ ይስማማሉ፡፡
ጠቢቡ ቤት ሄደውም፤ “ጠቢብ ሆይ! አንዲት የውሃ ኤሊ አየን፤ ከውሃው ወጥታ ወደ አሸዋው ዘልቃ እርቃ ሄደች፡፡ በኛ ግምት የመውለጃዋ ቀን ደርሶ ይሆናል ተባባልን፡፡ ግን አንድ ጥያቄ አነሳን፡፡ ወልዳ ወደ ባሕር ስትመለስ ልጆችዋን ማን ያመጣላታል? መቼም ህፃናት ናቸውና አውቀው ወደ ባሕሩ አይመጡም፡፡ ደግሞስ ያን ያህል ሰፊ ባሕር ውስጥ እናታቸው የት ትኑር የት እንደምን ያውቃሉ” ሲሉ ጠየቁት፡፡ ጠቢቡም “የአምላክን ተአምር የምታደንቁት እነዚህን አይነት ጉዳዮችን ለመመርመር ስትችሉ ነው፡፡ ኤሊዋ ልጆችዋን የምትወልደው እንዳላችሁት ከባሕሩ ራቅ ያለ ቦታ ሄዳ ነው፡፡ እንዳላችሁትም ከተገላገለች በኋላ የባሕሩ ዳርቻ አሸዋ እንዲሞቃቸው እዚያው ትታቸው ነው ወደ ባሕሩ የምትመለሰው፡፡ ልጆችዋ እስኪጠነክሩ ድረስ እዚያው አሸዋው ላይ ይቆዩና ሰፊውን አሸዋ አቋርጠው ወደ እናታቸው ይመለሳሉ፡፡ የተፈጥሮ ህግ ስለሆነ ያለ ጥርጥር በባሕሩ ውስጥ እናታቸው የቱ ጋ እንዳለች ያውቃሉ፡፡ ዋና አስገራሚ ነገር ግን ወደ ባሕሩ በሚመጡ ጊዜ መንገድ ላይ አደጋ መኖሩ ነው፡፡ በባሕሩ ዳርቻ ላይ የኤሊ ጫጩት እየተመገቡ የሚኖሩ ወፎች አሉ፡፡ ከጫጩቶቹ መካከል በወፎቹ ከመበላት ተርፈው እናታቸው እቅፍ ውስጥ ለመግባት የሚችሉት ጥቂቶቹ የታደሉቱ ናቸው፡፡ ይህ የአምላክ ስርዓተ ተፈጥሮ ነው፡፡ ትላንት እንደዚያ ነበረ፤ ዛሬም አለ፤ ነገም በአግባቡ ይቀጥላል፡፡” አላቸው፡፡
የፍጥረታትን ተዓምር እያደነቁ ወደመጡበት ተመለሱ፡፡
***
በዓለም ላይ በዚህም ቢሉት በዚያም ከመሆን የማይቀር ነገር አለ፡፡ መንግስታት ይለወጣሉ፤ አገሮች ባሉበት ይቆያሉ፡፡ የሚሠሩ ያገኛሉ፡፡ ዳተኞች ባዶ እጃቸውን ይቀራሉ፡፡ የሚጥሩ ዳር ይደርሳሉ፡፡ የተኙ ወደ ኋላ ይሄዳሉ፡፡ ይሄ ተፈጥሮአዊ የሆነው ነገር አይቀሬ ነው፡፡ ከኤሊ ጫጩቶች መካከል ተርፈው ለእናታቸው የሚኖሩ ጥቂቶቹ ይሁኑ እንጂ ይኖሩ ዘንድ የተፈቀደላቸው የታደሉ ናቸው፡፡ ያልታደሉት ባጭር ይቀጫሉ፡፡ ይህ ህግ ሁሌም የሚኖር ነው፡፡ ሰው የሚሰራው ነገር ተጨማሪ ነው፡፡ ያም ሆኖ
“አለ አንዳንድ ነገር
በዚህ ቢሉት በዚያ ከመሆን የማይቀር”  ይላሉ ደራሲ ከበደ ሚካኤል፡፡ በዚህ ውስጥ የተቃራኒዎች አንድነትና ትግል ሁሌም አይቀሬ ነው፡፡ ገዢው ፓርቲ መግዛቱን ለመቀጠል ተገዢዎች የኛም ፓርቲ የገዢነት ቦታ ሊኖረው ይገባል በማለት እስኪሸናነፉና እስኪለይላቸው ጉዞአቸውን ይቀጥላሉ፡፡
“ልምድን ከሩቅ ሆነህ አታየውም፤ ሲከሰት ግን መኖሩን ታውቃለህ” ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለመማር ዝግጁ የሆነ ባወቀው ይጠቀማል፡፡ አትማር ያለው ባወቀውም ይደነቁራል፡፡ በሀገራችን ብዙ ፓርቲዎች ተወልደዋል፡፡ ብዙዎች ሞተዋል፡፡ አንዳንዶች ቀንቷቸዋል፡፡ አንዳንዶች በአጭር ተቀጭተዋል፡፡ የሁሉም የጋራ ሀብት ግን ከኖሩት አለመማር ሆኖ ታዝበነዋል፡፡ አሸናፊው ድሉን ከማሸብረቅ በቀር የሄደበትን መንገድ ዳግመኛ ለመመርመር አይቃጣውም፡፡ ተሸናፊው ቂም በቀሉን ከማመንዠክ እና ጊዜ ከመጠበቅ በቀር ያለፈውን ሁኔታ አጥንቶ በወጉ ለነገ ለመዘጋጀት ከቶም ልቦና የለውም፡፡ ይህ ሀቅ ሁሌም ምርጫ በመጣ ቁጥር የሚያጋጥመው እውነታ ነው፡፡ ትላንት በምርጫው አሸናፊ ነኝ የሚለው ወገን ለአሸናፊነት ሁሌም የታጨሁና ሁሌም የሚሳካልኝ ነኝ የሚለውን አስተሳሰብ የማይለወጥ እውነታ አድርጐ መውሰዱን አይን ካለን እናያለን፡፡ በአንፃሩ ትላንት በምርጫው ተሸናፊ የሆነው ወገን ደግሞ በመጭበርበር ተሸነፍኩ እንጂ ልክ ነበርኩ የሚለውን ሃሳቡን ሳይለውጥ አምስት አመት ይኖራል፡፡ በኢትዮጵያ ሠርጉ ካልደረሰ በርበሬ አይቀነጠስም ይባላል፡፡ አድፍጦ፣ አሳቻ ጊዜ መርጦ ለማነቅ ጀግና መባል አንዱና ዋነኛው የትግል ዘዴ በሆነበት ሀገር፣ የዲሞክራሲ እውንነት ሁሌም ጥያቄ ውስጥ ነው፡፡
ያለ ዲሞክራሲያዊ መስተጋብር ህይወት የአዘቦት መንገዷን እንጂ የተለወጠ ጐዳና ወይም እግረ መንገድ እንኳ ልትቀዳጅ አይቀናትም፡፡ የትግሉን ሂደት ከማየት ይልቅ ስወለድም እንዲህ ነበርኩ ማለትም አጉል መመካት ነው ይሉናል አበው ጠበብት፡፡ እኛ ብቻ ነን ለዚህ ስልጣን የተቀባን የሚለው ሃሳብ ግዘፍ ነስቶ የምናየው ለዚህ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን ብለን እናማትብ፡፡ አንድ የፖለቲካ ድርጅት በእውነትም ሆነ በውሸት ምርጫ ሲያሸንፍ “ፍፁም ስለሆንኩ አሸነፍኩ” የሚል አስተሳሰብ ውስጥ መዋኘቱ አይገርሜ ነው! ግቡን መምታቱ ያላጋጠሙትን አሊያም አጋጥመውት ያልዘገባቸውን መንሸራተቶችና መሰናክሎች ወይም ሰንካላ እድሎች እንዲረሳ የደረሰበት ወንበር ክፉ ንቀት ይሰጠዋል! ዛሬ እዚህ የደረስከው በሠራኸው ጥሩም፣ መጥፎም ነገር  ነው፡፡ የሚለውን ልብ አይልም፡፡ “መሠላል ያላንሸራተተው ሁሌ ጫፍ የሚወጣ ይመስለዋል” የሚለው ተረት ከላይ የተጠቀሰውን ሁሉ ያጠቃልላል፡፡
“ጥሩው ብቻ አይደለም እዚህ ያደረሰህ
መጥፎም ነው እኮ ያንተ ማንነትህ” እንደማለት ነው በግጥም ሲለገጥ፡፡  




     በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የፓትርያርኮች መንበር (መንበረ ፕትርክና) በኾነችው ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብና ንብረት በአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች መመዝበሩን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ጥቆማው የቀረበው፣ የገዳሟ ማኅበረ ካህናትና የልማት ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያኒቱን የገንዘብና የንብረት አሰባሰብ በተመለከተ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲዘረጋ የገዳሟ ልማት ኮሚቴ የበላይ ጠባቂ ለኾኑት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ባቀረቡት ማመልከቻና ሪፖርት ነው፡፡የቤተ ክርስቲያኒቱ መተዳደርያ ቃለ ዐዋዲና ደንቡን መሠረት አድርጎ በሀገረ ስብከቱ የተዘጋጀው የገንዘብ ቆጠራ፣ የንብረት አመዘጋገብና አጠባበቅ መመሪያ የካህናቱን፣ የምእመናኑንና የእያንዳንዱን ሠራተኛ የሥራ ድርሻና ተጠያቂነት በግልጽ ማስቀመጡን የጠቀሱት ማኅበረ ካህናቱ÷ የገዳሟን ገንዘብና ንብረት የመቆጣጠርና የመከታተል መብታቸው በአስተዳደሩ ሓላፊዎች ተነፍጓቸው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራና የንብረት ቁጥጥር ለማድረግ ሳይችሉ መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ገዳሚቷ በየዕለቱና በየበዓላቱ ከምእመናን በስጦታና በስእለት የምታገኘው ሀብትና ንብረት ከራስዋ አልፎ ለተቸገሩ ገዳማትና አድባራት የሚተርፍ ቢኾንም ግልጽነትና ተጠያቂነት በጎደለው የአስተዳደሩ አሠራርና በሰበካ ጉባኤው የቁጥጥር ማነስ ሳቢያ የገቢ አቅሟን ለማጎልበት ከዓመታት በፊት የወጠነችው ኹለ ገብ ሕንፃ ግንባታ ከመጓተቱም በላይ ለሀገረ ስብከቱ መከፈል ለሚገባው ውዝፍ ዕዳ መዳረጓን ካህናቱ አስታውቀዋል፡፡ በገንዘብ አያያዝና በንብረት አሰባሰብ ረገድ በአስተዳደሩ እየተባባሰ የመጣው ሙስና እንዲወገድና ካለፈው ዓመት ነሐሴ ወር ጀምሮ የተስተጓጎለው የልማት ሥራ እንዲቀላጠፍ በኅዳር ወር አጋማሽ ፓትርያርኩን መጠየቃቸውንም አመልክተዋል፡፡ከገዳሚቷ የልማት ኮሚቴ ጋራ በመቀናጀት የቀረበውን የማኅበረ ካህናቱን ማመልከቻ መነሻ በማድረግ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ በሰጡትና በረዳት ሊቀ ጳጳሱ በኩል ተፈጻሚ በኾነው መመሪያ፤ የገዳሟን የገንዘብና ንብረት አሰባሰብ የሚከታተል አምስት ካህናት ያሉት የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ ኮሚቴ ኅዳር 18 ቀን መቋቋሙ ታውቋል፡፡ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ማግሥት አንሥቶ ኅዳር 19 እና 22 ቀናት ባካሔደው የሙዳየ ምጽዋት ቆጠራ የተገኘውን ከብር 826‚000 በላይ ገቢ ጨምሮ ከንብረት ሽያጭና በሞዴል 30 የተሰበሰበውን በማካተት ከ1.2 ሚሊዮን ብር በላይ አጠቃላይ ገቢ በአንድ ወር ብቻ መመዝገቡ ተገልጧል፡፡ በካህናቱ አስፈጻሚነት በአንድ ወር የተወሰነ ቆጠራ ብቻ ይህን ያኽል ገቢ መመዝገቡ፣ የገዳሟ ገቢ ‹‹የግለሰቦች መደራጃ ኾኖ መኖሩን የሚያሳይ ነው፤›› ብለዋል - ማኅበረ ካህናቱ፡፡ አያይዘውም ለሀገረ ስብከቱ መከፈል የሚገባው የኻያ በመቶ ውዝፍ ዕዳ ሳይፈጸም አኹን በካዝና ያለው ብር 129‚000 ብቻ እንደኾነ በመጥቀስ ገዳሟ በየዓመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ስትመዘበር እንደኖረችና ጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ኾነ ሀገረ ስብከቱ በየደረጃው ማግኘት የነበረባቸውን የፐርሰንት ፈሰስ ማጣታቸውን ስለሚያረጋግጥ ‹‹የአስተዳደር ሠራተኞቹን ተጠያቂ የሚያደርግ ነው፤›› ብለዋል፡፡   እንደ ማኅበረ ካህናቱ እምነት፣ የገዳሟ ገቢ ለአስተዳደር ሠራተኞቹ ምዝበራ የተጋለጠው የተጠናከረ ሰበካ ጉባኤ ባለመኖሩ ነው፡፡ አኹን ያለው የገዳሙ ሰበካ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው መሠረት፣ የገዳሙን የሥራ ክፍሎች አገልግሎት አፈጻጸም በወቅታዊ የክንውን መግለጫዎች የመከታተል፣ የሒሳብ አያያዙንና የንብረት እንቅስቃሴውን ጊዜውን ጠብቀውና እንዳስፈላጊነቱ በሚቀርቡ ሪፖርቶች የመቆጣጠር ሓላፊነቱን ካለመወጣቱም በላይ ‹‹ገዳሚቷ ችግር ላይ ስትወድቅ ዝም ብሎ የኖረ ተባባሪ›› በመኾኑና የሥራ ጊዜውም በማለፉ ጠንካራና ሓላፊነት በሚሰማው ሰበካ ጉባኤ እንዲተካ መመሪያ እንዲሰጥላቸው፣ ተጀምሮ የቆመው ልማት እንዲቀጥል፣ የገዳሟ ገቢና ወጪም በውጭ ኦዲተሮች እንዲጣራ ማኅበረ ካህናቱ ፓትርያርኩን ጠይቀዋል፡፡ ያለማኅበረ ካህናቱና ማኅበረ ምእመናኑ ፈቃድ ጊዜው በሀ/ስብከቱ ውሳኔ ተራዝሟል የተባለው ሰበካ ጉባኤ፣ በቆጠራ ኮሚቴው የተሰበሰበውን ከብር 440‚000 በላይ የገዳሚቷን ከፍተኛ ገንዘብ ያለተቆጣጣሪ ወጪ ማድረጉን ካህናቱ ገልጸው፣ ሕጋዊ ሰበካ ጉባኤ ሳይቋቋም ቀጣይ ቆጠራ እንደማይካሔድ አስጠንቅቀዋል፡፡ በገዳሚቷ አስተዳደር ውስጥ ሙስናዊ ጥቅማቸው የተነካባቸው ናቸው ያሏቸው ግለሰቦች፣ የቆጠራ ኮሚቴውን ለማፍረስ÷ ‹‹ማኅበረ ቅዱሳንና ግንቦት ሰባት ናችኹ፤ ምርጫውን ለማወክ ትንቀሳቀሳላችኁ፤ ወደ ሌላ ደብር እናዘዋውራችኋለን›› በሚል ከሚያደርሱባቸው ዛቻና ማስፈራራት እንዲቆጠቡ አስተዳደራዊ ርምጃ እንዲሰጥላቸው አመልክተዋል፡፡የማኅበረ ካህናቱንና የልማት ኮሚቴውን ጥያቄ ተከትሎ ፓትርያርኩ በሰጡት መመሪያ÷ ሰበካ ጉባኤው የሥራ ክንውን ሪፖርት ካቀረበ በኋላ የአዲስ ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሔድ፣ የገዳሚቷ ገቢና ወጪ ሒሳብ በአስቸኳይ በውጭ ኦዲተር ተከናውኖ እንዲቀርብ፣ የቆጠራ ኮሚቴው የአስተዳደሩን ዕውቅና አግኝቶ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በ48 ሚልዮን ብር ወጪ በኹለት ምዕራፎች የተጀመረውና የተጓተተው የባለስድስት ፎቅ የአገልግሎትና ኹለገብ ሕንፃ ግንባታ የብቃት ማረጋገጫ ባለው አካል ክትትል እንዲፋጠን ማዘዛቸው ታውቋል፡፡

Saturday, 27 December 2014 16:25

ዛሬም ይዞረኛል

ሄደ … አለፈ ብዬ ትንሽ ፋታ ሳገኝ፣
የተጫነኝ ችግር የጠፋ ሲመስለኝ፣
ተመልሶ መጥቶ ጎንተል ያደርገኛል፣
የራቀ ሲመስለኝ ዳግም ይቀርበኛል፣
ከጋለው ሊጥደኝ መልሶ ይዞረኛል፡፡
እኔ ቀርቤው ነው? ወይ እሱ እየመጣ፣
የማንለያየው - የማንተጣጣ፡፡
አንዴ እየራቀ፣ ዳግም እየመጣ …
        ይሽከረከረኛል፣
ቁራኛዬ ሆኖ አልለቅህም ብሎ …
        ያንዣብብብኛል፡፡
ከዚህ ችግር ዕዳ - ከእንቶ ፈንቶ ጣጣ፣
ሊያድነኝ ከሁሉም ከማጡ ሊያወጣ፣
ዳግም ወደ መሬት ክርስቶስ አይመጣ፣
ታዲያ እንዴት ልሁነው?
እንዲሁ እንዳለሁ ፍግም ልበለው!?
        … ኧረ አሳዝናለሁ፣
        … አፈር እከብዳለሁ፡፡
ይህ መንገራገጩ ጠቅልሎ አልሄድ ያለው፣
እንዴት ቢያፈቅረኝ ነው ከኔ የማይለየው!?
ፊትም፣ አምና፣ ዛሬ አልተውህ ብሎኛል፣
ነገሩ ምንድነው? - ዛሬም ይዞረኛል፡፡

ከአምሳሉ ጌታሁን ደርሰህ
ታህሣሥ 2007 ዓ.ም

ታዳጊዎች ለማጨስ እንዳይበረታቱ ከፍተኛ ቀረጥ ሊጣል ነው
በፓኬት እንጂ በነጠላ መሸጥ ሊከለከል ነው

    የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ሰሞኑን በቢሾፍቱ ከተማ ለመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ባዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራም ላይ በአገሪቱ የሲጋራ አጫሹ ቁጥር እየጨመረ እንደሆነ የተገለፀ ሲሆን በሲጋራ ምርት ላይ ከፍተኛ ቀረጥ እንደሚመጣል ተጠቆመ፡፡
በ2003 ዓ.ም የተደረገውን የሥነ ህዝብና ጤና ጥናት (DHS) ዋቢ በማድረግ በቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፎች እንደተመለከተው፤ የአጫሾች ቁጥር ወደ ስድስት ሚሊዮን ገደማ ይሆናል፡፡ ከአጫሾቹ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዙት ወንዶች ቢሆኑም የሴት አጫሾች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል፡፡ የአገሪቱ አጠቃላይ አመታዊ የሲጋራ ፍላጐትም ወደ 5 ቢሊዮን ፍሬ ደርሷል ተብሏል፡፡
ከአገሪቱ አጠቃላይ የሲጋራ ፍላጐት 53 በመቶ ያህሉ የሚሸፈነው በብሔራዊ ትምባሆ ሞኖፖል ሲሆን 4.6 በመቶ ከውጪ በማስገባት፣ 38 በመቶ ደግሞ በኮንትሮባንድ (ህገወጥ) ንግድ ነው፡፡ ትምባሆ፤ ሱስ አስያዥ የሆነውን ኒኮቲን የተባለ ንጥረ ነገር ጨምሮ ከአራት ሺህ በላይ ኬሚካሎችን በውስጡ ይይዛል፡፡ ከእነዚህ ውስጥም 250 ያህሉ እጅግ አደገኛ ኬሚካሎች ሲሆኑ 50 የሚደርሱት ደግሞ ካንሰር አምጪ ኬሚካሎች መሆናቸውን የአለም ጤና ድርጅት ተወካዩ አቶ ዋሲሁን መላኩ ተናግረዋል፡፡
አዕምሮአችን የተስተካከለ ጤና እንዳይኖረው ከሚያደርጉ ጉዳዮች አንዱ ሱሰኝነት ነው ያሉት ዶክተር ሙሴ ገብረሚካኤል፤ በትምባሆ ውስጥ የሚገኘውና ኒኮቲን የተባለው ንጥረ ነገር አንጐላችን ውስጥ የተለያዩ ለውጦችን በመፍጠር አንጐላችንን የኒኮቲን ጥገኛ ያደርገዋል ብለዋል፡፡ ትንባሆ ውስጥ የሚገኘው ሱስ አስያዥ ኒኮቲን መጠኑ እየጨመረ በመጣ ቁጥር  ለአዕምሮ ህመም እንዲሁም ለሞት የመጋለጥ እድል እንደሚጨምር ገልፀዋል፡፡
መከላከል እየተቻለ ለሞት መንስኤ ከሚሆኑ የአለማችን የጤና ጠንቆች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው ትምባሆ፤ ለከፍተኛ የደም ግፊት፣ ለልብ ህመም፣ ለተለያዩ ካንሰር ህመሞች፣ ለአይን ሞራ ግርዶሽ፣ ለጥርስ መበስበስ፣ ለጨጓራ ቁስለት፣ ለአንጐል በሽታ፣ ለጋንግሪንና ለስንፈተ ወሲብ እንደሚያጋልጥም የአለም ጤና ድርጅት መረጃ ያመለክታል፡፡
በ2013 የተደረገና በአለም ጤና ድርጅት ይፋ የሆነ የጥናት ውጤት እንደሚጠቁመውም፤ በአለማችን በትምባሆ ሣቢያ በሚከሰቱ የጤና ችግሮች ህይወታቸውን የሚያጡ ሰዎች ቁጥር በኤድስ፣ በትራፊክ አደጋ፣ በአደንዛዥ እፅ፣ በግድያ ወንጀልና ራስን በማጥፋት ከሚሞቱት ሰዎች አጠቃላይ ድምር ይበልጣል፡፡ በአሁኑ ወቅት በዓለማችን 1.3 ቢሊዮን የትምባሆ ተጠቃሚዎች የሚገኙ ሲሆን በየዓመቱም 5 ሚሊዮን የሚሆኑት በትምባሆ ምክንያት ህይወታቸውን ያጣሉ፡፡ የሟቾቹ ቁጥር ካደጉት አገራት ይልቅ ገና በማደግ ላይ ባሉት አገራት ይጨምራል፡፡
በአገራችን ትምባሆ በተለያዩ መንገዶች በጥቅም ላይ የሚውል ሲሆን ማጨስ፣ ማኘክ፣ መታጠንና ማሽተት ዋንኞቹ የትምባሆ ተጠቃሚዎች የሚያዘወትሯቸው መንገዶች ናቸው፡፡ በተለይ ከከተማ ወጣ ባሉ አካባቢዎች በማኘክና በማሽተት የትምባሆ ተጠቃሚ መሆን የተለመደ ነው፡፡
በከተሞች አካባቢ በፋብሪካ የሚዘጋጁ የትምባሆ ምርቶች የሚዘወተሩ ሲሆን በብሔራዊ ትምባሆ ሞኖፖል የሚመረቱት ግስላ፣ ኒያላ፣ ኢሌኒና ዲላይት የተባሉት የሲጋራ አይነቶች ገበያውን በከፍተኛ ደረጃ ተቆጣጥረውታል፡፡  
ማልቦሮ፣ ዊንስተን፣ ሮዝማን፣ ኤል ኤንድ ኤም እና ኬንት የተባሉት የሲጋራ አይነቶች ደግሞ በህጋዊ መንገድና በኮንትሮባንድ ከውጪ አገር እየገቡ ለአገራችን ገበያ የሚቀርቡ የሲጋራ አይነቶች ናቸው፡፡
የትምባሆ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ የሥራ ዕድል በመፍጠርና የታክስ ገቢ በማስገኘት ለአገሪቱ የሚሰጠው ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ ከፍተኛ ቢሆንም የሚያስከትለው ችግርና የሚፈጥረው ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ከፍተኛ በመሆኑ፣ ቁጥጥርና ክትትል በማድረግ፣ በትምባሆ ሣቢያ የሚሞቱ ዜጐችን መታደግ አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆኖ በመገኘቱ፣ ህግ አውጥቶ፣ አሠራሩን መቆጣጠር እንዳስፈለገ በኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን አማካሪ አቶ መንግስተአብ ወልደአረጋይ ተናግረዋል፡፡ በተለይም ማጨስ በሚጀመርበት የወጣትነት ዕድሜ ውስጥ የሚገኙ ዜጐች ሲጋራ በቀላሉ ለማግኘት እንዳይችሉ በትምባሆ ላይ የሚጣለውን ታክስ ከፍ በማድረግ፣ የሲጋራ መሸጫ ዋጋን ለመጨመር የሚያስችል ስትራቴጂ ተነድፎና ረቂቅ ህግ ወጥቶ በገንዘብና ኢኮኖሚ ሚኒስትር ጥናት እየተደረገበት እንደሆነ አማካሪው ጠቁመዋል፡፡ ህጉ በቅርቡ ፀድቆ ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልፀዋል፡፡
ባለፈው ዓመት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፀደቀውን የትምባሆ ቁጥጥር አዋጅ ለማስፈፀም ሥልጣንና ኃላፊነት የተሰጠው የኢትዮጵያ የምግብ፣ መድኀኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን፤ ህዳር 22 ቀን 2007 ዓ.ም የትምባሆ ቁጥጥር መመሪያ በማውጣት አፅድቋል፡፡ በቅርቡም ተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚጀመር ሲሆን በትምባሆ ምርቶች ሽያጭ፣ ዝውውርና አጠቃቀም ላይ ቁጥጥርና ክትትል እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡
በአዲሱ አዋጅና መመሪያ መሰረትም፣ ማንኛውም የኤሌክትሮኒክስ ኒኮቲን መስጫ መሳሪያ ማምረት ወደ ሀገር ውስጥ ማምጣት፣ ማከፋፈል፣ መሸጥ ወይም በማንኛውም መንገድ ገበያ ውስጥ ማስገባት የተከለከለ ነው፡፡
የትምባሆ ምርቱ ለጤና አደገኛ መሆኑን የሚገልፅ የማስጠንቀቂያ ፅሁፍ የሲጋራ ባኮውን 30 በመቶው ያላነሰ ቦታ በሚሸፍን መልኩ መገለፅ ይኖርበታል፡፡ የትምባሆ ምርትን በችርቻሮ የመሸጥ ፍቃድ የተሰጣቸው ሰዎች ምርቱን ለአይን በሚታይ መልኩ መደርደርና ገዥን መሳብ አይችሉም፡፡ የትምባሆ ምርት የሚሸጠው ባልተከፈተ ፓኬት ወይም ማሸጊያ ሲሆን ሲጋራን በነጠላ መሸጥ የተከለከለ መሆኑን አዲሱ አዋጅና መመሪያ ያዛል፡፡
ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊዎች በትምባሆ ምርት ግዥም ሆነ ሽያጭ ላይ ተሳታፊ መሆን እንደማይችሉ የደነገገው አዲሱ መመሪያ፤ የትምባሆ ምርት በችርቻሮ በሚሸጥበት ወቅት ሻጩ የገዥውን ዕድሜ ከተጠራጠረ ህጋዊ ፓስፖርት፣ የመንጃ ፈቃድ ወይም የነዋሪነት መታወቂያ ካርድ አይቶ ማረጋገጥ አለበት ይላል፡፡ አዲሱ መመሪያ ሲጋራ ማጨስ የማይፈቅድባቸውን ቦታዎች በዝርዝር የገለጸ ሲሆን፤ ሆቴሎች፣ የመጠጥ ቤቶች፣ የምሽት ክለቦች፣ መዝናኛ ክበቦች፣ ካፌዎች፣ ምግብ ቤቶች፣ የመንግስትና የግል መስሪያ ቤቶች፣ ሊፍቶች፣ መታጠቢያ ቤቶች፣ ፋብሪካዎችና የንግድ መደብሮች፣ ሲኒማ፣ ቲያትርና ቪዲዮ ቤቶች፣ ሙዚቃ ማሣያ አዳራሾች፣ የህዝብ መሰብሰቢያ ቦታዎች፣ የህዝብ ትራንስፖርቶች፣ እንዲሁም ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ልጆች በሚገኙባቸው ሥፍራዎች ሁሉ ማጨስ የተከለከለ ነው፡፡
አዲሱ ህግና መመሪያ በቅርቡ ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆን ደንብና መመሪያውን በማይተገብሩ አካላት ላይም ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ ተገልጿል፡፡ ከሶስት ወራት በኋላ በሚወጡ ፊልሞች ላይ ሲጋራ እንዳይጨስና የሚጨስባቸው አጋጣሚዎች ካሉም በፊልሙ ላይ የሲጋራን ጎጂነት የሚገልፁ ፅሁፎች በስክሪኑ ላይ እንዲጻፉ የሚያስገድድ አሰራርም እንደሚጀመር ተገልጿል፡፡

     ሂሳብ፣ የዛሬው የመጨረሻው ጭውውታችን ነው፣ ማርጀትና መሞትን የሚመለከት፡፡ ጥናቱን የሚያቀርብልን ጓድ አስተዳደር ነው፡፡ መድረኩ ይኸውልህ!
ኬሚስትሪ፣ ጓድ ሰብሳቢ፣ ይህ አርእስት ስጋት ላይ ጥሎኛል፣ ማለቴ ጡረተኛ ስለሞት ማውራት አለበት እንዴ? እንደኔ ከዚህ አርእስት መራቅ ይሻላል!
ምህንድስና፣ አቤት ፍርሃት! አይዞህ ጭውውቱን እስክንጨርስ አትሞትም፣ ለማናቸውም ብትሞትም አንዴ ነው፣ ደግመህ ትሞትም፡፡ ስለዚህ ፍርሃትህን ወደ ጎን አድርገው፡፡
አስተዳደር፣ ጓዶች፣ አርእስቱን እንተወው ለማለት ትንሽ የዘገየ ይመስለኛል፡፡ እኔም እኮ የማይናቅ ጊዜ መሰናዶው ላይ አጥፍቻለሁ፡፡
ሂሳብ፣ መልካም፣ በል ጥናትህን አቅርብልን፡፡
አስተዳደር፣ በመጀመሪያ ሦስታችሁንም ለማመስገን እፈልጋለሁ፣ የሚነበቡ ፅሁፎች ባትሰጡኝ ኖሮ በፍፁም ልወጣው ባልቻልኩ ነበር፡፡
በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፣ ስለ ፕሮቶን፣ ኤሌክትሮን ባላወራሁም ነበር፡፡ እስቲ ከመሰረቱ ልጀምር፡፡ ሳይንስ ሲያስተምረን ሁሉ ነገር፣ ማለትም ከድንጋይ እስከ ሰው ያለው ሁሉ የተገነባው ከአቶሞች እንደሆነ ነው፡፡
አቶሞች በተራቸው ከፕሮቶኖችና ኤሌክትሮኖች የተነቡ ሲሆን፣ ፕሮቶኖች ከኳርክ ዝርያዎች ተቀነባብረው የተሰሩ ናቸው፣ ኤሌክትሮን ግን እራሷን የቻለች ናት፡፡ ጓዶች፣ ከወር በፊት “ኳርክ” ምንድነው ብትሉኝ ኖሮ፣ እንቁራሪት የሚያሰማው ድምፅ    ነዋ! እል ነበር፡፡ እንደምታዩት እኔም መጠነኛ ትምህርት ቀስሜያለሁ!
የሚነሳው ጥያቄ የአቶሞች ዕድሜ ስንት ነው? ያረጃሉ ወይ? የሚል ነው፡፡ የፊዚክስ ባለሙያዎች ሲያስረዱ፣ የፕሮቶን እድሜ 1031 ዓመታት (ማለትም 10 ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን፣ ሚሊዮን) ሲሆን ኤሌክትሮን ግን ጨርሶ የማትለወጥ ናት፡፡
ታዲያ ይኸ እንዲህ ከሆነ በአቶሞች የተገነቡት ሀዋሳ፣ ብሎም ተክሎችና እንስሳት እንዴትና ለምን ማርጀት ቻሉ? አንዳንዶች ሲያስረዱ፣ ህዋስ ከአቶም የበለጠ ውስብስብ፣ እንቁራሪት (የህዋሳት ስብስብ) ከአንድ ህዋስ የበለጠ ውስብስብ ናቸው፡፡ እነኚህ ምሁራን እንደሚሉት ውስብስብነት (ኮምፕሌክሲቲ) ወደ ህይወት ያመራል፣ አይቀሬ ነው፡፡ ህይወት ወደ ሞት! ይህ አባባል ወደ ፍልስፍናው የሚያደላ ስለሚመስል ባንገፋበት ይሻላል፡፡
ባለአንድ ህዋስ ባክቲሪያም እኮ ታረጃለች፣ ማለትም ውስብስብነት በይፋ የማይታይበት፣ ለምን? እርጅናን የሚቆጣጠሩ ጂኖች አሉ? አንዳንድ ሰዎች እስከ 130 ዓመት እንደሚኖሩ የታወቀ ነው፣ ባካባቢያቸው ምክንያት ይሆን? ብዙ ጊዜ እነኚህ ሰዎች ዳገትማ ስፍራ፣ ንፁህ አየርና ውሃ በሚገኝበት የሚኖሩ ናቸው፡፡ ለምግባቸውም ከስጋ ይልቅስ ተክሎችን ያዘወትራሉ ይባላል፡፡ ተክሎችን ስንመለከት፣ በአሁኑ ወቅት በሰሜን አሜሪካ፣ ካሊፎርኒያ ግዛት ውስጥ “ሴኮያ” የተባለ ዛፍ እስከ 3,800 ዓመት እንዲኖር በተደረገ ምርምር በ C-14 እና ከግንዱ ቀለበቶች ቁጥር ተረጋግጧል፡፡
የዚህ ዓይነት ዛፍ፣ ትልቅና ረጅም ዕድሜ ያለው የግንዱ ግማሽ - ወገብ ስፋት (ሬዲየስ) 4,85 ሜትር፣ ዙሪያ ርቀት (ሰርከምፈረንስ) 30 ሜትር፣ የቅርፊት ውፍረት 61 ሴንቲሜትር መሆኑ ታውቋል፡፡ እርግጥ፣ ሴኮያ በንግዱ መወፈርና በቅርፊቱ ደንዳና መሆን ምስጥ፣ ዝናብ፣ በረዶ ሊያጠቁት የቻሉ አይመስልም፡፡ ሌላው የዛፉ ከፍታ ቦታ በማደግ ከእንስሳት መራቁ ነው፡፡ ከሴኮያ ህዋሳት የምንማረው ይኖራል?
[“ከዚህም ከዚያም” (የ4 ጡረተኞች ጭውውት) ከተሰኘው የፕሮፌሰር ግርማ ሙልኢሳ መፅሃፍ የተቀነጨበ]

እኔ የምላችሁ ግን … ኢህአዴግ ሥልጣን ከያዘ ስንት ዓመቱ ነው? ይሄንን ቀላል ጥያቄ የምጠይቃችሁ ወድጄ እንዳይመስላችሁ፡፡ ግራ ቢገባኝ ነው፡፡ ሌላም ጥያቄ አለኝ - ያለፈው ሥርዓት ከተገረሰሰ ምን ያህል ጊዜ ሆነው? (ውዥንብሩ መጥራት አለበት!) አንዳንዴ ያለፈው ሥርዓት “አስማተኛ” ይመስለኛል፡፡ ለምን መሰላችሁ? አንዳንድ ሰዎች አሁንም ከ24 ዓመት በኋላ እንኳን ስለሱ ማውራት አልተዉም፡፡ ለሁሉ ነገር ያለፈውን ሥርዓት ካልጠሩ አይሆንላቸውም - በተለይ የኢህአዴግ ካድሬዎች፡፡ (ፍሬሾቹን ማለቴ ነው!)
 ሰሞኑን EBC ባቀረበው የዜና ዘገባ ላይ “…የሴቶች ጥቃት ያለፈው ሥርዓት ችግር ስለሆነ እንታገለዋለን…” (really?!) የሚል ነገር የሰማሁ መሰለኝ፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል … ራሱ ኢህአዴግም እንኳን  የሴቶች ጥቃት “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ነው አይልም፡፡ እንዲያ ካለማ--- ያለፈው ሥርዓት አልተገረሰሰም ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ እንዳልኩት “አስተማኛ” ነው፡፡ (መቃብር እየፈነቀለ የሚወጣ!)
ይሄውላችሁ --- በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዓይነትም በመጠንም እየጨመሩ ለመምጣታቸው ከፖሊስ ፕሮግራም የበለጠ ማስረጃ የለም፡፡ (የሴቶች መብት ተሟጋቾችም ምስክር ናቸው!) አስገድዶ መድፈር፣ አሲድ መድፋት፣ ከባድ ድብደባና የአካል ማጉደል እንዲሁም አሰቃቂ ግድያዎች…በእጅጉ በርክተዋል፡፡ (ሰብዓዊ ልማት ተዘንግቷል!)
እናም--- የሰሞኑ የEBC ዘገባ blame shifting (“የእምዬን ወደ አብዬ”) እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡ ሃቁን እንነጋገር ከተባለ --- የሴቶች ጥቃት  “ያለፈው ሥርዓት” ችግር ሳይሆን የእኛው የራሳችን ችግር ነው፡፡ (የኋላ ቀርነት፣ የትምህርት አለመስፋፋት፣ የግንዛቤ ማነስ፣ የአመለካከት ችግር ወዘተ…) ነገርዬው እምብዛም ከስርዓት ጋር የሚያያዝ አልመሰለኝም (ፖለቲካ እኮ አይደለም!) የግድ የሥርዓት ችግር ነው ከተባለም ባለቤቱ የአሁኑ ሥርዓት ነው፡፡ እናሳ? … እናማ በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ወዳለፈው ሥርዓት ለማሻገር ከመታተር ይልቅ እውነታውን ተቀብሎ ለመፍትሄ መትጋት ይሻላል፡፡ (ያለፈው ሥርዓት ከበቂ በላይ የራሱ ኃጢያቶች እንዳሉት አንዘንጋ!!)
ይሄውላችሁ ----- እንኳንስ በቅርብ ዓመታት እየተባባሰ የመጣው “የሴቶች ጥቃት” ይቅርና በእርግጥም ካለፈው ሥርዓት የተወረሱ ናቸው የሚባሉት (እነ ድህነት፣ ሙስና፣ የስልጣን ጥመኝነት፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት፣ የነፃነት አፈና፣ የፍትህ መጓደል ወዘተ…) ቢሆኑም እንኳ --- 20 ዓመት ስላለፋቸው  ውርስነታቸው አብቅቷል፡፡ (ከአባት የተወረሰ ንብረትም እኮ ለዘላለም በውርስነት አይጠራም!) ከምሬ እኮ ነው… ከአሁን በኋላ ችግሮችን ባለፈው ሥርዓት ማሳበብ ራስን ለትዝብት ማጋለጥ ነው፡፡
በመጨረሻ አንድ ሃሳብ ላቅርብ፡ ከፆታዊ ጥቃቶች አንዱ የሆነው አስገድዶ መድፈር፣ ለምን በፀረ ሽብር ህጉ ውስጥ አይካተትም? ይሄ እኮ… ሥርዓቱን ወይም ህገመንግስቱን በኃይል ለመናድ ከመሞከር ፈፅሞ አይተናነስም፡፡ ሴቶች ላይ ጥቃት መፈጸም - ቤተሰብን --- ህዝብን --- መንግስትን ---- አገርን --- ማሸበር ነው!!

Saturday, 20 December 2014 13:19

የፀሃፍት ጥግ

(ስለ ምርጫ)
* ከአዲስ ምርጫ የምንማረው ነገር ቢኖር ከቀድሞው ምርጫ ምንም አለመማራችንን ነው፡፡
ጌራልድ ባርዛን
* ምርጫ የምናካሂድበት ብቸኛው ምክንያት ከህዝብ የተሰበሰበው አስተያየት ትክክል መሆኑን ለማወቅ እንደሆነ ተሰምቷችሁ ያውቃል?
ሮበርት ኦርቤን
* በኦሎምፒክ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ብር ያሸልማል፡፡ በፖለቲካ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ግን ያስረሳል፡፡
ሪቻርድ ኒክሰን
* በፖለቲካው ዓለም ሴቶች ደብዳቤ ይተይባሉ፤ ቴምብር ይለጥፋሉ፤ በራሪ ወረቀት ያሰራጫሉ፡፡ ከዚያም ከምርጫው ይወጣሉ፡፡ ወንዶች ይመረጣሉ፡፡
ክላሬ ቡዝ ሉሴ
* እጩ ተመራጭ ከመንገድ ማዶ ሆናችሁ ከለያችሁ የምርጫ ወቅት ሪቅ አይደለም ማለት ነው፡፡
ኪን ሁባርድ -
* የምርጫ ድምፅ መመዘን እንጂ መቆጠር የለበትም፡፡
ጆን ክሪስቶፍ ፍሬድሪክ ቮን ሺለር
* የነፃ ምርጫ ችግሩ ማን እንደሚያሸንፍ ቀድሞ አለመታወቁ ነው፡፡
ሊኦኒድ ብሬዥኔቭ
* የምርጫው ውጤት የሚወሰነው ድምፅ በሚሰጡ ሰዎች ሳይሆን ድምፁን በሚቆጥሩ ሰዎች ነው፡፡
ጆሴፍ ስታሊን
* እንግሊዞች ነፃ ነን ብለው ያስባሉ፡፡ ነፃ የሚሆኑት ግን በፓርላማ አባላት ምርጫ ወቅት ብቻ ነው፡፡
ዣን ዣኪዩስ ሩሶ
* ሰዎች ከአደን በኋላ፣ በጦርነት ወቅት ወይም ከምርጫ በፊት የሚዋሹትን ያህል መቼም አይዋሹም፡፡
ኦቶ ቫን ቢስማርክ

Saturday, 20 December 2014 12:47

ይድረስ ለህፃናት መምህራን

“ህፃናትን በፍቅር እናስተምራቸው”

     ልጆቼ የአምስትና የሶስት አመት ህፃናት ናቸው፡፡ የሚማሩት አንድ ትምህርት ቤት ሲሆን ትልቋ መካከለኛ የመዋዕለ ህፃናት፣ ትንሿ ደግሞ ጀማሪ የመዋዕለ ህፃናት ተማሪዎች ናቸው፡፡ ብዙ ጊዜ ከአንደበታቸው የማይጠፉ ሁለት አባሎች አሉ - “loser” እና “ shame on you” የሚሉ ናቸው፡፡ አንድ ቀን እኒህን አሉታዊ አባባሎች ከየት እንዳመጧቸው ስጠይቃቸው፣ ከትምህርት ቤት መሆኑን ነገሩኝ - ያውም ከመምህራኖቻቸው፡፡
ልጆቼ በሚማሩበት ት/ቤት መምህራን የህጻናቱን የዕለት ውሎ ለወላጆች ሪፖርት የሚያደርጉበትና ወላጆችም መመልከታቸውን ከአስተያየት ጋር (ካላቸው ማለት ነው) አክለው ፈርመው የሚልኩበት “ኮሙኒኬሽን ቡክ የሚሉት ትልቅ ጥራዝ አለ፡፡ በሌሎቹም የግል ት/ቤቶች ይኖራል ብዬ አምናለሁ፡፡
አንድ ቀን ታዲያ በመጀመሪያዋ ልጄ የ “ኮሙኒኬሽን ቡክ” ላይ ዲሲፕሊን በሚለው ስር “ጥሩ” የሚል አስተያየት ሰፍሮ በማየቴ (ከወትሮው ዝቅ ያለ ነው) ምክንያቱን ጠየቅኋት፡፡
እሷም “ግድግዳ ላይ ስለፃፍኩ ነው…” አለችኝ
“ይቅርታ ጠየቅሽ?”
“አዎ፤ መጀመርያ የቅጣት ወንበር ላይ ተቀመጥኩና የክፍል ልጆች ጮክ ብለው “loser እና  shame on you” እንዲሉኝ ሚስ አዘዘቻቸው፡፡ ከዚያም ሚስን ይቅርታ ጠይቄ ወደ መቀመጫዬ ተመለስኩ” በማለት ሂደቱን አስረዳችኝ፡፡ ከዚህ ቀደም እንዲህ ያለ ነገር ሰምቼ ስለማላውቅ ደነገጥኩ፡፡ ሃሳብም ገባኝ፡፡ “አንቺም ሌሎችን እንደዛ ብለሽ ታውቂያለሽ?” ጠየቅኋት፤ ልጄን፡፡ “አዎ ብዙ ቀን እከሌ እና እከሌን ብለናቸዋል”፡፡ የልጄ መልስ ነበር፡፡ በከተማችን በሚገኙ አምስት የግል ትምህርት ቤቶች ተማሪ የሆኑ ህፃናትን ጠይቄ ድርጊቱ በእነሱም ት/ቤቶች እንደሚፈፀም ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ልጆች በስነስርአት ታንፀው እንዲያድጉ ከተፈለገ፣ ያጠፉት ጥፋት ምን እንደሆነ በትክክል ተረድተው፣ ከጥፋታቸው እንዲቆጠቡ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ ቅጣት ያልተገባ ባህርይን ወይም ድርጊትን ለመቀነስ ብሎም ለማስወገድ እንደሚያግዝ አያከራክርም፡፡ ሆኖም በተለይ በህፃንነት ዕድሜ ባሉ ተማሪዎች ላይ የሚፈፀመው ቅጣት ጥንቃቄ የተሞላበትና ያልተፈለገ ውጤት የማያመጣ መሆን ይገባዋል፡፡
ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በልጆች ስነልቦና ላይ የሰሩትና በሙያቸው መምህር የሆኑት አቶ ማናዬ አደላ፤ ህፃናትን እንዴት ከጥፋት እንዲቆጠቡ ማድረግ እንደሚቻል ያስረዳሉ፤ “የመጀመሪያው አማራጭ የህፃናትን መልካም ስነምግባር ማበረታታት፣ ህፃናቱ ጥሩ ባህርይ እንዲላበሱ ያደርጋል፤ እግረመንገዱንም መጥፎውን እንዳይቀጥሉበት ይከለከላል፡፡ ነገር ግን በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያቸው ከስነ ምግባር ውጭ የሆኑ ነገሮችን መልመዳቸው ስለማይቀር ተገቢ ማረሚያ መንገዶችን መጠቀም ይገባል፡፡ ከማረሚያ መንገዶቹ አንዱ ቅጣት የምንለው ነው፡፡” የሚሉት አቶ ማናዬ፤ በስነልቦና ሙያ ቅጣት ሁለት አይነት ነው፡- አዎንታዊና አሉታዊ ቅጣት” በማለት ያብራራሉ፡፡
“አሉታዊ ቅጣት በድርጊት (አካላዊ ቅጣት ማለት ነው) ወይም በቃላት የሚፈፀሙ ናቸው፡፡ ይህ አይነቱ ቅጣት አካላዊ ጉዳትና ስነልቦናዊ ተፅዕኖ ስላለው በፍፁም አይመከርም፡፡ አዎንታዊ ቅጣት የሚባለው ምንም አይነት ስነልቦናዊና አካላዊ ጉዳት በህፃናቱ ላይ ሳያደርሱ፣ ከመሰረታዊ ፍላጎቶች ውጪ የሆኑ ነገሮችን እንደ መቀጣጫ በማስቀረት ስህተታቸውን  ደግመው እንዳይፈፅሙ ማስተማር አይነት ዘዴዎችን ያካተተ ነው፡፡” ይላሉ - ባለሙያው፡፡   
በህፃናት ላይ የሚሰነዘር ስድብና ማላገጥ የህፃናቱን በራስ የመተማመን መንፈስ ይጎዳል፣ ከሌሎች ጋር ሊኖራቸው የሚገባ መቀራረብን ያሳጣል፣ ለትምህርት ያላቸውን ተነሳሽነት ይገድለዋል፣ ፍርሀት በውስጣቸው  እንዲፈጠር በማድረግ የፈጠ አቅማቸውን ያዳክማል ያጠፋል ፣ ሌሎች ነገሮችን እንዳይሞክሩ ያደርጋል፣ የበታችነት ስሜት ይፈጥራል፡፡ ከዚያም አልፎ ትምህርት ቤትን እንዲጠሉና አንሄድም እንዲሉ ያደርጋል፣ የቀጣውን አስተማሪ ከእነሚያስተምረው ትምህርት ጭምር እንዲጠሉ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
ህፃናት መቀጣት ያለባቸው በመምህራቸው ብቻ እንደሆነ የሚናገሩት ባለሙያው፤ ተማሪን እያስጨበጨቡ  በቅጣት ላይ ማሳተፍ በተለይ በአቻ እድሜ ላይ ሲሆን የሚፈጥረው አሉታዊ ተፅዕኖ እጅግ ከባድ ነው ባይ ናቸው፡፡ በተመሳሳይ እድሜ ላይ ያሉ ልጆች  በመምህራቸው ትዕዛዝ የክፍላቸውን ተማሪ  “loser” እና  “shame on you” የመሳሰሉ አባባሎችን በመጠቀም እንዲያሾፉበት ሲደረግ ተማሪው ላይ የበታችነት ስሜት ይፈጠራል፤ ይህ ደግሞ በህፃናት ላይ መፈፀም ከሌለባቸው ድርጊቶች አንዱ ነው፡፡ ምክንያቱም የበታችነት ስሜት የሚሰማው ህፃን ተወዳዳሪነቱ ይቀንሳል፣ በራስ የመተማመን ስሜት ያጣል፣ በአጠቃላይም እጅግ አፍራሽ ውጤት የሚያስከትል ድርጊት ነው ይላሉ፤ አቶ ማናዬ፡፡ከሁለት አመት እስከ ሰባት አመትና ከሰባት እስከ አስራ አንድ አመት ያሉት ጊዜያት እጅግ ጥንቃቄ የሚያስፈልጋቸው፣ በህፃናት እድገት ላይ ወሳኝ ጊዜያት ናቸው ያሉት ባለሙያው፤ በዴቨሎፕመንታል ሳይኮሎጂ እጅግ ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል የሚባሉ የእድሜ ደረጃዎች መሆናቸውንም ይናገራሉ፡፡ ይህ እድሜ የልጆችን ሁለንተናዊ እድገት ማበረታቻ እንጂ ማጨናገፊያ መሆን የለበትም፡፡ አስተማሪዎች እጅግ ብልጠት የታከለበት ቅጣትን በመጠቀም ተገቢ ያልሆኑ ባህርያትን ማረም እንዳለባቸውም ባለሙያው ያስረዳሉ፡፡
 የልጆቼ ትምህርት ቤት ሄጄ ዳይሬክተሯን አነጋግሬ ነበር፡፡ “ልጆች እንዴት ከትምህርት ቤት ስድብ ተምረው ይመጣሉ፤ ስድቦቹ ለመዋዕለ ህፃናት ተማሪዎች ብቻ ሳይሆን ለአዋቂም እንኳን እጅግ የሚያሸማቅቁ ናቸው፣ እንዲህ አይነት አባባሎች በትምህርት ቤቱ እንዳይበረታቱ ሊደረግ ይገባል” በሚል ያቀረብኩትን ሃሳብ በቀናነት ተቀብለውኛል፡፡ ለመምህራኑ ተከታታይ ስልጠናዎችን ለመስጠት በዝግጅት ላይ እንደሆኑም ዳይሬክተሯ ጠቁመውኛል፡፡ ሌሎች ትምህርት ቤቶችም እንዲህ ያለ የህፃናትን በራስ የመተማመን ስሜት የሚጐዳ ስድብና ድርጊት ከመፈፀም በመታቀብ፣ ያጠፉ ህፃናትን አስተማሪ በሆነና ሰብዕናቸውን በማይጐዳ መልኩ መቅጣት ይኖርባቸዋል፡፡
በለጋ እድሜ ላይ ያሉ ህፃናትን መስደብና ማሾፊያ ማድረግ በትምህርታቸውና በማህበራዊ ህይወታቸው ላይ ትልቅ ጉዳት እንደሚያስከትል መገንዘብ ይገባል፡፡  ህፃናትን በፍቅር እናስተምራቸው!!